en
Feedback
የቡራዩ ደ/ሰላም መድኃኔዓለም ካቴድራል ፍኖተ ሰላም ሰንበት ት/ቤት

የቡራዩ ደ/ሰላም መድኃኔዓለም ካቴድራል ፍኖተ ሰላም ሰንበት ት/ቤት

Open in Telegram

ይህ ገፅ የቡራዩ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ካቴድራል ፍኖተ ሰላም ሰንበት ትምህርት ቤት መልዕክቶችን ዘመኑ በሚፈቅደው መንገድ እንዲተላለፍበት በህዝብ ግንኙነት ክፍል የሚመራ ይፋዊ ገጽ ነው። 📞+251944247165 ሀሳብ አስተያየት ካሎት @finoteselam27PR በinbox አድራሻችን ያድረሱን።

Show more
1 637
Subscribers
+124 hours
+57 days
-930 days
Posts Archive
"ምን አልባት እግዚአብሔር ፈተናዎቻችንን ያበዛብን በጣም እንድንጠራው ፈልጎ ይሆን? በአፋችን ብቻ ሳይሆን ከልባችን በጣም እንድንቀርበው ፈልጎ ቢሆንስ.….. እግራችንንና አፋችንን ብቻ ሳይሆን ልባችን
"ምን አልባት እግዚአብሔር ፈተናዎቻችንን ያበዛብን በጣም እንድንጠራው ፈልጎ ይሆን? በአፋችን ብቻ ሳይሆን ከልባችን በጣም እንድንቀርበው ፈልጎ ቢሆንስ.….. እግራችንንና አፋችንን ብቻ ሳይሆን ልባችንንም ወደ እግዚአብሔር እናቅርብ…! እግዚአብሔርን ጠርቶና ቀርቦ ያፈረ የለምና! እግዚአብሔርን ይዘን በትዕግስት ከጠበቅን እሩቁም ቅርብ ትልቁም እንደ ትንሽ ይሆናልና” መልካሙን ፍሬ ለማግኘት ሁሌም በትዕግስት እንጠብቅ፡፡"

#የመረጃ_ሰዓት በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና በብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው የተመራ የቤተክርስቲያናችን ልዑክ አርሲ-አቦምሳ ወረዳ ተገኝቶ ምዕመናንን አጽናና ጊዜያዊ እርዳታም አበረከተ። የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ በአርሲ ዞን አንዳንድ ወረዳዎች የተከሰተውን ችግር ተከትሎ በብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁና በብፁዕ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊው የሚመራ የቤተክርስቲያናችን ልዑክ በሥፍራው በመገኘት ተጎጂዎችን እንዲያጽናና ጊዜያዊ ርዳታም እንዲያደርግ ያስተላለፈውን ውሳኔ ተከትሎ ዛሬ ማለዳ ወደ አርሲ ዞን አቦምሳ ወረዳ በመጓዝ ጉዳት የደረሰባቸውን ወገኖች አጽናንቷል፤ ጊዜያዊ እርዳታም አበርክቷል። በአቦምሳ ወረዳ የትንሣኤ ብርሃን ደብረ ገነት መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን በመገኘት ተጎጂ ኦርቶዶክሳዊያንን ያጽናኑት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ፣የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት ቅድስት ቤተክርስቲያን በኦርቶዶክሳዊያን ልጆቿ ላይ በደረሰው ጉዳት እጅግ በጣም ማዘኗን ገልጸው እግዚአብሔር አምላክ ለሞቱት ወገኖቻችን መንግስተሰማያትን እንዲያወርስልን፣ለቤተሰቦቻቸው መጽናናት እንዲያድልልን የዘወትር ጸሎታችን ነው።በርቱ፣ጠንክሩ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን ብለዋል። አያይዘውም ቋሚ ሲኖዶስ በአካል ተገኝቶ እናንተን ለማጽናናትና ጊዜያዊ ድጋፍ ለማድረግ በመካከላችሁ ተገኝተናል ያሉት ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ችግሩን ከመሰረቱ ለመፍታትና የተቃጠለውን ቤተክርስቲያን ለመሥራት የሚያስቼል አቢይ ኮሚቴ በጠቅላይ ቤተክህነት ተሰይሞ ወደ ሥራ ገብቷል ብለዋል። በመርሐ ግብሩ ላይ የተገኙት ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት አባታዊ መልዕክት ቅድስት ቤተክርስቲያን በተከሰተው ችግር ጥልቅ ኃዘን የተሰማት መሆኑን ገልጸው ምዕመናን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ፣በፈተና ሁሉ እንዲታገሱ አደራ ካሉ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ኃዘንተኞችን እንዲያጽናና ከዳግም ኃዘን እንዲሰውርልን ዘወትር እንጸልያለን በማለት ቃለ ምዕዳንና ቃለ ቡራኬ ሰጥተዋል። በመጨረሻም ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ለተፈናቀሉ ወገኖች የተዘጋጀውን ርዳታ ለሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ለብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ አስረክበዋል።በዚሁ ጊዜ የአቦምሳ ከተማ የሀገር ሽማግሌዎችና አባ ገዳዎች ብፁዓን አባቶችን እንኳን ደህና መጣችሁልን በማለት በሀገሩ ባህል መሰረት የሰንጋ ስጦታ ካበረከቱ በኋላ የደረሰውን ጉዳት በመኮነን ሕዝቡ በስምምነት፣በአንድነትና በመቻል የኖረና ወደፊትም የሚኖር ሕዝበብ መሆኑን ጠቅሰው የተፈጠረውን ችግር ሃይማኖታዊ መልክ ለማስያዝ የሚደረገው ጥረት ተገቢነት የሌለው ነው ብለዋል።ለብፁዓን አባቶች የተበረከተው የሰንጋ ስጦታም ለተፈናቀሉ ወገኖች እንዲደርስ ተደርጎ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል። ምንጭ:- የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ _ ፍኖተ ሰላም ሚዲያ

