ንቁ ትውልድ-Niku Twld
الذهاب إلى القناة على Telegram
2 236
المشتركون
-424 ساعات
-187 أيام
-5130 أيام
أرشيف المشاركات
2 236
ቅዱስ ጊዮርጊስ ሆይ! አንተን በመታመን ለጠራህ ሁሉ ፈጥነህ ስትደርስለት ከዓውሎ ነፋስ ይልቅ በተፋጠነ ሩጫ ነው። ጊዮርጊስ ሆይ! የዘወትር ጸሎቴንና የቃሌንም የልመና ጩኸት ትቀበል ዘንድ ለይቅርታና ለምህረት ፈጥነህ ወደ እኔ ቅረብ። 🙏
(መልክአ ቅዱስ ጊዮርጊስ)
2 236
ዛሬ ነሀሴ 22 የሊቀ መላዕክት የቅዱስ ዑራኤል ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏
የእግዚአብሔር ህዝብ በባቢሎን ምርኮ በነበሩበት ዘመን ነቢዩ ዕዝራ (ዕዝራ ሱቱኤል) ስለ ቅድስት ከተማ ጽዮን መፈራረስ፣ ስለ ወገኖቹ መሰደድና መገፋት፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ በጦርነቱ ወቅት የእግዚአብሔር ህግ የተጻፈባቸው ቅዱሳት መጻሕፍት በመቃጠላቸው ልቡ በሀዘን ተሰበረ።
ዕዝራ "ህጉ ከጠፋ ህዝቡ እንዴት ይመራል? ትውልዱስ እንዴት ፈጣሪውን ያውቃል?" ብሎ በመጨነቅ ወደ ምድረ ራፌድ ወጣ። በዚያም መሪር ዕንባን እያፈሰሰ፣ ስለ ወገኖቹና ስለ መጻሕፍቱ መጥፋት እያለቀሰ 40 ቀንና 40 ሌሊት በጾምና በጸሎት ተቀመጠ።
ዕዝራ ጾሙንና ጸሎቱን በፈጸመ ጊዜ፣ ልዑል እግዚአብሔር ምስጢር ገላጭ የሆነውን ታላቁን መልአክ ቅዱስ ዑራኤልን ወደ እርሱ ላከው። ቅዱስ ዑራኤልም በእጁ "የእሳት ጽዋ" ይዞ ከሰማይ ወረደ።
መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ዕዝራን እንዲህ አለው፦ "አፍህን ክፈት፣ ይህንንም የጥበብ ጽዋ ጠጣ"። ዕዝራም አፉን ከፈተ፤ ያን የእሳት ጽዋም ጠጣው። እዝራ ሱቱኤል 13: 38
ያን ጊዜ የዕዝራ ልቡና እንደ ብርሃን በራ! የተሰወረ ምስጢር ተገለጠለት። የጠፉትና የተቃጠሉት መጻሕፍት ሁሉ በቃሉ ተቀረጹለት(ተገለጡለት)።
ከዚያ በኋላ ዕዝራ አምስት ጸሐፊዎችን አዘጋጅቶ፣ ቅዱስ ዑራኤል የገለጠለትን ምስጢርና ትምህርት በ40 ቀናት ውስጥ መጻሕፍትን በቃሉ እየነገራቸው መልሰው እንዲጽፉ አደረገ። በዚህም ምክንያት ዕዝራ "ዳግማዊ ሙሴ" ተብሎ ተጠራ።
የቅዱስ ዑራኤል ተራዳኢነትና የነቢዩ ዕዝራ በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን! ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ዑራኤል ጥበቡን፣ እውቀቱንና ምስጢሩን ለሁላችንም ይግለጥልን አሜን🙏
2 236
ዛሬ ነሀሴ 21 የእናታችን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏
ድንግል ሆይ ስለዚህ እንወድሻለን፤ ከፍ ከፍም እናደርግሻለን እውነተኛ የጽድቅ መብልንና እውነተኛ የህይወት መጠጥን ወልደሽልናልና። (ቅዳሴ ማርያም)
ድንግል ሆይ የእግዚአብሄር ማደሪያ ንጹህ አዳራሽ ነሽ ጠላቶቼ ያቺ የሚመካባት እመቤቱ ወዴት አለች ብለው እንዳይዘባበቱብኝ። እኔን ባሪያሽን ለሀዘን ለትካዜ አሳልፈሽ አትስጪኝ። (መልክአ ማርያም)
2 236
ወር በገባ በ20 የታዛዡና የትሁቱ አባታችን የቅዱስ ዮሐንስ ሐፂር ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏
