የወረቀት ብር ኖት ዘካ
~~~
በጥንት
ዘመን ሰዎች ግብይት የሚፈፅሙት እቃን በእቃ በመለዋወጥ ነበር። የልውውጥ ገበያ ለአጠቃቀም አስቸጋሪ በመሆኑ የተነሳ ቀስ በቀስ እየቀዘቀዘ ሄዶ አንዳንድ እቃዎችን (ለምሳሌ በሃገራችን አሞሌ ጨው) እንደመገበያያ ገንዘብ በመጠቃቀም ተተካ። ይሁን እንጂ እነዚህ እቃዎች ለአያያዝ አስቸጋሪ በመሆናቸው የተነሳ ሰዎች ወደ ሌሎች አማራጮች ማማተር ይጀምራሉ። በዚህም የተነሳ ነበር ወርቅና ብር ለመገበያያነት መዋል የጀመሩት። ወርቅና ብር ታዲያ በጊዜ ሂደት በአንጣሪዎች አማካኝነት ተመሳሳይ መጠንና ክብደት እንዲይዙ ተደርገው ለአስተማማኝነታቸው ማህተም ዲዛይን ተደርጎባቸው መዘጋጀት ያዙ። እነዚህን ገንዘቦች ለደህንነታቸው በመስጋት ገንዘብ መንዛሪዎችና አንጥረኞች ዘንድ በማስቀመጥ መተማመኛ ደረሰኞችን በምትካቸው ይቀበሉ ነበር። ሰዎች በነዚህ ድርጅቶች ላይ ያላቸው እምነት በጨመረ ቁጥር ደርሰኞቹ በግብይት ላይ ለክፍያ መዋል ያዙ።
የወረቀት ብር ኖት ታሪካዊ አነሳሱ በዚህ መልኩ ነበር። በጊዜው እነዚህ ከገንዘብ መንዛሪ ድርጅቶች የሚመጡ ወረቀቶች ሰውየው በነዚህ የግል ድርጅቶች ዘንድ ወርቅ/ ብር እንዳስቀመጠ በመግለፅ ወረቀቱን የተቀበለ ሰው ሄዶ ወርቁን/ ብሩን መውሰድ እንደሚችል ከመጠቆም ባለፈ ኦፊሴላዊ ይዘትም ሆነ የህግ ከለላ አልነበራቸውም። አገልግሎታቸው በሰፋ ቁጥር ግን በጊዜ ሂደት መንግስታት የህግ ሽፋን ሊሰጡ ግድ ብሏቸዋል። በዚህን ጊዜ የታወቀ ተመን በመስጠት ላምጪው እንዲከፈል አስገዳጅ ህግ ወጣ። የማተሙ/ የማሳተሙ ኃላፊነትም የመንግስታት ሆነ። ይህ ነገር የተጀመረው በ1833 እንደሆነ ድርሳናት ይጠቁማሉ። (ዘመኑ በሙሉ እንደ ጎርጎሮሳውያን አቆጣጠር ነው።)
መንግስታት ካላቸው ተቀማጭ የወርቅ መጠን በላይ እነዚህን የወረቀት መገበያያዎች ገበያ ላይ ሲያቀርቡ ጊዜ ግን በነባሩ የወርቅ መገበያያ ላይ ፈተና ተደቀነ። በዚህን ጊዜ የወረቀት መገበያያዎችን ወደ ወርቅ ከመቀየር የሚከለክል ህግ መውጣት ያዘ። በዚህ ረገድ ቀዳሚዋ ብሪታኒያ ስትሆን ይህ የሆነውም በ1931 ነበር። አሜሪካ በ1934 ተከተለቻት። የክልከላው ተግባራዊነት ግን ድንበር ተሻጋሪ ሳይሆን በሃገራቱ ውስጥ የተገደበ ነበር። ሃገራት ከሃገራት ጋር ሲገበያዩ ግን የወረቀት ብሩን ወደ ወርቅ የመቀየር ውላቸውን ይጠብቁ ነበር። ከ1971 ጀምሮ ግን የወርቅ መጠን እያነሰ ስለመጣ አሜሪካ ይህንኛውን አሰራር ጭምር አቆመች። የመጨረሻው ወርቅን ለግብይት ተመን የመጠቀም አሰራር በዚህ መልኩ ተዘጋ።