#“ኦርቶዶክሳዊ ኢኮኖሚ ትስስር” #እሁድ 3:30-5:30 #የጎልማሶች_ጉባኤ
#“ኦርቶዶክሳዊ ኢኮኖሚ ትስስር” #እሁድ 3:30-5:30 #የጎልማሶች_ጉባኤ

ቋሚ ሲኖዶስ በምሥራቅ አርሲ የተጎዱ ወገኖችን የሚያጽናኑ በፁዓን አባቶችን መደበ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ  በምሥራቅ አርሲ ሀገረ ስብከት ተገኝተው ጉዳት የደረሰባቸውን ኦርቶዶክሳዊያን የሚያጽናኑ ብፁዓን አባቶችን መደበ። የቋሚ ሲኖዶስ አባላት በምሥራቅ አርሲ ሀገረ ስብከት በአሰኮ፣ በሺርካ፣ በሆንቆሎ ዋቤ ወረዳዎች በኦርቶዶክሳውያን ወገኖቻችን ላይ የደረሰውን ጥቃት ተከትሎ በዛሬው ዕለት ባካሔደው መደበኛ ስብሰባው  በችግሩ ምክንያት ለተፈናቀሉ ወገኖች ድጋፍ እንዲደረግ፣ በብፁዓን አባቶች የሚመራ የቤተ ክርስቲያናችን ልዑካን ቡድን ችግሩ ወደ ተፈጠረበት ቦታ በመሄድ ተጎጂዎችን እንዲጎበኝ፣ እንዲያጽናና እና አስፈላጊውን ጊዜያዊ ድጋፍ አንዲያደርግ ወስኗል። ቋሚ ሲኖዶስ በጠቅላይ ቤተክህነት በኩል በሚቋቋም ኮሚቴ አስተባባሪነትም  በተፈጠረው ችግር ምከንያት የመቃጠል አደጋ የደረሰበት ጥንታዊው የጠላታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን እንዲያሰራ፣ከቀያቸው የተፈናቀሉ ወገኖች በቋሚነት ወደ መኖሪያቸው እንዲመለሱ፣ በሀገረ ስብከቱ  ዳግመኛ መሰል ችግሮች እንዳይፈጠርሩ ጥናት አካሒዶ ከመፍትሔ ሐሳብ ጭምር የሚያቀርብ ዐቢይ ኮሚቴ ተሰይሞ በአስቸኳይ ወደ ሥራ እንዲገባ ወስኗል። ምንጭ:- EOTC _ ፍኖተ_ሰላም_ሚዲያ