"ሐፂር" ማለት በግዕዝ "አጭር" ማለት ሲሆን፣ ጻድቁ በቁመታቸው አጭር ቢሆኑም በመንፈሳዊ ቁመናቸው ግን ሰማይ የደረሱ ታላቅ አባት ናቸው።
ዮሐንስ ሐፂር ገና በ18 ዓመታቸው የዓለምን ግርግር ትተው ወደ እስቄጥስ ገዳም ገቡ። በዚያም በአባ ባይሞይ እጅ እየተመሩ የመንፈሳዊ ህይወትን መሠረት መማር ጀመሩ። አባታችን ገና ከጅምሩ የታወቁት በጾምና በጸሎት ብቻ ሳይሆን፣ ለቃለ አበው ባላቸው ፍጹም "መታዘዝ" ነበር።
መምህራቸው አባ ባይሞይ የዮሐንስን ትሕትናና መታዘዝ ለዓለም ለማሳየት አንድ ፈተና አቀረቡላቸው። አንድ የደረቀ እንጨት ሰጧቸውና እንዲህ አሏቸው፦ "ይህን ደረቅ እንጨት ትከለውና ውኃ እያጠጣህ አብቅለው፤ ፍሬ እስኪያፈራም ተንከባከበው።"
ማንኛውም ሰው በምክንያት "ደረቅ እንጨት እንዴት ይበቅላል?" ብሎ ሊጠራጠር ይችላል። ዮሐንስ ግን ምንም ጥያቄ አላነሱም። "እሺ አባቴ" ብለው ተቀበሉ። ለሦስት ዓመታት ሙሉ፣ ውሃ ከሚገኝበት ሩቅ ቦታ በቀን ሁለት ጊዜ እየተመላለሱ ያንን የደረቀ እንጨት አጠጡት።
ከሦስት ዓመት በኋላ ያ ደረቅ እንጨት በተአምር ለመለመ! ታላቅ ዛፍ ሆኖ አብቦና አፍርቶ ጣፋጭ ፍሬ ሰጠ። አባ ባይሞይም ፍሬውን ለሌሎች ቅዱሳን እያደሉ እንዲህ አሉ፦ "የታዛዡንና የትሑቱን ሰው ፍሬ እንሆ ቅመሱ!" ዛሬም ድረስ በግብፅ በገዳመ አስቄጥስ ውስጥ ያ ዛፍ "የመታዘዝ ዛፍ" (Tree of Obedience) ተብሎ እንደ ቆመ ይነገራል።
አቡነ ዮሐንስ በትሕትናቸውና በተጋድሎአቸው እጅግ ከፍ ስላሉ፣ መለኮታዊ ሚስጥር ተገለጠላቸው። ቀና ቢሉ "ሥሉስ ቅዱስን" በግርማ መንግሥታቸው ይመለከታሉ፤ ዝቅ ቢሉ ደግሞ ኃጥአን የሚቀጡበትን "እንጦሮጦስን" ያያሉ። ጌታችንም ስለ ታዛዥነታቸው በገሃድ እየተገለጠ ያነጋግራቸው ነበር።
የታላቁ አባት የቅዱስ ዮሐንስ ሐፂር በረከታቸው ይደርብን። የደረቀውን ህይወታችንና የከሰመው ተስፋችንን ያለምልሙልን አሜን🙏
2 236
ዛሬ ነሀሴ 19 የገናናው መልአክ የሊቀ መላዕክት የቅዱስ ገብርኤል ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳችሁ!
ቅዱስ ገብርኤል ከክፉ ሁሉ ይጠብቀን አሜን🙏
2 236
📌ነገሮችን ከማድረጋችን በፊት ቆም ብለን እሺ ከዚያስ ወዲያ ብለን ብንጠይቅ በህይወታችን ብዙ ነገር አይበላሹም። አድርገን ሳይሆን ከማድረጋችን በፊት ቀድመን እናስብ!
አሁን ምናደርገው መጨረሻው ምንድነው?
እኛን ይጠቅመናል ወይስ ይጎዳል?
ሰውንስ ይጠቅማል ወይስ ይጎዳል?
ፈጣሪንስ ያስደሰታል ወይስ ያሳዝናል?
ቆም ብለን እንጠይቅ?
መልካም ቀን🙏🙏
2 236
ጊዜው የይሁዳ ንጉሥ ሕዝቅያስ በኢየሩሳሌም የነገሠበት ወቅት ነበር። ያኔ ምድርን በኃያልነቱና በጭካኔው ያንቀጠቀጠው የፋርስና የአሦር ንጉሥ ሰናክሬም፣ እጅግ ግዙፍና አስፈሪ ሠራዊቱን አስከትሎ ወደ ኢየሩሳሌም መጣ። ቅጽሯን አጥብቆ ከበባት፤ ህዝቡንም በታላቅ ፍርሃት አወከው።
ሰናክሬም በጉልበቱና በሠራዊቱ ብዛት በመታበይ፣ ከንቱ በሆነ ትዕቢት ተሞላ። የሰማይና የምድር ፈጣሪ የሆነውን እግዚአብሔርን በመሳደብና በማንኳሰስ ወደ ንጉሡ ወደ ሕዝቅያስና ወደ ይሁዳ ሕዝብ እንዲህ የሚል መልእክት ላከ፦
"በእውኑ ከእጄ ሊያድናችሁ የሚችል አምላክ አለን? አትታለሉ!"
