en
Feedback
ከመጻሕፍት ዓለም - Book shelf 📗📚📖

ከመጻሕፍት ዓለም - Book shelf 📗📚📖

Open in Telegram

"ስለመጻሕፍት ከመጻሕፍት መንደር እንዘምራለን!"

Show more

📈 Analytical overview of Telegram channel ከመጻሕፍት ዓለም - Book shelf 📗📚📖

Channel ከመጻሕፍት ዓለም - Book shelf 📗📚📖 (@bookshelf13) in the Amharic language segment is an active participant. Currently, the community unites 18 759 subscribers, ranking 1 857 in the Books category and 1 792 in the Ethiopia region.

📊 Audience metrics and dynamics

Since its creation on невідомо, the project has demonstrated rapid growth, gathering an audience of 18 759 subscribers.

According to the latest data from 16 June, 2026, the channel demonstrates stable activity. Although there has been a change in the number of participants by -149 over the last 30 days and by -5 over the last 24 hours, overall reach remains high.

  • Verification status: Not verified
  • Engagement rate (ER): The average audience engagement rate is 13.32%. Within the first 24 hours after publication, content typically collects 4.97% reactions from the total number of subscribers.
  • Post reach: On average, each post receives 0 views. Within the first day, a publication typically gains 933 views.
  • Reactions and interaction: The audience actively supports content: the average number of reactions per post is 0.

📝 Description and content policy

The author describes the resource as a platform for expressing subjective opinions:
"ስለመጻሕፍት ከመጻሕፍት መንደር እንዘምራለን!"

Thanks to the high frequency of updates (latest data received on 17 June, 2026), the channel maintains relevance and a high level of publication reach. Analytics show that the audience actively interacts with content, making it an important point of influence in the Books category.

18 759
Subscribers
-524 hours
-387 days
-14930 days
Posts Archive
ፍልስፍናን ከተዋወኳት ጊዜ ጀምሮ ካነበብኳቸው መጽሃፍት ውስጥ ማንኛውም ጥልቅ ሃሳብ ያለው ሰው ሊያነባቸው ይገባል ብዬ የማስባቸውን ምርጥ እስር መጽሃፍት ልጋብዛችሁ። እንግዲህ በሁሉም ትውልድ ውስጥ፣ ከመዝናኛነት ባለፈ ትልቅ ትርጉም ያላቸው መጽሐፍት አሉ። እነዚህ መጽሐፍት የለመድናቸውን አስተሳሰቦች ይሞግታሉ፣ ቅዠቶችን ያፈርሳሉ፣ የማይመቹ ጥያቄዎችን ያነሳሉ፣ እንዲሁም እራሳችንን እና ዓለምን የምንረዳበትን መንገድ ይለውጣሉ። እነዚህ የምጋብዛችሁ አስር መጽሃፍት ዝም ብለው የሚነበቡ መጽሐፍት ብቻ አይደሉም፤ የሰውን ልጅ የአስተሳሰብ አቅጣጫ ሊቀይሩ የሚችሉ የእውቀት ማዕበሎች ናቸው። ፈላስፋ፣ ተማሪ፣ ጸሐፊ፣ ወይም ዝም ብሎ ጥልቅ አስተሳሰብን የሚወድ ሰው ከሆናችሁ እነዚህ መጽሐፍት በመደርደሪያችሁ ላይም በአእምሯችሁ ውስጥም ቦታ ሊኖራቸው ይገባል። 1. The Republic— ፕላቶ ይህ መጽሃፍ ምናልባትም በፍልስፍና ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ ተጽዕኖ ያሳደረው ስራ ሊሆን ይችላል። በሶቅራጥስ አንደበት፣ ፕላቶ ስለ ፍትህ፣ እውነት፣ ፖለቲካ፣ ትምህርት እና ስለ እውነታ (reality) ምንነት የሚመረምርበት ስራ ነው። እስካሁን ድረስ የሰው ልጅ ስለ አላውቂነትና እና እውቀት ካሰፈራቸው ታላላቅ ምልከታዎች አንዱ የሆነው ታዊቂው 'የዋሻው ምሳሌ' (Allegory of the Cave) የሚገኘውም በዚህ ድንቅ መጽሃፍ ውስጥ ነው ለምንድን ነው ይሄን መጽሃፍ ማንበብ ያለብን ካላችሁኝ ምክንያቱም እያንዳንዱ አሳቢ ሰው ውሎ አድሮ ፍትህ ምንድን ነው? እውነትስ ምንድን ነው? እንዲሁም እውነተኛውን ነገር ከቅዠት እንዴት እንለያለን? የሚሉ ጥያቄዎችን ማንሳቱ አይቀርምና እላቸሃለው። 2. Meditations — ማርከስ ኦሪሊየስ በሮማዊው ንጉሠ ነገሥት እንደ ግል ማስታወሻ የተጻፈው ይህ ዘመን አይሽሬ ስራ፣ ስለ ራስ-ስርዓት (self-discipline)፣ ስቃይ፣ ሟችነት እና ውስጣዊ ነፃነት ጥልቅ ግንዛቤዎችን የሚሰጥ መጽሃፍ ነው። ለምን እናንባብበው ካላችሁኝ ምክንያቱም ህይወት እኛን ከችግር ጋር ማጋፈጧ አይቀርም፤ ከዚህ መጽሃፍ በተሻለ ስለ ጽናት እና ክብር የሚያስተምሩ መጽሃፍት ጥቂት ናቸውና እላቹሃለው። 3. Critique of Pure Reason—ኢማኑኤል ካንት እስካሁን ካነበብኳቸው መጽሐፍት ውስጥ እጅግ ጠቃሚ እና ለመረዳት ከባድ ከሆኑት መካከል አንዱ ይህ መጽሃፍ ነው። በዚህ ስራ ውስጥ ካንት የሰውን ልጅ የእውቀት ገደብ ይመረምራል፤ እንዲሁም ስለ እውነታ በእውነት ምን ማወቅ እንደምንችል ይጠይቃል። ለምንድን ነው መነበብ አለበት ካላችሁን ምክንያቱም ዓለምን ከመረዳታችን በፊት፣ ዓለምን ለመመልከት (perceive ለማድረግ) እና ለመተርጎም የምንጠቀምባቸውን መሳሪያዎች መረዳት ስላለብን ነው እላቹሃለው። 4. Thus Spoke Zarathustra — ፍሪድሪክ ኒቼ ይሄ ከፊል ፍልስፍና፣ ከፊል ግጥም፣ እና ከፊል ትንቢት የሆነ የጀርመናዊው ፍሬድሪክ ዊልሄልም ኒቼ (My favorite philosopher of all time) ስራ ነው። በዚህ ስራው ውስጥ ኒቼ ባህላዊ የሞራል እሴቶችን፣ የሃይማኖት ዶግማዎችን እና የአስተሳሰብ ተገዥነትን ይሞግታል፤ ጎን ለጎን ደግሞ አዳዲስ እሴቶች እንዲፈጠሩ ጥሪ ያቀርባል። ለምን እናንብበው ካላችሁኝ ምክንያቱም የድሮ እርግጠኛነቶች (እምነቶች) ከፈረሱ በኋላ "እንዴት መኖር አለብን?" የሚለውን ጥያቄ እንድንጋፈጥ ስለሚያስገድደን እላቹሃለው። 5. The World as Will and Representation — አርተር ሾፐንሃወር ይሄ ስለ ፍላጎት፣ ስቃይ እና ስለ ህልውና እረፍት አልባ ተፈጥሮ የተደረገ ጥልቅ ፍለጋ ነው። ሾፐንሃወር በዘመናዊ ፍልስፍና፣ ሳይኮሎጂ እና ስነ-ጽሑፍ ውስጥ ተጽዕኖ ያሳደረ ድንቅ ፈላስፋ ነው። ለምን እናንብበው ካላችሁኝ የሰው ልጆች ለምን እንደሚሰቃዩ ከተጻፉት እጅግ ጥልቀት ያላቸው ትንታኔዎች አንዱ ስለሆነ እላቹሃለው። 6. Beyond Good and Evil— ፍሬድሪክ ኒቼ በዚህኛው መጽሐፉ ኒቼ በተለመደው የሞራል እይታ ላይ ቀጥተኛ ጥቃት ይሰነዝራል፤ እንዲሁም አንባቢዎች ተቀባይነት ካገኙ እውነታዎች በስተጀርባ የተደበቁትን ውስጣዊ ግፊቶች እንዲመረምሩ ይጋብዛል። ለምን እናንብበው ካላችሁኝ እውነተኛ አስተሳሰብ የሚጀምረው ሌሎች ሰዎች ሁሉ ያለምንም ጥያቄ የሚቀበሏቸውን ሃሳቦች መጠየቅ ስንጀምር ስለሆነ እላቹሃለው። 7. On the Genealogy of Morality— ፍሬድሪክ ኒቼ ይሄ ስለ ሞራል እሴቶች አመጣጥ የተደረገ ፍልስፍናዊ ምርመራ ነው። ኒቼ ሞራል እውነት ነው ወይስ አይደለም ብሎ ከመጠየቅ ይልቅ ከየት መጣ እና የማንን ፍላጎት ያገለግላል የሚለውን የመረመረበት ድንቅ ስራ ነው። ለምን እናንብበው ካላችሁኝ የእሴቶችን ታሪክ መረዳት እራሳችንን እንድንረዳ ስለሚያግዘን እላቹሃለው። 8. Fear and Trembling— ሶረን ኪርኬጋርድ ይህኛው ኬርኬጋርድ ስለ እምነት፣ ጭንቀት፣ ግለሰብነት፣ እና የሰውን ልጅ ህይወት ስለሚተረጉሙ ከባድ ምርጫዎች የጻፈው ድንቅ ስራ ነው። ለምን እናንብበው ካላችሁኝ በህይወት ውስጥ አንዳንድ እጅግ አስፈላጊ የሆኑ ውሳኔዎች በሎጂክ (በምክንያታዊነት) ብቻ ሊወሰኑ ስለማይችሉ በቀጥታ ወደ ሕልውና እንድናይ ስለሚረዳን እላቹሃለው። 9. Civilization and Its Discontent— ሲግመንድ ፍሮይድ ፍሮይድ በሰው ልጅ ደመነፍስ (instincts) እና ስልጣኔ በሚጠይቃቸው ነገሮች መካከል ያለውን ውጥረት የመረመረበት ስራ ነው። በዚህ መጽሃፍ ውስጥ ያሰፈራቸው ምልከታዎቹ ዛሬም ስለ ባህል እና ሳይኮሎጂ በሚደረጉ ክርክሮች ላይ ተጽዕኖ ማሳደራቸውን ቀጥለዋል። ለምን እናንብበው ካላችሁኝ በግለሰብ ፍላጎቶች እና በማህበራዊ ስርዓት መካከል ያሉትን የተደበቁ ግጭቶች ስለሚመረምር ጠቃሚ ነው እላቹሃለው። 10. The Structure of Scientific Revolutions — ቶማስ ኩን ይሄ ሳይንሳዊ እውቀት እንዴት እንደሚለወጥ የሚያሳይ አብዮታዊ ጥናት ነው። ኩን የአእምሯዊ እድገት አብዛኛውን ጊዜ እውነታዎችን በማከማቸት ብቻ ሳይሆን፣ በመሰረታዊ የአመለካከት ለውጦች (paradigm shifts) የሚመራ መሆኑን ያሳየበት ትልቅ ስራ ነው። ለምን እናንብበው ካላችሁኝ በጣም የምናምናቸው የእውቀት ስርዓቶቻችን እንኳን በታሪክ የተቃኙ እና ለለውጥ የተጋለጡ መሆናቸውን ስለሚያስተምረን እላቹሃለው። -------------------------------------------------------- እነዚህ አስር መጽሐፍት አንድ ወጥ የሆነ ፍልስፍና የላቸውም። እንዲያውም፣ አብዛኛዎቹ እርስ በርሳቸው በጥልቀት የሚጋጩ ናቸው። ሆኖም ግን አንድ ላይ ሲጣመሩ፣ ስለ እውነታ፣ እውቀት፣ ሞራል፣ ስቃይ፣ ነፃነት፣ ማህበረሰብ እና ስለ ህይወት ትርጉም አስደናቂ የሆነ ውይይት ይፈጥራሉ። እነዚህ መጽሃፍቶች ያላነበባችሁ ስታነቧቸው የመጨረሻ መልሶችን ለማግኘት ሳይሆን የተሻሉ ጥያቄዎችን እንዴት መጠየቅ እንደሚቻል ለመማር አንብቧቸው። ምክንያቱም ፍልስፍና የሚጀምረው እርግጠኛነትን ስናገኝ አይደለም። የሚጀምረው ለመጠራጠር፣ ለመመርመር፣ እና በራሳችን ለማሰብ የሚያስችል ድፍረት ስናዳብር ነው። ያነበባቹሃቸው ደግሞ ከነዚህ ውስጥ የትኞቹን መጽሃፍት አንብባቹሃል? እንዴትስ አገኛችሗቸው? ሃሳባችሁን አጋሩን እንወያይበት!! ይመቻቹ✌️ © Yonatan Abyss

ድንጋዩ፣ ከግዙፍ አለት ወደ ብይ እያነሰ መጥቶ፣ ከዛም የተሰወረ ቢመስለውም፣ ነገር ግን፣ በሆነ የማይታይ ቅርፅ ማንነቱን ቀይሮ በህልውና መኖር መቀጠሉን ጠረጠረ። ከዚህ መነሻ ነው ወደ "Theory of the small" ትኩረቱን ያዞረው። 'በዐይን የማይታይን ነገር እምን ላይ ላንከባለው?'ብሎ አንድ የእውቀት ተራራ ፈጠረ። ተራራውም አሁን "Particle phys-ics" ተብሎ የሚጠራው መሆኑ ነው። ይህ የሌሊሳ ግርማ ትርጓሜ ሲሲፈስን ከጥንታዊው አፈታሪክ አውጥቶ ወደ ዘመናዊው የሳይንስ እና የፍልስፍና አድማስ ያሸጋገረበት መንገድ እጅግ ረቂቅ ነው። ሲሲፈስን ከጉልበት ሰራተኛነት ወደ "Theoretical Physicist" የቀየረበት ጥበብ አዝናንቶ ያስደምመኛል። ​ ​ድንጋዩ ሟምቶ ሲያልቅ ሲሲፈስ የደረሰበት መደምደሚያ "Theory of the Small" መሆኑ ደሞ ሌላ አጃኢብ ነው። ይህም ቁስ (Matter) አይጠፋም፣ ቅርፁን ይለውጣል እንጂ የሚለውን የሳይንስ ህግ ያስታውሰናል። ሲሲፈስ ግዙፍ ድንጋይ መግፋት አቁሞ የማይታይ "Particle" ላይ ትኩረቱን ማድረጉ፣ ከሥጋዊ ድካም ወደ አእምሯዊ ሽግግር ማድረጉ ቢሆንስ። ​በጥንቱ ታሪክ ተራራው የዙስ ቅጣት ነበር፤ በዚህኛው ትርጓሜ ግን ተራራው የእውቀት ተራራ ሆኗል እያለን ቢሆንስ? ሲሲፈስ አሁንም ይገፋል፣ ነገር ግን አሁን የሚገፋው ድንጋይ ሳይሆን ጥያቄዎችን ወይም ሀሳቦችን ነው። ◉በአሁኑ ዘመን የሰው ልጅ እንደ ጥንቱ ድንጋይ በመሸከም ብቻ ሳይሆን፣ የማይታዩ ረቂቅ ነገሮችን በመመርመር ላይ ተጠምዷል ነው ሌሊሳ እያለን ያለው። ሌሊሳ ሲሲፈስን ድንጋዩ ሟምቶ ካለቀ በኋላ ወደ "Theory of the Small" እና "Particle Physics" ትኩረቱን እንዳዞረ አድርጎ መሳሉ፣ የዘመናችንን ሳይንሳዊ ግስጋሴ አይወክልም ነው የምትሉት? የሌሊሳ ትርጓሜ ሲሲፈስን ከግሪክ ተራራ አውጥቶ በዘመናዊው የሳይንስ ላብራቶሪ ያስቀምጠዋል። የአሁኑ ዘመን የሰው ልጅ መከራን ወደ ልምድ፣ ችግርን ደግሞ ወደ ብቃት የመቀየር አቅሙን የሚያጎላ ነው። ስራው "ገድለ ሲሲፈስ" መባሉ ራሱ ይህንን በጽናት የመታገልና የመለወጥ ሂደትን የሚያንፀባርቅ ነው። ▭▭ © Mes Oud

◉ የካሙና የሌሊሳ Sisyphus የ Sisyphus አፈታሪክ በግሪክ ሥነ-ጽሑፍ ውስጥ ብቻ ሳይሆን በዘመናዊው የፍልስፍና ዓለም ውስጥም የሚንከባለል ትልቅ ቋጥኝ ነው። ​ሲሲፈስ ትልቅ ድንጋይ ወደ ተራራ ጫፍ እንዲገፋ፣ ጫፍ ላይ ሲደርስ ደግሞ ድንጋዩ ተንከባሎ ወደ ታች እንዲወርድ፣ እርሱም ያንኑ ደግሞ ተመልሶ እንዲገፋ ለዘላለም የተፈረደበት ምስኪን ነው። ሲሲፈስ የተቀጣበት ምክንያት በአጭሩ ሲቀመጥ አማልክትን በመናቁ እና ሞትን ለማታለል በመሞከሩ ነው። እኔ ግን ይሄ ጉደኛ የሰራው ስራ በአጭሩ ተሰትሮ ባይቀመጥ ደስስ ይለኛል። ያጠፋቸው ጥፋቶች ዛሬ ላይ ሁነን ስናስባቸው የሚያዝናኑ ናቸው። በግሪክ አፈታሪክ መሰረት ሲሲፈስ እጅግ ብልህ፣ ተንኮለኛ እና ክፉ ንጉስ ነበረ ይላሉ (የሚያውቁት ልበል?)። ከጥፋቱ አንዱ የተባለው የአማልክትን ሚስጥር ማውጣቱ ከሌሎች ሲነፃፀር ቀለል ነው። ምክንያቱም ሲሲፈስኮ ሞትን በሰንሰለት ያሰረ ሰው ነው😂 ዙስ ሲሲፈስን እንዲቀጣው የሞት አምላክ የሆነውን Thanatosን ላከው። ነገር ግን ሲሲፈስ በብልሃቱ ታናቶስን አታሎ በሰንሰለት አሰረው። በዚህም ምክንያት ለተወሰነ ጊዜ በምድር ላይ ማንም ሰው ሊሞት አልቻለም ነበር። ይህንን የተፈጥሮን ስርዓት በማናጋቱም አማልክትን ክፉኛ አስቆጣ። በዚህም አያበቃም ከሞት በኋላ ተመልሶ መምጣት የቻለ ቆቅ ሰው ነውኮ። ሲሲፈስ ሊሞት ሲል ለሚስቱ "ከሞትኩ በኋላ አስከሬኔን አትቅበሪው፣ መስዋዕትም አታቅርቢ" ብሎ አዘዛት። ወደ ሲኦል (Underworld) ሲወርድ፣ ለሲኦሉ ገዥ ለ Hades "ሚስቴ ስርዓቱን ስላልፈጸመች ሄጄ ላስተምራትና ልመለስ" ብሎ ፈቃድ ጠየቀ። ሀዴስ ቢፈቅድለትም፣ ሲሲፈስ ወደ ምድር እንደተመለሰ ዳግመኛ ወደ ሲኦል አልመለስም ብሎ ለብዙ ዓመታት በደስታ ኖረ። በመጨረሻም በጉልበት ተይዞ ወደ ሲኦል ሲመለስ፣ አማልክቱ "ከእንግዲህ በብልሃትህ ልታመልጠን አትችልም" ለማለት ዘላለማዊ የሆነውንና ምንም ውጤት የማይገኝለትን ያንን ድንጋይ የመግፋት ቅጣት ሰጡት። ➊ የ Albert camu ሲሲፈስ ​ታዋቂው ፈላስፋ ካሙ ይህን ታሪክ በመጠቀም "The Myth of Sisyphus" የተሰኘውን ድርሰት ፃፈ። ካሙ የሚለው የሚገርም ነገር አለ "ሲሲፈስ ደስተኛ እንደሆነ አድርገን ማሰብ አለብን።" ለምን? ምክንያቱም ሲሲፈስ እጣ ፈንታውን አውቆታል። ድንጋዩ ሁልጊዜ እንደሚወርድ እያወቀ መግፋቱን ይቀጥላል። ድካሙን በጸጋ መቀበሉ ለቅጣቱ ትልቅ ምላሽ ነው ይላል። በተለይ እኛ በምንኖርበት ዓለም ውስጥ፣ ብዙ ጊዜ የምናደርጋቸው ነገሮች ተደጋጋሚ እና አሰልቺ ሲሆኑብን የሲሲፈስ ታሪክ ትልቅ ትምህርት ይሰጠናል። ከሲሲፈስ ታሪክ እኩል የሚሰሩት meme ያዝናኑኛልም😂 ⎡Zeus finding out that some random French guy said that Sisyphus is happy and millions of other people agree😂 ምን የሚል ይመስላችኋል? ⎡ imagines Zeus being confused, annoyed, or offended that his punishment accidentally became inspirational philosophy.😂⎤ ◉ ካሙ ሲሲፈስን "Absurd Hero" በማለት ይጠራዋል። ሲሲፈስ የሕይወትን ትርጉም አልባነት ተረድቶ ነገር ግን ሳይሸነፍ መኖሩን ለመቀጠል በመወሰኑ። ደሞም አመፀኛ ነው ይለዋል። «The only way to deal with an unfree world is to become so absolutely free that you very existence is an act of rebellion.» በካሙ ፍልስፍና "አመጽ" ማለት ራስን ሲጥ ማድረግ ወይም ተስፋ በስለት መሸለት ሳይሆን፣ ትርጉም በሌለው ዓለም ውስጥ በጽናት መኖር ነው። አማልክቱ ሲሲፈስን ለመቅጣት የፈለጉት ተስፋ እንዲቆርጥና እንዲሰቃይ ነበር። ሲሲፈስ ግን ስቃዩን በጸጋ ተቀብሎ ድንጋዩን መግፋቱን ሲቀጥል፣ የአማልክቱን ቅጣት ትርጉም አልባ ያደርገዋል ነው የሚለው። ❷ የሌሊሳ Sisyphus በኛ ሀገርም ልክ እንደ ካሙ ሁሉ የሲሲፈስን ቅጣት ለመተርጎም የሞከረ ደራሲ አለ። ሌሊሳ ግርማ "ገድለ ሲሲፈስ" በተሰኘ መጣጥፉ የሲሲፈስን መጨረሻ ይተነብያል። እንደተለመደው ሲሲፈስ «ዳገቱ ላይ አትዘን ጉልበቴ» ብሎ እያንጎራጎረ ያንን ዲንጋይ ይገፋ ነበር። ያ ዲንጋይ ጫፍ ከደረሰ በኋላ ቁልቁል ይወርዳል። ሲሲፈስም «ቀላል ይሆናል» እያለ ያንን ዲንጋይ ሊገፋ ቁልቁል ይንደረደራል። በዚህ መልኩ እልፍ ዘመናት ተሻገሩ። በግዜ ብዛት ሲሲፈስ ያንን ዲንጋዩን ሲያንከባልል እጅግ ፈርጣማ ይሆናል። ዲንጋዩ ደግሞ አንሶ አንሶ ኳስ ያክላል። ከዛ ግን ያው እርግማኑ ስላለ ከተራራ ስር ሁኖ ዲንጋዩን ወደላይ ይጠልዘዋል። ተንከባሎ እግሩ ስር ይመጣል። እንደ ድንጋዩ ቅርፅ አማራጭ ጨዋታዎችን መፈልሰፍም ያዘ። አሎሎ፣ ፑል፣ የብይ ጨዋታ። ይህ የሌሊሳ ትርጓሜ ከካሙ ፍልስፍና በላይ ያስደንቀኛል። ካሙ ሲሲፈስን በስነ-ልቦናዊ ጥንካሬው ጀግና ሲያደርገው፣ ሌሊሳ ደግሞ ሲሲፈስን በሂደት ከቅጣቱ በላይ የገዘፈ ማንነት እንዳለው አድርጎ ስሎታል። በግሪክ አፈታሪክ ድንጋዩም ሆነ ሲሲፈስ የማይለወጡ ናቸው። በሌሊሳ እይታ ግን ግዜ በሁለቱም ላይ ለውጥ ያመጣል። በዚህ ታሪክ ውስጥ ስቃይን ወደ ጨዋታ የመለወጥን ጥበብ እናያለን። እንደ አንድ የነጻነት መንገድ ሆኗል። ሲሲፈስ ድንጋዩን ለመግፋት መታገል ትቶ እንደ ኳስ መጠለዝ ሲጀምር፣ አማልክቱ የሰጡትን ስቃይ ወደ መዝናኛነት ቀይሮታል ማለት ነው። ይህ ለቅጣቱ ሰጪዎች ትልቅ ንቀት ነው። ግን ደግሞ እንደዚህም ይላል... « የፈለገ አይነት ጨዋታ ቢፈለስፍም ድንጋዩ እና ሲሲፈስ የተረገሙ በመሆናቸው የመሄድ እና የመመለስ እጣ ፈንታቸው በድንጋዩም በሲሲፈስም ውስጥ አለ። አዳዲስ እስፖርታዊ ጨዋታዎች ቢፈጠሩም፣ የቀድሞው እርግማን ዘረ-መል በውስጣቸው ይገኝባቸዋል።» ◉ "የእርግማን ዘረ-መል" አለባቸው ሲለን፣ የሰው ልጅ ምንም ያህል ሁኔታዎችን ቢለምድና ቢቀይር፣ ከመሰረታዊው የህልውና ትግል (Existential struggle) ማምለጥ እንደማይችል ለማሳየት ይመስለኛል። ጨዋታውም በራሱ ተደጋጋሚ ነውና። ቢሆንም ሌሊሳ ሲሲፈስን ከአማልክት እስረኛነት አውጥቶ፣ በገዛ እጣ ፈንታው ውስጥ የራሱን ዓለም የፈጠረ "ፈጣሪ" አድርጎታል ማለት ይቻላል። ​ ◉ እናላችሁ ሲሲፈስ የመጨረሻ ድንጋይዋ ስታንስ የብይ ጨዋታን አበርክቶ ብቻውን ይቀራል። ድንጋይ ሳይኖር ምን እንደሚሰራ ግራ ግብት አለው። እድሜ ልክ ነው ድንጋዩን እንዲያንከባልል የተፈረደበት፤ግን ድንጋዩ ድንገት ሟምቶ አለቀ። ግራ ሲገባው፣ 'የማራቶን ሯጭ ልሁን እንዴ?” ብሎም አቅማምቶ ነበር። «የምገፋው ነገር ባይኖር እንኳን ዝም ብዬ አየር እየገፋሁ ልሩጥ» ብሎ እያመነታ ሳለ፣ አንድ ሀሳብ ብልጭ አለለት ይለናል። እዚህ ጋር የልምድ እስረኝነት አለ። ሲሲፈስ ድንጋዩ ሲያልቅበት ግራ መጋባቱ ትግል የህልውናው መሠረት እንደሆነና ሰው ያለ ትግል መኖር እንደማይችል ያሳያል። ስቃዩን ሲያጣ ስቃዩን መፈለግ የጀመረው ለዚህ ነው።

ከደሀ ችግር ይልቅ የሀብታምን ችግር መረዳት ከባድ ነው! (The poor fear hunger; the rich fear emptiness.) (እ.ብ.ይ.) ስለድሃ ብዙ ተፅፏል፤ ስለሃብታም ግን ብዙ አልተባለም፡፡ የድሃ ስቃይ የሚታይ ነው፤ የሃብታም ስቃይ ግን የተደበቀ ነው፤ ባለቤቱ እንጂ ባዳም ሆነ ዘመድ አያውቅለትም፡፡ ሙዚቃው፣ ግጥሙ፣ ሙሾው፣ ፉከራው፣ ቀረርቶው የድሃን ብሶት ብቻ የሚያስተጋባ ነው፡፡ የምስኪኑን ማጣቱን የሚያቀነቅን፣ አስከፊ ኑሮውን የሚናገር ዘፈን ሞልቷል፡፡ ስለሃብታም ችግር የዘፈነም ይሁን የተቀኘ ግን አላየሁም-አልሰማሁም፡፡ ስለሃብታም ጥጋብ እንጂ ስለነፍሱ ረሃብ የተናገረ አላጋጠመኝም፡፡ የሃብታሙ ችግር ተዘንግቷል፡፡ የሃብታሙን ብሶት የተነፈሰለት የጥበብ ሰው የለም ማለት ይቻላል፡፡ ሃብታም በገንዘቡ ብሶቱን የሚተነፍስ የሚመስለን ብዙ ነን፡፡ በርግጥ በየመሸታ ቤቱ የውስጡን እሳት ለማብረድ፤ የልቡን ህመም ለማስታገስ፣ የነፍሱን ስቃይ ለማከም ገንዘብ በመበተን፤ የስሜት ጎዶሎውን በአስረሽ ምቺው ለመርሳት የሚሞክር ብዙ አለ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ መፍትሄ ጊዜያዊ እንጂ ቋሚ አይደለም፡፡ ሀብትና ቁስ የማያድነው በሽታ ነው የሃብታም በሽታ፡፡ በገንዘብ ወጪ የማይታከም ህመም ነው ሃብታሙ ያለው፡፡ የብዙዎቻችን የድህነት ችግር በገንዘብ ሊፈታ ይችላል፡፡ የሃብታም ጭንቀት ግን በገንዘብ የሚወገድ አይደለም፡፡ ደሀ በዓይን ያስታውቃል፡፡ ልብሱ የታረዘ፤ ፊቱ የከሳ፣ ወዘናው የደረቀ ሰው የተቸገረው ምን እንደሆነ ለማወቅ ቀላል ነው፡፡ ሐብታም ደሀ የሆነበትን ነገር ማወቅ ግን አስቸጋሪ ነው፡፡ ያለው የሚመስልን የሌለው ምን እንደሆነ ለማወቅ የልብ-አውቃና አስተዋይ መሆንን ይሻል፡፡ ፊቱ የበራ ውስጡ ግን በሃዘን የጠቆረ እልፍ ነው፡፡ ጥርሱ የሚስቅ ልቡ ግን ሁሌ የሚያነባ መዓት ነው፡፡ ድሃው ሃብታም የሆነበት፤ ሃብታምም ድሃ የሚሆንበት ብዙ ነገር አለ፡፡ ያለው ሁሉም አለው ማለት አይደለም፤ የሌለው ብዙ ነገር አለ፡፡ የሌለውም ሁሉ ነገር የለውም ማለት አይደለም፤ የሌለው ያለው ብዙ ነገር አለ፡፡ የተንደላቀቀ ኑሮ፣ ውብ ቤት፣ ውድ ቁሳቁስ ግብዓት እንደተሟላለት እስር ቤት ሊሆን ይችላል፡፡ የኪስ ቦርሳው የሞላ ልቡ ግን ብዙ ነገር የጎደለው ሀብታም ይኖራል፡፡ ቁሳዊ ሃብት ተትረፍርፎለት ታማኝና የልብ ሰው ያጣ አይጠፋም፡፡ የሃብታም ቸግር ከድሃው ችግር በላይ ነው፡፡ ድሃው በልቶ ማደርን ነው የሚፈልገው፤ ሀብታሙ ግን ባለው ላይ መጨመርን ነው የሚሻው፡፡ ደሃ የዕለት እንጀራውን ካገኘ ጣፋጭ እንቅልፍ ይወስደዋል፡ ሀብታሙ የሚበላው ሳያጣ እንቅልፍ ያጣል፡፡ ብዙ ሃብታሞች ቁሳዊ ፍላጎታቸውን አሟልተዋል፤ አሳዛኙ ነገር ግን ብዙዎቹ መንፈሳዊ እርካታቸው የተሟላ አይደለም፡፡ የድሎት ኑሮ የነፍስን ርሃብ ይሸሽጋል፡፡ ሀብታም ለቤተሰቦቹ መስጠት የነበረበትን ጊዜ ሰውቶ ነው ሀብት የሚያደልበው፤ ድሃው ግን ጊዜ አባክኖ ነው የሚቸገረው፡፡ ሃብታም ውስጣዊ ነፃነቱን በውጫዊ ሃብቱ ማስጠበቅ የሚችል ይመስለዋል፡፡ የውስጡንና የውጪውን ማመጣጠን ባለመቻሉ በቁስ ብቻ ሲበለፅግ በመንፈስ ይደኸያል፡፡ ቱጃሩ ገንዘብን ማግኘት ብቻ እንደስኬት ይቆጥራል፡፡ ገንዘቡን ካገኘ በኋላ ግን ትርጉም ያጣበታል፡፡ ድሃው ግን በልቶ ማደር ነው የመጀመሪያ ግቡ፡፡ ሀብታምነት ተራ ሆኖ የመኖርን ነፃነት ያሳጣል፡፡ ድሃነት ደግሞ ከሰው እኩል የመሆንን ነፃነትን ይነፍጋል፡፡ ዋናውና ትልቁ ችግር ሃብታም በዙሪያው የከበቡት ሰዎች እውነት እሱን ይሁን ገንዘቡን ወደው የቀረቡት ስለመሆናቸው ጥርጣሬ ይገባዋል፡፡ የወደደውን፣ የተከተለውን፣ አመስጋኙን፣ አድናቂውን፣ አጭብጫቢውን ሁሉ አያምንም፡፡ መፅሐፈ ምሣሌ ‹‹ድሃ በባልንጀራው ዘንድ የተጠላ ነው፤ የባለጠጋ ወዳጆች ግን ብዙዎች ናቸው›› እንዲል ድሃውን የሚቀርበው፣ የሚወደውና የሚጠጋው ጥቂት ነው፤ የሀብታም ሰው አጨብጫቢውና አጋፋሪው ግን ለጉድ ነው፡፡ ታዋቂው አሜሪካዊ ፈላስፋ ሔነሪ ዴቪድ ቶሮው (Henry David Thoreau) ‹‹ከፍቅር ይልቅ፣ ከገንዘብ ይልቅ፣ ከዝና ይልቅ እውነት ስጠኝ›› የሚለው ወድዶ አይደለም፡፡ ለእሱ እውነት ማለት ለህሊና መኖር ማለት ነው፡፡ እንደእሱ ሃሳብ ብዙ ሰዎች መስዋዕትነት የሚከፍሉት ለዝና፣ ለቁሳዊ ስኬትና ለፍቅር ነው፡፡ ገንዘብ ባሪያ፤ ፍቅር ጥገኛ ያደርጋል፤ ዝና ደግሞ ከህሊና ያጋጫል ማለቱ ነው፡፡ ፍቅር እውነት ከሌለው ስሜት ብቻ የሆነ ቅዠት ነው፡፡ ፈላስፋው ከነዚህ ሁሉ ችግሮች ነፃ አውጪው እውነት ነው ብሎ ያምናል፡፡ እውነት ነው ሰውን ከነፍሱ ጋር የሚያስማማው፤ ሌላው የስጋ ፍላጎት ውጤት ነው፡፡ ጌታችንና መድሐኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በማርቆስ ወንጌል ምዕራፍ 8 ቁጥር 36 ላይ ‹‹ሰው ዓለምን ሁሉ ቢያተርፍ፤ ነፍሱንም ቢያጎድል ምን ይጠቅመዋል?”›› እንደሚለው እውነትን ሰውተህ፣ ልብህን አሳዝነህ፣ መንፈስህን አጎሳቁለህ፣ ነፍስህን አክስተህ፣ እውነትን ሸምጥጠህ፣ ሞራልህን ክደህ የምትሰበስበው ገንዘብ ከትርፉ ይልቅ ጉዳቱ ያመዝናል፡፡ ሰው በድለህ የምታገኘው ሀብት ቀስ በቀስ ያጠፋሃል እንጂ አያለማህም፡፡ ከምትደሰትበት ይልቅ የምትታመምበት ይበልጣል፡፡ የኋላ ኋላ የምታዝንበት እንጂ እስከመጨረሻው የምትፈነጥዝበት አይሆንም፡፡ ሰው ነህና የውስጥህ ጩኸት ሲያሸንፍህ የምትገባበት ይጠፋሃል፡፡ ነፍስህ መጠየቅ ሲጀምር አዕምሮህን ከመውቀስ በስተቀር ሌላ መልስ የለህም፡፡ ገንዘብን ብቻ ማሳደድ አይጠቅምም፡፡ ገንዘብን ከመገንዘብ ጋር አመጣጥነህ ካልያዝከው ያለምከውን እውነተኛ ደስታ አታገኘውም፤ ጭራሽ በሽታ ይዞብህ ይመጣል፡፡ ለዚህ ነው ቦብ ማርሌይ ‹‹ገንዘብ ቁጥር ነው፤ ቁጥር ደግሞ መጨረሻ የለውም፡፡ የደስታችንን ምንጭ ገንዘብ ብቻ ካደረግን መቼም ቢሆን ደስተኛ አንሆንም፡፡›› የሚለው፡፡ አሜሪካዊው ቱጃር ሮክ ፌለርም ‹‹ሠርቼ ብዙ ሚሊየን ብሮችን አግኝቼአለሁ፡፡ ነገር ግን አንዳቸውም እውነተኛ ደስታ አልሰጡኝም›› በማለት ገንዘብ ብቻውን እርካታና እረፍት እንደማይሰጥ ተናግሯል፡፡ ወዳጄ ሆይ… ገንዘብ ያለውን ሰው ጭንቀቱንና ችግሩን ተረዳ፤ የራሱ ውጊያ እንዳለበትም ተገንዘብ፡፡ ሁሌም ወዳጅነትህን፣ ጉርብትናህን፣ ዝምድናህንና ሌላ ሌላውንም በሃብቱ ላይ አትመስርት፡፡ ኪሱ ሙሉ ነውና አይጎድልበትም አትበል፡፡ አንተ ያለህ እሱ የለውም፤ እሱ ያለው አንተ የለህም፡፡ እዘንለት እንጂ አትቅናበት፡፡ ትክክለኛውንና አጭበርባሪውን ባለሃብት ለይ፡፡ ለፍቶ፣ ጥሮ፣ ወጥቶ ወርዶ ለራሱ የደረሰውንና ለሀገር የተረፈውን መልካሙን ባለሃብት አድንቀው አመስግነው፡፡ ሁሉንም በአንድ መነፅር አትመልከት፡፡ ‹‹የትም ፍቺው ዱቄቱን አምጪው›› በሚል ፈሊጥ በህገወጥ መንገድና በግፍ ገንዘብ በመሰብሰብ የናጠጠውን ደግሞ ተቃወመው እንጂ አታድንቀው፡፡ አንተም በመልካሙ እንጂ በክፉው መንገድ አትወሰድ፡፡ ቸር ጊዜ! ------------------------------------ © እሸቱ ብሩ ይትባረክ (እ.ብ.ይ.) ሠኞ ግንቦት ፫ ቀን ፳፻፲፰ ዓ.ም.

ብርሃኑ ዘርይሁንን ሳገኘው ከኔ የባሰ አይናፋር ነው። ማእበልን ጀምሬ መጨረስ አልቻልኩም። አፃፃፉ ጥሩ ነበር። ግን የረሃብ ሰቆቃውን ተቋቁሜ ማንበብ አልቻልኩም። እንዴት ችሎት ጻፈው! ―ስብሐት ስለ ብርሃኑ ዘርይሁን ❷❾ "የደራሲ ብእር ዥንጉርጉር ነው።" ደራሲ እናት ነው። አምጦ፣ አስቦ፣ ተጨንቆ መፅሀፍት ይወልዳል። አንዳንዴ መፅሀፍቱ ስለሚመሳሰሉ መንታ ይመስላሉ። ሌላ ግዜ ደግሞ ፍፁም የተለያዩ ይሆኑና የደራሲ ብእር ዥንጉርጉርነትን ይነግረናል። የስብሐት ገብረእግዚአብሔር ትኩሳት እና ሰባተኛው መልአክ ልብወለዶች መንትያ ናቸው―በመቼት ቢባል፣ በገፀባህሪ አሊያም በጭብጥ ተቀራራቢ ናቸው። ከስብሐት ሳንወጣ የስብሐት ሌቱም አይነጋልኝ፣ አምስት ስድስት ሰባት እንዲሁም ስምንተኛው ጋጋታ በቅርፅም በይዘትም የብርሃን አመት ያህል ይራራቃሉ። ሌቱም አይነጋልኝ በናቹራሊዝም ፣ አምስት ስድስት ሰባት በሪያሊዝም ፣ ስምንተኛው ጋጋታ ደግሞ በፋንታዚ የተፃፉ ናቸው። በዚህም ስብሐት ብዙ ኦሪጅናሊቲ(ወጥነት) ያለው ደራሲ ነው ማለት ይቻላል። ከሌሎች የኮረጀውንም ቢሆን የራሱን ቀለም ይጨምርበታል። ስብሐት በአንድ ምናብ ብዙ ዘውጎችን አስተናብሮ ማኖር የቻለ ዥንጉርጉር ደራሲ ነው። ❸❶ ሶስት ወንድማማቾች የተወለዱት አድዋ ርባገረድ። ታላቁ ስብሐት፣ ከዚያ ተወልደ፣ በመጨረሻ ዮሴፍ። ስብሐት ደራሲ ነው፤ ጋሽ ተወልደ በአካባቢ ጥበቃ ዶክተር ናቸው፣ ትንሹ ዮሴፍ ጠበቃ ነው። ታዲያ ዮሴፍም ምኞቱ ደራሲ መሆን ነበር። ስብሐት ከአንድ ቤት ሁለት ቺስታ አይኖርም ብሎ ታናሽ ወንድሙን ከደራሲነት ዝንባሌው ከለከለው። ያውቃላ የደራሲውን ኑሮ። ስለ ደራሲ መከራ የሚገልጽ አንድ ታሪክ ልንገራችሁ፦ ከእለታት አንድ ቀን እግዚአብሔር የእጁ ስራ የሆኑትን ፍጥረቶችን ለመጎብኘት ወደ ምድር ወረደ። በመንገድ ሲያልፍ አንድ ሰው ሲያለቅስ ደረሰ፦ "ምን ሆነህ ነው የኔ ልጅ?" "አይነስውር ነኝ" እግዚአብሔርም ፈወሰውና አይኑን አበራለት፤ ደስተኛም ሆነ። አሁንም ሲሄድ ሌላ የሚያለቅስ ሰው አየ፦ "ምን ሆነህ ነው ልጄ?" "አካለ ስንኩል ነኝ" እግዚአብሔርም እጁን አንስቶ ከሽባውነቱ ፈወሰው። ደስተኛም ሆነ። አሁንም በመንገዱ ሌላ የሚያለቅስ ሰው ገጠመው፦ "ምን ሆነህ ነው ልጄ?" "ደራሲ ነኝ!" ይሄን ግዜ እግዚአብሔር ከደራሲው ጋር ቁጭ ብሎ አብሮ መራር እንባን አነባ። ❤️ ❤️❤️ ስናጠቃልል አሜሪካኖች በየአመቱ አንድ ውድድር ያደርጋሉ—ኧርነስት ሄሚንግዌይን የመምሰል ውድድር። ሸበቶ፣ ጺማም አዛውንቶች ከመላው አሜሪካ ለዚህ ውድድር ይሰባሰባሉ። ሄሚንግዌይ የአልኮል ሱሰኛ ነበር። ውድድሩንም መለስተኛ የመጠጥ ፌስቲቫል ይመስላል። የአልኮል ዘር እንደ ጉድ ይጠጣል። ብዙ ግዜ ጥያቄ የሚፈጥርብኝ አንድ ጉዳይ ነበር። አሜሪካኖች ትልቁ ደራሱያቸው ሄሚንግዌይ ነው ወይ? ሄርማን ሜልቪልና ማርክ ትዌይን የት ገብተው ነው? ስለ ሄሚንግዌይ በደንብ ሳውቅ ግን ነገሩ ተገለጸልኝ። ሄሚንግዌይ ደራሲ ብቻ አልነበረም። ሄሚንግዌይ icon(ምልክት) ነበር። የጻፋቸው መጽሀፍት ብቻ ሳይሆን የኖረው ኑሮ አስደናቂ ነበር። በአንደኛው የአለም ጦርነት የአምቡላንስ ሾፌር ሆኖ ተሳትፏል፤ በስፔይን የእርስ በእርስ ጦርነትን ተመልክቷል፤ የጎሽ ውድድር(bullfighting) ተካፍሏል። አደንና አሳ ማጥመድ ነፍሱ ነበር። እንደ ሰለብሪቲ የተንደላቀቀ ህይወት ኖሯል። በአንደኛ ደረጃ ትኬት አለምን ዞሯል። ብዙ ብዙ . . . በአጭሩ ሄሚንግዌይ አስደናቂ ሰው ነበር። በስሙ ውድድር ቢዘጋጅለት አይበዛበትም። ይሄን ሃሳብ ይዤ ወደ እኛ ሃገር ልምጣ። ብዙ ድንቅ ደራሲዎች አሉን። ጋሽ ስብሐት አንዱ ነው። ስብሐት የኢትዮጵያ ስነጽሑፍ ንጉስ አይደለም። ውድድር ውስጥ መግባቱን ባልወደውም ስብሐትን የሚበልጡ ታላላቅ ደራሲዎች አሉን—ጸጋዬ ገብረመድህን፣ ሐዲስ አለማየሁ፣ ዳኛቸው ወርቁ፣ በአሉ ግርማ ወዘተ ወዘተ። ነገር ግን እንዲህ ያለ ደራሲን የመምሰል ውድድር ለማዘጋጀት ከተፈለገ ከስብሐት የበለጠ የሚመጥን የለም። አንደኛ ስብሐት እንደ ደራሲ ብቻ ሳይሆን እንደ ሰው የሚወደድ ነው—ስብእናው ግዙፍ ነው። ሌላው ደግሞ ስብሐት ከስነጽሁፍ ማእቀፍ ውጪም ታዋቂ ነው—ሰለብሪቲ ቢጤ ነው። የማያነበውም፣ መጽሀፍ ገልጦ የማያውቀውም ስብሐትን ያውቀዋል። Icon ነው። በስሙ ብዙ ቀልዶች ይነገራሉ—አብሮን እያለ ተረት ወደ መሆን ደረጃ ደርሷል። የተደበቁ፣ የማይወሩ ጉዳዮችን በመድፈር፣ አደባባይ በማውጣት የባህል አብዮት የፈጠረ ሰው ነው። ከነእንከኖቹ የሚወደድ ሰው ነበር። በስብሐት ገብረእግዚአብሔር የልደት ቀን እሱን የመምሰል አመታዊ ውድድር ቢዘጋጅ ለስነጽሁፍ፣ ለባህል ውለታ ዋልን ማለት ነው። © Tewodros Shewangizaw Zergaw

