8 594
Subscribers
+224 hours
+297 days
+13130 days
Posts Archive
ኢትዮጵያውያንን ጨምሮ 54 ሺህ የዲቪ ሎተሪ አሸናፊዎች የፍርድ ቤት ውሳኔ አገኙ
ዕለተ ሰኞ ጳጉሜን 2 – 2018 ረቢዕ አል አወል 25 – 1448
የአሜሪካ የፌዴራል ፍርድ ቤት በግሪን ካርድ ሂደቶች ላይ ገደብ ተጥለው የነበሩ ፖሊሲዎችን ውድቅ በማድረግ ኢትዮጵያን ጨምሮ ለ49 አፍሪካ ሀገራት ዜጎች የሚደግፍ ውሳኔ አሳልፏል።
የካሊፎርኒያው የአሜሪካ ዲስትሪክት ዳኛ ኤድዋርድ ዳቪላ በዲቪ አመልካቾች ላይ ተጥለው የነበሩ በርካታ ገደቦችን በጊዜያዊነት አግደዋል፡፡ ከነዚህም መካከል በታኅሣሥ 2018 በአንዳንድ የዲቪ ማመልከቻዎች ላይ የተጣለው ዕገዳ እና ከዚያ ቀደም ብሎ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የተደረገው የቪዛ ዕጣ ማቋረጥ ይገኙበታል።
የፍርድ ቤቱን ውሳኔ ተከተሎ የዲቪ አሸናፊ የነበሩ አመልካቾች ሂደታቸውን ለመቀጠል የሕግ በር ከፍቶላቸዋል ተብሏል። በዚህም አመልካቾች እስከ መስከረም 20 ድረስ ሰነዶቻቸውን ማቅረብ እና የተመደቡላቸውን ቃለ-መጠይቆች መከታተል እንደሚችሉም ተገልጿል።
በተያዘው ዓመት ታኅሣሥ ወር በብራውን ዩኒቨርሲቲ የሁለት ሰዎች ሕይወት ያለፈበትን የጅምላ ተኩስ ጥቃት ተከተሎ የፕሬዝዳንት ትራምፕ አስተዳደር የአሜሪካን የዲቪ ግሪን ካርድ ሎተሪ ፕሮግራም ማገዱን ማስታወቁ ይታወሳል።
ይህም ውሳኔ የተላለፈው ጥቃቱን የፈጸመው የ48 ዓመቱ የፖርቹጋል ዜጋ እ.ኤ.አ. በ2017 በዲቪ ሎተሪ ፕሮግራም አማካኝነት ወደ አሜሪካ የገባ እና የግሪን ካርድ መብት ያገኘ እንደነበር ከተገለጸ በኋላ ነው።
የወቅቱ የሀገር ውስጥ ደህንነት ሚኒስትሯ ክርስቲ ኖም በጊዜው እንደተናገሩት፣ በፕሬዝዳንት ትራምፕ መመሪያ መሠረት “ከዚህ አደገኛ ፕሮግራም ተጨማሪ አሜሪካውያን ላይ ጉዳት እንዳይደርስ ለማረጋገጥ” የቪዛ ፕሮግራሙ ታግዷል።
ቢዝነስ ኢንሳይደር አፍሪካ እንደዘገበው፣ ውሳኔው በተለይ ለዲቪ 2026 ከፍተኛ ድርሻ ላላቸው የአፍሪካ ሀገራት ትልቅ ትርጉም ይኖረዋል፡፡ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መረጃ መሠረት ከ49 የአፍሪካ ሀገራት የተወጣጡ 53 ሺህ 939 ሰዎች ተመዝግበዋል።
ይሁን እንጂ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፕሮግራሙን የማጣራት እና የመፈተሽ ሂደቶች መልሶ በመገምገም ላይ በመሆኑ ከነሐሴ 25 አንስቶ የዲቪ ቪዛ ህትመትን በሙሉ እንደገና በጊዜያዊነት አግዶታል።
በዚህም አመልካቾች ማስረጃዎቻቸውን ማቅረብ እና ቃለ መጠይቆችን ማድረግ ቢችሉም በዚህ የእገዳ ወቅት ምንም ዓይነት የዲቪ ቪዛ የማይሰጥ በመሆኑ አሁንም ስጋት አሳድሯል ተብሏል። የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እንደገለጸው እስከ መስከረም 20 ድረስ ቪዛቸውን ያላገኙ ወይም የስደተኝነት ደረጃቸውን ያላስተካከሉ አሸናፊዎች ዕድሉን ሙሉ በሙሉ እንደሚያጡት ነው።
በአፍሪካ የዲቪ ሎተሪ አሸናፊዎችን በመያዝ ከፍተኛ ቁጥር ካላቸው ሀገራት ውስጥ ግብፅ፣ አልጄሪያ እና ሱዳን እያንዳንዳቸው 5 ሺሕ በላይ የቪዛ አመልካቾች ያሏቸው ሲሆን ኢትዮጵያም ከ3 ሺሕ 200 በላይ እንዳላት ተጠቅሷል። (ሚንበር ቲቪ)