ንጉሡ ሕዝቅያስ ይህንን ዛቻና በፈጣሪው ላይ የተሰነዘረውን የስድብ ቃል በሰማ ጊዜ ልቡ በሐዘን ተሰበረ። ነገር ግን እንደ ሰናክሬም በጦርና በጋሻ ሳይሆን፣ እውነተኛው መሸሸጊያ በሆነው በፈጣሪው ተማመነ። ንጉሣዊ ልብሱን አውልቆ፣ የትሕትናና የንስሐ ምልክት የሆነውን ማቅ ለበሰ። ቀጥታም ወደ እግዚአብሔር ቤት (ቤተ መቅደስ) በመግባት በግምባሩ ተደፍቶ ሰገደ።
ሕዝቅያስ በዕንባና በታላቅ ልመና ወደ ሰማይ ጮኸ፦ "አምላክ ሆይ! አገራችንንና ቅድስት ከተማችንን ኢየሩሳሌምን ከዚህ ጨካኝ ጠላት እጅ አድን!" እያለ ማለደ።
እግዚአብሔር የሕዝቅያስን ትሕትና፣ የሕዝቡን ጭንቀትና እውነተኛ ጸሎት ሰማ። በዚያች በታላቅ የጭንቀት ሌሊት፣ ፈጣሪ የሰማይ ሠራዊት አለቃ የሆነውን፣ ታላቁን መልአክ ቅዱስ ሚካኤልን ወደ ሰናክሬም ሰፈር ሰደደው።
የብርሃን መልአክ ቅዱስ ሚካኤል እጅግ አስደናቂና አስፈሪ በሆነ መለኮታዊ ኃይል ወደ ሰናክሬም ሠራዊት መሃል ወረደ። በዚያች በአንድ ሌሊት ታላቅ ተአምር ተደረገ፤ የመልአኩ ሰይፍ በጠላት ሰፈር ላይ በተቃጣ ጊዜ፣ ከሰናክሬም ሠራዊት መካከል አሥራ ስምንት ዕልፍ ከአምስት ሺህ (185,000) የሚሆኑት ኃያላን ወታደሮች ሙሉ በሙሉ ወደቁ።
ታላቁ የይሁዳ ሕዝብና ቅድስት ከተማ ኢየሩሳሌም፣ አንድም ሰው ሳይሞትባቸውና ሳይደማባቸው፣ በሚያስደንቅ መለኮታዊ ጥበቃ ከጥፋት ዳኑ። ትዕቢተኛው ንጉሥ ሰናክሬምም በኃፍረትና በውርደት ተመትቶ ሸሸ።
የቅዱስ ሚካኤል ጥበቃ፣ ፈጣን አማላጅነትና ተራዳኢነት ከሁላችን ጋር ይሁን። አሜን🙏
2 236
ዛሬ ሐምሌ 8 የፃድቁ አባታችን የአቡነ ኪሮስ ዓመታዊ የእረፍት በዓል ነው። እንኳን አደረሳችሁ እንኳን አደረሰን🙏
️
አቡነ ኪሮስ ከሮም ነገስታት ወገን ሲሆኑ አባታቸ ንጉስ ዮናስ እናታቸው አንስራ ይባላሉ፡፡ ወላጆቹ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ቅዱሳን ነበሩና አቡነ ኪሮስ በታህሳስ 8 ተወለዱ፡፡ አቡነ ኪሮስ የመጀመሪያ ስሙ ዲላሶር ይባል ነበር፡፡ በኋላ አባቱ ከሞተ በኋላ ሀብቱን ከወንድሙ ተካፍሎ ለድሆች መጽውቶ ዓለምን ንቆ መንኖ ሄደ፡፡ ከአባ በቡነዳ ገዳም ገባ፡፡
በ17 ዓመቱ ሥርዓተ ምነኩስናን ተማረ፡፡ በአባ በቡነዳ እጅ መነኮሰ፡፡ ከዚህ በኋላ በጾም በጸሎት ተወስኖ ኖረ፡፡ስለ ዓለም መከራ ለ40 ዘመን ተኝተው ሲጸልዩ እላያቸው ላይ ሳር በቅሎባቸው ሳለ መላእክት መጥተው ተነስ ቢሉት አዳም የፍጡር ቃል ሰምቶ ወድቀዋል ጌታዬ ድምጹን ያሰማኝ አላቸው በኋላ ኪሩቤል አንስቶ ወስዶ ገነት አሳይተውት ጌታችንም ቃል ኪዳን ሰጣቸእ።
ቃል ኪዳናቸውም መካኖች ልጀ የሌላቸው ገድሉን አቅፈው ቢያለቅሱ ጸበሉን ቢጠጡ ስምህን ቢጠሩ፤ የመካኒቱን ማህጸን እከፍታለሁ፡፡ የሚሞትባቸውን እንዳይሞተባቸው አደርጋለሁ፡ በንጹ ገንዘቡ ቂምና በቀል ሳይዝ በህግ በስጋውና በደሙ የጸና ሰው በስምህም በተሠራው ቤተክርስቲያን ጧፍ ዘይት ያበራ መገበሪያ ያመጣውን ልጅ አሰጠዋለሁ፡፡ ብሎ ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ከዚም በኋላ በተወለዱ 270 ዓመታቸው ሐምሌ 8 አርፈዋል።
