አግባባዊ የመድኃኒት አጠቃቀም መመሪያ ቁጥር 1138/2018
የኢትዮጵያ የምግብና መድኃኒት ባለሥልጣን የሕክምና መድኃኒቶች ያለአግባብ መወሰድና መላመድን ለመግታት የሚያስችል ጠንካራ ቁጥጥር ሥርዓት የያዘ አዲስ «አግባባዊ የመድኃኒት አጠቃቀም መመሪያ ቁጥር 1138/2018» በሥራ ላይ ውሏል።
💊
የመድኃኒት በድጋሚ ዕደላና ቁጥጥር
• ታካሚዎች በታዘዘላቸው መመርያ መሠረት መድኃኒት በአግባቡ አለመጠቀማቸው፣ ለሱስ የመጋለጥ ሥጋት ማሳየታቸው ወይም የሕክምና ውጤታማነት ማጣት እንደገጠማቸው ሲታወቅ የመድኃኒት ባለሙያዎች መድኃኒቱን በድጋሚ ከመስጠት ተቆጥበው ታካሚውን ወደ ታከመበት ሐኪም ቤት እንዲልኩ መመሪያው ያስገድዳል።
• ማንኛውም የመድኃኒት ባለሙያ መድኃኒት በአንድ ማዘዣ እንደገና ለማደል የሚችለው የሕክምና ባለሙያ በመድኃኒት ማዘዣው ላይ በድጋሚ ማደል እንደሚቻል የገለጸ እንደሆነ ብቻ ነው።
• ማንኛውም የመድኃኒት ባለሙያ መድኃኒት በድጋሚ ሲያድል በመድኃኒት ማዛዣው ላይ ከተገለጸው መድኃኒት ዓይነት፣ የአወሳሰድ መንገድ፣ መጠን፣ ብዛት፣ ወይም ድግግሞሽ የተለየ ማደል እንደማይችልም ተገልጿል።
የመድኃኒት ባለሙያ መድኃኒት በድጋሚ ሲያድል፤
- ታካሚው መድኃኒትን በአግባቡ አለመጠቀም፣
- በመድኃኒቱ ሱስኝነት መጋለጥ፣
- የታዘዘን መመሪያ አለመከተል፣
- የሕክምና ውጤታማነት ማጣት ወይም የደኅንነት ሥጋቶች መኖሩን ሲጠረጥር መድኃኒቱን በድጋሚ ከመስጠት መቆጠብና ታካሚውን ወደ ሚመለከተው የሕክምና ክፍል ወይም ተቋም መላክ ይኖርበታል።
አንድ ፋርማሲስት ማንኛውንም መድኃኒት በድጋሚ ሲያድል እንደገና ማደሉ የተከናወነበት ቀን፣ በዕለቱ የታደለው መጠንና የሚቀረው ድግግሞሽ የተመለከተ መረጃን በአግባቡ መዝግቦ መያዝ አለበት።
🦠
የፀረ-ተዋህስያን መድኃኒቶች አጠቃቀም ሥርዓት
• መመሪያው፣ የፀረ ተዋህስያን መድኃኒቶች በተዋህሲያን መላመድን ለመከላከልና ለመቆጣጠር የሚያስችሉ ጥብቅ ድንጋጌዎችን አካቷል።
• ማንኛውም ሆስፒታል፣ ጤና ጣቢያ ወይም ልዩ የሕክምና ማዕከል ይህንን ሥጋት ለመግታት የሚያስችል አግባባዊ የፀረ ተዋህስያን መድኃኒቶች አጠቃቀም ሥርዓት የመዘርጋት ሕጋዊ ግዴታ ተጥሎበታል።
• ማንኛውም የሕክምና ባለሙያ ክሊኒካዊ ወይም የላቦራቶሪ ምርመራ ማስረጃ ሳይኖረው ለታካሚ የፀረ ተዋህስያን ሕክምና ማስጀመር እንደሌለበት ተደንግጓል። ሆኖም ለሕይወት አሥጊ የሆነ ኢንፌክሽን መኖሩ ከተጠረጠረ ሕክምናውን ወዲያውኑ መጀመር እንደሚቻል ተፈቅዷል።
የፀረ-ተዋስያን መድኃኒቶች መጋቢ ኮሚቴ ፦
እያንዳንዱ ሆስፒታልና ጤና ጣቢያ " የፀረ-ተዋስያን መድኃኒቶች መጋቢ ኮሚቴ" የማቋቋም ግዴታ አለበት።
ኮሚቴው የፀረ-ተዋስያን መድኃኒቶችን አቅርቦት፣ አያያዝ፣ አዘዘዝና አጠቃቀም ይከታተላል፤ ተገቢነቱን ለማረጋገጥም የቅድመ ኦዲትና የቅድመ ፈቃድ አሠራሮችን ተግባራዊ ያደርጋል።