#የመረጃ_ሰዓት በአርሲ ሀገረ ስብከት በኦርቶዶክሳውያን ላይ የደረሰውን ጥቃት አስመልክቶ  ከኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ሰላም ሚኒስቴርና ከኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ውይይት ተደረገ ! የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምሥራቅ አርሲ ሀገረ ስብከት አንዳንድ ወረዳዎች በታጣቂዎች በተፈጸመ ጥቃት በኦርቶዶክሳውያን ወገኖቻችን ላይ የደረሰውን ሕልፈተ ሕይወትና የቤተ ክርስቲያን መቃጠልን በማስመልከት የተሰማትን ጥልቅ ኀዘን በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት አማካኝነት ከገለጸች በኋላ ቋሚ ሲኖዶስ በጉዳዩ ዙሪያ ጥልቅ ውይይት በማድረግ ያሳለፈውን ውሳኔ ተከትሎ በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና በብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የተመራ ከፍተኛ የቤተክርስቲያናችን የልዑካን ቡድን ከሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ መሀመድ እድሪስ ፣ ከሚኒስትር ዲኤታው ከዶ/ር ኸይረዲን ተዘራና ከሚኒስትር መስሪያ ቤቱ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች ጋር ተወያይተዋል። በውይይቱ ወቅት ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስና ብፁዕ አቡነ ዲዮስሮስ በምሥራቅ አርሲ በአሰኮ፣ በሺርካ፣ በሆንቆሎ ዋቤ ወረዳዎች በኦርቶዶክሳውያን ወገኖቻችን ላይ በደረሰው የሕይወት ጉዳት እና በጥንታዊው ቤተ ክርስቲያን መቃጠል እጅግ ማዘናቸውን ገልጸው መንግሥት የችግሩን ምንጭ አጣርቶ ዘላቂ መፍትሔ እንዲፈልግና በአካባቢውም አስተማማኝ ሰላምን እንዲያሰፍን አጽንኦት ሰጥተው ገልጸዋል። አያይዘውም በአሁኑ ወቅት በችግሩ ምክንያት የተፈናቀሉ ወገኖች ወደ ቀያቸው የሚመለሱበትና መልሰው የሚቋቋሙበት ሥራ እንዲሠራ፣ ወንጀሉን የፈጸሙ ሰዎችም ለፍርድ ቀርበው ቅጣታቸውን እንዲያገኙ እንዲደረግ ጠይቀዋል። በውይይቱ ላይ የተገኙት ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የምሥራቅ አርሲና የጅግጅጋ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሀገረ ስብከታቸው የተከሰተውን ችግር በማስመልከት ዝርዝር መረጃዎችን በቊጥራዊ ማስረጃዎች አስደግፈው አቅርበዋል። የሰላም ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ መሐመድ እድሪስ በበኩላቸው በተፈጠረው ችግር እጅግ በጣም ማዘናቸውን ገልጸው በመንግሥት በኩል በአስቸኳይ አጣሪ ቡድን ተቋቁም ወደ ስፍራው ተልኳል ካሉ በኋላ የአጣሪ ቡድኑን ሪፖርት መሠረት በማድረግም አስፈላጊው እርምጃ ይወሰዳል ብለዋል። ከዚሁ ጉዳይ ጋር በተያያዘ ብፁዓን አባቶቻችን በኦሮሚያ ፕ/ት ጽ/ቤት ከኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና ከብልጽግና ፓርቲ ድ/ ቤት አመራሮች ጋር ዝርዝር ውይይት አድርገዋል። በውይይቱ ወቅት የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እንደገለጹት የክልሉ መንግሥት በሥፍራው የተከሰተውን ችግር ለመቆጣጠርና ሊከሰት ይችል የነበረውን ተጨማሪ አደጋን ለመከላከል የሚያስችል ከፍተኛ ተጋድሎ ማድረጉን፣ በአሁኑ ወቅትም ወደ ሥፍራው አጣሪ ቡድን መላኩንና የማጣራት ውጤቱን ተከትሎም አጥፊዎችን ለሕግ የማቅረቡ ሥራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ጠቁመው ቤተክርስቲያኗ ምዕመናንን ለማጽናናትና ድጋፍ ለማድረግ በምታደርገው ጥረት ሁሉ የክልሉ መንግሥት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደረግላት ገልጸዋል። በተያያዘ ዜና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቋሚ ሲኖዶስ እና የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የተፈናቀሉ ወገኖችን ለመደገፍ፣ወደ ቀያቸው ለመመለስ እንዲሁም የተቃጠለውን ቤተ ክርስቲያን መልሶ ለመገንባት እና በአካባቢው ዳግመኛ መሰል ችግር እንዳይፈጠር ለማድረግ የሚያስችል ሥራ በተጠናከረ መልኩ እንደሚያከናውኑ ከልዑካን ቡድኑ ጋር ባደረጉት የማጠቃለያ ውይይት ገልጸዋል። ምንጭ:- ኢኦተቤ ሕዝብ ግንኙነት መምሪያ _ ፍኖተ ሰላም ሚዲያ

