cookie

We use cookies to improve your browsing experience. By clicking «Accept all», you agree to the use of cookies.

avatar

ብራና ሚድያ - Birana Media

+ የወጣቶች መንፈሳዊ ሕይወት + ገዳማትና ታሪካዊ ስፍራዎች + የቅዱሳን አበው መንፈሳዊ ተጋድሎና ታሪክ + እንዲሁም በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች የውይይት መድረክ በማዘጋጀት ወደ እናንተ ውድ ተከታታዮች መንፈሳዊ ይዘቱን ጠብቆ በየእለቱ ይቀርባል። ቻናላችንን Subscribe በማድረግ ይቀላቀሉን። https://www.youtube.com/c/BiranaMedia ጥያቄ ካሎት በዚህ ይጻፉልን @birana259

Show more
Advertising posts
691
Subscribers
-124 hours
-37 days
-630 days

Data loading in progress...

Subscriber growth rate

Data loading in progress...

Photo unavailableShow in Telegram
"#በሥላሴሁ ሐነጸ ጥቅማ ቤተ ማርያም ሠመየ ስማ" #ሰኔ ፳፩  በዓለ እግዝእትነ ማርያም #በቅድስት ማርያም ስም በፊልጵስዩስ  የመጀመሪያዋ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ተሠርታ ቅዳሴ ቤት የተከበረበት ቀን ነው። "#በሥላሴሁ ሐነጸ ጥቅማ ቤተ ማርያም ሰመየ ስማ" "በሦስትነቱ አንድም በሦስት ድንጋይ ቤቷን ሠራ ስሟንም ቤተ ማርያም ብሎም ጠራ" በዓሉ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ከምታከብራቸው ከ፴፫ ቱ የእመቤታችን በዓላት መካከል አንዱ ነው። ወላዲተ አምላክ እመ ብርሃን ቅድስት ድንግል ማርያም የእናት ፍቅሯ በእምነት በምግባር ያጽናን። እንኳን አደረሳችሁ። ++++++++++++++++++++++++++++++++++ #ቅድስት በምትሆን በጽርሐ ጽዮን በሐዋርያት ላይ የወረደ የአብ በረከት የወልድ ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ አንድነት በሁላችን ላይ ይውረድ ዕፅፍ ድርብ ይሁን"  ሥርዓተ ቅዳሴ ቁ.፻፴፮
Show all...
በዚህ ስብከት ልባቸው ተነካ፤ ጴጥሮስንና ሌሎእንም ‹‹ምን እናድርግ›› አሏቸው፡፡ ጴጥሮስም ‹‹ንስሐ ግቡ፤ ኃጢአታችሁም ይሰረይላችሁ ዘንድ እያንዳንዳችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተጠመቁ፤ የመንፈስ ቅዱስንም ስጦታ ትቀበላላችሁ›› አላቸው፡፡ (የሐዋ.ሥራ ፪፥፭-፴፰) ቋንቋ የሚያናግረውን፣ በጥበብና በዕውቀት የሚሞላውን፣ በሀብቱ ስቦ በረድኤት አቅርቦ ሀብተ መንፈስ ቅዱስን የሚያሰጥ የኃጢአት ስርየትም የሚገኝበትን በክርስቶስ አምኖ በመጠመቅ የሚገኘውን የመንፈስ ቅዱስ ስጦታ እንዲቀበሉ መከራቸው፡፡ ቃሉንም የሰሙ፣ ሰምተውም ያመኑ ብዙ ነፍሳት ተጠመቁ፤ ቁጥራቸውም ሦስት ሺህ ያህል ነበሩ፡፡ እናም በዓለ ጰራቅሊጦስ እያልን ከዕርገት በዐሥረኛው ቀን፣ ከትንሣኤው በሃምሳኛው ቀን የምናከብረው ታላቅ በዓል መሠረቱ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ከሰማያት የወረደበት፣ ለጌታ ቤተ ሰቦች የተገለጠበትና በእያንዳንዳቸው ላይ ያደረበት፣ በዚህም ሕይወት የሚሰጠውን አምላካዊ ዕውቀት ያገኙበት፣ ዓለምን ተዘዋውረው ያስተምሩበትና ተአምራት መንክራት ያድርጉ ዘንድ ሕዝቡንም ሁሉ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የሚጠሩበትን የዓለም ቋንቋ የገለጠበት፣ በዚህም የመንፈስ ቅዱስን ድንቅ ሥራ የተመለከቱ፣ በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት ልባቸው የተነካ ብዙዎች በክርስቶስ ኢየሱስ አምነው የተጠመቁበትና ወደ በረቱ የተሰበሰቡበት ድንቅ የተአምራትና የምሥጢር ቀን በመሆኑ እንድናከብረው በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ተሠርቶልናል፡፡ መጽሐፈ ፍትሐ ነገሥት ‹‹በበዓለ ሃምሳ ሥራ አትሥሩ፤ ነገረ ክርስቶስን ባመኑ ምእመናን ላይ የወረደ መንፈስ ቅዱስ ተገልጦበታልና›› ይላል፡፡ (ፍት.ነገ.አን.፲፱፥፯፻፵) እናም እኛ ክርስቲያኖች ይህንን ታላቅ የበረከት በዓል፣ ይህንን የተቀደሰ ቀን ስናከብረው እንዴት ይሆን? በወይን ጠጅ ሰክረን ወይስ ኃጢአታችን ይሰረይልን ዘንድ ንስሓ ገብተን ወይስ በሌላ ሁኔታ? ጰራቅሊጦስ ነፍስና ሥጋን የሚያጸና፣ ለንጹሐን የክብር አክሊልና ሞገስ ነው፤ ይህን የእውነት መንፈስ በእኛ ላይ ያድር ዘንድ፣ ስብራታችን እንዲጠገን፣ ጎደሏችን እንዲሞላ፣ ድንቁርናችንን እንዲያስወግድ፣ ከኀዘናችን እንዲያጽናናን፣ እንለምነዋለን ወይስ በምግበ ሥጋ ተጠምደን ጨለማውን የማያርቀውን ዕውቀት የማይገልጸውን፣ ኀዘንና ትካዜ የሚጨምረውን የበዓል አከባበር እናከብራለን? ራሳችንን እንድናይ፣ ንስሐን የሚቀበል፣ ኃጢአትንም ይቅር የሚል፣ የሚያነጻ መንፈስ (ጰራቅሊጦስ) በእውነት ይርዳን! ተቀድቶ የማያልቅ የዕውቀት መጠጥ ነው፤ ምሥጢር ገላጭ በመሁኑ ምሥጢሩን እንዲገልጽልን በጽርሐ ጽዮን በሐዋርያት ላይ የወረደ መንፈስ ቅዱስ በእኛም ላይ ያድር ዘንድ አእምሮውን፣ ማስተዋሉን እንዲሰጠን መልካም ፈቃዱ ይሁን፤ አሜን! ወስብሐት ለእግዚአብሔር!
Show all...
#ጰራቅሊጦስ "ይፈኑ ለክሙ ጰራቅሊጦስሃ፤ አጽናኝ መንፈስ ይልክላችኋል" (ዮሐ.፲፬፥፲፮) እንኳን ለበዓለ ጰራቅሊጦስ አደረሳችሁ! የቤዛነት ሥራውን ከፈጸመ በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በክብር ሲያርግ ለሐዋርያት የሰጣቸው ተስፋ አጽናኝና የእውነት መንፈስ የሆነውን መንፈስ ቅዱስን አብ እንደሚልክላቸው፣ እርሱም አጽናኝ የሆነ ጰራቅሊጦስ እንደሆነ ለዘለዓለሙም ከእነርሱ ጋር እንደሚሆን ነግሯቸው ነበር፡፡ ጌታችን እንደተናገረውም በሰጣቸው ተስፋ መሠረት ባረገ በዐሥረኛው ቀን በተነሣ ደግሞ በሃምሳኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸዋል፡፡ ‹‹ወአነ እስእሎ ለአብ ይፈኑ ለክሙ ጰራቅሊጦስሃ፤ ካልአ ዘይሄሉ ምስሌክሙ ለዓለም፤ እኔም አብን እለምነዋለሁ፤ እርሱም ለዘለዓለም ከእናንተ ጋር ይኖር ዘንድ ሌላ አጽናኝ መንፈስ ይልክላችኋል›› እንዲል፡፡ (ዮሐ.፲፬፥፲፮) ይህንንም መንፈስ ቅዱስ የወረደበትን ቀን በዓለ ጰራቅሊጦስ እያልን እናከብረዋለን፤ ከጌታ ዐበይት በዓላትም አንዱ ነው፡፡ጰራቅሊጦስ ማለት መንፈስ ቅዱስ እንደሆነ ወይም ለመንፈስ ቅዱስ የሚሰጥ ሌላኛው ስሙ እንደሆነ ከርእሳችን እንረዳለን፡፡‹‹ጰራቅሊጦስ መንፈሰ አብ ወወልድ ስቡሕ፤ ጰራቅሊጦስ የተመሰገነ የአብና የወልድ መንፈስ ነው›› በማለት አምላክነቱን በአንድነት በሦስትነት ጸንቶ የሚኖር እውነተኛ አምላክ፣ ከአብ የሠረጸ የእውነት መንፈስ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ (ሰይፈ ሥላሴ ዘሐሙስ) ጰራቅሊጦስ ማለት ‹‹መንፈስ ቅዱስ፣ አጽናኝ፣ አስታራቂ፣ አሳምሮ የሚያናግር ማለት ነው›› ይላል፡፡ (ሕያው ልሳን) አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም ‹‹ጰራቅሊጦስ›› ማለት ‹‹ናዛዚ፣ መጽንዒ፣ መስተፍስሒ፣ መንፈስ ቅዱስ፣ በዓለ ሃምሳ፣ የትንሣኤ ሃምሳኛ፣ የዕርገት ዐሥረኛ፣ እሑድ ቀን የሚውል ወዘተ…›› እያሉ ይተረጉሙታል፡፡ (ገጽ ፱፻፯) በጥቅሉ ጰራቅሊጦስ ማለት መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ደግሞ ያዘኑትን የሚያጽናና፣ የራቁትን የሚያቀርብ፣ የተሰወረውን የሚገልጥ፣ የረቀቀውን የሚያጎላ፣ የተከፉትን የሚያስደስት፣ ለመምህራን አንደበት የሆነ መጽንዒ፣ የሚያጸና፣ መንጽሒ የሚያነጻ ኃጢአትን ይቅር የሚል የሚደመስስ የእውነት መንፈስ፣ የእውነት አምላክ ነው፡፡ ጌታችን እርሱን እስኪልክላቸው ኃይልን ብርታትን እስኪላበሱ አላዋቂዎችን አዋቂ የሚያደርግ ከሣቴ ምሥጢር፣ ፈሪዎችን ደፋር (ጥቡዓን) የሚያድርጋቸው፣ በአሕዛብ በዓላውያን ፊት ያለ ኀፍረት፣ ያለ ፍርሃት እንዲመሰክሩ፣ በእሳቱ፣ በስለቱ እንዳይሸማቀቁ የሚያደርጋቸውን የእውነት መንፈስ እንደሚልክላቸውና እርሱም ለዘለዓለሙ አብሯቸው እንደሚኖር ተስፋ ሰጥቷቸው ነበር፡፡ እንዲህም ብሏቸዋልና፤ ‹‹ዘኢይክል ዓለም ነሢኦቶ፤ ዓለም እኔን ለሕማም ለሞት አሳልፎ እንዲሰጠኝ ለሕማም ለሞት አሳልፎ ሊሰጠው የማይቻለው፤ እስመ ኢይሬእዮ ወኢየአምሮ፤ አያየውም፤ አያውቀውምና፤ ወአንትሙሰ ተአምርዎ፤ እናንተ ግን ታውቁታላችሁ፤ አድሮባችሁ ይኖራልና በውስጣችሁም ይኖራልና፡፡›› አድሮባቸው የሚኖረውን፣ ሕማመ ሥጋ፣ ድካመ ሥጋን የሚያርቅላቸውን፣ የምሥራቹን ለዓለም ሁሉ የሚያደርሱበትን ኃይል ጸወን የሚሆናቸውን እውነተኛ የሆነ የራሱንና የአባቱን መንፈስ ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በሃምሳኛው ቀን፣ ባረገ በዐሥረኛው ቀን በዕለተ እሑድ ጰራቅሊጦስ የተባለውን የእውነት መንፈስ ላከላቸው፡፡ እርሱ የእውነት መንፈስ ነው አለ፤ የሐሰት መንፈስ አለና ሲለይ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ በ፻፳ው ቤተ ሰብ ላይ እንደወረደ፡- ‹‹እንዘ ሀለዉ ኩሎሙ ኅቡረ አሀተኔ መጽአ ግብተ እምሰማይ ድምፅ ከመ ድምፀ ነፋሰ ዓውሎ፤በአንድነት ተሰብስበው ሳሉ ከወደ ሰማይ እንደ ዓውሎ ነፋስ ድምፅ ያለ ድምፅ ነጉዶ ተሰማ …›› (የሐዋ.ሥራ ፪፥፪) ዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት፣ ሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስትና ሰባ ሁለቱ አርድእት መቶ ሃያው ቤተ ሰብ በኅብረት በኢየሩሳሌም ይኖሩ ነበር፡፡ ምክንያቱም ከላይ እንዳየነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹አንትሙሰ ንበሩ ሀገረ ኢየሩሳሌም እስከ ትለብሱ ኃይለ እምአርያም፤ እናንተ ግን ከሰማይ ኃይል እስክትለብሱ ማለትም ሰማያዊ ሀብትን፣ ሰማያዊ ዕውቀትን፣ ሰማያዊ ኃይልን እስክትለብሱ በኢየሩሳሌም ቆዩ›› ብሏቸው ነበርና በኅብረት ይኖሩና፣ በኅብረት ይጸልዩ፣ የተስፋውንም ቃል ይጠብቁ ነበርና ድንገት በተሰበሰቡበት እንደ ዓውሎ ነፋስ ያለ ታላቅ ድምፅ አሰምቶ የተቀመጡበትን ቤት ሞላው፡፡ (የሐዋ.ሥራ ፪፥፪) ላንቃ ላንቃ ያለው እሳት መስሎም ታያቸው፤ በሁላቸውም ላይ መንፈስ ቅዱስ አደረባቸው፡፡ በዚህም ኃይል የሚሆናቸውን፣ ሀብት የሚሆናቸው ዕውቀትን ገንዘብ አደረጉ፡፡ ሁሉም በየራስ በየራሳቸው ሰባ ሁለት ቋንቋ መናገር ጀመሩ፡፡ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያትና በሌሎቹ ላይ እንደ ነፋሰ ዓውሎ ሆኖ ነው የወረደው፡፡ ምክንያቱም ነፋስ ረቂቅ ነው፤ መንፈስ ቅዱስም ረቂቂ ነውና፤ ነፋስ ኃያል ነው፤ ፍሬውን ከገለባው ይለያል፤ መንፈስ ቅዱስም ጻድቃንን ከኃጥአን ይለያልና፡፡ ነፋስ በምልዓት ሳለ አይታይም፤ አይታወቅም፤ ነገር ግን የሚታወቀው ባሕር ሲያናውጥ፣ ዛፍ ሰያወዛወዝ፣ ቅጠሉን ሲያረግፈው፣ አቧራውን ሲያስነሣው በሥራው ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስም በምልአት ሳለ አይታወቅም፤ ነገር ግን ቋንቋ ሲያናግር፣ ምሥጢር ሲያስተረጉም ይታያልና፡፡ ነፋስ መዓዛ ያመጣል፤ መንፈስ ቅዱስም መዓዛ ጸጋን ያመጣልና በነፋስ ተመስሎ ወርዷል፡፡ ሰባ ሁለት ቋንቋ ሲናገሩም ከልዩ ልዩ ቦታ የተሰበሰቡና ልዩ ልዩ ቋንቋ የሚናገሩ አይሁድ በዚያ (በኢየሩሳሌም) ነበሩና አደነቁ፤አንዳንዶቹ እንዲያውም ግራ ተጋብተው ‹‹እነዚህ ሰዎች ሁላቸውም የገሊላ ሰዎች አይደሉምን? በየሀገራችን ቋንቋ ሲናገሩ እንደምን እንሰማቸዋለን›› እያሉ ያደንቁ ነበር፤ አንዳንዶቹ ግን ይስቁባቸው ነበር፡፡ምክንያቱም ከከተማ የመጡ እኩያን አይሁድ ሰቃልያነ አምላክ ናቸውና የመንፈስ ቅዱስን ሥራ ላለማድነቅ በሐዋርያት ላይ ሳቁባቸው፤ ‹‹እሊህ ያልፈላ ጉሽ ጠጅ ጠጥተው የሆነ ያልሆነውን ይቀባጥራሉ›› ብለው ተሳለቁ፡፡ (የሐዋ.ሥራ ፪፥፭-፲፫) እንደ እውነቱ ከሆነ ያልፈላ ጉሽ የወይን ጠጅ የጠጣ፣ ጠጥቶም የሰከረ ሰው፣ እንኳን የማያውቀውን ቋንቋ ሊናገር ቀርቶ የሚያውቀውንም በተናገረው አይናገረም፤ ስካር አንደበትን ያስራል፤ ትንፋሽን ያሳጥራል እንጂ አዲስ ቋንቋ፣ ሁላቸውም የሚሰሙት የሀገራቸውን ቋንቋ ሊናገሩ አይችሉም ነበር፡፡ አይሁድ ግን ክፉዎች ነበሩና እውነቱን መቀበል አይሹም፡፡ የዘመናችን መናፍቃንም ወንጌል ተከድኖባቸው፣ እውነቱ ተሸፍኖባቸው፣ በዕውቀት የተራቀቁትን፣ መንፈስ ቅዱስ ተመልተው ምሥጢር የሚያመሠጥሩትን፣ ክብሩን የሚገልጡትን በመንፈስ ቅዱስ የሚመሩ መምህራንን፣ ሊቃውንትን እንደሚያቃልሉትና እንደሚያሾፉ ዓይነት ማለት ነው፡፡ ግን ጊዜው የስካር አይደለም፤ ምክንያቱ ገና ንጋት (ነግህ) ነውና፤ ነቢዩ ኢዩኤል የተናገረው ቢፈጸም ነው እንጂ፡፡ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስም ‹‹በሥጋዊ በደማዊ ሰው ሁሉ መንፈሴን አሳድርበታለሁ›› ያለው ጌታ አስቀድሞ በነቢዩ የተናገረው ትንቢት መፈጸሙ የእግዚአብሔር መንፈስ በእነርሱ ላይ ስለ መውረዱ አዲስ ዕውቀትን እንደገለጠላቸው ነገራቸው፤ ገሠጻቸው፤ ስለ ጌታችን ወደዚህ ዓለም መምጣት፣ አይሁድ ግን በክፋት እንደሰቀሉት፣ እርሱ ግን በሥጋ ሞቶ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ ስለ መነሣቱና ስለማረጉ ለዚህም ምስክሮቹ መሆናቸውን ጭምር ሰበከ፡፡
Show all...
ርኅሩኁና የይቅርታ መልአክ የርኅራኄ መዝገብ፣ ትሑት፣ ታዛዥና ለዘለዓለም ፈጣሪውን አመስጋኝ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ጌታ በሚያደርገው ቸርነት ላይ ለሰው አንድ ወገን የሚሆን መልአክ ነው፡፡ (ሄኖ.፮፥፭፣፲፪፥፭፣፲፥፲፪) አምላካችን እግዚአብሔርን የሚፈሩትን እንደ አጥር ሆኖ የሚጠብቃቸው፣ የመልእክት አለቃቸው፣ ምሕረት ማድረግን የተሰጠው፣ የክብር አክሊልን የተቀዳጀ፣ በግርማው የተፈራ፣ የቅዱሳን ወዳጅ፣ የኃጥአን የምሕረት አማላጅ፣ በብርሃን መጎናጸፍያ የሚጎናጽፍ፣ ከክብሩ ብርሃን የተነሣ ምድርን በብርሃን የሚሞላት፣ የቅዱሳንን ጸሎት ከዕጣኑ ጢስ ጋር ወደ እግዚአብሔር የሚያሳርግ፣ በትንሣኤ ዘጉባኤ የመለከት ድምጽ የሚያሰማ፣ በሰማይ ካሉ ሁሉ በላይ በማዕረግ የከበረ፣ ድንቅ ተአምራትን የሚያደርግ ቅዱስ ሚካኤል በዚህ ቀን ያደረገውን ነገር እወቁ! ኪልቂያ በምትባል አገር ሃይማኖቱ የጸና አስተራኒቆስ የሚባል ታላላቅ መኮንን ነበር፡፡ የሚስቱም ስም አፎምያ ይባላል፡፡ ሁለቱም እግዚአብሔርን የሚፈሩ፣ የመላእክት አለቃ የሚሆን ቅዱስ ሚካኤልንም በፍጹም ልቡናቸው የሚወዱ በየወሩ በቅዱስ ሚካኤል ስም ለነዳያን የሚመጸውቱ፣ የበዓሉን መታሰቢያ የሚያደርጉ፣ ለተራበ የሚያበሉ፣ ለተጠማ የሚያጠጡ፣ በፍቅርና በመከባበር የሚኖሩ ሰዎች ነበሩ። ቅድስት አፎሚያ ባሏ አስተራኒቆስ በታመመ ጊዜ እንዲህ አለችው፤ ‹‹ሴት ባሏ በሞተ ጊዜ ቤተ ፈት፣ ጋለሞታ፣ ሴተኛ አዳሪ እንደምትሆንና የዕለት ምግቧንም ለማግኘት ልዩ ልዩ ፈተና እንደሚደርስባት አንተ ታውቃለህ። እናም አንተ በምትሞትበት ጊዜ ከኀዘኔ የሚያረጋጋኝ፣ እንደ አባት እንደ እናት የሚሆነኝ፣ የሚያጽናናኝ በመዓልትና በሌሊት ከሰይጣን ጠብ የሚያድነኝ የምማፀንበት የመላእክት አለቃ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል ታሠራልኝ ዘንድ እጠይቅሃለሁ›› አለችው። አስተራኒቆስም የጠየቀችውን በወርቅና በብር አሠርቶ አስመጣላት። ቅድስት አፎምያ ባሏ አስተራኒቆስ ካረፈ በኋላ ዘወትር በቅዱስ ሚካኤል ፊት እየሰገደች ‹‹ቅዱስ ሚካኤል ሆይ ጠብቀኝ፤ አትለየኝ፤ ይቅር ይለኛና ይምረኝ ዘንድም ወደ እግዚአብሔር ጸልይልኝ›› በማለት ትለምነው ጀመረ። በጎ ሥራዋንም ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረች ሄደች። ለነዳያንና ለችግረኞች ምጽዋት መስጠትንም የየዕለት ተግባሯ አደረገች። ‹‹ምጽዋት ከርኅራኄ የምትበልጥ ርኅራኄ፣ ሰው ፈጣሪውን የሚመስልባት፣ ለአምላክ የሚያበድሯት ብድር፣ ወደ አምላክ የሚነግዷት የታመንች ንግድ፣ ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያኖሯት አደራ፣ እግዚአብሔር የሚቀበላት ቁርባን ናትና›› እንዲል፡፡ (ፍትሐ ነገሥት፣ አንቀጽ ፲፮) ቅድስት አፎሚያ የሚበላውን የሚጠጣውን በከርሠ ነዳያን፣ የሚለበሰውን በዘባነ ነዳያን በእግዚአብሔር ዘንድ አደራዋን ማስቀመጥን አበዛች። ከዚህ በኋላ የሰው ልጆችን ድኅነት የማይወድ ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ በምቀኝነት ተነሣባት። ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ሰይጣን ራሱ የብርሃንን መልአክ እንዲመስል ራሱን ይለውጣልና›› እንዳለ የብርሃን መልአክ መስሎ ወደ እናታችን ቅድስት አፎምያ ቀረበ። (፪ኛ ቆሮ. ፲፩፥፲፬) ቀርቦም “አፎምያ ሆይ፥ ሰላም ለአንቺ ይሁን፤ ጸሎትሽ፣ በጎ ምግባርሽ ወደ ሰማይ ዐርጎ ከእግዚአብሔር ዙፋን ፊት ቀርቦአል፤ ፈጣሪሽም ከመላእክቶቹ ጋር በጣም ተደስቶአል። እኔንም ስለ በጎ ሥራሽ ባለ ዘመንሽ ሁሉ እጠብቅሽ ዘንድ ወደ አንቺ ላከኝ” አላት። ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹መንፈስን ሁሉ አትመኑ፤ ነገር ግን መናፍስት ከእግዚአብሔር ሆነው እንደሆነ መርምሩ›› እንዳለ ቅድስት አፎምያ ‹‹አንተ ማን ነህ? ስምህስ ማን ይባላል?›› አለችው፤ (፩ኛ ዮሐ.፬፥፩) የሐሰት አባተ ዲብሎስም “እኔ የመላእክት ሁሉ አለቃ ሚካኤል ነኝ” በማለት መለሰላት። የቤተ ክርስቲያን ልጆች አስተዋላችሁን? ሐሰተኛውና ተንኮለኛው ዲያብሎስ ዛሬ ላይስ ማን ነኝ እያል እያታለለን ይሆን? ሲያሻው ባሕታዊ፣ አጥማቂ፣ “ነጻ አውጭ ጳጳስ”፣ መነኩሴ፣ መምህር በመምሰል፣ በእኛ ዘመን “እኔ ክርስቶስ ነኝ” እስከ ማለት ደርሶአልና መመርመርና በጸሎት መበርታት ያስፈልጋል። ቅድስት አፎምያ “እኔ የመላእክት ሁሉ አለቃ ሚካኤል ነኝ” ሲላት ‹‹በቤቴ ውስጥ እንዳለው በዘንግህ ጫፍ ላይ ትእምርተ መስቀል ለምን የለበትም? ትሳለመውም ዘንድ የቅዱስ ሚካኤልን ሥዕል አመጣዋለሁ›› ብላ ወደ ቤት ስትገባ አንቆ ያዛት። ዲያብሎስ ምንም እንኳን ዓይኑን አፍጥጦ፣ ጥርሱን አግጥጦ ሊይዛት ቢመጣም ‹‹ሚካኤል! ሚካኤል ብላ ስትጣራ ቅዱስ ዳዊት ‹‹የእግዚአብሔር መልአክ በሚፈሩት ሰዎች ዙርያ ይሰፍራል፤ ያድናቸውማል›› እንዳለ (መዝ.