ጋሽ ስብሐት ከርባገረድ፣ አድዋ ለመጀመሪያ ግዜ ወጥቶ ወደ አዲስአበባ እያመራ ነበር። እርግጠኛ ባልሆንም 12 አመቱ ይሆነዋል። ከአጎቱ ጋር ነው የሚሄደው። ሁሌ ጠዋት ፍሪታታ ይጋብዙታል በሱ ምርጫ። ያቺ ፍሪታታ እንዴት እንደምትጥም ጩጬው ስብሐትለአብ ብቻ ነው የሚያውቀው። ጠዋት ጠዋት ለ30 ደቂቃ ያህል ገነት የገባ ያህል ነው። ርባገረድ እያለ የጓደኛው እናት ይሞታሉ። እሱም ጓደኛውም ነፍስ አያውቁም ልጆች ናቸው። ታዲያ ለቀስተኞች ጓደኛውን "የሟች ልጅ ነው አይደለ!" ብለው ግንባሩን ይስሙታል። ስብሐት በትንሽ ልቡ እንዲህ ተመኘ፦ "ምነው የእኔም እናት በሞተችና እንዲህ ባዘኑልኝ!" ❷❹ ማስታወሻ ላይ ከሚደንቁኝ ክፍሎች አንዱ ስብሐት ለስንዱ የፃፈላት የፍቅር ደብዳቤ ነው። ስንዱ ራሷ ደብዳቤው የፍቅር መሆኑን አታውቅም ነበር። ይህንኑ ለስብሐት ስትነግረው "አለማወቅሽ ነው እርፍናው" ብሏታል። ዘነበ ወላ ስለዚህ ደብዳቤ ሰምቶ ማስታወሻ ውስጥ ለማካተት ስንዱን ያገኛትና ሲጠይቃት ፈቃደኛ ሆና ደብዳቤዎቹን ትሰጠዋለች። ግን አንድ ጥያቄ አስከተለች፦ "ለመሆኑ እድሜህ ስንት ነው?" ዘነበ የጥያቄው ድንገተኝነት ምክንያቱ ሳይገባው "አርባዎቹ ውስጥ ነኝ" "በል ሃምሳዎቹ ውስጥ ሳትገባ ጨርሰው። ሃምሳዎቹ ውስጥ የገባ ሰው ከመስራት ይልቅ ትዝታዎቹን ማውጋት ነው የሚቀናው" አብረው ተሳሳቁ። በሌላ ቀን የማን ደብዳቤ እንደሆነ ለስብሐት ሳይነግሩት አነበቡለት። ስብሐት በመሃል እያስቆመ እያስደገመ ሲሰማ ቆየና "ማንም ይሁን ማን የፃፈው ታላቅ ገጣሚ ነው" አለ እያዳነቀ። በመጨረሻ ፀሃፊው እራሱ እንዲሆነ ሲነግሩት ስብሐት በመደመምም በማሾፍም "ታላቅ ፖኤት ነኝና" ሲላቸው በሳቃቸው አጀቡት። ደብዳቤው እንዲህ ይጀምራል፦ ሻህራዛድ ሆይ ...... ( ሻህራዛድ በአንድ ሺህ አንድ ሌሊት ውስጥ ተረቶቹን ለንጉሱ የምትተርክለት ንግስት ናት) ሻ ነብሴ እያለ ይቀጥላል ስብሐት ❷❺ ዛሬ ስነፅሁፍን ወደ ጎን ትተን ሂሳብ እንስራ። ስብሐት + በአሉ= ደራሲው ስብሐት + ዘነበ= ማስታወሻ ስብሐት + አለማየሁ= ህይወትና ክህሎት ስብሐት + 30 ደራሲዎች= መልክአ ስብሐት ስብሐት የነካው ሁሉ ጥበብ ያፈራል። ❷❻ "ጋሽ ስብሐት በደርግ ዘመን እንዴት ኢሠፓ አልሆንክም?" "እኔኮ የቄስ ልጅ ነኝ አንተ ብሽቅ!" "ታድያ እንዴት ሃይማኖተኛ አልሆንክም?" "በእግዚአብሔር የማላምን ኤቲስት ስለሆንኩ ነዋ!" ❷❼ ❝ስብሐት ለምን በእግር ትሄዳለህ?❞ ❝ከንቲባና ደራሲ በእግራቸው ነው መሄድ ያለባቸው። ደራሲ የህብረተሰቡን ኑሮ ህብረተሰቡ መሐል ተገኝቶ ካልተካፈለ ምኑን ደራሲ ሆነው!❞ ❷❽ ስብሐት ስለ ደራስያን ምን ይላል? ማስተርፒስ ወደ አማርኛ ስነፅሁፍ እየመጣች ነው ―ስብሐት ገብረእግዚአብሔር የዘነበ ወላን "ልጅነት" ካነበበ በኋላ ዶስቶቭስኪ ሲፅፍ ዝርክርክ ነበር። በቴክኒክ ረገድ ያልተዝረከረከው ‘ወንጀልና ቅጣት’ ብቻ ነበር። ታድያ ማንበቡ ሲጥምህ እንኳንም ተዝረከረከ ነው የምትለው። ―ስብሐት ስለ ዶስቶቭስኪ በአማርኛ ስነፅሁፍ ውስጥ እንደ አዳም ረታ የተዋጣለት የአጭር ልብወለድ ደራሲ የለም። ―ስብሐት ስለ አዳም ረታ(ልብ ማለት ያለብን ስብሐት አብዛኛዎቹን የአዳም ረዣዥም ልብወለዶች ለማንበብ አልታደለም ካፒታልን ያነበብኩት በደርግ ዘመን መፅሀፉን ወደ አማርኛ እንዲመልስ በተዋቀረው ኮሚቴ አባል ሆኜ ነው። ሰዎች ማርክስ ቤተሰቡን አስርቦ ነው የፃፈው ይላሉ። ፍልስፍናው ሲገባህ አውራጃም በተራበ ነው የምትለው። ―ስብሐት ስለ ካርል ማርክስ አደፍርስን ሳነበው "ሌቱም አይነጋልኝን" በእንግሊዝኛ የተተየበ 65 ገፅ ላይ ደርሼ ነበር። ከዛ በፊት አማርኛ ለስነፅሁፍ ብቁ አይደለም የሚል እምነት ነበረኝ። ዳኛቸው በአማርኛ መፃፍ እንደሚቻል ከሰተልኝ። ―ስብሐት ስለ ዳኛቸው ወርቁ ፍሩይድ ተአምረኛ ነበር። ወደ ራሱ ውስጥ ገብቶ የመረመረ ጂኒየስ ነው። እራሱ በርቶለት የኔንም ውስጤን አበራልኝ። ―ስብሐት ስለ ፍሩይድ በአሉ ጎበዝ አለቃ ነው። ከዛ ቀጥሎ ነው ደራሲነቱን የማደንቀው። በአሉ ባህሪውም መልኩም የስነጽሑፍ ችሎታውም ያማረ ሰው ነበር። ‘አይገኝም እንጂ እንዳማሩ መሞት’ የሚለውን የአንዳንድ ግዜ ህግ ጥሶታል። ―ስብሐት ስለ በአሉ ግርማ በዛኛው አለም አራት የአጭር ልብወለድ ጠበብቶች አሉ። አንደኛው ጊ ደ ሞፓሳ ነው። ሞፓሳ በ43 አመቱ ከ400 በላይ አጭር ልብወለድ ያመረተ ጎበዝ ደራሲ ነበር። ምን ያደርጋል ቂጥኝ በአጭር አስቀረው(ስብሐት ከአይኑ እንባ ዱብ አለ) ―ስብሐት ስለ ጊ ደ ሞፓሳ ፀጋዬ የኛ ዎሌ ሾይንካ ነው። ኦክስፎርድ ድረስ ሄዶ ስነፅሁፋችንን አለማቀፋዊ ያደረገ ደራሲ ነው። ―ስብሐት ስለ ፀጋዬ ዲክንስ የታችኛውን ማህበረሰብ ህይወት ነው የፃፈው። እንደ ሩስያ ስነፅሁፍ እንባ በእንባ ነው የሚያደርግህ። የእንግሊዝ ነገሥታትና ልኡላን ዲክንሰን አነበቡት። ከዛ በኋላ ነው ድሆችን የሚረዳ ድርጅት በእንግሊዝ መቋቋም የጀመረው። ዲክንስ በስነፅሁፉ ጉልበት በሃገር ደረጃ ማህበራዊ ተፅእኖ መፍጠር የቻለ ታላቅ ደራሲ ነው። ―ስብሐት ስለ ቻርልስ ዲክንስ ኃይለመለኮት መዋእል ‘ጉንጉን’ ውስጥ አማርኛን ከነለዛዋ ከነማእረጓ ፅፎ አስደነቀኝ። ደግሞም ኃይለመለኮት ብእሩ ብቻ ሳይሆን አንደበቱም ርቱእ ነው። ―ስብሐት ስለ ኃይለመለኮት ፕሩስት አይሁድ ነው። የፈረንሳይ አይሁድ። ጂንየስ ነው። አይሁድ መሆን ጂኒየስ ያደርጋል መሰለኝ። ሰባት ልብወለድ ጽፏል። ስለ ራሱ ነው የፃፈው። በልብወለዱ ውስጥ ያሉት ሁለት መቶውም ገፀባህሪያት ፈረንሳይ ውስጥ በሕይወት ያሉ ሰዎች ናቸው። በፈረንሳይኛ ነው ያነበብኩት። ፈረንሳይኛን እንደሱ የሚያውቅበት ደራሲ የለም። ―ስብሐት ስለ ማርሴል ፕሩስት ጋሽ ሐዲስ አለማየሁ ቆንጆ ስታይል ነው ያላቸው። ተረታዊ አቀራረባቸውን እወደዋለሁ። በአማርኛ የሚፅፉ ቶልስቶይ ልትላቸው ትችላለህ። ―ስብሐት ስለ ሐዲስ አለማየሁ ኒቼ ከዘመናዊ ታላላቅ ፈላስፎች አንዱ ነው። ግማሽ ጎኑ ፖላንድ ነው። በጣም ብሪሊያንት ነበር። ከኤግዚስቴንሽያሊዝም አያቶች አንዱ ነው። ፍልስፍናው በጣም ተፅእኖ ፈጣሪ ነው አሁን ድረስ። ኒቼ የሚጥል በሽታ ነበረበት። በዚሁ ጦስ አብዶ ነው የሞተው። ―ስብሐት ስለ ፍሬድሪክ ኒቼ ከበደ ሚካኤል በዘመናቸው ለነበረ ትውልድ ትክክለኛ ደራሲ ናቸው። ለአሁኑ ትውልድ ግን እንጃ። ምክንያቱም ስራቸው ግብረገብ ይበዛበታል። ቢሆንም መደነቅ ይገባቸዋል። ―ስብሐት ስለ ከበደ ሚካኤል አልቤር ካሙ ጋዜጠኛም ፈላስፋም ደራሲም ነበር። ደግሞም ሰው ነው። ላመነበት ነው የሚኖረው። በእኛ ዘመን ካሙን እና ሳርትርን ያላነበበ ኢንተሌክችዋል ወጣት አልነበረም። ስራቸው ፍልስፍናም ምርምርም ነበር። ―ስብሐት ስለ አልቤር ካሙ ከተርጓሚዎቻችን መሐል ያነበብኳቸው እና የወደድኳቸው ሳህለሥላሴ ብርሃነማርያም፣ ባሴ ሃብቴና መስፍን አለማየሁ ናቸው። በተለይ ባሴ በሲራኖ ትርጉሙ አስደንቆኛል። ―ስብሐት ስለ ተርጓሚዎች ገተ የጀርመን የስነጥበብና የባህል አባት ነው። በአውሮፓ የመጀመሪያውን ሮማንቲክ የሆነ አብይ ልብወለድ የፃፈው ገተ ነበር። ፎስት ይባላል። ፎስት የታወቀ የጀርመን ሌጀንድ ሲሆን ገተ በስነፅሁፍ ህያውና ዘለአለማዊ አድርጎታል። ―ስብሐት ስለ ዎልፍጋንግ ገተ

እንግዲህ ምቀኛው ፣ አሻጥረኛው ጋሽ ስብሐት መሆኑ ነው። ስብሐት ይህን አነበበ። ከዚያ በኋላ ተቀየረ። ከዚህ በኋላ ስብሐት ለጀማሪ ደራሲዎች እውነተኛ ስሜቱን መንገር አቆመ። የሚፅፋቸው አስተያየቶች እንዲህ ያሉ ሆኑ፦ "እስከአሁን እንዲህ አይነት ድንቅ ልብወለድ አልተፃፈም፤ ወደፊትም አይፃፍም።" "ቁንጮ የልብወለድ ስራ ነው።" "የስነጽሑፍ አድባር ተወለደ" ⓱ አንድ ድሮ ያነበብኩት የስነ ልቦና መፅሀፍ እንዲህ ይላል፦ " ሰዎች በሚያወሩበት ወቅት ከሚያስተላልፉት መልእክት ፣ በንግግር/በቃላት የሚገልፁት ሐያ ፐርሰንቱን ብቻ ነው" እንግዲህ የቀረው ሰማንያ ፐርሰንት፣ የፊት ገፅታ፣ የአካል አቋም፣ የእጅ እንቅስቃሴ ወዘተ ይሸፍናሉ ። ታዲያ ይሄ 20/80 ጉዳይ ትኩሳትን ብሎም ባህራምን አስታወሰኝ። ባህራም የፋርስ፣ ስብሐት ደግሞ የአቢሲኒያ ሰዎች ናቸው። ያገናኛቸው ፈረንሳይ ፣ የሚያግባባቸው ፈረንሳይኛ ነው። ታዲያ የባህራም ፈረንሳይኛ የተሰባበረ ነው። በእርግጥ ከጃምሺድ ይሻላል። የባህራም የቋንቋ ችግር የትምህርት ውጤቱ ላይ እንኳን ጥላውን እያጠላበት ፣ ባህራምን ሲያበሳጨው እናነባለን። ነገር ግን ይህ የቋንቋ ችግር፣ ስብሐት የባህራምን ትልቅ ነፍስ ከማየት አላገደውም።ስብሐት ይህንን በተመለከተ እንዲህ ይላል፦ " አንድ ሰው ከሚናገረው ነገር ተነስቶ ስለ አእምሮው ብቃት መናገር ይቻላል። ስለ ነፍሱ ለማወቅ ግን የአካል እንቅስቃሴውን፣ ፈገግታውን ፣ የአይን መርገብገቡን ወዘተ ማየት ያበቃል።" ባህራም ኩሩ፣ በራሱ የሚተማመን ፣ ሩህሩህ መሆኑን ለመረዳት ለስብሐት ምንም አላገደውም ፤ ነፍስ ለነፍስ ተግባብተዋል! ከሰው ስታወጋ የሚነግርህን ትተህ የማይነግር ህን ስማ ይላል አንድ ጥንታዊ ምሳሌ። ⓲ ደራሲዎች ለብዙ ምክንያት ሊፅፉ ይችላሉ። ለምሳሌ ዝናን ለማግኘት ፣ እንጀራ ለመብላት ፣ ማህበረሰቡን ለመጥቀም፣ አመለካከታቸውን ለሚሊየኖች ለማካፈል ወዘተ እውነተኛ ደራሲ ግን የሚፅፈው ድርሰት እንደ መተንፈስ ሁለተኛ ተፈጥሮው ስለሆነ ነው። ዝናንም ባያገኙ ፣ አንጀራም ባያበላቸው መፃፋቸውን አያቋርጡም። ባይታተሙም ይጽፋሉ። ስብሐት ገብረእግዚአብሔር ለ30 አመት ሳይታተም ቢቆይም መጻፉን አላቋረጠም። አብዛኛዎቹ ታዋቂ የኢትዮጵያ ደራስያን የሚፅፉት ተፈጥሯቸው ስለሆነ ይመስለኛል። በድርሰት እንጀራ የሚበሉት እንኳን የሚፅፉት በውስጣቸው ካለው መነሳሳት ነው ብሎ ደፍሮ መናገር ይቻላል። መፃፍ እንደ መተንፈስ ሕይወታቸው ነበር። ለዛም ነው የተዋጣላቸው ደራሲ የሆኑት። ድርሰት እንደሚያርስ ገበሬ አይደለም። ገበሬው የሚያርሰው ለመብላት ነው። ከግብርና የተሻለ ስራ ቢያገኝ ግብርናውን ይተዋወል። ማረስ ቢተው መኖሩ አይቋረጥም። ህይወት በሌላ መስክ ይቀጥላል። ደራሲን መመሰል ካለብን ግን ከእናት ጋር ነው። ደራሲ በአእምሮው ሃሳብ ይፀንሳል። በግዜ ሃሳቡ ጎልምሶ አድጎ ልጅ ሆኖ ወረቀት ላይ ይወለዳል። አንድን እናት ለምን ትወልጂያለሽ ብለን አንጠይቅም። ለደራሲም እንዲሁ። ደራሲነት የእድሜ ዘመን ተፈጥሮ ነው። እናት ልጇን ያለ ልክ እንደምታፈቅር ደራሲም ለድርሰት ያለው ስሜት መጠንየለሽ ነው። ⓳ የስም ነገር ስብሐት ገብረ እግዚአብሔር ባህር ማዶ ሄዶ ለሚያርፍበት ሆቴል እንግዳ መቀበያ ፓስፖርቱን ይሰጠዋል። ስሙ Sebhat Gebre Egziabher ነበር የሚለው። ሪሰፕሽኒስቱ በሃገራቸው እንደተለመደው(Given name/middle name/surname) በsurname "Mr Egziabher?" ብሎ ጠራው። "Yes" አለ ስብሐት በአፉ። በልቡ ደግሞ ወቸው ጉድ ሰው ሃገር መጥቼ እግዚአብሔር ሆንኩ! ⓴ በሃገራችን ስነፅሁፍ ውስጥ እንደ ስብሐት ገብረእግዚአብሔር እና ዘነበ ወላ ያለ ጓደኝነት አልተመሰረተም። ከዚህ ጓደኝነት ውስጥ ታላቁ ማስተርፒስ "ማስታወሻ" ተወለደ። ስብሐት እና ዘነበ የተዋወቁባት ቀን የተባረከች ናት። የተዋወቁት ሁለቱም የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት በሚሰሩበት ወቅት ነበር። ማንም አጨባብጦ አላስተዋወቃቸውም። መጀመሪያ የአንገት ሰላምታ መለዋወጥ ጀመሩ። ቀጥለው ሻይ ቡና መገባበዝ ጀመሩ። ጓደኞች ሆኑ። ስነፅሁፍ ይበልጥ አቀራረባቸው። ግንኙታቸው አንዳንዴ የአባትና የልጅ፣ የጓደኛማቾች ወይም የአስተማሪና የተማሪ ሆኖ ይቀያየራል። ሲያወሩ ሲያወሩ ይሄ ታላቅ መፅሀፍ ተወለደ። ስለ ስብሐት ሳስብ ሁሌ የሚገርመኝ ነገር አለ። ስብሐት ከበአሉ ግርማ፣ ከጸጋዬ ገብረመድህን ፣ ከደምሴ ፅጌ፣ ከተስፋዬ ገሰሰ፣ ከሰለሞን ደሬሳ፣ ከአስፋው ዳምጤ፣ ከአለማየሁ ገላጋይ ብቻ ከሁሉም ጋር ጓደኛ ነበር። ከማንም ጋር ከማይግባባው ከዳኛቸው ወርቁ ጋር እራሱ የጠበቀ ወዳጅነት ነበረው። ከድርሰቱ አለም ውጪም ቢሆን ስብሐት የሁሉም ጓደኛ ነበር። ምክንያቱም ስብሐት ሰው ነበር። የዚህ ሰው ነፍስ የታላቅ ደራሲ ብቻ ሳይሆን የታላቅ ሰውም ነበር። ❷❶ ሶቅራጥስ እንዲህ አለ፦ "አግባ! ጥሩ ሚስት ካገኘህ ደስተኛ ትሆናለህ። ጨቅጫቃ ሚስት ከገጠመህ እንደኔ ፈላስፋ ትሆናለህ" ደራሲ በጣም ፕራይቬሲ ይፈልጋል። ግዜ ይፈልጋል፤ ፀጥታ ይፈልጋል። ያ ደግሞ ትዳር ላይ አይገኝም። ትዳር እና ደራሲነት በጣም የሚራራቁ፣ የማይጣጣሙ ነገሮች ናቸው። ደራሲ ወይ ሚስት/ባል ያገባል ወይ ድርሰትን ያገባል። ስብሐት ሁለቴ አግብቷል። በመጀመሪያ ጥሩ ሚስት ገጠመው—ሀና ደሬሳ። ስነፅሁፍ የምታውቅ የምትረዳ የምታደንቅ―"የኔ ድንቅ ደራሲ" ብላ የምትክበው። ደስተኛ ነበር። ነገር ግን በሌላ ምክንያት ሃገር ጥላ ኮበለለች። ስብሐት ሁለተኛ ሚስቱ ጨቅጫቃ ናት―እንደ ሶቅራጥስ ፈላስፋ የምታደርግ። ስብሐት በቤቱ ነፃነት የለውም፤ ፀጥታ የለውም፤ ሰላማዊ ሁኔታ የለውም። ተረጋግቶ መፃፍ አይችልም። በዚህም ይበሳጫል። ፍልስፍና ከስቃይ ጥግ የሚወለድ ማደንዘዣ ይሆን?! አግባ! ወይ እንደ ስብሐት ደስተኛ ትሆናለህ ወይም እንደ ስብሐት ፈላስፋ ትሆናለህ!!! ❷❷ ስብሐት በልጅነቱ አንድ ሰው ገጥሞት ነበር። ለሰውዬው አድናቆትም፣ ንቀትም ነበረው። አያችሁ ሰዎች ውስብስብ ናቸው። ነጭና ጥቁር ብቻ ብላችሁ የማትገልጿቸው ናቸው—በመሀል ግራጫ አለ። አብዛኛዎቻችን ግራጫ ነን። እና ሰውዬውን በሆነ ምክንያት እጅግ ያደንቀዋል፣ በሌላ ምክንያት ደግሞ ይጸየፈዋል። ሁለቱንም አብረን እንይ፦ ሰውዬውን አደንቀዋለሁም እንቀዋለሁም። ከማደንቀው ልጀምርልህ። በጣልያን ወረራ ዘመን ነው። 13 አመት ቢሆነው ነው። የኢትዮጵያን ባንዲራ አልቀድም ብሎ ጣልያናውያንን አስቆጣ። ገና በ13 አመቱ በጣልያኖች እጅ ብዙ መከራ ተቀበለ። በዚህ በጣም አደንቀዋለሁ። እንድንቀው ያደርገኝ እሱ ራሱ አዋቂ ከሆነ በኋላ ለልጆች ያለው አመለካከት ነው። እሱ "ልጅና ጫማ ወደ አልጋ ስር" ከሚሉት ወገን ነው። የልጆችን ነፃነት አያከብርም። ለሱ ልጅ ማለት የአዋቂዎችን ፈቃድ የሚፈፅም ማሽን ነው። ❷❸ የዋህነት በልጅነት ስብሐት የገጠሩን ኑሮ አይወደውም ነበር። ጠዋት በግዜ ተነስቶ የከብት ጭራ እየተከተለ መጠበቅ አለበት። ሁሌ ጠዋት እንቅልፉን ሳይጨርስ መነሳት አለበት። ታዲያ የስብሀትን ስንፍና የሚያውቁት እናቱ አደይ መአዛ እንዲህ ብለው መከሩት፦ "አዲሳባ ከሄድክ በግዜ መነሳት አይጠበቅብህም። የምቾት ሃገር ነው"

