EBS TV
Ir al canal en Telegram
4 644
Suscriptores
-724 horas
-77 días
-11830 días
Archivo de publicaciones
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
#TPLF
አሜሪካ በህወሓት (TPLF) አመራሮች እና የቅርብ ቤተሰቦቻቸው ላይ የቪዛ እገዳ ጣለች።
የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ማርኮ ሩቢዮ፣ በሰሜን ኢትዮጵያ እንዲሁም በመላው ቀጠና ያለውን ሰላምና ደህንነት አደጋ ላይ ጥለዋል ባሏቸው የህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አባላት እና የቅርብ ቤተሰቦቻቸው ላይ የቪዛ ገደብ መጣሉን አስታውቀዋል።
ውሳኔው የተላለፈው በስደተኞችና ዜግነት አዋጅ አንቀጽ 212(a)(3)(C) በተሰጣቸው ስልጣን መሰረት መሆኑን የገለጹት ሚኒስትሩ፤ እገዳው በትግራይ ክልል ያለውን ቀውስ ለመፍታት የሚደረገውን ጥረት በሚያስተጓጉሉ " አክራሪ አቋም " ባላቸው አባላትና የቅርብ ቤተሰቦቻቸው ላይ ያነጣጠረ መሆኑን ገልጸዋል።
የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ፣ በህወሓት አመራሮችና በኢትዮጵያ መንግሥት መካከል እየተባባሰ የመጣው ውጥረት የሰሜን ኢትዮጵያን ሰላም ዳግም ስጋት ላይ መጣሉን ጠቅሷል።
በተለይም በዚህ ዓመት መጀመሪያ ላይ በትግራይ የፀጥታ ኃይሎች (TSF) እና በኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት (ENDF) መካከል የተከሰተው ቀጥተኛ ግጭት የፕሪቶሪያውን የሰላም ስምምነት ተከትሎ የተገኘውን አንጻራዊ መረጋጋት የሚፈታተን መሆኑ አመልክቷል።
አሜሪካ በሰላምና በክብር መኖር የሚፈልገውን የትግራይን ጨምሮ መላውን የኢትዮጵያ ሕዝብ መደገፏን እንደምትቀጥል የገለጸው መግለጫው፤ በቀጠናው ሰላምና መረጋጋትን በሚያናጉ አካላት ላይ ተጠያቂነትን ለማስፈን ያሉትን አማራጮች ሁሉ ጥቅም ላይ እንደምታውል አስታውቃለች።
የቪዛ እገዳ የተጣለባቸው "አክራሪ/ግትር አቋም ያራምዳሉ" የተባሉት የህወሓት (TPLF) አባላት ስም ዝርዝር በይፋ አልተገለጸም።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሰኔ 11 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
የምርጫ አስፈጻሚዎች ክፍያ መዘግየት ቅሬታና የቦርዱ ምላሽ !
የ7ኛው ጠቅላላ ሀገራዊ ምርጫ አስፈፃሚዎች የውል ክፍያቸው በወቅቱ ባለመከፈሉ ምክንያት ለከፍተኛ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጫና መዳረጋቸውን ገለጹ።
" የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በውል ስምምነቱ ላይ የተቀመጠውን የጊዜ ገደብ አላከበረም " ሲሉ ቅሬታ አቅርበዋል።
እንደ ቅሬታ አቅራቢዎቹ ገለጻ፣ ከቦርዱ ጋር በተደረገው የስራ ውል መሠረት ለ54 የሥራ ቀናት በቀን 548 ብር ታስቦ በአጠቃላይ 29,592.00 ብር ሊከፈል ስምምነት ተደርጓል።
ይሁን እንጂ አጠቃላይ የምርጫ ሥራው ተጠናቆ የሥራ ማስፈጸሚያ ቁሳቁሶች በሰነድ በተረከቡ በ15 ቀናት ውስጥ መፈጸም የነበረበት የ60 በመቶ የመጨረሻ ክፍያ (17,755.20 ብር) እስካሁን ሊከፈላቸው አልቻለም።
ከዚህም በተጨማሪ የ14 ቀናት የሥራ ክፍያ 7,672 ብር እና የ4 ቀናት የስልጠና አበል 2,192 ብር በደብዳቤ ሊከፈላቸው ቃል ተገብቶ እንደነበር አስታውሰዋል።
አሁን ባለው የኑሮ ውድነት ወቅት የክፍያው መዘግየት የዕለት ተዕለት ሕይወታቸውን ከማናጋቱም በላይ፣ ለተከናወነው ከፍተኛ አገራዊ ሥራ የሚገባውን ሙያዊ ክብር የሚያሳጣ መሆኑን አስፈፃሚዎቹ ጠቁመዋል።
ስለሆነም፣ ምርጫ ቦርድ የገባውን የውል ስምምነት በማክበር፣ የተዘገየውን አጠቃላይ ክፍያ በሰነድ ላይ በተጠቀሰው የባንክ ሒሳብ ቁጥራቸው መሠረት በአስቸኳይ ገቢ እንዲያደርግላቸው ጠይቀዋል።
ምን ምላሽ ተሰጠ ?
ትላንት በነበረው መግለጫ ወቅት ቲክቫህ ኢትዮጵያ ይህንኑ የአስፈጻሚዎች ቅሬታ ለቦርዱ አቅርቧል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉም በጉዳዩ ላይ ምላሽ ሰጥተዋል።
ወ/ሮ ሜላተወርቅ ኃይሉ ምን አሉ ?
" ከምርጫ አስፈጻሚዎች ጋር በነበረው ውል መሰረት የመጀመሪያውን 40% ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ ከፍሏል። ይህንን ለመክፈል ትልቅ ችግር ገጥሞን የነበረው በሶማሌ ክልል እና አፋር ክልል ነው።
አስፈጻሚዎቻችን አስፈጻሚዎቻችን የባንክ አካውንት ስላልነበራቸው የምርጫ ቦርድ ሰራተኞች በቦታው ተገኝተው ገንዘብ በካሽ አውጥተው መክፈል ነበረባቸው ይህንን አድርገዋል፤ የክፍያ ሂደቱን አጠናቀዋል።
ቀሪ 60 በመቶው የሚከፈለው የምርጫ አስፈጻሚዎች ከቦርዱ የተቀበሉትን ንብረት ለቦርዱ ሙሉ ለሙሉ አስረክበው ሲጨርሱ የሚከፈል ይሆናል። ይህንን የማጥራት ሂደት ጀምረናል።
ምንም አይነት የቦርዱ ንብረት በእጃቸው የሌለ አስፈጻሚዎች መክፈል ጀምረናል። ከእነሱ ጋር ያለው ንብረት ተጠናቆ ሲገባ ከሥር ከሥር ክፍያው ይፈጸማል " ብለዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
አዲስ አበባ
ሰኔ 11 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
ብልፅግና ፓርቲ ዕጩ ባላቀረበበት በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የምርጫ ክልል 11 የትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት ዕጩ የነበሩት እና የፓርላማ አባሉ አበባው ደሳለው (ዶ/ር) ድል ሳይቀናቸው ቀርቷል።
በዚህ የምርጫ ክልል ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት (ፓርላማ) አብላጫ ድምፅ በማግኘት ያሸነፉት በግል የተወዳደሩት የሪፍት ቫሊ ዩኒቨርሲቲ ምክትል ፕሬዝዳንት አበበ ገመቹ (ዶ/ር) ናቸው።
#EthiopiaElection
ሰኔ 11 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
#ምርጫ2018
ብልጽግና ፓርቲ እጩ ባቀረበበት የምርጫ ክልል ኢዜማ ፓርቲ ከፍተኛ ድምጽ አገኘ። በዚሁ አካባቢ ከዚህ ቀደም በነበረው ምርጫ ብልጽግና አሸናፊ የሚያደርገውን የህዝብ ድምጽ አላገኘም።
በትላንትናው ዕለት የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 40 የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና 35 የክልል ምክር ቤት ውጤቶችን ይፋ አድርጓል።
ይፋ ከሆኑት 40 የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ድምጾች መካከል 23 በሚሆነው የምክር ቤቱ ወንበር የብልጽግና ፓርቲ እጩዎች መቀመጫ ሲያገኙ በተቀሩት 17ቱ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ድምጽ አግኝተዋል።
ተቃዋሚ ፓርቲዎች ድምጽ ካገኙባቸው 17 ምርጫ ክልሎች በ16ቱ ብልጽግና ፓርቲ እጩ አላቀረበም ነበር። በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አማሮ ኬሌ ምርጫ ክልል ላይ ብልጽግና፤ ትብብር ለኢትዮጵያ አንድነት እና ኢዜማ ተወዳድረው የኢዜማ እጩ አብላጫ ድምጽ ማግኘት ችሏል።
የኢዜማው እጩ አወቀ አምዛዬ አሳ ከተመዘገቡት 87,521 ዜጎች 35,545 ድምጽ በማግኘት አሸናፊ የሆኑ ሲሆን፤ ይህ ውጤት እስካሁን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ አጽድቆ ይፋ ካደረጋቸው ውጤቶች ብልጽግና ፓርቲ እጩ አቅርቦ በተቃዋሚ ፓርቲ የተበለጠበት ምርጫ ክልል ያደርገዋል።
በተጨማሪም በአዲስ አበባና በኦሮሚያ የተወዳደሩ ሦስት የግል እጩዎች ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ አግኝተዋል።
የትኞቹ የተቃዋሚ ፓርቲ እጩዎች የፓርላማ መቀመጫ አገኙ ?