የፃድቁ አባታችን የአቡነ ኪሮስ ረድኤት፣ በረከታቸውና አማላጅነታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን🙏
2 236
ሐምሌ 7 በዚች ቀን ሥላሴ ያደረጉት ተአምር ይህ ነው፡፡
እግዚአብሔርን የሚፈራ ቸር ጻድቅ የሆነ ስሙ አብርሃም የተባለ ምድያም በሚባል አገር አንድ ሰው ይኖር ነበር የሚስቱም ስም ሳራ ይባላል፡፡ እነዚህ ቅዱሳን በሥላሴ ሕግ ተጠብቀው ስደተኛውን እንግዳውን እየተቀበሉ ያስተናግዱ ነበር፡፡ እንግዳ ሳይዙ ወይም ሣይኖር የሰናፍጭ ቅንጠት ሰንኳ ያህል ምግብ ምንም ምን አይቀምሱም ነበር፡፡
የበጎ ነገር ጠላት የሆነ ሰይጣንም ይህን በተመለከተ ጊዜ ከጭፍሮቹ አንዱን እንዲህ ሲል ላከው፡፡ እንግዶች ሁሉ ወደ አብርሃም ቤት እንዳሄዱ በምድያም ገዳና ተቀምጠህ ዕውነቱን በሐሰት ለውጠህ ተናገር፡፡ እንሆ ደምህ በመሬት ላይ እስኪወርድ ድረስ ራስክን በድንጋይ ፈጥፍጠው አለው፡፡
ሰይጣኑም ይህን ትእዛዝ ከተቀበለ በኃላ ወደ ምድያም ወረደና ደሙ በምድር ላይ እስኪፈስ ራሱን በድንጋይ ገምሶ በጎዳና ላይ ተቀመጠ፡፡ በጎዳና የሚያልፋ መንገደኞች ሰዎች ወደ እርሱ በደረሱ ጊዜ እናንት መንገደኞች ከወዴት መጥታችኋል ወዴትስ ትሄዳለችሁ ሲል ጠየቃቸው፡፡መንገደኞቹም እኛስ ወደ ደገኛው ወደ አብርሃም ቤት እንሄዳለን አሉት፡፡
በውኑ አብርሃም ደግነቱ በክፋት እንደተለወጠና ክፋ ሰው እንደሆነ አልሰማችሁምን፡፡እንሆ እንግዳ ከመጥላቱ የተነሳ ደሜ ከመሬት ላይ እንደ ውሃ እስኪፈስ ድረስ የፈተነከተኝን ራሴን መጥታችሁ ተመልከቱ ይልቁንስ በኔ የደረሰ እንዳይደርስባችሁ አትሂዱ አላቸው፡፡
እንግዶቹም ያ ቸርና መልካም ሰው የነበረ አብርሃም ምን ነክቶት ክፋ ሰው ሊሆነ ቻለ በማለት እርስ በራሳቸው ተወያዩ፡፡ ይህንንም ከተባባሉ በኃላ ተመልሰው ወደ ሀገራቸው ሄዱ፡፡
በዚችም ዕለት አብርሃም ከቤቱ ወጥቶ በጎዳና እንግዳ ፈልጉ አጣ፡፡ ከዚያም ወደ ቤቱ ተመልሶ ገባና ምንም ሳይቀምስ ተኛ፡፡
በማግስቱ አምስት ሰዎች ወደ አብርሃም ቤት ሲሄዱ ያ ተንኮለኛ ሰይጣን አገኛቸውና እንደቀድሞ እናንተ ሰዎች ወዴት ትሄዳላችሁ ሲል ጠየቃቸው እነሱም ወደ አብርሃም ቤት እንሄዳለን አሉት፡፡
ሰይጣን መልሶ ወንድሞቼ ሆይ አብርሃም ራሴን ፈንክቶኝ ከማህል ራሴ የሚወርደው ደሜን ተመልከቱ አላቸው፡፡ እንሆ አሁንም እንደኔ እንዳትሆኑ በሰላም ወደ ሀገራችሁ ተመለሱ አላቸው፡፡ በዚህን ጊዜ እነዚያ እንግዶች እርስ በራሳቸው አብርሃም ከሚገድለንስ ወደ ሀገራችን ብንመለስ ይሻላል ተባባሉ፡፡
ዳግመኛም እንደልማዱ ወደ ጎዳና ወጥቶ ፀሐይ እስኪ ጠልቅ ድረስ ሲጠብቅ ውሎ ምንም እንግዳ ሳይገኝ ቀረ፡፡ ከዚያም ወደቤት ተመልሶ ምንም ሳይቀምስ ተኝቶ አደረ፡፡ በሦስተኛውም ቀን አጋዕዝተ ዓለም ሥላሴ የአብርሃም የልቡን ቆራጥነና የሰይጣንን ተንኮል ተመልክተው ወደ አብርሃም ቤት ሄዱ፡፡ በዚህ ጊዜ የሰይጣን ምክሩ ሁሉ ተሻረ ይዘውም ወደ መጨረሻይቱ የሲኦል ረግረግ ጣሉት፡፡ እሊህ ሥላሴም በእንግዳ ደንብ በአብርሃም በቤቱ ደጃፍ ተቀመጡ፡፡