ዘነበ ወላ ስለ ስብሐት የንባብ ልምድ ብዙ ከነገረን በኋላ አንድ ሰው እንዴት ይህንን ያህል ሊያውቅ ይችላል ብሎ ይደነቃል። ነገር ግን ይላል ዘነበ ነገር ግን እንደማንኛውም ሰው ጋሽ ስብሐት ምንም የማያውቃቸው ርእሰ ጉዳዮች አሉ። ያኔ መላ ሰውነቱ ጆሮ ይሆናል። ስብሐት በራሱ አንደበት ደግሞ እንዲህ ይለናል፦ "አሁን ያልንበት ዘመን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ዘመን ነው። በዚህ ረገድ እኔ የተሟላ አላዋቂ ነኝ" ይቺ የስብሐት አባባል አንድ ቁምነገር ትከስትልናለች። ጋሽ ስብሐት 7000 መፅሀፍት ጭው አድርጎ እንደጠጣ ይነገርለታል። ታዲያ ምንም ያህል ብታነብ ከእውቀት ውቅያኖስ በማንኪያ ብትቀምስ ነው። እንደውም ብዙ ባወቃችሁ ቁጥር ምንም እንደማታውቁ ነው የሚገለጥላችሁ። ለዚህ አይደል ሶቅራጥስም የማውቀው አለማወቄን ነው ያለው!!! ⓮ አርትኦት ጋሽ ስብሐት በአንድ ወቅት ስለ አርትኦት እንዲህ ብሎ ነበር፦ "እስቲ መፅሀፍ ቅዱስን ተመልክቱ። አለምን ያጥለቀለቀው አርትኦት ስላልተደረገ ነው። በቢሊየን ቅጂዎች በሺህ ቋንቋዎች ተተርጉሞ በየቤታችን ይገኛል። ቀላል ምሳሌ ልስጣችሁ። እግዚአብሔር ዳዊትን እንደልቤ ይለዋል። ዳዊት ግን የጦር አዛዡን ኦርዮንን ሚስት ቤርሳቤህን ለመተኛት ሲል በጦር ሜዳ ፊት ለፊት ተሰልፎ እንዲሞት አድርጎታል። መፅሀፍ ቅዱስ ይህንን ሳይጨምር ሳይቀንስ አስፍሮታል። እውነቱ ሳይቀባባ ሳይጠለሽ እንደወረደ ከሺህ አመታት በፊት ተፃፈ። ይኸው እስከአሁን ቢሊየኖች ያነቡታል። የእልፍ አእላፋት የሕይወት መመሪያ ነው። እስከአሁን ድረስ ለማመን የሚከብዱን የመፅሀፍ ቅዱስ እውነቶች አሉ፦ የአዳምና የሄዋን የእግዚአብሔርን ትእዛዝ ጥሰው የተከለከለችውን ፍሬ መብላት፣ የቃየን ወንድሙን አቤልን ደም ማፍሰስ፣ አብርሃም ልጁን ይስሃቅን ለመስዋዕትነት ማቅረብ፣ ኤሳው ብኩርናውን በምስር ወጥ መሸጥ፣ ያእቆብ ራሄልን ለማግባት 14 አመታት ላባን ማገልገል፣ ዮሴፍ በ30 ብር ለግብጾች መሸጥ፣ ሙሴ ቀይ ባህርን ከፍሎ እስራኤላውያንን ማሻገር ፣ የኢዮብ ትእግስት የሰለሞን ጥበብ፣ የክርስቶስ ፍቅርና ተአምራት ፣ የይሁዳ አሳልፎ መስጠት፣ የጴጥሮስ ክህደት፣ የቶማስ ጥርጣሬ ብዙ ብዙ። ሁሉም ኤዲት አልተደረጉም፤ አልተከለሱም። የብዙዎችን ልብ ለማሸነፍ፣ አእምሮ ለመግዛት የሚያስፈልገው ጥበብ የነጠረ እውነት ነው። ከእውነት የበለጠ ውበት የለም። በአስቀያሚ እውነት ውስጥ እንኳን ውበት አለ። ምክንያቱም እውነት ምንም ያህል ቢደበቅ በመጨረሻ ነጥሮ ይወጣል። እውነት ልትመነምን ልትኮሰምን ትችላለች እንጂ አትሞትም።" በመጨረሻ ስብሐት ሲያጠቃልል የመፅሀፍ ቅዱስ ታላቅነት የሚመነጨው ከእውነተኛ ሰነድነቱ ነው። ሌላ ምሳሌ ከጋሽ ስብሐት። ጋሼ በ60ዎቹ ሶስት ተፈጥሮአዊ ልብወለዶች ፅፏል―ሌቱም አይነጋልኝ፣ ትኩሳት፣ ሰባተኛው መልአክ። ያውም በ60ዎቹ ያውም ኢትዮጵያ ውስጥ! ስብሐት እንደማይታተም ያውቅ ነበር። ግን ለገዛ ስሜቱ ፃፈው። ግዜ አለፈ። አዲስ ቀን መጣ። በ90ዎቹ ደምሴ ፅጌና ጥቂት የስብሐት ጓደኞች ሶስቱን ልብወለዶች አለዘቡት። የሚቆረጠውን ቆርጠው የሚተወውን ትተው አሳተሙት። ስብሐት በሕይወት ዘመኑ ይታተማል የሚል እምነት አልነበረውም። በልጅ ልጆቼ ዘመን ታትሞ ጥቂት ፍራንክ ያገኙበታል የሚል እምነት ነበረው። ግን ለዝቦ ታተመ። አንባቢው አመዱ ቡን አለ። ደነገጠ። ስብሐት በጓዳ የማይደረገውን አልፃፍኩም አለ። ይግረማችሁ ተብሎ ከጥቂት አመታት በኋላ ሳይጨመር ሳይቀነስ እንደወረደ ታተመ። የስብሐትን ብእር ራቁቱን አየነው ያለ አርታኢ ቀለም። ለጥሬ አንባቢ ፖርኖግራፊ ሲሆን ለነቄ አንባቢ ቁምነገር ነው። አልጋ ላይ የሚደረገው ነገር "ተራ ብልግና" ሳይሆን የሕይወታችን ዋነኛ አካል፣ የደስታ ምንጭ፣ የትውልድ አስቀጣይ ነው። ስታደርገው ያላሳፈረህ ስታወራው ምኑ ከበደህ። ስብሐትን ባለጌ የሚለው ግብዝ ነው። በአደባባይ እየተቹት በስውር የሚያነቡት ደግሞ እጥፍ ግብዝ ናቸው። ቅልብጭ ያለውን እውነት ቁልጭ አድርጎ ስለፃፈ ተወዳጅነቱን ሊቋቋም አልቻሉም። አርትኦት ያልተደረገ የነጠረ እውነት ጉልበቱ ይሄን ያህል ነው። ወደ አርትኦቱ ጉዳይ ልመለስ። አርትኦት አስፈላጊ ነገር ነው። ጥሩ አርታኢ የአንድን የስነጽሑፍ ስራ በቋንቋ በገለፃ በስታይል በቅርፅ በሰዋሰው ከፍ ሊያደርግ ይችላል። ይዘቱን መከርከም ሲጀመር ግን የስነጽሑፍ ሞት እየፈፀመ ነው። ይዘቱ የደራሲው ነው። የራሱን ይዘት ማስረፅ የፈለገ አርታኢ የራሱን መፅሀፍ መፃፍ አለበት። የመፅሀፍ ይዘት የደራሲው ነፍስ መስታወት ነው። በአርትኦት ስም ይዘቱን መቀየር መስታወቱን መስበር ነው። በተሰባበረ መስታወት የሚታየው ምስል ደግሞ የተበታተነ ነው። አርታኢ ልክ እንደ መንፈስ መሆን አለበት። መኖሩ የማይታይ ግን የሚሰማ አላማውም የስራው ባለቤት ደራሲው ደምቆ እንዲወጣ ማድረግ እንጂ እንዳይሸፈን ነው። ⓯ ስብሐት በአሜሪካ ጋሽ ስብሐት በ70ዎቹ ላይብረሪ ሳይንስ ለማጥናት ወደ አሜሪካ አቅንቶ ነበር። የታዘበውን እነሆ፦ ፨ ገና ከአውሮፕላኑ ወርዶ ተርሚናሉን ሲመለከት ተደነቀ። ብዙ ሚሊየኖች እንደወጣበት ያስታውቃል አለ ለራሱ። ሰዎቹ ግን አይተያዩም፤ በፊታቸውም ፈገግታ የለም። ሃብታም ሮቦቶች ሆነዋል ብሎ አዘነ። ፨ ስብሐት በዲትሮይት ከተማ ተቀብለው ያስተናገዱት ነጭ አሜሪካኖች ነበሩ። እናት የስነጥበብ ምሩቅና ድምፅዋም እንደ ወፍ ዝማሬ የጣመ ነበር። ግን እሷን የሚሰማት የለም። አባትዬው ደግሞ ትልቅ የመኪና ፋብሪካ ውስጥ የሚሰራ ሜካኒካል ኢንጂነር ነበር። የሚያወራው ስለ ሞተር ስለ ፈረስ ጉልበት ምናምን ነበር። ስብሐት ሰለቸው። ከወወክማ እርካሽ አልጋ ተከራይቶት ቤቱን ለቆ ወጣ። ፨ አንዱ አሜሪካዊ የስብሐት ጓደኛ ስልክ ለመደወል ዝርዝር ሳንቲም ስላልነበረው ከስብሐት አስር ሳንቲም ተበደረ። ታድያ ከብዙ ቀናት በኋላ አስታውሶ ያቺን አስር ሳንቲም እንካ አለው። ስብሐት በጣም ተደነቀ። እሱ ጭራሽ ረስቶታል። ከዚህ በኋላ እኛና እነሱ ገንዘብን በእኩል እንደማናይ ተረዳሁ ይላል። ፨ አንዱ አሜሪካዊ ሲያወራው እንዲህ አለው፦ "ሳሎን ቤት አንድ ቲቪ አለን፤ ዋናው መኝታ ሌላ ቲቪ አለን። አሁን ለልጄ መኝታ ቤት አንድ ቲቪ ለመግዛት ኦቨርታይም እየሰራሁ ነው" በመጨረሻ ስብሐት የአሜሪካኖች የቁስ ፍቅር እንዳሳዘነው ይገልፃል። ⓰ አንዱ ልብወለድ ፅፎ ጋሽ ስብሐት ጋር ይመጣል። "እዪልኝ እስቲ" ጋሽ ስብሐት ግዜ ወስዶ በደንብ አነበበው። "ጥሩ ነው። ግን ገፀባህሪያቱ በደንብ አልተሳሉም። ታሪኩ ተአማኒነቱ ይጎድለዋል። ሴራው ወንፊትነት አለው። ጭብጡ ግልፅ አይደለም" ብሎ የተሰማውን ነገረው። ደራሲው ጬሰ። እዚህ ጋር ስብሐት እንዲህ ይለናል፦ "ደራሲዎች ለራሳቸው የተጋነነ ግምት አላቸው። እራሳቸውን እንደ ፈጣሪ ነው የሚቆጥሩት። ፈጣሪ ደግሞ ለትችት ክፍት አይደለም" ደራሲው ለመስማት የጠበቀው ሌላ፤ የሰማው ሌላ። እራሱን አዘጋጅቶ የመጣው አድናቆት ለመስማት ብቻ ነበር። የልብወለዱን ረቂቅ ከስብሐት ላይ አመናጭቆ ተቀበለው። ከጥቂት ወራት በኋላ ልብወለዱ ምንም ማሻሻያ ሳይደረግበት እንዳለ ታተመ። ደራሲው አንድ ቅጂ ለስብሐት ላከለት። ከጀርባ ሽፋኑ ላይ እንዲህ ይላል፦ "ይህ ምርጥ ልብወለድ በአንዳንድ ምቀኞች የትችት አሻጥር ቢደረግበትም የስነጽሑፍ አማልክት ፈቅደው ለመታተም በቅቷል"