• ሙሳ አደም ዑመር (አፋር ህዝብ ፓርቲ) በአዋሽ ፈንታሌ ምርጫ ክልል -አፋር
• አራርሶ ቢቂላ ኤሌሞ (የግል እጩ) በደደር • 2 የምርጫ ክልል - ኦሮሚያ
• ዲማ ኖጎ ሰርቦ (የግል እጩ) ጎሬ ምርጫ ክልል - ኦሮሚያ
• ሰለሞን ታደሰ ከበደ (አዲስ ትውልድ ፓርቲ) በኮፈሌ 2 ምርጫ ክልል - ኦሮሚያ
• ደግፍ ተመስገን ሽኩሮ (ኢዜማ) እነሞርና ኤነር ምርጫ ክልል - ማዕከላዊ ኢትዮጵያ
• ዝኑር አብዱልወሀብ ኮርሴራ (ነጻነትና እኩልነት) ቅበት ምርጫ ክልል - ማዕከላዊ ኢትዮጵያ
• ጋሻው መርሻ ይማም (አብን) እስቴ 1 ምርጫ ክልል - አማራ
• መልካሙ ጸጋዬ ገላው (አብን) ላይ ጋይንት 1 ምርጫ ክልል - አማራ
• ገብረመሰቀል አደመ አንለይ (አዲኃን) - ገርጨጭ ምርጫ ክልል - አማራ
• ዩሱፍ ኢብራሂም ሽፋው (አብን) ኩታበር ምርጫ ክልል - አማራ
• ሙሐመድ ቡሹራ ዑመር (ነጻነትና እኩልነት) ሳይንት 2 ምርጫ ክልል - አማራ
• ተፈራ ጀበሮ አባሮ (ኢዜማ) ሎማ ቦሳ ምርጫ ክልል - ደቡብ ምዕራብ
• ብርሃኑ ሚስል ጳሳጋላ (ነጻነትና እኩልነት) ማጀት መደበኛ ምርጫ ክልል - ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ
• አበበ ገመቹ ሌንጮ (የግል እጩ) ምርጫ ክልል 11 - አዲስ አበባ
• ጎበዜ ጎአ ዳዱ (ወህዴግ) ሶዶ ዙሪያ ምርጫ ክልል - ደቡብ ኢትዮጵያ
• ታደሰ ወራሳ ጎዲ (ጌህዲድ) ወናጎ 3 ምርጫ ክልል - ደቡብ ኢትዮጵያ
• አወቀ አምዛዬ አሳ (ኢዜማ) አማሮ ኬሌ ምርጫ ክልል - ደቡብ ኢትዮጵያ
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሰኔ 11 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
ያለአግባብ ከተፈጸሙ ክፍያዎች ውስጥ ወደ 15 ቢሊዮን ብር አሁንም ለመንግሥት አልተመለሰም።
በ2016 በጀት ዓመትና ከዚያ በፊት ከተለያዩ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች ከሕግ ውጭ የተፈጸሙ ክፍያዎች መሆናቸው በሒሳብ ምርመራ ተረጋግጦ፣ 21 ነጥብ 5 ቢሊዮን ብር እና ከ23 ሺህ በላይ ዶላር (በአሁን ምንዛሬ 3.6 ሚሊዮን ብር) ለመንግሥት ተመላሽ እንዲሆን ጥፋቱን የፈጸሙ ተቋማት በደብዳቤ ተጠይቀው ነበር።
ይሁንና ዛሬ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የቀረበው የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የ2017 በጀት ዓመት የኦዲት ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ ከተጠየቀው ገንዘብ ውስጥ ለመንግሥት ተመላሽ የተደረገው 31 በመቶው ወይም 6 ነጥብ 6 ቢሊዮን ብሩ ብቻ ነው።
ያላግባብ ወጭ ተደርጓል፤ ለመንግስት ይመለስ የተባለው እና በውጭ ምንዛሬ 23,200 ዶላር መቶ በመቶ ለመንግስት ሳይመለስ ቀርቷል።
ተቋማቱ ሕግ ጥሰው ያላግባብ ወጪ ካደረጉት ውስጥ እስካሁን ለመንግሥት ያልመለሱትና ወደ 15 ቢሊዮን ብር የተጠጋ ገንዘብ በአስቸኳይ ተመላሽ እንዲያደርጉ በድጋሚ ጥብቅ ማሳሰቢያ ተሰጥቷቸዋል።
ከህግ ውጭ የተከፈሉ እና ለመንግስት መመለስ አለባቸው የተባሉት በአብዛኛው ፦
- በጉምሩክ
- በገቢዎች ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች
- በዩኒቨርስቲዎች የተፈፀሙ ክፍያዎች መሆናቸው ሪፖርቱ ያሳያል፡፡
ከሕግ ውጭ ከወጣው ገንዘብ ውስጥ ከ32 እስከ 99 በመቶ የሚሆነውን ለመንግሥት ካዝና ተመላሽ ያደረጉ ተቋማት የሚከተሉት ናቸው፦
✅ የቃሊቲ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ፦ 3 ነጥብ 2 ቢሊዮን ብር
✅ የኮምቦልቻ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ፦ ከ800 ሚሊዮን ብር በላይ
✅ የኤርፖርት ጉምሩክ ፦ 621 ሚሊዮን ብር
✅ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ፦ 120.7 ሚሊዮን ብር
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የመንግሥትና የሕዝብ ሀብት ባክኖ እንዳይቀር እንዲህ ያለው የሒሳብ አያያዝ መዝረክረክ በአስቸኳይ እንዲታረምና አስፈላጊው እርምጃ እንዲወሰድ በጥብቅ አስጠንቅቋል።
በሌላ በኩል ፥ የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የሒሳብ አያያዝ መመሪያዎችን በመጣስ ማስረጃ ሳይቀርብ፣ እንዲሁም መከፈል ካለበት በብልጫና በድጋሚ በተፈጸመ ክፍያ በቢሊዮን የሚቆጠር ብር ያለአግባብ ወጪ ማድረጋቸው ተረጋግጧል።
የዋና ኦዲተር በሪፖርቱ ይፋ ያደረጋቸው ተጨማሪ ግኝቶች የሚከተሉት ናቸው።
• የተሟላ የወጪ ማስረጃ ሳይቀርብ በወጪ የተመዘገበ ➔ ከ1.1 ቢሊዮን ብር በላይ
በብልጫና በድጋሚ ያላግባብ የተፈጸመ ክፍያ ➔ 280.6 ሚሊዮን ብር
• ደንብና መመሪያ ያልተከተለ ወጪ ➔
57.8 ሚሊዮን ብር
• ማስረጃ ሳይቀርብ ወጪ የተደረገ ➔ 35.8 ሚሊዮን ብር
በብልጫና በድጋሚ ያላግባብ ክፍያ የፈጸሙ ተቋማት እነማን ናቸው
?