አብርሃም በደጁ እንደተቀመጡ በተመለከቱ ጊዜ ወደ ቤቱ እሮጦ ገብቶ ለሚስቱ እንዲህ ሲል ነገራት፡፡ እኅቴ ሣራ ሆይ እንሆ የከበሩ አረጋውያን ሦስት እንግዶች መጥተዋልና፡፡
እንግዲህ አንቺ ፈጥነሽ እንጀራና ወጡን ጥሩውን ጠላና መልካሙን ጠጅ አዘጋጂ እኔም የወይፈን ፍሪዳ አርዳለሁ አላት፡፡ ሣራ ሚስቱም እሺ ጌታዬ እንዳልከኝ አደርጋለሁ አለች፡፡ ዳግመኛም ዕርጎውን ማሩን አንድ ታዘጋጅና ለእግራቸው መታጠቢያ ውሀ በምንቸት ታሞቅላቸው ዘንድ አዘዛት፡፡
ከዚህም በኃላ ለእያንዳቸው ለራሳቸው ሦስት ታላላቅ ዳቦ ትጋግር ዘንድ አዘዛት፡፡ አብርሃም ይህን ከተናገረ በኃላ ወይፈኑን አርዶ ሥጋውን በየብልቱ አወጣው፡፡
ከዚያም የታረደውን የወይፈንኑን ሥጋ በትከሻው ተሸክሞ ወደ ቤቱ ይዞ ከገባ በኃላ ለሚስቱ ሰጣትና እኔ እግራቸውን እስካጥብ ድረስ ይህን ሥጋ ቅባቱን በዛ አድርገሽ በጨውና በቅመም አጣፍጠሽ ስሪው አላት እሷም እሺ በጄ አለችው አብርሃምም ከቤቱ መድረክ በስተውጭ ሥላሴን ባገኛቸው ቦታ ላይ ልብሱን አነጠፈና ጌቶች እግራችሁን አጥባችሁ ዘንድ ወደ ወንድማችሁ ቤት ዝለቁ አላቸው፡፡
ከዚህ በኃላ ተነሥተው ወደ ድንኳን ወይም አዳራሽ ገቡና ባነጠፈላቸው ምንጣፍ ላይ ተቀመጡ፡፡ በዚህ ጊዜ የአብን እግር ማጠብ ጀመረና አብን ካጠበ በኋላ ወልድና መንፈስ ቅዱስም ታጥበው አገናቸው ያለመለየት አንድ ናቸውና፡፡ በዚህ ጊዜ ማዕዱን በገበታ ሠርቶ ወይኑንም በማድጋ ቀድቶ አቀረበላቸውና እስኪጠግቡ ድረስ በሉ ጠጡ፡፡
ማዕዱ ከተነሣ በኋላ ለእንግዶች እራት የታረደው ወይፈን በቤቱ በራፍ ፊት ለፊት ከውጭ በኩል ቆሞ አየው፡፡ አብርሃም ይህን ወይፈን ባየ ጊዜ ፈጽሞ ፈራ ተንቀጠቀጠ፡፡
በዚህ ጊዜ ሥላሴ አብርሃም ሆይ ሰይጣን እንደቀናብህ ጠንቅቀህ እወቅ እንግዳ በመጣልህ ጊዜ በብሩህ ልቡና እና በንቁ ኅሊና ሆነህ ተቀበለው፡፡ ነገር ግን እንግዳ ካልመጣ እራትህን በጊዜ ብላ መጠጥህንም ጠጣ እንጂ ጦምህን አትደር አሉት፡፡
ይህንንም ተናግረው እኒህ በአምሳልና በህልውና ትክክል የሆኑ ሥላሴ ወደ ሰማይ አረጉ፡፡ ይህም ሁሉ የሆነው ሐምሌ ሰባት ቀን ነው፡፡ የምድያም ሰዎች ስለዚህ ለምግብ ከተዘጋጀ በኃላ ሥላሴ ሰላስነሡት ወይፈን እንዲሁም በሥላሴ ዘንድ በተደረጉት ድንቅ ድንቅ ሥራዎች ሁሉ ፈጸመው ተደነቁ፡፡
ይቅርታቸው ሀብተ ረድኤታቸው በመላው ህዝበ ክርስቲያን ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን፡፡
(ሰይፈ ሥላሴ ዘእሁድ)
2 236
ሰላም ለቃልኪ፦ የተበተነ ልቡናን ለሚሰበስብ ቃልሽ ሰላምታ ይገባል፡፡ የኃጢአት ደዌን ለሚፈውሰው መድኃኒት ለሆነው እስትንፋስሽም ሰላምታ ይገባል፡፡ ተስፋ ለቆረጡት ተስፋ፣ ለደከሙትም መጽናኛ የሆንሽ ቅድስት አርሴማ ሆይ ጨለማው በማይገፋ እሳቱም በማይጠፋ በጭንቅ ቀን በታመነው ቃል ኪዳንሽ ፈጽመሽ አድኚኝ፡፡ 🙏
መልክአ ቅድስት አርሴማ
2 236