#የመረጃ_ሰዓት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙሃን አግልግሎት ሥርጭት ድርጅት ለቀንዲል ሚዲያ  እና ፕሮዳክሽን  መርሐግብርን በሳተላይት በቴሌቪዥን እንዲያቀርብ  የውል ስምምነት አድርገ። ቀንዲል ሚዲያ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ዶግማ ቀኖና እና ትውፊትን በጠበቀ መልኩ በሳተላይት በቴሌቪዥን መርሐግብሩን እንዲያቀርብ  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን አግልግሎት ሥርጭት ድርጅት ጋር    የውል ስምምነት አድርገዋል። በውል ስምምነቱ መጋቤ ሃይማኖት ቆሞስ አባ አብራሃም ገረመው  የሰሜን አፍሪካ ሀገረ ስብከት ዋና ስራ አስኪያጅ ፣የቅዱስ ሲኖዶስ ም/ጻሐፊ እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን አግልግሎት ሥርጭት ድርጅት ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ቀሲስ አካለወልድ ተሰማ እንዲሁም  የቀንዲል ሚዲያ ባለቤት እና ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ዲያቆን ቀዳሜፀጋ ዮሐንስ በተገኙበት የውል ስምምነቱ ተካሂዷል። ዶ/ር ቀሲስ አካለወልድ ተሰማ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቴሌቪዥን በቅዱስ ሲኖዶስ የተቋቋመ ሚዲያ እንደመሆኑ መጠን የቤተክርስቲያኗን መንፈሳዊ መልዕክቶች እና አስተምህሮዎች በተጨማሪም የቤተክርስቲያኗን  የልማት ሥራዎች  እና አስተዳደራዊ እንቅስቃሴዎችን በሳተላይት ቴሌቪዥን እና በሌሎች ዲጂታል ሚዲያዎች ለምእመናን ተደራሽ እያደረገ እንደሚገኝ  በመግለጽ እስካሁን በቤተክርስቲያችን ሊቃውንት ወንጌልን የማስተማር ሥራ እና አጠቃላይ የቤተክርስቲያኗ ገጽታ ምን እንደሚመስል ለመላው ለዓለም ለማሳየት እየተሠራ መቆየቱን ገልጸዋል። የዲጂታል ሚዲያ በመጠቀም  በርካታ ቤተክርስቲያንን የተመለከቱ ይዘቶች ከሚሠሩ የቤተክርስቲያን ልጆች መካከል የቀንዲል ሚዲያም ባለቤት ሊቀ ዲያቆን ቀዳሜጸጋ አንዱ መሆኑን በመግለጽ ከአሁን በፊት በቅንዲል ሚዲያ የሚስተላለፍቸውን ይዘቶች ከቤተክርስቲያን አኳያ መዝነን በጋራ ለመሥራት ፈቅደናል ተናግረዋል። ይህ ስምምነት ለሌሎች ዲጂታል ሚዲያዎችን ተጠቅመው ለሚሠሩ  የቤተክርስቲያን ልጆች በር የከፍተ ነው በማለት ሰዓቱም ዘውትር እሑድ ከምሽቱ ሁለት ሰዓት እስከ ሦስት ሰዓት እንደሆነ እና  ለሚዲያውም ተጨማሪ አቅም እንደሚሆን ተናግረው መልካም  የሥራ ጊዜ እንዲሆንላችው መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል። መጋቤ ሃይማኖት ቆሞስ አባ አብርሃም ባድረጉት ንግግር ቀንዲል ሚዲያ በተጨማሪ በሳተላይት ቴሌቪዥን የአየር ሰዓት ማግኘት መቻሉ ለሚዲያው ጥሩ እድል መሆኑን ገልጸው ሚዲያው የቤተክርስቲኗ ልሣን እና ትልቅ ሚዲያ መሆኑን በመገንዘብ በትጋት መሥራት እንደሚገባ አባታዊ መልዕክት አስተላልፈዋል። ሊቀ ዲያቆን ቀዳሜጸጋ ዮሐንስ በበኩላቸው ከዩቲዮብ አልፎ  ወደ ሳተላይትን ቴሌቪዥን እንድንሠራ ይህን ፍቃድ ማግኝት በመቻላችን ትልቅ ዕድል ነው በማለት  ለሁሉም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መገናኛ ብዙኃን አግልግሎት ሥርጭት ድርጀት የሥራ ሓላፊዎችን አመስግነዋል። በቀጣይም ቤተክርስቲያንን በሚገልጽ መልኩ ለማግልገልና ድምፅ ለመሆን ለመሥራት ጥረት እናደርጋለን ብለዋል። መገናኛ ብዙኃን አግልግሎት ሥርጭት የዲጂታል ሚዲያ ማስታወቂያ እና ገበያ ዋና ክፍል ኃላፊ መ/ር አቤል አሰፋ ድርጀቱ ከሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት እና ከጉራጌ ሀገረ ስብከት ጋር እየሠራ መሆኑን ገልጸው ሌሎች አህጉረ ስብከት እና መንፈሳዊ ተቋማት በአየር ሰዓት መጋራት አብረው እንዲሠሩ ጥሪ አቅርበዋል። _ ፍኖተ ሰላም ሚዲያ