- የጤና ሚኒስቴር ➔ 231.1 ሚሊዮን ብር
- የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ➔ 23 ሚሊዮን ብር
- የኢትዮጵያ ስፖርት አካዳሚ ➔ ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ
- የቃሊቲ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ➔ 2.4 ሚሊዮን ብር
- ጅማ ዩኒቨርሲቲ ➔ 2.1 ሚሊዮን ብር
የተሟላ የወጪ ማስረጃ ካልቀረበበት 1.1 ቢሊዮን ብር ውስጥ ከፍተኛውን ድርሻ የያዙት ፦
° የሞያሌ ጉምሩክ ➔ 25.4 ሚሊዮን ብር
° የኢትዮጵያ ጂኦሎጂካል ኢንስቲትዩት ➔ 23.4 ሚሊዮን ብር
° የመንግሥት ኮሚኒኬሽን አገልግሎት ➔ 7.5 ሚሊዮን ብር
° የማዕድን ልማት ኢንስቲትዩት ➔ 6.6 ሚሊዮን ብር
° የማዕድን ሚኒስቴር ➔ ከ6 ሚሊዮን ብር በላይ
° የባህር ዳር ጉምሩክ ➔ 4.7 ሚሊዮን ብር
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት ያለበቂ ማስረጃ ክፍያ መፈጸምን ጨምሮ ደንብና መመሪያ ተጥሰው የሚፈጸሙ ክፍያዎች ተጠያቂነትን እንደሚያስከትሉ በመግለጽ፣ ገንዘቡ በአስቸኳይ ተመላሽ እንዲደረግና እንዲህ ያለው መዝረክረክ እንዲታረም በጥብቅ አስጠንቅቋል።
ይህ መረጃ ባለቤትነቱ የሸገር ኤፍ ኤም ሬድዮ ጣቢያ ነው።
ሰኔ 11 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
በ138 የመንግሥት መ/ቤቶችና ቅርንጫፎች ከ16.3 ቢሊዮን ብር በላይ ያልተወራረደ ውዝፍ ሒሳብ መኖሩ ተገለጸ።
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት የ2017 በጀት ዓመት የፋይናንሺያል፣ ሕጋዊነትና ክዋኔ ኦዲት ባለ 65 ገጽ ሪፖርቱን ዛሬ ለፓርላማ አቅርቧል።
በሚኒስትሮች ም/ቤት ደንብ ቁጥር 190/2002 እና በመንግሥት መሥሪያ ቤቶች መመሪያ መሠረት፣ ለውሎ አበል፣ መጓጓዣና ሥራ ማስኬጃ የተሰጡ ቅድሚያ ክፍያዎች ሠራተኛው ሥራውን አጠናቆ ከተመለሰ በኋላ በ7 ቀናት ውስጥ መወራረድ አለባቸው።
ይሁንና በ138 መሥሪያ ቤቶች እንዱሁም በ18 ቅርንጫፎች በወቅቱ ያልተወራረደ በጠቅላላው ከ16.3 ቢሊዮን ብር በላይ ውዝፍ ሂሳብ መኖሩ ተረጋግጧል። ነገር ግን ይህ ውዝፍ ሂሳብ ካለፈው ዓመት ከነበረው 32.9 ቢሊዮን ብር ጋር ሲነጻጸር በ50 በመቶ ቅናሽ አሳይቷል።
የፌዴራል ዋና ኦዲተር መሥሪያ ቤት፥ ውዝፍ ሂሳብ በወቅቱ አለመወራረዱ ለመንግሥት ገንዘብ መባከን ምክንያት ስለሚሆን፣ ሳይሰበሰቡ የተገኙት እንዲወራረዱና ሊሰበሰቡ በማይችሉት ላይ ደግሞ ከመዝገብ እንዲሰረዙ ለየተቋማቱ ማሳሰቡን ጠቅሷል።
የውዝፍ ተሰብሳቢ ሂሳቡ የዕድሜ ቆይታ ምን ይመስላል ?
• ከአንድ ወር እስከ አንድ ዓመት ➔ 4.6 ቢሊዮን ብር
• ከአንድ ዓመት እስከ አምስት ዓመት ➔ 6.6 ቢሊዮን ብር
• ከአምስት ዓመት በላይ እስከ አሥር ዓመት ➔ 4.8 ቢሊዮን ብር
• ከአሥር ዓመት በላይ ➔ 154 ሚሊዮን ብር
• የቆይታ ጊዜው የማይታወቅ ➔ ከ5 ሚሊዮን ብር በላይ
ከፍተኛ ተሰብሳቢ ሒሳብ የተገኘባቸው ተቋማት እነማን ናቸው ?
° የጤና ሚኒስቴር ➔ 3.4 ቢሊዮን ብር
° የዋቸሞ ዩኒቨርሲቲ ➔ 1.3 ቢሊዮን ብር
° የከተማና መሰረተ ልማት ሚኒስቴር ➔ 982 ሚሊዮን ብር
° የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ➔ 958 ሚሊዮን ብር
° የባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ➔ 926 ሚሊዮን ብር
° የትምህርት ሚኒስቴር ➔ 762 ሚሊዮን ብር
° የአደጋ ሥጋት አመራር ኮሚሽን ➔ 648 ሚሊዮን ብር
° የጎንደር ዩኒቨርሲቲ ➔ 593 ሚሊዮን ብር
በ2016 እና ከዚያ በፊት አለአግባብ ከተፈጸሙ ክፍያዎች እንዲመለስ አስተያየት ከተሰጠበት 21.5 ቢሊዮን ብር ውስጥ ተመላሽ የተደረገው 31 በመቶ ብቻ ሲሆን፣ ቀሪው 15 ቢሊዮን ብር (69 በመቶ) አልተመለሰም።
በግኝቱ መሠረት እርምጃ የወሰዱ ተቋማት አፈጻጸም ፦
✅ የኮምቦልቻ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ➔ 99%
✅ የኤርፖርት ጉምሩክ ቅርንጫፍ ➔ 94%
✅ አርባ ምንጭ ዩኒቨርሲቲ ➔ 80%
✅ ምዕራብ አዲስ አበባ ገቢዎች ቅርንጫፍ ➔ 63%
✅ የኮምቦልቻ ገቢዎች ቅርንጫፍ ➔ 42%
✅ የቃሊቲ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ➔ 40%
✅ የሞጆ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ➔ 34%
✅ አዳማ ጉምሩክ ቅርንጫፍ ➔ 32%
በ2016ና ከዚያ በፊት ባልተሟላ ሰነድ ለተፈጸሙ ክፍያዎች ማስረጃ መቅረቡን ለማረጋገጥ በተደረገ ኦዲት፣ በ35 መሥሪያ ቤቶች ማስረጃ ሊቀርብለት ከሚገባው 2.9 ቢሊዮን ብር ውስጥ ማስረጃ የቀረበው ለ51 ሚሊዮን ወይም 1.8% ብቻ ሲሆን፣ ቀሪው 98.2% ወይም ወደ 2.9 ቢሊዮን ብር ገደማ ማስረጃ አልቀረበለትም።
ወራቤ ዩኒቨርሲቲ በግኝቱ መሠረት ሙሉ በሙሉ 100% እርምጃ ወስዷል።
በተቃራኒው ትምህርት ሚኒስቴር ማስረጃ ያቀረበው ለ5.8 ሚሊዮን ብር ወይም 1.3% ክፍያ ብቻ መሆኑ ተገልጿል።
ይህ መረጃ ባለቤትነቱ የሸገር ኤፍ ኤም ነው።
ሰኔ 11 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
ዓለም አቀፍ የነዳጅ ዋጋ አሽቆለቆለ።
በአሜሪካና ኢራን መካከል ለወራት የዘለቀውን ጦርነት ለማስቆምና የሆርሙዝ ሰርጥን ለመክፈት ያለመ ጊዜያዊ ስምምነት መፈረሙን ተከትሎ የዓለም የነዳጅ ዋጋ ቀንሷል።
እንደ ሮይተርስ ዘገባ የተፈረመው ስምምነት በአቅርቦት ላይ የነበረውን ስጋት በማቃለሉ የብሬንት ድፍድፍ ነዳጅ ዋጋ በበርሜል 78.66 ዶላር ሆኗል።
በተመሳሳይ ፣ የዌስት ቴክሳስ ኢንተርሚዲየት (WTI) ዋጋም ወርዶ በበርሜል $75.81 ሆኖ ተመዝግቧል።
ሰኔ 10 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
" የመጨረሻው ስምምነት ላይ መድረስ ካልተቻለ በቦምብ እንደበድባቸዋለን " - ትራምፕ
የአሜሪካ እና ኢራን ፕሬዚዳንቶች ጦርነቱን ከአሁን ጀምሮ የሚያስቆመውን የመጀመርያ ስምምነት ፈረሙ።
ስምምነቱ የሆርሙዝ ሰርጥ እንደገና መክፈት፣ የ300 ቢሊዮን ዶላር ኢራን " መልሶ የመገንባት " ዕቅድ፣ አሜሪካ ኢራን ላይ የጣለችውን " ሁሉንም ዓይነት ማዕቀቦች " የሚያስቆም ነው።
ነገር ግን የኢራን ጦርነት እንዲቀሰቀስ ዋነኛ ምክንያት የሆነው የኒውክሌር ፕርግራም ሊራዘም በሚችል 60 ቀናት ውስጥ ድርድር የሚካሄድበት ጉዳይ ሆኗል።
የአሜሪካውን ፕሬዚዳንት ፈረንሳይ በተካሄደው የቡድን ሰባት ጉባዔ ላይ በተሳተፉበት ወቅት ፊርማቸውን ሲያኖሩ " ምጣኔ ሃብታዊ ቀውስን " የሚያስቀር ዕቅድ ነው ሲሉ ተናግረዋል።
ነገር ግን ከኢራን ጋር የመጨረሻው ስምምነት ላይ መድረስ ካልተቻለ " በቦምብ እንደበድባቸዋለን " ሲሉ ዝተዋል።
የኢራኑ ፕሬዚዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያን ረቡዕ ዕለት ስምምነቱ ላይ ፊርማቸውን ማኖራቸውን ቴህራን አረጋግጣለች።
የኢራን ቁልፍ ተደራዳሪ የሆኑት የምክር ቤቱ አፈ ጉባዔ ሞሃመድ ባግሃር ጋሊባፍ ለአገር ውስጥ መገናኛ ብዙኃን አሜሪካ ላይ ያላቸው ጥርጣሬ እንዳለ መሆኑን አስታውቀው " ጣቶቻችን አሁንም ቃታ ለመሳብ ዝግጁ ናቸው " ብለዋል።
" ጠላት የተጠየቅነውን ቋንቋ ካልተረዳ ወደ ኃይል ቋንቋ ተመልሰን እንገባለን " ሲሉ ለፋርስ ኒውስ ተናግረዋል።
መረጃው የቢቢሲ ነው።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሰኔ 11 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
"ሴትነት እና እናትነት ብቻውን ፕሮፌሰርነት ነው " - ፕሮፌሰር አቻምየለሽ ገብረፃድቅ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ
የሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ ሰኔ 8/2018 ዓ.ም. ባካሄደው የዩኒቨርሲቲው ሴኔት ስብሰባ፣ ለ9 ምሁራን የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ ሰጥቷል። በዚህም ዶክተር አቻምየለሽ ገብረፃድቅ ተክሌ በዩኒቨርሲቲው ታሪክ የመጀመሪያና ብቸኛ ሴት ሙሉ ፕሮፌሰር በመሆን ታሪክ ሰርተዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ ይህን ደማቅ ስኬት አስመልክቶ በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የህክምና እና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ መምህርና ተመራማሪ ከሆኑት ከፕሮፌሰሯ ጋር ያደረገውን ቆይታና የባለሙያዋን ማህደር እንደሚከተለው አደራጅቶታል።
የትምህርት ጉዟቸው ምን ይመስላል ?
