en
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

Open in Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

Show more
613
Subscribers
+124 hours
-37 days
-1130 days
Posts Archive
🌼 ቅዱስ ዮሐንስ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፡፡ በሕይወቱና በኑሮው ሁሉ ጌታችንን ለመምሰል ይጥር ነበርና ጌታችንም እጅግ ይወደው ስለነበር "ፍቁረ እግዚእ" ተባለ፡፡ የታላቁ ያዕቆብ ታናሽ ወንድም ስለሆነና አባቱም ዘብድዮስ ስለሚባል "ዮሐንስ ወልደ ዘብድዮስ" ተባለ፡፡ ለጌታችን ባለው ቅናትና ከወንድሙ ጋር ሆነው ባሳዩት የኃይል ሥራ እንዲሁም የጌታችንን አምላክነት በመግለጡ "ወልደ ነጎድጓድ" ተብሏል፡፡ ነገረ መለኮትን ከሌሎቹ በበለጠ ሁኔታ አስፍቶና አምልቶ በማስተማሩ "ነባቤ መለኮት ወይም ታኦሎጎስ" ተብሏል፡፡ ኃላፊውንና መጻዒውን ጊዜ በራእዩ ስለገለጠ "አቡቀለምሲስ" ተባለ፣ ይህም በግሪክኛ ባለራእይ ማለት ነው፡፡ የጌታችንን መከራ መስቀሉን እያስታወሰ 70 ዘመን ሙሉ እያለቀሰ ስለኖረና ፊቱም በሀዘን ስለተቋጠረ "ቁጽረ ገጽ" ተብሏል፡፡ ከሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያስትፈን። በጸሎቱ ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን።                                                                               ✝ ✝ ✝ 🌼 #የእስክንድርያ_ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_መቃርስ፦ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ከቍጥራቸው ውስጥ ነው። ይህም አባት ከታናሽነቱ ጀምሮ በገድል የተጠመደ ሆነ የምንኲስናንም ልብስ ሊለብስ ወዶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ወጣ። በዚያም በመጀመሪያው አባት በአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መነኰሰ በምንኲስና ያለውንም ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ። 🌼 ይህምእርሱም ሁልጊዜ መጻሕፍትን የሚያነብና ትርጓሜያቸውንም የሚያስረዳ ሁኗልና በትሩፋት ስራ ከፍ ከፍ ባለ ጊዜ ቅስና ተሾመ። ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤልም በዐረፈ ጊዜ ኤጲስቆጶሳቱ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔዱ። ከእርሳቸውም ጋር ሃይማኖታቸው የቀና ብዙዎች አዋቂዎች ካህናት ነበሩ በአስቄጥስ ገዳም ከሚኖሩ ከታላላቅ መነኰሳትም ጋራ ስብሰባ አድርገው ለዚች ለከበረች ሹመት ስለሚገባው ሰው እየመረመሩ ብዙ ቀኖች ተቀመጡ። 🌼 ከዚህም በኋላ የተሻለና ለዚች ለከበረች ሹመት የሚገባ ይህን አባ መቃርስን አግኝተው ሊቀ ጵጵስና ሊሾሙት ሁሉም በአንድ ምክር ተስማው። ስለ ትሩፋቱና ስለ ተጋድሎው በአስቄጥስ ገዳም የሚኖሩ ብዙ መነኰሳት ምስክሮች ሁነዋልና ይዘውትም ሊሔዱ ያለ ፍቃዱ ይዘው አሰሩት እርሱ ግን እንዲህ እያለ ይጮህ ነበር። "እኔ ለዚች ለከበረች ሹመት የማልገባ ነኝ እናቴ ሁለት ባሎችን አግብታ ስለነበር" ይህንንም ያለው እንዲተዉት እንጂ እናቱ ግን በአንድ ባል ብቻ የኖረች ሌላ የማታውቅ ንጽሕት እንደሆነች ስለርሷ ብዙዎች ምስክሮች ሁነዋልና። ስለዚህ እርሱ  የተናገረውን ምክንያት አልተቀበሉትም። 🌼 ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ወስደው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት ከዚያም ወደ ምስር አውጥተው በመዓልቃ በሚገኘው አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሹመቱ ደብዳቤ በዮናኒ በቅብጥ በአረብ ቋንቋ ተነበበች። 🌼 ከዚህም በኋላ በሹመቱ ወራት በጎ ስራ ትሩፋትን ተጋድሎውን አብዝቶ የሚሰራ ሆነ ። ሁል ጊዜም ለህዝቡ እግዚአብሔርን እንዲፈሩ ያስተምራቸዋል ስለ ነፍሳቸውም ድኀነት ይገሥጻቸው ነበር። 🌼 በሹመቱ ወራትም ከራሱ ከሚገባው ከግብሩ ለቤተ ክርስቲያን ይሰጣል ለድኆችና ለችግረኞችም ይመጸውታል እንጂ ከቤተ ክርስቲያን ገንዘብ ምንም ምን አልወሰደም። በሹመቱም ሃያ ሰባት ዓመት ኖረ እግዚአብሔርንም አገልግሎ ደስ አሰኝቶ በሰላም በፍቅር ሳለ ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ መቃርስ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 4 ስንክሳር።                           ✝ ✝ ✝ 🌼 "#ሰላም_ለመቃርስ_በእስክንድርያ_ዘተአምነ። መርዔተ ክርስቶስ ይርዓይ መሲሐውያነ። ለእለ ኀረይዎ ሕዝብ ዘይሰመዩ ኄራነ። ጸሊዖ ሢመተ እንዘ ውእቱ ኢኮነ። ወልደ ዳግሚት ብእሲት ይቤሎሙ አነ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_4።                          ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወወሀብኮሙ ትእምርተ ለእለ ይፈርሁከ። ከመ ያምሥጡ እምገጸ ቅስት። ወይድኀኑ ፍቁራኒከ"። መዝ 59፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት 1 ጢሞ 3፥1-8፣ 1 ጴጥ 5፥9-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 7፥44-51። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 6፥1-22። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ ዮሐንስ የልደት በዓል እና የብፁዕ አባ ሙሴ የዕረፍት በዓል ለሁላችንም ይሁንል።

