ch
Feedback
ንቁ ትውልድ-Niku Twld

ንቁ ትውልድ-Niku Twld

前往频道在 Telegram

እኛ ንቁ ትውልዶች ነን!

显示更多
2 364
订阅者
-124 小时
-177
-5230
帖子存档
ዛሬ ሰኔ 5 የፃድቁ አባታችን የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳችሁ🙏 አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስ ከአባታቸው ከቅዱስ ስምኦን ከእናታቸው ከቅድስት አቅሌሲያ በገብርኤል ብስራት መጋቢት 29 ተፀንሰው፣ ታህሳስ 29 በደቡባዊ ግብፅ በንሂሳ አውራጃ ተወለዱ። ከእናት ከአባታቸው ጋር ሶስት ዓመት ከኖሩ በኋላ መላዕክት እየመሩት ወደ ገዳም ወጣ የእናቱን ጡት አልጠባም የዚህን ዓለም ጣዕም አላወቀም። በዛም በብርድና በሀሩር ሳይበገሩ፣ እንደ ሰማይ ወፍ ሳይዘሩና ሳያጭዱ፣ ልብስ ሳይለብሱ፣ ከሰው ተለይተው ለፈጣሪ እየተገዙ ለ300 ዓመት ቆዩ ከዛም ወደ አስራት ሀገራቸው ኢትዮጵያ በመምጣት በዝቋላና በምድረ ከብድ በታላቅ ተጋድሎ 262 ዓመት እህል ሳይበሉ፣ ውሃ ሳይጠጡ ኖረዋል። 100 ዓመት የኢትዮያን ህዝብ ማርልኝ ብለው በዝቋላ ሀይቅ ቁልቁል ተዘቅዝቀው ፀልየዋል። በምድር ላይ እንደ ሰው ሳይሆን እንደ መላዕክት ኖሩ። ንዑድ ክቡር አባታችን ገብረ መንፈስ ቅዱስ ከዚህ ከኀላፊው ዓለም በሞት የሚለይበት ቀን በደረሰ ጊዜ ታመመ ብዙ ስውራን ባህታውያን ወደ እርሱ መጡ ስማቸውም ፍሬ ቅዱስ፣ ዘርዐ ብሩክ፣ያዕቆብ፣ብንያም፣ዮሴፍ ይባላል። አባታችን ታመውም ቢሆን የአምላክን ምስጋና እና ለኀጥአን ምህረትን ከመለመን አላቋረጡም። ሌሊት ስድስት ሰዓት በሆነም ጊዜ ከሰማይ ታላቅ የነጎድጓድ ድምፅ ተሰማ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እመቤታችን ድንግል ማርያምን ፣አስራ ሁለቱን ሐዋርያት፣አስራ አምስቱን ነቢያት፣ በመከራው የመሰሉት ሰማዕታትን ፣አገልጋዮቹ ፃድቃንንና መላዕክቱንም አስከትሎ ወደ አባታችን መጣ። ጌታችንም የታመንክ አገልጋዬ ለስምህ መታሰቢያ ቃልኪዳኔን አፀና ዘንድ እነሆ ወደ አንተ መጣሁ አለው መታሰቢያህን ያደረገውን ፣ስምህን የጠራውን፣በፀሎትህ የተማመነው፣የገድልህን መፅሀፍ የፃፈውን፣ያፃፈውን፣ያነበበውን፣ በፅኑ ልብ አምኖ የሰማውን ሁሉ፣ እስከ ዘላዓለም ድረስ በማይጠፋ በሰማያት ባለ በህይወት መጽሀፍ እኔ ስሙን እጽፋለሁ። ለቤተክርስትያንህ መባ የሚያገባውን ይኸውም ስንዴ፣ዘይት፣እጣን፣ዘቢብ፣ ሌላውንም ንዋየ ቅድሳት በመታሰቢያህ ቀን ያቀረበውን እኔ ሀጥያቱን ይቅር እለዋለሁ። ተደላ ደስታ በሚደረግበት በሺው ዘመን ከእኔ ጋር አስቀምጠዋለሁ ። ለድሆች፣ ለጦም አዳሪዎች የሚራራውን፣ለተራበ የሚያበላውን፣ለተጠማ የሚያጠጣውን፣ጥቂትም ቢሆን ብዙም ቢሆን በአንተ ስም አምኖ ይህን ሁሉ ያደረገውን፣ እኔ በመንግስተ ሰማያት የህይወትን እንጀራ ከአንተ ጋራ አበላዋለሁ። በአንተ ስም የታረዘውን የሚያለብስ፣ የተቸገረውን የሚረዳ፣በመታሰቢያህ ቀን ያዘነውን የሚያረጋጋ፣ባለጽጋም ቢሆን፣ ድሃም ቢሆን፣ ሀጥያቱ የበዛም ቢሆን ሀጥያቱን ትቶ በፀሎትህ ከታመነ የቀደመ በደሉን አላስብበትም፣ የእዳ ደብዳቤውን እደመስስለታለሁ እንዳልበደልም አደርገዋልሁ። ዝክርህን የሚያደርገውን ብቻ የምምርልህ አይደለም እስከ አስራ አምስት ትውልድ ድረስ እምርልሃለሁ እንጂ። ዳግመኛም ለሌሎች ቅዱሳን ያልተሰጠውን ቃል ኪዳን እሰጥሃለሁ መታሰቢያህን ዝክርህን የሚያደርግ፣ እናት አባቱ ሙተው ወደ ሲኦል ከወረዱ በኋላ ከሲኦል አውጥቼ ነፍሳቸውን ለአንተ እሰጥሃለሁ አለው። ከእንግዲስህ ወዲህ ወደ ብርሃን ቤቶች ግባ 12 የብርሃን አክሊልም ሰጠው ከዚ በኋላ ከእርሱ ተሰወረ። በጴጥሮስና በጳውሎስ በዓል በመጋቢት አምስት እሁድ ቀን አረፈ። የመላዕክት ሰራዊትም በክብር፣ በብዙ ምስጋና፣በዕልልታ በነጋሪት ድምፅ ወደ ብርሃን ቤቶች ነፍሱን አስገቧት። በአርያምም ታላቅ ደስታ ሆነ። የጌታችን የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ይቅርታውና ቸርነቱ፣ የአባታችን የገብረ መንፈስ ቅዱስ በረከቱና ረድኤቱ በእኛ በልጆቹና በመላው ህዝበ ክርስትያን እንዲሁም በሀገራችን በኢትዮጵያ፣ ለዘለዓለሙ ፀንቶ ይኑር ። አሜን! 🙏 ምንጭ፡- ገድለ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ

ዛሬ ሰኔ 1 የፃድቁ አባታችን የቅዱስ ዮሴፍ ዓመታዊ የእረፍት በዓል ነው ። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 ዮሴፍ ቅዱስ ያዕቆብ ከራሄል ከወለደችው ሁለት ልጆች አንዱ ሲሆን ቅን፣ታዛዥና የፍቅር ሰው ስለነበር አባቱ ያዕቆብ ከሌሎች ወንድሞቹ አብልጦ ይወደው ነበር። ወንድሞቹም በዚህና እግዚአብሄር ገልጦለት ባየው ህልም ሊነግስብን ነው ብለው ቀኑበት። እሱን ሚያጠምዱበትንም ጊዜ ነው ቦታ ይጠብቁ ነበር። አንድ ቀን ወንድሞቹ ከብቶቻቸውን ለማሰማራት ርቀው ሄዱ። አባታቸው ያዕቆብም የልጆቹን ደኅንነት ለማወቅና ምሳ እንዲያደርስላቸው ዮሴፍን ላከው። ዮሴፍም የአባቱን ትእዛዝ በደስታ ተቀብሎ ሄደ። ከሩቅ ሲመጣ ያዩት ወንድሞቹ ግን የፍቅር እጃቸውን አልዘረጉለትም። ይልቁኑ "ያ ባለ ህልም መጣ፤ ኑ እንግደለውና ህልሙ ምን እንደሚሆን እንይ!" ተባባሉ። በመጨረሻም፣ ሊገድሉት የነበረውን አሳብ አሻሽለው ልብሱን ገፈፉትና ውኃ በሌለበት ጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ጣሉት። ከዚያም ወደ ግብፅ ለሚጓዙ ነጋዴዎች በሃያ ብር በባርነት ሸጡት። የአባታቸውን ልብ ለመስበር ደግሞ፣ የአንድ ፍየል ደም አርደው የዮሴፍን ቀሚስ በደሙ ለወሱት። ወደ አባታቸው ተመልሰው "ይህችን አገኘናት፤ የልጅህ ቀሚስ እንደሆነች እወቅ" አሉት። ያዕቆብም ልብሱን አውቆ "ክፉ አውሬ በላው! " እያለ ምርር ብሎ አለቀሰ፣ ሊጽናናም አልፈለገም። ዮሴፍ በወንድሞቹ ተሸጦ በግብፅ ምድር በጲጢፋራ ቤት ገባ። ነገር ግን ዮሴፍ በሄደበት ሁሉ አንድ የማይለየው ነገር ነበር እርሱም የእግዚአብሔር አብሮነት ነው። ዮሴፍ በጲጢፋራ ቤት ሲያገለግል ተራ ሰራተኛ አልነበረም። ስራውን በታማኝነት፣ በትጋት እና በቅንነት ያከናውን ነበር። ጌታው ጲጢፋራ እግዚአብሔር ከዮሴፍ ጋር እንደሆነና በእጁም የሚደረገው ሁሉ እንደሚከናወን ባየ ጊዜ፣ የቤቱን ኃላፊነትና ያለውን ንብረት ሁሉ ለዮሴፍ አሳልፎ ሰጠው። ዮሴፍ ለጌታው ታማኝ ነበር፤ ቤቱንም እንደራሱ ቤት ይንከባከባል። ዮሴፍ ሥልጣንና ክብር አገኘ፤ ነገር ግን ከበረከት ጋር ፈተናም አብሮ መጣ። የዮሴፍ ውበትና መልከ መልካምነት የጌታውን ሚስት ቀልብ ሳበ። በየቀኑ ኃጢአት እንዲሰራ፣ ታማኝነቱን እንዲያጎድልና ፈጣሪውን እንዲበድል በየቀኑ ትወተውተው፣ታባብለው ነበር። ዮሴፍ ራሱን ሊያሳምን ይችል ነበር። “ማንም አያውቅብኝም... ከቤቴ ርቄያለሁ... ቀድሞውኑ ተበድያለሁ... ለምን ትንሽ ደስታ አላገኝም?” ሊል ይችል ነበር። እሷ በምትገፋፋው ሰዓት ግን ዮሴፍ እንዲህ አለ፦ "ጌታዬ የቤቱን ኃላፊነት ሁሉ ለእኔ ሰጥቶኛል... ካንቺ በቀር በእኔ ላይ ያልተወው ነገር የለም። ታዲያ እኔ እንዴት እንዲህ ያለ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? በእግዚአብሔር ፊትስ እንዴት ኃጢአት እሠራለሁ?" (ዘፍጥረት 39:9) አንድ ቀን በቤቱ ውስጥ ማንም በሌለበት ወቅት ልብሱን ይዛ በሀይል ጎተተችው። በዚያች ቅጽበት ዮሴፍ የወደፊት እጣ ፈንታውን የሚወስን ውሳኔ ወሰነ። ሮጠ! ልብሱን ጥሎላት ሸሸ፤ ክብሩንና ማንነቱን ግን ይዞ ወጣ።ዮሴፍ ለሰው ሳይሆን ለእግዚአብሔር ታማኝ ነበረ። ኃጢአትን የሸሸው ሰው ስለሚያየው ሳይሆን፣ የልብን የሚያይ አምላክ አብሮት እንዳለ ስለሚያውቅ ነው። በንዴትና በውርደት የተሞላችው የጲጢፋራ ሚስት በሀሰት ከሰሰችው። ትቶት የሄደው ልብሱ በእርሱ ላይ እንደ ማስረጃ ቀረበ። ንጹሑ ዮሴፍ ወደ ወህኒ ተጣለ። ታማኝነቱ ዋጋ ያስከፈለው ቢመስልም፣ እግዚአብሔር ግን በወህኒ ቤትም ቢሆን ከእርሱ ጋር ነበር ።ውድቀት የመሰለው ነገር በእውነቱ ወደ ቤተ-መንግሥት የሚወስደው የእግዚአብሔር መንገድ ነበር። እስር ቤቱ ለንግሥናው መሰላል ሆነለት። ንጉሡ ፈርዖን ማንም ሊፈታው ያልቻለውን ሁለት አስጨናቂ ህልሞች አየ። ሰባት የከሱ ላሞችሰባቱን የሰቡ ላሞች ሲውጧቸው፤ እንዲሁም ሰባቱ የጠወለጉ እሸቶች፣ ሰባቱን መልካም እሸቶች ሲውጧቸው አየ። በዚህ ጊዜ የጠጅ አላፊው በወህኒ ቤት ህልም ፈትቶለት የነበረውን ዕብራዊውን ወጣት ዮሴፍን አስታወሰው። ዮሴፍ ከወህኒ ቤት ፈጥኖ ወጣ በንጉሡ ፊትም ቆመ። ህልሙንም እንዲህ ሲል ፈታው፡ "እግዚአብሔር ሊያደርገው ያለውን ለፈርዖን አሳይቶታል። ሰባቱ መልካም ዓመታት በግብፅ ምድር ታላቅ ጥጋብ ይሆናል፤ ከዚያ በኋላ ግን ምድሪቱን የሚያጠፋ ሰባት ዓመት የረሃብ ዘመን ይመጣል። ስለዚህ ንጉሥ ሆይ፣ ጥበበኛ ሰው ፈልገህ በግብፅ ላይ ሹም፤ በጠገቡት ዓመታትም እህል አከማች" አለው። ፈርዖንም በዮሴፍ ጥበብ ተደንቆ ከፈርዖን ቀጥሎ የግብፅ ጠቅላይ ገዥና ባለሥልጣን አደረገው። ዮሴፍም እህልን በጎተራ አከማችቶ ግብፅንና አካባቢዋን በሙሉ ከሚመጣው ከባድ የረሃብ ዘመን አዳናቸው። የረሃብ ዘመኑ በመላው ዓለም በረታ። በከነዓን ምድር የነበረው ያዕቆብና ልጆቹም የሚበሉት አጡ። ያዕቆብ በግብፅ እህል መኖሩን ሰምቶ፣ የዮሴፍን ታናሽ ወንድም ብንያምን አስቀርቶ፣ አስሩን የዮሴፍን ወንድሞች እህል እንዲሸምቱ ወደ ግብፅ ላካቸው። ወንድሞቹ ግብፅ ደርሰው በምድሪቱ ገዥ ፊት ተደፉ። እነርሱ የሸጡትን ወንድማቸውን ጨርሶ አላወቁትም፤ እርሱ ግን ወዲያውኑ አወቃቸው። ሊበቀላቸው ግን አልፈለገም። ማንነቱን ከመግለጡ በፊት ግን በልባቸው ተጸጽተው እንደሆነ ለማወቅ በተለያየ መንገድ ፈተናቸው። በመጨረሻም ወንድሞቹ ላደረጉት በደል እርስ በርሳቸው ሲጸጸቱና ለታናሽ ወንድማቸው ለብንያም ሲጨነቁ ሲያይ፣ የፍቅር ልቡ መቋቋም አልቻለም። የግብፅ ባለሥልጣናትና አገልጋዮች ሁሉ እንዲወጡ ካደረገ በኋላ፣ ድምፁን ከፍ አድርጎ አለቀሰ። "እኔ ወንድማችሁ ዮሴፍ ነኝ! አባቴ በህይወት አለን?" አላቸው። ወንድሞቹ በድንጋጤ ክው ብለው ቀሩ። ዮሴፍ ግን ወደ እርሱ አስጠግቶ እንዲህ አላቸው፡ "ወደዚህ ስለሸጣችሁኝ አትዘኑ፣ አትቆጩም፤ ህይወትን ለማዳን እግዚአብሔር ከእናንተ በፊት ወደዚህ ሰዶኛልና። ክፉ ነገርን አሰባችሁብኝ፣ እግዚአብሔር ግን ዛሬ እንደሆነው ሁሉ ብዙ ህዝብ እንዲድን ለመልካም አደረገው።" ዮሴፍ ክፋት ላደረጉበት ወንድሞቹ ፍጹም ይቅርታን አደረገላቸው። አቅፎም ሳማቸው። ከዚያም አባቱን ያዕቆብንና መላው ቤተሰቡን ወደ ግብፅ አስመጥቶ፣ በለመለመውና ምርጥ በሆነው የጎሸም ምድር እንዲቀመጡ አደረገ፤ በረሃቡም ዘመን ሁሉ መገባቸው። ቅዱስ ዮሴፍ በመንገዱ ሁሉ እግዚአብሔርን አስደስቶ፣ ከአባቱ ያዕቆብም ምርቃትና በረከትን ተቀብሎ፣ በ110 ዓመቱ በመልካም ሽምግልና በዚች ቀን በክብር አርፏል። የፃዱቁ አባታችን የቅዱስ ዮሴፍ በረከትና አማላጅነት ከሁላችን ጋር ይሁን! አሜን🙏

ዛሬ ግንቦት 25 የጻድቁና ሰማዕቱ አቡነ አቢብ (አባ ቡላ) ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳችሁ🙏 በ13ኛው ክፍለ ዘመን በሮሜ ሀገር የኖሩት ደጎቹ ባልና ሚስት አብርሃምና ሐሪክ፣ በወቅቱ በነበረው ከሃዲ ንጉሥ ስደት ቢበረታባቸውም ልጅ በማጣታቸው ዘወትር በጾምና በጸሎት ፈጣሪያቸውን ይለምኑ ነበር። እግዚአብሔርም ጸሎታቸውን ሰምቶ በነገራቸው መሠረት መልኩ ከብርሃን ይልቅ የሚያበራ ወንድ ልጅ ሰጣቸው። እናቱ በፀነሰች ጊዜ በቤታቸው አደባባይ የበቀለው ታላቅ ዛፍ ቅጠል ላይ “የእግዚአብሔር አገልጋይ ቡላ” የሚል የዕብራይስጥ ጽሕፈት ተገኝቶ ነበር። ሕፃኑ የአንድ ዓመት ልጅ ሳለ፣ እመቤታችን ድንግል ማርያም ለሊቀ ጳጳሳቱ ተገልጣ ባዘዘችው መሠረት የክርስትና ጥምቀት ተጠመቀ፤ ስሙም “ቡላ” ተባለ። በዚያው ዕለት ከሰማይ የቊርባን ኅብስትና ወይን ወርዶ ሲቀደስ፣ ሕፃኑ ቡላ አንደበቱ ተከፍቶ ስለ ቅድስት ሥላሴ አንድነትና ሦስትነት በጥልቅ ምስጢር መሰከረ። በ10 ዓመቱ ወላጆቹን ያጣው ሕፃኑ ቡላ፣ ሕዝቡ ለጣዖት እንዲሰግድ የሚያስገድድ መኮንን በመጣ ጊዜ በፊቱ ቆሞ ጣዖታቱን ረገመ። በዚህም ምክንያት ሥጋውን ሰነጣጥቀው ቆዳውን ገፈፉት፣ እጅና እግሩን በመጋዝ ቆረጡት፣ከነፋስ መንኮራኩር ውስጥ ጨምረው በመንገድ ላይ ጎተቱት።ይሁን እንጂ በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ረዳትነት በተአምር ይድን ነበር። በኋላም ሌላ መኮንን ራሱን በሰይፍ እንዲያስቆርጠው ቢያደርግም፣ ቅዱስ ሚካኤል ከሞት አስነስቶ የምንኩስና ልብስና አስኬማ አለበሰው። ከዚያም ወደ ደረቅ ተራራ በመሄድ በታላቅ ተጋድሎ መኖር ጀመረ። የኢየሱስ ክርስቶስን መከራ እያሰበ ከረጅም ዕንጨት ላይ ራሱን ወደ ታች ይወረውር ነበር። በአንድ ወቅት ሰይጣን በቅናት ተነሥቶ በዛፍ ላይ ሲወረወር ቢገድለውም፣ ጌታችን አስነስቶት “የብዙዎች አባት ትሆናለህና ከእንግዲህ ስምህ ቡላ ሳይሆን አቢብ ይባል” አለው። አቡነ አቢብ ለ42 ዓመታት ያህል