ፕሮፌሰር አቻምየለሽ ገብረፃድቅ ለአሁኑ የላቀ የሙሉ ፕሮፌሰርነት ማዕረግ ለመብቃት ተስፋ ሳይቆርጡ የተጓዙበት የትምህርት መስመር እጅግ አርአያነት ያለው ነው።
👉 እ.ኤ.አ በ1996 በጎንደር ህክምና ሳይንስ ኮሌጅ በኮምፕሬሄንሲቭ ነርሲንግ ዲፕሎማ
👉 እ.ኤ.አ በ2004 ከደቡብ ዩኒቨርሲቲ በህብረተሰብ ጤና (Public Health) የመጀመሪያ ዲግሪ
👉 እ.ኤ.አ በ2010 ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የማስተርስ ዲግሪ
👉 እ.ኤ.አ በ2015 ከሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ እና ከአዲስ ኮንቲኔንታል የህብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት በጋራ በተመራ የትምህርት ፕሮግራም የዶክትሬት ዲግሪያቸውን በስኬት አግኝተዋል።
በትምህርት እና ምርምር ጉዟቸው ውስጥ ሴት በመሆናቸውና ቤተሰብ በመምራታቸው የገጠሟቸውን ተደራራቢ ፈተናዎች ያነሱት ፕሮፌሰር አቻምየለሽ " ሴትነትና እናትነት ብቻውን ፕሮፌሰርነት ነው " በማለት ጥንካሬንና ትዕግስትን የሚጠይቁትን እነዚህን ድርብ ማህበራዊ ኃላፊነቶች በብቃት መወጣት ራሱ ትልቅ ማዕረግ መሆኑን ገልጸዋል።
ለዩኒቨርሲቲው ሆነ ለህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጁ የመጀመሪያዋ ሴት ሙሉ ፕሮፌሰር መሆናቸውን የጠቀሱት ምሁሯ፤ ይህ ስኬት በተቋም ደረጃ ብቻ ሳይሆን በአገራችንም ካሉ እጅግ ጥቂት ሴት ፕሮፌሰሮች መካከል አንዷ ለመሆን መብቃታቸውን በኩራት ተናግረዋል።
ፕሮፌሰር በግላቸው ካስመዘገቡት ስኬት ባሻገር፣ ሌሎች ሴቶች በምርምርና በአካዳሚክ ዘርፍ እንዲበረቱና እርስ በእርስ እንዲደጋገፉ የጀመሩትን አበረታች ስራ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ አጋርተዋል።
ሌሎች ሴቶችን ለማገዝ በነበራቸው ቁርጠኝነት መሰረት፣ ቀደም ሲል ከጓደኞቻቸው ጋር በመሆን በ10 ሴቶች ብቻ የጀመሩት " የኢትዮጵያ ሴት ተመራማሪዎች ማህበር " በአሁኑ ወቅት በአስደናቂ ሁኔታ አድጎ የአባላት ቁጥሩ ከ600 በላይ መድረሱን ገልጸዋል።
ከቲክቫህ ኢትዮጵያ ማህደር የተገኘው መረጃ እንደሚያመላክተው፣ ፕሮፌሰር አቻምየለሽ በህብረተሰብ ጤና፣ በክሊኒካዊ ምግብ እና በአካዳሚክ መሪነት ላይ ከሁለት አስርት ዓመታት በላይ የላቀ አገራዊና ዓለም አቀፋዊ አገልግሎት ያበረከቱ እውቅ ባለሙያ ናቸው።
በተለይ በእናቶችና ህጻናት ጤና፣ በስነ-ምግብ፣ በካንሰር ኤፒዲሚዮሎጂ እና የጤና ስርዓትን በማጠናከር ረገድ በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚጠቀሱ ተመራማሪ ናቸው።
ፕሮፌሰር አቻምየለሽ ገብረፃድቅ ከጤና ሚኒስቴር ጋር በመሆን ብሄራዊ የስነ-ምግብ መመሪያዎችን በማዘጋጀት የሀገሪቱን የጤና ፖሊሲ በቀጥታ ቀርጸዋል፤ ለዚህም የ“ከፍተኛ ተመራማሪ” ሽልማት ተበርክቶላቸዋል።
እስካሁን ከ50 በላይ የሚሆኑ የምርምር ፅሁፎች ያሳተሙት ምሁሯ በአሁኑ ወቅት፦
• በሐዋሳ ዩኒቨርሲቲ የጥራት ማረጋገጫ ዳይሬክተር፣
• በኢትዮጵያ የህብረተሰብ ጤና ማህበር (EPHA) የእናቶችና አራስ ህጻናት ጤና ቡድን ተባባሪ ሊቀ-መንበር፣
• የሴት አካዳሚሻኖች ኔትወርክ ሰብሳቢ ሆነው በማገልገል ላይ ናቸው።
በተጨማሪም የፒኤችዲና ኤምፒኤች ተማሪዎችን እያማከሩ ለዩኒሴፍ፣ ለግሎባል ፈንድ እና ለዓለም ጤና ድርጅት (WHO) የባለሙያ ድጋፍ በመስጠት ላይ ይገኛሉ።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሀዋሳ
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
የኢራንን ጦርነት የሚያስቆመው ስምምነት መቼ ይፈረማል ?