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼           🌼  #መስከረም ፬ (4) ቀን። 🌼 እንኳን #ለሐዋርያው_ለወንጌላዊው ለወልደ ነጎድጓድ #ለቅዱስ_ዮሐንስ_ለልደት_በዓል፣ #ለነዌ_ልጅ_ለቅዱስ_ኢያሱ ለመታሰቢያ በዓሉና ለእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት #ለአባ_መቃርስ_ዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #በአንጾኪያ_በሰማዕትነት_ከዐረፉ_ከ_2መቶ_ሰዎች ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                          ✝️ ✝️ ✝️ 🌼 #ቅዱስ_ዮሐንስ_ወንጌላዊ፡- ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን ለመስበክ ዕጣ የደረሰው እስያ ስለነበር ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን አስከትሎ ሄደ፡፡ ይኽችውም ኤፌሶን በጥንቱ በታናሽ እስያ በዛሬው የቱርክ ግዛት ውስጥ ከተማ ናት፡፡ ዛሬ ኢያዞሎክ ተብላ የጥንት ታሪኳ ጠፍቷል፡፡ አስቀድሞ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን ሰብኮባታል፡፡ ደቀ መዝሙሩን ቅዱስ ጢሞቴዎስንም በከተማዋ ላይ ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾሞት ነበር፡፡ እርሱም በግፍ እስከተገደለበት ጊዜ ድረስ ቅዱስ ዮሐንስን እየረዳው በከተማዋ ብዙ አገልግሏል፡፡ በኋላ ግን በግፍ ገድለውታል፡፡ 🌼 ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ኤፌሶን ለመሄድ በመርከብ ሲሳፈር መርከቡ በማዕበል ተሰበረ፡፡ ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን ማዕበሉ ወደ አንዲት ደሴት አደረሰው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በመርከቡ ስባሪ ተንጠልጥሎ በባሕሩ ማዕበል መካከል 40 ቀንና 40 ሌሊት ከኖረ በኋላ ማዕበሉ ተፍቶ አብሮኮሮስ ካለበት ደሴት አደረሰውና ተያይዘው ኤፌሶን ከተማ ገቡ። የከተማይቱም ሰዎች እጅግ ክፉዎች ስለነበሩ መጀመሪያ ላይ ቅዱስ ወንጌልን መስበክ አልቻሉም ነበር፡፡ እነርሱም እጅግ ክፉዎች መሆናቸውን ስላወቀ ቅዱስ ዮሐንስ ገና ዕጣው ሲደርሰው በሀዘን አልቅሶ ነበር፡፡ አሁንም ከተማው በገቡ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ምክንያት በመፍጠር ሮምና ለምትባል ሴት የውሽባ ቤቷ እሳት አንዳጅ ሆኖ አብሮኮሮስም ዕቃ አጣቢ ሆነው ተቀጠሩ፡፡ የቀጠረቻቸው ሴትም እጅግ ታሠቃያቸው ጀመር፡፡ ባሮቿ እንደሆኑ ተስማምተው ስለጻፉላት ትደበድባቸውም ነበር፡፡ እነርሱም በታላቅ ጉስቁልና ውስጥ እየኖሩ እያለ በአንዲት ዕለት የአገረ ገዥው ልጅ ለመታጠብ ወደ ውሽባው ቤት ገባ፡፡ በውሽባ ቤቱም የሰይጣን ኃይል ስለነበረበት የመኰንኑን ልጅ አንቆ ገደለው፡፡ የአገሪቱም ሰዎች ሁሉ ለሞተው የመኰንን ልጅ ሊያለቅሱ ሲሰበሰቡ ቅዱስ ዮሐንስም አብሮ ቆሞ ሲመለከት ሮምና መጥታ "በጌታዬ ልጅ ሞት ልትደሰት መጣህን" እያለች ረገመችው፡፡ እርሱም "አይዞሽ አትዘኚ" አላትና ወደ ሞተው ልጅ ቀርቦ በመስቀል ምልክት ካማተበበት በኋላ በፊቱ እፍ አለበት፡፡ የሞተውም ልጅ ድኖ ተነሣ፡፡ የሀገሪቱም ሰዎች እጅግ ደነገጡ፡፡ ሮምናም ደንግጣ "እግዚአብሔር የሚሉት አምላክ አንተ ነህን" ብላ ጠየቀችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም "በፍጹም እኔ አምላክ አይደለሁም፣ እኔ የእርሱ አገልጋዩና ሐዋርያው ነኝ እንጂ" አላት፡፡ ሮምናም ስለበደለቻቸው በደል ሁሉ መሪር ዕንባን እያለቀሰች ይቅር እንዲሏት ለመነቻቸው፡፡ እነርሱም አረጋጉዋት፡፡ ከሕዝቡም ውስጥ ብዙዎቹ በጌታችን አመኑ፡፡ 🌼 ቅዱስ ዮሐንስም ሌሎች ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ ወንጌልን እየሰበከ ከጣዖት አገልጋዮች በቀር ሁሉንም አሳምኖ አጠመቃቸው፡፡ አገልጋዮችን ኤጲስቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ከሾመላቸው በኋላ ወደ ሌሎች አቅራቢያ አገሮች ሄደ፡፡ በመጨረሻም በከሃዲውና በጨካኙ በድምጥያኖስ ዘመን በጣዖት አምላኪዎች ተከሶ ለፍርድ ቀረበ፡፡ በፈላ ውኃ ካሠቃዩት በኋለ በፍጥሞ ደሴት አጋዙት፡፡ በዚያም ሳለ ራእዩን ተመልክቶ ጻፈው፡፡ ድምጥያኖስም ከተገደለ በኋላ ከግዞቱ ተመልሶ ሦስቱን መልእክታቱንና ቅዱስ ወንጌሉን ጽፏል፡፡ 🌼 ጌታችንም አስቀድሞ ሞትን እንደማይቀምስ ለዮሐንስ ቃል ገብቶለት ነበርና (ዮሐ 21፡22) ጥር 4 ቀን እንደ ኤልያስና ሄኖክ ሞትን እንዳያይ ወደ ብሔረ ሕያዋን ወስዶታል፡፡ ጌታችን ለዮሐንስ ያልነገረው እርሱም ያላስተማረው ምሥጢር የለም፡፡ ወንጌሉን መጻፍ ሲጀምር "በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ..." ብሎ የጌታችን ነገር ተመራምሮ ለመድረስ ሲል በመሀል መልአኩን በዮርዳኖስ ባሕር ላይ ሲሄድ አገኘው፡፡ መልአኩም የዮርዳኖስን ባሕር በእንቁላል ቅርፊት እየጨለፈ ወደ ውጭ ሲያፈስ ተመለከተው፡፡ ዮሐንስም ተገርሞ "ምን ማድረግህ ነው" አለው፡፡ መልአኩም "የዮርዳኖስን ባሕር ቀድቼ እየደፋሁ ልጨርሰው ነው" ሲለው ዮሐንስም መልሶ "ታዲያ በእንቁላል ስባሪ ነውን?" አለው፡፡ መልአኩም "አዎን" አለው፡፡ ዮሐንስም "በከንቱ ደከምክ" አለው፡፡ ይህን ጊዜ መልአኩም መልሶ "አንተስ እንጂ ደግሞ የአምላክን መገኘት፣ አኗኗሩንም ተመራምረህ በጥበብ ለማግኘት ብለህ "በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ.." ብለህ ጀምረህ የለምን? አንተ ጌታን ተመራምረህ ካገኘህና ከደረስክበት እኔም የዮርዳኖስን ወንዝ በዚህ እንቁላል ቅርፊት ቀድቼ እጨርሰዋለሁ" አለው፡፡ ዮሐንስም ይህን ጊዜ ደንግጦ ዝቅ ብሎ "ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ…" ብሎ ሀሳቡን ለወጠና ሌላ ታሪክ ቀጠለ፡፡ 🌼 ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ክርስቲያኖችን ሁሉ ወክሎ እመቤታችንን በአደራ የተቀበለ እርሱም ለእመቤታችን በአደራ የተሰጠ ሲሆን እመቤታችንን ከወሰዳት በኋላ ለ15 ዓመት እየተንከባከበ ጠብቋታል፡፡ እናቱም በሕፃንነቱ ስለሞተች እመቤታችን ናት እየተንከባከበች ያሳደገችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በመልኩም ከጌታችን ጋር ይመሳሰል ነበር፡፡ 🌼 ቅዱስ ዮሐንስ ሥዕል የመሳል ተሰጥኦም ነበረው፡፡ ጌታችን በተሰቀለበት ዘመን የነበረው ጢባርዮስ ቄሳር ልጁ በሽተኛ ነበር፡፡ የጌታችንን የማዳን ሥራ እየሰማ እነ ጲላጦስም ስለጌታችን የሚጽፉለትን ይሰማ ስለነበር ልጁን ከጌታችን መቃብር ላይ እንዲያኖሩለት ላከው፡፡ ልጁም ፈጥኖ ተፈወሰለት፡፡ ጢባርዮስ ቄሳርም በልጁ መዳን ምክንያት የጌታችንን ውለታ ማስቀመጥ ፈልጎ የጌታችንን ሥዕሉን የሚሥልለትን ሲያጠያይቅ ቅዱስ ዮሐንስን አገናኙት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ጌታችንን ልክ በዕለተ ዓርብ እንደተሰቀለ አድርጎ በመሣል ለጢባርዮስ ቄሳር ሰጠው፡፡ ሲሥለውም በመጀመሪያ ጌታችንን ልክ እንደተሰቀለ አድርጎ ራቁቱን ነበር የሳለው፡፡ ዮሐንስ የሳለው የጌታችን ሥዕልም አፍ አውጥቶ "በመጀመሪያ አይሁድ በኢየሩሳሌም ራቁቴን ሰቀሉኝ፣ አሁን ደግሞ አንተ ድጋሚ በሮም ራቁቴን ትሰቅለኝን?" ብሎ ተናገረው፡፡ ዮሐንስም እጅግ ደንግጦ "እንዴት አድርጌ ልሳልህ?" ብሎ የሳለውን ሥዕል ቢጠይቀው ሥዕሉም "ከለሜዳ አልብሰህ ሳለኝ" አለው፡፡ ዮሐንስም እንዳለው ከለሜዳ አልብሶ ከሳለው በኋላ ሥዕሉን ትኩር ብሎ ተመልክቶ ቢስመው ከንፈሩ አንድ ቀን ተኩል ያህል ተጣብቆ ቆይቷል፡፡ ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የምትጠቀምባቸውን የጌታችንን ስነ ስቅለት የሚያሳዩ ሥዕሎች መገኛቸው ይህ ወንጌላዊው ዮሐንስ የሳለው ሥዕል ነው፡፡