፴፫፥፯) ቅዱስ ሚካኤል ፈጥኖ ደርሶ አዳናት፤ ከዲያብሎስ እጅም አወጣት። የቤተ ክርስቲያን ልጆች! ዛሬም በእኛ ዘመን “እኔ መልአክ ነኝ፤ ሰማዕት ነኝ፤ መነኩሴ ነኝ፤ ጳጳስ ነኝ...” ሲላችሁ የመነኮሳትንና የጳጳሳትን ግብር ንገሩት፤ “አንተ ለምን እንደ እነርሱ አልሆንክም” በሉት። ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክቱ ‹‹ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም፥ በሕያውና ለዘለዓለም በሚኖር በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ›› እያለ በሐዋርያት እግር በአንብሮተ እድ ተሹሞ “የእኔ ይሹም ይግዛ” ሲላችሁ እንደ ቅድስት አፎምያ “አባ አስኬማከ ሠናይ ወቃልከሰ እኩይ ወኢሠናይ ውእቱ፤ አባ አስኬማህስ መልካም ነው፤ ቃልህ ግን መጥፎ ነው” እንበለው። (፩ኛ ጴጥሮስ ፩፥፳፫) ቅድስት አፎሚያ ተጋድሎዋንም ጭርሳ በዚች ቀን በሰላም ዐረፈች። የእግዚአብሔር ምስክርም ሆነች፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን፤ እኛንም በጸሎቷ ይማረን፤ የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሚካኤል ጸሎት፣ ምልጃና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!!! ወብስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!! ምንጭ፡- ድርሳነ ሚካኤል ሰኔ ዐሥራ ሁለት ቀን
Show all...
🙏 2 1
Photo unavailableShow in Telegram
1
ዕርገተ ክርስቶስ፤ እንኳን ለብርሃነ ዕርገቱ አደረሳችሁ (ሰኔ 06 2016)      ዕርገት ከታች ወደ ላይ፥ከምድር ወደ ሰማይ መውጣት ማለት ነው።ቅዱስ ዳዊት፡-የጌታ ርደቱን (ከሰማይ ወደ ምድር መውረዱን) በመዝሙረ ትንቢት እንደ ተናገረ ሁሉ ነገረ ዕርገቱንም ተናግሯል።ይኸንንም:-“እግዚአብሔር በእልልታ፥ ጌታችንም በመለከት ድምጽ ዐረገ፥ዘምሩ ለአምላካችን ዘምሩ፤” በማለት የራቀውን አቅርቦ፥ የረቀቀውን አጉልቶ በመንፈስ ዘምሯል።መዝ፡፵፮፥፭      ይህ ትንቢት የሚፈጸምበት ሰዓት በደረሰ ጊዜም ጌታ ከሙታን ተለይቶ በተነሣ በአርባኛው ቀን ደቀ መዛሙርቱን አስከትሎ ወደ ቢታንያ ሄዷል። በአንብሮተ እድም ባርኳቸዋል (ሹሟቸዋል)። እየባረካቸውም ራቃቸው፥ወደ ሰማይም ዐረገ። (ዕርገቱ በርህቀት እንጂ በርቀት አልነበረም)።ሉቃ፡፳፬፥፶።      ከዚያ በፊት ትንሣኤውን እርግጠኞች እንዲሆኑ በተለያየ ቦታ እየተገለጠ ተዳስሶላቸዋል፥አብሯቸው በልቷል፥ጠጥቷል፥ምሥጢረ መጻሕፍትን ገልጦላቸዋል።መጽሐፈ ኪዳንንም አስተምሯቸዋል ።“ኢየሱስ የመረጣቸውን ሐዋርያትን በመንፈስ ቅዱስ ካዘዛቸው በኋላ እስከ ዐረገበት ቀን ድረስ ያደርገውና ያስተምረው ዘንድ፥ ዐርባ ቀን እየታያቸው፥ስለ እግዚአብሔርም መንግስት ነገር እየነገራቸው፥በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለእነርሱ ራሱን አሳያቸው።”ይላል።የሐዋ ፩፥፫።       የጌታ ዕርገቱ በትንቢት የተነገረ፥በቅዱሳን መላእክትና በቅዱሳን ሐዋርያት የተመሰከረ ነው።እነርሱ በእውነት የዓይን ምስክሮች ናቸውና።የሐዋ፡፩፥፱-፲፩።ስለሆነም ዕርገቱ የታመነ ነው ።ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ዕርገቱ ፍጹም የታመነ መሆኑን ሲያስረዳ “ሕማም የሚስማማውን ግዙፍ ሥጋን ተዋሕዶ ሳለ ከስቅለቱ አስቀድሞ በባሕር ላይ ከሄደ፥ዛሬ ነፋስን ከፍሎ ሲያርግ ቢታይ ማንም ማን አይጠራጠር፤ሥጋው አልተለወጠምና።”ያለው ለዚህ ነው።ሃይ፡አበው፡ክፍል ፲፫፥፲፭።     የጌታ ጥንተ ዕርገቱ ሐሙስ ግንቦት ፰ ቀን ፴፬ ዓ.ም. በዘመነ ማርቆስ ነበር።
Show all...
ከቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በቅዱሳን አበው ሐዋርያት ትውፊት በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የርክበ ካህናት መደበኛ ስብሰባውን ከግንቦት 21 እስከ ግንቦት 28 ቀን 2016 ዓ/ም ድረስ በርካታ አጀንዳዎችን በመቅረጽ ውይይት ሲያካሄድ ሰንብቷል፡፡ ምልዓተ ጉባኤው ለቤተ ክርስቲያናችን አንድነት፣ ለሐዋርያዊ ተልእኮ መስፋፋት፣ ለመንፈሳዊ ዕድገትና ለምእመናን ደኅንነት ትኩረት በመስጠት ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን ጠቃሚ የሆኑ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ በዚሁ መሠረት፡- ፩.በቅድስት ቤተ ክርስቲያንና በሀገራችን መንግሥት መካከል ሊኖር ስለሚገባው መልካም የሥራ ግንኙነት በቅዱስ ፓትርያርኩ መሪነት ከመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች ጋር የሚመካከር የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ልዑክ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰይሟል፤ ፪.በመላው ሀገራችን በተፈጠሩ ግጭቶች፣ አለመግባባቶችና የሰላም ዕጦት በርካታ የሰው ሕይወት መጥፋትና የንብረት ውድመት እንደቀጠለ መሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስን በእጅጉ አሳዝኗል፡፡ ስለዚህ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሁሉም ባለድርሻ አካላት ከግጭትና ከጥፋት ድርጊት ተቆጥበው የተፈጠረውን አለመግባባትና ግጭት በውይይትና በምክክር እንዲፈቱ እና ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ጥሪውን ያቀርባል፤ ፫.በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እየተከናወነ ባለው የኮሪደር ልማት ምክንያት ለፈረሱ የቤተ ክርስቲያናችን ይዞታዎች የከተማ አስተዳደሩ ምትክ ቦታ በመስጠትና ቤተ ክርስቲያናችን ወደ መልሶ ማልማት እንድትገባ ድጋፍ በማድረግ፤ በተለይም ክብርት ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አበቤ በፈረሰው የጽርሐ ምኒልክ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕንፃ ምትክ በከተማ አስተዳደሩ ሙሉ ወጭ ተጨማሪ ምድር ቤትና የቦታ ስፋት ያለው B+G+4 ሕንፃ ገንብቶ ለማስረከብ ቃል በመግባትና የቤተ ክርስቲያናችን የበላይ ኃላፊ አባቶች በተገኙበት የመሠረት ድንጋይ እንዲጣል ማድርጋቸውን ቅዱስ ሲኖዶስ ከምስጋና ጋር የተቀበለው ሲሆን በተሰጠን ምትክ ቦታ ላይም የከተማው ፕላን በሚፈቅደው መሠረት የመልሶ ማልማት ሥራው እንዲከናወን ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ ፬.የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከተቋቋመበት አዋጅ መረዳት እንደሚቻለው ባለድርሻ አካላትን ባሳተፈ ሁኔታ ሀገራዊ ችግሮችን በምክክርና በውይይት ለመፍታት የተቋቋመ መሆኑን ተረድተናል፡፡ ይሁን እንጅ ሀገረ መንግሥትን ከመመሥረት ጀምሮ በአስታራቂነትና በሰላም ግንባታ ግንባር ቀደም ተጠቃሽ ለሆነችው እናት ቤተ ክርስቲያን እስከአሁን ድረስ በይፋ የቀረበ የተሳትፎ ጥሪ ሳይኖር ኮሚሽኑ የተሳታፊ ልየታንና አጀንዳ መረጣ አጠናቆ ወደ ምክክር ትግበራ እየገባ መሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስን ቅር አሰኝቷል፡፡ በመሆኑም የቤተ ክርስቲያኒቱ ተሳትፎና አጀንዳ የማቅረብ መብቷ እንዲረጋገጥ ከኮሚሽኑ ጋር በመነጋገር ጉዳዩን ተከታትሎ ለፍጻሜ የሚያበቃ ኮሚቴ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰይሟል፡፡ ፭.የብፁዓን አባቶች የዝውውርና የአህጉረ ስብከት ሥያሜን አስምልክቶ የቀረቡ ጥያቄዎችን ምልዐተ ጉበኤው ተመልክቶ ተገቢውን ውሳኔ አሳልፏል፤ ፮.የሃይማኖት ጉዳዮች ረቂቅ አዋጅ ላይ ቅዱስ ሲኖዶስ በሰፊው ከተወያየ በኋላ በረቂቅ አዋጁ ሊሻሻሉ ይገባቸዋል ብሎ ያመነባቸውን የማሻሻያ ሐሳቦች በማዘጋጀት ለሚመለከተው መንግሥታዊ ተቋም እንዲላክና ረቂቅ አዋጁ ከመጽደቁ በፊት የተሰጡት የማሻሻያ ሐሳቦች በረቂቁ ስለመካተታቸው ክትትል የሚያደርግ ኮሚቴ ቅዱስ ሲኖዶስ ሰይሟል፡፡ ፯.