"ይቺን የመሰለች ልጅ ብቻዋን ትተህ ከሽማግሌ ጋር ምን ትሰራለህ? በል አሁን ተነስተህ ሂድና ሸኛት" ዘነበ ታዘዘ። ❽ በአንድ ወቅት አንዱ ስብሐትን ይጠጋውና "ጋሽ ስብሐት ጽሁፎችህ ተወዳጅነት አላቸው። በተለይ ወጣቶች በብዛት ያደንቁሃል። ለምን መጽሀፍትህን ሁሉም በነፃ የሚያገኙበትን መንገድ አናመቻችም?" ስብሐት "በጣም ደስ ይለኛል" ልጁ ደስታውን ከፊቱ ላይ ለመደበቅ እየታገለ፦ "በቃ ስራዎችህ የህዝብ እንዲሆኑ የሚያስፈልገውን የህግ ሰነድ አርቅቄ እመጣለሁ" ከጥቂት ቀናት በኋላ ልጁ ከሰነዱ ጋር ወደ ስብሐት መጣ። ስብሐት ሰነዱን ተቀብሎ በሚገባ አነበብ። ሃሳቡ ሲጨመቅ ስብሐት የፃፋቸውን ሁሉም ልብወለዶች እንዲሁም ለዘመናት የከተባቸው እልፍ መጣጥፎች ባለቤትነት በፍቃዱ ለአንድ አሳታሚ ድርጅት ማስተላለፉን ይገልፃል። ልጁ የአሳታሚ ድርጅቱ ባለቤት ነው። ስብሐት በሰነዱ ላይ ያሉትን ሁሉንም መጠይቆች ሞላ። ስም አድራሻ የመሳሰሉትን። በዚህ መሐል ልጁ ምራቁ እየተዝረበረበ ነው። በአእምሮው ምንም ሳይሰራ የሚያገኘውን ገንዘብ እያሰላ ነው። ይህንን ከሰማይ የወረደለትን መና እየቆጠረ ነው። ከሰከንዶች በኋላ ያልለፋበት ብዙ ሺህ ብር ኪሱ ይገባል። ስብሐት በተረጋጋ ስሜት ሁሉንም መረጃ ሲያስገባ ከቆየ በኋላ ልክ የፊርማው ቦታ ሲደርስ ይህንን በአማርኛ ፃፈ፦ "FUCK YOU" ❾ ጋሽ ስብሐት ለአንድ የጋብቻ ሽምግልና ከሌሎች ሶስት ጎልማሶች ጋር ወደ ልጂቱ ቤተሰቦች ቤት ይሄዳል። በሩ ተከፍቶላቸው ወደ ሳሎን ገቡ። የልጅቷ አባት ቆመው እየጠበቋቸው ነበር። ታድያ ሌሎቹ ምንም ነገር ከመናገራቸው በፊት ስብሐት ተሽቀዳደመና "ይኸውሎት ልጁ እና ልጅቷ ተነጋግረው ጨርሰዋል። እኛ ምንም የምንጨምረው የምንቀንሰው ነገር የለም። ስለዚህ ለምን ሌላ ነገር አንጫወትም" ሰውዬው ስብሐትን ያውቁት ስለነበር እንደመሳቅ አሉና እሺ ብለው በምግብ እና በመጠጥ እያዋዙ ሌላ ሌላውን ሲጫወቱ መዋላቸውን አንብቤያለሁ። ❿ አንድ አስገራሚ የስብሐት ባህሪ ለንባብ ቦታ አይመርጥም―ፌርማታ ላይ ፣ ታክሲ ውስጥ ፣ ሰው በተሰበሰበበት አደባባይ ብቻ የትም ይሁን ለማንበብ አይገደው። መለያው የሆነችው የስብሐት ፌስታል የምታስፈልገው ለዚህ ነው። በየትኛውም ቦታ ሊያነብ ስለሚችል እያነበበው ያለውን መፅሀፍ በፌስታል ሸክፎ የትም ይዞ ይሄዳል። መጽሐፉ ዳጎስ ያለ ከሆነ ይገነጥለውና አንብቦ ሲጨርስ ደንበኞቹ እንደ አዲስ ይጠርዙለታል። ስብሐት ከንባብ ሌላ የሚወደው አረቄ ነው። አረቄውን በውሃ እያወራረደ ነበር የሚጠጣው። ከእለታቱ በአንድ ቀን መጽሐፉን በፌስታል ሸክፎ አረቄ ቤት ተገኘ። አንድ ሁለት መለኪያ እንደቸለሰ መጽሐፉን ከፌስታሉ አውጥቶ ንባቡን ተያያዘው። የአረቄ ቤቱ ባለቤት ድምፅ ግን ከንባብ ተመስጦው አናጠበው፦ "አንቱ! የደብተራ መፅሀፍ ይዘው በቤቴ አይድገሙብኝ" ከስብሐት ጋር የነበሩት ወዳጆቹ "ጋሽ ስብሐት ናቸው" ብለው ሲሉ ሴትዮዋም ቀበል አድርገው "ውይ እሳቸው ናቸው እንዴ! ለእሳቸውስ ችግር የለም" ብለው የማርያም መንገድ ሰጥተዋል። እንግዲህ ሴትዮዋ ጋሽ ስብሐትን በዝና ብቻ ነበር የሚያውቃቸው። ይህም ስብሐትን አረቄ ቤት እንዲያነብ ፍቃድ የተሰጠው ብቸኛ ዜጋ ያደርገዋል። ⓫ ስብሐት ስለ ጣልያኖች ለሃገሬ የምመኝላት ስልጣኔ የጣልያንን ነው። ጣልያናውያን ይበላሉ፣ ይጠጣሉ ይደሰታሉ። መንገድ ላይ ብታገኛቸው ደማቅ ፈገግታ ይለግሱሃል። ቁስ አምላኪ አይደሉም። ደግሞም ድሃ አይደሉም። በቂ ሃብት አላቸው። ስብሐት ስለ ፈረንሳውያን ፈረንሳይ የአለም የስነጥበብ ማእከል ነች። ፓሪስ የጥበብ ዋና ከተማ ናት። ጠቢበኛ ለመሆን በፓሪስ በኩል ቢያንስ አንዴ ማለፍ አለብህ ይባላል። ፈረንሳውያን ፍቅር ያውቃሉ። ደግሞም ለራሳቸው የተጋነነ አመለካከት አላቸው። ፍሬንች ኪስና ፍሬንች ፍራይስ ከፈረንሳይ ለአለም የተበረከቱ ስጦታዎች ናቸው። ስብሐት ስለ አሜሪካውያን አሜሪካ ገብቼ ከአውሮፕላኑ እንደወረድኩኝ አየር ማረፊያውን ስመለከተው ብዙ ሚሊየን ዶላር እንደወጣበት ያስታውቃል። አሜሪካውያን ግን እርስ በእርስ አይተያዩም። በፊታቸው ፈገግታ የለም። ደግሞም በጅምላ ቁስ አምላኪ ናቸው። ⓬ ስብሐትና ገንዘብ ስብሐት ሲሰጥ ፩) አንድ ቀን ስብሐት ከጓደኞቹ ጋር ሰብሰብ ብለው ሊበሉ ይሁን ሊጠጡ እየሄዱ ነው። ለቆይታቸው ድምቀት የሚሆነውን 50 ብር የያዘው ጋሽ ስብሐት ነው። በመንገዳቸው በጣም የቸገረው ሰው አጋጠማቸው። ስብሐት አላመነታም። ያቺን 50 ብር ከኪሱ አውጥቶ ሰጠ። ጓደኞቹ ተበሳጩበት፦ "እኛስ?" "ለኛ ደግሞ አማልክቱ ይልኩልናል" ብሎ አበረዳቸው። ፪) ስብሐት ደሞዝ የተቀበለ ቀን በመጀመሪያ ዱቤዎቹን ይከፍላል―የሱቅ፣ የመጠጥ የመሳሰሉት። ሰፈር ሲደርስ ለለማኞቹ እጁን በሰፊው ይዘረጋል። ቤቱ ሲገባ ባዶ ኪሱን ነው። ታድያ ገንዘብ አያያዝ ስለማይችልበት ከወር ወር እንደተቸገረ ነው። ስብሐት ሩህሩህ ነፍስ ነው። አለም ደግሞ ለሩህሩሆች ጨካኝ ናት፤ ለጨካኞች ደግሞ ሩህሩህ! ስብሐት ሲቀበል ፩) በአንድ ወቅት ስብሐት ተቸገረ። ለአንድ አመት አንድ ወር ፈሪ ስራ አልነበረውም። ዳኛቸው ወርቁ ወዳጁ ነው። ቀጥታ እሱ ጋር ሄደና እንዲህ አለው፦ "ስራ የለኝም። እስከማገኝ ድረስ በየወሩ አንተ ጋር እመጣለሁ። 50 ብር ታበድረኛለህ" ዳኛቸው ተስማማ። በስምምነታቸው መሰረት በየወሩ ዳኛቸው ስብሐትን ምሳ ይጋብዘውና 50 ብር ሰጥቶ ይሸኘዋል። በዚሁ አይነት 11 ወር ዘለቁ። ስብሐት ስራ አገኘ። ደምወዙን እንደተቀበለ ዳኛቸው ጋር መጣ። "ካበደርከኝ ገንዘብ ግማሹን እነሆ" አለው። ዳኛቸው ተቆጣ፦ "በእኔና አንተ መሐል ብድር የለም" ስብሐት መልሶ፦ "ዛሬ ካልተቀበልከኝ ሌላ ግዜ ሲከፋኝ መምጣት አልችልም" ዳኛቸው ሳይወድ በግዱ ብሩን ተቀበለ። ፪) በሰማንያዎቹ ውስጥ ስብሐት የአዲስ ዘመን አምደኛ ነበር ― እግረ መንገድ። አለቃው ተስፋዬ ገብረአብ ነበር። ለነገሩ ስብሐት የስም እንጂ የግብር አለቃ ኖሮት አያውቅም። በ70ዎቹ በአሉ ግርማ እና ደበበ እሸቱ "አለቃው" ነበሩ። በግብር ግን ስብሐት የራሱ አለቃ ነበር ሁሌም። ስራውን በፍቅር እንጂ በትእዛዝ አይሰራም። ወደ አዲስ ዘመን ልመልሳችሁና ስብሐት ቸገረው። በቀጥታ "አለቃው" ተስፋዬ ገብረአብ ጋር ሄደና እንዲህ አለው፦ "ያለፈውን ወር ደሞዜን ወስጄያለሁ ስለዚህ እሱን ልጠይቅ አልችልም። የመጪውን ወር ደሞዜንም ወስጄያለሁ እሱንም ልጠይቅ አልችልም። ስለዚህ ለምን ሞዴል ሰራተኛ ብላችሁ አትሸልሙኝም " ⓭ ስብሐት ለአብ አንድ ስብሐት በአንድ ወቅት ግእዝ መማር ጀምሮ ነበር። እንግዲህ ልብ በሉ ስብሐት ትግርኛ ይችላል። መቻል ብቻ ሳይሆን አፉን የፈታበት ቋንቋ ነበር። ስብሐት እንደነገረን ደግሞ ግእዝ እና ትግርኛ በቂ ይቀራረባሉ። አብረውት የሚማሩት ደግሞ አይችሉም። ተንቀራፈፉበት። እነሱን መጠበቅ ሲሰለቸው እርግፍ አድርጎ ተወው። ስብሐት ለአብ ሁለት ስብሐት ላይብረሪ ሳይንስ ለማጥናት አሜሪካ ሄዶ ነበር። እሱንም ከሶስት ወር በላይ አልገፋበትም። ለምን? ሲባል ትምህርቱ አሰልቺ ነው። የአሜሪካ ኮንግረስ ቤተመፅሀፍት ስንት ቮልዩም አለው ምናምን ነው። "ይሄ ለኔ ምን ያደርግልኛል?" ግን የስብሐትን ቀለም በደንብ የሚያሳየውና እኔም ሳነበው ያሳቀኝ ምክንያት "የምታስተምረን ሴትዮ ባለሻኛ አሮጌት ናት። አፍንጫዋ ስር ሙስታሽ ያላት። ደበረችኝ"😆 Typical Sebhate ስብሐት ለአብ ሶስት

ልደቴን መላው ኢትዮጵያውያን ነው የሚያከብሩልኝ ምክንያቱም የተወለድኩት ሚያዝያ 27 ነው። —ስብሐት ገብረእግዚአብሔር ነገ ሁላችንም የስብሐት ወዳጆች የአርበኞች ድልን አክብረን ስንመለስ፣ እዚያው ውቤ በረሃ ስብሐት ሐውልት ጋር ተገናኝተን ልደቱን እናክብርለት። ❤️❤️❤️ ታሪኮች ውብ ናቸው። ቁምነገር አይነጥፋባቸውም፣ ለዛ አይጎድልባቸውም፣ ተሰምተው አይጠገቡም። ዛሬም ታሪኮች ጋር ነን። ርእሳችን ጋሽ ስብሐት ነው። ስለ ስብሐት ብዙ ታሪኮች ለመስማት ተዘጋጁ። አንዳንዶች አቦይ ይሉታል። ሌሎች ደግሞ ጋሽ ስብሐት። በጣም የሚቀርቡት ደግሞ ሲቢ፣ ሲቢቲ ይሉታል። ጋሼ ካረፈ ዘንድሮ 2018 አስራአራተኛ አመቱን ይዟል። ለማንኛውም የሚከተሉት ፅሁፎች ባለፉት ብዙ አመታት ስለ ስብሐት የጻፍኳቸው ናቸው። የተፃፉት በተለያየ ድባብ በመሆኑ ስታነቡትም በየአውዱ ይሁን። ረዥም ስለሆነ እያረፋችሁ አንብቡት! ❶ በሁለት መንታ ታሪኮች እንጀምር፦ የመጀመሪያው— አንድ ተቆርቋሪ ነኝ ባይ ስብሐት ጋር ይመጣና “ጋሽ ስብሐት፡ እነ እከሌ እኮ ታዋቂ የሆኑት ከአንተ በወሰዱት ሀሳብ ነው” ቢለው “እስቲ የምትላቸው ሰዎች ሁሉንም ሀሳቦች ወስደው ካልጨረሱ፡ አንተ የቀረውን ወስደህ ታዋቂ ሁን!” ብሎ ተቆርቋሪያችንን ኩም አድርጎታል። ሁለተኛው— አንዱ ደግሞ ይመጣና ስብሐትን ብዙ ጥያቄዎችን ይጠይቀዋል።ስብሐት ጥያቄዎቹን መመለስ ሲጀምር፡ ጠያቂያችን ከአፉ እየቀማ እራሱ መመለስ ይጀምራል።ስብሐት አንድ ሁለቴ ሰማውና ”ሻይ ትፈልጋለህ?“ አለው። ልጁም መስማማቱን ገለጸ። ስብሀት ማንቆርቆሪያውን አንስቶ ብርጭቆው እስኪሞላ፡ ሞልቶም እስኪፈስ ያንቆረቁረዋል።የስብሐትን ጤነኝነት የተጠራጠረው አድራቂያችን ”እንዴ ጋሽ ስብሐት፡ ምን ነካህ?ሻዩ እኮ እየፈሰሰ ነው“ ቢለው ”አንተም ልክ እንደዚህ ብርጭቆ ነህ!በምትጠይቀኝ ጥያቄዎች መልስ ታጭቀህ እየፈሰስክ ነው። እኔን አታድርቀኝ!“ እዚህ ጋር ስለ ስብሐት የሚደንቀኝን ነገር ልንገራችሁ። ማንም የስብሐት አድናቂ ሊተዋወቀው ሲመጣ፣ ስብሐት ታዋቂ ሳይሆን አዋቂ ሆኖ የሚቀርባቸው። የስብሐት ድንቅ ስብእና የሚገለጠው እዚህ ጋር ነው። ስብሐት ሻንጣ ሙሉ አድናቆት በልብህም ሆነ በሻንጣህ ይዘህ ብትመጣለት አይደንቀውም። የሚመለከተውም ያንተን አድናቆት ሳይሆን ነፍስህን ነው። ስብሐት ሁለት ተሰጥኦዎችን የታደለ ስብእና ነበር። አንደኛው በቀላሉ የሰዎችን ስብእና መረዳት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ያለ ይሉኝታ መውደድ አለመውደዱን ፍርጥ አድርጎ መግለጹ ነው። ስብሐት አያመቻምችም፣ አይሞዳሞድም። የውሸት ፈገግታ አይስቅም። ከሌሎች ጥቅም አገኛለሁ ወይም ሌላ አንዳች ጥቅም ይቀርብኛል ብሎ አያስመስልም። ❷ በ1950ዎቹ ስብሀት ላይብረሪ ሳይንስ ለማጥናት አሜሪካን ሐገር ሄዶ ነበር። ታዲያ በአትላንታ ከተማ ዶክተር ሻድለር ከተባለ ግለሰብ ጋር ምሳ ለመገባበዝ ተቀጣጥረው ታክሲ ቢጠብቁ የሚያቆምላቸው ጠፋ፤ በእጅ ምልክት ቢያሳይዋቸውም አልፈዋቸው ይሄዳሉ። በመሐል አንዱ ታክሲ ይቆምና " አትልፉ! ታክሲ አታገኙም! አድማ ላይ ነን!" በዚህን ግዜ ስብሀትና ሚስተር ሻድለር ተመካከሩና መላ ዘየዱ። ዶክተር ሻድለር ቀጥ ብሎ፣ ወደ አንዱ ታክሲ ተጠጋና፣ ወደ ስብሀት እያመለከተ " ይታይሃል እዛጋ የቆሙት! የአቢሲኒያ ንጉስ ቀዳማዊ ሃይለስላሴ ናቸው። ሃገራችንን እንደተራ ሰው መጎብኘት ፈልገው ነው እዚህ የተገኙት።ለኚህ ትልቅ እንግዳ ስትል አድማውን ጣስና ዳውን ዘ ሀች ምግብ ቤት አድርሰን።" በዛን ግዜ ቀዳማዊ ሃይለስላሴ በዝናቸው በአለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቁ መሪ ነበሩ። ባለ ታክሲው ተስማማ። ነገር ግን ሌሎች ባለታክሲዎች እንዳይናደዱብኝ እልፍ ብላችሁ ጠብቁኝ አላቸው ። ባለታክሲው በቃሉ መሰረት ትንሽ ቆይቶ መጣ። ከምግብ ቤቱም አደረሳቸው። ዶክተር ሻድለር ሂሳብ ሊከፍል ሲል ባለታክሲው በፍፁም አለ። እንግዳህ፣ የሁላችንም እንግዳ ናቸው ብሎ ጨመረ። ይሄ ኃይለሥላሴ የሚለው ስም ግን የማይሠራው ተአምር የለም። ስብሃትና ዶክተር ሻድለር ከታክሲው ወርደው ምግብ ቤቱ ገቡ። እዚህ ደግሞ የድራማው ገቢር ሁለት ይቀጥላል ። ዶክተር ሻድለር ልትታዘዛቸው ለመጣችው አስተናጋጅ " ተመልከቺ የኢትዮጵያው ንጉስ ጃንሆይ ሃገራችንን እንደ ተራ ሰው ሊጎበኙ መጡ" አላት። አስተናጋጇም "My goodness! ክብር ይሰማኛል " አለች። በጥሩ ሁኔታ አስተናገደቻቸው። ሊሄዱ ሲሉ ናፕኪን አምጥታ "ታላቁን ንጉስ" ፈርሙልኝ አለቻቸው ። ስብሀትን ጨምሮ ማንም የግዜው ወጣት የሀይለስላሴን ፊርማ ያውቃል። ስብሀት ፊርማውን ፈረመላትና ተያይዘው ወጡ። ቲያትሩም በዚሁ ተጠናቀቀ። ለማንኛውም ስብሀት ምርጥ ደራሲ እና ሰው ብቻ ሳይሆን ምርጥ ተዋናይም ጭምር መሆኑን የተረዳሁበት አጋጣሚ ነው! ❸ ጋሽ ስብሐት እጅግ በጣም ብዙ አድናቂዎች እንዳሉት ይታወቃል — በተለይ ወጣቶች። ስብሐት የወጣቶችን መንፈስ የሚማርክበት ሚስጥር ግልጽ ነው ለኔ። ስብሐት እንደ ብዙዎቻችን በወግ፣ ባህል፣ አጉል ይሉኝታ የተተበተበ አይደለም። ወጣቶች ደግሞ ደማቸው የሚንተከተከተክ፣ መንፈሳቸው የሚፋጅ፣ ባህልና ማህበረሰብ ላይ የሚያምጹ ነፍሶች ናቸው። ይሄኔ ስብሐት ይመቻቸዋል። ስለ ወሲብ ማንንም ሳያፍርና ሳያፍር መጻፉ፣ በኑሮውም ከወጣቶች ጋር እንደ ጓደኛ ተቀራርቦ መኖሩ፣ ነጻ ሰው መሆኑ ብዙ ወጣቶችን ይማርካል። ነገር ግን ስብሐት የገዛ ራሱ አድናቂ እንደሆነ የምናውቀው ምን ያህሎቻችን ነን?! ዘኔ እና ስብሐት የሞቀ ወሬ ይዘዋል። በመሐል ዘኔ አንድ ጥበብ የጠገበ ነገር ይናገራል። ስብሐት በጣም ተደመመ፤ እንዲህም አለ፦ " ይኼንን የተናገረው ሰው ማንም ይሁን ማን በጣም አስተዋይ ነው!" ዘኔ ተገርሞ፦ " ጋሽ ስብሐት ረሳኸው እንዴ! ይኼንኑ እራሱኑ ከጥቂት ወራት በፊት የነገርከኝ እራስህ እኮ ነህ!" ስብሐትም መልሶ፦ "እንዴት ያለሁ ጠቢብ ነኝ" ሳቅበሳቅ 😂😂😂 ❹ ስብሐት እና ፖለቲካ ስብሐት ፈረንሳይ ኤክስ ፕሮቫንስ እያለ "የታህሳሱ ግርግር" ተከሰተ። ኢትዮጵያዊ ጓደኞቹ ሬዲዮ የሙጢኝ ብለው ዜናውን ይከታተላሉ። ስብሐት ጆሮ ዳባ ልበስ ብሎ መጽሐፉን ያነባል። አንዱ ጓደኛው(ተስፋዬ ገሠሠ ይመስለኛል) ተበሳጨና "የሃገርህ ጉዳይ አይደለም? አትከታተልም?" አለው። ስብሐት መጽሐፉን እንደያዘ "ለፖለቲካ ትግል እንኳን ሕይወቴን፣ እንኳን ግዜዬን እንቅልፌን ራሱ መስዋእት አላደርግም።" ብሎ መልሶለታል። ❺ ስብሐት ሁሌ የሚደጋግማት አንድ አባባል አለች።በእርግጥ አባባሏ የዊንስተን ቸርችል ናት። እንዲህ ትላለች፦ "በ20 አመቱ አብዮታዊ ያልሆነ ከ40 አመቱ በኋላ አብዮታዊ ሆነ የቀጠለ ሁለቱም ዴዴብ ናቸው" ስብሐት ጨምሮ ሲያስረዳ፦ "በ20 አመትህ አለምን ለመለወጥ እንደምትችል ታስባለህ፤ ተራራውን ሜዳ የምታደርግ ይመስልሃል፤ ደምህ በለውጥ ስሜት ይንተከተካል። በ40 አመትህ ያ ሁሉ ይቀራል፤ ትሰክናለህ" ❻ ዘነበ ወላ ጋሽ ስብሐትን አንድ ጥያቄ ጠየቀው፦ "ጋሽ ስብሐት ንባብን ለማበረታታት ምን መደረግ አለበት?" (ጋሽ ስብሐት ቱግ አለ ተቆጣ) "ለምንድነው ማበረታታት የሚያስፈልገው? ደራሲው ጎበዝ ከሆነ አንባቢ ራሱ ነው የሚፈጥረው። መኖር ነው ዋናው ቁምነገር" ❼ ስብሐት እና ዘነበ ወላ እየተጨዋወቱ የዘነበ ገርልፍሬንድ መጣች። ዘነበ ሼም ይዞት ብዙም ሳያናግራት ልትሄድ ሆነ። ቻው ብሏት ከስብሐት ጋር ሲቀመጥ ጋሼ በጥፊ ጭው አደረገው፦

