ru
Feedback
Gurage Zone Government Communication Affairs

Gurage Zone Government Communication Affairs

Открыть в Telegram

Gurage Zone Government Communication Affairs

Больше
1 569
Подписчики
Нет данных24 часа
+77 дней
-630 день
Архив постов
በዞኑ ለሁለት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የነበረው የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በሰላማዊ መልኩ መጠናቀቁን የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ገለጸ። ሰኔ 9/2018ዓ.ም (ወልቂጤ) በዞኑ የዘንድሮ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በስኬት እንዲጠናቀቅ በቅንጅት የተሰራው ስራ በቀጣይም በ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ላይ መድገም እንደሚገባም ተመላክቷል። የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ መብራቴ ወልደማርያም የፈተናው መጠናቀቅ አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ በዞኑ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ያለምንም ችግር በሰላማዊ መልኩ መጠናቀቁን ገልጸዋል። በዞኑ በ3መቶ 80 አስፈታኝ ትምህርት ቤቶችና በጉድኝት ማእከላት በማደራጀት 18 ሺህ 3 መቶ 90 ተማሪዎች ክልል አቀፍ ፈተናው መውሰዳቸው ገልፀዋል። በዞኑ የዘንድሮ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በሰላማዊ መልኩ ለማጠናቀቅ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት በማድረግ በቅንጅት በተሰራው ስራ ፈተናው በስኬት ማጠናቀቅ መቻሉንም አስረድተዋል። ክልል አቀፍ ፈተናው በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላደረጉ በየደረጃው ላሉ አመራሮች፣ አስፈጻሚዎች፣ ለትምህርት አመራሮች እና ለጸጥታ አካላት አቶ መብራቴ ምስጋና አቅርበውዋል። ይህ ውጤታማነትና ቅንጅት በቀጣይ ከሰኔ 11 እስከ 12 በሚሰጠው የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ላይ መድገም እንደሚገባም አስገንዝበዋል።

የዘንድሮ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተናው ከኩረጃ ነጻና በሰላማዊ መልኩ በመስጠት በስኬት ለማጠናቀቅ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ ሊወጣ እንደሚገባ ተገለጸ። ሰኔ 8/2018ዓ.ም (ወልቂጤ) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ እና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፈቃዱ በዛሬው እለት እየተሰጠ ያለውን ክልል አቀፍ ፈተና አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሀን ማብራሪያ ሰጥተዋል በአዲሱ ትምህርት እና ስልጠና ፖሊሲ በ6ኛ፣በ8ኛ እና በ12 ኛ ክፍል በተለያዩ እርከኖች ተማሪዎች ክልል አቀፍ እና ሀገር አቀፍ ፈተና ይወስዳሉ በማለት ርዕሰ መስተዳድሩ አብራርተዋል። በተያዘው የትምህርት ዘመን የ6 ኛ ክፍል ተማሪዎች ለፈተና በቂ ዝግጅት እንዲያደርጉ በትኩረት መሰራቱን ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ አመላክተዋል። ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት በክልሉ 91ሺህ 9መቶ 18 የ6ኛ ክፍል ተማሪዎች ክልላዊ ፈተናውን እየወሰዱ ይገኛሉ። ቢሮው በዘንድሮ ዓመት ለሚሰጠው ሀገራዊና ክልላዊ ፈተና ተማሪዎች የማዘጋጀት ስራ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል። የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተናው ከሰኔ 8 እስከ 9 ከኩረጃ ነጻ በሆነ መልኩ እንደሚሰጥ የጠቀሱት አቶ አንተነህ በቀጣይ ከሰኔ 10 ጀምሮ በክልሉ የ8ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተና ይሰጣል ብለዋል። የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ መብራቴ ወልደማርያም በበኩላቸው ፈተናው በዞኑ በ3መቶ 80 አስፈታኝ ትምህርት ቤቶችና በ2 መቶ 24 የፈተና ማዕከላት 18 ሺህ 4መቶ 60 ተማሪዎች እንደሚወስዱ አንስተው ከነዚህም ውስጥ 8ሺህ 9መቶ 71 ተማሪዎች ሴቶች መሆናቸውንም ተገልጿል። ለፈተናው ከአመቱ መጀመሪያ ጀምሮ ተማሪዎች የማብቃትና የመደገፍ ስራ መሰራቱን ያነሱት አቶ መብራቴ ከዚህም ባለፈ ለፈታኞች፣ ለሱፐርቫይዘሮች፣ ለጣቢያ ኃላፊዎች፣ ለፈተና ማዕከላትና ለጸጥታ አካላት ልየታና ኦረንቴሽን የመስጠት ስራ ሲሰራ መቆየቱንም ተናግረዋል። በዞኑ የዘንድሮ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በስኬት ለማጠናቀቅ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት ሲደረግ መቆየቱንም አንስተዋል። ፈተናው ከአዲስ አበባ ከህትመት ማዕከል በሰላማዊ መልኩ ወደ ዞኑ በማስገባት ከዞኑ ወደ ሁሉም ወረዳና ከተማ አስተዳደሮችና ፈተና ጣቢያዎች በሰላማዊ መልኩ እንዲሰራጭ መደረጉንም አመላክተዋል። ክልል አቀፍ ፈተናው በሰላማዊ መልኩና ከኩረጃ ነጻ በመስጠት በስኬት እንዲጠናቀቅ ወላጆች፣ ፈታኝ መምህራን፣ ፈተና አስፈጻሚዎች፣ ቤተሰብና የጸጥታ አካላት ጨምሮ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ መወጣት እንዳለበትም አስገንዝበዋል።

ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) የ6ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተና አስጀመሩ ሰኔ 8/2018(ወልቂጤ) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድ እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) የ6ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተና በወልቂጤ ከተማ በያበሮስ 2ኛ ደረጃ ት/ቤት አስጀምረዋል። ርዕሰ መስተዳድ እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) በማዕከሉ የፈተና አሰጣጥ ሂደት ምን እንደሚመስል በየክፍሉ ተዟዙረው የተመለከቱ ሲሆን ተማሪዎች በራስ መተማመን መንፈስ ፈተናውን በተረጋጋ መልኩ እንዲሰሩ አበረታተዋል። በክልሉ 