en
Feedback
ሰዋስው ☘☘☘☘

ሰዋስው ☘☘☘☘

Open in Telegram

በሰዋስወ ብርሀን ቅዱስ ዻውሎስ ገዳም እና ለተለያዩ ቤተክርስቲያን ለክብረ በአላት ማውጫ ። በተጨማሪም-ዋዜማ ሥርዓተ ማኅሌት - መዝሙራት ስንክሳር - የየእለቱን ምስባክ ቅኔያት ጥያቄዎች እንዲሁም የወቅታዊ ነገር መወያያ በተጨማሪም @eotcww ብለው ይቀላቀሉን ለወዳጅ ዘመድዎ share#Share#Share# ያድርጉ።

Show more
1 161
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
❤ ሌሎችም ከአገረ ፍዩም የጎልማሳውን ሥጋ ሰርቀው ወደ ፍዩም አገር ሲአደርሱት የእግዚአብሔር መልአክ ነጥቆ ወደ አባቱ ሥጋ መለሰው መነኰሳቱም ብዙ ጊዜ ፈተኑት የወጣቱን ሥጋ ከአባቱ ሥጋ የሚለዩት ሁነው ነበር። በጥዋትም በአንድነት ያገኙአቸዋል ከመነኰሳቱም አንዱ እንዲህ የሚለውን እስኪያይና እስከሚሰማ ድረስ። "ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛ በሕይወተ ሥጋ ሳለን እርስበርሳችን አልተለያየንም በጌታችን ክርስቶስም ዘንድ አልተለያየንም እናንተ እርስ በርሳችን ለምን ትለያዩናላችሁ" ከዚያችም ቀን ወዲህ የለያቸው የለም። ❤ አረማውያንም የአስቄጥስን ገዳም በአጠፉ ጊዜ ስለ ቅዱሳን ሰማዕታት ሥጋ መነኰሳቱ ፈሩ ከቦታቸውም አፍልሰው ወስደው በከበረ አባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን ጎን አኖሩዋቸው የመቃብር ቦታም ሠሩላቸው በላዩም ሊቀ ጳጳሳት ታውዳስዮስ ዘመን በስማቸው ቤተ ክርስቲያን ሠሩላቸው። ሊቀ ጳጳሳት አባ ብንያሚንም ወደ አስቄጥስ ገዳም በመጣ ጊዜ የካቲት አምስት ቀን እንዲከበር በዓልን ሠራላቸው ይኸውም ሥጋቸው የተገለጠበት ነው ቤተ ክርስቲያናቸውም እስከ ዛሬ አለች በቅብጢ ቋንቋ ብህም ብሲት በመባል የታወቀች ናት ይህም አርባ ዘጠኝ ማለት ነው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 26 ስንክሳር። + + + ❤ "ሰላም ለክሙ ሱቱፋነ ፃማ ወሕማም። አርብዓ ወተሰዓቱ አእሩገ ገዳም። ምስለ ላእከ ንጉሥ ወወልዱ ዘተከልክሙ ዮም። ለአንስጣስያ ቅድስት ዓዲ ሰላም። ጽንዐ ወራዙት ዘሞዐት በድካም"። ሊቁ አርከ ሥሉስ (አርኬ)የጥር26። + + + ❤ የዕለቱ ምስባክ፦ "እበውእ ቤተከ ምስለ መባእየ። ወእሁብ ብጽዓትየ ዘነበብኩ በአፉየ። ዘእቤ በከናፍርየ አመ ምንዳቤየ"። መዝ 65፥13-14። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 2፥1-8፣ 1ኛ ጴጥ 5፥9-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 16፥14-16። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 11፥1-19። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ቅዳሴ ነው። መልካም በዓል የቅድስት ለሁላችንም ይሁንልን። ❤ በየቀኑ ይህን ቴሌግራም ላይ ማግት ከፈለጉ ከታች ያለውን ሊኩን ይጫኑት። https://t.me/Eotcw

