ch
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

前往频道在 Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

显示更多
638
订阅者
-224 小时
-57
-1130
帖子存档
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #ሰኔ ፳፩ (21) ቀን። ❤ እንኳን #ለአዳም_ለዘር_ሁሉ_ድኅነት ለተደረገባት #አምላክን_ለወለደች_ለእመቤታችን_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም በስሟ የተሠራችው የመጀመርያ #ቤተ_ክርስቲያን_በልጇ_በወዳጇ_እጅ #ለተቀደሰችበት_ለከበረችበት_ዓመታዊ_በዐሏና በዓለም ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን መታነጽ መታሰቢያ ታላቅ በዐል፣ እመቤታችን በጌታችን መቃብር በጎልጎታ ለሰው ልጆች በሙሉ ምሕረት ለጸለየችበት፣ #እመቤታችን_ለቅዱስ_ባስልዮስ_ዘቂሣርያ ለተገለጠችለትና ሥዕሏን እንዲያሠራላት ለነገረችውና ድንቅ ድንቅ ተአምራትን ላደረገች፣ ለሐዋርያው #ቅዱስ_ቶማስ በመሸታ ቤት ባረድዋት በአንዲት ሴት ላይ ላደረገው ተአምር መታሰቢያ በዐል፣ ለምስር አገር ለሆነ #ለቅዱስ_ጢሞቴዎስ_ሰማዕትነት_ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓልና #ለእስክድርያ_አራተኛ_ሊቀ_ጳጳስ #ለአባ_ከላድያኖስ_ለዕረፍት_በዐል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ሜሮን_ከተገኘችበትና_የአስታፍን_ዐፅም ከተገኘችበት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                  ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #በዚች_ዕለት_የአዳምና_የዘሩ_ድኅነት የተደረገባት #አምላክን_የወለደች_የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የታላቁ በዓል መታሰቢያና በዓለም ሁሉ የቤተ ክርስቲያን መታነፅ መታሰቢያ ነው። ከሁሉ አስቀድሞ ያቺ ቤተ ክርስቲያን በሐዋርያት ዘመን ብቻዋን ታነፀች። ❤ ይኸውም ቅዱሳን ጳውሎስና በርናባስ በአሕዛብ ውስጥ በሰበኩ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ከሰዎች ቤቶች በቀር ቅዱስ ቊርባንን የሚቀበሉበት ቤተ ክርስቲያንም አልነበራቸውም ነበር። ስለዚህም ወደ ቅዱሳን ጴጥሮስና ወደ ሐዋርያት ሁሉ ስለ ቤተ ክርስቲያን መታነፅ ጉዳይ እየለመኑ መልእክትን ላኩ። ሐዋርያትም እንዲ ብለው መለሱላቸው "ክብር ይግባውና ያለ ጌታችን ፈቃድ እኛ ምንም ምን አንሠራም። ነገር ግን የምንሠራውን እስኪያስረዳን ድረስ ወደ እግዚአብሔር እየጸለዩና እየማለዱ አንድ ሱባኤ ይጾሙ ዘንድ ወደ ሃይማኖት የተመለሱ አሕዛብን እዘዙአቸው" እንዲህም አዘዙአቸው። ❤ በሱባኤውም ፍጻሜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾላቸው ሐዋርያትም ሁሉ ከየአገሮች ሁሉ እስከ ፊልጵስዩስ በደመና ሰበሰባቸው ከእርሳቸውም ጋር ቅዱሳን ጳውሎስና በርባስ ነበሩ ጌታችንም ባረካቸው እንዲህም ብሎ ነገራቸው "ይቺ ዕለት በእናቴ በማርያም ስም በአራቱ ማእዘነ ዓለም አብያተ ክርስቲናት እንዲታነፁ የፈቀድኩባት ናት"። ይህንንም ብሎ በከተማዋ በስተ ምሥራቅ በኵል አወጣቸው የቤተ ክርስቲያኒቱም ቦታና መሠረቷን ወሰነላቸው ከእርሳቸውም ጋራ የእግዚአብሔር ኃይል ነበረ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕንፃዋ እስከ ተፈጸመ ድረስ ሦስቱ ደንጊያዎች በሐዋርያት እጆች ውስጥ ይለመልሙ ነበር ጌታችንም ንዋየ ቅዱሳቷን አልባሳትዋንና መሠዊያዋን አዘጋጀ። ❤ ከዚህም በኋላ ጌታችን እጁን በቅዱስ ጴጥሮስ ራስ ላይ ጭኖ በአራቱ ማዕዘነ ዓለም ውስጥ "አርሳይሮስ" ብሎ ሾመው ይህም ሊቀ ጳጳሳት ማለት ነው "ለሐዋርያት አለቃ ለቅዱስ ጴጥሮስ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የጳጳሳት አለቃ ይሆን ዘንድ ይገባዋል ይገባዋል ይገባዋል" እያሉ ሰማያውያን መላእክትና ምድራውያን ሰዎች ሦስት ጊዜ አሰምተው ተናገሩ። ❤ ከዚህም በኋላ ጌታችን ሐዋርያትን የቊርባኑን ቅዳሴ ሥርዓት ያከናውኑ ዘንድ ለሕዝቡም ሥጋውን ደሙን ያቀብሏቸው ዘንድ አዘዛቸው እንዲህም የሚል አለ ራሱ መድኃኒታችን ቀድሶ ሥጋውንና ደሙን ለሐዋርያት አቀበላቸው። እንዲህም አላቸው "በዚች ቀን የእጃቸውን ሥራ እንዳይሠሩ ሕዝቡን ሁሉ እዘዙአቸው ይኸውም በሰኔ ወር ሃያ አንድ ቀን ነው"። ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን ከእርሳቸው ዘንድ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ። ከዚያች ቀን ጀምሮ አባቶቻችን ሐዋርያት በዓለሙ ሁሉ ውስጥ አምላክን በወለደች በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ቤተ ክርስቲያን የሚያንሳንፁ ሆኑ።                            ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #በቂሣርያው_ሊቀ_ጳጳሳት_በአባ_ባስልዮስ ዘመን እንዲህ ሆነ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ቤተ ክርስቲያን በሠራ ጊዜ በውጡ የእመቤታችን የማርያምን ሥዕል ይሥልበት ዘንድ ሠሌዳ ፈለገ ሰዎችም በአንድ ባለጸጋ ዘንድ ስለ አለ አንድ መልካም ሠሌዳ ነገሩት። ❤ ቅዱስ ባስልዮስም ሠሌዳውን እንዲሰጠው ወደ ባለጸጋው ላከ፤ ባለጸጋውም "ይህ ሠሌዳ ለልጆቼ ነው" አለ እንጂ ፈቃደኛ አልሆነም ከዚያም አልፎ በመድፈር በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ላይ የስድብ ቃል ተናገረ ወዲያውኑም በድንገት ወድቆ ሞተ ልጆቹም ፈሩ ያንንም ሠሌዳ ከብዙ ወርቅና ዕንቊ ጋራ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ አምጥተው የአባታቸውን በደል ያቃልልለት ዘንድ ለመኑት። ቅዱስ ባስልዮስም ያንን ሠሌዳ ወስዶ የእመቤታችንን ሥዕል ይሥልበት ዘንድ ለሠዒሊ ሰጠው። ❤ እመቤታችንም ቅድስት ድንግል ማርያም በሌሊት ራእይ ለቅዱስ ባስልዮስ ተገለጸችለት ሥዕሏንም በዚያ ሠሌዳ እንዳይሥል ከለከለችው። ከዐመፀኛም ሰው እጅ ወስዶታልና። እጅግም ያማረ የእመቤታችን ሥዕሏ የተሣለበት የሁለት ደናግልም ሥዕል ያንዲቱ በቀኝ ያንዲቱ በግራ ሆኖ የተሣለበት ቀይ ሠሌዳ ያለበትን ቦታ ነገረችው። ቅዱስ ባስልዮስም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ አመለከተችው ወደዚያ ቦታ ሔደ ያንንም ሠሌዳ አገኘው ወደዚያች ቤተ ክርስቲያንም በታላቅ ደስታ አመጣው። ❤ ከዚህም በኋላ ዳግመኛ በአንድ ጣዖት ቤት ሁለት ምሰሶዎች እንዳሉ አስረዳችው እነርሱንም አምጥቶ በመቅደሱ ፊት ለፊት እንዲአቆማቸው በላያቸውም ሥዕሏን እንዲያኖር አዘዘችው። ቅዱስ ባስልዮስም እነዚያን ምሰሶዎች ያመጣቸው ዘንድ ሔደ መሠርያኑም ሊከለክሉት ፈለጉ ጌታችንም ኃይላቸውን ደመሰሰ እነዚያንም ምሰሶዎች አምጥቶ በቤተ መቅደሱ ፊት ለፊት አቆማቸው በላያቸውም የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕሏን አስቀመጠ እግዚአብሔርም ከእነዚያ ምሰሶዎች በታች የውኃ ምንጭ ጠበል አፈለቀ በውስጥዋም የሚታጠብ ሁሉ ከአለበት ደዌ ሁሉ የሚድን ሆነ። እንዲሁም ከእመቤታችን ማርያም ሥዕል በሽተኞችን ሁሉ የሚፈውስ የዘይት ቅባት ፈሰሰ ይህ ሁሉ የሆነ የእመቤታችን ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በከበረችበት በሰኔ ዘር በሃያ አንድ ቀን ነው። ❤ በዚያችም ቀን እንዲህ ሆነ አንዲት ሴት መጥታ ታጠበች ወዲያውኑም ሁለመናዋ በለምጽ ተሸፈነ ቅዱስ ባስልዮስም ወደርሱ አስቀርቦ በእርሷ ላይ የሆነውን ጠየቃት እርሷም የእኅቷን ባል እንደወደደችና እኅቷን በመርዝ ገድላ እንዳገባችው ነገረችው። ቅዱስ ባስልዮስም "ታላላቅ ሦስት ኃጢአቶችን ሠራሽ ግን ወደ እግዚአብሔር ንስሐ ግቢ ምንአልባት በደልሽን ይቅር ይልሽ እንደ ሆነ" አላት በዚያን ጊዜም ምድር ተሠንጥቃ እንደ ዳታን ዋጠቻት እርሷ የረከሰች ስትሆን ቤተ ክርስቲያን መግባትን ደፍራለችና።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤          ❤ #ሰኔ ፳ (20) ቀን። ❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ መሰቀልህን በቅዱሳት መጻሕፍት ሰማሁ ይኽን በዐይኔ አሳየኝ በማለት #መድኃኔዓለምን_ለጠየቁት_እሱም ለገለጸላቸው፤ የንጉሡን መልዕክተኞች ከንጉሡ ቤት እንገናኝ በማለት መልዕክተኞቹ ዘጠኝ ቀን ተጉዘው ሲደርሱ እሳቸው ቀድመዋቸው ንጉሡ ቤት ለተገኙት #አቡነ_ዐሥራ_ወልድ_ለልደታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የአቡነ_ዐሥራተ_ወልድ_ልደት፦ የትውልድ ሀገሩ ከዳሞት አውራጃ ልዩ ስሟ እነሴ ትባላለች የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ፃማ ክርስቶስ የእናቱ ስሙ ጽጌ ማርያም