በቅዱሳት መጻሕፍት ላይ ተመሥርቶ አባታዊ ምክርና ተግሣጽ ማስተላለፍ ከቀድሞ ጀምሮ የነበረ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሠረት ያለው መሆኑ ቢታወቅም በሀገራችን ኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተፈጠሩ አለመግባባቶች የተከሰቱትን ወቅታዊ ችግሮች አስመልክቶ እየተላለፉ ያሉ ቤተ ክርስቲያንን የማይወክሉ መልእክቶችን ቅዱስ ሲኖዶስ የማይቀበላቸውና በጥብቅ የሚቃወማቸው መሆኑን እየገለጸ ወደፊት እንዲህ ዓይነት ተመሳሳይ ድርጊት እንዳይፈጸም ለማድረግ ይቻል ዘንድ ወጥ የሆነ የመግለጫ አሰጣጥና የትምህርተ ወንጌል ተልእኮ ሕገ ደንብ ተዘጋጅቶ ለምልዐተ ጉበኤ እንዲቀርብ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤ ፰.ግብረ ሰዶማዊነትና የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻ በሕገ ተፈጥሮም ሆነ በሰው ልጅ የሰብዓዊ አኗኗር ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው፣ ፈጣሬ ዓለማት እግዚአብሔር መለኮታዊ ፈቃዱ በተገለጠባቸው ቅዱሳት መጻሕፍት ፈጽሞ የተከለከለ፣ በቀኖናተ ቤተ ክርስቲያን፣ በፍትሕ መንፈሳዊና በፍትሐ ብሔር ድንጋጌዎች፣ በሥነ ልቦና ደንቦች የተወገዘ፣ ሥነ አእምሮዊ ሚዛንን የሚያዛባ፣ ግለሰባዊ ማንነትን፣ ቤተሰባዊ ሕይወትን፣ ማኅበራዊ ትሥሥርን የሚጎዳ ተግባር በመሆኑ ቅዱስ ሲኖዶስ እያወገዘ የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻና የግብረ ሰዶማዊነትን ኃጢአት በተመለከተ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አቋም በሚገልጽ መልኩ ራሱን ችሎ ዓለም አቀፋዊ ይዘቱን ባገናዘበ ሁኔታ ዝርዝር መግለጫ እንዲሰጥ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፤ ፱.በደቡብ የሀገራችን ክፍል የቤተ ክርስቲያኒቱን አብነት ትምህርት ከማስፋፋትና ከፍ ያለ መዐርግ ከመስጠት አንፃር የጋሞና አካባቢው ዞኖች ሀገረ ስብከት የዝጊቲ ደብረ ሰላም አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያን የአራቱ ጉባኤያት ማስመስከሪያ ትምህርት ቤት እንዲሆን በቀረበው ጥናት መሠረት ቅዱስ ሲኖዶስ ለምሥክር ጉባኤ ቤቱ ዕውቅና በመስጠት ወደ ትግበራ እንዲገባ ወስኗል፡፡ ፲.ከሀገራችን ውጭ ባሉ አህጉረ ሰብከት መደበኛ አገልግሎት ለመስጠት የሚላኩ አገልጋዮች በክፍሉ ሊቀጳጳስ ሲጠየቅ በሙያ ብቃታቸው፣ በምግባራቸውና በመንፈሳዊነታቸው የተመሰከረላቸው አገልጋዮች ከሁሉም አህጉረ ስብከት በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት አቅራቢነት በውድድር እየተለዩ በቋሚ ሲኖዶስ ውሳኔ እንዲላኩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ ፲፩.የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ዘመኑን የዋጀ እንዲሆን ቅዱስ ሲኖዶስ የዐሥር ዓመት መሪ ዕቅድ በማጽደቅ ወደ ትግበራ እንዲገባ መወሰኑ ይታወሳል፡፡ በዚሁም መሠረት ለአፈጻጸሙ ያመች ዘንድ በባለሙያዎች ተዘጋጅቶ የቀረበውን መዋቅራዊ አደረጃጀት በማጽደቅ በሕገ ቤተ ክርስቲያኑና በቃለ ዓዋዲው ተካቶ ሥራ ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ ፲፪.በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ተዘጋጅቶ የቀረበውን የ2017 ዓ.ም. ዓመታዊ በጀት በማጽደቅ በሥራ ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ በአጠቃላይ ቅዱስ ሲኖዶስ በመንፈስ ቅዱስ እየተመራ ላለፉት ተከታታይ ቀናት በመንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ሀገራዊ ጉዳዮች ላይ በመወያየትና ተገቢውን ውሳኔ በማስተላለፍ መደበኛ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በጸሎት አጠናቅቋል፡፡ መሐሪና ሁሉን ቻይ የሆነ እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችን፣ ለሕዝባችን፣ ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣ ፍቅሩንና አንድነቱን ይስጥልን፡፡ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ግንቦት ፳፱ ቀን ፳፻፲፮ ዓ.ም. ኢትዮጵያ አዲስ አበባ ©የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት #ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን በአማን ተንሥአ እሙታን
Show all...
Choose a Different Plan

Your current plan allows analytics for only 5 channels. To get more, please choose a different plan.