እህልና ውኃ ሳይቀምሱ፣ ለ12 ወራትም በራሳቸው ተተክለው በመጸለያቸው ናላቸው ፈስሶ አለቀ። በመጨረሻም የጌታን ሕማም እያሰቡ ሰይፍ ተክለው ከዕንጨት ላይ በመውደቅ ሲያርፉ፣ እመቤታችን መጥታ በከበሩ እጆቿ ዳስሳ አስነሳቻቸው። በጥቅምት 25 ቀን ከዚህ ዓለም ድካማቸው የሚያርፉበት ጊዜ ሲደርስ፣ ጌታችን ክርስቶስ ተገልጦ እንዲህ አላቸው። “ወዳጄ አቢብ ሆይ፥ በማያልቅ ተድላ ደስታ ደስ አሰኝህ ዘንድ ወደ እኔ ና፤ ስምህን ለሚጠራ መታሰቢያህን ለሚያደርግ እኔ ኃጢአቱን አስተሠርይለት ዘንደ በራሴ ማልኩልህ፤ ወይም ለተራቆተ የሚያለብሰውን፣ ለተራበም የሚያጠግበውን፣ ለተጠማ የሚያጠጣውን፣ የገድልህን መጽሐፍም የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውንና የሚሰማውን፣ በጸሎትህም የሚታመኑትን ሁሉ እስከ ዐሥር ትውልድ እምራቸዋለሁ፤” ዳግመኛም ታላቅ የምሕረት ቃል ኪዳን ሰጣቸው ጻድቁ አቡነ አቢብ ሰው ሁሉ ሳይመገብ አይውልምና በተመገበ ጊዜ ስማቸውን የጠራውን እንዲምርላቸው ለመኑ። ጌታችንም ለሰዎች ያላቸውን ፍቅር አድንቆ፦ “ከማዕድ በኋላ ‘ስብሐት’ ተብሎ የተረፈውን ‘በእንተ አቡነ አቢብ’ (ስለ አቡነ አቢብ) እያለ ሦስት ጊዜ ቀምሶ የለመነኝን ሁሉ እምርልሃለሁ” አላቸው። አልፎ ተርፎም ያልተጠመቀ አረማዊ እንኳ በዚህ ስም ቢማጸን፣ ወደ ቀናች እምነት ሳይመራ በሞት እንደማይወሰድ ቃል ገባላቸው። በመጨረሻም ጌታችን ነፍሳቸውን በክብር ስሞና በደረቱ አቅፎ ወደ ሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም አወጣት። ዛሬም ምእመናን ከተመገቡ በኋላ ዘወትር ሦስት ጊዜ “በእንተ አቡነ አቢብ” እያሉ በመቅመስ ከበሽታና ከኃጢአት ይፈወሳሉ። የጻድቁና ሰማዕቱ የአቡነ አቢብ ረድኤትና በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን! አሜን🙏 ምንጭ: ገደለ አቡነ አቢብ

ዛሬ ግንቦት 14 ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ዓለምን፣ ንግሥናንና የጫጉላ ቤትን ንቆ የክርስቶስን መስቀል ለመሸከም ከቤት የወጣበት ዕለት ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ የቁስጥንጥንያው ንጉሥ ቴዎዶስዮስ እና የንግሥት መርኬዛ ብቸኛ ልጅ ነበር። በምግብና በሃይማኖት ተንከባክበው አሳደጉት። ለአካለ መጠን ሲደርስም፣ የአባቱን መንግሥት እንዲወርስ አስበው የሮሙን ንጉሥ ልጅ አጋቡት።ነገር ግን እርሱ የሰማዩን ንግሥና እንጂ የምድሩን አላለመም! በሠርጉ ዕለት ሌሊት፣ እርሱም ሆነ ሙሽራይቱ ድንግልናቸውን እንደጠበቁ፣ የጫጉላ ቤቱን ጥሎ በምስጢር ወጣ። ቅዱሱ ንግሥናውንና ሃብቱን ጥሎ ወደ ሩቅ ሀገር ተሰደደ። በቤተክርስቲያን ደጅ ወድቆ ከነዳያን ጋር መኖር ጀመረ። የሚለምነውንና የሚያገኘውን ሁሉ ለሌሎች እየመጸወተ፣ በጾምና በጸሎት ለ15 ዓመታት በተጋድሎ ኖረ።የእግዚአብሔር ምስጢር ሲገለጥና ጽድቁ በሰው ዘንድ መታወቅ ሲጀምር፣ "ውዳሴ ከንቱን ልሽሽ" ብሎ በድጋሚ በመርከብ ተሳፈረ። ነገር ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ ሌላ ነበር፤ መርከቢቱ ሳታስበው ወስዳ የአባቱ ደጅ ላይ ጣለችው! ገብረ ክርስቶስ ወደ ቤተሰቦቹ ቤት አልገባም፤ ማንነቱንም አልገለጠም። ይልቁንም በአባቱ ደጅ እንደ መጻተኛ ወድቆ፣ ለአባቱ ውሾች የሚሰጠውን ፍርፋሪ እየተመገበ ሌላ 15 ዓመታት ኖረ! የአባቱ አሽከሮች እጣቢና ቆሻሻ ይደፉበት ነበር። እርሱ ግን ሁሉን በትዕግሥት ቻለ። የሰው ልጅ ጨክኖበት ቆሻሻ ሲደፋበት፣ የአባቱ ውሾች ግን መጥተው የእግሩን ቁስል ይልሱለት ነበር! በአጠቃላይ ለ30 ዓመታት ሙሉ (15 ዓመት በስደት፣ 15 ዓመት በአባቱ ደጅ) ስለ ክርስቶስ ፍቅር ሲል ራሱን አዋረደ። በመጨረሻም ጌታችን ከቅዱሳን መላእክትና ጻድቃን ጋር ተገልጦ ታላቅ ቃልኪዳን ሰጠው፤ ክብርት ነፍሱንም በክብር ተቀበለ። ያረፈ ዕለት(ጥቅምት 14) በቁስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳስ አባ ቴዎፍሎስ መሪነት ሥጋው ሲፈለግ፣ በአባቱ ደጅ ወድቆ ተገኘ። በእጁ ላይ በጥብቅ የተያዘች ጥቅል ወረቀት ነበረች። ከብዙ ጸሎት በኋላ ወረቀቱ ከእጁ ተለቆ ሲነበብ፣ ገብረ ክርስቶስ ስለ አምላኩ ፍቅር