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤ ❤ ጥር ፳፮ (26) ቀን። ❤ እንኳን ከቁስጥንጥንያ ቤተ መንግሥት ታላላቆች ለአንዱ ልጅ ለሆነች በዋሻ ውስጥ ለብቻዋ ወንድ መስላ በመኖር ለ28ዓመታት በታላቅ ተጋድሎ ለተጋደለች ለታላቋ ጻድቅ ለቅድስት አንስጣስያ ለዕረፍት በዓልና ለጻድቅ አርቃዴዎስ ልጅ በሆነ በጻድቁ ቴዎዶስዮስ ዘመነ መንግስት አርባ ዘጠኝ ለሆኑ ለከበሩ አረጋውያን መነኰሳት ከንጉሥ መልክተኛ ከልጁም ጋር ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓላቸው። በተጨማሪ በዚችን ከሚታሰቡ፦ ከከበሩ መጥረያስ፣ ከስርስንዮስ ሰማዕትና ከመፍቀሬ ነዳያን ከዮሴፍ ከመታሰቢያቸው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። + + + ❤ ቅድስት አንስጣስያ፦ ይቺም ቅድስት ከቊስጥንጥንያ ቤተ መንግሥት ታላላቆች የአንዱ ልጅ ናት። እርሷም በላይዋ በደም ግባቷ እጅግ ያማረች ናት ንጉሥ ብስጥያኖስም ሊአገባት ፈለገ እርሷ ግን ይህን በልቧ አልወደደችም የንጉሡም ሚስቱ በሕይወት ነበረች ንጉሡ እንደሚሻትም ለንግሥት ሚስቱ አስረዳቻት በዚያንም ጊዜ ንግሥቲቱ ወደ ግብጽ በመርከብ አሳፍራ በሥውር ሸኘቻት ከእስክንድርያም ከተማ ውጭ ገዳም አሠራችላት በዚያም ኖረች ያም ገዳም በስሟ ተጠራ። ❤ የከበረች አንስጣስያም በግብጽ አገር እንዳለች ንጉሥ በአወቀ ጊዜ ፈልገው ወደርሱ ያመጡአት ዘንድ መልክተኞችን ላከ ይህንንም ነገር ተረድታ ተነሣች የወንዶችንም ልብስ ለብሳ መስፍንን መሰለች ወደ አስቆጥስ ገዳም ሔዳ ወደ አበ ምኔቱ ወደ አባ ዳንኤል ገባች ምሥጢርዋን ሁሉ ገለጠችለት። እርሱም ወስዶ በዋሻ ውስጥ ለብቻዋ አኖራት እርሷም ሴት እንደሆነች ማንም አላወቀም በየሳምንቱም በእንስራ ውኃ ቀድቶ ከዚያ ዋሻ ደጃፍ እንዲያኖር አንዱን ደግ አረጋዊ አባ ዳንኤል አዘዘው ያም ሽማግሌ አያውቅም ይችም ቅድስት አንስጣስያ በጸሎት በጾምና በመስገድ በመትጋትም እየተጋደለች ሃያ ስምንት ዓመት ኖረች። ውኃ ሲቀዳላት የነበረ ያ ሽማግሌ በዐረፈ ጊዜ አባ ዳንኤልም ያ ሽማግሌ ሲሠራ እንደ ነበር ይሠራ ዘንድ ረዳቱን አዘዘው ቅድስት አንስጣስያም ሀሳቧን በገል ላይ እየጻፈች በበዓቷ ደጃፍ ታኖረው ነበር ረድኡም ወደ መምህሩ ወደ አባ ዳንኤል ይወስደዋል። የምትጽፈውንም ምን እንደሆነ አያውቅም። ❤ በአንዲት ዕለትም የጻፈችበትን ገል አመጣ አባ ዳንኤልም በአነበባት ጊዜ አለቀሰ ረድኡንም "ልጄ ሆይ ተነሥ የዚያን ቅዱስ ሰው ሥጋ ሒደን እንቅበር እርሱ ከዚህ ዓለም ይለያልና" አለው። በሔዱም ጊዜ ወደ በዓቷ ገብተው ከእርሷ ተባረኩ እርሷም አባ ዳንኤልን "አባቴ ሆይ ስለ እግዚአብሔር ብለህ በላዬ ካለው በቀር በምንም ልብስ እንዳትገንዘኝ" አለችው ከዚህም በኋላ የከበረች አንስጣስያ ተነሥታ ጸለየች "እኔ በእግዚአብሔር ዘንድ አደራ አስጠበቅኋችሁ" አለችና በምድር ላይ ተቀምጣ ዐረፈች በላይዋም አለቀሱ ሊቀብሩዋትም አስበው ረድኡ ይገንዛት ዘንድ ሲቀርብ እንደ በለስ ቅጠሎች ደርቀው ጡቶቿን ተመለከተ። ከተጋድሎ ብዛትም የተነሣ እንዲህ ሁኗልና አባ ዳንኤልም አይቶ በማድነቅ ዝም አለ። ❤ ከቀበርዋትም በኋላ ወደ በዓታቸው ተመለሱ ረድኡም ወደ አባ ዳንኤል ቀርቦ ሰገደለትና እንዲህ ሲል ለመነው "ስለ እግዚአብሔር ብለህ የዚችን ቅድስት ዜናዋን ንገረኝ ሴት እንደሆነች አይቻለሁ"። አባ ዳንኤልም የገድሏን ዜና ሊነግረው ጀመረ እንዲህም አለው "እርሷ ከቊስጥንጥንያ አገር ከመንግሥት ታላላቅ ወገኖች ውስጥ የሆነች ስትሆን ሰውነቷን ለክርስቶስ ሰጥታ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ክብር ሁሉ ተወች። ሰይጣንን ተዋጋችበት ከዚህ ከታላቅ ተጋድሎዋ ለእኛ ለወንዶች መመከሪያ ሊሆነን ይገባል ከእርሷም የሴቶችን ደካማነት አርቃ የኃይለኞች ወንዶችን ብርታት ገንዘብ እስከማድረግ ደርሳ እግዚአብሔርን አገልግለችው" አለው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት አንስጣስያ በጸሎቷ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን። + + + ❤ በጻድቁ ንጉሥ በቴዎዶስዮስ ዘመን የከበሩ አርባ ዘጠኝ አረጋውያን መነኰሳትና ከንጉሥ መልክተኞች ከልጁም ጋር ሰማዕት መሆጋቸው፦ የሰማዕትነታቸው ምክንያት ቴዎዶስዮስ ልጅ አልነበረውም በአስቄጥስ ገዳም ወደ ሚኖሩ አረጋውያን መነኰሳት ልጅን ይሰጠው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲማልዱለት እየለመናቸው መልእክትን ላከ ከውስጣቸውም ስሙ ቢስዱራ የሚባል አንድ ታላቅ አረጋዊ ስለ እርሱም ወደ ንጉሥ እንዲህ ብሎ ጻፈ "ከአንተ በኋላ ከሚነሡ መናፍቃን ጋር አንድ እንዳይሆን ልጅን ይሰጥህ ዘንድ እግዚአብሔር አልወደደም"። መልእክቱን በአነበበ ጊዜ ንጉሥ ደስ ብሎት እግዚአብሔርን አመሰገነው ሃሳቡንም አሳረፈ። ❤ ዳግመኛም ግብዞች ሰዎች ሌላ ሚስት አግብቶ ከእርሱ በኋላ በዙፋኑ የሚቀመጥ ልጅን ይወልድ ዘንድ መከሩት እርሱም "የትሩፋታቸው ዜና በዓለም ዳርቻ ሁሉ ደርሷልና በአስቄጥስ ገዳም ከሚኖሩ ቅዱሳን አረጋውያን ትእዛዝ በቀር ምን ምንም አላደርግም" ብሎ መለሰላቸው። ስለዚህም አረጋውያንን ይጠይቅ ዘንድ ንጉሥ መልክተኛውን ዳግመኛ ላከ ለንጉሡም መልእክተኛ ልጅ ነበረው ልጁም በረከታቸውን ይቀበል ዘንድ ከእርሱ ጋራ ወደ አረጋውያን እንዲወስደው አባቱን ለመነው መልክእተኛው ከልጁ ወደ አረጋውያን በደረሰ ጊዜ የንጉሥ ደብዳቤ ሰጣቸው እርሱንም አነበቧት ያን ጊዜ ግን አባ ቢስዱራ ስለሞተ አልተገኘም አረጋውያንም የንጉሡን መልእክተኛ የአባ ቢስዱራ ሥጋ ወዳለበት ወሰዱትና አደረሱት ሥጋውንም "አባታችን ሆይ እነሆ የንጉሥ መልክት ወደ እኛ ደረሰ እኛም የምንመልስለትን አናውቅም" አሉት። በዚያንም ጊዜ አረጋዊ አባ ቢስዱራ ተነሥቶ "እግዚአብሔር ልጅን ሊሰጥህ አልፈቀድም አላልኩህምን አለ በሉት ለንጉሥ አሁንም ከዓላውያን ጋር አንድ ሁኖ እንዳይረክስ ሌሎች ሴቶችንም ቢአገባ ልጅን አይሰጠውም" ይህንንም ተናግሮ ተመልሶ ተኛ። ❤ አረጋውያንም ይህን ቃል በክርታስ ጽፈው ለንጉሥ መልእክተኛ ስጡት እርሱም ወደ አገሩ ሊመለስ በተነሣ ጊዜ እነሆ የበርበር አረማውያን ደረሱ አባ ዮሐንስ የሚባል አረጋዊም ቁሞ ወገኖቹን እንዲህ አላቸው "እነሆ የበርበር ሰዎች ይገድሉን ዘንድ መጡ ምስክርነት የሚሻ ከእኔ ጋር ይቁም የሚፈራ ግን ወደ ግንብ ሒዶ ይሠወር" አለ። የሸሹም አሉ ከአባ ዮሐንስም ጋር የቀሩ አርባ ዘጠኝ አረጋውያን መነኰሳት የንጉሥ መልእክተኛም ልጅ ከጎዳና ጒዞ ላይ ዘወር ሲል በአረጋውያን ሰማዕታት ራሶች አክሊላትን ሲያኖሩ መላእክትን አያቸው የዚያም ጎልማሳ ስሙ ድያስ ነው አባቱንም "እነሆ በአረጋውያን ራሶች ላይ አክሊላትን ሲያኖሩ ረቂቃን መላእክትን አያለሁ አሁንም እንደርሳቸው አክሊልን ለመበቀል እኔ እሔዳለሁ" አለው አባቱም "ልጄ ሆይ እኔም ከአንተ ጋር እሔዳለሁ" አለው። በዚያችም ጊዜ አረጋውያን መነኰሳት ለአረማውያን ተገለጡላቸው አረማውያንም ገደሏቸው የምስክርነት አክሊልንም ተቀበሉ። ❤ አረማውያንም ከሔዱ በኋላ መነኰሳቱ ከተሠወሩበት ግምብ ወርደው የሰማዕታትን ሥጋቸውን ሰበሰቡ ገንዘውም በበዓት ውስጥ አኖሩዋቸውም በእርሳቸውም ዘንድ ሌሊቱን ሁሉ የሚጸልዩና የሚዘምሩ ከእርሳቸውም የሚባረኩ ሆኑ የአባ ዮሐንስንም ሥጋ ሰዎች ሰርቀው ባታኑን ወደሚባል አገር ወሰዱት ከእርሳቸውም ዘንድ ጥቂት ቀኖች ኖረ ከዚህም በኋላ ቅዱሳን ወደቦታው መለሱት።