+3
ሙጀመዑ ተቅዋ መስጂድ ለአንድ ዓመት የቁርኣን ሒፍዝ ሲከታተሉ የቆዩ ተማሪዎች ተመረቁ
በአዲስ አበባ ኮልፌ ቀራንዮ ክፍለ ከተማ የሚገኘው ሙጀመዑ ተቅዋ መስጂድ፤ የመጀመሪያዎቹን 25 የቁርኣን ሒፍዝ ተሚሪዎች እሑድ ጳጉሜን 1/2018 አስመርቋል። በምርቃት ሥነ ሥርዓቱ ላይ እንደተገለጸው፣ ተማሪዎቹ በቁርኣን ሒፍዝ ጥናት የቆዩት ለአንድ ዓመት ነው።
በሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኙት የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የፕሬዝዳንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ኡስታዝ አቡበከር አሕመድ፣ ተመራቂ ተማሪዎች የተሸከሙትን አማና ትልቅነት በመረዳት ጉዟቸውን በማስተዋል እንዲሆን የአደራ መልዕክት አስተላልፈዋል።
የመስጂዱ ኻጢብ ኡስታዝ ካሚል ሸምሱ በበኩላቸው፣ ስለ መርከዙ የመማር ማስተማር ሒደት ገልፀዋል። በዚህም በአሁኑ ሰዓት ከአዳሪ ተማሪዎቹ ጎን ለጎን ከ400 በላይ ተመላላሽ ተማሪዎችን ተቀብሎ በማስተማር ላይ ይገኛል ብለዋል።
በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሸይኽ ሐጅ ኢብራሂም ቱፋ እና የአዲስ አበባ እስልምና ጉዳዮች ከፍተኛ ምክር ቤት ፕሬዝዳንት ሸይኽ ሐጅ ሡልጣን አማንን ጨምሮ በርካታ እንግዶች ተሣታፊ ሆነዋል። (ሚንበር ቲቪ)
+1
ተጨማሪ መረጃ፡ በአዲስ አበባ ከተማ አዲስ ከተማ ክፍለ ከተማ፣ ወረዳ 08 ልዩ ቦታው ከአመዴ ገበያ ዝቅ ብሎ በሚገኘው ሸማ ተራ አካባቢ በሚገኙ ሱቆች ላይ አጋጥሞ የነበረው ድንገተኛ የእሳት አደጋ ሙሉ በሙሉ በቁጥጥር ስር ውሏል ሲል የእሳት አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን አስታውቋል።
የእሳት አደጋው መንስኤ እንዲሁም የደረሰው የጉዳት መጠን በባለሙያዎች በጥረት እየተጣራ እንደሚገኝም ኮሚሽኑ ገልጿል። (ሚንበር ቲቪ)
+1
#ኸበር፡ በአዲስ አበባ ከተማ ትልቁ የከተማዋ የገበያ ማዕከል መርካቶ በተከሰተ የእሳት አደጋ በርካታ መደብሮች ላይ ቃጠሎ መድረሱን ሚንበር ቲቪ በሥፍራው ከሚገኙ የዓይን እማኞች ሰምቷል። እንደ ዓይን እማኞች ከሆነ በአሁኑ ሰዓት በሥፍራው የተከሰተውን የእሳት አደጋ ለመከላከል የአደጋ ጊዜ ሠራተኞች ቢሠማሩም እስከ ምሽቱ 3:00 ድረስ በቁጥጥር ስር አልዋለም። በተለምዶ አጠራሩ በታችኛው ጣሳ ተራ አካባቢ የእሳት አደጋው የተነሳው አመሻሽ ላይ መሆኑ ተገልጿል። (ሚንበር ቲቪ)
የመዲናዋ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ የአከራይና ተከራይ ውል እድሳት ማጠናቀቂያ የጊዜ ገደብን ለመጨረሻ ጊዜ ማራዘሙን ገለጸ
የአዲስ አበባ ከተማ ቤቶች ልማትና አስተዳደር ቢሮ የአከራይና ተከራይ ውል እድሳት ማጠናቀቂያ የጊዜ ገደብን ለመጨረሻ ጊዜ እስከ ጳጉሜ 5/2018 ተራዝሟል ሲል አሳውቋል።
የውል ምዝገባው ከሐምሌ 1/2018 ጀምሮ ሲሰጥ መቆየቱን ያስታወሰው ቢሮው፣ እስከ ነሐሴ 30/2018 እንዲጠናቀቅ ጊዜ ገደብ አስቀምጦ የነበረ ቢሆንም፣ አስፈላጊ ቅድመ ሁኔታዎችን በጊዜው አሟልተው ያልቀረቡ፣ በተሰጠው የጊዜ ገደብ በልዩ ልዩ ምክንያት ከአዲስ አበባና ከሀገር ውጭ የነበሩ ተዋዋዮች መኖራቸውን መረዳቱን ገልጿል።