በአባቱ ደጅ ያሳለፈውን መከራ ራሱ በዝርዝር የጻፈው ታሪኩ ኖረ! ንጉሥ አባቱና እናቱ ይህንን ሲሰሙ ኀዘናቸው ወሰን አጣ። ይበልጥ የሚያስገርመው ግን፣ ያቺ በሠርጉ ዕለት የተዋት የሮሙ ንጉሥ ልጅ (ሙሽራይቱ) ለባሏ ታማኝ ሆና፣ 30 ዓመታት ሙሉ በእናትና አባቱ ቤት ስትጠብቀው መኖሯ ነበር! ታሪኩን ስትሰማ ልቧ በኀዘን ተሰበረ። ሊቃውንት እንዲህ ይላሉ "ሁለት ዓይን የተሰጠን በአንዱ የራሳችንን፣ በሌላው የሌላውን ለማየት ነው። ሁለት ጆሮ የተሰጠን በአንዱ የራሳችንን፣ በሌላው የሌላውን ለመስማት ነው። ሁለት እጅ የተሰጠን በአንዱ ለመስጠት፣ በሌላው ለመቀበል ነው። ሁለት እግር የተሰጠን በአንዱ ወደ ራሳችን፣ በሌላው ወደ ሌላው ለመሄድ ነው።" የሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ታሪክ ስለ ፍቅር፣ ስለ ትዕግሥትና ስለ መለገስ ያስተምረናል። እኛስ ለሌሎች የምንሰጥበት፣ የሌሎችን ችግር የምናይበት ልብ አለን? የጻድቁ አባታችን የሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ረድኤትና በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን! አሜን🙏

ዛሬ ሚያዚያ 29 ከሌሎች ቅዱሳን ለየት ያለ ታሪክ ያላቸው የአቡነ ፄዋ ለጽድቅ ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 አቡነ ፄዋ ለጽድቅ ከመጠመቃቸውና ወደ ቅድስና ከመምጣታቸው በፊት ስጋ ለበስ የአየር አጋንንት ነበሩ። ስማቸውም "መጥቆራ" ይባል ነበር።የአቡነ ፄዋ ለጽድቅ አባት "ፈረጎ" የተባለ የአየር አጋንንት ሲሆን እናቱ ደግሞ "ሰዓሪተ ሰንበት" የምትባል ኃጢአተኛ ሴት ነበረች። በመንገድ ስትሄድ ደክሟት አረፍ ባለችበት ያ የአየር አጋንንት ተገናኝቷት "መጥቆራ" የተባለውና ሁለት ክንፍ ያለው ኃይለኛ ጋኔን ተወለደ። መጥቆራም እንደ አባቱ በአየር እየበረረ የክፋት ሥራን ይሠራ ነበር። በዘመኑ የነበሩት ታላቁ አባታችን አቡነ ተክለሃይማኖትና አቡነ ዜና ማርቆስ ወንጌልን ሲሰብኩና ለፀሎት ሲቆሙ ይህ ጋኔን እጅግ ይፈትናቸው ነበር። ሆኖም ወደ ፈጣሪ ፀልየው በመስቀሉ ቢያማትቡበት ተንቀጥቅጦ ከእግራቸው ሥር ወደቀ፤ በጻድቃኑ ፊት ቀርቦም "ምን ላድርግ? እንዴትስ ድኅነት አገኛለሁ?" ብሎ ጠየቀ። ንስሃ ገባ ከዚያም በአቡነ ዜና ማርቆስ ገዳም (ደብረ ብስራት) እየታዘዘ፣ የሰው ልጅ ሊሠራው የማይችለውን ከባድ ሥራ መሥራት ጀመረ።ይህ ለአጋንንት ፍጥረት የማይታሰብና የማይቻል የሚመስል ነገር ነበር። ነገር ግን በእግዚአብሔር ዘንድ ሁሉ ይቻላል። አቡነ ተክለ ሃይማኖትና አቡነ ዜና ማርቆስ መጥቆራ ወደ ሰው አርአያነት እንዲመለስ ወደ ፈጣሪ ለመኑ። አምላክም ልመናቸውን ሰምቶ፣ በሰው ክንድ 140 የነበረው ቁመቱ ተለወጠ፤ መልኩም የቀዳማዊ አዳምን መሰለ። ከዚያም በሥላሴ ስም ተጠምቆ "ፄዋ ለጽድቅ" (ለጽድቅ የተማረከ) የሚል ስም ተሰጠው። "ጋኔን እንዴት ሰው ይሆናል?" ለሚሉ መጽሐፍ ቅዱስ ንጉሥ ናቡከደነጾር በትዕቢቱ ምክንያት ወደ እንስሳነት ተለውጦ ቆይቶ፣ በንስሐ ሲመለስ እግዚአብሔር ወደ ቀድሞ የሰው ባሕርይው እንደመለሰው ይነግረናል (ዳን 4፡28-37)። መሐሪው አምላክ መጥቆራንም ይቅር ብሎ ለጽድቅ አበቃው። አቡነ ፄዋ ለጽድቅ ከተጠመቁ በኋላ ከአቡነ ተክለሃይማኖትና ከአቡነ ዜና ማርቆስ ዘንድ እየተማሩና እያገለገሉ በታላቅ ተጋድሎ ኖሩ። ከቀድሞው ክፉ ግብራቸው ሙሉ በሙሉ ተለይተው፣ የትሕትና፣ የፍቅርና የጸሎት አባት ሆኑ። ህዳር 29 ተጋድሏቸውን ጨርሰው አረፉ። ስርዓተ ቀብራቸውም በኢትዮጵያ በሚገኘው በእንደቅላላ አቡነ ፄዋ ለጽድቅ ገዳም ተፈፀመ። ጌታችንም ስለ ተጋድሏቸው ፅኑ የምህረት ቃል ኪዳን ሰጣቸው "በመጨረሻው ዘመን ክብራቸው የሚገለጠውና ለሰው ልጆች ድኅነት የሚሆኑት" ተብለው ትንቢት ተነገረላቸው። ይህ ቃል ኪዳን ጻድቁ በዓለም መጨረሻ ላይ ለሰው ልጆች የመዳን ምክንያት መሆናቸውን ያሳያል። ጋኔን እንኳ ንስሐ ገብቶ ለጽድቅ ከበቃ፣ እኛ የሰው ልጆች ተስፋ የምንቆርጥበት ምን ምክንያት አለን? የአባታችን ታሪክ የእግዚአብሔርን ወሰን የሌለው ምሕረትና ንስሐ ለመግባትና ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ ለማንኛውም ፍጥረት ጊዜው እንዳልረፈደ ትልቅ ማሳያ ነው። የጻድቁ አቡነ ፄዋ ለጽድቅ ረድኤትና በረከት፣ የአባቶቻችን የአቡነ ተክለሃይማኖትና የአቡነ ዜና ማርቆስ ምልጃ አይለየን አሜን🙏