የአሜሪካ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ የኢራንን ጦርነት የሚያስቆመው ስምምነት እንደተፈረመና ዝርዝሩም ይፋ እንደሚደረግ አስታወቁ።
የስምምነቱ ዝርዝር ይፋ ይደረጋል ተብሎ እየተጠበቀ ሲሆን፤ ይፋዊ ፊርማ የማኖር ሥነ ሥርዓቱ የፊታችን አርብ በጄኔቫ የሚከናወን ይሆናል።
የእስራኤል ጠ/ሚ ቤንያሚን ኔታንያሁ በበኩላቸው “ትግሉ አላከተመም” ብለዋል። አገራቸው አሁንም በተጠንቀቅ እንደቆመች እና በደቡብ ሊባኖስ “ከውጊያ ነጻ የሆነ ቀጣና” እንደሚኖራት ገልጸዋል።
የኢራን ፕሬዝዳንት ማሱድ ፔዤሽኪያን ስምምነቱ በአግባቡ ከተተገበረ ለኢራን “የሚያኮራ ሰነድ” ነው ማለታቸውን የአገሪቱ መገናኛ ብዙኃን ዘግበዋል።
አንድ የአሜሪካ ከፍተኛ ባለሥልጣን እንደተናገሩት የመግባቢያ ስምምነቱ መፈረሙን ተከትሎ የሆርሙዝ ወሽመጥ “በአፋጣኝ” ይከፈታል ተብሎ ይጠበቃል።
በስምምነቱ መሠረት በሊባኖስ “ወታደራዊ ዘመቻ” መቆም እንዳለበት ተገልጿል። የሊባኖስ ባለሥልጣናት ተፈናቃዮች የአካባቢው ደኅንነት ሳይረጋገጥ እንዳይመለሱ ቢያሳስቡም ብዙዎች ወደ ቤታቸው እየተመለሱ መሆኑን ቢቢሲ ዘግቧል።
ሰኔ 9 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
" በቢሮ ውስጥ ባለ የተመቻቸ ወንበር ተቀምጠህ ወጣቶችን ልቀሟቸው ማለት ምን ለማምጣት ነው ? " - ወ/ሮ ኣኸዛ ሕሉፍ ከመታሰራቸው በፊት የተናገሩት
በትግራይ ክልል ደቡባዊ ምስራቅ ዞን እንደርታ ወረዳ የሚኖሩት የ76 ዓመቷ አዛውንት ወ/ሮ ኣኸዛ ሕሉፍ፣ በክልሉ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ በጽኑ የገመገሙበትን ቃለ-መጠይቅ መስጠታቸውን ተከትሎ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ መታሰራቸው ከፍተኛ ቁጣና ተቃውሞ ቀሰቀሰ።
ጉዳዩን የሚከታተሉ አካላት ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ቃል ፣ ነባር ታጋይና የሰማዕት እናት የሆኑት ወ/ሮ ኣኸዛ የታሰሩት ሰኔ 8 ቀን 2018 ዓ.ም. ሲሆን፣ በአሁኑ ወቅት በመቐለ ከተማ በሚገኝ የፖሊስ ጣቢያ ውስጥ ይገኛሉ።
የእናቲቱ መታሰር መነሻ ' Landa Report ' ከተሰኘ የዲጂታል ሚዲያ ጋር ያደረጉት ቆይታ እንደሆነ ታውቋል።
ወ/ሮ ኣኸዛ በቃለ-መጠይቃቸው በክልሉ ያለውን አስገዳጅ ውትድርና እና የወጣቶች እፍሳ አጥብቀው አውግዘዋል።
በተለይ በስልጣን ላይ ያለውን አካል " በጉልበታችን ያሻንን እናደርጋለን ማለት ምን ማለት ነው ? ዛሬስ ማንን ነው በጉልበት የምታንበረክከው ? በቢሮ ውስጥ ባለ የተመቻቸ ወንበር ተቀምጠህ ወጣቶችን ልቀሟቸው ማለት ምን ለማምጣት ነው ? ለመሆኑ ይህንን ትዕዛዝ የሚያዘው ሰው ወልዶ ስሞ ያቀፈ ነው ? " በማለት የሰነዘሩት ትችትና ወቀሳ በማህበራዊ ትስስር ገጾች ላይ በሰፊው ተሰራጭቶ ነበር።
እንደ ምንጮች መረጃ፤ አዛውንቷ እናት ከመኖሪያ መንደራቸው ፈለገማያት ተወስደው ከታሰሩ በኋላ ቤተሰቦቻቸው እንዳይጠይቋቸውና ስንቅ እንዳያገቡ ተከልክለዋል። ይህም ድርጊት በዕድሜያቸውና በጤና ሁኔታቸው ላይ ስጋት ፈጥሯል።
የእናትየው መታሰር ይፋ መሆኑን ተከትሎ ከወጣት እስከ አንጋፋ የፖለቲካ አመራሮች፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች እና በርካታ የማህበራዊ ሚዲያ ተጠቃሚዎች ድርጊቱን በጽኑ እየኮነኑት ይገኛሉ።
ተቃዋሚዎቹ ድርጊቱን " በትግራይ ያለውን የፖለቲካ አፈና ለመሸፈንና የህዝብን ድምጽ ዝም ለማሰኘት ያለመ የጭካኔ ተግባር " ሲሉ የገለጹት ሲሆን፣ ለአገዛዙ ታማኝ የነበሩና ልጃቸውን በጦርነት ያጡ እናትን ማሰር የሞራል ዝቅጠት ነው ብለዋል።
በአሁኑ ሰዓት በማህበራዊ ድረ-ገጾች ላይ " ፍትህ ለወይዘሮ ኣኸዛ " በሚሉ መፈክሮች አስቸኳይ መፈታታቸውን የሚጠይቁ የተቃውሞ ድምጾች በስፋት እየተስተጋቡ ይገኛሉ።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሰኔ 9 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
" አሁንም እንደታሰረች ናት። እስከ ዛሬዋ እለት ድረስ ፍርድ ቤት አልቀረበችም " - የታሳሪ ቤተሰብ
ከዚህ ቀደም በዋልታና ፋና ሚዲያዎች የሰራችው ጋዜጠኛ ሣልሳዊት ባይነሳኝ የጸጥታ አካላት ልብስ በለበሱ አካላት ከቤቷ ተወስዳ ከታሰረች ሳምንት ቢሆናትም ፍርድ ቤት አለመቅረቧን ቤተሰብና የታሳሪዋ የቅርብ ሰው ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ተናገሩ።
የታሳሪዋ እህት ሃይማኖት ባይነሳኝ ዛሬ በሰጠችን ቃል፣ ግለሰቧ ከታሰረች ሳምንት እንዳለፋት አስረድታ፣ " አሁንም እንደታሰረች ናት። እስከ ዛሬዋ እለት ድረስ ፍርድ ቤት አልቀረበችም" ብላለች። ፖሊስን ሲጠይቁ የሚሰጣቸው ምላሽ "ጠብቁ" የሚል ብቻ መሆኑን ገልጻለች።
የእስሩን ሁነት ስታስረዳም፣ "ከቤቷ ነው የወሰዷት። ከቤት ሠራተኛዋ ጋር ነው የወሰዷት። የፖሊስ ልብስ የለበሱ ሰዎች ናቸው ይዘዋት የሄዱት። የታሰረችበት ቦታ ፒያሳ አካባቢ ሦስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ወይም ማዕከላዊ የሚሉት ጋር ነው " ብላለች። ሠራተኛዋ ግን ከእስር መለቀቋ ተገልጿል።
ለእስር የሚያበቃት ወይም ቀድሞ የደረሳት ማስጠንቀቂያ፣ ሲወስዷት የነገሯት ጉዳይ እንዳለ ስንጠይቃት፣ "ምንም የለም። የአርሲው የግድያ ጉዳይ ይመስላል። እሱንም እርግጠኞች አይደለንም" ስትል ግምቷን ገልጻ፣ "እሷም 'ምንም ነገር አልነገሩኝም' ነው ያለችው" የሚል ምላሽ ሰጥታለች።
ታሳሪዋ፣ ከዚህ ቀደም በዋልታና ፋና ሚዲያዎች መስራቷን ተናግራ፣ " ከጥቂት ወራቶች በኋላ ግን እሱን ለቃው በግሏ መንቀሳቀስ ጀምራለች። በራሷ ዩትዩብ፣ ቲክቶክና ፌስቡክ ነው እየሰራች የነበረችው " በማለት አስረድታለች።
በተያያዘ፣ ከቤቷ የወሰዷት አካላት መጥሪያ ደብዳቤ እንዳልያዙ ገልጻ፣ "ሰኞ ሰኔ 1 ቀን 2018 ዓ/ም ከቀኑ 7 ሰዓት አካባቢ ከወሰዷት ቀኋላ ቤቱን በፖሊስ እያስጠበቁ ቆይተው ዘጠኝ ሰዓት አካባቢ ተመልሰው ማዘዣ ይዘው መጥተው ቤት ብርበራ አድርገዋል" ነው ያለችው።
የታሳሪዋ ቤተሰብ ባስተላለፈችው መልዕክት፣ "የልጅ እናት ናት። እናት፣ ልጇም እኛ ሙሉ ቤተሰቦቿ ተጨንቀን ነው ያለነው። የቤተሰብም አስተዳዳሪ ናት። በአግባቡና በሥርዓቱ ፍትህ ይሰጠን። ፍትህ አግኝታ ትፈታልን" ስትል ጠይቃለች። ሌላኛው መረጃ አቀባይ ግለሰቧ መታሰሯን ገልጸዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ፣ የግለሰቧን መታሰር እና ፍርድ ቤት አለመቅረብ በተመለከተ ምን ምላሽ እንዳለው ማብራሪያ ለመጠየቅ ወደ ፌዴራል ፖሊስ ያደረገው ሙከራ ስልክ ባለመነሳቱ ለጊዜው አልተሳካም።
በተጨማሪ ለጉዳዩ ማብራሪያ የጠየቅናቸው የአዲስ አበባ ፖሊስ ጠቅላይ መምሪያ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ ኮማንደር ቶማስ እሸቴ፣ "መረጃውን እናጣራ" ብለው፣ "ትክክለኛ ነው ወይ ጋዜጠኛ ናት? የሚለውን ነገር ማረጋገጥ ተገቢነት ያለው ይመስለኛል" ብለዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