Jan 30, 05.22 PM(1)_Telephone(1).mp31.89 MB

1.24 MB

photo content

photo content

photo content
+1

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤ ❤ ጥር ፳፭ (25) ቀን። ❤ እንኳን ለታላቁ ሰማዕት ለሮም ንጉሥ ልጅ ለከበረ ለሰማዕቱ ለቅዱስ ስብስትያኖስ ምስክርነቱ ለፈጸመበት ለዕረፍቱ በዓልና አስቀድሞ ቀራጭ ለነበነ ራሱን ለሸጠው በገድል ለተጸመደ ለኖረ ለከበረ ቅዱስ ጴጥሮስ ለዕረፍቱ በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ከሰማዕት ቅዱስ አስኪላ ከመታሰቢያው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። + + + ❤ ሰማዕቱ ቅዱስ ስብስትያኖስ፦ ይህም የቅዱስ የሮሜ ንጉሥ ልጅ ነው። እርሱንም ወላጆቹ በተግሣጽና እግዚአብሔርን በመፍራት የአሳደጉት ነው። አባቱም ከሞቱ በኋላ ዲዮቅልጥያኖስና መክስምያኖስ ነገሡ ይህንንም ቅዱስ አገረ ገዥነት ሾሙት እንደ አባቱም እጅግ አከበሩት። እርሱሜ በጥበብና በማስተዋል ይጓዝ ነበር በሽተኞችን ሁሉ የዕውራንንም ዐይኖች በጸሎቱ ከፈተ። ❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ክርስቶስን ዲዮቅልጥያኖስ በካደው ጊዜ ለጣዖት ይሰግድ ዘንድ ስብስትያኖስን ግድ አለው ባልሰማውም ጊዜ ከደረቀ ግንድ ጋር አሠረው ቊጥር በሌላቸው ፍላጻዎች ይነድፉት ዘንድ አዘዘ እንደሞተም ጠርጥረው ትተውት ሔዱ ምእመናንም በሌሊት ሲመጡ በሕይወት አገኙት ፈትተውም ወደ ደሴት መካከል ወስደው በዚያ አኖሩት። ❤ ዲዮቅልጥያኖስም ሰምቶ ወደርሱ አስቀረበውና በብረት ዘንጎች ይደበድቡት ዘንድ አዘዘ እየደበደቡትም ብዙ ቀኖች ኖሩ ከዚህም በኋላ ነፍሱን አሳለፈ። ለቅድስት ውሉድስና በሕልም ተገልጦ ሥጋው ያለበትን ነገራት እርሷም ሒዳ ወደ ቅዱስ ጴጥሮስና ጳውሎስ መቃብር ወስዳ ቀበረችው። ጌታችንም መታሰቢያውን ለሚያደርግና ስሙን ለሚጠራ የቸነፈር ሕመም እንዳይቀርበው ቃል ኪዳንን ሰጠው። + + + ❤ የከበረ ቅዱስ ጴጥሮስ፦ ይህም ቅዱስ አስቀድሞ ቀራጭ ነበረ እርሱም ልቡ የደነደነ ርኅራኄ የሌለው ነው በዚህም ክፉ ስም ጨካኝ ርኅራኄ የሌለው ብለው ይጠሩታል። ከዚህም በኋላ የኃጢአተኞች ሞት የማይሻ ጌታችን ከእርሱ ምጽዋት የሚለምነውን ድኃ ላከለትና ለመነው በዚያንም ጊዜ አገልጋዩ እንጀራ ተሸክሞ ደረሰ አገልጋዩ ከተሸከመው ከራሱ ላይ አንድ እንጀራ ለዚያ ድኃ ጣለለት ይህንንም ያደረገ ስለ ርኅራኄ አይደለም ከአጠገቡ እንዲሔድለትና ከቶ ወደርሱ እንዳይመለስ ነው ምስኪኑም ተቀብሎ ወደ ማደሪያው ሔደ። ❤ በዚያችም ሌሊት ተኝቶ ሳለ በሕልሙ እንዲህ አየ ብዙዎች ሊተሳሰቡት ይሻሉ በእጆቻቸውም ሚዛኖች ተይዘዋል ብዙዎችም መልካቸው እጅግ የከፉ ጥቋቊሮች ኃጢአቱ ሁሉ ከእርሳቸው ጋር አለ በግራ በኩል ባለው ሚዛን ውስጥ አኖሩት ደግሞ ልብሳቸቻው ነጫጭ የሆኑ ከብርሃናውያን መላእክት መልካቸው ያማረ ብዙዎች ነበሩ እነርሱም ቁመው በማዘን "ምንም ያገኘነው ነገር የለም በቀኝ ባለው ሚዛን ውስጥ ምን አናኖራለሁ" ይሉ ነበር በዚያንም ጊዜ ከእርሳቸው አንዱ መልአክ ጴጥሮስ ለድኃው የጣላትን ያችን እንጀራ አምጥቶ "ከዚች እንጀራ በቀር ሌላ ከበጎ ሥራ ምንም አላገኘሁለትም" አለ ባልንጀሮቹ መላእክትም "በእነዚህ ሁሉ ኃጢአቶቹ አንጻር ይቺ ምን ትጠቅማለች" ብለው መለሱ በዚያንም ጊዜ እየፈራና እየደነገጠ ከእቅልፋ ነቅቶ ከተኛበት ተነሣ። ❤ ከዚያችም ዕለት ወዲህ ስለቀደመች ክፉ ሥራው ተጸጸተ እጅግም የሚራራ ሆነ ቤቱንና ጥሪቱን ሁሉ ሽጦ ለድኆችና ለምስኪኖች ሰጠ ራሱንም ሸጠ። ብዙዎችም ከበጎ ሥራዎች ይህን ስለ ሠራ እንደሚአመሰግኑትና እንደሚያደንቁት በአወቀ ጊዜ ከዚያ በመሸሽ ወደ አስቄጥስ ገዳም ገብቶ ከአባ መቃርስ ገዳም በዚያ መነኰሰ ፍጹም በሆነ ተጋድሎም ተጠምዶ እግዚአብሔርን አገልግሎ የዕረፍቱን ጊዜ አውቆ የከበሩ አረጋውያንን ጠርቶ ተሳለማቸውና በዚያን ጊዜ ጥር24 ቀን ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቱ በቅዱስ ሰብስትያኖስና በአባ ጴጥሮስ በጸሎታቸ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር25 ስንክሳር። + + + ❤ "ሰላም ለከ ስብስትያኖስ ሰማዕተ ዋሕድ ወልድ። ዘንዱፍ በአሕፃ ወእሡር በጒንድ። ተውላጠ ዝንቱ ፃማከ ወሕማምከ ፍድፉድ። መጽሐፈ ገድልከ በኀበ ሀሎ ዐፀድ። እግዚአብሔር አሕረመ ኢይባዕ ብድብድ"። ሊቁ አርከ ሥሉስ (አርኬ) የጥር 25። + + + ❤ የዕለቱ የማኅሌት ምስባክ፦ "ተፈሣሕ በእግዚአብሔር ወይሁበከ ስእለተ ልብከ። ክሥት ለእግዚአብሔር ፍኖተከ። ተወከል ቦቱ ወውእቱ ይገብር ለከ"። መዝ 36፥4-5። የሚነበበው ወንጌል + + + ❤ የዕለቱ የቅዳሴ ምስባክ፦ "ዘረወ ወወሀበ ለነዳይ። ወጽድቁኒ ይነብር ለዓለም። ወይትሌዓል ቀርኑ በክብር"። መዝ 111፥9-10። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 9፥5-ፍ.ም፣ 1ኛ 3፥16-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 4፥29-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማር 10፥17-28። የሚቀደሰው ወንጌል የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ነው። መልካም የአቡነ ሕፃን ሞዐ የልደት በዓልና የቅዱስ መርቆሬዎስ የተአምራት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን። ❤ በየቀኑ ይህን ቴሌግራም ላይ ማግት ከፈለጉ ከታች ያለውን ሊኩን ይጫኑት። https://t.me/Eotcw