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼            🌼 #መስከረም ፬ (4) ቀን። 🌼 እንኳን #ከግብጽ_ለኢትዮጵያ_ሊቀ_ጳጳስ ተሾመው ለመጡ በመላው ዓለም እና በኢትዮጵያ ብዙ የዋሻ እና የሕንጻ ቤተ ክርስቲያንን ላነጹ #ለብፁዓዊ_አቡነ_ሙሴ ዘድባ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                             ✝ ✝ ✝ 🌼 #ብፁዕ_አቡነ_ሙሴ_ዘድባ፦ በአባታቸው የእቤታችን ጠባቂ የአረጋዊ ቅዱስ ዮሴፍ የልጅ ልጅ ሲሆኑ፤ በእናቸው በኩል ድንግል ማርያም ከልጇ ጋር በቃና ዘገሊላ ሰርግ የተገኘችበት የዶኪማስ የልጅ ልጅ ናቸው። የአባታቸው ስም ቅዱስ ዮስጦስ ሲባል፤ የእናታቸው ስም ቅድስት ጵስርስቅላ (ሶልያና፡ማርያም) ይባላል። 🌼 በሊቀ መላእክት በቅዱስ ገብርኤል አብሳሪነት ታኅሣሥ 8 ቀን ተወለዱ። በዚህች ቀን ከእናታቸው እቅፍ በመውረድ "ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን፤ ከጨለማ ወደ ብርርሃን ላወጣኸኝ" ብለው ፈጣርያቸውን አመስግነዋል። በ40 ኛው ቀን የጌታ ሐዋርያት ቅዱሳን ጴጥሮስ፣ ያዕቆብ፣ ፊሊጶስና እንድርያስ ሆነው ጥር 18 ክርስትናን አቡነ ሙሴን አነሱዎቸው። 🌼 በ3 ዓመታቸው ወላጆቻቸው ለቤተ ክርስቲያን ሰጧቸው። ቅዱስ ፋኑኤልና ቅዱስ ዮናኤል ሕብስት ሰማያዊ እያመጡ ይመግቧቸው ነበር። ከዚህ በኋላ መምህራቸው ዝክረ ጻድቅ ብሉያትንና ሐዲሳትን አስተማራቸው። በወንጌላዊው በቅዱስ ማርቆስ እጅ ዲቁና ተሾሙ። እመቤታችን ማርያምም ለብፁዓዊ ሙሴ ልፋፈ ጽድቅ፣ ሰኔ ጎልጎታን፣ ባርቶስና ራዕየ ማርያምን ሰታቸዋለች። ወገባቸውን ከጠጉር በተሰራ መታጠቂያ ይታጠቁ ነበር። አቡነ ዘበሰማያትም በጀመሩ ጊዜ ሰባቱ ሰማያት ተከፍተውላቸው ከአጋዕዝተ ዓለም ሥላሴ ጀምሮ ሁሉንም ቅዱሳን በግልጥ ያያሉ። ሲሰግዱ እንባቸው ደረታቸውና እግራቸውን እያራሰ በመሬት ይፈሳል። በዓለም ብዙ የዋሻ ቤተ ክርስቲን አንጸዋል። 🌼 የህንፃ ሥራ ከመደመራቸው በፊት 40 ቀን ይጾማሉ። ሁለቱ መላእክት ቅዱስ ፍርክኤልና ቅዱስ ፍናኤል እየረዷቸው መቅደስን ያንጻሉ። የዋሻ ቤተ መቅደስ ሥራ ጎን ለጎን መስቀልና ሌሎች ንዋየ ቅዱሳት ይሠራሉ። የሚሠሯቸው መቅደሶች ከፊሉ የሚታዩ ምዕመናን የሚገለገሉባቸው ሲሆን የቀሩት የማይታዩ ስውራን የሚገለገሉበት ነው። አቡነ ሙሴ ጵጵስና የተሾሙት በ 12ቱ ሐዋርያት በአንድነት ነው። ዘመናቸውን ሁሉ ከ24ቱ ካህናተ ሰማይ ጋር በመሆን የአብ የወልድ የመንፈስ ቅዱስን መንበር አጥነዋል። በድንግልናቸው በንጽሕናቸው የከበሩ 12 ክንፍ የተጎናጸፉ ናቸው። ጥቂቶች ለማየት የታደሉትን ብሔረ ብፁዓን ሄደው አይተዋል። 🌼 አቡነ ሙሴ በግብፅና በእስራኤል መካከል ሲካር በሚባል ቦታ ካገለገሉ በኋላ ጣዖታትን ለማሳፈር ወደ መቄዶንያ ሄደው ጣዖት አምላኪውን ንጉሥ ገሰጹት። ንጉሥ ተቆጥቶ አጥንታቸው እስኪሰበር ድረስ በብረት አስደብድቦ በብረት አልጋ ላይ አስተኝቶ እሳት አነደደባቸው። ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል ግን ዳሰው ፈወሷቸው። በማግስቱ ወደ ፍርድ አደባባይ ቢወስዷቸው ምንም እንዳልሆኑ ንጉሡ በማየቱ በንዴት ሰውነታቸውን በሰይፍ አስቆራረጠ። ከሰውነታቸው ደም፣ ውሃ፣ ወተትና መዓር ወጣ። ጌታችንም አድኗቸው "በስምህ የተማፀነውን መልካም ነገር አደርግታለሁ" ብሎ ቃል ኪዳን ገባላቸው። 🌼 በግብጽ አንስጣስዮስ ቴዎዶስዮስ ተብለው ሢነግሡ መላእክት የአባቱ የዳዊት መንግሥት ቅባት ቀቧቸው፤ የመንግሥት ልብስ አለበሷቸው፤ የመንግሥት ሥርዓት ሁሉ ሰጧቸው። የጣዖታትን ቤት አፍርሱ "ቤተ ክርስቲያንን ሥሩ" በማለት ኅዳር 12 ቀን አዋጅ ነጋሪን ላኩ። ጌታችን በግብፅ ተሶዶ ሳለ ለአረጋዊ ቅዱስ ዮሴፍ የተናገረው ትንቢት ተፈፀመ "ከልጅህ የሚወለድ በግብፅ ያሉትን ጣዖቶች አፍርሶ ሃይማኖትን ያጸናል" ብሎ ነበር። እዲሁም ቅድስት አርሴማ ሳትወለድ በስሟ የተሰየመውን ታቦት በግብፅ ያገኙና ያከበሩ ናቸው (ገድለ አርሴማ 7ኛ ተአምር)። 🌼 በግብፅ ደብረ ምጥማቅ ማርያም በመጀመሪያ ሰርተው የቀደሱት አቡነ ሙሴ ናቸው። በተጨማሪ ብዙ የሕንጻ ቤተ ክርስቲያንና የዋሻ ቤተ ክርስቲያን አንጸዋል። እንደ ቅዱሳን ብዙ ድንቅ ተአምር አድርገዋል። ለምሳሌ አውሬ ገድሏቸው ተጠራቅሞ የነበረ አፅም ላይ ጸልየው አራት ሺህ የሞቱ ሰዎችን ከሞት አስነስዋል። 40 ዓመት በንግሥና ከቆዩ በኋላ ከብዙ ተከታዮቻቸው ጋር ወደ አስቄጥስ ገዳም ለምነና ስጓዙ በበረሃው ተርበው ለወደቁት ወደ እግዚአብሔር ሲጸልዩ መና ወርዶላቸው መግበዋል አስቄጥስ ገዳም ሲደርሶ አቡነ መቃርስ ነበሩ የተቀበሏቸው፡፡ 🌼 በአስቄጥስ በአቡነ እንጦንስ ስም የመጀመሪያውን ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ከፈፀሙ በኋላ አቡነ እንጦንስንና አቡነ መቃርስ በምንኵስና ልብስ፣ በመላእክት አስኬማ፣ በቅንዓት፣ በቀሚስና በቆብዕ ላይ ለ40 ቀን ጸልየው ጥር 22 ቀንተክለ ማርያም ብለው ሰይመው አመነኰሷቸው። በዚያውም አቡነ መቃርስ ከበታቻቸው ሾሙ። በአስቄጥስ ብዙ ተከታዮቻቸውን አመንኵሰው ቀድሞ ወደ፡ሠሯቸው ቤተ መቅደሶች ይልኳቸው ነበር። የቀሩት ደግሞ በኋላ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ አብረዋቸው መጥተዋል። 🌼 የኢትዮጵያ የመጀመርያው ጳጳስ አቡነ ሰላማ በማረፋቸው ነገሥታት አብርሃ ወአጽብሃ ጳጳስ እንዲልኩላቸው ከእጅ መንሻ ጋር ወደ ግብፅ ላኩ። አቡነ አትናቴዎስ ፈቃደ እግዚአብሔር ጠይቀው አቡነ ሙሴ ከአስቄጥስ ገዳም ለኢትዮጵያውያን አባት እዲሆኑ አቡነ ሚናስ ብለው ሾሙ። ከሦስት ሺህ ልጆቻቸው ጋር ሆነው ብዙ ቅርስ ይዘው አባታችን ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ሕዝቡ በደስታ ተቀበሏቸው። ብዙ መጽሐፍትን ከአረብኛ ወደ ግእዝ ቋንቋ ተርጉመው ጽፈዋል። ይጽፉበት የነበረው ብዕር አድሮ በማግስቱ ለምልሞ አብቦ ይገኛል። ቀለም ይበጠብጡበት የነበረው የቀንድ ዋንጫም ከመሬት ተጣብቆ ያገኙት ነበር። በእጃቸው ሲያላቅቁት ከመሬት ጠበል ይፈልቃል፣ በጠበሉም ህሙማንን ፈውሰውበታል። 🌼 በኢትዮጵያ 5መቶ የዋሻ ቤተ ክስቲያን ያነጹ ሲሆን በአጠቃላይ በመላው ዓለም ከ10 ሺህ በላይ ቤተ ክርስቲያ ሰርተዋል፣ አንጸዋል (መለከት መጽሔት 2007 ዓ.ም)። በእንቁና በእብነ በረድ ከሠራቸው ቤተ ክርስቲያኖች መካከል በአራራት ደብር (ከምድር ጥፋት በኋላ የኖኅ መርከብ መጀመርያ ያረፈችበት) በጻድቁ ኖኅ ስም፣ አብርሃም ሥላሴን በድንኳኑ ባስተናገደበት ስፍራ በቅድስት ሥላሴ ስም፣ በሕንድ (በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ መቃብር ቦታ) በቅዱስ ቶማስ ስም፣ በአርማንያና በፋርስ (በሰማዕቱ ቅዱስ ጊዮርጊስ ስጋውን ባሳረፉበት ቦታ) በቅዱስ ጊዮርጊስ ስም። 🌼 በኢትዮጵያ በአቡነ ሙሴ ከታነጹት ቤተ ክርስቲያ ውስጥ የተወሰኑት፦ 1.የድባ መቅደሰ ማርያም አቡነ ሙሴ አንድነት ገዳም (ባለ ሰባት መቅደስ ፎቅ)፣ የረፍታቸው ቦታ፣ በትረ ሙሴያቸውና የእጅ መስቀላቸው ያለበት (ሰሜን ወሎ ዳውንት) 2.አእማድ ቅድስት ሥላሴ ገዳም (መቄት) እንደ አቡነ አሮን መንክራዊ ጣራው ክፍት ሆኖ ዝናብ የማይገባው፣ 🌼 በመጨረሻ ብፁዕ አቡነ ሙሴ በቤተ ሚናስ ቤተመቅደስ የድባ መቅደሰ ማርያም አቡነ ሙሴ ገዳም መሰከረም 4 በዕለተ እሁድ ዐረፋ። ወርሃዊ በዓላቸው ወር በገባ በ4 ነው። በተለይ ጋብቻን የሚቀድሱ፣ ክህነት የሚባርኩ፣ መናንያንን የሚያጸኑ አረጋዊን አባት ናቸው። ከአባታችን ከብፁዕ አቡነ ሙሴ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትንና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸውም ይማረን!። ምንጭ፦ የድባ መቅደሰ ማርያም አቡነ ሙሴ አንድነት ያሳተመው መጽሔት ላይ የተወሰደ።

✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን ሰላም  እንደምን ዋላቹ ዉድ የፍኖተ ብርሃን ሰንበት ት/ቤት አባላት የእሁድ መርሀግብር  ዛሬም እንደሚኖር ለማሳወቅ እንወዳለን !!