ዛሬ ሚያዚያ 26 የኢትዮጵያዊው ፃድቅ የአቡነ ሀብተ ማርያም ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 ከዚህም በኋላ ሰይጣን መጥቶ በእግዚአብሔር ፊት ቆመና አቤቱ ጌታየ በሀብተ ማርያም መ
ዛሬ ሚያዚያ 26 የኢትዮጵያዊው ፃድቅ የአቡነ ሀብተ ማርያም ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 ከዚህም በኋላ ሰይጣን መጥቶ በእግዚአብሔር ፊት ቆመና አቤቱ ጌታየ በሀብተ ማርያም መከራ አጸናበት ዘንድ ፍቀድልኝ ብሎ ጮኾ ተናገረ፣ እንደ ኢዮብ ብዙ መከራ ሳይቀበል እንደ አብርሃም ጽኑ ኀዘን ሳይታገስ በከንቱ ትወደዋለህና ብሎ ተካሰሰ፣ ጸዋትዎ መከራውን ከተቀበለ በኋላ ይሰድበሃልና ብሎ ጌታየ መከራ አመጣበት ዘንድ ፍቀድልኝ ሲል ሰማው ስለዚህ እንባየ በጉንጩ እስኪፈስ ድረስ ብዙውን አለቀስኩ፤ ፈጣሪየን የሐሰት ምስክር ተነሥቶብኛልና ሰውነቴን መከራ ለሚያጸናባት አሳልፈህ አትስጣት ብየ ለመንሁት፤ ሰይጣንማ መከራ አጸናበት ዘንድ ፍቀድልኝ እንጅ አቤቱ ሥራ እንደ ፈታ ይቀር ዘንድ አትተወው ብሎ አዘነ፣ በመከራ ከተፈተነ በኋላ በደግነቱ ጸንቶ ከተገኘ በእውነት ደግ እንደ ሆነ በዚህ አውቃለሁ አለ፤ እግዚአብሔር ግን በሰይጣን ላይ ተቆጥቶ በነፍሱም በሥጋውም መከራ ታጸናበት ዘንድ አልፈቅድም አለው፤ እኔ ከእናቱ ማኅፀን ጀምሮ መርጨዋለሁና በንጽሕናም አጽድቼዋለሁ ኃጢኦት እንዳይሠራ ዘወትር እጠብቀዋለሁ፣ በእርሱ ላይ ማሰልጠንስ ይቅርና በሀብተ ማርያም ጸሎት በተማጸነኝ ሁሉ ላይ እንኳን አላሠለጥንህም አለው። ሠይጣንም ይህን ቃል ሰምቶ ስለ አፈረ እያዘነ ሄደ፤ እኔም ለወገኖቹ ኃይልን፣ ጽንዕን ለሚሰጥ ለእግዚአብሔር እየሰገድሁ ክብር ምስጋና የሚገባው እርሱን አመሰገንሁት ። ምንጭ:- ገደለ አቡነ ሀብተ ማርያም አምላካችን በፃድቁ አቡነ ሀብተ ማርያም ምልጃና ፀሎት ከጠላት ወጥመድ ይጠብቀን አሜን🙏

ዛሬ ሚያዚያ 25 የታላቁ ሰማዕት የቅዱስ መርቆሬዎስ ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 በ፪ኛው (2ኛው) ክፍለ ዘመን ሮም ውስጥ ከአረማዊ ቤተሰብ የተወለደው ቅዱስ መርቆሬዎስ፣ የቀድሞ ስሙ "ፒሉፓዴር" ነበር። የአባቱ ስም አሮስ የእናቱም ስም ሲዲሮስ ነበር። አባቱ በዱር ለአደን ሳለ በአራዊት ሊበላ ሲል በመለኮታዊ ጥበቃ ዳነ ከእርሱ ሚወለድ መልካም ፍሬ አለና። በኋላ ቤተሰቡ በሙሉ ወደ ክርስትና ተመለሱ። የክርስትና ስምንም አገኙ አባቱ ኖህ፣ እናቱም ታቦት፣ ልጃቸውም መርቆሬዎስ ተባለ ትርጉምም የአብ ወዳጅ አንድም የክርስቶስ አገልጋልይ ማለት ነው። መርቆሬዎስ በወጣትነቱ የሮም ወታደር በመሆን ተቀጠረ፤ በሰውነቱ ጥንካሬና በውጊያ ብቃቱም በንጉሥ ዳክዮስ ዘንድ እጅግ ተወደደ። የሮም መንግሥት ከበርባሮች ጋር በገጠመው አስፈሪ ጦርነት ወቅት፣ መርቆሬዎስና ወታደሮቹ ሊሸነፉ ተቃርበው ነበር። በዚያን ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ገብርኤል በታላቅ ብርሃን ተገልጦ የሚነድ ሰይፍ ሰጠውና እንዲህ አለው፦ "መርቆሬዎስ ሆይ! አትፍራ፤ በዚህ ሰይፍ ጠላቶችህን ድል ታደርጋለህ። ካሸነፍክ በኋላ ግን አምላክህን እንዳትረሳ።" መርቆሬዎስም በሁለቱ ሰይፎች (በምድራዊውና ከመልአኩ በተቀበለው) ጠላቶቹን ድል አድርጎ ተመለሰ። የሁለት ሰይፎች አባት(ባለቤት) ሚባለውም ለዚ ነው። ንጉሥ ዳክዮስ ከድሉ በኋላ ለጣዖታቱ መሥዋዕት እንዲያቀርብ መርቆሬዎስን ባዘዘው ጊዜ፣ ቅዱስ መርቆሬዎስ ፈቃደኛ አልሆነም። "እኔ የክርስቶስ ባሪያ ነኝ እንጂ የጣዖት አምላኪ አይደለሁም" በማለት ክብሩንና ማዕረጉን በሙሉ ጥሎ ክርስትናውን መሰከረ። ንጉሡም እጅግ ተቆጥቶ በሰይፍ እንዲቀላ እስከታዘዘበት ጊዜ ድረስ በተለያዩ አስፈሪና ፅኑ ስቃዮች እንዲያልፍ አደረገው። ሰማዕቱ ግን በመልአኩ እርዳታ እየዳነ ጽናቱን አሳየ። በመጨረሻም ቅዱስ መርቆሬዎስ ሕዳር ፳፭ (25) ቀን በሰማዕትነት ዐረፈ። ቅዱስ መርቆሬዎስ በሰማዕትነት ካረፈ በኋላ በ፬ኛው (4ኛው) ክፍለ ዘመን የነገሠው ንጉሥ ዩልያኖስ ክርስትናን ክዶ ወደ ጣዖት አምልኮ በመመለስ በክርስቲያኖች ላይ ታላቅ መከራ አውጆ ነበር። በዚያን ጊዜ ቅዱስ ባስልዮስ እና ቅዱስ ጎርጎሪዮስ የቤተክርስቲያን መሪዎች ነበሩ። ዩልያኖስ ወደ ፋርስ ጦርነት ከመሄዱ በፊት ቅዱስ ባስልዮስን፦ "ከጦርነት ስመለስ የከተማዋን ክርስቲያኖች በሙሉ እፈጃለሁ፣ ቤተክርስቲያንንም አጠፋለሁ" በማለት ዛተባቸው። ቅዱስ ባስልዮስና አማኞች በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ጮኹ። ቅዱስ ባስልዮስ በቤተክርስቲያን ውስጥ ሆኖ ሲጸልይ፣ በግድግዳው ላይ ተሥሎ የነበረውን የቅዱስ መርቆሬዎስን ስዕል ይመለከት ነበር። ድንገት ግን የቅዱስ መርቆሬዎስ ስዕል ከመቀመጫው ጠፋ፤ የያዘው ሰይፍም በቦታው አልነበረም። በዚያው ሰዓት ቅዱስ መርቆሬዎስ በጦር ሜዳ ላይ የነበረውን ንጉሥ ዩልያኖስን በጦር ወግቶ ገደለው ።በቤተክርስቲያን ውስጥ ሲጸልይ የነበረው ቅዱስ ባስልዮስ ከጥቂት ጊዜ በኋላ የቅዱስ መርቆሬዎስ ስዕል ወደ ቦታው ተመልሶ ተመለከተ። ነገር ግን በዚህ ጊዜ በስዕሉ ላይ ያለው የቅዱስ መርቆሬዎስ ሰይፍ በደም ተለውሶ ነበር። ታላቁ ሰማዕት ቤተክርስቲያንን ከጠላቶችዋ የታደገና ክርስትና እንዲቀጥል ያደረገ ታላቅ ባለውለታ ነው። ዛሬም ድረስ በቃል ኪዳኑ የሚማጸኑትን ሁሉ ከፈተና የሚጠብቅ ኃያል ሰማዕት ነው። የታላቁ ሰማዕት የቅዱስ መርቆሬዎስ ምልጃና ጥበቃ ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን🙏

ዛሬ ሚያዝያ 23 የኢትዮጵያ ገበዝ፣የልዳ ኮከብ፣ የሊቀ ሰማዕታት የቅዱስ ጊዮርጊስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 በቤተክርስቲያን ታሪክ እንደ ቅዱስ ጊዮርጊስ መከራን በትዕግሥት የተቀበለ፣ እንደ እርሱም ያለ ተአምራትን የገለጠ ሰማዕት የለም። ሚያዝያ 23 ቀን ሰባት ዓመታት የቆየው ታላቅ ተጋድሎው በድል ተፈጸመ። ቅዱስ ጊዮርጊስ ስለ ክርስቶስ ፍቅር ሲል 70 በሚሆኑ ጨካኝ ነገሥታት ፊት ቆመ። እነርሱም በልዩ ልዩ ስቃይና መከራ ሊያሸንፉት ሞከሩ። በነዚህ ሰባት ዓመታት ውስጥ ሶስት ጊዜ ሞቶ በእግዚአብሔር ኃይል ተነስቷል። እያንዳንዱ ሞቱና ትንሣኤው ለአሕዛብ ድንቅ ምልክት ሆኖ ብዙዎችን ወደ እምነት መርቷል። በቅዱስ ጊዮርጊስ ጽናትና ተአምራት ተማርከው የንጉሥ ዱድያኖስ ሚስት እለእስክንድርያን ጨምሮ፣ ብዙ የንጉሡ መኳንንትና ወታደሮች የጣዖት አምልኮን ትተው በክርስቶስ አመኑ። መከራው ማሰቃያ ሳይሆን የብዙዎች የመዳን ምክንያት ሆነ። በሰማዕትነት የሚያርፍበት ሰዓት በደረሰ ጊዜ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ ፈጣሪው ጸለየ። ያን ጊዜ ከሰማይ እሳት ወርዶ ሰባት ዓመት ሲያሰቃዪት የነበሩትን ሰባውን ነገሥታትና ጨካኙን ዱድያኖስን አጠፋቸው። ከዚያም ጌታችን ለቅዱስ ጊዮርጊስ ተገልጦለት ታላቅ የምህረት ቃል ኪዳን ሰጠው። "ስምህን የጠራውን፣ መታሰቢያህን ያደረገውንና በቃል ኪዳንህ የተማጸነውን ሁሉ እምርልሃለሁ" አለው። ዳግመኛም ለሌሎች ቅዱሳን ያልሰጠውን ቃልኪዳን ሰጠው በመከራና በጭንቅ ውስጥ ሆኖ "አምላከ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሆይ እርዳኝ!" ብሎ ሦስት ጊዜ የጠራኝን ሰው ሁሉ፣ እኔ ራሴ ፈጥኜ በመድረስ ከመከራው ሁሉ አድነዋለሁ፤ እረዳዋለሁም።" አለው። ቅዱስ ጊዮርጊስ ለሰዎች ሁሉ የሚሆን የምህረት ቃል ኪዳን ከተቀበለ በኋላ፣ ሚያዝያ 23 በ 303 ዓ.ም በ 27 ዓመቱ አንገቱን ተሰይፎ በሰማዕትነት አረፈ። የሊቀ ሰማዕታት፣የፍጡነ ረድኤት የቅዱስ ጊዮርጊስ ረድኤትና በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን🙏

ዛሬ ሚያዚያ 22 የሊቀ መላዕክት የቅዱስ ዑራኤል ወርሃዊ መታሰቢያ ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 ታሪኩ የሚጀምረው የእግዚአብሔር ሕዝብ በባቢሎን ምርኮ በነበሩበት ዘመን ነው። ነቢዩ ዕዝራ (ዕዝራ ሱቱኤል) ስለ ቅድስት ከተማ ጽዮን መፈራረስ፣ ስለ ወገኖቹ መሰደድና መገፋት፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ በጦርነቱ ወቅት የእግዚአብሔር ሕግ የተጻፈባቸው ቅዱሳት መጻሕፍት በመቃጠላቸው ልቡ በሐዘን ተሰበረ። ዕዝራ "ሕጉ ከጠፋ ሕዝቡ እንዴት ይመራል? ትውልዱስ እንዴት ፈጣሪውን ያውቃል?" ብሎ በመጨነቅ ወደ ምድረ ራፌድ ወጣ። በዚያም መሪር ዕንባን እያፈሰሰ፣ ስለ ወገኖቹና ስለ መጻሕፍቱ መጥፋት እያለቀሰ 40 ቀንና 40 ሌሊት በጾምና በጸሎት ተቀመጠ። ዕዝራ ጾሙንና ጸሎቱን በፈጸመ ጊዜ፣ ልዑል እግዚአብሔር ምስጢር ገላጭ የሆነውን ታላቁን መልአክ ቅዱስ ዑራኤልን ወደ እርሱ ላከው። ቅዱስ ዑራኤልም በእጁ "የእሳት ጽዋ" ይዞ ከሰማይ ወረደ። መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ዕዝራን እንዲህ አለው፦ "አፍህን ክፈት፣ ይህንንም የጥበብ ጽዋ ጠጣ"። ዕዝራም አፉን ከፈተ፤ ያን የእሳት ጽዋም ጠጣው። እዝራ ሱቱኤል 13: 38 ያን ጊዜ የዕዝራ ልቡና እንደ ብርሃን በራ! የተሰወረ ምስጢር ተገለጠለት። የጠፉትና የተቃጠሉት መጻሕፍት ሁሉ በቃሉ ተቀረጹለት(ተገለጡለት)። ከዚያ በኋላ ዕዝራ አምስት ጸሐፊዎችን አዘጋጅቶ፣ ቅዱስ ዑራኤል የገለጠለትን ምስጢርና ትምህርት በ40 ቀናት ውስጥ መጻሕፍትን በቃሉ እየነገራቸው መልሰው እንዲጽፉ አደረገ። በዚህም ምክንያት ዕዝራ "ዳግማዊ ሙሴ" ተብሎ ይጠራል። የቅዱስ ዑራኤል ተራዳኢነትና የነቢዩ ዕዝራ በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን! ሊቀ መላዕክት ቅዱስ ዑራኤል ጥበቡን፣ እውቀቱንና ምስጢሩን ለሁላችንም ይግለጥልን አሜን🙏

በመንፈሳዊ ህይወት ውስጥ ትልቅ ለመሆን መጀመሪያ ትንሽ መሆንን፣ ከፍ ለማለት ደግሞ ዝቅ ማለትን በተግባር ያሳዩን ታላቁ አባት አቡነ ዮሐንስ ሐፂር ዛሬ ሚያዚያ 20 ወርሃዊ መታሰቢያቸው ነው። እንኳን አደረሰን አደረሳቹ🙏 "ሐፂር" ማለት በግዕዝ "አጭር" ማለት ሲሆን፣ ጻድቁ በቁመታቸው አጭር ቢሆኑም በመንፈሳዊ ቁመናቸው ግን ሰማይ የደረሱ ታላቅ አባት ናቸው። ዮሐንስ ሐፂር ገና በ18 ዓመታቸው የዓለምን ግርግር ትተው ወደ እስቄጥስ ገዳም ገቡ። በዚያም በአባ ባይሞይ እጅ እየተመሩ የመንፈሳዊ ህይወትን መሠረት መማር ጀመሩ። አባታችን ገና ከጅምሩ የታወቁት በጾምና በጸሎት ብቻ ሳይሆን፣ ለቃለ አበው ባላቸው ፍጹም "መታዘዝ" ነበር። መምህራቸው አባ ባይሞይ የዮሐንስን ትሕትናና መታዘዝ ለዓለም ለማሳየት አንድ ፈተና አቀረቡላቸው። አንድ የደረቀ እንጨት ሰጧቸውና እንዲህ አሏቸው፦ "ይህን ደረቅ እንጨት ትከለውና ውኃ እያጠጣህ አብቅለው፤ ፍሬ እስኪያፈራም ተንከባከበው።" ማንኛውም ሰው በምክንያት "ደረቅ እንጨት እንዴት ይበቅላል?" ብሎ ሊጠራጠር ይችላል። ዮሐንስ ግን ምንም ጥያቄ አላነሱም። "እሺ አባቴ" ብለው ተቀበሉ። ለሦስት ዓመታት ሙሉ፣ ውሃ ከሚገኝበት ሩቅ ቦታ በቀን ሁለት ጊዜ እየተመላለሱ ያንን የደረቀ እንጨት አጠጡት። ከሦስት ዓመት በኋላ ያ ደረቅ እንጨት በተአምር ለመለመ! ታላቅ ዛፍ ሆኖ አብቦና አፍርቶ ጣፋጭ ፍሬ ሰጠ። አባ ባይሞይም ፍሬውን ለሌሎች ቅዱሳን እያደሉ እንዲህ አሉ፦ "የታዛዡንና የትሑቱን ሰው ፍሬ እንሆ ቅመሱ!" ዛሬም ድረስ በግብፅ በገዳመ አስቄጥስ ውስጥ ያ ዛፍ "የመታዘዝ ዛፍ" (Tree of Obedience) ተብሎ እንደ ቆመ ይነገራል። አቡነ ዮሐንስ በትሕትናቸውና በተጋድሎአቸው እጅግ ከፍ ስላሉ፣ መለኮታዊ ሚስጥር ተገለጠላቸው። ቀና ቢሉ "ሥሉስ ቅዱስን" በግርማ መንግሥታቸው ይመለከታሉ፤ ዝቅ ቢሉ ደግሞ ኃጥአን የሚቀጡበትን "እንጦሮጦስን" ያያሉ። ጌታችንም ስለ ታዛዥነታቸው በገሃድ እየተገለጠ ያነጋግራቸው ነበር። የታላቁ አባት የቅዱስ ዮሐንስ ሐፂር በረከታቸው ይደርብን። የደረቀውን ህይወታችንና የከሰመው ተስፋችንን ያለምልሙልን አሜን🙏

ብዙ ጊዜ ስለ ለውጥ ስናስብ ወይም አንድን ነገር ለማሳካት ስንነሳ አይምሮአችን ላይ ሚመጣው ነገር ይሳካ ይሆን ፣ ማድረግ እችል ይሆን ? እወድቅ ይሆን? የሚል አፍራሽ ሃሳብ ነው። እነዚንና ሌላም ገ
ብዙ ጊዜ ስለ ለውጥ ስናስብ ወይም አንድን ነገር ለማሳካት ስንነሳ አይምሮአችን ላይ ሚመጣው ነገር ይሳካ ይሆን ፣ ማድረግ እችል ይሆን ? እወድቅ ይሆን? የሚል አፍራሽ ሃሳብ ነው። እነዚንና ሌላም ገዳቢ ሃሳቦችን እያሰብን ገና ሳንጀምረው ጉልበታችን ይዝላል። እስከሚሆን ድረስ ሁል ጊዜ የማይቻል ይመስላል ይለናል ኔልሰን ማንዴላ፤ ካልሞከርንና ካልጣርን መስራቱንና መሳካቱን ማወቅ አንችልም እናም ተወዳጆች የምትፈልጉት ነገር ምንም ይሁን ምን እንደሚሳካ አስቀድማቹ እመኑ ከዛ ለተግባራዊነቱ ተንቀሳቀሱ ምትችሉትን ሁሉ አድርጉ። መልካም ቀን🙏