አዲስ አበባ
ሰኔ 9 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+2
ሰሜ ባላገሩ 🌟
አንጋፋው የባህል ሙዚቃ ተጫዋች ድምጻዊ ሰማኸኝ በለው (ሰሜ ባላገሩ) ባደረበት ሕመም በህክምና ሲረዳ ቢቆይም ህይወቱ ሊተርፍ አልቻለም።
ከባህል ድምጻዊነቱ በተጨማሪ የዜማና ግጥም ደራሲ የሆነው የሰማኸኝ ስርዓተ ቀብር ነገ ይፈጸማል።
ሰሜ ከመደበኛ በላይ የሆነ ውፍረቱ ይህ ነው የተባለ የጤና ችግር እንዳልፈጠረበት (ስኳር፣ ግፊት ... የመሳሰሉ) ከአንድ አመት በፊት ተናግሮ ነበር። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ውፍረቱን ለመቀነስ የተለያዩ የህክምና ዘዴዎችን ሲከታተል የቆየ ሲሆን ጥሩ ለውጥ እያመጣ መሆኑን ከሰሞኑን በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ እራሱ ሲገልጽ ነበር።
ሰኞ ሰኔ 8 ጥዋት ላይ በርካቶችን ባስደነገጠና ባልተጠበቀ ሁኔታ በህመም ምክንያት ከዚህ ዓለም በሞት መለየቱ ተሰምቷል።
የመጨረሻ ሰዓታቱን በተመለከተ ልጆቹን ዋቢ አድርጎ የገለጸው አቻሬ ሚዲያ ፤ ሰኞ ሰኔ 8 ጥዋት የድካም ስሜት ተሰምቶት በልጆቹ አማካኝነት ወደ ሆስፒታል እየተወሰደ ነበር። ወደ ሆስፒታል በሚወሰድበት ወቅት ግን ወንበር ላይ ዘንበል ያለ ሲሆን ሆስፒታል ደርሶ ከገባ በኋላ ብዙም ሳይቆይ ህይወቱ አልፏል።
በአማራ መዲና፣ ባህር ዳር ተወልዶ ያደገው ድምጻዊ ሰሜ፣ ገና በ14 ዓመት ታዳጊነቱ በባህር ዳር ሕጻናት ክፍል ፣ በመቀጠል በአዮማ እና በግሽ አባይ ኪነጥበብ ቡድኖች ውስጥ በመሳተፍ የጥበብ ጅማሮውን አድርጓል፤ በዚህም ረጅም ዓመታትን ለዘለቀው ስኬታማ የጥበብ ጉዞው ጠንካራ መሠረት ጥሏል።
ሰሜ ባላገሩ በረጅም ዓመታት የጥበብ ስራዎቹ በተለይ የሀገር ባህል የሙዚቃ ዘርፍን ወጉን እና ስርዓቱን ጠብቆ በከፍተኛ ደረጃ ያስተዋወቀ ሲሆን በተለያዩ ክለቦችም ዘመናዊ ሙዚቃዎችን በመጫወት ልዩ ብቃቱን ያሳየና በርካታ የባህል ሥራዎችን ለአድማጭ ያበረከተ የጥበብ ባለውለታ ነው።
ከተወዳጅ የባህል ስራዎቹ መካከል ፦
- ባላገር
- ደቦት እንስራ
- ዘገኛ
- አለሽ ነገር
- ዝናቡ
- አለምን እንደምነሽ .... የሚሉት ይጠቀሳሉ።
ከተሰጥዎው ባሻገር በተገኘበት ቦታ ሁሉ ሳቅን የሚፈጥር ፣ እጅግ ተጫዋች ፣ ቀልድ አዋቂ እንዲሁም በመልካም ስብዕናው ይታወቅ የነበረው ሰማኸኝ፤ በአንድ ወቅት " ሦስት ነገር እወዳለሁ፤ ሀገሬን፣ ትዳሬን እና ሥራዬን " በማለት መርሁን ገልጾ ነበር።
ከ35 ዓመታት በላይ በዘለቀው የትዳር ህይወቱ የአራት ልጆች አባት የነበረው ድምጻዊ ሰማኸኝ በለው (ሰሜ ባላገሩ) በሠራቸው ውብ የሙዚቃ ሥራዎቹ ሁልጊዜም ይታወሳል።
የሰሜ ባላገሩ ስርዓተ ቀብር ማክሰኞ ሰኔ 9 ቀን 2018 በቡልቡላ መድኃኔዓለም ቤተክርስቲያን ይፈጸማል።
ነፍስ ይማር !
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
የደቡብ አፍሪካ መጤ ጠል ጥቃት 🇿🇦
የዓለም ጤና ድርጅት ዋና ዳይሬክተር ዶክተር ቴድሮስ አድሃኖም በደቡብ አፍሪካ "ሌላ ዙር መጤ ጠል ጥቃት" እያገረሸ መሆኑንና ድርጊቱ "አገሪቱ ለነጻነት ያደረገችውን ትግል የሚክድ አሳዛኝ ሁኔታ" መሆኑን ገለጹ።
በቅርቡ የኢትዮጵያዊ እና ሞዛምቢካዊ ዜጎች ሕይወት በአጭሩ መቅጠፉን በምሳሌነት በማንሳትም አውግዘዋል።
ሆኖም፣ የደቡብ አፍሪካ መንግሥት ዶክተር ቴድሮስ በሰጡት አስተያየት አለመደሰቱን ገልጾ፣ ለዜጎቹ ሞት ማዘኑን ነገር ግን ምክንያቱ መጤ ጠልነት ሳይሆን ከተደራጀ ወንጀልና በምርመራ ላይ ካሉ ጉዳዮች ጋር የተያያዘ ነው በማለት አስተባብሏል።
በአገሪቱ ውስጥ ስደተኞችን የሚቃወሙ ሰልፎችና ጥቃቶች መከሰታቸው ቢዘገብም፣ መንግሥት ዜጎች ሕግን በእጃቸው በማስገባት እርምጃ እንዳይወስዱ እያስጠነቀቀ ይገኛል።
ስጋት የገባቸው እንደ ጋና እና ናይጄሪያ ያሉ አገራት ግን ዜጎቻቸውን ማውጣት ጀምረዋል።
መረጃው የቢቢሲ ነው።
ሰኔ 8 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
" መኪናው የቆየ ነው። ካቻማሌ የሚባለው መኪና ነው። በምልከታ አሮጌ እንደሆነ ያሳያል " - የኮምቦልቻ ከተማ ፖሊስ
ከደሴ ከተማ ተነስቶ ወደ አዲስ አበባ በመጓዝ ላይ እያለ "ሐረጎ" በተሰኘው ጠመዝማዛ መንገድ ላይ ባጋጠመው የመገልበጥ አደጋ የ31 ሰዎች ህይወት እንዲቀጠፍ ምክንያት የሆነው ተሽከርካሪ "አሮጌ" መሆኑን ቦታው ላይ ተገኝቶ መመልከቱን ፖሊስ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ ገለጸ።
ተሽከርካሪው "የማርጀት" ሁኔታ እንደሚታይበት ከቦታው የወጡ መረጃዎች ጭምር የሚያሳዩ ሲሆን፣ በአካባቢው ያለፉ ተጓዦች በበኩላቸው ይህንኑ ገልጸዋል። "መኪናው ያረጀ ነው፤ እንዲህ ያለ መኪና ለምን ጉዞ ይገባል?" በሚል ሲጠይቁ ተስተውለዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያም፣ ተሽከርካሪው "ያረጀ ነው" ተብሏል፤ ፖሊስ ይህን ጉዳይ ተመልክቶት ነበር? ሲል የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያን ጠይቋል።
የአደጋውን ሁኔታ ለማየት በቦታው ተገኝተው የነበሩት የመምሪያው ህዝብ ግንኙነት ክፍል ኃላፊ ኢንስፔክተር አለባቸው ደምሰው፣ የአደጋው መንስኤ ገና በትክክል እንዳልታወቀና ገና እየተጣራ መሆኑን ገልጸው፣ ተሽከርካሪው "አሮጌ" መሆኑን ግን መመልከታቸውን ተናግረዋል።
ኃላፊው "መኪናው የቆየ መኪና ነው። ካቻማሌ የሚባለው መኪና ነው። በምልከታ አሮጌ እንደሆነ ያሳያል። ተገኝቼ ያየሁት እሱን ነው " ብለዋል። " ከታች ድቅቅ ያለ ነገር አለው። በጣም ከፍተኛ ጉዳት ነው የደረሰበት " ሲሉም ተናግረዋል።
በሌላ በኩል፣ በተለምዶ "ሐረጎ" በመባል በሚጠራው አካባቢ የሚገኘው ይሄው የመንገድ ክፍል "ኤስ" ምልክት ያለው ጠመዝማዛና ገደላማ የመንገድ ክፍል ሲሆን፣ ከዚህ ቀደምም ተደጋጋሚ አደጋ ደርሶበት የሰዎች ህይወት ተቀጥፏል፤ የንብረትም ወድመትም አስከትሏል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ፣ መንገዱ ተደጋጋሚ አደጋ የሚደርስበት ነው፤ ከዚህ አኳያ የተለየ የሚያስፈልገው ትኩረት እንዳለ የጠየቃቸው ኢንስፔክተር አለባቸው፣ "ሐረጎ መንገድ የታወቀ ነው። ጥንቃቄ የሚያሻው መንገድ ነው። ሁሉም አሽከርካሪ በልዩ ጥንቃቄና ትኩረት ማሽከርከር ይኖርባቸዋል" ብለዋል።
መንገዱ ልዩ ትኩረት የሚሻው "ጠመዝማዛ መንገድ የሚበዛበት ስለሆነ" መሆኑን አስረድተው፣ በተያያዘ፣ "አሽከርካሪዎች ከማሽከርከራቸው በፊት የተሽከርካሪውን ቲክኒካል ጉዳይ ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል፤ አንደኛው የአደጋ መንስኤ እንደዚህ አይነት ነገር ነው" ሲሉ አስገንዝበዋል።
"ይሄ አደጋ የደረሰው ሹፌሩን ፍሬን እምቢ ብሎት ይሁን አልታወቀም" ያሉት ኃላፊው፣ "ከርቩ ላይ መመለስ ሲገባው ከርቩን፣ የመመለሻ ተብሎ የተሰራውን መከላከያ ሁሉ ንዶት ነው ገደል የገባው" ሲሉ በቦታው ሂደው የተመለከቱትን ገልጸዋል።
ተሽከርካሪው በትክክል ስንት ሰዎች አሳፍሮ እንደነበር ስንጠይቃቸው፣ "31 ሰዎች አንዲት ህፃንን ጨምሮ ሞተዋል ከነሹፌሩ። ወደ 30 ሰዎች ቀላልና ከባድ ጉደት ደርሶባቸዋል። የተሳፋሪዎቹን ብዛት በትክክል ማወቅ አልተቻለም። ሌላውን መረጃ በሌላ ጊዜ እናሳውቃለን" ብለዋል።
ተሽከርካሪው የተገለበጠበት ቦታ "170 ሜትር ነው ለክተነዋል" ያሉት ኢንስፔክተር አለባቸው፣ "ኤስ መንገዱ/መታጠፊያው ላይ ገደል ነው የገባው። ከወደቀበት እስከ የታችኛው ዞሮ ከሚመጣው መንገድ ድረስ ሲለካ 170 ሜትር ይደርሳል" ብለዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሰኔ 8 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+2
በቢሾፍቱ እየተገነባ ላለው አዲሱ ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ ግንባታ ሂደት በየቀኑ ከ 6 መቶ 50ሺ ሊትር በላይ ነዳጅ እየቀረበ መሆኑን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ (ዶ/ር) ገለጹ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ (ዶ/ር) በቢሾፍቱ እየተገነባ ያለውን አዲሱን ዓለም አቀፍ የአውሮፕላን ማረፊያ የግንባታ ሂደት ጎብኝተዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በጉብኝታቸው ወቅት እንደገለጹት፣ ይህ ፕሮጀክት በኢትዮጵያ ታሪክ ትልቁ ብቻ ሳይሆን፣ በሳይዙ፣ በሰው ኃይሉ እና በየሚንቀሳቀሰው ሃብት በአፍሪካ ደረጃም ቢሆን " ትልቁ ነጠላ ፕሮጀክት " (Single Project) ነው ብለዋል።
ፕሮጀክቱ የሀገሪቱን የልማት ጉዞ አዲስ ምዕራፍ ላይ የሚያሸጋግር እና ኢትዮጵያውያን ትልልቅ ነገሮችን ማለምና ማሳካት እንደሚችሉ ለዓለም የሚያሳዩበት መሆኑን ገልጸዋል።
በግንባታው ቦታ ላይ የሚታየውን ሰፊ እንቅስቃሴ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዝርዝር አብራርተዋል።
በማብራሪያቸውም (ግንባታው በሚካሄድበት) በ30 ኪሎሜትር ራዲየስ ውስጥ:-
• ከ8ሺህ በላይ ሰራተኞች እና ከ3ሺ 8መቶ እስከ 4ሺህ የሚጠጋ ማሽነሪዎች እንቅስቃሴ መኖሩን።
• በየቀኑ ከ 6 መቶ 50ሺ ሊትር በላይ ነዳጅ ለማሽኖቹ እንቅስቃሴ መቅረብ እንዳለበት (በ10 ቀን ውስጥ ከ6 ነጥብ 5 እስከ 7 ሚሊየን ሊትር ነዳጅ) ጠቁመዋል።
የፕሮጀክቱን የአመራር ሂደት በሚመለከት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲያብራሩ"ነዳጁን ማቅረብ፣ ማሽነሪ ማቅረብ፣ መኪናዎች ማቅረብ፣ ይሄንን መኪና መተላለፍ ማኔጅ ማድረግ ደግሞ ሲስተም ይፈልጋል ከሲቹዌሽን ሩም ቨርቹዋሊ በድሮንስ እያንዳንዱ መኪና እንቅስቃሴ ኮንትሮል ይደረጋል" ብለዋል።
የድሮኖችን የስራ ክንዋኔ በተመለከተም"እያንዳንዱ ድሮን የሚንቀሳቀሱ መኪናዎች ብቻ ሳይሆኑ አንደኛው መኪና ከየት ተነስቶ የት እንደሚቆም ስንት አፈር እንዲሞላ በቀን ምን ያህል እንደተሞላ ሁሉ ኢሜጅ እየወሰዱ ያን እያስተሳሰሩ ሪፖርት ያቀርባሉ" ነው ያሉት።
"በሀገር ደረጃ ኤርፖርቱን መስራት ብቻ ሳይሆን 4ሺህ መኪና ማኔጅ ማድረግ መቻል በራሱ በቀን ምን ያክል የአፈር ብዛት ከየት ቦታ ተነስቶ የት ጋር እንደሚያርፍ ማወቅ በራሱ ኦፕሬቲንግ ሲስተሙን በደንብ መረዳት ለአመራሮች በጣም አስፈላጊ ነገር ነው"ሲሉም አብራርተዋል።
በኢትዮጵያ ቀደም ሲል ለነበሩ የፕሮጀክት መዘግየቶች እና ለተጨማሪ ወጪ መዳረግ ምክንያት የነበረውን የአመራር ችግር ለመቅረፍ በዚህ ፕሮጀክት ላይ ልዩ ትኩረት መደረጉን ገልጸዋል።
ፕሮጀክቱ አይሳካም የሚሉ ወገኖች መኖራቸውን የጠቀሱት ዐቢይ አህመድ፣ ለነዚህ አካላት በሰጡት ምላሽ "ብዙዎች አትችሉም፣ ገንዘቡም አይገኝም፣ ስራውን መምራት አይሆንላችሁም፣ ይሄን የሚያክል ግዙፍ ነገር ለምን ታስባላችሁ የሚል ምልከታ ያለው እሳቤ ሲያራግቡ ይሰማል። እውነታቸውን ነው ከእነሱ አንጻር አይገባንም። እኛ ደግሞ እንችላለን፣ ይገባናል፣ የሚመጥነን ትልቅ ነገር ነው እያልን ነው ማን እንደሚያሸንፍ ጊዜው ሲደርስ እናያለን"ብለዋል።
ፕሮጀክቱ በከፍተኛ ክትትል የሚመራ በመሆኑ በተቀመጠለት ጊዜ እንደሚጠናቀቅም አረጋግጠዋል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አክለውም "ይሄ ሲዝን የኛ ጊዜ ነው። ይሄ ጊዜ የኢትዮጵያ ጊዜ ነው። ይሄ ጊዜ የአፍሪካ ጊዜ ነው። ይሄ ጊዜ የኛ ጊዜ መሆኑን መናገር ብቻ ሳይሆን ያንን ለመተርጎም የሚያስችል ስራ መስራት ያስፈልጋል" በማለት ሃሳባቸውን አጠናክረዋል።
ለፕሮጀክቱ ግንባታ ሲባል ይዞታቸውን ለለቀቁ የአካባቢው አርሶ አደሮችም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ምስጋና አቅርበዋል።
መንግሥት አርሶ አደሮችን ለልማት ሲያነሳ እንደ ከዚህ ቀደሙ ሜዳ ላይ እንደማይጥላቸው በመግለጽ፣ ለእነዚህ ወገኖች ቤቶች እና የቢዝነስ ተቋማት መገንባታቸውን ገልጸዋል።
"ማንም አርሶ አደር በዚህ ፕሮጀክት ምክንያት የሚጎዳ አይኖርም ይሄ ፕሮጀክት ለዚህ አካባቢ አርሶ አደሮች ትልቅ በረከት ነው" ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፣ ፕሮጀክቱ ለኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን ለምስራቅ አፍሪካና ለመላው አፍሪካ "እንደሚቻል ማሳያ" እና "የሀብት ምንጭ" እንደሚሆን ተናግረዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
አዲስ አበባ
ሰኔ 8 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+3
#Ethiopia 🇪🇹 #GreenLegacy
ጠ/ሚ ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) የዘንድሮውን የአረንጓዴ ዐሻራ ችግኝ ተከላ መርሃ-ግብር ዛሬ በይፋ ማስጀመራቸውን አስታወቁ።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባስተላለፉት መልዕክት፣ በያዝነው የክረምት ወቅት 8 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ትልቅ ግብ መቀመጡን ገልጸዋል።
ይህ በእቅድ የተያዘው መርሃግብር አገሪቱ በአረንጓዴ ዐሻራ ንቅናቄ በአጠቃላይ 65 ቢሊዮን ችግኞችን ለመትከል ያስቀመጠችውን አገራዊ ራዕይ ለማሳካት የሚደረገውን ጉዞ በጽናት የሚያስቀጥል መሆኑን ጠቁመዋል።
ጠ/ሚ ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) መላው የኅብረተሰብ ክፍል የተጀመረውን አገራዊ ንቅናቄ በመቀላቀል ለመጪው ትውልድ የሚተርፍ የአረንጓዴ ዐሻራቸውን እንዲያሳርፉም ጥሪ አቅርበዋል።
ሰኔ 8 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
