uk
Feedback
አቡቀለምሲስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

አቡቀለምሲስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሚዲያ

Відкрити в Telegram

አቡቀለምሲስ ማለት ረአየ ኅቡኣት አበ ራዕይ አበ ትንቢት ማለት ሲሆን የተሰወረውን የተደበቀውን የተከደነውን የሚገልጥ ማለት ነው። መሠራታዊ ዓለማው በሀገረ ስብከታችን ብሎም በመላ ቤተ ክርስቲያናችን የተሰወሩ ገዳማትን የተደበቁ ሊቃውንትን የተከደኑ ታሪኮችን የተሸሸጉ ቅርሶችን ማውጣት እና የተንሸዋረረ ታሪክ ማስተካከልና የጎበጠውን አዲሱን ትውልድ ማነጽ ነው መረጃ t.me/AbukelemsisSMSbot

Показати більше
2 443
Підписники
+124 години
+77 днів
+730 день
Архів дописів
"ከእግዚአብሔር ጋር የኾኑ ሰዎች እግዚአብሔር አላቸው፤ እግዚአብሔር ያግዛቸዋል ይረዳቸዋል በችግር ውስጥ ሲኾኑ እረዳት ያዝላቸዋል።" ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ቀዳማዊ የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በየዓመቱ ሐምሌ ፲፱ የሚከበረው የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል በድምቀት ተከብሮ ዋለ። ሐምሌ ፲፱ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም ፦ አቡቀለምሲስ ሚዲያ (ደብረ ብርሃን) +++++ +++++ +++++ +++++ +++++ ብርሃናዊው መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስ እና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ከእሳት የማዳኑ ነገር የሚታሰብበት ዓመታዊ ክብረ በዓል በደብረ ብርሃን ከተማ በጠባሴ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ቀዳማዊ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያና የሰሜን ሸዋ ሀገረስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት በድምቀት ተከብሮ ውሏል። በክብረ በዓሉ ላይ የደብሩ ሊቃውንት እንዲሁም የሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያን በዓሉን የሚገልጥ ስብሃተ እግዚአብሔር ያቀረቡ ሲኾን በመጋቤ ብሉይ ወሐዲስ መምህር ግሩም በዓሉን የተመለከተ ትምህርት "መሰንቆ" በሚል ርእስ ተሰጥቷል። በመሰንቆ ብዙ ጭራዎች ተሰብስበው አንድ ድምጽ እንደሚወጡ ያነሱት መምህሩ መሰንቆ አበው በአንድነት የለበሱት ሃይማኖት ነው በማለት ሃይማኖትን በመሰንቆ መስለው አስተምረዋል። ቅዱስ ቂርቆስ እና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ በሃይማኖታቸው የተነሳ ከሀገራቸው እንደተሰደዱ፤ ንጉሥ እለእስክንድሮስ ለጣዖት ይሰግዱ ዘንድ መከራን እንዳጸናባቸው አንስተው በሰፊው ያስተማሩ ሲኾን ለሃይማኖት ልንሞት ልንሰደድ እንደሚገባ አመላክተዋል። ቅዱስ ቂርቆስ በንጉሡ ፊት ቆሞ ስሙን በተጠየቀ ጊዜ "ክርስቲያን ነኝ" በማለት መለሰ ያሉት መምህሩ ቅዱስ ቂርቆስ የራሱን ስም ትቶ በአምላኩ ተጠራ ብለዋል። ንጉሡ ቅዱስ ቂርቆስ እና ቅድስት ኢየሉጣ ለጣዖት እንዲሰግዱ ልዩ ልዩ ማባበያዎች እንዳቀረቡላቸው ሕጻኑ እና እናቱ ግን እግዚአብሔርን በማመን ጸንተው እንደቆሙ ገልጠዋል። ስለሃይማኖታቸው ጽናት ልዩ ልዩ መከራ እንደጸናባቸው እግዚአብሔርን በማመናቸው ተስፋም በማድረጋቸው አዳኝ መልአክ እየላከ እንደታደጋቸው በመጨረሻም በዛሬው እለት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ ከእሳት እንዳዳናቸው አብራርተዋል። መምህሩ ለሕጻኑ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ ስለተጋድሎው የተገባለትን የምሕረት ቃልኪዳን ገልጠው ከቅዱሳኑ መማር ስለሚገባን የሃይማኖት ጽናት በብዙ ሞሳሌ እየመሰሉ አብራርተዋል። ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ቀዳማዊ በክብረ በዓሉ ላይ አባታዊ ቡራኬ የሰጡ ሲኾን ቅዱሳን በሕይወት የኖሩትን እኛ የምንማረው ተጋድሏቸውን ሰምተን እንደነርሱ እንድንኖር መኖር ባንችል እንኳ በእነርሱ በረከት መልካም ሥራ መሥራት እንድንችል ነው ብለዋል። ብፁዕነታቸው ከእግዚአብሔር ጋር የኾኑ ሰዎች እግዚአብሔር አላቸው፤ እግዚአብሔር ያግዛቸዋል ይረዳቸዋል በችግር ውስጥ ሲኾኑ እረዳት ያዝላቸዋል ሲሉም አክለዋል። ብፁዕነታቸው ዛሬ ያየነው ቅዱስ ቂርቆስ እና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣ ከእግዚአብሔር ጋር ንግግር ከጣዖት አምላኪዎች ጋር ክርክር ያደረጉትን ነው ጣዖት አምላኪዎች ሁልጊዜ ሰዎች ለጣዖቶቻቸው እንዲገዙ እንደሚሹ ዛሬም በሕይወታችን መሰናክል የሚፈጥሩ በክርስትና ሕይወታችን ላይ ፈተና የሚያመጡ ብዙዎች ናቸው። ነገር ግን እንደ ቅዱሳኑ በፈተና ጸንተን ለክርስትናችን መታመን ይገባናል ሲሉ መክረዋል። ዛሬ ክርስትናችንን መናገር እናፍራለን፤ ክፋት፣ መለያየት፣ መነቃቀፍም ክርስትናችን መሰናክል እንዲገጥመው እያደረጉን ነው፤ ለቅዱሳኑ፣ ለእውነተኞቹ፣ ጥርጥር ለሌላቸው ቅዱስ እግዚአብሔርን ቅርብ ነው፤ እግዚአብሔር ለክርስቲያኖች ይበቀልላቸዋል ያሉ ሲኾን ዛሬም ክርስቲያኖች እየደረሰባቸው ላለው ፈተና ዋጋን ይከፍላቸዋል ብለዋል። አላዊው ንጉሥ ቅዱስ ቂርቆስን እና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን ለጣዖት እንዲሰግዱ ባደረገ ጊዜ በመጽናታቸው ስለሃይማኖታቸው መከራንም በመቀበላቸው እግዚአብሔር መልአኩን ልኮ አዳናቸው ተበቀለላቸው ያሉት ብፁዕነታቸው የሚለካን የሚመዝነን የሚያድነን ቅዱስ እግዚአብሔር አለ ነገር ግን እኛ በእምነት መጽናት መልካም መሥራት ይገባናል ብለዋል። ዛሬ የቅዱስ ቂርቆስን ሕይወት እያየን የእኛን እየገመገምን ነው። ዛሬ የምንሠራው በደል ጽድቅ እየመሠለን መጥቷል ክፋት በዝቷል የቅዱሳን ታሪክ ለሕይወት ስንቅ ነውና በቅድስና ሕይወታችን እንዲመራ ያግዘናል ሲሉም አክለዋል። ችግርን አስወጋጅ እግዚአብሔር ነውና ለሚደርስብን ፈተና እራሳችንን በማየት ወደርሱ መመለስ ወደሱ መጠጋት ያስፈልጋል ይህን እናደርግ ዘንድ የቅዱሳን ታሪክ ያግዘናል ቅዱስ ቂርቆስ እና ቅድስት ኢየሉጣ በመጽናታቸው መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል መጥቶ ችግራቸውን አስወገደላቸው እኛም ዛሬ በዚህ የተሰበሰብን ሁላችን የምንፈልገው በረከት ነውና የሰማነው የእግዚአብሔር ቃል የደረቀውን መራራ ሕይወታችንን ያለመልማል ይህ የሚሆነው ግን ታማኝ ስንኾን ነው፣ እግዚአብሔር የታማኞች አምላክ ነውና ሲሉም አባታዊ የሕይወት መመሪያ ሰጥተዋል። በክብረ በዓሉ ላይ የሀገረስብከቱ ልኡካን፣ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ የአብነት ደቀመዛሙርት እና መምህራን፣ የወንጌል ሰባክያን፣ ካህናት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ዘማርያን እንዲሁም በርካታ ቁጥር ያላቸው የአካባቢወሰ ምእመናን ተገኝተዋል።