ዛሬ ሐምሌ 5 የዓለም ብርሃናት፣ የቤተክርስቲያን ምሰሶዎች ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ምድራዊ ሩጫቸውን በሰማዕትነት የፈፀሙበት ታላቅ ዕለት ነው። እንኳን አደረሳችሁ እንኳን አደረሰን🙏
የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ የመጀመሪያ ስሙ ስምዖን ይባል ነበር፤ የገሊላው ዓሣ አጥማጅ። ነገር ግን የሰው ልጅ ሊደርስበት ያልቻለውን ምሥጢረ ተዋሕዶን ገልጦ “አንተ የህያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ በመመስከሩ፣ ጌታችን “አንተ ጴጥሮስ (ዐለት) ነህ፤ በዚህችም ዓለት ላይ ቤተክርስቲያኔን እሠራታለሁ” አለው። የመንግሥተ ሰማያትንም መክፈቻ ተቀበለ።
ጴጥሮስ ፍቅሩ የበረታ፣ ንስሓው የልብ ስብራት የነበረው አባት ነው። ጌታውን ሦስት ጊዜ ቢክደውም፣ በፍጹም ዕንባና ንስሓ ተመልሶ “በጎቼን አሰማራ” የሚለውን ታላቅ አደራ ተቀበለ። በጥላው እንኳ ድውያንን የፈወሰው ይኸው ዐለት፣ በሩቅ ሀገራት ወንጌልን ሰብኮ በመጨረሻ ሮም ደረሰ።
የሮሙ ጨካኝ ንጉሥ ኔሮን ከተማዋን አቃጥሎ በክርስቲያኖች ላይ አሳቦ ክርስቲያኖችን ማሳደድና መግደል ጀመረ፣ ጴጥሮስ ከሞት እንዲተርፍ ከሮም አስወጡት በመንገድ ላይ ሳለም ጌታችን መስቀል ተሸክሞ ወደ ሮም ሲገባ አየው። “ጌታ ሆይ ወዴት እየሄድክ ነው?” አለው። ጌታችንም “ልሰቀል ወደ ሮም እሄዳለሁ” አለው። ጴጥሮስ ፍጻሜው እንደደረሰ አውቆ ተመለሰ። ሊሰቅሉት ሲሉ ግን “እንደ ጌታዬ ልሰቀል አይገባኝም፣ ቁልቁል ዘቅዝቃችሁ ሰቀሉኝ” ብሎ ለመናቸው። በ 67 ዓ.ም ሐምሌ 5 ቀን ራሱን ቁልቁል አድርጎ በመስቀል ላይ ተጋድሎውን ፈጸመ።
ምርጡ ዕቃ ቅዱስ ጳውሎስ የዕብራይስጥ ስሙ ሳውል ነበር፤ ህግን የተማረ ቀናተኛ ፈሪሳዊ። መጀመሪያ ላይ ክርስቲያኖችን ያሳደደ፣ የመጀመሪያው ሰማዕት እስጢፋኖስ ሲወገርም የገዳዮችን ልብስ ይጠብቅ ነበር። ነገር ግን ወደ ደማስቆ ክርስቲያኖችን ሊያጠፋ ሲጓዝ፣ ከሰማይ የወረደ ታላቅ ብርሃን መታው፤ “ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ?” የሚል የአምላክን ድምፅ ሰማ።
ከዚያች ሰዓት ጀምሮ ሳውል ጳውሎስ ምርጥ ዕቃ ሆነ! አይኖቹ ታውረው በሐናንያ እጅ ከተጠመቀ በኋላ፣ ፍርሃትን አውልቆ ጣለ። በሦስት ታላላቅ የስብከት ጉዞዎቹ በሺዎች የሚቆጠሩ ኪሎሜትሮችን በእግሩ ተጉዞ አሕዛብንና ነገሥታትን አሳመነ። 14 የእምነትና የፍቅር መልዕክታትን ለዓለም አበረከተ።
በመጨረሻ በኔሮን ዘመን በሮም በጨለማ ቤት ታስሮ ከቆየ በኋላ፣ ሊሰይፉት ወሰዱት። ቀደም ሲል “መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፣ ሩጫውን ጨርሻለሁ፣ ሃይማኖትን ጠብቄአለሁ፤ ወደፊት የጽድቅ አክሊል ይጠብቀኛል” ብሎ እንደጻፈው፣ በደስታና በክብር አንገቱ በሰይፍ ተመተረ።በነገረ መለኮት ምላሱ ዓለምን ያሸበረው ጳውሎስ፣ አንገቱን ለሰይፍ ሰጠ። ሰያፊው ራሱን ሲቆርጠው አስገራሚ ተአምር ሆነ፤ ከደሙ ጋር ወተት ፈሰሰ!