የተሰጠው የመጨረሻ ዕድል በኅብረተሰቡ ተደጋጋሚ ጥያቄ መሰረት የተሰጠ ነው ብሏል።
በመሆኑም እስከ ዛሬ ውላቸውን ያላደሱ ሁሉም አከራዮችና ተከራዮች ይህንን የመጨረሻ እድል በመጠቀም እስከ ጳጉሜ 5/2018 ድረስ በክፍለ ከተሞች፣ በሁሉም የመሶብ አንድ ማዕከላት እና ለዚሁ አገልግሎት በተዘጋጁ ቦታዎች በመቅረብ ውላቸውን እንዲያድሱ ቢሮው ጥሪ አቅርቧል። (ሚንበር ቲቪ)
በዓመት 20 ሚሊዮን ገደማ ሕፃናት በኢንተርኔት አማካኝነት ለጾታዊ ጥቃት ተጋልጠዋል - ዩኒሴፍ
የተባበሩት መንግሥታት የሕፃናት መርጃ ድርጅት (ዩኒሴፍ)፤ በየዓመቱ ኢትዮጵያን ጨምሮ በ21 ሀገራት የሚገኙ ወደ 20 ሚሊዮን የሚጠጉ ሕፃናት በዲጂታል ቴክኖሎጂዎች አማካኝነት ለጾታዊ ጥቃት ወይም ብዝበዛ መጋለጣቸውን አዲስ ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል።
ዩኔሴፍ በሪፖርቱ፤ በአፍሪካ፣ እስያ፣ ላቲን አሜሪካ እና ካሪቢያን እንዲሁም ምሥራቅ አውሮፓ ባሉ ሀገራት የሚገኙ ዕድሜያቸው ከ12 እስከ 17 ዓመት ከሆኑ አምስት ሕጻናት አንዱ ለዲጂታል መድረኮች ጥቃት ተጋላጭ ነው፡፡
“Through Children's Eyes: How Digital Technologies Enable Child Sexual Abuse” በተሰኘው በዚህ ሪፖርት ላይ እንደተመላከተው፤ 15 ሚሊዮን ገደማ ሕፃናት ያለፍላጎታቸው የጾታዊ ይዘት ያላቸውን ምሥሎችና ቪዲዮዎች እንዲመለከቱ ተደርገዋል።
ተጨማሪ ዝርዝሩን በድረ ገጽ ያንብቡ፦ https://minbertv.com/?p=11771
ኒውዮርክ ከተማ እስከ 8ኛ ክፍል ባሉ ተማሪዎች ላይ የሰው ሰራሽ አስተውሎት አጠቃቀምን አገደች
ዕለተ ሐሙስ ነሐሴ 28 – 2018 ረቢዕ አል አወል 21 – 1448
የኒውዮርክ ከተማ ከንቲባ ዞህራን ማምዳኒ በ2019 ትምህርት ዘመን በከተማቸው የሚገኙ እስከ ስምንተኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች የሰው ሰራሽ አስተውሎት (ኤአይ) ቴክኖሎጂዎችን እንዳይጠቀሙ መታገዳቸውን አስታውቀዋል። ከንቲባው ይህን ባስታወቁበት መግለጫ፤ “ልጆች ለመማር እና ለማደግ መምሕራን እና ሰዋዊ ግንኙነት ያስፈልጋቸዋል” ብለዋል።
አክለውም ከእኩዮቻቸው ጋር በመሆን ክህሎቶችን ማዳበር፣ ከመምሕራን ጋር ግንኙነት መገንባት እና ፈታኝ ችግሮችን በራሳቸው መጋፈጥ አለባቸው ብለዋል። ርምጃው በአሜሪካ የኤአይ አጠቃቀምን በመግታት ረገድ ሰፊ ሽፋን ያለው እንደሆነ የተገለጸ ሲሆን፣ ወደ 600 ሺሕ ገደማ የመንግሥት ትምህርት ቤት ተማሪዎችን ያካተተ ነው።
እገዳው ተማሪዎችን ኢላማ ያደረጉ የትኞቹንም የሰው ሰራሽ አስተውሎት ሶፍትዌሮችን በሙሉ የሚያካትት ቢሆንም ለመምህራን የመማር ማስተማር እንቅስቃሴያቸውን እንዲያከናውኑ እና ለተቋማዊ ሥራዎች መጠቀም እንደሚችሉ ይፈቅዳል። ይህም የሚሆነው መምህራን የኒው ዮርክ ከተማን የመንግሥት ትምህርት ቤቶች የደኅንነት መስፈርቶች እስካሟሉ ድረስ ብቻ ነው፡፡
ከመምህራን በተጨማሪም አካል ጉዳተኛ ተማሪዎች፣ የቋንቋ ተማሪዎች እና እንደ ኮምፒውተር ሣይንስ ባሉ ለሥራ ዝግጁነት በሚያሰለጥኑ ፕሮግራሞች ላይ የሚሳተፉ ተማሪዎች የሚጠቀሙባቸው አጋዥ ቴክኖሎጂዎች በእገዳው ውስጥ አለመካተታቸው ተጠቅሷል።
የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች በአንጻሩ በዓመት ሁለት ጊዜ የኤአይ እውቀትና ግንዛቤ ትምህርቶችን የሚያገኙበት ሥልጠና እንደሚሰጣቸው ተገልጿል። ትምህርቱ ስለ ኤአይ ምንነት፣ ሊኖሩት ስለሚችሉ አድሎዎች፣ አደጋዎች፣ የሥነ ምግባር እሴቶች እና በወደፊት ሥራዎችና ክህሎቶች ላይ ስላለው ተፅዕኖ የሚዳስሱ ሁለት የ45 ደቂቃ ክፍለ ጊዜዎችን ያካተተ ይሆናል።
የከተማዋ የትምህርት ፖሊሲ በተማሪዎች የዲጂታል ስክሪን እይታ ጊዜ ላይም ገደብ የጣለ ሲሆን ከ3ኛ እስከ 5ኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች በቀን ቢበዛ 30 ደቂቃ፣ ከ6ኛ እስከ 8ኛ ክፍል ላሉት ደግሞ በቀን ቢበዛ 45 ደቂቃ እንዲጠቀሙ ይመክራል ሲል አናዶሉ ዘግቧል። (ሚንበር ቲቪ)
በአውስትራሊያ በፍሊንደርስ ዩኒቨርሲቲ የሚገኙ ተመራማሪዎች ቡና እና ሻይ በዕድሜ የገፉ ሴቶች አጥንት ጤና ላይ የተለያየ ተፅዕኖ ሊኖራቸው እንደሚችል የሚያሳይ አዲስ ጥናት ይፋ አድርገዋል። በኒውትሪየንትስ የሳይንስ መጽሔት ላይ የታተመው ጥናቱ ዕድሜያቸው 65 እና ከዚያ በላይ የሆኑ ወደ 10 ሺሕ ገደማ ሴቶች ላይ ለ10 ዓመታት ያህል ክትትል አድርጓል፡፡
ተመራማሪዎቹ አዘውትሮ ቡና እና ሻይ መጠጣት የአጥንት ማዕድን ጥግግት (Bone Mineral Density - BMD) ለውጥ ጋር የሚገናኝ መሆኑን መርምረዋል። የሕክምና ባለሞያዎች የአጥንት ማዕድን ጥግግት የሚሉት በአንድ የተወሰነ የአጥንት ሥፋት ወይም መጠን ውስጥ የሚገኘውን ካልሲየም እና ሌሎች አስፈላጊ ማዕድናት መጠን የሚመዝን የሕክምና መለኪያ ነው፡፡ ይህ መለኪያ የአጥንትን ጠንካሬ እና የመሰበር ተጋላጭነት ለማወቅ ያገለግላል፡፡
የአጥንት መሸርሸር በዓለም ዙሪያ ዋና የጤና ችግር ነው ተብሎ ይታሰባል። በተለይም ዕድሜያቸው ከ50 በላይ ከሆኑ ሦስት ሴቶች መካከል አንዷን የሚያጠቃ ሲሆን፣ በየዓመቱ ለሚከሰቱ በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ የአጥንት ስብራቶች በምክንያት ይጠቀሳል፡፡
የፍሊንደርስ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ከአጥንት መሸርሸርና ስብራት ጥናት የተገኘ መረጃን ተጠቅመው የተሳታፊዎችን የመጠጣት ልማድ እና የአጥንት ጥግግትን በተደጋጋሚ ገምግመዋል። በዚህም የዳሌ እና የጭን አጥንቶች ለስብራት አደጋ ተጋላጭ ሆነው ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። በ10 ዓመቱ የጥናት ወቅት ሴቶቹ ምን ያህል ቡና እና ሻይ እንደሚጠጡ ዘወትር ያሳውቁ የነበረ ሲሆን፣ ተመራማሪዎቹ የአጥንት ጥግግት ለውጦችን ለመከታተል የላቁ የምስል መከታተያ ዘዴዎችን ተጠቅመዋል።
በግኝቱም ቡና የሚጠቀሙ ሴቶች ላይ የነበረው ውጤት ሻይ ከሚጠቀሙት የተለየ ሆኖ ያገኘው ሲሆን በቀን ከአምስት ሲኒ በላይ የሚጠጡ ሴቶች አነስተኛ የአጥንት ጥግግት እንደነበራቸው ገልጿል። ይህም እጅግ ከፍተኛ የቡና አጠቃቀም አሉታዊ ተፅዕኖ ሊኖረው እንደሚችል ይጠቁማል ብሏል። ሆኖም በቀን ከሁለት እስከ ሶስት ሲኒ የሚደርስ መካከለኛ መጠን ያለው ቡና መጠጣት በአንጻሩ በአጥንት ጤና ላይ ከሚደርስ ጉዳት ጋር አለመያያዙን አክሏል። በጥናቱ ሻይ የሚጠጡ ሴቶች ሻይ ካልጠጡት ጋር ሲነፃፀሩ መጠነኛ ከፍ ያለ የአጠቃላይ ዳሌ አጥንት እንዳላቸው አሳይቷል።