🌿🌿🌿🌿  የዕለቱን ወንጌል እናንብብ! 🌿🌿🌿🌿          ዕለተ ሰንበተ ክርስቲያን! መስከረም 3 ቀን  2019 ዓ.ም          የዮሐንስ ወንጌል ም 1 ቁ 15 - 38 —————————————————————————— ¹⁵ ዮሐንስ ስለ እርሱ መሰከረ እንዲህም ብሎ ጮኸ፦ ከእኔ በኋላ የሚመጣው እርሱ ከእኔ በፊት ነበረና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፤ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነበረ። ¹⁶ እኛ ሁላችን ከሙላቱ ተቀብለን በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጥቶናልና ሕግ በሙሴ ተሰጥቶ ነበርና፤ ¹⁷ ጸጋና እውነት ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ሆነ። ¹⁸ መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው። ¹⁹ አይሁድም፦ አንተ ማን ነህ? ብለው ይጠይቁት ዘንድ ከኢየሩሳሌም ካህናትንና ሌዋውያንን በላኩበት ጊዜ፥ የዮሐንስ ምስክርነት ይህ ነው። ²⁰ መሰከረም አልካደምም፤ እኔ ክርስቶስ አይደለሁም ብሎ መሰከረ። ²¹ እንኪያስ ማን ነህ? ኤልያስ ነህን? ብለው ጠየቁት። አይደለሁም አለ። ነቢዩ ነህን? አይደለሁም ብሎ መለሰ። ²² እንኪያስ፦ ማን ነህ? ለላኩን መልስ እንድንሰጥ፤ ስለራስህ ምን ትላለህ? አሉት። ²³ እርሱም፦ ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለ፦ የጌታን መንገድ አቅኑ ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ እኔ ነኝ አለ። ²⁴-²⁵ የተላኩትም ከፈሪሳውያን ነበሩና፦ እንኪያስ አንተ ክርስቶስ ወይም ኤልያስ ወይም ነቢዩ ካይደለህ፥ ስለ ምን ታጠምቃለህ? ብለው ጠየቁት። ²⁶ ዮሐንስ መልሶ፦ እኔ በውኃ አጠምቃለሁ፤ ዳሩ ግን እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሞአል፤ ²⁷ እኔ የጫማውን ጠፍር ልፈታ የማይገባኝ፥ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ከእኔ ይልቅ የሚከብር ይህ ነው አላቸው። ²⁸ ይህ ነገር ዮሐንስ ያጠምቅበት በነበረው በዮርዳኖስ ማዶ በቢታንያ በቤተ ራባ ሆነ። ²⁹ በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ። ³⁰ አንድ ሰው ከእኔ በኋላ ይመጣል፥ ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል ብዬ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነው። ³¹ እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ እያጠመቅሁ እኔ መጣሁ። ³² ዮሐንስም እንዲህ ብሎ መሰከረ፦ መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ ሲወርድ አየሁ፤ በእርሱ ላይም ኖረ። ³³ እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን በውኃ አጠምቅ ዘንድ የላከኝ እርሱ፦ መንፈስ ሲወርድበትና ሲኖርበት የምታየው፥ በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው አለኝ። ³⁴ እኔም አይቻለሁ እርሱም የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ መስክሬአለሁ። ³⁵ በነገው ደግሞ ዮሐንስ ከደቀ መዛሙርቱም ሁለት ቆመው ነበር፥ ³⁶ ኢየሱስም ሲሄድ ተመልክቶ፦ እነሆ የእግዚአብሔር በግ አለ። ³⁷ ሁለቱም ደቀ መዛሙርት ሲናገር ሰምተው ኢየሱስን ተከተሉት።

🌼 #ነገ_መስከረመ_3_ቀን_ሰንበተ_ሰንበታት 🌼 በዓመት ውስጥ አራት ሰንበተ ሰንበታት አሉ ። እነዚህ ቀናት የሚሰሉት #የዓመቱን_365_ቀናት_ለ4 በመክፈል (#91_ቀናት በመቁጠር) ነው። 🌼 የ2019 ዓ.ም የሰንበተ ሰንበታት ቀናት መስከረም 1 ቀን አርብ ስለዋለ፣ በዚህ ዓመት የሚውሉባቸው ቀናት እንደሚከተለው ይሆናሉ፡ 1ኛው ሰንበተ ሰንበታት  #መስከረም_3 2ኛው ሰንበተ ሰንበታት  #ታኅሣሥ_4 3ኛው ሰንበተ ሰንበታት  #መጋቢት_5 4ኛው ሰንበተ ሰንበታት  #ሰኔ_6 ይሆናል ። 🌼 በሌላ ቀላል ዘዴም ማወቅ ይቻላል ይኸውም መስከረም ፣ ታህሣሥ፣ መጋቢት ፣ ሰኔ በእነዚህ 4 ወራት የመጀመሪያው እሁድ ሰንበተ ሰንበታት ይሆናል። የእነዚህ የ4ቱ ዕለታት ማሳረጊያ ደግሞ ጳጕሜን 3 ናት። -> በእነዚህ ዕለታት ርኆተ ሰማይ የሚሆንባቸው በመሆናቸው  የዚህ ዓመት 1ኛው ሰንበተ ሰንበታት #መስከረም_7 ስለሆነ ከወትሮው በተለየ መልኩ  እግዚአብሔርን የምናመሰግንበት፣ ምሕረትን የምንለምንበት እና ለራሳችንና ለሀገራችን ሰላም የምንጸልይበት ታላቅ ዕለት ነው። ጸሎታችንና ምልጃችን በፊቱ ይድረስ!።

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼 🌼 እንኳን ለዚህ ዓመት የመጀመሪያ ሳምንት ዕለተ እሑድ #ለዘመነ_ዮሐንስ ስለ #መጥምቀ_መለኮት_ቅዱስ_ዮሐንስ ለሚታሰብበት ዕለት ሰንበት እሑድ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፭ "#ዮሐንስ_አኅድዐ_እምካልዓኒሁ_አንሐ_ወክሐ እንዘ ይብል እምላዕሉ ወረደ እንዘ ይብል እምላዕሉ ወረደ ቃለ አብ #ወተሐውከ_ማየ_ዮርዳኖስ እምግርማ መለኮት ወደንገጹ ኵሉ ኃይለ ሰማያት ወምድር ከማሁ ኮነ በቢታንያ በቤተ ራባ በማዕዶተ ዮርዳኖስ ወሶበ ርእዮ #ዮሐንስ_ለኢየሱስ ከልሐ ወይቤ ነዋ በግዑ #ለእግዚአብሔር_ይቤሎ_ኢየሱስ_ለዮሐንስ አጥምቀኒ በማይ ከመ ይትቀስ ማይ በማዕተበ ሰማይ። አጥመቆ ዮሐንስ ለኢየሱስ በፈለገ ዮርዳኖስ እምድኅረ አጥመቀ ለሊሁ ተጠምቀ ምህሮሙ ለሕዝብ ወይቤሎሙ አክብሩ ሰንበተ ተገበሩ ጽድቀ። ትርጉም፦ #የአብ_ቃል_ከላይ_ወረደ፤ የአብ ቃል ከላይ ወረደ እያለ ዮሐንስ ከሌሎቹ ይልቅ አሰምቶ ተናገረ፤ #የዮርዳኖስ_ውኃ_ከመለኮት_ግርማ የተነሣ ታወከ፤ የሰማያትና የምድር ኀይል ሁሉ ደነገጡ፤ በቢታንያና በቤተ ራባ በዮርዳኖስም ማዶ እንዲሁ ሆነ፤ #ዮሐንስ_ኢየሱስን ባየው ጊዜ እነሆ #የእግዚአብሔር በግ እያለ ጮኸ፤ #ኢየሱስም_ዮሐንስን በሰማይ ምልክት ውኃ ይቀደስ ዘንድ በውኃ አጥምቀኝ አለው። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።                              ✝ ✝ ✝ 🌼 ዘመነ ቅዱስ ዮሐንስ፤ ርእሰ ዐውደ ዓመት። 🌼 የኢትዮጵያ ዘመን መለወጫ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት መስከረም አንድ ቀን ይከበራል፡፡ ስያሜው ቅዱስ ዮሐንስ በመባል ሲታወቅ ከመስከረም አንድ እስከ ሰባት ድረስ ያሉት ዕለታትንም ያካትታል፡፡ በዚህ ወቅት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚዘመረው መዝሙር ክብረ ቅዱስ ዮሐንስንና ርእሰ ዐውደ ዓመትን የሚያወሳ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ያስተማረውን ትምህርትና ገድሉን የሚያመለክት ስብከት ይሰበካል፤ ትምህርቱም ይሰጣል፡፡ አዲስ ዓመት ዘመን መለወጫ በመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ስም የተሰየመበት ምክንያት፡- ፩. የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል መነሻ በመሆኑ 🌼 ቅዱስ ማርቆስ በወንጌሉ "እነሆ÷ መንገድህን በፊትህ የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ፡፡ የእግዚአብሔርን መንገድ ጥረጉ፤ ጥርጊያውንም አስተካክሉ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኽ የአዋጅ ነጋሪ ድምጽ፤ ዮሐንስም በምድረ በዳ ያጠምቅ ነበር፤ ኃጢአትንም ለማስተስረይ የንስሓ ጥምቀትን ይሰብክ ነበር፡፡ የይሁዳና የኢየሩሳሌምም ሰዎች ሁሉ ወደ እርሱ ይሄዱ ነበር፤ ኃጢአታቸውንም እየተናዘዙ በዮርዳኖስ ወንዝ ሁሉንም ያጠምቃቸው ነበር"  ማር.፩፥፪-፭ ብሎ ጽፎልናል፡፡ 🌼 የካህኑ ዘካርያስ ልጅ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በዘመነ ብሉይ መጨረሻና በዘመነ ሐዲስ መጀመሪያ ላይ ተነስቶ "መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ" እያለ ስለ ክርስቶስ አዳኝነት በምድረ በዳ እያስተማረና የንስሓ ጥምቀት እያጠመቀ በዘመነ ወንጌል መጀመሪያ ምዕራፍ ተገኝቷል፡፡ እንዲሁም መጥምቁ ዮሐንስ በነቢያት መጨረሻ በሐዋርያት መጀመሪያ ተገኝቶ ዘመነ ሐዲስን እንደሰበከና ከዘመነ ብሉይ ወደ ዘመነ ሐዲስ መሸጋገሪያ ጊዜ ላይ ስለነበረ ያለፈውን ዘመን የምንሸጋገርበት የዘመን መለወጫ ቀን የቅዱስ ዮሐንስ መታሰቢያ እንዲሆን ተደርጓል፡፡ ፪. መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የጻድቃን የሰማዕታት ርእስ ነውና 🌼 በቅዱስ ማቴዎስ ወንጌል ላይ "እውነት እላችኋለሁ፤ ሴቶች ከወለዱአቸው ወገን ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም" ማቴ.፲፩፥፲፩ ብሎ ጌታችን ስለ ዮሐንስ በተነገረለት መሠረት የጻድቃን የሰማዕታት ርእስ እንደመሆኑ አዲስ ዓመትም የበዓላት ሁሉ በኩር ርእስ ነውና በስሙ ተጠርቷል፡፡ እንደዚሁም ጌታ ባረገ በ180 ዘመን በእስክንድርያ 12ኛ ሊቀ ጳጳሳት ሁኖ የተሾመው ቅዱስ ድሜጥሮስ  ባሕረ ሐሳብን ሲደርስ ከዮሐንስ ጀምሮ ደርሶታል፤ ሲጨርስም ለኢየሩሳሌም፣ ለሮም፣ ለኤፌሶንና ለአንጾኪያ ሊቃነ ጳጳሳት ልኳል፡፡ 🌼 በእስክንድርያ (ግብጽ) በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በዓላት የሚከበሩትና አጽዋማት የሚገቡት ከመስከረም አንድ ተነስቶ በመቁጠር ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የበዓላቱና የአጽዋማቱ መደብ የሚታወቅበትና የዘመናቱ ሂደት ተቀምሮ የሚታወጅበት መስከረም አንድ በመሆኑ ርእሰ ዐውደ ዓመት ይባላል፡፡ ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድም የዘመን መለወጫን አዲስ ዓመት በዓል አስመልክቶ እንደነገረን "ርእሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ ወላዴ መጥቅዕ ወአበቅቴ" ፤ የዓመት በዓል ራስ ዮሐንስ መጥቅዕና አበቅቴን የምትወልድ ነህ" እየተባለ ይዘመርለታል፡፡ ምንጭ፦ ማኅበረ ቅዱሳን በዲያቆን ዘክርስቶስ ፀጋዬ።                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዚህ_ሳምንት_የዕለቱ_ምስባክ፦ "ሣህል ወርትዕ ተራከባ። ጽድቅ ወሰላም ተሰዐማ። ርትዕሰ እምድር ሠረፀት"። መዝ 84፥10-11። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 11፥17-ፍ.ም፣ ያዕ 2፥17 እና የሐዋ ሥራ 18፥24-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 1፥15-38። የሚቀደሰው የቅዱስ አትናቴዎስ ቅዳሴ ነው። መልካም የዓመቱ መጀመሪያ ዕለተ ሰንበት ለሁላችንም ይሁንልን።

🌼 ያን ጊዜም ሳሙኤል መጣ ንጉሥ ኢጋቦም በበረሃ ውስጥ ወደአነፃት ቤተ ክርስታያን ወሰደው እርሷም ገዳማውያን የሚሰበሰቡባት ተሰውራ የምትትኖር ናት ወደርሷም በደረሱ ጊዜ ቅዱሳን ተሰብስበው መሥዋዕትን ሲያሳርጉ አገኙና በአንድነት ሥጋውንና ደሙን ተቀበሉ ሰንብትም ከሆን በኋላ ከቅዱሳን መቃብር በረከትን ሊቀበሉ ከአባ ሳሙኤል ጋራ አብረው ሔዱ ከዚያም ደርሶ አባ ሙሴ ሰገደ ወዲያውም ዐረፈ አባ ሳሙኤልም ቀበረው ገድሉንም ጻፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ሙሴ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 2 ስንክሳር።                          ✝️ ✝️ ✝️ 🌼 "#ሰላም_ለሙሴ_ዘረሰየ እምዓለም ተፈልጦ። ቈጽለ ሆሣዕና አራዘ ወፍሬ ዘይቶን ሥብጦ። በብዙኅ መከራ አምድኅረ ሰይጣን አስፈጦ። #እግዚአብሔር መሐሪ መንገደ ገዳም ሜጦ። ኀበ ሥጋሁ የዓርፍ ወነፍሶ ይትሜጦ። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_3።