ይባላል። ሁለቱም ደጋጎች በእግዚአብሔር ሕግና በበጎ ሥራም ተስማምተው ይኖሩ ነበር እንደ ካህኑ ቅዱስ ዘካርያስና ቅድስት ኤልሳቤጥ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ዘወትር ወደ እግዚአብሔርና ወደ ድንግል ማርያም ይለምኑ ነበር። ያውም በጾምና በጸሎት ተወስኖ ለእግዚአብሔር የሚታዘዝ በጸሎቱ ሰው የሚጠቅም በጻድቃንም ዘንድ የተመረጠ ልጅ ይመኙ ነበር። እነርሱም እግዚአብሔር የሚፈሩ በሀብት የበለጸጉ ነበርሩ። ለድሆችና ለሚስኪኖች አብዝተው ይመጸውቱ ነበር እስከ ዘጠኝ ሰዓትም እየጾሙ ያለ ድሆችና ምስኪኖች ሁል ጊዜ አይበሉም ነበር። ❤ ከዕለታት በአንድ ቀን የእግዚአብሔር ሰው ለጽጌ ማርያም እንዲህ አላት "ዝናው በአራቱ መዓዘነ ዓለም ሁሉ የሚደርስ በሕይወተ ሥጋ እያለ የብዙ ሰዎች ነፍስን በጸሎቱ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ የሚያወጣ ወደ ሰማይም ወጥቶ የሥላሴን የሚያይ ልጅ ትወልጂ ዘንድ አለሽና ደስ ይበልሽ" አላት ቅድስት ጽጌ ማርያም ከእግዚአብሔር ሰው ይህን በሰማች ጊዜ "የፈጣሪዬ ፈቃድ ከሆነ" ብላ በልቡናዋም ተደሰተች። ❤ ከጥቂት ቀናትም በኋላ ፀንሳ ሰኔ በባተ ሃያ (20) ቀን ወለደች በእናትና በአባቱ ቤትም ታላቅ ደስታ ሁኖ ለድሆችና ለጦም አዳሪዎች ለዘመዶቻቸውና ለጎረቤቶቻቸው ታላቅ የምሳ ግብዣ አደረጉ እነርሱም በልተው ከጠገቡ በኋላ እነርሱንም ሕፃኑንም መረቋቸው በ40ኛው ቀንም "ዐሥራተ ወልድ" አሉት። ሥራው ልዩና ድንቅ የሆነ እግዚአብሔር ግን በእርሱ ላይ የማያልቅ ይቅርታውን አሳድሮ በበረከት ፍፁም ያደረገው ይህ ቅዱስ ልጅ ዐሥራተ ወልድን ሰጣቸው በእነርሱም ዘንድ የጽድቅን ሥራ ገለጠ። እርሱም በተወለደ በስምንተኛ ቀን ተነስቶ በሰዎች መካከል አንድ ሰዓት ያህል ቆሞ እንዲህ አለ፦ "ለአብ ምስጋና ይገባል፣ ለወልድም ምስጋና ይገባል፣ ለመንፈስም ቅዱስ ምስጋና ይገባል" በዚህም በዘመኑ ሁሉ ለጽድቅ ሥራ እንደሚነሣሣ ያመለክታል የእናቱ ጡት ሲጠባም ከቀኝ በቀር አይጠባም በዚህም የመንፈሳዊ ውሃ በቀር እንደማይጠጣ ይገልጣል። ይኸውም የእግዚአብሔር ቃል ነው። ❤ ከተወለደም በኋላ ከእናት ከአባቱ ጋር በሁሉ ነገር ቀንና ሌሊት አየታዘዘ የኖረው ዐሥራ ሁለት ዓመት ብቻ ነው ከዱር ዕንጨት ለቅሞ የሚያመጣበት ጊዜ ነበር ውሃም ከወንዝ እየቀዳ የወላጆቹን እግር የሚያጥብበት ጊዜም ነበር። እንዲህ አድርገው እየመረቁ መልካም አስተዳደግ በምክርና በተግሣፅ አሳደጉት። የዚህም ቅዱስ አቡነ ዐሥራተ ወልድ ዕድሜው ዐሥራ ሁለቱ ዓመት ከሆነው በኋላ የእግዚአብሔር ጸጋ አነሣሥታ ቀሰቀሰችውና ብሉያትንና ሐዲሳትን የዳዊትን መዝሙር ይማር ዘንድ ወደ አቡነ ተጠምቀ መድኅን ሄደ። ከአባታችን አቡነ ዐሥራተ ወልደ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ አቡነ ዐሥራተ ወልድ።

❤ ከዚያም በኋላ የሶርያ ንጉሥ ወልደ አዴር ሠራዊቱን ሁሉ ሰበሰበና ወጥቶ ሰማርያን ከበባት፡፡ በሰማርያም ታላቅ ራብ ሆኖ ነበር፤ እነሆም፥ የአህያ ራስ በአምሳ ብር፥ የርግብም ኩስ የጎሞር ስምንተኛ የሚሆን በአምስት ብር እስኪሸጥ ድረስ በሀገራቸው የሶርያ ሰዎች ሰፍረው ተቀመጡ፡፡ በዚህም ጊዜ እናት ልጇን ቀቅላ እስክትበላ ድረስ እጅግ አሠቃቂ ታላቅ ርሃብ ሆነ፡፡ ይህም ክፉ የርሃብ ዘመን በነቢዩ ኤልሳዕ ጸሎት በአንዲት ቀን ተለውጦ የጥጋብ ዘመን ሆኗል፡፡ 2ኛ ነገ 6፥8-33፣ 7፥1-20፡፡ ኤልሳዕም በዘመኑ ትንቢትን እየተናገረ እጅግ ታላላቅ ተአምራን እያደረገ እግዚአብሔርንም ሕዝቡንም ሲያገለግል ከኖረ በኋላ ሰኔ 20 ቀን ዐርፏል፡፡ ከሞተም በኋላ ዐፅሙ የሞተን ሰው አሥነቷል፡፡ 2ኛ ነገ 13፡21፡፡ ይኸውም የሞአብ ሰዎች አገራቸውን ከበው ሳለ አንድ ሰው ሞቶ ሊቀብሩት ሲወስዱት አደጋ ጣዮች አዩአቸው፡፡ እነርሱም ደንግጠው ሬሳውን በአልሳዕ መቃብር ላይ ጣሉት፡፡ በዚህም ጊዜ ሬሳው የአልሳዕ ዐፅም በነካው ጊዜ አፈፍ ብሎ ከሞት ተነሥቶ በእግሮቹ ቆሟል፡፡ ❤ ይህም ነቢይ በአራት ነገሥታት ዘመን ትንቢት ተናገረ እሊህም ኢዮራም፣ አካዝያስ ኢዩና ዮአስ ናቸው የትንቢትም ዘመን ከሃምሳ ዓመት በላይ ነው። ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም ከመምጣቱ አስቀድሞ ትንቢት ተናገረ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በነቢዩ በቅዱስ ኤሌሳዕ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 20 ስንክሳርና መዝገበ ቅዱሳን።                