91918 የ6ኛ ክፍል ተማሪዎች ክልላዊ ፈተናውን እየወሰዱ እንደሆነ ተጠቅሷል። የ6ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተናው ዛሬ እና ነገ ተሰጥቶ የሚጠናቀቅ ሲሆን ቀጥሎ በክልሉ የ8ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተና መሰጠት እንደሚጀምር ተገልጿል። ቢሮው በዘንድሮ ዓመት ለሚሰጠው ሀገራዊና ክልላዊ ፈተና ተማሪዎች የማዘጋጀት ስራ በትኩረት ሲከናወን መቆየቱን ጠቁመዋል። በማስጀመርያ መርኃ ግብሩ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው(ዶ/ር)፣ የክልሉ የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ ክብርት ወይዘሮ ፋጤ ስርሞሎ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈ-ጉባኤ አቶ አቡቶ አኒቶ፣ የክልሉ ምክትል ርዕሰ መስተዳድርና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፍቃዱ፣ የዞኑ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ ጨምሮ ሌሎችም የክልሉ፣ የዞኑና የከተማው ከፍተኛ የመንግስት የስራ ኃላፊዎችና ሌሎችም ተገኝተዋል።

በጉራጌ ዞን የጽዱ ኢትዮጵያ እሳቤ አመርቂ ውጤት እያስመዘገበ ከመሆኑም ባሻገር ህብረተሰቡ ባህል እያደረገው ይገኛል፦አቶ አየለ ፈቀደ ሰኔ 6/2018 ዓ.ም (ወልቂጤ) በጉራጌ ዞን ጌታ ወረዳ የኽብያቴ ጽዱ ቀበሌ የተለያዩ እንግዶችና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ነጭ ባንድራ በመስቀል በዛሬው እለት ተመርቋል። በወረዳው ከጽዱ ቀበሌነት ባለፈ ከቤት ለቤት ወሊድ ነጻ የሆኑ መንደሮችን የመፍጠርና የጆፎረ ማስፋት የኮሪደር ልማት ስራዎች በስፋት እየተከናወኑ ይገኛሉ። በምረቃው ስነ ስርአት ላይ የተገኙት የጉራጌ ዞን ጤና መምሪያ ሀላፊ አቶ አየለ ፈቀደ እንዳሉት በዞኑ የጽዱ ኢትዮጵያ ኢንሼቲቭ ተግባራዊ በማድረግ በርካታ ቀበሌዎች ጽዱ ማድረግ መቻሉም አስታውሰዋል። በዞኑ 87 በመቶ የሚሆኑ ቀበሌዎች ሜዳ ላይ ከመፀዳዳት ነፃ በሚል የማስመረቅ ስራ መሰራቱም የተናገሩት አቶ አየለ እስከ ሰኔ 30/2018 ድረስ ሁሉም ቀበሌዎች ጽዱ በማድረግ ለማስመረቅ አቅደው እየሰሩ እንደሆነ ተናግረዋል። የዞኑ የተሻሻለ መጸዳጃ ቤት ሽፋኑ ከፍ ለማድረግ አጽኖት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሚገኝ የተናገሩት አቶ አየለ በዞኑ አጠቃላይ ካለው አባወራ 69 በመቶ የሚሆኑ አባወራዎችና እማወራዎች መጸዳጃ ቤታቸው የተሻሻለ ማድረግ ችለዋል ብለዋል። በጌታ ወረዳ የኽብያቴ ቀበሌ ከአር ነጸና ጽዱ ቀበሌ በሚል በዛሬው እለት ነጭ ባንድራ የመስቀል ማስመረቅ እንደተቻለ የጠቆሙት ሀላፊው በወረዳው እናቶች ገንዘብ በሠቆጠብ የአካባቢና የግል ንጽህና ስራዎች በስፋት እየሰሩ ያለበት ሁኔታ መኖሩም አስረድተዋል። የጌታ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ በህሩ ኽይረዲን በበኩላቸው እንዳሉት ጤና የሁሉም ነገር መሰረት ነው ብለው በጤናው ዘርፍ የሚሰሩ ስራዎች በተደራጀ መንገድ በመምራት የተሻለ ውጤት ማምጣት ይቻላል ብለዋል። የአካባቢና የግል ንጽህና ለመጠበቅ በወረዳው ከ2017 መግቢያ ጀምሮ በብዙ ቀበሌዎች ተግባራዊ ማድረግና በዘርፉ ውጤታማ ስራዎች በመስራት ማህበረሰቡ ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉም አስረድተዋል። ስንቀናጅና ስንተባበር ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል የተናገሩት አቶ በህሩ በወረዳው ጽዱ ቀበሌና መንደር ለመፍጠር እየተሰሩ ያሉ ውጤታማ ስራዎች በሁሉም ቀበሌዎች ማስፋት እንደሚገባም አመላክተዋል። ከግልና ከአካባቢ ጽዱ ቀበሌነት ባለፈ የቤት ለቤት ወሊድ ጭምር ነጻ የሆነ ቀበሌ ነጻ ቀበሌ እንዲሁም ከኮሪደር ልማት ጋር ተያይዞ በገጠር ቀበሌ የጆፎሮ ማስፋት በሚል በርካታ ስራዎች ሲሰሩ መቆየታቸውም አስረድተዋል። የጌታ ወረዳ ጤና ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ አብድሃሚድ መሀመድ እንዳሉት ጥራቱን የጠበቀ፣ ፍትሃዊና ተደራሽ የጤና አገልግሎት ለማህበረሰቡ በመስጠት በወረዳው የህዝቡ የጤና ደህንነት ለመጠበቅ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እየተከናወነ ይገኛል። በንጽህና ጉድለት የሚመጡ ተላላፊና መሰል በሽታዎች ለመከላከል ደረጃውን የጠበቀ የግለሰብና የጋራ መጸዳጃ ቤቶች ገንብተው እንዲጠቀሙ በማድረግ እንዲሁም ከመጸዳጃ ቤት መልስ እጅን በአግባቡ በውሃና በሳሙና እንዲጠቀሙ ለማድረግ ሰፊ የግንዛቤ ስራ መሰራቱና በዚህም በተጨባጭ ውጤት እየተመዘገበ ይገኛል ብለዋል። የጽዱ ኢትዮጵያ ኢንሼቲቭ በወረዳው ተግባራዊ መደረግ ከተጀመረ በኋላ በርካታ ስራዎች ማከናወን የተቻለ ሲሆን በዚህም ጽዱ ቀበሌ ለመፍጠር ሰፊ የማህበረሰብ ንቅናቄ በመፍጠርና በዘርፍ ውጤታማ ስራ ማከናወን መቻሉም አስታውሰዋል። የጠቅላይ ሚኒስቴር ዶክተር አብይ አህመድ የጽዱ ኢትዮጵያ ኢንሼቲቭ ከዩኒሴፍ ጋር በመተባበር ላውንች ከተደረገበት ጊዜ አንስቶ በርካታ ስራዎች ማከናወን የቻሉ እንደሆነም የተናገሩት ሀላፊው በ2018 በጀት አመት በወረዳው 7 ቀበሌዎች ታርጌት በማድረግ ሶስት ቀበሌዎች ሙሉ ለሙሉ ጽዱ በማድረግ ነጭ ባንድራ በመስቀል ማስመረቅ እንደተቻለና 4 ቀበሌዎች ለማስመረቅ ጫፍ መድረሳቸውም አስረድተዋል። ወይዘሮ አመቱ ብዛ እና ወይዘሮ ወርቅነሽ ንበርጋ በወረዳው የኽብያቴ ቀበሌ ልዩ ስሙ የሰህረይ መንደር ነዋሪ ሲሆኑ ቀበሌያየው ጽዱ ለማድረግ የተሻሻለ መጸዳጃ ቤት ገንብተው እየተጠቀሙ እንደሆነም ተናግረዋል። የግልና የአካባቢ ንጽህና ለመጠቅ ሴቶች በአንድ ለአስር አደረጃጀት ገንዘብ በመቆጠብ የተሻሻለ መጸዳጃ ቤት መገንባት ፣ግቢያቸው በማጽዳትና ጆፎሮን በመጥረግና በማስዋብ ውጤታማ ስራ እየሰሩ እንደሆነ ተናግረዋል ሲል የዘገበው የጉራጌ ዞን የመንግስት ኮሚኒኬሽን መምሪያ ነው።

በዞኑ ከሰኔ 8 ጀምሮ የሚሰጠው የ6ኛና 8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በስኬት ለማጠናቀቅ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት ሊሰሩ ይገባል:- አቶ መብራቴ ወልደማርያም የፊታችን ሰኞ ሰኔ 8 የሚጀምረው የ6ኛና 8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በዞኑ 38 ሺህ 277 ተማሪዎች ፈተናው ይወስዳሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ተመላክቷል። ሰኔ 4/2018ዓ.ም (ወልቂጤ) የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ የ2018 ዓ.