#የመረጃ_ሰዓት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት በአርሲ ሀገረ ስብከት በቤተ ክርስቲያናችን እና በኦርቶዶክሳውያን ላይ የደረሰውን ጥቃት በማስመልከት  አባታዊ መልእክት አስተላለፉ። ቅዱስነታቸው  ያስተላለፉት አባታዊ የኀዘን  መልእክት እንደሚከተለው  ነው፦ መልእክተ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡ ‹‹ወረሰዩ አብድንቲሆሙ ለአግብርቲከ መብልዐ ለአዕዋፈ ሰማይ፣ ወሥጋሆሙኒ ለጻድቃኒከ ለአራዊተ ገዳም፦ የአገልጋዮችህንም በድኖች ለሰማይ ወፎች መብል አደረጉ፥ የቅዱሳንህንም ሥጋ ለምድር አራዊት።›› (መዝሙረ ዳዊት ፸፰፥፪) በአርሲ ሀገረ ስብከት በአሰኮ፣ በሽርካ፣ በሆንቆሎ፣ በዋቤ እና በሙኔሳ ወረዳዎች በመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችንና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ላይ ስለደረሰው አሰቃቂ ጥቃት የሰማነው በተሰበረ ልብ ነው። የእምነት ነፃነት ተደፍሮ መቶ ዓመታት ያስቆጠረው የጠላታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በተቃጠለበት፣ እንዲሁም የካራ ኩፍቴና መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በተዘረፈበት በዚህ ክፉ ቀን፤ በርካታ ምእመናን በግፍ መሰዋታቸውና በመቶዎች የሚቆጠሩ ወገኖቻችን ከቀዬአቸው መፈናቀላቸው ቤተ ክርስቲያናችንን በእጅጉ ያሳዘነ ክስተት ነው። የሰላም፣ የፍቅርና የታሪክ ማህደር የሆነችው ቤተ ክርስቲያን በምድራዊ መከራ ውስጥ ያሉትን ምእመናን በምታጽናናበት በዚህ ወቅት ራሷ በፈተና ውስጥ ሆና ከመቸገሯም በላይ በአርሲ ምድር በተደጋጋሚ የሚስተዋለው በደልና ግፍ በሁላችንም ልቡና ውስጥ "እስከ መቼ?" የሚል የቁጭት እና የኀዘን ጥያቄን ፈጥሯል። በመሆኑም ይህ መከራ እያበቃ ሳይሆን እየሰፋ በመምጣቱ የዜጎችን ደኅንነት የመጠበቅና ሰላምን የማስፈን አደራ የተጣለባችሁ የጸጥታ አካላትና በየመዋቅሩ ያላችሁ ሓላፊዎች ከምንም በላይ ታሪክ የሚጠይቃችሁ በሥልጣን ዘመናችሁ ለዜጎች ደኅንነት በምትከፍሉት ዋጋ ነውና ይህንን የጥቃት ሰንሰለት በማስቆምና ወንጀለኞችን ለሕግ በማቅረብ ከታሪክ ባለዕዳነት ትድኑ ዘንድ በቤተ ክርስቲያናችን ስም አበክረን እናሳስባለን። በየአካባቢው የምትገኙ ምእመናንና መላው ኢትዮጵያውያንም በወንድማማችነት መንፈስ ተጋግዛችሁ፣ የተፈናቀሉ ወገኖችን በመደገፍና በጸሎት ከቤተክርስቲያናችን ጎን እንድትሆኑ ጥሪያችንን እናቀርባለን። በመጨረሻም ቤተ ክርስቲያናችን ለሰላም፣ ለይቅርታና ለሰው ልጆች ክብር ሁል ጊዜ የምትቆም መሆኑን በመግለጽ ይህንን የኀዘን ሰዓት አምላካችን በምሕረቱ ያሳልፍልን፣ የሞቱትን ነፍሶቻቸውን በመንግሥቱ ይቀበልልን፣ የተጎዱትንም በቸርነቱ ያጽናናልን በማለት አባታዊ የኀዘን መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን። እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!! ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!! አሜን።  አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ግንቦት 26 ቀን 2018 ዓ.ም. አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ ምንጭ:- የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት _ ፍኖተ ሰላም ሚዲያ