በየዓመቱ ሐምሌ ፲፱ የሚከበረው የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ክብረ በዓል በጠባሴ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በብፁዕነታቸው ቡራኬ በድምቀት እየተከበረ ነው። ሐምሌ ፲፱ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም ፦ አቡቀለምሲስ ሚዲያ (ደብረ ብርሃን) ++++ +++++ +++++ ++++ ++++ +++++ +++ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ሕጻኑ ቅዱስ ቂርቆስን እና እናቱ ቅድስት ኢየሉጣን በምልጃው የመርዳቱ ነገር የሚታሰብበት በዓል በጠባሴ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ቀዳማዊ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ጠቅላይ ቤተ ክህነት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያና የሰሜን ሸዋ ሀገረስብከት ሊቀ ጳጳስ ቡራኬ በድምቀት እየተከበረ ነው።

"ሥልጠናቸውን ሲከታተሉ የቆዩ 49 ካህናት፣ ማኅበረሰባዊ ሰላምን የመገንባትና ምእመናን የማስታረቅ ትልቅ አደራ በመቀበል ዛሬ በደመቀ ሁኔታ ተመረቁ" ሐምሌ ፲፩ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም (አቡቀለምሲስ ሚዲያ ፤ ደብረ ብርሃን) ++++ +++++ +++++ +++++ +++++ ++++ በመንዝ ማማ ምድር ወረዳ ለ3 ወራት የተሰጠውን መንፈሳዊና መዋቅራዊ ሥልጠና ሲከታተሉ የቆዩ 49 ካህናት፣ ማኅበረሰባዊ ሰላምን የመገንባትና የማስተማር ትልቅ ሐዋርያዊ አደራ በመቀበል በዛሬው ዕለት ተመርቀዋል። በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት የትምህርትና ሥልጠና ክፍል ኃላፊ መልአከ ሕይወት ሙሉጌታ መኮንን እንደገለጹት፦ካህናቱ ያገኟቸውን በርካታ መንፈሳዊ እውቀቶች፣ የዜማና የቅዳሴ ጥበቦችን መሠረት በማድረግ ለቤተክርስቲያን ዕድገትና ለሕዝቡ መንፈሳዊ ሕይወት መታደስ በትጋት ማገልገል ይኖርባችኋል ብለዋል። ​ሓላፊው አክለውም «ጥበብ እንደ ጡት አሳደገችኝ» የሚለውን የቅዱስ ያሬድን ትምህርት በመጥቀስ፣ ካህናቱ በእውቀት ላይ እውቀትን፣ በጥበብ ላይ ጥበብን ጨምረው ሕዝባቸውን ወደ እግዚአብሔር የበረከት መንገድ የመምራት ትልቅ አደራ እንደተጣለባቸው አስገንዝበዋል። ሥልጠናው በተለይም ወቅቱ አስቸጋሪ በነበረበትና ማኅበራዊ ትስስሮች ፈታኝ በሆኑበት ወቅት የተሰጠ በመሆኑ፣ ካህናቱ ሌትና ቀን ሳይሉ በታላቅ ተጋድሎ እውቀት ሲገበዩ መቆየታቸው ተገልጿል። ተመራቂ ካህናቱ ከተሰማሩበት የአገልግሎት መስክ ባሻገር፣ ወደ ማኅበረሰቡ ዘልቀው በመግባት ሰላምን የማስፈን፣ የተጣሉትን የማስታረቅና የተከዘውን ሕዝበ ክርስቲያንን የማጽናናት የወቅቱ የላቀ ኃላፊነት እንዳለባቸው መልአከ ሕይወት ሙሉጌታ በጽንኦት አሳስበዋል። የወረዳው ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት በጽሐ ወንድአፍራሽ በበኩላቸው ልጠናው ከወትሮው በተለየ መልኩ ሌሊትን ጨምሮ በከፍተኛ ትጋትና ቁርጠኝነት የተሰጠ በመሆኑ የተገኘውን ዕውቀት ወደ ተግባር መለወጥ እንደሚገባ አሳስበዋል። ​ለ3ኛ ዙር የተሰጠውን ይህንን የካህናትና ሥልጠና ወደፊት ራሱን የቻለ ተቋም በማድረግ ወደ ኮሌጅ ደረጃ ለማሳደግ ራእይ እንዳለው ጠቁመው ለዚህም የወረዳው አስተዳደር ለኮሌጁ መሥሪያ የሚሆን ቦታ ለመስጠት ቃል መግባቱን ገልጸዋል። መንዝ የሃይማኖት መገኛና የታሪክ ማኅደር መሆኑን የጠቀሱት ሊቀ ካህናት በጽሐ፦ከተለያዩ የዓለም ክፍሎች ወደ ዘብር ገብርኤል፣ አርባ ሐራ እና እመዕጓል ገዳማት የሚመጡ ምእመናንና ጎብኚዎችን በአግባቡ ለማስተናገድና በቂ መረጃ ለመስጠት ሠልጣኞቹ የተማሩትን ዕውቀት ሊጠቀሙበት ይገገባል ብለዋል። ምንም ዓይነት የገንዘብ ክፍያና ደመወዝ ሳይጠይቁ፣ ለሀገርና ለሃይማኖት ካላቸው ፍቅር የተነሳ በነፃ ስልጠናውን የሰጡ መምህራንንና አሰልጣኞችን ያመሰገኑ ሲሆን ለወደፊቱም በብፁዕ አባታችን አቡነ ቀሌምንጦስ ፊርማ ልዩ ዕውቅናና ሽልማት እንደሚበረከትላቸው ቃል ገብተዋል። የመንዝ ማማ ምድር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ መርሻ ኃይሉ ለሰልጣኞቹ የመንዝን ሃይማኖታዊና ባህላዊ ፣ ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ሀብቶች እንዲሁም የእንግዳ አቀባበል ዕሴቶቻችንን በማስተዋወቅ ለአካባቢው የቱሪዝም ኢኮኖሚያዊ አበርክቶ የድርሻችሁን መወጣት አለባችሁ ብለዋል። ከውጭም ሆነ ከሀገር ውስጥ ወደ መንዝ የሚመጡ እንግዶችን በተገቢው እንክብካቤ ማስተናገድ እንደሚገባ እና ልዩነቶችን በመቻቻልና በሰላማዊ መንገድ መፍታት እንዲቻል የሃይማኖት አባቶች በጎ አሻራ ታሳርፉ ዘንድ አደራ ለማለት እወዳለሁ ብለዋል። የሞላሌ ከተማ ከንቲባ አቶ አብርሃም አድምቄ በበኩላቸው በሃይማኖታዊ ዘርፍ የሚሰጠውን ትምህርትና ሥልጠና ወደ ኮሌጅ ደረጃ ለማሳደግ በወረዳው ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ለቀረበው የቦታ አቅርቦት ጥያቄ ከተማ አስተዳደሩ ፈጣን ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል። ​አቶ አብርሃም አክለውም የቀረበውን ጥያቄ የአመራር አካላት ውይይት ካደረጉ በኋላ በከተማዋን ማስተር ፕላን መሠረት ለ5ቱም መንዞችና ለ2ቱ የከተማ አስተዳደሮች የተቀናጀ አገልግሎት የሚሰጥና ለቀጣዩ ትውልድ በዘላቂነት የሚያገለግል የጋራ ማዕከል ምቹ ቦታ ለመስጠት ዝግጁነን ብለዋል። በመጨረሻም በምረቃው የሀገረ ስብከቱ ጠቅላላ አገልግሎት ክፍል ሓላፊ መልአከ ሰላም ደረጀ ካሳን ጨምሮ የገዳማትና የአድባራት አስተዳዳሪዎች የተገኙ ሲሆን በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የተፈረመ የምሥክር ወረቀት እና የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ ሰልጣኞች እውቅና በመስጠት መርሐ-ግብሩ በጸሎት ተጠናቋል።