photo content
+1

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤ ❤ ጥር ፳፭ (25) ቀን። ❤ እንኳን ለኢትዮጽያዊ ጻድቅ ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት ለአጎት ልጅ ለታላቁ አባት ከበሬ ጋር ተጠምደው በማረስ ሰማዕትነት ለተቀበሉት ለአቡነ ሕፃን ሞዐ ለልደታቸው በዓልና ለታላቁ ሰማዕት ለቅዱስ መርቆሬዎስ በሥዕሉ ላይ አድሮ ቅዱሳን ለሆኑ ባስልዮስንና ጎርጎርዮስን በመርዳት ከሃዲውን ንጉሥ ዑልያኖስን ለገደለባት በዓል በሰላም አደረሰን። + + + ❤ "ሰላም ለጎርጎርዮስ ወለባስልዮስ ዘተናገሮሙ ሥዕሉ ለቅዱስ መርቆሬዎስ፤ ዘከመ ቀተሎ ለዑልያኖስ"። ትርጉም፦ ዑልያኖስን እንዴት እንደገደለው የቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕሉ የተናገራቸው ለኾነ ለጎርጎርዮስና ለባስልዮስ ሰላምታ ይገባል። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በተአምኆ ቅዱሳን ላይ። + + + ❤ ሰማዕቱ ቅዱስ መርቆሬዎስ ያደረገው ተአምር፦ በቀጰዶቅያና በቂሳሪያ በተሾመ በኢጲስቆጶስ ቅዱስ ባስልዮስ ዘመን ዑልያኖስ በነገሠ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ካደ። ከቅዱስ ባስልዮስ ተአምራት በአንዷ ውስጥ እንደተጻፈው ከሓዲ ዑልያኖስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምኑትን ከባድ ሥቃይ አደረሰባቸው። በቅዱስ ባስልዮስ ላይም ተቈጣ፤ አሰረውም። በክርስቲያኖች ላይ ከባድ ሥራ ባበዛባቸው ጊዜ ቅዱስ ባስልዮስ ስለ ከሐዲ ዑልያኖስ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ይለምን ጀመረ። ወደ ቅዱስ መርቆሬዎስ ለመነ። ❤ እግዚአብሔር ጸሎቱን ሰማና ታላቁን ሰማዕት ቅዱስ መርቆሬዎስን ላከለት። በፈረስ ተጭኖ መጣና ከሓዲ ዑልያኖስን አንገቱን በጦር ወጋው። በፋርስ ምድር በውጊያ በክፉ አሟሟት ሞተ። ቅዱስ ባስልዮስ ይህን ራእይ በቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕል ላይ ባየ ጊዜ ፈጽሞ ደስ አለው። የታላቁ ሰማዕት የቅዱስ መርቆሬዎስ አካለ ሥጋ ያለበት ቦታ ተገልጦለት እየጸለየና እያደነቀ ገባ። ያን ጊዜ የቅዱስ መርቆሬዎስ ሰይፍና ጦር ከቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕል ሥር ያለበት ቦታ እስኪሞላ ድረስ ከእነርሱ ብዙ ደም እየፈሰሰ ወደ ቦታቸው ተመለሱ። ❤ ያን ጊዜ ቅዱስ ባስልዮስ ጮኸ። "የክርስቶስ ሰማዕት ሆይ፤ የእውነት ጠላት የሆነውን ዑልያኖስን ገደልከውን?" አለ። ቅዱስ መርቆሬዎስ በቅዱስ ባስልዮስ ፊት "አወን ገደልኩት" እያለ በሥዕሉ ላይ ራሱን ዘንበል አደረገ። ቅዱስ ባስልዮስ የእግዚአብሔርን ክብርና ምስጋና የኢየሱስ ክርስቶስ ሰማዕት የሆነውን የቅዱስ መርቆሬዎስን ብዙ ተአምርና ድንቅ ድንቅ ሥራ አደነቀ። የሰማዕቱ የቅዱስ መርቆሬዎስ ጸሎቱና በረቱ ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን። ምንጭ፦ የቅዱስ መርቆሬዎስ ገድል ተአምር 2። + + + ❤ አቡነ ሕፃን ሞዐ፡- በአባታቸው አርከሌድስ እናታቸው ትቤ ጽዮን ይባላሉ፡፡ የተወለዱት ጥር25 ነው፡፡ አቡነ ሕፃን ሞዐ እና ከእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ጋር የሥጋ ዝምድና አላቸው፡፡ ይኸውም አባታቸው አርከሌድስና ጸጋ ዘአብ ወንድማማቾቸ ናቸው፡፡ አርከሌድስና ጸጋ ዘአብ ሌሎች ሌሎች አራት ወንድሞች አሏቸው፡፡ ❤ እነርሱም እንድርያስ፣ ዘርዐ አብርሃም፣ ቀሲስ ዮናስ እና ቀሲስ ዮሐንስ ናቸው፡፡ አርከሌድስ ሕፃን ሞዐን ይወልዳል፣ ጸጋ ዘአብ ተክለ ሃይማኖትን ይወልዳል፣ እንድርያስ ሳሙኤል ዘወገግን፣ዘርዐ አብርሃም ታላቁ አኖሬዎዮስን፣ ቀሲስ ዮናስ ገላውዲዮስንና የፈጠጋሩን ማትያስን፣ እና ቀሲስ ዮሐንስ ዜና ማርቆስን ይወልዳሉ፡፡ እነዚህ የከበሩ ቅዱሳን አባቶቻችን በእናታቸውም ወገን ቢሆን እንዲሁ በዝምድና የተቆራኙ ናቸው፡፡ አቡነ ሕፃን ሞዐ በሌላኛው ስማቸው ሕፃን ዘደብረ በግዕ ተብለውም ይጠራሉ፡፡ ይኸውም የደብረ በግዕን ገዳም የመሠረቱት እርሳቸው ስለሆኑ ነው፡፡ ❤ ከአራባ ሰባቱ የአገራችን ቀደምት ቅዱሳን ውስጥ አንዱ ናቸው፡፡ በመንዝና በተጉለት የሚገኙ ታላላቅ ገዳማትን አብዛኞቹን የመሠረቷቸው አቡነ ሕፃን ሞዐ ናቸው፡፡ ጻድቁ በክፉዎች ወሬና ሴራ ምክንያት ከበሬ ጋር ተጠምደው ሰማዕትነት የተቀበሉ አባት ናቸው፡፡ ከበሬ ጋር ሲታረሱ ውለው በእጅጉ ከደከማቸ በኋላ በኃይል የተነፈሱባት ምድሪቱ ዛሬም ድረስ ልክ እንደሰው የሚሞቅ ትንፋሽ ታወጣለች፡፡ ያም በጻድቁ እስትንፋስ አምሳል ከመሬት ውስጥ የሚወጣው እስትንፋስ ለአስም በሽታ መድኃኒት ሆኖ ብዙዎችን እየፈወ ነው፡፡ ገዳማቸው ከደብረ ብርሃን ከተማ በእግር የሁለት ሰዓት መንገድ ርቀት ይገኛል፡፡ ይኸውም ከወንይዬ ተክለ ሃይማኖት ገዳም አጠገብ ነው፡፡ ጻድቁ ጥር 25 ቀን ልደታቸው፣ ጥቅምት25 ቃል ኪዳን የተቀበሉበት ዕለት ሲሆን ሐምሌ25 ደግሞ ዕረፍታቸው ነው፡፡ ምንጭ፦ ከገድላት አንደበት። ❤ በየቀኑ ይህን ቴሌግራም ላይ ማግት ከፈለጉ ከታች ያለውን ሊኩን ይጫኑት። https://t.me/Eotcw