ም ክልል አቀፍ የእርከን ማጠቃለያ የ6ኛ እና 8ኛ ክፍል ፈተና አስተዳደር የኦረንቴሽን መድረክ በወልቂጤ ከተማ ተካሂዷል። የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ መብራቴ ወልደማርያም እንዳሉት በዞኑ የ6ኛና 8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ለመስጠት መፈተኛ ክፍሎች፣ አስፈታኞች፣ የጣቢያ ኃላፊዎች፣ ሱፐርቫይዘችና ሌሎችንም የቅድመ ዝግጅት ስራ ማጠናቀቅ ተችሏል። የዘንድሮ ክልል አቀፍ ፈተና በ6ኛ ክፍል በ3መቶ 80 ትምህርት ቤቶች 18 ሺህ 4መቶ 60 ተማሪዎች ፈተናው እንደሚወስዱ አንስተው ከእነዚህ ውስጥ 8ሺ 971 ተማሪዎች ሴቶች መሆናቸውን ጠቅሰዋል። የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በ3መቶ 28 ትምህርት ቤቶች 19 ሺህ 817 ተማሪዎች ፈተናው ይወስዳሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ያነሱት ኃላፊው ከእነዚህም ውስጥ 10 ሺህ 252 ሴት ተማሪዎች ናቸው ብለዋል። ለዚህ ፈተና ነባራዊና ከባባዊ ሁኔታ ከመለየት ባለፈ የከዚህ ቀደም የ6ኛና 8ኛ ክፍል የፈተና አሰጣጥ ልምድ ይበልጥ በመጠቀም ፈተናው በሰላማዊ መልኩ ለማጠናቀቅ መስራት እንደሚገባም አመላክተዋል። ክልል አቀፍ ፈተናው በሚሰጥበት ወቅት የነዳጅ አቅርቦት ችግሮችም እንዳያጋጥሙ ከባድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እንደሚሰራ አንስተዋል። ከተማ ቀመስ አካባቢዎች ለውሸት መልስ ተጋላጭ ናቸው ያሉት አቶ መብራቴ ከዚህ ቀደም ፌክ የማህበራዊ ሚዲያ ፔጅ በመክፈት ተማሪዎች ለማደነጋገር ሲሰራ እንደነበር አስታውሰው ለዚህም ዘንድሮ ተማሪዎች ተረጋግተው ፈተናው እንዲፈተኑ ጥብቅ ጥበቃና ፍተሻ ከማጠናከር ባለፈ ለተማሪዎች ግንዛቤ መስጠት እንደሚገባ ገልጸዋል። ለፈተናው ስኬታማነት ቅንጅታዊ አሰራር ወሳኝ መሆኑን አንስተው ይህም ከጸጥታ አካላት፣ ከመምህራን ማህበርና ከሌሎችም በመቀናጀት መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል። የጉራጌ ዞን ፖሊስ አዛዥ ተወካይ ምክትል ኮማንደር ገና ደገሙ በበኩላቸው የፈተናው ደህንነት ለመጠበቅ የጸጥታ አካላት ፈተናው ከዞን እስከ ታችኛው መዋቅርና ፈተና ጣቢያዎች ድረስ ከማድረስ ባለፈ ለፈተናው ልዩ ጥበቃ ማድረግ ይኖርባቸዋል ብለዋል። ተማሪዎች ወደ ፈተና አዳራሽ ሲገቡ ከእርሳስና ከላፒስ ውጪ የኤሌክትሮኒክስ እቃዎችን ይዞ መግባት የተከለከለ መሆኑን ጠቅሰው ለዚህም ለተማሪዎች በተገቢው ኦሬንቴሽን በመስጠት ፈተናው ያለምንም ችግር በስኬት ለማጠናቀቅ መስራት እንደሚገባ ገልጸዋል። ፈተናው ተጀምሮ በሰላም እንዲጠናቀቅ የጸጥታ አካላት ሚና ወሳኝ ነው ያሉት ምክትል ኮማንደር ገና የጸጥታ ስጋት ያለባቸው አካባቢዎች በመለየት ከፌደራል ፖሊስና ከሌሎችም የጸጥታ አካላት በመቀናጀት ያለምንም የጸጥታ ችግር ለማጠናቀቅ ይሰራል ነው ያሉት። የውይይቱ ተሳታፊዎች እንዳሉት ፈተናው በሁሉም ጣቢያዎች በሰላማዊ መልኩ ለመስጠት አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት እያደረጉ መሆኑን አንስተው ይህም ይበልጥ በማጠናከር እንደሚሰሩ ጠቁመዋል። ለዚህም ፈተና ተማሪዎች በስነልቦና ዝግጅት እንዲያደርጉና ከትምህርት ቤት እንዳይርቁ እየሰሩ መሆኑን ተናግረው ከዚህ ቀደም የፈተና አሰጣጥ ልምድ ይበልጥ በመጠቀም ፈተናው በሰላማዊ መልኩ ለመስጠት እንደሚሰሩም ገልጸዋል። ይህ ኦሬንቴሽን በታችኛው መዋቅር ባለድርሻ አካላት ባማሳተፍ መልኩ ከመስጠት ባለፈ ለተማሪዎች ለመስጠት እንደሚሰሩም ተናግረዋል። በዞኑ ውስን የፀጥታ ችግር ባለባቸው ቀበሌያት አካባቢ በቂ የጸጥታ አካላት ከመመደብ ባለፈ ፈተናው ለማጓጓዝ የነዳጅ አቅርቦት ልዩ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል ብለዋል።

አመራሩ በሚቀጥሉት 20 ቀናት በበጀት ዓመቱ ልዩ ትኩረት የሚሹ ቀሪ ስራዎችን በፍጥነት በጥራትና በቁርጠኝነት ሊያሳካ ይገባል፦ክቡር አቶ ላጫ ጋሩማ ግንቦት 29/2018(ወልቂጤ)የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ክቡር አቶ ላጫ ጋሩማ በበይነ መረብ ልዩ ትኩረት የሚሹ ወቅታዊና መደበኛ ስራዎችን በመገምገም የበጀት አመቱ ቀሪ ስራዎች በሚቀጥሉት 20 ቀናት እንዲጠናቀቁ አቅጣጫ አስቀመጡ!! የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አስተዳዳሪ ክቡር አቶ ላጫ ጋሩማ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት ልዩ ትኩረት የሚሹ ወቅታዊና መደበኛ የንቅናቄ ስራዎች በበይነ መረብ ገምግመዋል!! ክቡር ዋና አስተዳዳሪው የፋይዳ መታወቂያ ስርጭት፣የኢቲዮ ኮደርስ ስልጠና፣የገጠርና የከተማ ኮሪደር ልማት ስራዎች፣የገቢ ፣የግብርና፣የንግድ፣ የስራ እድል ፈጠራና የነዳጅ ስርጭት ሁኔታ የደረሱበት አፈፃፀም ገምግመው በቀጣይ 20 ቀናት ታቅደው መሰራት ባለባቸው ተግባራት ላይ አቅጣጫ አስቀምጠዋል። ዞናችን በተያዘው በጀት ዓመት በሁሉም ዘርፎች ውጤት እያስመዘገበ የመጣና በሌሎች እካላትም በተለያዩ የሱፐርቪዥን ስራዎች የተረጋገጠ ነው በማለት እነዚህን የካበቱ ልምዶችንና የህዝባችንን አቅም በመጠቀም በሚቀጥሉት 20 ቀናት ውስጥ ቀሪ ስራዎች ሊጠናቀቁ እንደሚገባ አሳስበዋል። የህብረተሰባችን የኑሮ ጫናን ለመቀነስ በገበያ ዋጋ ማረጋጋት ላይ የምንሰራው ስራ ልዩ ትኩረት ልንሰጠው ይገባል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው የሰንበት ገበያዎች በቂ ግብዓት እንዲኖራቸው መስራት እንደሚገባ ገልፀዋል። ህገወጥ የንግድ ስራዎች ላይ ልዩ ቁጥጥር በማድረግ አላስፈላጊ የዋጋ ንረት በሚፈጥሩ ነጋዴዎች ላይ አስተማሪ እርምጃ መውሰድ ይገባል ብለዋል። በነዳጅ አቅርቦት ስጭትና ህገወጥነቶች ላይ እየተሰሩ ያሉት ስራዎች ውጤት እያስገኙ ቢሆንም አሁንም ቀሪ ስራዎች ስላሉ አቅዶ መስራት ያስፈልጋል ብለዋል። በዞኑ በተለይም በከተሞች ህገ ወጥ የነዳጅ ክምችት በሚያደርጉና በአላስፈላጊ መንገድ ነዳጅ እየሸጡ የሚገኙ አካላት ላይ ልዩ እርምጃ ሊወሰድ እንደሚገባም ጠቁመዋል። በሚቀጥሉት 20 ቀናት ያላሳካናቸው ቀሪ የአመቱ እቅዶቻችንን ምርጫን ባሳካንበት መንገድ ሙሉ በሙሉ ልናሳካ ይገባል ያሉት ክቡር አስተዳዳሪው በተለይም የገቢ ስራችን ያሉንን ሁሉም አማራጮች ተጠቅመን ገቢን አሟጣን ልንሰበስብ እንደሚገባ አሳስበዋል። በገቢ አሰባሰብ ላይ አፈፃፀማቸው ዝቅተኛ የሆኑ መዋቅሮች በሚቀጥሉት 20 ቀናት በልዩ ሁኔታ እቅዳቸውን ሊያሳኩ እንደሚገባም በመግለፅ ሁሉም አስተዳደሮች 100% እቅዳቸው ማሳካት እንደሚገባቸው አፅንዎት ሰጥተዋል። በዞኑ የተከለሰውን የገቢ እቅድ ጨምሮ እስካሁን ለመሰብሰብ ከታቀደው ከ83 በመቶ በላይ መሰብሰብ መቻሉን የጠቀሱት ዋና አስተዳዳሪው በሚቀጥሉት 20 ቀናት ውስጥ ከ810 ሚሊየን ብር በላይ በመሰብሰብ ቀሪ እቅዱን ማሳካት ይገባል ብለዋል። ወቅታዊ የግብርና ልማት ስራዎችም በተገቢውና በልዩ ትኩረት መምራት እንደሚገባ በመጠቆም ዘወትር እንደምንለው አመራሩ ከግብርና ልማት ስራዎች አይኑ ሊነቅል አይገባውም ብለዋል። በዞኑ አንድም ያልታረሰ መሬት እንዳይኖር እየተሰራ ያለው ስራ ውጤት እያስገኘ ቢሆንም በአንዳንድ መዋቅሮች የሚታየው ጉድለት በፍጥነት ማረም እንደሚገባ አሳስበዋል። ዲጂታል ኢትዮጵያ 2030 እውን ለማድረግ የፋይዳ መታወቂያ ሁሉም ሊኖረው ይገባል ያሉት ዋና አስተዳዳሪው ካለ ፋይዳ መታወቂያ ምንም አገልግሎት ማግኘት የማይቻልበት ደረጃ እየደረስን እንደሆነ ልናውቅና ህዝቡንም ልናስገነዝብ ይገባል ብለዋል። ክቡር ጠቅላይ ሚንስትራችን የ100% ግብ ብለው የያዙት የፋይዳ መታወቂያ ጉዳይ በተያዘው በጀት አመት 100% ለማሳካት መስራት እንደሚገባ በማመላከት አሁን ከተደረሰበት አፈፃፀም አንፃር ሰፊ ውስንነት እንዳለበት ጠቁመዋል። በአምስቱም ከተሞቻችን የተጀመሩ የኮሪደር ልማት ስራዎች በአጭር ቀናት እንዲጠናቀቅ ተቋራጮች 24 ሰዓት እንዲሰሩ ማድረግ ይገባል ያሉት አቶ ላጫ ለዚህም አመራሩ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አሳስበዋል። የገጠር ኮሪደር በተመለከት በአንዳንድ መዋቅሮች ተስፋ ሰጪ ጅምሮች እንዳሉ በመጠቆም ፕሮግራሙ ከሌማት ትሩፋትና ከፅዱ መንደር ጋር ማያያዝ ያስፈልጋል ብለዋል። ሞዴል የገጠር መንደር መፍጠር ላይ ታዳጊ ማዘጋጃዎች ላይ ቦታ መርጦ ወደ ተግባር የገባ መዋቅር ቁጥር አነስተኛ መሆኑን በመግለፅ በቀሪ ጊዜት በአስሩም መዋቅር ስራው ሊጀመር እንደሚገባ አሳስበዋል። ከቋሚና ጊዜያዊ ስራ እድል ፈጠራ አንፃር ያሉ አፈፃፀሞች እድገት ቢያሳዩም በelmis ከመመዝገብ አንፃር ግን ያሉ ውስንነቶች እንዲታረሙና የተለዩ ስራ አጥ ዜጎችም ከአጋሮች ጋር በመሆን ወደ ስራ የሚገቡበት መንገድ ለማመቻቸት እየተደረገ ያለው ጥረት መጠናከር እንደሚገባው ጠቁመወል። ኢትዮጵያን ወደ ተምሳሌት ሀገርነት ለመቀየር በምናደርገው ጥረት የኢትዮ-ኮደርስ ስልጠና ወሳኝ ነው ያሉ ሲሆን የነገይቱን ኢትዮጵያን ከአለም ጋር ተፎካካሪ ለማድረግ ያለመና ለቴክኖሎጂ ቅርብ የሆነ ትውልድ ለመፍጠር ፕሮግራሙ ትልቅ ሚና እንዳለው አብራርተዋል። የኢትዮ ኮደርስ ስልጠናው ከመስጠት ባሻገር ስልጠናውን ተጠቅመው ገቢ ማግኘትና ፈጠራ የጀመሩ ልጆችን ማበራከትና ማበረታታት ይገባል ብለዋል። ክቡር አስተዳዳሪው በመጨረሻም ወቅታዊ የግብርና የትምህርትና የጤና ስራዎችም በ20 ቀናት እንዲፈፀሙ ከታቀዱ ስራዎች ጋር አቀናጅቶ መምራት እንደሚገባ በመጠቆም ስራዎቹ ተገቢውን የክትትልና ግምገማ ስራዓት እንደተበጀላቸውም አስገንዝበዋል። በውይይቱ የክልል፣የዞን የወረዳና የከተማ አስተዳደር ከፍተኛ አመራሮች ጨምሮ የሚመለከታቸው ሌሎች የስራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል።