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼           🌼  #መስከረም ፫ (3) ቀን። 🌼 እንኳን #ለገዳመ_ሲሐቱ_ለአባ_ሙሴ ለዕረፍት በዓል፣ የከበረ አባት #ሊቀ_ጳጳሳት_አባ+ዲዮናስዮስ ከተሾመ በሁለተኛው ዓመት በእስክንድርያ ከተማ ነፍስ ከሥጋዋ ጋር ትሞታለች በዕለተ ትንሣኤም ከሥጋዋ ጋር አብራ ትነሣለች ስለሚሉ ክፉዎች #የኤጲስቆጶሳት_የአንድነት_ጉባዔ ለተደረገበት ቀን በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከሰማዕት_ከአባ_ዲዮስቆሮስ፣ ሰማዕት ከሆነ ከሊቀ ጳጳሳት #አባ_ዲዮናስዮስ፣ #ከዲያቆን_በትንከል፣ ከብዙዎች የፋርስ ሰማዕታት ከዕረፍታቸው መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                          ✝️ ✝️ ✝️ 🌼 በዚች ቀን የከበረ አባት ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ዲዮናስዮስ ከተሾመ በሁለተኛው ዓመት በእስክንድርያ ከተማ የኤጲስቆጶሳት የአንድነት ጉባዔ ተደረገ። 🌼 ይህም ጉባዔ የሆነው ነፍስ ከሥጋዋ ጋር ትሞታለች በዕለተ ትንሣኤም ከሥጋዋ ጋር አብራ ትነሣለች ስለሚሉ ክፉዎች በዐረቢያ አገር ስለ ተነሡ ሰዎች ነው። እነርሱም ለከፋችና ብልሹ ለሆነች ሃይማኖታቸው የፈጠራ ድርሰትን ደርሰው በእስክንድርያ ከተማ ወደሚኖሩ ሰዎች ላኩ። 🌼 አባታችን ሊቀ ጳጳሳት አባ ዲዮስናስዮስም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ ከዚህ ከክፉ ሥራም እንዲመለሱ አስተማራቸው ገሠጻቸውም እነርሱ ግን አልሰሙትም አልተመለሱም። ስለዚህም በእነርሱ ላይ ይህን ጉባዔ ሰብሰቦ ተከራከራቸው ስሕተታቸውንም ገልጾ አስረዳቸው እነርሱ ግን ሰይጣን አሳውሮአቸዋልና ተጸጽተው አልተመለሱም ይህም ጉባኤ ረግሞ ከቤተ ክርስቲያን አንድነት ለይቶ አሳደዳቸው። 🌼 ይህም አባት ዲዮናስዮስ ስለርሳቸው ድርሳናትን ደረሰ በውስጣቸውም እንዲህ የሚል "በዚህ በቸርነቱ ስጦታ ውስጥ የእግዚአብሔር ፍቅር የጎላ የተረዳ ሆነ ነፍስ ረቂቅ ስለሆነች እንደ መላእክት በሕይወት እንድትኖር እንጂ እንዳትሞት እንዳትጠፋ ማድረጉ ነው። 🌼 ከሥጋዋም በምትወጣ ጊዜ ስለ በጎ ሥራዋ እንደሚገባት መጠን ወደ ሕይወት ቦታዋ ይወስዷታል ወይም እንደ ሥራዋ ክፉነት ወደ ሥቃይ ይወስዷታል። በትንሣኤ ቀንም ንቃሕ መዋቲ ተብሎ ዓዋጅ ሲነገር በፈጣሪያቸው ትእዛዝ የሙታን በድኖች ሲነሡ ነፍሳት እንዲህ ይሆናሉ እያንዳንዲቱ ነፍስ ከሥጋዋ ተዋሕዳ አብራ ትነሣለች"። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን አባቶቻችን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ትድረሰን ለዘላለሙ አሜን።                           ✝️ ✝️ ✝️ 🌼 #የገዳመ_ሲሐት_አባ_ሙሴ፦ ይህም ቅዱስ ከመነኰሰ ጀምሮ ዓለምን ትቶ ከበረሀ ገብቶ በጾም በጸሎት በመጠመድ ተጋደለ። እግዚአብሔር ዘይቶንና የተምር አትክልት ያለባትን የአትክልት ቦታ በማየት ልቡን ብሩህ እስከ አደረገለት ድረስ በወሩ መባቻም ከዘንባባ ዕንጨትና ከዘይቶን የወደቀውን ፍሬ ወስዶ ይበላል። ምግቡም ታናሽ ወፍ በሚመገበው መጠን ልክ ነው ልብሱም ከዘንባባ ቅጠል የተሠራ ሰሌን ነው። ስለዚህ ለሚያስጨንቅ ለክረምት ቅዝቃዜና ለበጋ ቃጠሎ የተጋለጠ ከዚህም ጋር በጾምና በጸሎት የተጠመደ ነው ። 🌼 ነገር ግን መጻሕፍትን የሚያውቅ አይደለም የዱር አራዊትም በየወገናቸው ወደርሱ ይመጡ ነበር እርሱም ያረጋጋቸዋል። የጸሎት ጊዜም ሲደርስ በእጁ ሲጠቅሳቸው ይሔዳሉ። ድርቅ የሆነ እንደሆነም ሊያነጋግሩት እንደሚሹ ሁነው መጥተው በፊቱ ይቆማሉ እርሱም የሚሹትን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ በጸሎቱ ዝናብን ያወርድላቸዋል። እንዲሁም እያደረገ ከእርሳቸው ጋር አርባ አምስት ዓመት ኖረ ። 🌼 ሰይጣንም ቀናበት ዘመኑ በአለፈና እጅግ በአረጀ ሽማግሌ አምሳል በጥቂት በጥቂት ሲያዘግም ከበዓቱ ውስጥ ሁኖ አየው ለዚህ ቅዱስ አባ ሙሴም ገዳማዊ መናኒ መስሎት ወደርሱ ሒዶ አምጥቶ ወደ በዓቱ አስገባው አራዊት ግን በሽማግሌ የተመሰለውን ሰይጣን በአዩት ጊዜ ከእርሱ ሸሹ። 🌼 ከዚህ በኋላ አባ ሙሴን አገሩንና ሃይማኖቱን ጠየቀው እርሱም ሁሉን ነገረው ደግሞ አባ ሙሴ ኑሮው እንዴት እንደሆነ ሽማግሌውን ጠየቀው ። በሽማግሌ የተመለሰ ሰይጣንም እንዲህ ብሎ መለሰለት "እኔ በዓለም ኃጢአት በመሥራት ብዙ ዘመናት ኖርኩ አንዲት ሴት ልጅንም ወለድኩ ። ከዚያም የዓለምን ኃላፊነትና ጠፊነት አሰብኩ ከዓለምም ወጥቼ በበረሀ ውስጥ አርባ ዓመት ኖርኩ። ልጄን ያገባት እንደሌለ በአሰብኩ ጊዜ በዚህ ነገር ምክንያት ወዳንተ መጣሁ ከአንተ በቀር የሚያገባት የለምና በሞትኩም ጊዜ የምትቀብረኝ አንተ ነህ ብዙ ስፍራዎችና የአታክልት ቦታዎችም ስላሉኝ ሁሉንም እንተ ትወርሳለህ"። 🌼 አባ ሙሴም ሰምቶ ደነገጠ "እኔ መነኲሴ ስሆን ይህን እንዴት አደርጋለሁ" አለ የተመረጡ ጻድቃን ሲሆኑ ሚስቶች የነበሩአቸው አብርሃምን ሙሴን ዳዊትን ከብሉያት መጻሕፍት ምስክር ማስረጃ አድርጎ አመጣለት በዚህም ወደ ተንኰሉ ልቡን አዘነበለው። በውስጡ ያጌጠች ሴት ልጅ ያለችበትን የተሸለመ አዳራሽ አሳየውና ከዚያም በኋላ እንደሞተ ሆነ አባ ሙሴም አይቶ በለዩ አለቀሰ ገንዞም ቀበረው። 🌼 ልጅቷ ወዳለችበት ለመግባት በፈለገ ጊዜ ጥቅል ነፋስ ነፍሶ የኋሊት ጣለው ከዚህ በኋላ ልቡ ሲመለስለት አዳራሹንም ልጅቷንም የአትክልት ቦታዎችንም አጣ ፈጽሞ እያደነቀ ወደ ማደሪያው ተመለሰ ከዕንጨቱም ፍሬ ምግቡን ሊመገብ ፈለገ በአፉም ውስጥ መራራ ሆነበት በረኃብም ስለ ተጨነቀ ወደ ዱር ወጥቶ ሔደ። 🌼 ከዚህም በኋላ በአህያው ላይ ተቀምጦ ወደ እስክንድርያ በሚሔድ በሽማግሌ ነጋዴ አምሳል ሰይጣን ተገናኝው መብልና መጠጥም ይዞ ነበር አባ ሙሴንም ከርሱ ጋር ወሰደው ወዳንድ አገርም አድርሶ በዚያ ተወው ። 🌼 ዳግመኛም በገዳማዊት በመናኒነት በምትኖር አምሳል ሰይጣን ታየው እርሷም ውኃ የምትቀዳ መስላ ነው ሥራውን ጠየቀችው ሰይጣን እንደ ፈተነው ሁሉን ነገራት በልቧም ሳቀችበት ወደ ቤቷም ወስዳው አብልታ አጠጥታ ከዚያ በኋላ የጋብቻን ነገር አሳሰበችው ብዙ ገንዘብም እንዳላት እርሷም የሟች ንጉሥ እንደሆነት ነገረችው። ልቡም እንደአዘነበለ አይታ "እኔ አይሁዳዊት ነኝ እኛም ብዙዎች ነን" ሃይማኖቱንም እስከካደ ድረስ በብዙ ተንኰል ተስፍ አስደረገችው ። 🌼 ዳግመኛም እንዲህ አለችው "ና ወደ በረሀ እንውጣና ያኖርኩትን ገንዘብ እንውሰድ" ብላ ውኃ ወደሌለበት በረሀ ወሰደችው ከተራራ በላይም ወጥታ ተለወጠችበት እንዲህም አለችው "እኔ ብዙዎችን ያሳትኩ ሰይጣን አንተነንም ከገዳምህ አስመጣሁህ ሃይማኖትህንም አስካድኩህ እነሆ በዚህ በረሀም ሙተህ ነፍስህ ወደገሃነም ትወርዳለች" ይህንንም ብሎ ሰይጣን ከርሱ ተሠወረ። በተመለሰም ጊዜ በቀኝም በግራም መንገድ አጣ የሚጠጣውም ውኃን አላገኘም ምድር ጠበበችው በምድር ላይም ወድቆ በፊቱ ውስጥም አፈርን በተነ ነፍሱም ከሥጋው ለመለየት እስከደረሰች ደረስ ተንከባለለ ጭኸ መሐሪና ይቅር ባይ ሰውን የሚወድ እግዚአብሔር ራራለት ያጽናናው ዘንድ መልአኩን ላከለት እርሱም "ኃጢአትህ ተሠረየልህ እስከ ሰባት ቀንም ታርፍለህ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሳሙኤልም ይቀብርሃል" ብሎ አጽናናው ሰላምታም ሰጥቶት ዐረገ ።