Share 'ሥርዓተ_ማኅሌት_ዘበዓለ_አቡነ_ተክለሃይማኖት_ጥር_፳፬.pdf'

10.00 KB

**👉ዘ ነግህ

photo content

photo content
+1

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤ ❤ ጥር ፳፬ (24) ቀን። ❤ እንኳን ከእስክድርያ አገር ከታላላቆቿ ወገን ለሆነች በዓቷን በማጽናት ለ22 ዓመታት ዘግታ ለኖረችውና የላመ የጣፈጠ ቀምሳ ለማታውቀው፤ ለከበረች ተጋዳ ቅድስት ማርያ ለዕረፍቷ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ከሚታሰቡ፦ ከተመሰገነ ቀሲስ አብሳዲ ከመታሰቢያው፣ ከግብጽ አገር ከጥሐ አውራጃ ስፍጥ ከምትባል መንደር ከሆነ ከከበረ ከታላቅ አባት ከቢፋ በሰማዕትነት ከዐረፈና ከሐውዚን ጻድቃን ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። + + + ❤ "ሰላም ለጻድቃን እለ በሐውዜን"። ትርጉም በሐውዜን ያሉ ለኾኑ ጻድቃን ሰላምታ ይገባል። ሊቁ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በተአምኆ ቅዱሳን ላይ። + + + ❤ ቅድስት ማርያ፦ ይቺም ቅድስት ከእስክንድርያ አገር ከታላላቆቿ ወገን የሆነች ነች። የዚችም ቅድስት ወላጆቿ ክርስቲያኖች ናቸው በአደገችም ጊዜ ሊአጋቧት አሰቡ እርሷ ግን ይህን ጋብቻ አልወደደችም እናትና አባቷም በሞቱ ጊዜ የተዉላትን ገንዘብ ሁሉንም ለድኆች ሰጥታ ከእስክንድርያ አገር ውጭ ከአሉ ገዳማት ወደ አንዱ ገዳም ገባች የምንኵስና ልብስንም ለብሳ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለች ድል እስካደረገችውም ድረስ እንቅልፍን ዐሥራ ሁለት ዓመት ስትታገለው ኖረች ከቶ አትተኛም ነበር እንደዚያ ገዳም ሕግ በእሊህ በዐሥራ ሁለት ዓመታት ሁልጊዜ እስከማታ ትጾም ነበር። ❤ ከዚህም በኋላ የከበረ አስኬማን ለበሰች ያን ጊዜ ከጥጥ ባዝቶ የተሠራውን ልብስ ከላይዋ አውልቃ ማቅ ለበሰች ትችል እንደሆነ ወይም አትችል እንደሆነ ራሷን ትፈትን ዘንድ ለመዝጋት ትፈቅድላት ዘንድ እመምኔቷን ለመነቻት እርሷም ፈቀደችላት በዚያንም ጊዜ በዓቷን ዘጋች ምግቧን የምትቀበልበት ትንሽ መስኮት ቀደደች ሥጋውንና ደሙን በዚያው ትቀበላለች በዚያችም በዓት ውስጥ ሃያ ሁለት ዓመት ዘግታ ኖረች። ❤ በዚህ ሁሉ ዘመን ቁማ ትጸልያለች በመኝታ ጊዜም ጥቂት ትተኛለች የቀረውንም ሌሊት እስቲነጋ ቁማ ስትጸልይ ታድራለች። በየሁለት ቀን የምትጾም ሆነች የምትመገበውም በውኃ የራሰ ለምለም እንጀራ ነበር በከበረችም በአርባ ጾም እንጀራ አትበላም በየሦስት ቀን እየጾመች በውኃ የራሰ ሽምብራ ትመገባለች እንጂ። ❤ ጥር ዐሥራ አንድ ቀን የከበረ የጥምቀት በዓልም በሆነ ጊዜ ከተባረከው ውኃ ያመጡላት ዘንድ ለምና አመጡላት ፊቷንና እጆቿን ታጥባ ሥጋውንና ደሙን ተቀበለች ከተባረከውም ውኃ ጠጣች ከዚህም በኋላ ታመመች እስከ ሃያ አንድ ቀንም በመኝታዋ ላይ ተኛች ዳግመኛ በዚች ቀን በጥር በሃያ አንድ ሥጋውንና ደሙን ተቀበለች። ❤ ከዚህም በኋላ እመ ምኔቷን አስጠራቻት እግሮቿንም እንታቀርብላት ብዙ ልመናን ለመነቻትና ስታቀርብላት ሳመቻቸው ፊቷንም አሸችባቸው "ወደ ክብር ባለቤት ጌታዬ ክርስቶስ ላቀረቡኝ እግሮችሽ እገዛለሁ" አለች ዳግመኛም ደናግሉን ሁሉ አስጠርታ ተሳለመቻቸውና ከሦስት ቀን በኋላ እንዲጐበኟት ለመነቻቸው ይኸውም ጥር ሃያ አራት ቀን ነው በመጡም ጊዜ ሙታ አገኟት ገንዘውም ከደናግል አስከሬን ጋር አኖሩዋት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት ማርያ ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ ጥር 24 ስንክሳር። + + + ❤ "ሰላም ለማርያም ዘአጥብዓት ትፍዲ። ለነዳያን ምጽዋተ ንዋየ አቡሃ ወላዲ። ወወጠነት ገድለ በአጽርዖ ንዋም ዓዲ። እምአምኆ ዛቲ ዕለት እንበለ ሕቀ እጐንዲ። ሰላም እብል ለቀሲስ አብሳዲ"። ሊቁ አርከ ሥሉስ (አርኬ) የጥር 24። + + + ❤ የዕለቱ የማኅሌት ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኃይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 1-17። + + + ❤ የዕለቱ የቅዳሴ ምስባክ፦ "ካህናቲከ ይለብሱ ጽድቀ። ወጻድቃኒከ ትፍሥሕተ ይትፌሥሑ። በእንተ ዳዊት ገብርከ"። መዝ 131፥9-10። የሚነበቡት መልዕክታት ቲቶ 2፥1-9፣ 1ኛ 3፥1-5 እና የሐዋ ሥራ 4፥29-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 18፥1-9። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የአቡነ ተክለ ሃይማኖት የስብረተ አፅማቸው በዓል ለሁላችንም ይሁንልን። ❤ በየቀኑ ይህን ቴሌግራም ላይ ማግት ከፈለጉ ከታች ያለውን ሊኩን ይጫኑት። https://t.me/Eotcw