በዞኑ በ2018 በጀት ዓመት ኢኮኖሚው የሚያመነጨው የገቢ እቅድ ለማሳካትና ውጤታማ ለማድረግ የተቀናጀ ርብርብ መደረግ ይኖርበታል:- አቶ ሚነወር ሀያቱ ግንቦት 29/2018ዓ.ም(ወልቂጤ) የጉራጌ ዞን ገቢዎች መምሪያ የ2018 በጀት ዓመት የቀሪ ጊዜያት ስራዎችንና የደረጃ "ለ" ግብር አሰባሰብ የቅድመ ዝግጀት የተግባር ስራዎች አስመልክቶ በየደረጃው ከሚገኙ የገቢ አመራርና አስተባባሪ አካላት ጋር በወልቂጤ ከተማ የምክክር መድረክ አካሂዷል። የጉራጌ ዞን ገቢዎች መምሪያ ኃላፊ አቶ ሚነወር ሀያቱ እንዳሉት በዞኑ በ2018 በጀት ዓመት ኢኮኖሚው የሚያመነጨው የገቢ እቅድ ለማሳካት የቀሪ ጊዜያት ስራዎችን ውጤታማ ለማድረግ ሁሉም የገቢ አማራጮችን አሟጦ ለመሰብሰብ የተቀናጀ ርብርብ ማድረግ ይገባል። በዞኑ በበጀት አመቱ ለመሰብሰብ ከታቀደው 4 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር ከነበረበት ዞኑ ካለው ፖቴንሺያል አንጻር እቅዱ በመከለስ 4 ነጥብ 8 ቢሊዮን ለመሰብሰብ መታቀዱን ገልጸዋል። የተከለሰው እቅድ ሙሉ ለሙሉ ለማሳካት እየተሰራ መሆኑን አንስተው ይህ ዜና እስከጠናቀረበት ጊዜ ድረስ 4ቢሊዮን 18 ሚሊዮን ብር በመሰብሰብ የእቅዱ 83 ከመቶ ማሳካት መቻሉንም አቶ ሚነወር አመላክተዋል። የበጀት ዓመቱ እቅድ በማሳካት የተጀማመሩ የልማት ስራዎችን ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ በቀሪ ጊዜያት የገቢ ስራዎችን አመራሩ በልዩ ትኩረትና ቁርጠኝነት መስራት እንዳለበት ተናግረዋል። በተለይም የተለከለሰው እቅድ ተከትሎ በእስካሁኑ የተሻለ የፈጸሙ ያሉ መዋቅሮች መኖራቸውን ያነሱት ኃላፊው ከዚህም ባለፈ የአፈጻጸም ልዩነት ያለባቸው መዋቅሮች በዞኑ ልዩ ድጋፍ በማድረግ እቅዳቸውን እንዲያሳኩ ይደረጋል ነው ያሉት። ከዚህም ባለፈ በበጀት አመቱ 1ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር ከቫት ለመሰብሰብ እየተሰራ ስለመሆኑንም አንስተው ይህም በትኩረት በመሰብሰብ ገቢ ለማድረግ እየተሰራ ነው መሆኑን ጠቁመዋል። አክለውም ታክስ ካልሆኑ ከጤና፣ ከትምህርት ተቋማት፣ ከፍርድ ቤትና ንግድ ከሚያድሱ ነጋዴዎችና ከተወረሱ ንብረቶች የሚገኙ ገቢዎችን በመሰብሰብ ወደ መንግስት ቋት በማስገባት ለልማት መዋል እንዳለባቸውም ጠቁመዋል። በዞኑ በተሰበሰበው ገቢ በርካታ የልማት ስራዎች እየተሰራ መሆኑን የገለጹት አቶ ሚነወር በተለይም እየተከናወኑ ያሉ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎች ይበልጥ ውጤታማ ለማድረግ በቀሪ ጌዜያት የበጀት አመቱ እቅድ ማሳካት ይገባል ብለዋል። የበጀት ዓመቱን የገቢ ዕቅድ ለማሳካት የደረጃ 'ለ' የ2018 ግብር ዘመን ቅድመ ግብር ክፍያ በወቅቱ እንዲጠናቀቅ ልዩ ትኩረት ሠጥቶ መስራት እንደሚጠበቅም አውስተዋል። በ2019 በጀት ዓመት ለሚሰበሰበው የገቢ አሰባሰብ የመረጃ ማደራጀትና የቅድመ ዝግጅት ስራዎችም አመራሩና ባለሙያዎች በትኩረት መስራት እንዳለባቸውም አስገንዝበዋል። በመምሪያው የደንበኞች አገልግሎት የታክስ አሰባሰብና አወሳሰን ዳይሬክቶሬት አስተባባሪ አቶ ሷሊህ ጀማል የዉይይቱ ሰነድ ባቀረቡበት ወቅት ሁሉም አመራርና ባለሙያዎችን የቀሪ ጊዜት የእቅድ አፈጻጸም ለማሳካት በትኩረት መስራት ይኖርባቸዋል ብለዋል። የመድረኩ ተሳታፊዎች እንዳሉት በበጀት ዓመቱ የታቀደውን እቅድ በቀሪ ጊዜያት ለማሳካት በቁርጠኝነት እንደሚሰሩ አውስተዋል። በተለይም በዞኑ በወረዳዎችና በከተማ አስተዳደር ያሉ የገቢ አማራጮችን አሟጦ በመሰብሰብ ህብረተሰቡ እያነሳቸው ያሉ የልማትና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን ምላሽ እንዲያገኙ አመራሩና ባለሙያዎች ርብርብ ማድረግ ይገባል ብለዋል።