ውጤቱ ከቡና እና ሻይ በተጨማሪ በሌሎች የጤና እና የሕይወት ዘይቤ ሁኔታዎች ላይ ተመስርቶ የተለያየ እንደሆነም ተገልጿል። በህይወት ዘመናቸው ከፍተኛ የአልኮል አጠቃቀም የነበራቸው ሴቶች ከቡና ጋር የተያያዘ የከፋ አሉታዊ ተፅዕኖ አስተናግደዋል ብሏል።
በአውስትራሊያ በፍሊንደርስ ዩኒቨርሲቲ የሚገኙ ተመራማሪዎች ቡና እና ሻይ በዕድሜ የገፉ ሴቶች አጥንት ጤና ላይ የተለያየ ተፅዕኖ ሊኖራቸው እንደሚችል የሚያሳይ አዲስ ጥናት ይፋ አድርገዋል። በኒውትሪየንትስ የሳይንስ መጽሔት ላይ የታተመው ጥናቱ ዕድሜያቸው 65 እና ከዚያ በላይ የሆኑ ወደ 10 ሺሕ ገደማ ሴቶች ላይ ለ10 ዓመታት ያህል ክትትል አድርጓል፡፡
ተመራማሪዎቹ አዘውትሮ ቡና እና ሻይ መጠጣት የአጥንት ማዕድን ጥግግት (Bone Mineral Density - BMD) ለውጥ ጋር የሚገናኝ መሆኑን መርምረዋል። የሕክምና ባለሞያዎች የአጥንት ማዕድን ጥግግት የሚሉት በአንድ የተወሰነ የአጥንት ሥፋት ወይም መጠን ውስጥ የሚገኘውን ካልሲየም እና ሌሎች አስፈላጊ ማዕድናት መጠን የሚመዝን የሕክምና መለኪያ ነው፡፡ ይህ መለኪያ የአጥንትን ጠንካሬ እና የመሰበር ተጋላጭነት ለማወቅ ያገለግላል፡፡
የአጥንት መሸርሸር በዓለም ዙሪያ ዋና የጤና ችግር ነው ተብሎ ይታሰባል። በተለይም ዕድሜያቸው ከ50 በላይ ከሆኑ ሦስት ሴቶች መካከል አንዷን የሚያጠቃ ሲሆን፣ በየዓመቱ ለሚከሰቱ በሚሊዮኖች ለሚቆጠሩ የአጥንት ስብራቶች በምክንያት ይጠቀሳል፡፡
የፍሊንደርስ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎች ከአጥንት መሸርሸርና ስብራት ጥናት የተገኘ መረጃን ተጠቅመው የተሳታፊዎችን የመጠጣት ልማድ እና የአጥንት ጥግግትን በተደጋጋሚ ገምግመዋል። በዚህም የዳሌ እና የጭን አጥንቶች ለስብራት አደጋ ተጋላጭ ሆነው ማግኘታቸውን ጠቅሰዋል። በ10 ዓመቱ የጥናት ወቅት ሴቶቹ ምን ያህል ቡና እና ሻይ እንደሚጠጡ ዘወትር ያሳውቁ የነበረ ሲሆን፣ ተመራማሪዎቹ የአጥንት ጥግግት ለውጦችን ለመከታተል የላቁ የምስል መከታተያ ዘዴዎችን ተጠቅመዋል።
በግኝቱም ቡና የሚጠቀሙ ሴቶች ላይ የነበረው ውጤት ሻይ ከሚጠቀሙት የተለየ ሆኖ ያገኘው ሲሆን በቀን ከአምስት ሲኒ በላይ የሚጠጡ ሴቶች አነስተኛ የአጥንት ጥግግት እንደነበራቸው ገልጿል። ይህም እጅግ ከፍተኛ የቡና አጠቃቀም አሉታዊ ተፅዕኖ ሊኖረው እንደሚችል ይጠቁማል ብሏል። ሆኖም በቀን ከሁለት እስከ ሶስት ሲኒ የሚደርስ መካከለኛ መጠን ያለው ቡና መጠጣት በአንጻሩ በአጥንት ጤና ላይ ከሚደርስ ጉዳት ጋር አለመያያዙን አክሏል። በጥናቱ ሻይ የሚጠጡ ሴቶች ሻይ ካልጠጡት ጋር ሲነፃፀሩ መጠነኛ ከፍ ያለ የአጠቃላይ ዳሌ አጥንት እንዳላቸው አሳይቷል።
ውጤቱ ከቡና እና ሻይ በተጨማሪ በሌሎች የጤና እና የሕይወት ዘይቤ ሁኔታዎች ላይ ተመስርቶ የተለያየ እንደሆነም ተገልጿል። በህይወት ዘመናቸው ከፍተኛ የአልኮል አጠቃቀም የነበራቸው ሴቶች ከቡና ጋር የተያያዘ የከፋ አሉታዊ ተፅዕኖ አስተናግደዋል ብሏል።