photo content

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤ ❤ ጥር ፳፬ (24) ቀን። ❤ እንኳን ለታላቁ አባት ለሐዲስ ሐዋርያ ለፀሐይ ዘኢትዮጵያ ለአቡነ ተክለሃይማኖት በቁመትና በጸሎት ብዛት አንዲቱ የእግሩ አገዳ ለተሰበረበት (ለስብተ አፅማቸው) ዓመታዊ መታሰቢያ በዓልና ለኢትዮጵያዊው ጻድቅ እንደ ነዳይ ሆነው ለምነው ያገኙትን ለጦም አዳሪዎች በመመጽወት ለሚታወቁት ለአቡነ እጨጌ መርሐ ተክርስቶስ (ዘሸዋ) ለዕረፍት በዓል በሰላም አደረሰን። + + + ❤ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ስብረተ አፅም፦ "...ከበዐቱ ሳይወጣ ሌሊትና ቀን ቆመ። አልተቀመጠም ወደ ግራና ወደ ቀኝም አልተንቀሳቀሰም። ውኃም ቅጠልም ቢሆን ከቅዳሜና ከእሑድ በቀር በዚያ ወራት ምንም ምን አልቀመሰም። እህል ግን ከመነኰሰ ጀምሮ እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስ አልቀመሰም። ፀሓይንም ጨረቃንም ከዋክብትን በጋና ክረምትንም ቡቃያና አበባንም ፍሬውንም አላየም። ዓይኖች ሳሉት እንደ ዕውር ጆሮዎች ሳሉት እንደ ደንቆሮ የሚናገር የተከናወነ አንደበት እያለው እንደ ዲዳ ሆነ። ከምስጋና በቀር ምንም ምን አይናገርም። ሌሊትና ቀንም እግዚአብሔርን አመሰገነ። ዓለምንም እንደ ትቢያና እንደ ጉድፍ ቆጠረው ከክርስቶስ ጋር እንደተሰቀለ ሆነ ልቡናውም ዘወትር ወደ ዓየር የተመሰጠ ነበር። እንዲህ ባለም ገድል ብዙ ዘመን (22ዓመታት) ኖረ። ቁመትንም ካበዛ ወዲህ አንዲቱ የእግሩ አገዳ ተሰበረች ደቀ መዛሙርቱ አንሥተው አክብረው በሰበን ጠቅልለው ከመንበሩ እግር በታች ቀበሯት። ከዚህም ባንዲት እግሩ ሰባት ዓመት ቆመ። ከነዚህም አራቱን ዓመት ውሃው አልጠጣም"። ምንጭ፦ ገድለ ተክለ ሃይማኖት ምዕ53፥8-11። + + + ❤ እጨጌ መርሐ ክርስቶስ (ዘሸዋ)፡- ትውልዳቸው አገራቸው ሸዋ ሚዳ ሲሆን ለገዳማት ብዙ የደከሙ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ በተለይም በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ገድል አላቸው፡፡ ይኸውም እንደ ነዳይ ሆነው ለምነው ያገኙትን ለጦም አዳሪዎች በመመጽወት ይታወቃሉ፡፡ ከባለ ሀብቶች ለምነው ያገኙትን ለድሆች ይመጸውቱትና በቀረው ቤተ ክርስቲያን ይሠሩበታል፡፡ አስደናቂ ገድላቸውና ዐፅማቸው በደብረ ሊባኖስ ይገኛል፡፡ በትግራይም ትልቅ ገዳም አላቸው። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን። ❤ በየቀኑ ይህን ቴሌግራም ላይ ማግት ከፈለጉ ከታች ያለውን ሊኩን ይጫኑት። https://t.me/Eotcw

በጠቅላይ ሚኒስተሩ የንግግር ያሉ ግድፈቶች ግድፈቶች * ጠቅላይ ሚንስትሩ ቅድስት ቤተክርስትያን ያጋጠማትን ፈተና ላይ ያደረጉትን ንግግር አዳመጥኩኝ። ባለውለታ ሆኜ እንዴት እታማለው አይነት ልብ የሚያራራ ንግግሮች ረጅሙን ሰዓት ቢወስዱም እነዚህ ግድፈቶች ግን ፈጠው ይታያሉ። የጠላይ ሚንስትር ንግግር ህግን የሚያስከብር እንደ ትልቅ ሀገራዊ የመንግስት መሪ ሳይሆን በሁለት ጎን ተወዳጅ ሸንጋይ ቃል ወርዋሪ አካል ተጫውተው አልፈዋል። ብቻ ግድፈቱን እስኪ እንመልከት * ግድፈት ፪ << "ብጽኡ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፊሎስን ለኃይለስላሴ መንግስት ቃለ ማህላ ፈጽመው የመጡት ፓትርያሪክ">> ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስተሩ ነካ አድርገው ለማለፍ የሞከሩት ንግግር ከዬትኛው የታሪክ ዶሴ እንደተገኘ ባላውቅም "የነገስታት ሃይማኖት" ተብላ በሐሰት ለማማት በር ላይ ለቆሙ ሰዎች አይዟችሁ በርቱ አይነት ጉልበት ሰጪ ንግግር ሆኖ አይቸዋለው። ግድፈት ፪ ""የትግራይ ጳጳሳት ከኢ/ኦ/ተ/ቤ ሲገነጠል መግለጫ ሳይወጣ የኦሮሚያው ጉዳይ ላይ ግን ጮኸት በዛ" ይህ ደግሞ ሊደብቁት ያሰቡትን የወሊሶ ህገወጥ ድርጊት ስውር ድጋፍ ሰጪነት ያመላከተ ይመስለኛል። ይህን ንግግር ከእሳቸው በፊት የወሊሶ ህገ ወጥ ሹመት ደጋፊዎች ሲያደነቁሩን የወላቱን ቃል ከአንድ ሀገር መሪ መስማት በጣም ያስተዛዝባል። የትግራይ ሊቃነጻጻሳት ኩርፊያን መሰረት ያደረገ ግንጠላ ለማካሄድ ወሰኑ እንጅ የእራሳቸውን ሲኖዶሳዊ መስመር አልዘረጉም። የትግራይ ጉዳይ በሁሉም ሃይማኖቶች ላይ ፓለቲካው ያመጣው ጥቁር ጠባሳ እንጅ በኢ/ኦ/ተ/ቤ ላይ በተናጠል የተካሄደ ልዩ ዘመቻ አይደለም። የትግራይ ፍትህ ነገስትን ጨፍልቀው ህገወጥ ሲመት እና ቅዱስ ፓትርያርክ ምርጫ እቃቃዎሽ ላይ አልገቡም። ስለዚህ የወሊሶው እን የትግራይ ጉዳይን ማነጻጸር አኩራፊ እና ወንበዴ ልጅን በእኩል ለመዳኘት እንደሞሞከር ነው። * ግድፈት ፫ << በቋንቋ የመማር ጥያቄን ሳያፍኑ ችግርን መፍታት አለባችሁ።>> ይህን ንግግር ሲሉ ድንጋጤ ነው የተሰማኝ። የእዚህ ንግግር አወንታዊ ትርጉም ቅድስት ቤተክርስቲያን የቋንቋ አገልግሎትን ታፍናለች ለሚል ትርጉም ይጠጋጋል። እግዚኦ ብለን እንለፈው ይህን ። *** ግድፈት ፬ ለኦርቶዶክስ ለሁሉም ቤተ እምነት 350,000 ካሬ ስንፈቅድ ለኦርቶዶክስ ግን 1,000,045 ካሬ ሰጥተን አብልጠን ደግፈናታል"" ይህ ንግግራቸው ደግሞ የአኃዝ ማጭበርበር ተጠቅመው ህዝቡን ህጻን በማድረግ ለመሸወድ ጥረዋል ። ሃቁን ስንበረብር ግን ወ/ሮ አዳነች አበቤ ከወራት በፊት ለአዲስ አበባ ምክር ቤት ባደረጉት ሪፓርት ለእስልምና....................... 260,938 ለወንጌላውያን አማኞች........98,290 ለአድቨንቲስት ቸርች............6812 ለካቶሊክ.......................... 7700 ለኦርቶዶክስ .....................ከአንድ ሚሊዬን በላይ ተብሎ ተገልፆል። ይህን አሃዝ ስናሰላ ከኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ውጪ 373,740 ካሬ ሲያገኙ በጠቅላይ ሚንስትር ንግግር ግን ፣350,000 ሲሉ አሃዝ ለመቀነስ ሞክረዋል። በነገራችን ላይ የአዲስ አበባ ህዝብ ሃይማኖታዊ ንጽጽር መንግስት እጅ ላይ ባለው ይፋዊ ሰነድ ስንመለከት ኦርቶዶክስ...... 74.6℅ ሙስሊም....... 16.2℅ ፕሮቴስታንት.....7.8℅ ካቶሊክ ..........0.5% እና ሌሎች....... 0.9 ይይዛሉ። አጠቃላይ ድምሩም ....373,740 ካሬ ሆኖ ሳለ ጠቅላይ ሚንስትሩ ግን 350 ካሬ ሲሉ አሃዙን ሊያዛቡት ሽተዋል። በተነገረልን አሐዝ እንኳን ስንመለከት ለአንድ ፐርሰንት ሙስሊም ተከታይ.....16,107 ካሬ መሬት ለአንድ ፐርሰንት ካቶሊክ ተከታይ....... 15,400 ካሬ መሬት ለአንድ ፐርሰንት ኦርቶዶክስ ተከታይ.... 13,405 ካሬ መሬት መሬት እንደተከፋፈለ ያሳያል። ስለዚህ በመሬት እድላ በኩል እንኳን ለኦርቶዶክስ ልታደሉ ቀርቶ ከሌላው ቤተእምነት ጋር እኩል መመልከት እንዳልቻላችሁ ያሳያል እና የድጋፍ መሰብሰቢያ የመሬት ፊሽካዋ ብትቆም መልካም ነው። Via Kune