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼             🌼 #መስከረም ፫ (3) ቀን። 🌼 እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ ታላቁ የሥውራ ቅዱሳን መኖርያ የሆነው ገዳም #ደብረ_ሐዘሎው ለመሰረቱ፤ አንበሳ እንደ ፈረስ ያገለግላቸው ለነበሩ #ለታላቁ_አባት_ለአቡነ_አንበስ ለዕረፍት በዓል በሰላም አደረሰን።                          ✝️ ✝️ ✝️ 🌼 #አባ_አንበስ፦ እኚህ አባት ከቅድስናቸው የተነሣ ከቦታ ቦታ የሚንቀሳቀሱት በአንበሳ ላይ ተጭኖ ነው፡፡ ተአምራትን በማድረግና ወንጌልን በማስተማር በጾም ጸሎት አብዝቶ የደከመ ሲሆን ስለ ሀገራችን ኢትዮጵያ ሌት ተቀን በጸሎት ይተጉ የነበረ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ አቡነ አንበስ ትውልዳቸው ትግራይ አድዋ በእንጭጮ ወረዳ ነው፡፡ በስማቸው ትግራይ አድዋ "እንጭጮ አቡነ አንበስ ገዳም" እና በትግራይ ሽሬ ሁለት ትላልቅ ገዳማት አሏቸው፡፡ ቅዱስ ያሬድ በድርሰቱ ደጋግሞ የጠቀሳቸው ሲሆን የያሬድንም የድርሰቱን የአቋቋም ሥርዓት ያመጡት አቡነ አንበስ ናቸው፡፡ 🌼 አቡነ አንበስ በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና በአቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ ጊዜ የነበሩ ሲሆን እሳቸውንም አንበሶች ያገለግሏቸው ነበር፡፡ ጻድቁ አቡነ አንበስ ከአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጋር የተገናኘ ትልቅ ታሪክ አላቸው፡፡ የላዕላይ ግብጹ አባ ብንያም፣ በአቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ እና የሐዘሎው አቡነ አንበስ እነዚህ 3ቱ ቅዱሳን ከየአሉበት በአንበሳቸው ተጭነው ምድረ ከብድ አቡዬ ዘንድ እንደደረሱ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንበሶች የ3ቱንም ቅዱሳን አንበሶች ዋጡዋቸው፣ አቡዬም በዚህ አዝነው ከበዓታቸው ወጥተው አንበሶቻቸውን "ትፉ" ብለው የበሉአቸውን አንበሶቻቸውን አስተፍተዋቸው ለ3ቱም ቅዱሳን የተበሉባቸውን አንበሶቻቸውን መልሰውላቸዋል፡፡ 🌼 ይኸውም የሆነው እኝዲህ ነው፡- አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በዝቋላ 7ቱ ሊቃነ መላእክት እየረዷቸው 70 ሺህ እልፍ አጋንንትን በእሳት ሰይፍ ፈጅተው ካጠፏቸው በኋላ ወደ ምድረ ከብድ ተመለሱ፡፡ ከዚህም በኋላ መንፈስ ቅዱስ የጠራቸው ሦስቱ ቅዱሳን አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ አቡነ አንበስ ዘሐዘሎ እና የላዕላይ ግብጹ አቡነ ብንያም በአንበሶቻቸው ሆነው ወደ ጻድቁ አባት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ዘንድ ምድረ ከብድ ገዳም መጡ፡፡ አባታችን ግን ስለተሰወራቸው እስከ 7 ቀን ድረስ በምህላ ሰነበቱ፡፡ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንበሶችም መጥተው የ3ቱን ቅዱሳን አንበሶች በልተውባቸው ተሰወሩ፡፡ 3ቱም ቅዱሳን ፈጽመው ደነገጡ፡፡ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስም የቅዱሳኑን ሀዘንና ድንጋጤ ተመልክተው በታላቅና በሚያስፈራ ግርማ ሆነው ስልሳ ነብሮችንና ስልሳ አንበሶችን አስከትለው ተገለጡላቸው፡፡ ቅዱሳኑም ከአቡነ ገብረ መንፈስቅዱስ ግርማ የተነሣ ስለደነገጡ እንዳይፈሩም አረጋጉአቸው፡፡ 🌼 ከዚህም በኃላ አባታችን "በምን ምክንያት ወደዚህ ገዳም ወደ እኔ መጣችሁ?" አሏቸው፡፡ ሦስቱ ቅዱሳን እንዲህ አሉ፡- "ጸሎትህ ቅድስት እንደሆነች ባወቅን ጊዜ ወደ አንተ መጣን፤ አንተ በሁሉ ርእሰ ባሕታውያን ነህና የእግዚአብሔርን ሥራ ትነግረን ዘንድ መጣን፤ ባላገኘንህም ጊዜ እስከ 7ቀን አለቀስን" አሉት፡፡ 🌼 ዳግመኛም "አንበሶችህ መጥተው አንበሶቻችንን ደማቸውን ጠጡ ቆዳቸውንም በጥፍራቸው በጣጠሱ" ብለው ነገሯቸው፡፡ አባታችንም ይህንን ሲሰሙ አንበሶቻቸውን "እስከ ዕለቴ ሞቴ ድረስ በእግሬ ከረገጥኩት ትቢያ በቀር ምንም እንዳትበሉ ታዛችሁ የለምን? እግዚአብሔር ያላዘዛችሁትን ለምን በላችሁ? በሉ አሁንም የበላችሁትን ትፉ" አላቸው፡፡ እነዚያም አንበሶች አፋቸውን ከፍተው አንዳች ሳያስቀሩ አጥንታቸውን ሥጋቸውን በሙሉ ተፉአቸው፡፡ ጻዲቁ አባታችንም ወደ ምሥራቅ ተመልሰው እግዚአብሔርን ከለመኑ በኋላ በአንበሶቹ ሥጋ ላይ ባረኩና "በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ተነሡ" አሏቸው፡፡ አንበሶቹም እንደ ዐይን ፈጥነው ተነሥተው እንደ ቀድሞው ሆኑ፡፡ ከአባታችን ከአቡነ አንበስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸውም ይማረን። ምንጭ፦ ከገድላት አንደበት።

²⁴ ወጥታም ለእናትዋ፦ ምን ልለምነው? አለች። እርስዋም፦ የመጥምቁን የዮሐንስን ራስ አለች። ²⁵ ወዲያውም ፈጥና ወደ ንጉሡ ገብታ፦ የመጥምቁን የዮሐንስን ራስ በወጭት አሁን ልትሰጠኝ እወዳለሁ ብላ ለመነችው። ²⁶ ንጉሡም እጅግ አዝኖ ስለ መሐላው ከእርሱም ጋር ስለ ተቀመጡት ሊነሣት አልወደደም። ²⁷ ወዲያውም ንጉሡ ባለ ወግ ልኮ ራሱን እንዲያመጣ አዘዘው። ሄዶም በወኅኒ ራሱን ቈረጠ፥ ²⁸ ራሱንም በወጭት አምጥቶ ለብላቴናይቱ ሰጣት፥ ብላቴናይቱም ለእናትዋ ሰጠች። ²⁹ ደቀ መዛሙርቱም ሰምተው መጡ በድኑንም ወስደው ቀበሩት።

🌿🌿🌿🌿 የዕለቱን ወንጌል እናንብብ! 🌿🌿🌿🌿 ዕለተ ቀዳሚት ሰንበት (ምትረተ ርእሱ ለቅዱስ ዮሐንስ ነቢይ ወመጥምቀ መለኮት)! መስከረም 2 ቀን 2019 ዓ.ም የማርቆስ ወንጌል ም 6 ቁ 1
+1
🌿🌿🌿🌿  የዕለቱን ወንጌል እናንብብ! 🌿🌿🌿🌿          ዕለተ ቀዳሚት ሰንበት (ምትረተ ርእሱ ለቅዱስ ዮሐንስ ነቢይ ወመጥምቀ መለኮት)! መስከረም 2 ቀን  2019 ዓ.ም          የማርቆስ ወንጌል ም 6 ቁ 14 - 30 —————————————————————————— ¹⁴ ስሙም ተገልጦአልና ንጉሡ ሄሮድስ በሰማ ጊዜ፦ መጥምቁ ዮሐንስ ከሙታን ተነሥቶአል ስለዚህም ኃይል በእርሱ ይደረጋል አለ። ¹⁵ ሌሎችም፦ ኤልያስ ነው አሉ፤ ሌሎችም፦ ከነቢያት እንደ አንዱ ነቢይ ነው አሉ። ¹⁶ ሄሮድስ ግን ሰምቶ፦ እኔ ራሱን ያስቈረጥሁት ዮሐንስ ይህ ነው እርሱ ከሙታን ተነሥቶአል አለ። ¹⁷ ሄሮድስ የወንድሙን የፊልጶስን ሚስት ሄሮድያዳን አግብቶ ነበርና በእርስዋ ምክንያት ራሱ ልኮ ዮሐንስን አስይዞ በወኅኒ አሳስሮት ነበር፤ ¹⁸ ዮሐንስ ሄሮድስን፦ የወንድምህ ሚስት ለአንተ ልትሆን አልተፈቀደም ይለው ነበርና። ¹⁹ ሄሮድያዳ ግን ተቃውማው ልትገድለው ትፈልግ ነበር አልቻለችም፤ ²⁰ ሄሮድስ ዮሐንስ ጻድቅና ቅዱስ ሰው እንደ ሆነ አውቆ ይፈራውና ይጠባበቀው ነበር፤ እርሱንም ሰምቶ በብዙ ነገር ያመነታ ነበር፤ ²¹ በደስታም ይሰማው ነበር። ሄሮድስም በተወለደበት ቀን ለመኳንንቱና ለሻለቆቹ ለገሊላም ሹማምንት ግብር ባደረገ ጊዜ ምቹ ቀን ሆነላትና ²² የሄሮድያዳ ልጅ ገብታ ስትዘፍን ሄሮድስንና ከእርሱ ጋር የተቀመጡትን ደስ አሰኘቻቸው። ንጉሡም ብላቴናይቱን፦ የምትወጂውን ሁሉ ለምኚኝ እሰጥሽማለሁ አላት፤ ²³ የመንግሥቴ እኩሌታ ስንኳ ቢሆን የምትለምኚውን ሁሉ እሰጥሻለሁ ብሎ ማለላት።