" 31 ሰዎች ሞተዋል ፤ 29 ሰዎች ደግሞ ቀላልና ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው ደሴና ኮምቦልቻ ሆስፒታሎች ሕክምና ላይ ይገኛሉ " - ኮማንደር ብርሃኑ ከተማ
⚫ " ተሽከርካሪው መንገድ ስቶ 170 ሜትር ጥልቀት ያለው ገደል ውስጥ ነው የወደቀው ! "
ከደሴ ተነስቶ ወደ አዲስ አበባ 60 መንገደኞችን አሳፍሮ ሲጓዝ የነበረ የሰሌዳ ቁጥር ኮድ 3 - 070898 ኢት የሆነ የሕዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪ ዛሬ ማለዳ 12:30 ላይ ኮምቦልቻ አቅራቢያ ልዩ ስሙ 'ሐረጎ' በተባለ ቦታ ከባድ አደጋ አጋጥሞታል።
የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ የትራፊክ ደህንነት ቁጥጥር ክፍል ኃላፊ ኮማንደር ብርሃኑ ከተማ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ቃል ፤ ተሽከርካሪው ለጊዜው ባልታወቀ ምክንያት መንገድ ስቶ 170 ሜትር ጥልቀት ባለው ገደል ውስጥ በመግባቱ እስካሁን የ31 ሰዎች ሕይወት አልፏል።
በአደጋው ቀላልና ከባድ ጉዳት የደረሰባቸው 29 ሰዎች ደግሞ በደሴና ኮምቦልቻ ሆስፒታሎች የሕክምና እርዳታ እየተደረገላቸው የሚገኝ ሲሆን የፖሊስ የትራፊክ ክፍልም የአደጋውን መንስኤ ለማጣራት ምርመራ እየደረገ መሆኑን ለቲክቫህ ኢትዮጵያ አስታውቀዋል።
አንድ የዓይን እማኝ ተጓዥ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ በሰጡት ቃል " ከከሚሴ ወደ ደሴ እየተጓዝኩ ነበር፤ ሐረጎ ስንደርስ ከባድ አደጋ ደርሶ መኪናዎች ሁሉ ቆመው መንገድ ተዘጋግቶ ነበር። ወርደን ስናይ የሆነውን ለመግለጽ እጅግ ከባድና ዘግናኝ ነው " ሲሉ ተናግረዋል።
" ብዙ አስክሬን ነበር ፤ ከዳገቱ ተንከባለው ወርደዋል ፤ ግማሾቹ በዛው ዳገቱ ጫካ ውስጥ ናቸው፤ ሌሎቹ ተስፈጥረው አስፓልቱን አልፈው ታች ወርደዋል " ያሉት ተጓዡ፣ " አንድ ሀይሩፍ ሦስት የተጎዱትን ይዞ አብረን ደሴ ሪፈራል አስገብተናቸዋል " ሲሉም አሽከርካሪውን አመስግነዋል።
ቦታው ላይ ተገኝው ባዩት መሰረት ስንት ሰዎች እንደሞቱ ስንጠይቃቸው፣ " አራት ሰዎች መትረፋቸውን አይቻለሁ " ብለው፣ የሟቾች ቁጥር በርካታ መሆኑን ገልጸዋል።
ምንም እንኳን ቃላቸውን ለቲክቫህ ኢትዮጵያ የሰጡት የኮምብልቻ ኮሚዩኒኬሽን መምሪያ እና ሌላ መረጃ አቀባይ የሟቾች ቁጥር 28 እና 24 እንደሆነ ቢገልጹም የኮምቦልቻ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ የትራፊክ ደህንነት ቁጥጥር ክፍል ኃላፊ ኮማንደር ብርሃኑ ከተማ ግን የሟቾች ቁጥር 31 መሆኑን ገልጸዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ የሹፌሩም ህይወት ማለፉን ሰምቷል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሰኔ 8 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
በ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ ሂደት የቀረቡ 43 ጥሰት እና ቅሬታዎችን የመስማት ሂደት ነገ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የመጨረሻ ውሳኔ እንደሚያገኝ የቦርዱ የክልል ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ማስተባበሪያ ክፍል ኃላፊ ቀነኒ እንሰርሙ አስታወቁ።
ኃላፊዋ ቦርዱ ሲያጣራቸው የቆያቸውን ዝርዝር ቅሬታዎችን ጠቁመዋል።
- መራጮች ፍላጎታቸው ባልሆነ መልኩ የአንድን የተወሰነ ፓርቲ ወይም የግል እጩ ብቻ እንዲመርጡ በተለያየ አካልና መንገድ በድምፅ መስጫው ቀን ተፅዕኖ መደረጉና መገደዳቸው፣
- የፓርቲና የግል እጩ ወኪሎች በድምፅ መስጫ ቀን ምርጫ ጣቢያ እንዳይገኙ መከልከላቸው፣ እንዲሁም የተወሰኑት ከገቡ በኋላ ሂደቱን ተከታትለው የድምፅ አሰጣጡ ተጠናቆ ቆጠራ ሊጀመር ሲል ከጣቢያ መባረራቸው፣
- በድምፅ መስጫው ቀን የምርጫ ቅስቀሳ ሲከናወን መቆየቱ፣
- ዕድሜያቸው ያልደረሰ ዜጎች በድምፅ አሰጣጥ ሂደቱ ላይ መሳተፋቸው፣
- ምርጫ አስፈጻሚዎች የድምፅ አሰጣጡን ምስጢራዊነት መጣሳቸውና በሌሎች አካላትም እንዲጣስ ማድረጋቸው፣
- የወረዳ አስተዳደሮች በምርጫ ሂደቱ ውስጥ ጣልቃ በመግባት፣ የፓርቲ ወኪሎችና ታዛቢዎች በጣቢያው ያላቸውን ሚና ወደ ጎን በመተው በሂደቱ ላይ ተፅዕኖ መፍጠራቸው የሚሉ ይገኙባቸዋል።
እነዚን አቤቱታዎች በሕጉ መሠረት የማስረዳት ሸክም የቅሬታ አቅራቢዎች በመሆኑ፣ ቦርዱ ያቀረቧቸውን የሰነድ፣ የቪዲዮና የፎቶግራፍ ማስረጃዎች ሲመረምር መቆየቱን ጠቁመዋል።
የሰው ምስክሮች በአካል ቀርበው በቃለ መሃላ፣ ርቀት ላይ ያሉት ደግሞ ማንነታቸው በቪዲዮና በስልክ ጥሪ ተረጋግጦ ቃላቸው መሰማቱን ገልጸዋል።
ቅሬታ የቀረበባቸው ፓርቲዎችና የአስተዳደር አካላትም በጽሑፍ ምላሽ እንዲሰጡ ዕድል የተሰጠ ሲሆን በጊዜ ገደቡ ያላቀረቡት መብታቸው ታልፎ ሂደቱ በመቀጠሉ ነገ በሚሰጥ ውሳኔ 43ቱ ጉዳዮች ሙሉ በሙሉ እንደሚጠናቀቁ ኃላፊዋ አሳውቀዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
አዲስ አበባ
ሰኔ 10 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
4 645
Repost from TIKVAH-ETHIOPIA
+1
#ምርጫ2018
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እስካሁን ምርጫ ከተካሄደባቸው 1139 የምርጫ ጣቢያዎች 723 ውጤቶችን ማጽደቁን አስታውቋል።
ቦርዱ ዛሬ ይፋ ካደረጋቸው ውጤቶች መካከል የብልፅግና ፓርቲ ፕሬዚዳንት የሆኑትና በጎማ 2 የተወዳደሩት የወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስቴር ዐብይ አሕመድ አሊ (ዶ/ር) ውጤት ይገኝበታል።
ጠ/ሚ ዐብይ አህመድ (ዶ/ር) በምርጫ ክልሉ ድምጽ ለመስጠት ከተመዘገቡ 108,725 መካከል የ106,028 ዜጎችን ድምጽ በማግኘት ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ፓርቲያቸውን ወክለው መቀመጫ አግኝተዋል።
በሌላ በኩል፤ በባህርዳር ከተማ ምርጫ ክልል ብልጽግና ፓርቲን ወክለው የተወዳደሩት የወቅቱ ም/ጠቅላይ ሚኒስትር ተመስገን ጥሩነህ ድንቁ ከተመዘገቡት 183,350 ውስጥ 168,787 ድምጽ በማግኘት የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ አግኝተዋል።
ቦርዱ በዛሬው ዕለት ለተጋባዥ እንግዶች ባስተላለፈው ጥሪ ላይ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ይፋዊ ውጤት ሰኔ 14 ቀን 2018 ዓ.ም እንደሚገለጽ አስታውቋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
አዲስ አበባ
ሰኔ 10 ቀን 2018 ዓ/ም
@tikvahethiopia
¡Ya disponible! Investigación de Telegram 2025 — los principales insights del año 