ማዕከላዊው የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ፤ ከዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን (IFC) ጋር የቤት መግዣ ብድር መልሶ ማጠናከሪያ ኩባንያ ለማቋቋም የሚያስችል የትብብር ማዕቀፍ መፈራረሙን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ገልጸዋል፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ይህን ይፋ ያደረጉት ዛሬ ሐሙስ ነሐሴ 28/2018 ነው፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዳሉት ከሆነ ኩባንያው በ100 ቢሊዮን የኢትዮጵያ ብር ካፒታል የተቋቋመ ሲሆን፣ በዓለም አቀፍ የፋይናንስ ኮርፖሬሽን ደግሞ 200 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ አስተዋፅኦ የሚደረግበት ነው፡፡ ይህ ተቋም በባንክ ዘርፍ ውስጥ የጥሬ ገንዘብ ፍሰት አለመመጣጠንን የሚቀርፍ እና በመላው ኢትዮጵያ ተደራሽ የሚሆን የቤት መግዣ ብድር ፋይናንስን የሚያስገኝ ይሆናል ብለዋል፡፡
ይህ አጋርነት በተመጣጣኝ ዋጋ የሚገነቡና የኢትዮጵያውያንን ክብር የጠበቁ 1.5 ሚሊዮን ቤቶችን ለማቅረብ እንዲሁም በፋይናንስ ሥርዓታችን ውስጥ የግል ዘርፉን ተሳትፎ ለማስፋት የተቀመጠውን ግብ የሚያሳካ ወሳኝ ርምጃ ነው ሲሉም አብራርተዋል፡፡
የፋይናንስ ባለሞያዎች እንደሚናገሩት፣ የቤት መግዣ ብድር መልሶ ማጠናከሪያ በፋይናንስ ዘርፍ ውስጥ ባንኮችና የብድር ተቋማት ለቤት መሥሪያ ወይም መግዣ የሚሰጡትን የረዥም ጊዜ ብድር (Mortgage) የሚያጠናክር እና የገንዘብ እጥረት እንዳይኖርባቸው ፈንድ (ገንዘብ) የሚያቀርብ ተቋም ነው፡፡
በተለመደው አሠራር እነዚህ ኩባንያዎች ለግለሰቦች ብድር አይሰጡም፡፡ ይልቁንም ለሕዝብ የቤት መግዣ ብድር የሚሰጡ ባንኮችንና የብድር ተቁማትን ይደግፋሉ፡፡ ይህን የሚያደርጉት ባንኮች ለረዥም ጊዜ (ከ10 እስከ 30 ዓመት) የቤት ብድር ሲሰጡ ገንዘባቸው ስለሚታሰር፣ እነዚህ ኩባንያዎች ከባንኮች የብድር ሰነዶችን በመግዛት ወይም በዋስትና በመያዝ ለባንኮች ተጨማሪ ፈንድ ያቀርባሉ፡፡ (ሚንበር ቲቪ)
የፈረንሣይ ሙስሊም ካውንስል በሒጃብ ዙርያ የሚደረጉ አደገኛ ፖለቲካዊ ንግግሮችን አወገዘ
ዕለተ ረቡዕ ነሐሴ 27 – 2018 ረቢዕ አል አወል 20 – 1448
በፈረንሣይ ሒጃብ የሚለብሱ ሙስሊም ሴቶችን ኢላማ ያደረጉ “ኃላፊነት የጎደላቸው” ፖለቲካዊ ንግግሮችን እንደሚያወግዝ ‘ዘ ፍሬንች ካውንስል ኦፍ ሙስሊም ፌይዝ’ አስታውቋል። ካውንስሉ ሒጃብ የሚለብሱ ሙስሊም ሴቶችን “ከአክራሪ ርእዮተ ዓለም ጋር ለማያያዝ” የሚደረጉ ንግግሮችን “በጽኑ እንደሚያወግዝ” ገልጿል።
ከፖለቲከኞች የሚሰጡ አስተያየቶች ሴቶቹን ለበለጠ ጥቃት እና ጥላቻ ሊያጋልጧቸው እንደሚችሉም አስጠንቅቋል። በፈረንሣይ የእስልምና ጥላቻን ማባባስ ላይ የሚሳተፉ አካላት “የፖለቲካ እና የሞራል ኃላፊነት መውሰድ አለባቸው” ያለው ካውንስሉ እነዚህ ንግግሮች ሴቶችን ለሕዝብ ጥላቻ ለመዳረግ እና ለአደጋ ለማጋለጥ አስተዋጽዖ የሚያበረክቱ መሆናቸውንም አክሏል።
ሒጃብ የሚለብሱ ሴቶች ቀደም ሲልም የስድብ፣ ዛቻ፣ ማስፈራራት እና የጥቃት ሰለባ እንደሆኑም በመግለጽ ሂጃብን “የዘመናዊ አክራሪ ርእዮተ ዓለም ፈጠራ” አድርጎ ማቅረብ ተቀባይነት የሌለው ነው ብሏል።