ቴዲ በመሬማ ምን እያለን ነው? እውነት ለስደተኛ ልጆቻችን ነው የተዘፈነው ወይስ ለሌላ? . . ልገባው ነው.... ልግባው? . . . ገባሁት . . . አንድ ርእሱን የረሳሁት የአህመዲን ጀበል ቆንጆ መፅሀፍ አለ ("ኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች" ይመስለኛል ካልተሳሳትኩ )። ኢትዮጵያዊያን ሙስሊሞች በኢትዮጵያ እና ከኢትዮጵያ ውጪ ስለመሰረቷቸው ስርወ ንግስቶች ነው የሚያነሳው መፅሀፉላይ። እና መፅሀፉላይ ከተጠቀሱት ስርወ መንግስቶች መሀል በየመን የነበረው በኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች የተመራውና ለሁለት መቶ አመታት ያህል የመንን ያስተዳደረው ስርወ መንግስት አንዱ ነው (ቁጥር ከተሳሳትኩ አርሙኝ አመተምህረቱንም የምታስታውሱ ኮመንትላይ ብታስቀምጡልኝ 🙏 )። ይሄ ማለት የአክሱም ስልጣኔ ቀይባህርን ተሻግሮ የመንን በገዛበት ወቅት ማለት አይደለም። አክሱም ግዛቱ አንሶ አንሶ። ስልጣኔው ወድቆ ከተረሳ በኋላ የመን ውስጥ በቀሩ ኢትዮጵያውያን በራሳቸው ጥረት የተመሰረተ ስርወ መንግስት ነው። በሰአቱ ይሄን ሳነብ በጣም ነበረ የተገረምኩት። ግን ከስርወ መንግስቱ መውደቅ በኋላ እነዛ ኢትዮጵያውያን እንዴት ሆነው ይሆን የሚለው ነገር ቴዲ "መሬማ" ብሎ እስኪዘፍን ድረስ አልተገለጠልኝም ነበረ። እንደ ማንኛውም የመናዊ ዜጋ ሀገራቸው ላይ በሰላም የሚኖሩ ነበረ የሚመስለኝ። በመልካቸው ተለይተው እንደሚገፉ ምንም መረጃው አልነበረኝም። ይሄን ብዙሰዎች የምትጋሩኝ ይመስለኛል። እና ይሄን ካልን ዘንዳ ቴዲ በመሬማ ምንድነው unlock ያደረገው የሚለውን ግጥሞቹን እያየን እንጨዋወትስቲ ዘፈኑ ሲጀምር እንዲህ ብሎ ነው... "ማዶ ባብል የመን በሰንአ ከተማ ውበትሽን እያየሁ ስወጣ ስገባ እንዳፋር አፍሌታ የጠየመው ፊቴን ሌላው ቢቀርንኳን እይው ማንነቴን .....ዞረሽ" የመን ውስጥ ለጥቂት ግዜ የኖረ ኢትዮጵያዊ ይመስላል። ሲወጣ ሲገባ የሚያያት መንገድ ጠራጊ ጥቁር የመናዊት አለች። አንገቷን ደፍታ ስለሆነ የምትጠርገው ሰው ቀና ብላ በሙሉ አይኗ አታይም። ምክንያቱም ጭቁን minority ናት። በገዛ ሀገሯ ማንም እንደሰው አይቆጥራትም። እሷም ቀና ብላ የምትሄድበት ድፍረቱ የላትም። ለዛነው ሲወጣ ሲገባ እያያት እሷግን የማታየው። ለዛ ነው ሌላውንኳ ቢቀር "እንዳፋር አፍሌታ የጠየመው ፊቴን አንዴ ዞረሽ ብታዪው" የሚላት። ምናልባት ቢጤዋን አምሳያዋን ስታይ ደስ ቢላት ሞራሏ ቢነቃቃ ብሎ ይሆናል። ግን መሬማ አታየውም። እሱግን አላየችኝም ብሎ አያልፋትም። ኢትዮጵያዊ አንጀቱ አልችል ብሎት ጠጋ ብሎ ሊያወራት ይሞክራል። ምናልባት ጠቆር ብላ ስላያት ሀበሻ ሳትመስለው አልቀረም። እዚህ ጋር ነው የመኒያ መሆኗንም የሚረዳው። "ላላ አትበይኝ በቃ አይሆንም ጠጋ ብለሽ አውሪኝ እስኪ ያለሽበት ሁኔታውን እያየሽው በትካዜ የምትጠርጊው ጎዳናውን አጎንብሰሽ ስትቆዝሚ ተደግፈሽ መጥረጊያውን አሳዘንሽኝ እኔማ ስንት አለ በሆድሽ መሬማ" እንደ ሀበሻ እህቴ ብሎ በአማርኛ ሊያወራት ሲሞክር በአረብኛ " ላላላ " የተባለ ይመስላል። "እስኪ ያለሽበትን ሁኔታ አውሪኝ መጥረጊያውን ይዘሽ ስትቆዝሚ አሳዝነሽኝኮነው መሬማ" ሲላት መሬማ በአረብኛ "ማነህ ደሞ አታድርቀኝ ስራዬን ልስራበት" ብላው ወደ ስራዋ ትገባለች። በስንት መከራ ያገኘቻትን ስራም በሱ ምክንያት ማጣት አትፈልግማ። ምስኪን መሬማ ታዲያ እዚህጋር ግን በቋንቋ ካልተግባቡ ስሟን በምን አወቀው የሚል ጥያቄ አይፈጥርብንም? አብሽሩ ዘፈኑ ለዚህም መልስ አለው። "ወዲህ አላቃት አቃተኝ ደሞ ላልፋት ስሟን ጠይቄ ብጠራት አትዞር ብከተላት" ስሟን ከሰዎች ነው የጠየቀው። ሁሌ መጥረጊያዋን ይዛ ቆዝማ ሲያያት አካባቢው ላይ ካሉት ሰዎች አንዱን "ያቺ ልጅ ግን ማነው ስሟ?" ብሎ ጠይቆ "መሬማ ናት" ብለውት ነው ሄዶ ሊያናግራት የሞከረው። ግን ለምን ሊያናግራት ሞከረ? ስንል "ወዲህ አላውቃት ግን ደሞ አይቻት ማለፍ አቃተኝ " ይለናል። ወገን ወገን ነው። የራስን ሰው ተቸግሮ እያዩት ማለፍ ይከብዳል። አንድ በኢትዮጵያዊነቱ የሚኮራ ሰው ቢያንስ ጠጋ ብሎ ያለችበትን ሁኔታ ማወቅ ፣ አይዞሽ ብሎ ማፅናናት ይፈልጋል። ለዚህ ነው " ላላ አትበይኝ " እያለ የሚያስቸግራት። ከዛ... "ባያት አምሳያዬን ብጠራት አትሰማ መሬማ መሬማ..... ያ መሬማ" ይላል ለማውራት መግባባት ቢያቅታቸውም ጥላው ስትሄድ መጣራቱን አያቆምም። "ማሬማ...." እያለ ይጣራል። ይሄን ጥሪ ወደ ሀገሩም ተመልሶም የተወው አይመስልም። ከዘመናት በኋላም ጮክ ብሎ "መሬማ...." እያለ ሲጣራ ድምፁ ድንበር ተሻግሮ ቀይባህርን አቋርጦ እስኪሰማ ድረስ ነው። ከወዲህ ማዶ ወደ ባብል ማዶ የተደረገ ወገናዊ ጥሪ ነው። የአለሁልሽ የአልረሳሁሽም ድምፅ ነው። "ኑሮሽ ኑሮሽ እንዴት ነው በሰንአ ከተማ መሬማ.... " የሚለው ጥያቄም በጣም ያሳሰበው ሰው ጥያቄ ነው። ግን ምን ያህል ነው ያሳሰበው ብለን መጠየቃችን አይቀርም ። የዚች ኢትዮጵያዊ ደም ያላት የመናዊት ጉዳት ለሱ ምን ያህል ነው ህመሙ? ስንል እንደተለመደው ከታች መልስ ይሰጠናል። "ሊብናን ቤሩት ካታር ባህሬን ሳኡዲ ዱባይ እንደሚያዝነው ልቤ እህት ወንድሜን ሳይ ባያት አምሳያዬንን ብጠራት አትሰማ መሬማ...." ደሜ ነሽ ወገኔ ነሽ ሲላት እንደማነፃፀሪያ የሚያቀርበው በሌሎች አረብ ሀገራት በስደት የሚንገላቱትን ወንድምና እህቶቹን ነው። ሊብናን ፣ ሳኡዲ ፣ ካታር ፣ ዱባይ ላይ ያሉትን ወገኖቹን ሲያይ ልቡ እንደሚያዝነው ነው እቺን አምሳያውን አይቶ ያዘነው። ከዚህ በላይ ወገንተኝነት አለ? ከዚህ በላይ ድንበር ተሻጋሪነት አለ? ከዚህ በላይ ሀገረመንግስ ግንባታ (Nation Building) አለ? የለም! ይሄ ግዛት የማስመለስ ምኞት አይደለም። ይሄ ቀይባህርን ተሻግሮ ዳግም የመግዛት ህልም አይደለም። ይሄ በታሪክ አጋጣሚ ተቆርጦ ለቀረ ወገን የቀረበ የአለኝታነት ጥሪ ነው። ይሄ የታላቋ ኢትዮጵያ ከራሷ አልፋ ደሞቼ ናቸው የምትላቸውን በመላው አለም የተበተኑ ልጆቿን የምታስከብርበት የረዥም ግዜ ህልሟ ነው። መሬማ ማለትም እቺ ናት። ያ መሬማ..... Tadios Alemayehu