መድኃኒቶቹን "በተደራሽ"፣ "ትኩረት የሚሹ" እና "መጠባበቂያ" በማለት ይመድባል። ብክነትን ለመከላከል፣ በብሔራዊ መዘርዝር "በመጠባበቂያ" ሥር ያሉትን መድኃኒቶች ወደ ትኩረት የሚሹ ወይም ተደራሽ ዝርዝር ዝቅ አድርጎ ማካተት ፈጽሞ የተከለከለ ነው።
💻
የኤሌክትሮኒክስ ማዘዣ (Electronic Prescription) ሥርዓት፦
• እያንዳንዱ የኤሌክትሮኒክስ ማዘዣ ተከታታይ መለያ ቁጥር (Serial Number) ሊኖረውና ለተፈቀደላቸው የጤና ባለሙያዎች ብቻ ተደራሽ መሆን አለበት።
• አንዴ ከተሰጠ በኋላ ከራሱ ከሐኪሙ ውጪ በማንም ሊቀየር አይችልም፤ ከተቀየረም የተሟላ መረጃው መመዝገብ አለበት።
• ታካሚው መድኃኒቱን ከተቋሙ መግዛት ካልፈለገ፣ ተቋሙ ማዘዣውን አትሞ (
Print አድርጎ) የመስጠት ግዴታ አለበት።
• ማዘዣዎች በማዕከላዊ ቋት (
Database) ወይም በወረቀት ታትመው
ቢያንስ ለሁለት ዓመታት መቀመጥ አለባቸው። ሲስተሙም አስተማማኝ የምትክ ቅጂ (
Backup) ሊኖረው ይገባል።
⚖️
ጥፋቶችና አዲሱ የአስተዳደራዊ ቅጣት መሰላል ፦
ነባሩ መመሪያ ፈቃድ ለማያሳግዱ ጥፋቶች ማስጠንቀቂያ የሚሰጥና ማስተካከያ ካልተደረገ ወደ ሌላ እርምጃ የሚሻገር የነበረ ሲሆን፣ አዲሱ መመሪያ ግን ይበልጥ ግልጽና ጠንካራ የቅጣት መሰላል ዘርግቷል።
በዚህም ማንኛውም ሰው ግዴታውን ካልተወጣ ወይም ሕገወጥ ድርጊት ፈጽሞ ከተገኘ፣ ፈቃድ የሰጠው አካል ከማስጠንቀቂያና ከገንዘብ መቀጮ ባለፈ የብቃት ማረጋገጫን ወይም የሙያ ፈቃድን እስከ ማገድና መሰረዝ የሚደርስ ከባድ እርምጃ በቀጥታ የመውሰድ ሥልጣን ተሰጥቶታል።
ባለሥልጣኑ መመሪያው መጣሱን ካረጋገጠ፣ ምርቱን ከመያዝ፣ እንዲወገድ ወይም ወደ መጣበት ተቋም እንዲመለስ ከማዘዝ በተጨማሪ፣ ጥፋቱን ፈቃድ ለሰጠው አካል በማሳወቅ እርምጃ እንዲወሰድ ያደርጋል።
አግባብ ያለው አካል የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ እንዲሰጥ የሚያስገድዱ 11 የጥፋት ዓይነቶች ተለይተዋል። ከእነዚህም መካከል ፦
° ያለ ምርመራ መድኃኒት ማዘዝ፣
° ሕግ ያላሟላ ማዘዣ መጠቀም፣
° ያለ በቂ ምክንያት በንግድ ስም (Brand Name) ማዘዝ ወይም ማደል ይገኙበታል።
የአገልግሎት ጊዜያቸው ያለፈባቸውን ማዘዣዎች መጠቀም የተከለከለ ሲሆን፣ ከተጻፈ 30 ቀናት ያለፈበትን መደበኛ ማዘዣ ወይም ከተገዛ 7 ቀናት ያለፈበትን የአንቲባዮቲክስ ማዘዣ በመጠቀም መድኃኒት ያደለ ባለሙያ የጽሑፍ ማስጠንቀቂያ ይሰጠዋል።
መመሪያው ጥፋት በሚያዘወትሩና የደኅንነት ሥጋት በሚፈጥሩ ባለሙያዎችና ተቋማት ላይ እስከ 1 ዓመት የሚደርስ የፈቃድ ዕገዳ ጥሏል። እርምጃው የሚወሰደውም፦
- በኮፒ ማዘዣ መድኃኒት በጨመረ፣
- በአንድ ማዘዣ ከአንድ ጊዜ በላይ ባደለ፣
- የተሳሳተ ወይም ያልታዘዘ መድኃኒት በሰጠ፣
- የታካሚን ክብርና ሚስጥር ባልጠበቀ፣ እንዲሁም ያለ ማዘዣ ወይም ባልተፈቀደ ተቋም መድኃኒት በቀመመ ላይ ነው።
ይህ መረጃ ባለቤትነቱ የሪፖርተር ጋዜጣ ነው።
@tikvahethiopia