ሒጃብን በሃይማኖታዊ ወይም በግል ምክንያቶች በነፃነት የመረጡ ሰዎችን በክልከላ መገደብ አይቻልም ያለው ካውንስሉ፤ ሒጃብ ለመልበስም ይሁን ላለመልበስ የመረጡ ሴቶች ጥበቃ ሊደረግላቸው እና ነፃ ምርጫቸው ሊከበርላቸው ይገባል ሲል አሳስቧል። ለዚህም የፈረንሣይ መንግሥት ውሳኔው ግልጽ ሊሆን ይገባል ብሏል።
የምርጫ ቀናት እየተቃረቡ ባለበት በዚህ ወቅት ታላቅ ሀገር ለማስተዳደር የሚመኝ የፖለቲካ ፓርቲ ሽብርተኝነት፣ ወንጀል፣ የዕፅ ዝውውር እና በሰዎች ላይ የሚፈጸሙ በርካታ ቅድሚያ የሚሰጣቸው ተልእኮዎች እያሉበት በሕዝብ ቦታዎች የሴቶችን አለባበስ ለመቆጣጠር መሰማራቱ ካውንስሉ እንዳስደነቀው ገልጿል። በተጨማሪም የፖለቲካ መሪዎች ለነፃነት፣ እኩልነት እና ወንድማማችነት ቁርጠኛ በመሆን ድምጽ እንዲሆኑ ጥሪ ማቅረቡን አናዶሉ ዘግቧል፡፡ (ሚንበር ቲቪ)
ዒድ አል ፊጥር እና ዒድ አል አድሓ በካሊፎርንያ ግዛት ይፋዊ በዓል ሊሆኑ ነው
ዕለተ ረቡዕ ነሐሴ 27 – 2018 ረቢዕ አል አወል 20 – 1448
በአሜሪካ ውስጥ የሚገኘው የካሊፎርንያ ግዛት፤ ሁለቱን የእስልምና በዓላት (ዒድ አል ፊጥር እና ዒድ አል አድሓ)ን ይፋዊ በዓል አድርጎ ለመቀበል የተዘጋጀው የሕግ ረቂቅ ለአገረ ገዥው ፊርማ ከመላኩ በፊት የመጨረሻ ምዕራፍ ላይ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡
የሕግ ረቂቁ የሚጸድቅ ከሆነ፣ የግዛቱ ሠራተኞች በእነዚህ ቀናት በበዓል ፈቃድ ከሥራ ነጻ መሆን ይችላሉ፡፡ ሕጉን ያቀረቡት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባሉ ማት ሐኒ፣ “ካሊፎርንያ በሀገሪቱ ትልቁ እና የነቃ ተሳትፎ የሚያደርግ ሙስሊም ማኅበረሰብ የሚኖርባት ቦታ ነች” ብለዋል፡፡ ረቂቁ የካሊፎርንያ ሙስሊሞች በጉልሕ እንዲታዩ፣ ዋጋ እንዲሰጣቸው እና በግዛታችን ውስጥ እንዳለው ማንኛውም ማኅበረሰብ ሁሉ በተመሳሳይ ክብር እንዲስተናገዱ ለማድረግ ያለመ ነው” ሲሉ አክለዋል፡፡
የሕግ ረቂቁ ባለፈው ግንቦት ወር መጨረሻ ላይ በምክር ቤት ቀርቦ በ64 ለ 1 ድምጽ ያለፈ ሲሆን፣ አሁን ደግሞ ሙሉ የሴኔት ድምጽ እየጠበቀ ይገኛል፡፡ እስከሚቀጥለው ሰኞ ይጠናቀቃል ተብሎ የሚጠበቀው የሕግ መውጫ ዘመን ላይ ለአገረ ገዥው እንዲላክ ይደረጋል፡፡ ሕጉ ከጸደቀ፣ ሁለቱ የበዐል ቀናት ግዛቷ እውቅና ከሰጠቻቸው እንደ ዲዋሊ እና የጨረቃ አዲስ ዓመት ያሉ የማኅበረሰብ አቀፍ በዓላት ዝርዝር ውስጥ እንደሚካተቱ ኒውዮርክ ፖስት ዘግቧል፡፡ በግዛቱ የሚገኙ የሙስሊም ማኅበረሰብ ቡድኖች ካሊፎርንያ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ የሙስሊም ነዋሪዎች ያላት መሆኑን በመጥቀስ ሕጉ እንዲጸድቅ አሳስበዋል፡፡
በአሜሪካ ትልቁ የሙስሊሞች ድርጅት ዘ ካውንስል ኦን አሜሪካን ሪሌሽንስ የካሊፎርንያ ቅርንጫፍም፤ ሙስሊም ተማሪዎች አብዛኛውን ጊዜ በእነዚህ በዓላት ምክንያት አስቸጋር ሁኔታ እንደሚገጥማቸው በመጥቀስ የሕጉን መጽቀድ አስፈላጊነት አጽንኦት ሰጥቷል፡፡ (ሚንበር ቲቪ)
ዑጋንዳ በምሥራቅ አፍሪካ ቀዳሚውን የሐላል ማረጋገጫ ማዕከል ልትከፍት ነው
ዕለተ ማክሰኞ ነሐሴ 26 – 2018 ረቢዕ አል አወል 19 – 1448
ዑጋንዳ ለምሥራቅ አፍሪካ እና ለሠፊው የአፍሪካ ገበያ ዋና የሐላል ማዕከል ለመሆን የምታደርገው ጥረት አካል ነው የተባለውን በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያለው ብሔራዊ የሐላል ማረጋገጫ ሥነ ምሕዳር ለመገንባት በእንቅስቃሴ ላይ እንደምትገኝ የሀገሪቱ ባለሥልጣናት ይፋ አድርገዋል፡፡