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤             ❤ #ሰኔ ፳ (20) ቀን። ❤ እንኳን #ለታላቁ_ነቢይ ለየሳፋጥ ልጅ #ለቅዱስ_ኤልሳዕ_ለዕረፍቱ_መታሰቢያ_በዓልና #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ_ለአቡነ_ዘርዐ_ሃይማኖት_ዘሳይንት_በዐለ_ለዕረፍት እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከሰማዕት_አርጣልስ፣ #ከሚናስና_ከዘቡፍር_ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #ታላቁ_ነቢይ_ቅዱስ_ኤልሳዕ፦ የዚህም ነቢይ መጠራቱ እንዲህ ኾነ ኤልያስ አልፎ ሲሔድ የሳፋጥ ልጅ ኤልሳዕን በፊቱ ዐሥራ ሁለት ጥማድ አስጠምዶ ሲያሳርስ አገኘው እርሱም በነዚያ የተሾመ ነበር ኤልያስም ሔዶ መጎናጸፊያውን በላዩ ጣለበት። ኤልሳዕም ጥማዱን ትቶ ኤልያስን ተከተለው ኤልሳም "አባቴ እወድሃለሁ አንተንም እከተላለሁ" አለው ኤልያስም "ብላቴናዬ አድርጌሃለሁና ተመለስ" አለው። እርሱም ኤልያስን ከመከተል ተመለሰ ዐሥራ ሁለቱንም ጥማድ በሬዎች ወስዶ አረደ በላመ ፈጅ ጋኖችም ቀቅሎ ለሕዝቡ አቀረበላቸው እነርሱም በሉ ኤልያስንም ተከተሎት ሔደ ብላቴናውም ሆነ። ብዙ ዘመናትም ሲያገለግለው ኖረ። ❤ ኤልያስም በሚያርግበት ጊዜ ኤልሳዕን "ከአንተ ተለይቼ ወደ ሰማይ ሳልወጣ አደርግልህ ዘንድ የምትሻውን ለምነኝ" አለው ኤልሳዕም "በአንተ ያደረ ሀብተ መንፈስ ቅዱስ ዕጥፍ ሁኖ ይደርብኝ" አለው። ኤልያስ ኤልሳን "ድንቅ ነገርን ለመንከኝ ነገር ግን ከአንተ ተለይቼ ወደ ሰማይ ስወጣ ብታየኝ ይደርብህ ከአንተ ተለይቼ ወደ ሰማይ ስወጣ ባታየኝ ግን አይሆንልህም" አለው። ሁለቱም እየተነጋገሩ ሲሔዱ የእሳት ፈረስና እሳት ሠረገላ መጣ ወደ መካከላቸውም ገብቶ አራራቃቸው ኤልያስም በመነዋወጥና በጥቅል ነፋስ እንደዚህ ወደ ሰማይ ዐረገ። ❤ ኤልሳዕም አይቶ "የእስራኤል ኃይላቸውና ጽንዓታቸው አባ አባ ብሎ ጮኸ። ከዚህ በኋላም ዳግመኛ አላየውም ልብሶቹንም ከሁለት አድርጎ ከፈላቸው። ኤልያስም ለኤልሳዕ መጠምጠሚያውን ጣለለት በኤልሳዕ ራስ ላይም ወረደ ኤልሳዕም ተመልሶ በዮርዳኖስ ባሕር ዳር ቆመ። በራሱ ላይ የወረደች የኤልያስንም መጠምጠሚያ ይዞ ውኃውን መታባት ውኃውም አልተከፈለም "የኤልያስ ፈጣሪ ወዴት ነው ይህስ እንዴት ነው" አለ ከዚህ በኋላም ውኃውን መታው ውኃውም ተከፍሎ ወዲያና ወዲህ ቆመ ኤልሳዕም ተሻገረ። በዚህም ኤልሳዕ የመንፈስ ቅዱስን ሀብት በዕጥፍ እንደተቀበለ ታወቀ። ኤልያስ የወንዙን ውኃ አንድ ጊዜ ከፈለ ኤልያስ አንድ ምውት አስነሣ ኤልሳዕ ግን ሁለት ምውት አስነሣ። ❤ ከዚህም በኋላ ኤልሳዕ ወደ ኢያሪኮ ሲገባ የሀገሪቱ ሰዎች ውኃቸውን ሲጠጡት ሴቶቹ እንደሚመክኑ ነገሩት፡፡ እርሱም "ጨው ጨምራችሁ አዲስ ሸክላ አምጡልኝ" ብሎ ወደ ምንጩ ውሃ ሄዶ ጨውን ጨመረው፡፡ ውሃውም ጣፋጭ ሆነ፣ እርሱን ሲጠጡ የሚመክኑትም ሴቶች ወላዶች ሆኑ፡፡ ወደ ቤቴልም በወጣ ጊዜ ከከተማው ሲወጡ ታናናሽ ልጆችን አገኘ፡፡ እነርሱም "አንተ ራሰ በራ ውጣ" እያሉ ሲዘባበቱበት የእግዚአብሔርን ስም ጠርቶ ቢረግማቸው ወዲያው ሁለት ድቦች ከዱር ወጥተው አርባ ሁለት ልጆችን ገደሉ፡፡ ❤ ኤልሳዕ ሌላው የሚታወቅበት ነገር የመበለቲቷን ቤት በበረከት በመሙላቱ ነው፡፡ ሴቲቱ ወደ ኤልሳዕ መጥታ "የምታውቀው የእግዚአብሔር ሰው የሆነው ባሌ ስለሞተ አሁን ባለዕዳ ሁለቱን ልጆቼን ወስዶ በባርነት ሊገዛቸው" አለችው፡፡ እርሱም በቤቷ ምን እንዳለ ጠየቃት፡፡ "ለእኔ ለባሪያህ ከዘይት ማሰሮ በቀር በቤቴ አንዳች የለኝም" አለችው፡፡ እርሱም ከጐረቤቶቿ ባዶ ማድጋዎችን ተውሳ እንድታመጣ ነግሯት ማድጋዎቹን ሁሉ በጸሎቱ በተአምራት በዘይት ሞልቶላታል፡፡ እርሷም ዘይቱን ሸጣ ለባለ ዕዳው ከፈለች፡፡ የተረፈውንም ከልጆቿ ጋር ተመገበች፡፡ ነቢዩ ኤልሳዕ መካን ስለነበረችው ስለሱነማዊቷ ሴት ግያዝ ነግሮት ኤልሳዕ ካስጠራት በኋላ "በሚመጣው ዓመት በዚህ ወራት ወንድ ልጅ ትታቀፊአለሽ" ብለ ከነገራት በኋላ በዓመቱ ፀንሳ ወልዳለች፡፡ ልጁም ካደገ በኋላ ከአባቱ ጋር ወደ አዝመራ ወጥቶ ሳለ ታመመና በእናቱ እቅፍ እያለ ሞተ፡፡ በሞተም ጊዜ በእግዚአብሔር ሰው በነቢዩ አልጋ ላይ አስተኝታው በሩንም ዘግታበት ወጣች፡፡ ሎሌዋን ይዛ አህያዋን ጭና የእግዚአብሔርም ሰው ኤልሳዕ ወዳለበት ወደ ቀርሜሎስ ተራራ ወጣችና የልጇን መሞት ነገረችው፡፡ ኤልሳዕም ሄዶ የሞተውን ልጇን ከሞት አስነሣላትና "ልጅሽን አንሥተሽ ውሰጂ" አላት፡፡ እርሷም ለኤልሳዕ ከሰገደችለት በኋላ ልጇን ወሰደች፡፡ ❤ ነቢዩ ኤልሳዕ የሶርያ ንጉሥ ሠራዊት አለቃ ንዕማንን በዮርዳኖስ ውኃ እንዲጠመቅ ካደረገው በኋላ ከለምጹ ፈውሶታል፡፡ ንዕማንም ከለምጹ ከዳነ በኋላ ለኤልሳዕ ወርቅና ብር ልብስም ሊሰጠው ሲል አልሳዕ በሕያው እግዚአብሔር ስም ምሎ አልቀበልም አለው፡፡ ንዕማንም "እነሆ ከእስራኤል ዘንድ በቀር በምድር ሁሉ አምላክ እንደሌለ አወቅሁ" ብሎ ከመሰከረ በኋላ ሁለት የበቅሎ ጭነት አፈር ወስዶ ወደ ሀገሩ ሶርያ ሄደ፡፡ ❤ ደቀ መዝሙሩ ግያዝ ግን ንዕማንን በመንገድ ተከትሎ "ሁለት ጎልማሶች ከተራራማው ከኤፍሬም አገር ወደ እኔ መጥተዋልና አንድ መክሊት ብርና ሁለት መለወጫ ልብስ ትሰጣቸው ዘንድ እለምንሃለሁ ብሎ ጌታዬ ላከኝ" በማለት በኤልሳዕ ስም ዋሽቶ ተቀበለ፡፡ ኤልሳዕም ግያዝ በሥውር ያደረገውን ዐውቆ አዘነ፡፡ ወደ እርሱም ተመልሶ በመጣ ጊዜ "ግያዝ ሆይ፥ ከወዴት መጣህ?" አለው፡፡ እርሱም "እኔ ባሪያህ ወዴትም አልሄድሁም" አለ፡፡ ኤልሳዕም "ያ ሰው ከሰረገላው ወርዶ ሊቀበልህ በተመለሰ ጊዜ ልቤ ከአንተ ጋር አልሄደምን?" ብሎ ያደረገውን እንዳወቀበት ከነገረው በኋላ "እንግዲህስ የንዕማን ለምጽ በአንተ ላይ ለዘላለምም በዘርህ ላይ ይጣበቃል" አለው፡፡ ግያዝም እንደ በረዶ ለምጻም ሆኖ ከእርሱ ዘንድ ወጣ፡፡ ከዚህም ሌላ ኤልሳዕ ውኃ ውስጥ የወደቀውን የብረቱን ምሳር በውኃው ላይ ዕንጨቱን ጥሎ የሰመጠውን ብረት ተንሳፎ እንዲወጣ አድርጎታል፡፡ ❤ የሶርያ ንጉሥ ከእስራኤል ጋር ለመዋጋት በዱር ሰፍሮና ተደብቆ ሳለ የእግዚአብሔር ሰው ኤልሳዕ "ሶርያውያን በዚያ ተደብቀዋልና በዚያ ስፍራ እንዳታልፍ ተጠንቀቅ" ብሎ ወደ እስራኤል ንጉሥ ላከ፡፡ የእስራኤልም ንጉሥ በዚያ ባለመሄድ ራሱን አዳነ፡፡ የሶርያም ንጉሥ ባሪያዎቹን ጠርቶ "ከእኛ ዘንድ ከእስራኤል ንጉሥ ጋር የተወዳጀ እንዳለ ንገሩኝ?" አላቸው፡፡ ከባሪያዎቹም አንዱ "ጌታዬ ሆይ በእልፍኝህ ውስጥ ሆነህ የምትናገረውን በእስራኤል ዘንድ ያለ ነቢይ ኤልሳዕ ለእስራኤል ንጉሥ ይነግረዋል" አለው፡፡ የሶርያ ንጉሥ ኤልሳዕ ያለው በዶታይን እንደሆነ ሲነግሩት የዶታይንን ከተማ ከበባት፡፡ የኤልሳዕ ሎሌ ማለዳ ተነሥቶ የከበባቸውን ጭፍራና ፈረሶቻቸውን ሲመለከት እጅግ ፈራ፡፡ ኤልሳዕም "ከእኛ ጋር ያሉት ከእነርሱ ጋር ካሉት ይበልጣሉና አትፍራ" አለው፡፡ "አቤቱ ያይ ዘንድ ዓይኖቹን እባክህ ግለጥ" ብሎ በመጸለይ የብላቴናውን ዐይኖች ገለጠ፡፡ ❤ ኤልሳዕም በጸሎቱ ሁሉንም ዕውር አደረጋቸው፡፡ ወደ ሰማርያም እየመራቸው ከወሰዳቸው በኋላ ዳግመኛ ያዩ ዘንድ ጸለየና ሁሉም ማየት ቻሉ፡፡ የእስራኤልም ንጉሥ ባያቸው ጊዜ አልሳዕን "አባቴ ሆይ?" ባለው ሰዓት እንዳይገድላቸው ይልቁንም አብልቶ አጠጥቶ እንዲልካቸው ነገረው፡፡ እነርሱም በልተው ጠጥተው ሲያበቁ ወደ ጌታቸው ሄዱ፡፡

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤           ❤ #ሰኔ ፳ (20) ቀን። ❤ እንኳን #ለእናታችን_ለእመቤታችን_ለቅድስት #ድንግል_ማርያም_በኬልቄዶን_አውራጃ_በቂሣርያ አገር ያለ ዕንጨት ያለ ጭቃና ውኃ በሦስት ደንጊያዎች #የመጀመሪዋ_ቤተ_ክርስቲያኗ በተወደደ ልጅዋ እጅ #ለታነፀችበት_ለሕንጸተ ቤተ ክርስትያን_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረን።                        ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_እግ_ነግ_ዜማ፦ "አመ የሐንፃ #እግዚአብሔር_ለጽዮን ወይኄድሳ ለኢየሩሳሌም #ኢየሱስ_ክርስቶስ ምስለ #መላእክቲ_ ዖዳ በደሙ ቀደሳ በዕፀ መስቀሉ ዐተባ"። ትርጉም፦ #እግዚአብሔር_ጽዮን ባነጻት (በሰራት)ና #ኢየሩሳሌምንም በሚያድሳት ጊዜ #ኢየሱስ_ክርስቶስ #ከመላእክቱ_ጋር_ዞራት በደሙም ቀደሳት (አመሰገናት) በዕፀ (በዕንጨት) መስቀሉም ባረካት። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ በዚች ቀን #በኬልቄዶን_አውራጃ_በቂሣርያ አገር #የእመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም_ቤተ_ክርስቲያን_ያለ_ዕንጨት_ያለ_ጭቃና_ውኃ_በሦስት_ደንጊያዎች_በተወደደ_ልጅዋ_እጅ_የታነፀችበት_ነው። ልመናዋ በረከቷም ወንዶችና ሴቶች ባሮቿ ከሆነ ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን።                                                  ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እማዕምቅ ጸዋዕኩከ እግዚኦ። እግዚኦ ስምዐኒ ቃልየ። ወይኩን ዕዝንከ ዘያፀምዕ ቃለ ስእለትየ"። መዝ 129፥1-2። የሚነበበው ወንጌል ወይም ማቴ 13፥44-ፍ.