" ጽዮን ሙሽራየ" (መኃልዬ መኃልዬ ዘቴዎድሮስ) ማዕረጌ ጌታቸው ፩-በእንድርያስ በኩል ከብዙ ሰው ጋር ከመስማማት ይልቅ ከአንድ ጋሽ መስፍን ወ/ማርያም ጋር ብከራከር እመርጣለሁ፡፡(ቃል በቃል አይደለም) በርግርጥም የእኔም አቋም ከዚህ አይቀርቅም፡፡ ከእልፍ የግል አመለካከቴን ከሚያቀነቅኑ ድምፃዊያን ይልቅ ከቴዲ አፍሮ ጋር ብሟገት እወዳለሁ፡፡ ፪--በእንተ- ቴዎድሮስ የቴዎድሮስ ካሳሁን ምናብ ሙዚቃዊ እንቆቅልሽ መፍጠር አይታክተውም፡፡ "ከባልደራሱ" እስከ "ማን ዘንድ ይደር" ብንጓዝ እንኳን ብዙ ግጥማዊ መንታነት (poetic Ambigutiy) ያላቸውን ሥራዎች ሲያሰማን ኑሯል፡፡ አሁን ደግሞ ተራው የ"ጽዮንሙሽራዬ" ነው፡፡ ፪-የተዳረች አገር! አዲስ በወጣው የቴወድሮስ ካሳሁን "ኢቶሪካ" አልበም ውስጥ አብዝተው ከሚያሟግቱ ሙዚቃዎች ዋናው "ጽዮን ሙሽራዬ" ይመስለኛል፡፡ ይህ ሥራ ለሐይማኖት፣ለፖለቲካና ለኪን ክርክር ክፍት ነው፡፡ ነጣጥለን እንመልከታቸው፡፡ ቀዳሚው ጎራ ቴዎድሮስ ካሳሁን "ጽዮን ሙሽራዬ" እያለ ያዜመው ለቅድስት ድንግል ማርያም ነው ብሎ ያምናል፡፡ ለዚህም በርካታ የትንቢት ንግግሮችን ማሳያ ያደርጋል:: ከዚህ በተቃራኒው ደግሞ ዜማውን በፖለቲካ ማዕቀፍ የተመለከቱ አድማጮች "ጽዮን ሙሽራየ" ለዛሬዋ ኢትዮጵያ የቀረበ ደስታ ነው ሲሉ ጽፈዋል፡፡ ሰርጉ ለአገር ደጋሹም ብልጽግና ነው ብለውም ሞግተዋል፡፡ ከኪን አንፃር ያለው ክርክር ግን ከፍ ይላል፡፡ ቴዲ አፍሮ ሲጀምር በ"ዳስ ጣል" አገር መሞቱን አውጆ፤ሲጨርስ ከንጋቱ አስራ አንድ ሰዓት መሆኑን ተናግሮ መሀል ላይ ኢትዮጵያን መሞሸሩ የአልበሙን "ቶን" አሳክሮታል ይላሉ፡፡ ፫-ጽዮን ሙሽራዬ ጽዮን የሚለውን ቃል ግዕዙ "ጸወን" ብሎ ይፈታዋል፡፡ ትርጉሙም አምባ መጠጊያ ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስቲያን ውስጥ ያለው ፍች ግን ከዚህም ከፍ ይላል፡፡ ቃሉ በትንቢታዊ ምስጢሩ ከቅድስት ድንግል ማርያም ጋር ይያያዛል፡፡ እዚህ ላይ ሌላም ነገር ልጨምር፡፡ በመኃልዬ መኃልዬ ዘሰሎምን ትንቢት ቅድስት ድንግል ማርያም በሙሽራም ተመስላለች፡፡ ቃሉ እንዲህ ይላል፡፡ "ሙሽራዬ ሆይ፤ ከሊባኖስ ከእኔ ጋር ነይ፡፡"(መኃልዬ መኃልዬ ዘሰለሞን 4፣8) ይህ ቃል እንደ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ሊቃውንት አስተምሮ ንጉሥ ሰሎሞን የቅድስት ድንግልማርያም የመወለጃ ሥፍራ ተገልጦለት አስቀድሞ የተናገረው ቃል ነው፡፡ በርግጥም የፊታችን ግንቦት አንድ የሚከበረው የቅድስት ድንግል ማርያም የልደት ቀን ድንገቴ ሳይሆን በኦሪት መጽሐፍት አስቀድሞ የተተነበዬ ነበር፡፡ ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስ፡፡ ቴዎድሮስ ካሳሁን በ"ጽዮን ሙሽራዬ" ዜማው ሁለቱን የትንቢት መፈጸሚያ ቃላት አንድ ላይ አምጥቷቸዋል፡፡ ይህ ብቻውን አንድ ቁልፍ ጥያቄን ይመለስሳል፡፡ እርሱም ሐዘንና ቁጭት ባረበበት "ኢቶሪካ" አልበም ውስጥ የ"ጽዮን ሙሽራዬ" መኖር ትንቢታዊ እንጂ አሁን ያለን አገራዊ ሁኔታና ስሜት ለማንፀባረቅ የመጣ አለመሆኑ ነው፡፡ እውነታው እንዲህ ከሆነ ከፍ ብለን ከጠቀስነው ተቃርኗዊ አመለካከት ውስጥ ቢያንስ ሁለት ቡድኖች ስህተት ሰርተዋል ማለት ነው፡፡ ቀዳሚዎቹ ይህ ዜማ ለዛሬዋ ኢትዮጵያ የቀረበ ነው የሚሉት ፖለቲከኞች ናቸው፡፡ ሁለተኛዎቹ በአንፃሩ ይህ ሥራ የአልበሙን "ቶን" አዛንፎታል ከሚለው የተሳሰሩ የኪን ሀያሲያን ይመስላሉ፡፡ "ጽዮን ሙሽራዬ" ሚቶኪን ንሸጣው ከ"መኃልዬ መኃልዬ ዘሰሎሞን" ስለሚነሳ፤ ገለፃውም ሆነ ደስታው የዛሬ ሳይሆን የነገ ነው፡፡ ፬- አምሳለ ጦቢት የኢትዮጵያ ሙዚቃ አንዱ ገናን የነገረ ኪን ጠባዩ አገርን በድንግል ማርያም መመሰሉ ነው፡፡ ይህን ጉዳይ አስመልክቼ በ"የከተማው መናኝ" እና "ጠመንጃና ሙዚቃ" መጽሐፍቶቼ ላይ ሰፋ አድርጌ ለማብራራት ሞክሪያለሁ፡፡ ለዚህ አጭር ጽሁፍ ግን የዮፍታሔ ንጉሤን ስንኝ ልዋስ፡፡ ድንግል ሀገሬ ሆይ ጥንተ ተደንግሎ… ልጅሽ ተሰደደ አንችን ተከትሎ የዮፍታሔ ግጥም ወዲህ ድንግል ማርያምን የኢትዮጵያ አምሳል ሲደርግ ወዲያ የቴዎድሮስ ካሳሁንን ጽዮን ለመዘከር በር ይከፍታል፡፡ ቴዲ አፍሮ በሙዚቃው አንድም ድንግል ማርያምን በልቡናው እያስበ አንድም ኢትዮጵያን በትንቢቱ እየዳረ ቁልቁል ይወርዳል፡፡ሀይማኖታዊ መታገጊያው ሥነ-ግጥማዊ ብቻ አይደለም፡፡ ዜማው ውስጥ ያለው ማኅሌተ ገንቦ ( ታቦታት ፊት የሚቀርቡ ባሕላዊ ሐይማኖታዊ ሙዚቃ) ወደ ቤተ-ክርስቲያን ይወስዳል፡፡ ዳግማዊ ሔዋን፣ የፍቅር እናትና መሰል ሀረጋትን እያመጣ ቅድስት ድንግል ማርያምን ያስታውሳል፡፡ አያቆምም፡፡በገጠሩ የአገራችን ክፍል የተለመደውን የታቦት ማጀቢያ ይዋሳል፡፡ የት ወለም ዘለም ትላለህ(2) አምሳለ ጦቢትን ስንድር እያየህ፤ እያለ፡፡ ቴዎድሮስ ትንቢትን ከምናብ አዳቅሎ ሰርጉ ቦታ ይወስደናል፡፡ ያችን የሚወዳትን ኢትዮጵያን ድሮ ዜማ ያወርዳል፡፡ "ኧረ እግ እኔ ሰው መሆኔ ፣ምኔን ልስጣት ልሸልማት" እያለ የደስታውን ወደር ማጣት ይገልጣል፡፡ ቴዲ አፍሮ እዚህ ሥራ ላይም እንደተለመደው ጦቢትን ያነሳል፡፡ ከመጽሐፍ ቅዱስ እስከ ድርሳነ ሩፋኤል የተዘረጋው የጦቢት ታሪክ በቴዲ አፍሮ ሙዚቃ ውስጥ ተደጋግሞ መምጣቱ የዋዛ አይመስለኝም፡፡ አስቀድሞ በ"ማን ዘንድ ይደር" ውስጥ አንስቶታል፡፡ "ኢቶሪካ" ላይም ደግሞታል፡፡ ሁለቱን አዋዶ ሌላ ዝርዝር ውስጥ መግባት አንባቢን ስለሚሰለች ላቆየውና ስለቴዲ ምናብ አንድ ነገር ብዬ ላብቃ፡፡ ቴዲ አፍሮ ለምትጠላው ቡድን ቢጫወት እንኳን አድናቆትህን የማትነፍገው ምርጥ ተጫዋች ነው፡፡ አኮቴት ለቴዎድሮስ! © Maereg Getachew

መሬማን ፍለጋ ቴዲ አፍሮ ያው እንደልማዱ በጥበብ ካሳበደን ይኸው 2 ቀን ሆነን፣ ዛሬም አልተሻለን። የቱን ወደን የቱን መጣል እስኪያቅተን፣ ጆሮ አዋጅ ሆኖብን በጥበብ እንደተሳከርን ይኸው አለን እስካሁን። ከ18ቱ ዘፈኖች፣ ቁጥር 15 ላይ የተቀመጠው ዘፈን ግን እንግዳ ነገር ጥሎብኝ አለፈ፣ 'መሬማ'። ለመሆኑ መሬማ ማናት? መጀመሪያ ስሰማው እንደብዙዎቹ አድማጮች እኔም፣ ቴዲ ይህንን ዘፈን በአረብ አገር ላሉ እህቶቻችን ነው የዘፈነው ብዬ ነበር። በርግጥ እነዚህን ውድ እህቶቻችንን በዚሁ ዘፈን ላይ አንድ ቦታ ላይ ይዘክራቸዋል፦ ''ሉብናን በይሩት ኳታር፣ ባህሬን ሳኡዲ ዱባይ፣ እንደሚያዝነው ልቤ እህት ወንድሜን ሳይ...'' በማለት፣ በአረብ በረሃ ቀን ከሌት እየለፉ ኑሮን የሚገፉትን እነዚያን ውድ ዜጎቻችንን ያስታውሳል። ነገር ግን፣ መሬማን ከነርሱ ምድብ እንዳለስቀመጣት የሚገባን፣ ''ባያት አምሳያዬን ብጠራት አትሰማ፣ መሬማ'' ሲለን ነው። ቴዲ መሬማን ሲያያት፣ መልኳ ወገኖቹን ስለምትመስል፣ በተለይ በአረብ አገራት ያሉ እህቶቹን አስታውሶ አዘነላት እንጂ፣ መሬማ ከእነዚያ እህቶቹ መሀል አንዷ አይደለችም። የወገን አምሳያ እንጂ፣ ራሷ ወገን አይደለችም። ስለዚህ ማናት መሬማ? ''ወዲህ አላቃት፣ አቃተኝ ደሞ ላልፋት..'' ይልና ስትሄድ ይከተላታል፣ እሷ ግን አትመልስም። እንዲያውም በዝምታዋ ስታስቸግረው፣ ''ላ ላ አትበይኝ በቃ አይሆንም፣ ጠጋ ብለሽ አውሪኝ እስቲ ያለሽበት ሁኔታውን..'' እያለ ያለመሰልቸት ይለምናታል። ልብ በሉ፣ 'ላ ላ' ማለት በአረቢኛ አይሆንም ማለት ነው። ያ ማለት መሬማ አረቢኛ ነው የመግባቢያ ቋንቋዋ። እንዴት ነው ነገሩ? ''...ጠጋ ብለሽ አውሪኝ እስቲ ያለሽበት ሁኔታውን፣ እያየሽው በትካዜ የምትጠርጊው ጎዳናውን፣ አጎንብሰሽ ስትተክዢ ተደግፈሽ መጥረጊያውን፣ አሳዘንሽኝ እኔማ፣ ስንት አለ ሆድሽ መሬማ'' ቆይ አንዴ...በየአረብ አገሩ ጎዳና በመጥረግ የሚተዳደሩ ሴቶች እህቶቻችን ሊኖሩ ይችላሉ። ግን እነዚህ እህቶቻችን ባብዛኛው የሚታወቁት በቤት ውስጥ ሰራተኝነት ነው፣ እንዲያውም 'የማዳም ቅመሞች' የሚል የተለምዶ ስም አላቸው። መሬማ ግን፣ 'በሀሩሩ መንደር በሃጋይ በረሃ፣ ማዶ ባብል የመን በሰንአ ከተማ...'' የጎዳና ፅዳት ሰራተኛ ሆና ነው ቴዲ ያገኛት፣ ሰነአ ጎዳና ላይ። የቴዲ አምሳያ ነች፣ የየመን ዋና ከተማ የሰንአን ጎዳና ትጠርጋለች፣ ከዚህ በፊት አይቷት ባያውቅም አምሳያው ነችና ሳያናግራት ማለፍ አቃተው። ስሟን ከሰው ጠይቆ ሊያናግራት ሲጠራት አትመልስም፣ ምናልባት ማናገር አትፈልግም፣ ወይም ደሞ የቴዲን ቋንቋ መናገር አትችልም፣ ስለዚህ 'ላ ላ' አለችው፣ ማናገር አልፈልግም፣ ወይም ያንተን ቋንቋ አልችልም ማለቷ ነው። ምክንያቱም ቋንቋዋ አረብኛ ነው። ስለዚህ መሬማ ኢትዮጵያዊ አይደለችም። እና ታዲያ መሬማ ማነች? ቅድም እንዳልኩት፣ ቴዲ መሬማን የተጠጋት፣ በየአረብ አገሩ ካሉ ታታሪ እህቶቹ መካከል አንዷ መስላው እንደሆነ ነግሮናል። እሷ ግን ያገሬ ልጅ ብላ በጉጉት አልተቀበለችውም፣ ጭራሽ 'ላ ላ' አለችው። ከስሟ እንደተረዳው ሙስሊም ነች፣ እንደ አፋር አፍሌታ የጠየመው የርሱና የሷን መልክ መመሳሰል አይቶ ያገሬ ልጅ ነች ብሎ አሰበ። የድሬዋ አይሻ፣ የሀረሯ ረምላ፣ የጅማዋ አለውያ፣ የወልቂጤዋ አልፊያ፣ የወራቤዋ ሂክማ፣ የአዲሳባዋ ሀናን፣ የደሴዋ ፈቲያ፣ የሰመራዋ ሀያት፣ የጂግጂጋዋ ዘይነብ፣ የውቆሮዋ ማህፉዛ ትሆናለች ብሎ አሰበና ሰላም ሊላት ቢጠጋት የሷ መልስ 'ላ ላ' ብቻ ሆነ። ስለዚህ ማነች መሬማ? ነገሩ ወዲህ ነው፣ ከአንድ ሺህ አምስት መቶ አመት በፊት፣ በአክሱም ዘመነ መንግስት፣ ኢትዮጵያ ባህር ተሻግራ የየመንን ምድር ሳይቀር ትገዛ ነበር። ከባህር ወዲያ ያለውን አገር ለማቅናት በርካታ ወታደሮች እዚያ ሄደው፣ ተፈርተው ተከብረው በታላቅ ክብር ይኖሩ ነበር። እዚያው ወልደው፣ ርስት አቅንተው እየኖሩ እያለ፣ እዚሁ አገር ቤት በተነሳ ተከታታይ የርስ በርስ ጦርነት የአክሱም ስልጣኔ ወደመና የኢትዮጵያ ከፍታ ተገታ። የመን የሰፈሩት የትናንቶቹ አገር አቅኚዎች ህልውና አደጋ ላይ ወደቀ። የትናንት ተፈሪዎች ዛሬ ፈሪ ሆኑና ጭራሽ አገር አልባ ሆኑ። ትናንት አዝካሩል ሃበሽ(የኢትዮጵያ ወታደሮች) ይባሉ የነበሩ ባለገርማ ህዝቦች ዛሬ፣ Muhamasheen(የተናቁ፣ የተገለሉ) ተብለው የትም ተጣሉ። መላው የመናዊ ላለፉት ሺ አመታት 'አል አኽደም' ወይም ባሮች እያለ ይጠራቸው ጀመር። በጎሳ በተከፋፈለች የመን፣ እነርሱን እንደ አንድ ማህበረሰብ የሚቀበላቸው ጠፍቶ፣ ርስት አልባ ሆነው፣ በሰንኣ ከተማ ዳር ዳር ላይ ዳስ ሰርተው ነው ኑሯቸውን የሚገፉት። በዘመናት ታሪክ ከተቀያየሩ የየመን ገዢዎች መሀል አንዳቸውም ሙሀመሺኖቹን እነመሬማን፣ አይደለም እንደዜጋ፣ እንደሰው እንኳን ቆጥረዋቸው አያውቁም። ወንዶቹ በየቤቱ ቆሻሻ ማንሳት፣ ሴቶቹ ደሞ የሰንአን ጎዳናዎች መጥረግ ብቻ ነው ለነርሱ የተፈቀደ ስራ። በዚህ የመከራ ኑሮ ላይ ሆና ነው እንግዴህ፣ መጥረጊያዋን ተደግፋ ትክዛ እያለች ቴዲ መሬማን ያገኛት። አምሳያውን እንዴት ያዋራት? ቋንቋ የለማ፣ ምስኪን መሬማ። ላለፉት ብዙ አመታት እነዚህ አምሳያዎቻችን፣ እነመሬማ፣ ማንነታቸውን ለማስከበር መራራ ትግል እያደረጉ ነበር። እንዲያውም የአሜሪካኖቹን አይነት 'Black Lives Matter' አይነት እንቅስቃሴ ጀምረው፣ ለአለም መንግስታት ድምፃቸውን እያሰሙ ነበር ሁላ። በኋላ ግን ትልቁ የየመን የርስ በርስ ጦርነት ሲጀምር የነርሱን ጉዳይ አቤት የሚለው ጠፋ። እንግዲህ ጉደኛው ቴዲ፣ ይህንን የታፈነ የወገኖቻችንን ድምፅ ነው በዚህ ስራው ይዞ የወጣው። ለመብታቸው የሚያደርጉትን ትግል ከማገዝ በፊት ግን፣ መጀመሪያ እርስ በርስ መተዋወቁ ይቀድማል ብሎ ነው ቴዲ መሬማን መከተል የያዘው:- ''ማዶ ባብል የመን በሰንአ ከተማ፣ ውበትሽን እያየሁ ስወጣ ስገባ፣ እንደአፋር አፍሌታ የጠየመው ፊቴን፣ ሌላው ቢቀር እንኳን እይው ማንነቴን'' ይላታል መሬማን። እናንተም እወቋት ኢትዮጵያዊቷን የየመን ከርታታ፣ የትናንቷ ጀግና የዛሬ አገር አልባዋን፣ መሬማን። © Bilelegn Gashaw Mengistu