በዑጋንዳ ብሔራዊ የደረጃዎች ቢሮ ዋና ዳይሬክተር ጀምስ ካሲግዋ የሚመራው ይህ እንቅስቃሴ፣ የሐላል ማረጋገጫን ከመደበኛ መስፈርትነት ባለፈ “ለንግድ፣ ለኢንዱስትሪ፣ ለእሴት ጭማሪ እና ኢንቨስትመንትን ለማሳደግ” እንደ መሣሪያ ለመጠቀም ያለመ ነው፡፡
ለዚሁ እንዲያግዘው በሐላል ማረጋገጫ ከምትታወቅው ከማሌዥያ የሐላል ልማት ኮርፖሬሽን ባለሞያዎችን በመጥራት በሐላል ሥነ ምሕዳር፣ መሠረተ ልማት እና የሕግ ማዕቀፍ ላይ ግምገማ እያደረጉ ይገኛሉ ተብሏል፡፡
የሐላል ሰርተፍኬት አንድ ምርት፣ አገልግሎት ወይም የንግድ እንቅስቃሴ የሸሪዓ ሕጎችን ያከበረ እና ለሙስሊሞች ጥቅም ላይ እንዲውል ወይም ለመመገብ የተፈቀደ (ሐላል) መሆኑን የሚያረጋግጥ ኦፊሴላዊ አሠራር ነው፡፡ የዐለም አቀፉ የሐላል ኢኮኖሚ በአሁኑ ወቅት 7 ነጥብ 3 ትሪሊዮን ዶላር የሚገመት ሲሆን፣ ከአራት ዓመት በኋላ ከ10 ትሪሊዮን ያልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
የዑጋንዳ ባለሥልጣናት ሀገሪቱ ያላት የግብርና እና የእንስሳት ሐብት፣ በምሥራቅ አፍሪካ ካላት ስትራቴጂካዊ ቦታ ጋር ተደምሮ እያደገ ከመጣው የሐላል ዘርፍ ገበያ ትልቅ ደርሻ እንድታገኝ ያስችላታል ብለው ያምናሉ፡፡ ሀገሪቱ በምሥራቅ አፍሪካ ማኅበረሰብ ብቸኛዋ የእስላማዊ ትብብር ድርጅት (ኦአይሲ) አባል ሀገር በመሆኗ ከፍተኛ የሙስሊም ቁጥር ያላቸውን ገበያዎች በቀላሉ እንድታገኝ እንደሚያስችላት የዑጋንዳ መገናኛ ብዙኃን ዘገባ ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም 57 አባል ሀገራትን ባቀፈውና ለእስላማዊ ገበያዎች የሚያስፈልጉ ደረጃዎችን በሚያዘጋጀው የኦአይሲ የእስላማዊ ሀገራት የደረጃዎች እና ትንበያ ኢንስቲትዩት ውስጥ በመሳተፍ ላይ ትገኛለች፡፡
የሐላል መረጋገጫው ማዕከሉ ከመከፈቱ በፊት ሀገሪቱ ለትግበራ እንቅፋት የሚሆኑ ሕጎችን ለማሻሽል እየሰራች እንደምትገኝም ተገልጿል፡፡ የዑጋንዳ ንግድ ሚኒስትር ጀነራል ዊልሰን ምባሱ፣ ሀገራቸው “ወደ ዓለም አቀፍ ገበያ መግባት ብቻ ሳይሆን፣ ገበያው ውስጥ ዘልቆ መቆየት ላይ” ትኩረት ማድረግ አለባት ብለዋል፡፡ ከሐላል ምርት እና ማረጋገጫ ጋር የተያያዙ ሕጋዊ ክፍተቶችን ለመቅረፍ የዑጋንዳ የሕግ ማዕቀፍ እንዲከለስ ጠይቀዋል፡፡
የሀገሪቱ ፕሬዝዳንት ልዩ አማካሪ ማማ ምባባዚ፣ እንቅስቃሴው በተለይም ዑጋንዳ የኢኮኖሚ ዕድገቷን ለማፋጠን በምትጥርበት በአሁኑ ሰዐት መምጣቱ ተስማሚ እንዳደረገው ገልጸዋል፡፡ “ሐላል ማረጋገጫ የሀይማኖት ጉዳይ ብቻ አይደለም፣ የንግድ እና ኢኮኖሚ እድልም ጭምር ነው፤ ከዚህ በኋላ ወደ ኋላ መቅረት አንችልም” ብለዋል፡፡
ዑጋንዳ በአሁኑ ወቅት በየዓመቱ የ4 ነጥብ 4 ቢሊዮን ዶላር ግብርና እና የምግብ ምርቶችን ወደ ውጭ የምትልክ ቢሆንም፣ ወደ ባሕረ ሰላጤው ገበያ የሚደርሰው ግን ከ10 በመቶ ያነሰ ነው፡፡ ባለሥልጣናት በአዲሱ የማረጋገጫ ሥርዐት አማካኝነት በሚቀጥሉት ዓመታት ውስጥ የተባበሩት ዐረብ ኢሚሬቶች፣ ሳዑዲ ዐረቢያ፣ ኦማን፣ ኩዌት፣ ባህሬን እና ቀጣርን ወደሚያቅፈው ወደ ገልፍ ሀገራት የሚላከውን የግብርና ምርት ኤክስፖርት በእጥፍ ለማሳደግ አቅደዋል፡፡ (ሚንበር ቲቪ)