የወረቀት ብር ኖት እነዚህን ታሪካዊ ለውጦች በማሳለፉ የተነሳ ምንነቱን በመግለፅ ላይ የኢስላም ምሁራን እይታቸው ሊለያይ ችሏል። የብዙሃን ዑለማዎችን አቋም ብቻ ሳሰፍር የወረቀት ብር ማለት እራሱን የቻለ የተለየ መገበያያ ገንዘብ ሲሆን ወርቅና ብርን (ሲልቨር) የሚመለከቱ ህጎች ይመለከቱታል። የየሃገራቱ የወረቀት ኖት እራሱን የቻለ አንዱ ከሌላው የሚለይ ገንዘብ ነው። ለማሳጠር ስል ለዚህ ትርጓሜ የሚውሉ አጋዥ መረጃዎችን አልጠቅስም።
እነዚህ የወረቀት ብር ኖት ሲጀመሩ አካባቢ ዘካ ይወጅብባቸዋል ወይስ አይወጅብባቸውም በሚለው ላይ በኢስላም ምሁራን መካከል ውዝግብ ተከስቶ ነበር። የልዩነቱ መነሻ ለዚህ ገንዘብ ምንነት የተሰጡ ትርጓሜዎች መለያየት ነበር። ነገር ግን ይሄ መገበያያ በከፍተኛ መጠን በመስፋፋቱና የወርቅና የብርን ቦታ በመተካቱ የተነሳ ውዝግቡ ሙሉ ለሙሉ በሚባል መልኩ ከስሟል። ስለዚህ ትኩረታችን ይህ የወረቀት ብር ኖት ለዘካ መጠን በሚደርስበት መነሻ ተመን (ኒሷብ) ላይ ይገደባል ማለት ነው።
የወረቀት ብር ኖት ዘካ የሚወጅብበት መነሻው ተመን (ኒሷብ) ስንት ነው? በዚህ ላይ ሶስት የተለያዩ ሃሳቦች ተሰንዝረዋል።
አንደኛ:– የወረቀት መገበያያ ኖት መነሻ የዘካ ተመን የብር (ሲልቨር፣ ፊዷ) ኒሷብ ነው ያሉ አሉ። ይህም 200 ዲርሃም ማለትም 595 ግራም ነው።
ሁለተኛ:– ኒሷቡ የወርቅ ኒሷብ ማለትም 20 ዲናር ውይም 85 ግራም ነው ያሉም አሉ።
ሶስተኛ:– መነሻው መጠን ከወርቅና ከብር መነሻ ተመኖች ዝቅ ያለው ነው ያሉም አሉ።
ከሶስቱ ሃሳቦች ውስጥ ሶስተኛው ሚዛን የሚደፋ እንደሆነ በርካታ ዑለማዎች ደምድመዋል። መነሻቸውም:–
1ኛ፦ ድሃዎቹን የተሻለ ተጠቃሚ ያደርጋል።
2ኛ፦ ለዘካ አውጪውም ከውዝግብ ቀጠና ለመውጣት፣ ከተጠያቂነት ስጋት ለመትረፍ ይበልጥ ሰላማዊ ነው።
3ኛ፦ የመጀምሪያዎቹን ሁለት አቋሞች ያንፀባረቁ ምሁራን የሚያቀርቧቸውን መርጃዎችና ትንታኔዎች አንፃራዊ በሆነ መልኩ የተሻለ የሚያቀራርብ ነው።
4ኛ፦ ለዚህ የወረቀት መገበያያ ኖት የዘካ ተመን ከወርቅና ከብር (ሲልቨር) አንዱን መጠቀም ግድ ከሆነ ከሁለት አንዱ ቀድሞ የደረሰውን ኒሷብ በምን አሳማኝ መነሻ ልንዘለው እንችላለን? እንደሚታወቀው የብር (ሲልቨር) ኒሷብ ዛሬም በነብዩ ﷺ ዘመን ከነበረው አይቀየርም። ዛሬም እንደ ጥንቱ 200 ዲርሃም ማለትም 595 ግራም ብር ያለው ሰው ዘካ ማውጣት ግድ ይለዋል።
ይህ አቋም የሰዑዲያ የታላላቅ ዑለማእ ምክር ቤት፣ የእውቀታዊ ምርምር ቋሚ ኮሚቴ (ለጅነተ ዳኢማህ)፣ በራቢጦተል ዓለሚል ኢስላሚ ስር ያለው ቀራረል መጅመዒል ፊቅሂይ እና የሌሎችም ምርጫ ነው።
የዘንድሮ የወረቀት ብር ዘካ መነሻ (ሂሳብ) ስንት ነው?