እውነት ትቅደም_ በውኑ ኢትዮጵያ በሕገ ወጥነት በራሷ ፈቃድ ጳጳስ ሾማለችን???? በፍጹም አልሾመችም። ሰይጣንን ለምን ካድክ ቢሉት በውሸት ለአዳም አልሰግድም ብየ ነው አለ እንደሚባለው (ገድለ ጊዮርጊስ)። የግሉ ትእቢትና ከንቱ ውዳሴ ከልዕልናው ጥሎት ሳለ መውደቁን በአዳም ለማላከክ መሮጡ የሰይጣንን ቀላልነት ያሳውቃል። በፍትሐ ነገሥቱ የኢትዮጵያ ሰዎች ከራሳቸው ጳጳስ አይሹሙ የሚል ሥርዋጽ ተቀምጦ ለብዙ ዘመናት ጳጳስ ከግብጽ እየመጣ ኖረናል። ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፬፣ ቁጥር ፶-፶፩። በዚህም ምክንያት ቋንቋውን የማያውቅ የማያስተምር ሰው እየመጣ ኖሯል። ኢትዮጵያም በሊቃውንቶቿ ትጋት ወንጌልን ለሕዝቡ እያስተማረች ክርስትናን ጠብቃ ቆየች።  የጵጵስና ዋና ሥራው ሕዝቡን ማስተማር፣ ከሃድያንን ወደ አሚነ ሥላሴ ማምጣት፣ ሕዝቡን ከገቢረ ኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ መመለስ፣ ደጋጉን በመልካም ሥራ ማጽናት ነው። በቋንቋ ምክንያት ግን ከግብጽ ተሹሞልን የሚመጣው ጳጳስ ይህንን ሊያደርግልን አልቻለም ነበር። በኋላ ሊቃውንት ተሰብስበው ይህ ለምን ይሆናል ኢትዮጵያ የራሷ ጳጳስ ይኑራት ብለው መከሩ። ነገር ግን ምንም እነርሱ ቢመክሩ የግብጽ ፓትርያርክ ካልፈቀደ ጉዳዩ እንደማይሆን ስላወቁ ሊቃውንት ተመርጠው ለግብጽ ፓትርያርክ አስረዱ። የግብጽ መንበረ ማርቆስም በጉዳዩ ተስማምቶ ብፁዕ አቡነ ባስልዮስን ሹመልንና ወደ ኢትዮጵያ ላከልን። የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ የኢትዮጵያ ፓትርያርክ አቡነ ባስልዮስ ናቸው። ስለዚህ ኢትዮጵያ በራሷ እምቢተኝነት ጳጳስ አልሾመችም። ከመንበረ ማርቆስ አስፈቅዳ አደረገችው እንጂ። ክህነት ፲ መዓርግ አላት። እኒህም:-      ፩) ሊቀ ጳጳሳት (ፓትርያርክ) [ፍት. ነገ. ፬]      ፪) ጳጳስ (መጥሮጶሊስ)      ፫) ኤጲስ ቆጶስ [ፍት. ነገ. ፬]      ፬) ቆሞስ (አብሮጥሮስ) [ፍት. ነገ. ፬፣፷፪-፷፫]      ፭) ቄስ (ቀስ) [ፍት. ነገ. ፮]      ፮) ዲያቆን [ፍት. ነገ. ፯]      ፯) ንፍቀ ዲያቆን [ፍት. ነገ. ፰]      ፰) አናጉንስጢስ [ፍት. ነገ. ፰]      ፱) መዘምራን [ፍት. ነገ. ፰]      ፲) አጻዌ ኆኅት [ፍት. ነገ. ፰]                             ። የእነዚህም የየራሳቸው የሥራ ድርሻ አላቸው። ዐጻዌ ኆኅት ዘበኞች ናቸው። በወንዶች መግቢያ ሆነው ወደ ቤተክርስቲያን የሚገባውን ይቆጣጠራሉ። በስሕተትም በድፍረትም የተወገዙ ሰዎች እንዳይገቡ ይጠብቃል። መዘምራን ዳዊት ደጋሚዎች ናቸው። ይጸልያሉ ይዘምራሉ። አናጕንስጢስ አንባቢዎች ናቸው። ቅዱሳት መጻሕፍትን በቤተክርስቲያን የሚያነብ ነው። ንፍቅ ዲያቆንም ከሦስቱ በመዓርግ ከፍ ያለ ነው። ይሁንና እኒህ ሁሉ በአንብሮተ እድ አይሾሙም። እንዲሁ በኤጲስ ቆጶሱ ቃል ይሾማሉ። ንዋየ ቅድሳትን ልብሰ ተክህኖን መንካት መልበስ አይፈቀድላቸውም። ዲያቆናት በአንብሮተ እድ የሚሾሙ ናቸው። ተንሥኡ ለጸሎት እያሉ ምእመናንን የሚያተጉ ናቸው። ቀሳውስት ማቁረብ ማስተማር ይችላሉ። ቄስንም ዲያቄንንም የሚሾማቸው ኤጲስ ቆጶሱ ነው። ቆሞስ መነኵሴ ሆኖ ከቄስ በመዓርግ ከፍ ያለ የኤጲስ ቆጶሱ አማካሪ ነው። ኤጲስ ቆጶስን በፓትርያርኩ ፈቃድ በሲኖዶስ ፈቃድ ሦስት ወይም ከዚያ በላይ ኤጲስ ቆጶሳት አንብሮተ እድ አድርገው ይሾሙታል። ዘመኑ ከፍቶ ሦስት ኤጲስ ቆጶሳት ካልተገኙ ግን በሁለት ኤጲስ ቆጶሳትም ተፈቅዷል። ይህ ሁሉ ሲሆን ግን ጳጳሱና ሊቀ ጳጳሳቱ ፈቅደው እንጂ ሳይፈቅዱ መሆን አይችልም።                              ። ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፬ ስለ ሊቃነ ጳጳሳት ይናገራል። ፓትርያርክ (ሊቀ ጳጳሳት) ርእሰ ኤጲስ ቆጶሳት ነው። ሊቃነ ጳጳሳትሰ ውእቶሙ ተላውያነ ክርስቶስ። ሊቃነ ጳጳሳትስ እንደምናቸው ብትል ክርስቶስን የመሰሉ የክርስቶስ ተከታዮች ናቸው። የሊቀ ጳጳሳት ሊቅነቱ በምእመናንና በኤጲስ ቆጶሳት ላይ ነው። የኒቅያ ሊቃውንት ሊቃነ ጳጳሳት በዓለም ላይ አራት ብቻ እንዲሆኑ አዝዘዋል። ፍት. ነገ. ፬፣ ቁጥር ፵። አራቱ የተባሉትም መንበረ ማርቆስ (እስክንድርያ)፣ መንበረ ዮሐንስ ቴዎጎሎስ (ኤፌሶን)፣ መንበረ ጴጥሮስ (ሮምያ)፣ መንበረ ጴጥሮስ ካልእ (አንጾኪያ) ናቸው። በየዘመናቱ የተነሡ አባቶቻችን ደግሞ እንደየዘመኑ ሥርዐትን ማሻሻል ስለሚችሉ አሁን የአኃት አብያተ ክርስቲያናት ሊቃነ ጳጳሳት ፮ ደርሰዋል። ይህ ሁሉ ሲሆን ግን በሲኖዶስ ፈቃድ እንጂ በጉልበትና በማን አለብኝነት አልሆነም። አንቀጽ ፭ ስለ ኤጲስ ቆጶሳት ይናገራል። ኤጲስ ቆጶሳትን እንድናከብር እንድንወድ ታዘናል። ፍት ነገ. ፭፣ ፻፵፬ ኤጲስ ቆጶስ ውእቱ አቡክሙ እምታሕተ እግዚአብሔር ዘወለደክሙ ዳግመ እማይ ወእመንፈስቅዱስ። ኤጲስ ቆጶስ ከውሃ ከመንፈስቅዱስ የወለዳችሁ ከእግዚአብሔር በታች ያለ አባታችሁ ነው። ተብሏል። በዚሁ ምዕራፍ ቁጥር ፻፵፮ ወበእንተ ዝንቱ ይደልወክሙ ከመ ታፍቅርዎ ለኤጲስ ቆጶስ በፍቅረ አብ። ስለዚህ ኤጲስ ቆጶስን በአባት ፍቅር ልትወዱት ይገባል ተብሏል። በመሆኑም ያልተረጋገጠ ወሬ ይዞ እንኳንስ ጳጳስን ማንኛውንም ሰው ማማት ትልቅ ነውር ነው። ጳጳስን የምንወደው ግን ከእግዚአብሔር በታች ነው። ምን ማለት ነው?የምንወደው የእግዚአብሔርን ሕግና ሥርዐት ጠብቆ ሲገኝ ብቻ ነው። ካልጠበቀ ግን አናከብረውም አንወደውም። ረስጣ ፶፪ "እመቦ ኤጲስ ቆጶስ ዘፈቀደ በሕጸተ አእምሮቱ በቀለ ኢኮነ ውእቱ ኤጲስ ቆጶስ። ዳእሙ ስም ሕስው ሀሎ ላዕሌሁ። አኮ ውእቱ እምኀበ እግዚአብሔር ዳእሙ እምኀበ ሰብእ" እንዲል በቀለኛ የሆነ ነውር ያለበት ከሆነ ቆብ ብቻ አደረገ እንጂ ኤጲስ ቆጶስ ሊባል አይገባውም አይደለም ተብሏል። የተሾመውም ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከሰው ነው ተብሏል። በቤተክርስቲያን አስተዳደራዊ ጉዳይ ችግር አለ ብሎ ያሰበ ሰውም በሕገ ወጥነት ጳጳስ መሾም ሳይሆን በሲኖዶስ ስብሰባ ጉዳዩን ማቅረብ ነው። ፍት. ነገ. ፭፣ቁጥር ፻፷፭  "ኤጲስ ቆጳሳት ከጳጳሳቸው ወይም ከሊቀ ጳጳሳታቸው በዓመት ሁለት ጊዜ ይሰብሰቡ። በዘ ያሰስሉ እከየ ወቍጥዐ። ቂም በቀልን ያርቁ ዘንድ" ተብሎ እንደተጻፈው።በዚህ ጉባኤ አጀንዳ አስይዞ ተነጋግሮ ችግርን መፍታት ነው።                                ። መውጫ ፍት. ነገ. ፭፣፻፸ "ኢይሠየሙ ክልዔቱ ኤጲስ ቆጶሳት ላዕለ አሐቲ ሀገር" ይላል። የሎዶቅያ ሊቃውንትም በ፶፯ኛው አንቀጽ ይህንኑ ብለዋል። ስለዚህ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ከተመደቡት ጳጳሳት ውጭ ሌላ በእነ አባ ሳዊሮስ በወሊሶ ያለ ሥርዐት የተሾመ ኤጲስ ቆጶስን ምእመናን ሊቀበሉት አይገባም። እንዲያውም በዚሁ አንቀጽ ይህን ያደረገ ቢኖር ይወገዝ ተብሏል። ስለዚህ ከሥርዐተ ቤተክርስቲያን ወጥታችሁ በሕገ ወጥነት የተሾሙትን ግለሰቦች እንዳትቀበሉ። ብትቀበሉ ግን ጠባችሁ ከሥርዐተ ቤተክርስቲያን ባለቤት ከእግዚአብሔር ጋር መሆኑን ከወዲሁ እወቁት። ጵጵስና በጉቦ፣ በጉልበት፣ በተንኮል ኤጲስ ቆጶስነትን የተቀበለ ይሻር። የሾመው ጳጳስም ይሻር። ተብሎ ፍት. ነገ. ፭፣ ቁጥር ፻፸፫-፻፸፬። ተገልጿል። ቤተክርስቲያን ባለቤቷ ክርስቶስ ነው። ስለዚህ ባለቤት ያላትን ቤተክርስቲያንን ባለቤት እንደሌላት በጉልበት የሚሿሿሙባት አይደለችም።                                ። ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።