"የእኛ ሕይወት የእግዚአብሔር ድንኳን ነው" ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ሐምሌ ፯ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም (አቡቀለምሲስ ሚዲያ ፤ ደብረ ብርሃን) ++++ +++++ +++++ +++++ +++++ ++++ በየዓመቱ ሐምሌ 7 ቀን የሚከበረው የቅድስት ሥላሴ ዓመታዊ በዓል ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽሕፈት ቤት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያና የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በተገኙበት በድምቀት። በዓሉን በማስመልከት መጋቤ ሐዲስ ነቅዐጥበብ ከፍያለው (ኢንጂነር) "የአብርሃም ድንኳን" በሚል ኃይለ ቃል በበዓሉ ላይ ለታደሙ ምእመናን ትምህርተ ወንጌል ሰጥተዋል ። በተለይም በአብርሃም ድንኳን ውስጥ የተከናወኑት ምሥጢራት እጅግ ሰፊ መሆናቸውን በመጥቀስ፣ አምስቱ አዕማደ ምሥጣራት በዚህ ታሪክ ውስጥ በጥልቀት እንደሚገለጡ አስረድተዋል። ​አብርሃም ቀድሞ አብራም (የጥቂቶች አባት) ይባል እንደነበርና በኋላ ግን እግዚአብሔር ስሙን ቀይሮ አብርሃም (የብዙዎች አባት) እንዳለው ተገልጿል። የአምልኮተ ጣዖት ስርጭት በዓለም ላይ በሰፋበትና የሰው ልጅ በጠፋበት ወቅት፣ አብርሃም ጣዖታትን ሰባብሮ እውነተኛውን ፈጣሪ መፈለጉና እግዚአብሔርም በአካል ሳይሆን በድምጽ ጠርቶት ከአባቱ ቤት ወጥቶ ወደ ተስፋይቱ ምድር መጓዙ ትልቅ የእምነት ምሳሌ ነው ብለዋል። ለአብርሃም የተገለጠውን መለኮታዊ ምሥጢር ሲተርኩ ሦስቱ ሰዎች (ሥላሴ) በአብርሃም ድንኳን ደጃፍ፣ በመምሬ አድባር ዛፍ ሥር በቀትር ሰዓት መገለጣቸውን መምህሩ አብራርተዋል። ቀትር አዳም ዕፀ በለስን የበላበት ፤ ሳምራዊቷን ሴት ውኃ አጠጭኝ ብሎ የጠየቀበት እና ሰብአዊነት በጠፋበትና የሰው ልጅ በኃጢአት በዛለበት በቀትር ሰዓት፣ ጌታችን መጥቶ ሁላችንንም ለማዳን በመስቀል ላይ የተገለጠበት መሆኑን አስረድተዋል። በድንኳኑ ደጃፍ የታዩት ሦስት ሰዎች መሆናቸውን መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚናገር እና አብርሃምም ይህንን ምሥጢር ተረድቶ ሦስት መስፈሪያ ዱቄት አምጥቶ ሳራ አንድ ቂጣ እንድታደርገው ማዘዙ ሦስቱ መስፈሪያ የሦስትነታቸው አብ፣ ወልድ፣ መንፈስ ቅዱስ አንዱ ቂጣ ደግሞ የአንድነታቸው የአንድ አምላክ ምሳሌ መሆኑን ምሥጢረ ሥላሴን ይገልጣል ብለዋል። ​ከሦስቱ አካላት አንዱ የሆነው እግዚአብሔር ወልድ በኋላ ዘመን ከድንግል ማርያም ተወልዶ ሰው እንደሚሆን ለማሳየት ሦስቱም ሰው መስለው ታይተዋል ፣ በዚህም ሥላሴ ለአብርሃም የነገሩት የምሥራች የይስሐቅን መወለድ ብቻ ሳይሆን፣ ከይስሐቅ ዘር ክርስቶስ ተወልዶ ዓለምን እንደሚያድን ምሥጢረ ሥጋዌን ያስረዳል ብለዋል። አብርሃም ሦስቱን እንግዶች ውኃ ላምጣና እግራችሁን ታጠቡ ማለቱ የጥምቀት ምሳሌ መሆኑን ያብራሩት መምህሩ ጌታችንም በዮሐንስ ወንጌል ላይ በተመሳሳይ መልኩ የደቀ መዛሙርቱን እግር በማጠብና በአብ፣ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም አጥምቁ ማለቱ ምሥጢረ ጥምቀትን በተግባር አሳይቷል ብለዋል። ​አብርሃም ቁራሽ እንጀራ ላምጣላችሁና ልባችሁን ደግፉ ማለቱ በቀጥታ የጌታችንን ቅዱስ ስጋና ክቡር ደም የሚያመለክት ሲሆን ይህ መለኮታዊ ምግብ የሰውን ልጅ ልብ የሚደግፍና ዘላለማዊ ሕይወትን የሚሰጥ መሆኑን ያሳያል ብለዋል። ​ የይስሐቅ ለመሥዋዕትነት ወደ ሞርያም ተራ መውጣት እና ሳይታረድ መዳኑ እንዲሁም የሳራ በእርጅና ዘመኗ መውለድ የምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን ምሳሌ መሆኑን አብራርተዋል። ዛሬ በየደጃችን፣ በየኪሳችንና በየስልካችን ጣዖት የሌለው የለም የገንዘብ፣ የዝሙት፣ የመለያየትና የጥላቻ ጣዖታት በየቤታችን ገብቷል እና እግዚአብሔር አብርሃምን ከጣዖት አምልኮ ነጻ እንዳወጣው ሁሉ እኛንም ከዚህ ሁሉ ጣዖት አምልኮ ሕይወታችንን ይጠብቅልን ትውልዱንም ይታደግልን ብለዋል። ​ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ለመንፈስ ቅዱስ ልጆቻቸው ባስተላለፉትን ቃለ በረከት የእያንዳንዱ ሰው ሕይወት ከእግዚአብሔር ጋር ሊኖረው የሚገባውን ጥልቅ ትስስርና የአባታችን የአብርሃምን ሕይወት አርአያነት አብራርተዋል። ​ብፁዕነታቸው በትምህርታቸው መግቢያ ላይ እንደገለጹት፣ አባታችን አብርሃም በተፈጥሮ ተመራምሮ፣ በአእምሮ ጠባዩ እግዚአብሔርን ያወቀና ያገኘ ታላቅ አባት ሲሆን በሕይወቱ በመታዘዝና እግዚአብሔርን በፈቃዱ በመከተሉ ሕይወቱ ተባርኳል ብለዋል። ​የአብርሃም ድንኳን የሥላሴ ማደሪያ ነበረች ያሉት ብፁዕነታቸው የአብርሃምን ሕይወትና ድንኳን ከእኛ የዕለት ተዕለት ሕይወት ጋር በማስተሳሰር የእኛ ሕይወት እግዚአብሔር የሚቆጣጠረው፣ የሚቃኘውና ከእግዚአብሔር የማይሰወር ሕያው ነፍስ ተዋሕዶት ያለ ድንኳን ነው ብለዋል። የንስሐና የመታዘዝ ሕይወት፦ ይህ የሕይወት ድንኳናችን ከእድፍና ከእርኩሰት ነጽቶ ሊቀደስ የሚችለው ንስሐ መግባት ስንችልና ለእግዚአብሔር ስንታዘዝ ብቻ ነውም ብለዋል። የእግዚአብሔር ማደሪያ ለመሆን የወንድማማች ፍቅር፣ የሀገራዊ ፍቅርና የቤተሰባዊ ፍቅር በውስጣችን ሊኖር ይገባል ያሉት ብፁዕነታቸዎ የወደድነውን ነገር መተው ስንችል እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ይሆናል ብለዋል። ሲሉ ብፁዕነታቸው አስተምረዋል። ​ ​ዛሬ ላይ በገዛ ፈቃዱ ከእግዚአብሔር የራቀና የእግዚአብሔርን ቸርነት ረስቶ የሚኖር ሰው ቁጥሩ ቀላል አለመሆኑን የገለጹት ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ለዚህ ሁሉ ችግር መፍትሔው የአብርሃማዊ ሕይወትና ሥነ-ምግባር ባለቤት መሆን እንደሚገባ አሳስበዋል። እኛ እልከኝነቱን፣ ክፋቱን፣ ተንኮሉን፣ ምቀኝነቱን፣ ቅናቱንና አድመኝነቱን በአጠቃላይ ክፉ ሕይወትን ከእኛ ማስወገድ ይገባናል፤ ሥላሴም ያስወግዱልናል ሲሉ አሳስበዋል። የጎደለው ሁሉ እንዲሞላ፣ የሻከረው እንዲለሰልስና የጠፋው እንዲገኝ የእግዚአብሔር ቸርነት አይለየን ሀገራችን ኢትዮጵያን ይባርክ፤ ከክፉ ነገር ሁሉ ይጠብቃት ፤ የከበደውን ሁሉ ያቅልልን፤ ፍቅሩንም በልባችን ያሳድርብን በማለት ቃለ በረከት አስተላልፈዋል። ​በክብረ በዓሉ ላይ የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ክቡር መጋቤ ሐዲስ ነቅዐጥበብ አባቡን ጨምሮ የሀገረ ስብከቱ የየክፍል ሓላፊዎች ፣ የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት የሰው ኃይል አስተዳደር ክፍል ሓላፊ እና የደብሩ ጸሐፊ ሊቀ ሥዩማን ፍጹም እንግዳ እና የደብሩ አስተዳዳሪ መልአከ ሰላም ቄስ ፈቃደ ጎሽሜ ተገኝተዋል። በተመሳሳይ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች ፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፣ ታዋቂ ዘማርያን ፣ የደብሩ ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ፣በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ምእመናን በተገኙበት በታላቅ ድምቀት ተከብሮ ውሏል።