🌼 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼             🌼 #መስከረም ፪ (2) ቀን። 🌼 እንኳን #ለታላቁ_ነቢይ_ሰማዕት_ሐዋርያ_ካህን #ለመጥምቀ_መለኮት_ለሰማዕቱ_ለቅዱስ_ዮሐንስ ሕግ አፍራሽ በሆነ በንጉሥ ሄሮድስ እጅ አንገቱን በመሰየፍ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል በሰላም አደረሰን። በዚች ቀን በጨማሪ ከሚታሰቡ፦ በግብጽ ውስጥ ታዕዳ ከሚባል አገር በሰማዕትነት ከዐረፈ #ከቅዱስ_ዳስያ፣ #ከሰማዕት_ዲዲሞስና #ቅድስት_መሪና ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                        ✝ ✝ ✝ 🌼 #የታላቁ_ነቢይ_ሰማዕት_ሐዋርያ_ካህን፣ #የመጥምቀ_መለኮት_የቅዱስ_ዮሐንስ_ሰማዕትነት፦ ይህም እንዲህ ነው ፊሊጶስ ሚስት በሄሮድያዳ ምክንያት ነቢዩ ቅዱስ ዮሐንስ በገሠጸው ጊዜ ፊሊጶስ ወንድሙ ስለሆነ ቅዱስ ዮሐንስም የወንድህን ሚስት ልታገባ አይገባህም ይለው ነበርና። 🌼 ቅዱስ ዮሐንስም ሄሮድስን የወንድሙን የፊልጶስን ሚስት ሄሮድያዳን ስለማግባቱና ሌላም ያደርገው ስለነበረ ክፉ ሥራ ሁሉ ይገሥጸው ነበር። ደግሞም በተግሣጽ ላይ ተግሣጽን ጨመረ። ስለዚህም ቅዱስ ዮሐንስን ተቀየመውና በግዞት ቤት አኖረው። 🌼 ሄሮድስም ቅዱስ ዮሐንስን ይፈራው ነበር ጻድቅ ቅዱስ ሰው እንደሆነ ያውቅ ነበርና ብዙ ይጠባበቀውም ነበር። ሄሮድስ የተወለደባትን ቀን በዓል የሚያከብርባት ዕለት ነበረች መኳንንቱን አለቆቹን መሣፍንቱን ሹሞቹን በገሊላ አገር ያሉትን ታላላቅ ሰዎች ግብር አገባ። 🌼 የሄሮድያዳ ልጅም ወደ አዳራሹ ገብታ ዘፈነች ሄሮድስንም ደስ አሰኘችው ከእርሱ ጋር በማዕድ የነበሩትንም ንጉሡም ያቺን ብላቴና "የምትሺውን ለምኚኝ እሰጥሻለሁ" አላት። እስከ መንግሥቱ እኩሌታ ድረስም ቢሆን የለመነችውን ሊሰጣት ማለላት። ወጥታም እናቷን "ምን ልለምነው" አለቻት እናቷም "የመጥምቁ ዮሐንስን ራስ" አለቻት። 🌼 ያን ጊዜም እየሮጠች ወደ ንጉሡ ገብታ "የመጥምቁ ዮሐንስን ራስ በውጭት አሁን እንድትሰጠኝ እሻለሁ" ብላ ለመነችው። ንጉሡም ስለ መሐላው አብረውት ስለ ነበሩትም ሰዎች አዘነ እምቢ ሊላት ግን አልወደደም። 🌼 ያን ጊዜም ባለወጎችን ላከ በእሥር ቤትም ሳለ የቅዱስ ዮሐንስን ራስ ቆረጡ ራሱንም በወጭት አምጥተው ለዚያች ብላቴና ሰጡአት እርሷም ወስዳ ለእናቷ ሰጠች። 🌼 በዚያችም ቀን የቅዱስ ዮሐንስ ራስ ከሄሮድያዳ ከእጆቿ ላይ ወደ አየር ስለ በረች ታላቅ ድንጋፄ ሆነ። "ደግሞም ሄሮድስ ሆይ የወንድምህን ሚስት ልታገባ አይገባህም" እያለች በመጮኸ ዘልፋዋለችና። 🌼 ደቀ መዛሙርቱም በሰሙ ጊዜ መጥተው በድኑን ወስደው ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበረ በአጥማቂው ቅዱስ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                            ✝ ✝ ✝                           🌼 #ቅዱስ_ዳስያ፦ ይህም ቅዱስ በግብጽ ውስጥ ታዕዳ ከሚባል አገር ነው። ቅዱስንም የእንዴናው አገረ ገዥ አርያኖስ አሠቃየው ጽኑ ሥቃይንም ከአሠቃየው በኋላ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ። የቅዱስ ዳስያ በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 2 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወእመኒ ነሣእኩ ክንፈ ከመ ንስር። ወሠረርኩ እስከ ማኅለቅተ ባሕር። ህየኒ እዴከ ትመርሀኒ ወታነብረኒ የማንከ"። መዝ 138፥9። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 14፥1-13።                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወይርአዩ አሕዛብ በቅድመ አዕይንቲነ። በቀለ ደሞሙ ለአግብርቲከ ዘተክዕወ። ይባዕ ቅድሜከ ገዐሮሙ ለሙቁሓን"። መዝ78፥10-11። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 6፥1-11፣ 1ኛ ዮሐ 3፥10-16 እና የሐዋ ሥራ 13፥24-28። የሚነበበው ወንጌል ማር 6፥14-29። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቅዳሴ ነው። መልካም የመጥምቀ መለኮት የቅዱስ ዮሐንስ የዕረፍት በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።

¹¹ እውነት እላችኋለሁ፥ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ አልተነሣም፤ በመንግሥተ ሰማያት ግን ከሁሉ የሚያንሰው ይበልጠዋል። ¹² ከመጥምቁም ከዮሐንስ ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ መንግሥተ ሰማያት ትገፋለች፥ ግፈኞችም ይናጠቋታል። ¹³ ነቢያት ሁሉና ሕጉ እስከ ዮሐንስ ድረስ ትንቢት ተናገሩ፤ ¹⁴ ልትቀበሉትስ ብትወዱ፥ ይመጣ ዘንድ ያለው ኤልያስ ይህ ነው። ¹⁵ የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ። ¹⁶ ነገር ግን ይህን ትውልድ በምን እመስለዋለሁ? በገበያ የሚቀመጡትን ልጆች ይመስላሉ፥ እነርሱም ባልንጀሮቻቸውን እየጠሩ። ¹⁷ እንቢልታ ነፋንላችሁ ዘፈንም አልዘፈናችሁም ሙሾ አወጣንላችሁ ዋይ ዋይም አላላችሁም ይሉአቸዋል። ¹⁸ ዮሐንስ ሳይበላና ሳይጠጣ መጣ፥ እነርሱም፦ ጋኔን አለበት አሉት። ¹⁹ የሰው ልጅ እየበላና እየጠጣ መጣ፥ እነርሱም፦ እነሆ፥ በላተኛና የወይን ጠጅ ጠጭ፥ የቀራጮችና የኃጢአተኞች ወዳጅ ይሉታል። ጥበብም በልጆችዋ ጸደቀች።

🌿🌿🌿🌿 የዕለቱን ወንጌል እናንብብ! 🌿🌿🌿🌿 ዕለተ አርብ (አውደዓመት)! መስከረም 1 ቀን 2019 ዓ.ም የማቴዎስ ወንጌል ም 11 ቁ 1 - 20 ——————————————————————————
🌿🌿🌿🌿  የዕለቱን ወንጌል እናንብብ! 🌿🌿🌿🌿          ዕለተ አርብ (አውደዓመት)! መስከረም 1 ቀን  2019 ዓ.ም          የማቴዎስ ወንጌል ም 11 ቁ 1 - 20 —————————————————————————— ¹ ኢየሱስም አሥራ ሁለቱን ደቀ መዛሙርቱን ማዘዝ በፈጸመ ጊዜ በከተሞቻቸው ሊያስተምርና ሊሰብክ ከዚያ አለፈ። ² ዮሐንስም በወህኒ ሳለ የክርስቶስን ሥራ ሰምቶ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለት ላከና፦ ³ የሚመጣው አንተ ነህን? ወይስ ሌላ እንጠብቅ? አለው። ⁴ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላቸው፦ ሄዳችሁ ያያችሁትን የሰማችሁትንም ለዮሐንስ አውሩለት፤ ⁵ ዕውሮች ያያሉ አንካሶችም ይሄዳሉ፥ ለምጻሞችም ይነጻሉ ደንቆሮችም ይሰማሉ፥ ሙታንም ይነሣሉ ⁶ ለድሆችም ወንጌል ይሰበካል፤ በእኔም የማይሰናከለው ሁሉ ብፁዕ ነው። ⁷ እነዚያም ሲሄዱ ኢየሱስ ለሕዝቡ ስለ ዮሐንስ ሊናገር ጀመረ እንዲህም አለ፦ ምን ልታዩ ወደ ምድረ በዳ ወጣችሁ? ⁸ ነፋስ የሚወዘውዘውን ሸምበቆን? ወይስ ምን ልታዩ ወጣችሁ? ቀጭን ልብስ የለበሰ ሰውን? እነሆ፥ ቀጭን ልብስ የለበሱ በነገሥታት ቤት አሉ። ⁹ ወይስ ምን ልታዩ ወጣችሁ? ነቢይን? አዎን እላችኋለሁ፥ ከነቢይም የሚበልጠውን። ¹⁰ እነሆ፥ መንገድህን በፊትህ የሚጠርግ መልክተኛዬን በፊትህ እልካለሁ ተብሎ የተጻፈለት ይህ ነውና።