````````
`````````
የሚችል ሰው
ወቅታዊን የወርቅና የብር ዋጋ አጣርቶ በራሱ ማስላት ይችላል። በኔ በኩል በተወሰኑ ወንድሞች አማካኝነት ለማጣራት እንደሞከርኩት ወቅታዊ (የ 2014) ወርቅ የሚሸጥበት ዋጋ በግራም ከ 3800 እስከ 4,500 ብር ነው። የብር መሸጫ ዋጋ ደግሞ ከ 120 እስከ 150 ብር ነው። ስለዚህ፡
[ሀ] የወርቅ ዘካ ኒሷብ የሆነውን 20 ዲናር (85 ግራም) በወቅቱ ዋጋ 3,800 ብር ስናባዛው 323,000 ብር ሲሆን
[ለ] የብር ዘካ ኒሷብ ደግሞ 200 ዲርሃም (595 ግራም) በወቅቱ ዋጋ 120 ብር ሲባዛ 71,400 ብር ይሆናል። ስለዚህ ከሁለቱ ኒሷቦች የብሩ ስለሚያንስ ከላይ በቀረበው 3ኛው አቋም መሰረት ለዚህ አመት (1443 ሂጅሪያ) ይህንን መጠን 71,400 መነሻ እናደርጋለን ማለት ነው። እናም 71,400 ብር እና የበለጠ አመት የቆየ ብር ያለው ሰው ዘካ ማውጣት ግድ ይለዋል ማለት ነው። ስለሆነም ለዘካ መጠን የደረሰ ገንዘብ ኖሮት አመት ከቆየ የገንዘቡን የ1/10ኛውን እሩብ ማለትም 2.5% ዘካ ያወጣል ማለት ነው። ስሌቱን ግልፅ ለማድረግ ጥቂት ምሳሌዎችን ልስጥ፦
1– አመት የዞረ 300,000 ብር ያለው ሰው የ 300,000ን 2.5% ያወጣል፡፡ 300,000 x 0.025=7,500 ብር
2– አመት የዞረ 450,000 ብር ያለው ሰው የ 450,000ን 2.5% ያወጣል፡፡ 450,000 x 0.025=11,250 ብር
3– አመት የዞረ 5 ሚሊዮን ብር ያለው ሰው የ 5,000,000ን 2.5% ያወጣል፡፡ 5,000,000 x 0.025=125,000 ብር ይሆናል ማለት ነው። ወይም ደግሞ አጠቃላይ ገንዘቡን ለ40 ቢያካፍለው ማውጣት ያለበትን የዘካ መጠን ይሰጠዋል። የቀረቡትን ምሳሌዎች ለ40 ቢያካፈል ተመሳሳይ መጠን ያገኛል።
ማሳሰቢያ፦
~
በብሄራዊ ባንክ በኩል የሚወጣውን የወርቅና የብር ዋጋ ያልተጠቀምኩት ህዝብ የሚገባያይበት ትክክለኛ ዋጋ ነው ብየ ስላላመንኩበት ነው። ወሏሁ አዕለም።
(ረመዳን 15/1442፣ ሚያዚያ 20/ 2013)
https://t.me/IbnuMunewor