በዚያ የነበረችውና ያዘነችው አንዲት ብላቴና ሳይሰየፍ በፊት ለቅዱስ ጳውሎስ መጎናጸፊያ ሰጠችው፣ የሞት ፍርድ አስፈጻሚው ወታደር ራሱን ቆርጦ በዚያ መጎናፀፊያ ፊቱን ሸፈነው። ሰያፊውም ለንግሱ ሊነግረው ሲመለስ ያቺ ብላቴና አገኘችውና ያ ጳውሎስ ወዴት አለ? ብላ ጠየቀችው እሱም የተቆረጠበት ቦታ ወድቋል ራሱም በመጎናጸፊያ ተሸፍኗል አላት እሷም ዋሽተሃል አለችው ቅዱስ ጳውሎስ በክብርና በዕንቁ አክሊል አጊጦ መጎናጸፊያዋን እንደመለሰላት አሳየችው። ወታደሮቹም ይህን ድንቅ አይተው በክርስቶስ አመኑ፤ ሰማዕትነትንም ተቀበሉ።
(በተጨማሪም በዚሁ ዕለት የ72ቱ አርድእት፣ የቅዱስ ሳቁኤል መልአክ፣ የሰማዕቱ ቅዱስ ይስሐቅና የደብረ ዓሣ ጻድቃን መታሰቢያ ነው)
የቅዱሳን ሐዋርያት የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ረድኤትና በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን! አሜን🙏
2 236
ዛሬ ሐምሌ 3 የእናታችን የእመቤታችን በዓታ ማርያም ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏
ቅድስት ሐና እና ቅዱስ ኢያቄም ለብዙ ዘመናት ልጅ አጥተው ያዘኑ፣ በሰው ዘንድም የተናቁ ነበሩ። ነገር ግን እግዚአብሔር ጸሎታቸውን ሰምቶ አለም ሁሉ የሚድንበትን ድንግል ማርያምን ሰጣቸው። እነርሱም "ልጅ ብናገኝ ለእግዚአብሔር ቤት አገልጋይ አድርገን እንሰጣለን" ብለው የተሳሉትን ስእለት አልረሱም።
ድንግል ማርያም የሦስት ዓመት ሕፃን ስትሆን፣ ወላጆቿ ስእለታቸውን ለመፈጸም ወደ ኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ይዘዋት ሄዱ። ሊቀ ካህናቱ ዘካርያስ በደስታ ተቀበላት። በቤተ መቅደስም ውስጥ ለ12 ዓመታት ስትኖር ምግቧ ከሰማይ የሚወርድ ሰማያዊ መና፣ መጠጧም የሕይወት ውኃ ነበር። ሊቀ መላእክት ቅዱስ ፋኑኤል በብርሃን ክንፎቹ እየጋረዳት፣ ሰማያዊ ምግብ እየመገባት በቅድስና አደገች።
ድንግል ማርያም ለሀገራችን ሰላምን፣ ለሕዝባችን ፍቅርንና አንድነትን ታድለን። አሜን🙏
2 236
ዛሬ ሰኔ 30 በእግዚአብሔር ፊት ታላቅ የሆነው፣ በፅንስ ሳለ ለጌታው የሰገደው፣ የነቢያት መደምደሚያና የሐዋርያት መጀመሪያ የሆነው የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ የልደት በዓል ነው።እንኳን አደረሳችሁ እንኳን አደረሰን🙏
«በእውነት እላችኋለሁ፥ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም…» (ማቴ 11፥11)
ታሪኩ የሚጀምረው በይሁዳ ተራራማ ሀገር ነው። ካህኑ ዘካርያስና ሚስቱ ኤልሳቤጥ በሰው ዓይን መካን፣ በዕድሜም የሸመገሉ ነበሩ። ልጅ የመውለድ ተስፋቸው በምድራዊ ስሌት አብቅቶ ነበር። ነገር ግን እግዚአብሔር የዘካርያስን ጸሎት ሰማ። ታላቁ መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በቤተ መቅደስ ተገልጦ የምስራቹን አበሰረው፦ «ሚስትህ ኤልሳቤጥ ወንድ ልጅ ትወልድልሃለች፥ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ። ደስታና ተደላም ይሆንልሃል በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል።» ሉቃ 1:13-14 ዘካርያስ ነገሩን ማመን ስላቃተው ምልክት እንዲሆነው እስከሚወለድ ድረስ ዲዳ ሆነ።
እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የኤልሳቤጥን መፅነስ በሰማች ጊዜ ልትጠይቃት መጣች። ድንግል ማርያም ሰላምታዋን ስታቀርብ፣ በኤልሳቤጥ ማህፀን የነበረው የስድስት ወር ፅንስ (ዮሐንስ) በደስታ ዘለለ! ገና ሳይወለድ በቅዱስ መንፈስ ተሞልቶ በማህፀን ሳለ ለጌታው ሰገደ። ዛሬ ሰኔ 30 ቀን ህጻኑ ተወለደ።
በስምንተኛውም ቀን ስሙ ማን ይባል። ሲሉ ዘካርያስ በሰሌዳ ላይ «ስሙ ዮሐንስ ነው» ብሎ ጻፈ ትርጉሙም ፍስሃ ወሀሴት ማለት ነው። በዚያው ቅጽበት አንደበቱ ተፈትቶ እግዚአብሔርን ማመስገን ጀመረ።
ይህ ህጻን ግን እንደማንኛውም ልጅ በምቾት አላደገም። ገና በሕፃንነቱ የአባቱን መገደል ተከትሎ፣ እናቱ ኤልሳቤጥ ይዛው ወደ ምድረ በዳ ሸሸች። እናቱ ስታርፍም ዮሐንስ በዚያች አስፈሪ ምድረ በዳ ብቻውን በእግዚአብሔር ጥበቃ አደገ።ልብሱ የግመል ጠጉር፣ በወገቡም ጠፍር ታጥቆ ነበር። ምግቡ አንበጣና የበረሃ ማር ነበር። የሰው ፊት ሳያይ፣ በጾምና በጸሎት፣ ከኃጢአት በራቀ ቅድስና እስከ 30 ዓመቱ በበረሃ ኖረ።
ጊዜው ሲደርስ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ዮሐንስ መጣ። ከበረሃ ወጥቶ በዮርዳኖስ ዙሪያ «መንግስተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ!» እያለ ማስተማር ጀመረ። እርሱ ለብርሃኑ ሊመሰክር የመጣ የብርሃን መብራት፣ የጌታን መንገድ የሚጠርግ «በምድረ በዳ የሚጮህ ሰው ድምፅ» ነበር።
ታሪኩ ከፍታ ላይ የደረሰው የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግደውን የእግዚአብሔርን በግ — ኢየሱስ ክርስቶስን በዮርዳኖስ ወንዝ ሲያጠምቅ ነው። ፈጣሪ በፈቃዱ በፍጡሩ እጅ ተጠመቀ፤ ዮሐንስም የመለኮትን ራስ በመንካቱ «መጥምቀ መለኮት» ተባለ።
ቅዱስ ዮሐንስ እውነትን ለንጉሥም ቢሆን ከመናገር ወደኋላ አላለም። የገሊላው ገዥ ሄሮድስ የወንድሙን ሚስት ሄሮድያዳን በግፍ አግብቶ በነበረ ጊዜ፣ ዮሐንስ ፊት ለፊት ተቃወመው፦ «የወንድምህ ሚስት ለአንተ ልትሆን አልተፈቀደም!» አለው።
በዚህ ምክንያት ወህኒ ወረደ። በመጨረሻም በሄሮድያዳ ተንኮልና በሄሮድስ የትዕቢት መሐላ ምክንያት፣ በዚያው በወህኒ ቤት ሳለ ራሱ በሰይፍ ተቆረጠች። ቅዱስ ዮሐንስ ስለ እውነትና ስለ ጽድቅ ህይወቱን የሰጠ ታላቅ ሰማዕት ሆነ።
የታላቁ ነብይ የመጥምቀ መለኮት የቅድስ ዮሐንስ በረከት፣ምልጃና ጥበቃ ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን🙏