ም።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ግሩም ምክሩ እምዕጓለ እመሕያው። ዘይሬስያ ለባሕር የብሰ። ወበተከዚ የኃልፋ በእግር"። መዝ 65፥5-6 የሚነበበው ወንጌል ሉቃ4፥24-38። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 14፥29-34፣ 2ኛ ጴጥ 3፥1-8 እና የሐዋ ሥራ 13፥38-44። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የሕንጸተ ቤተ ክርስቲያን በዓል፣ ነቢዩ ኤልያስ የዕረፍት በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ ከዚህ በኋላ በዚያች ቀንና በዚያች ሌሊት በሥጋው ላይ እሳትን አነደዱ እሳቱም በላዩ እየነደደ ምንም ምን አልነካውም ወስደውም በገበያ ውስጥ ጣሉት ከዚያም አንሥተው በባሕር ውስጥ ጣሉት በእግዚአብሔርም ፈቃድ ወደ ደሴቱ ወደብ ዳር ደረሰ እናቱም ጠብቃው ነበርና ወስዳ ገነዘችው ለጥቂት ወራትም በቤቷ ውስጥ ሸሸገችው። ❤ ከዚህም በኋላ ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያን ሠሩለት ሥጋውንም በውጧ አኖሩ ከእርሱም ታላላቅና ብዙዎች ድንቆችና ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቱ በሐዲስ ቅዱስ ጊዮርጊስ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።                            ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #አባ_ብሶይ_አኖብ፦ የስሙ ትርጓሜውም የጠራ ወርቅ ማለት ነው። ይህም ቅዱስ ከድምያጥ አውራጃ ስሟ ባኖስ ከሚባል አገር ከአቅራብ መኰንን ከቆጵርያኖስ ጭፍሮች ውስጥ ከከተማዋ ታላላቅ ሰዎች ልጆች ወገን ነበር በዚህም ቅዱስ በመኰንኑ ዘንድ ነገር ሠሩበት። ቅዱሱም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በፊቱ ታመነ። ❤ ወደ እንዴናውም ወሰዱት በመኰንኑ አርያኖስ ፊት ቁሞ በጌታችን ታመነ አርያኖስም በእርሱ ላይ ተቆጣ "ለአማልክትም ሠዋ" አለው። አልታዘዘለትም ሥቃዩንም አልፈራም መኰንኑም ወስዶ ጽኑዕ ሥቃይ አሠቃየው ከዚያም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡት አዘዘ ወደሚገድሉበት ቦታም ሊወስዱት አወጡት ብዙ ሕዝብም ይከተሉት ነበር እነሆ ከዚያም የአርያኖስ መኰንን አንበሶች ነበሩ። የሚጠብቃቸውም ሰው ነበር እነርሱም በብረት ሰንሰለት ታሥረው ነበር ከእነርሱም አንዱ አንበሳ የብረት ሰንሰለቱን በጥሶ ሩጦ ወደ ቅዱስ ደረሰ። የእግዚአብሔርም መልአክ ቅዱሱን በአንበሳው ጀርባ ላይ አወጣውና ዐይነ ፀሐይ ወደሚባል አገር እስከሚያደርሰው በረረበት ቅዱሱ ግን ዐይኑን ሸፍኖ ስለ ነበር ውዴት እንዳለ አላወቀም በዚያም ራሱን በሰይፍ ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ብሶይ አኖብ በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 19 ስንክሳር።                           ✝️ ✝️ ✝️ ❤ "#ሰላም_ለጻድቃን_እለ_በቋዓት"። ትርጉም፦ በቋዓት ያሉ ለኾኑ #ጻድቃን_ሰላምታ_ይገባል። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_በተአምኆ_ቅዱሳን ላይ።                                                        ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወይርአዩ አሕዛብ በቅድመ አዕይንቲነ። በቀለ ደሞሙ ለአግብርቲከ ዘተክዕወ። ይባዕ ቅድሜከ ገዐሮሙ ለሙቁሓን"። መዝ 78፥10-11። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ተሰ 1፥1-8፣ 1ኛ ዮሐ 2፥14-20 እና የሐዋ ሥራ 19፥11-18። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 24፥8-13። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ቄርሎስ ወይም የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ቅዳሴ ነው። መልካም በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤               ❤ #ሰኔ ፲፱ (19) ቀን። ❤ እንኳን #ለሰማዕቱ_ሐዲስ_ቅዱስ_ጊዮርጊስ፣ #ለአባ_ብሶይ_አኖብ ሰማዕትነት ለተቀበሉት #ለዕረፍታቸው_በዓልና_ለአምስት_ጭፍሮች እሊህም #ለአርሶፎኒስ_ለጴጥሮስ_ለአስኪርዮን #ለአርጌንዮስ_ለቢልፍዮስ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት #ለዕረፍታቸው_መታሰቢያ_በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከደብረ_ቋዓት ቅዱሳን አባቶቻችን ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #አምስቱ_ጭፍሮች፦ እሊህም ስማቸው አርሶፎኒስ፣ ጴጥሮስ፣ አስኪርዮስ፣ አርጌንዮስና ቢልፍዮስ ነው። በዲዮስጲልዮስ ቅጽር ውስጥ ይኖሩ ነበር። መኰንኑም ለጣዖታት እንዲሠው በአስገደዳቸው ጊዜ "እኛስ የንጉሣችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ትእዛዝ እንፈጽማለን ለእርሱም እንሰዋለን" አሉት መኰንኑም ሰምቶ ተቆጣ በአንድ ቤት ውስጥም እንዲዘጉባቸውና እስከ ሁለት ቀን ያህል ውኃ እንዳይሰጧቸው አዘዘ። ❤ ከዚህም በኋላ እንዲያመጧቸው አዘዘ በፊቱም በቆሙ ጊዜ "ለአማልክት ሠዉ" አላቸው እነርሱም በአንድ ቃል "እኛስ ለፈጣሪያችን ለክርስቶስ እንሠዋለን ለረከሱ አጋንንትን ግን አንሠዋም" አሉት። አንገታቸውንም አሥረው ወደ ሌላ አገር ይወስዱአቸው ዘንድ አዘዘ። አርጌንዮስም ወንድሞቹን "እኔ እውነትን እነግራችኋለሁ የእግዚአብሔር መልአክ አምስታችንንም በስማችን ሲጠራን ሸምቼዋለሁና" አላቸው። ❤ ዳክስ ወደሚባል መኰንንም በአደረሷቸው ጊዜ መኰንኑ አስቀድሞ አርሶፎኒስን ወስዶ "ለአማልክት ሠዋ" አለው እምቢ በአለውም ጊዜ በፈረስ ጅራት ላይ አሥረው በከተማ ውስጥ እንዲጎትቱትና እንዲአዞሩት አዘዘ። በመለሱትም ጊዜ በውሽባ ቤት ማንደጃ ውስጥ ፊቱን እንዲአጠወልጉት አዘዘ ሁለተኛም እስከ ሚጨነቅ ድረስ በሠረገላ ውስጥ አሥረው ቊልቊል ሰቀሉት ሃይማኖቱንም ጠብቆ ክብር ይግባውና ለጌታችን ነፍሱ ሰጠ። ❤ ሁለተኛም ጴጥሮስን አቀረቡት ዳክስም "ለአማልክት ሠዋ" አለው ትእዛዙንም ባልተቀበለው ጊዜ እንዲአሠቃዩትና እንጨት ተክለው ዘቅዝቀው እንዲሰቅሉት አዘዘ ሁለተኛም ምድሩን ቆፍረው ከትከሻው በታች ቀብረው በቅሎዎችን በላዩ እንዲነዱበት አዘዘ ይህንንም እግዚአብሔር እየረዳው ታገሠ ከጉድጓድም በአወጡት ጊዜ ከሥቃዩ ብዛት የተነሣ ሥጋው ጠወለገ መናገርም ተሣነው በግንድ ውስጥም አሥረው ጣሉት። ❤ ከዚህም በኋላ አርጌንዮስን አቀረቡት ዳክስም "ለአማልክት ሠዋ" አለው እምቢ ባለውም ጊዜ እስከሚገድሉት ድረስ ያሠቃዩት ዘንድ አዘዘ ያለ መብልና መጠጥም በተበሳ ግንድ ውስጥ አሥረው ዘቅዝቀው ሰቀሉት። ❤ ዳግመኛም አስኪርዮንን አቀረቡት ዳክስም "ለራስህ እዘን በክፉ አሟሟትም እንዳትሞት ለአማልክት ሠዋ" አለው እምቢ ባለውም ጊዜ እንዲሰነጥቁት አዘዘ ወታደሮችም ተረከቡትና በጽኑ ሥቃይ አሠቃዩት በትዕግሥቱም በአሸነፋቸው ጊዜ ለመኰንኑ ነገሩት በረኃብና በጽም ይሞት ዘንድ በግንድ ውስጥ አሥረው በባዶ ቤት እንዲዘጉበት አዘዘ እንዲሁም አደረጉበት። ❤ ደግመው ዲያቆን ቢፍዮስን አቀረቡት መኰንን ዳክስሞ "እንዳትሞት ለአማልክት ሠዋ" አለው ባልሰማውም ጊዜ እስከሚገድሉት ድረስ እንዲአሠቃዩት አዘዘ ሥጋውን ሠነጣጥቀው በከተማው አደባባይ ጎተቱት እንጨት ተክለውም ቊልቊል ሰቀሉት በአንገቱም ከባድ ደንጊያ አንጠለጠሉ ከሃይማኖቱም ባልተናወጸ ጊዜ በረኃብና በጽምዕ እንዲሞት በግንድ ውስጥ አሥረው በላዩ መዝጊያ ሠርተው ዘጉበት። በየዕለቱም ወንድሞች ምእመናን ከውጭ ሆነው ይጎበኙት ነበር ጳሔን የተባለው የሰኔ ወር በባተ በሠላሳ ጴጥሮስ ነፍሱን ሰጠ። እርሱንም አውጥተው ደጁን በሌሎቹ ላይ ዘጉ። ❤ የከበረ አርጌንዮስም ከአምስት ቀን በኋላ ዐረፈ እርሱን አውጥተው በቀሩት ላይ ደጁን ዘጉ። ብፁዕ አስኪርዮንም ከዐሥራ ሁለት ቀን በኋላ ዐረፈ። እርሱንም አውጥተው በቅዱስ ቢልፍዮስ ላይ ደጃፍ ሠርተው ዘጉበት እርሱም የሚያርፍባት ቀን ስትደርስ ወንድሞቼ ታገሡኝ በዚች ሌሊት እወጣለሁና አላቸው። ከዐሥራ ዘጠኝ ቀን በኋላ በዚያች ልሊት ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በእሊህ ገድለኞች ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                            ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #ሰማዕቱ_ሐዲስ_ቅዱስ_ጊዮርጊስ፦ የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም መዛሕዝም ነው ትርጓሜውም ድንገተኛ ማለት ነው። እርሱም እስላም ነበር ከግብጽ ደቡብ ድምራ ከሚባል አገር ክርስቲያን ሴት አግብቶ ከእርሷም ሦስት ልጆችን ወለደ ከሦስቱም አንዱ ይህ ቅዱስ ነው። ከእናቱም ጋራ ወደ ቤተ ክርስቲያን ይሔድ ነበር ቅዱስ ቁርባንንም ይቀበል ዘንድ እናቱን ለመናት እርሷም ማንም የክርስትናን ጥምቀት ሳይጠመቅና ንጹሕ ሳይሆን ቁርባን ሊቀበል አይችልም አለችው። ❤ ከዚህም በኋላም ከተረፈ መሥዋዕቱ ሰጠችው በጎረሳትም ጊዜ ጣዕሟ በአፉ ውስጥ እንደ ማር ሆነ "የዚች የቁራሿ ጣዕም በአፌ ውስጥ እንዲህ የሆነ የዋናው የቁርባኑ ኅብስት ጣዕም ምን ያህል ይሆን" ብሎ በልቡ አሰበ ከዚች ጊዜ ጀምሮ ክርስቲያን ይሆን ዘንድ ወደደ። ❤ በአደገም ጊዜ ክርስቲያን ሴት አገባ ክርስቲያን ይሆን ዘንድ መፈለጉንም ነገራት እርሷም ወደሌላ አገር ሒዶ የክርስትናን ጥምቀት እንዲጠመቅ መከረችው እርሱም ወደ ሌላ አገር ሒዶ ተጠመቀ ስሙንም ለውጦ ጊዮርጊስ ተባለ። እስላሞችም በአዩት ጊዜ ይዘው ታላቅ ሥቃይን አሠቃዩት ከዚያም አምልጦ ሳፍጥ ወደሚባል አገር ሸሸ በዚያም ሦስት ዓመት ኖረ። ወሬውም በተገለጠ ጊዜ ቀጡር ወደ ሚባል አገር ሒዶ የልዳዊው ሰማዕት የቅዱስ ጊዮርጊስን ቤተ ክርስቲያን እያገለገለ ኖረ። ❤ ከዚህ በኋላ ወደ አገሩ ድምራ ተመለሰ እስላሞችም ሰሙ ይዘውም ለመኰንኑ ሰጡት የመኰንኑም ሚስት ክርስቲያን ነበረች ለመኰንኑም "አታሠቃየው" አለችው መኰንኑም አሥሮ በወህኒ ቤት ዘጋበት። እስላሞችም ተሰብሰቡ የወህኒ ቤቱንም ደጅ ሰብረው ታላቅ ግርፋት ገረፉት አካላቱም ቈራርጠው በሕይወትና በሞት መካከል ጣሉት። ሲነጋም ክርስቲያኖች የሞተ መስሏቸዋልና ሊቀብሩት መጡ ነገር ግን በሕይወት አገኙት። ❤ ከዚህም በኋላ እስላሞች ተሰብስበው "ከዚህ ምክርህ ካልተመለስክ እኛ ጽኑ ሥቃይ አሠቃይተን እንገድልሃለን" አሉት የመዛሕዝም ልጅ የከበረ ጊዮርጊስም "ሰማይና ምድርን የፈጠረ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስን አልክደውም የፈለጋችሁትን አድርጉ" አላቸው። እጅግም ተቆጡ በመርከብ ምሰሶ ላይም ሰቅለው ታላቅ ሥቃይን አሠቃዩት መኰንኑም ከስቅላት አውርደው በእሥር ቤት እንዲአሥሩት አዘዘ እንደዚሁም አደረጉ። ሚስቱም ታጽናናውና እንዲታገሥ ታደርገው ነበር ሰይጣንም እንዳያስተውና የደከመበትን ዋጋ እንዳያጣ በልቡ ወደ ክርስቶስ ያስብ ዘንድ ትመክረው ነበር። ❤ ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸለትና አረጋጋው አበረታታውም ከሰማዕታትም ጋራ እንደ ተቈጠረ በማግሥቱም ራሱን በሰይፍ እንደሚቆርጡት ነገረው። በነጋም ጊዜ እስላሞች ወደ መኰንኑ ተሰብስበው ጊዮርጊስን ይሰጣቸው ዘንድ ፈለጉ መኰንኑም የወደዱትን ያደርጉበት ዘንድ እንዲሰጧቸው አዘዘ። ❤ ከዚህም በኋላ ከእሥር ቤት አወጡት ድምራ በምትባል አገር በከበረ የመላእክት አለቃ በቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ራሱን በሰይፍ ሰኔ 19 ቀን ቆረጡ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።

❤ አባ ጰላሞንም እየጸለየ ቃሉ ወዳመለከተው ወደ አባ ለትጹን በዓት ደረሰ፡፡ አባ ጰላሞንም ባየው ጊዜ በደስታ ተቀብሎ ሰላምታ ሰጠው፡፡ ወደ ተራራውም ወጥተው ከጸለዩ በኋላ ተቀምጡ፡፡ አባ ጰላሞንም የመረረ ልቅሶን እያለቀሰ ሰይጣን በፈተናው እንደጣለው ለአባ ለትጹን ይነግረው ጀመረ፡፡ እንዲህም አለው፡- "በአንዲት ዕለት የእጅ ሥራዬን ለመሸጥ በግብፅ ገበያ መንገድ ስጓዝ ሰይጣን መጥቶ ልቤን አዘነጋት፤ መድኃኒት የሚሆነኝን የጌታዬ የኢየሱስ ክርስቶስን ስም እጠራ ዘንድ አልተወኝም፡፡ ዳግመኛም እንደ ንጉሥ ከተማ የታነፀች ውኃዎችና ተክሎች መልካም ዛፎችም ያሏት ከተማን አሳየኝ፡፡ የእጅ ሥራዬንም ልሸጥ ሳስብ ባሏ ብዙ ገንዘብ ትቶላት ሙቶ በምታዝን ሴት አምሳል ታየኝ፡፡ "የእጅ ሥራህን እኔ እገዛሃለሁ" ብለኝ ወደ አዳራሽ አስገባችኝ፡፡ እንቅቦቹንም ከላዬ አውርዳ አኖረች፣ እግሮቼንም አጠበች፣ አሽከሮቿንም ምግብ ያቀርቡ ዘንድ አዘዘቻቸው፡፡ ከእርሷ ጋርም እበላ ዘንድ ብዙ ማለደችኝ፣ በልተን ጠጥተን ሰከርን፡፡ ስንጨዋወትም አሽከሮቿ ሁሉም ወጡና ሁለታችን ብቻችንን ቀረን፡፡ ያንጊዜም ልቤ በዝሙት እሳት ተቃጠለ፡፡ እግዚአብሔርንም መላእክቶቹንም ቢሆን አላሰብኩም በእርግጥ ከእርሷ ጋር እንደሚተኛ ሆንኩ፡፡ ❤ ከዚህ በኋላ በነቃሁ ጊዜ ብመለከት ምንም ነገር አላገኘሁም፡፡ ሴትም ቤትም ማዕድም አትክልትም ቢሆን አላገኘሁም፡፡ ነገር ግን ራሴን ከተራራው በታች አገኘሁት፡፡ ምንም እንዳልበላና እንዳልጠጣም ሰው ሆንኩ፡፡ እጅግም አለቀስኩ፡፡ ሰይጣንም በሩቁ ቆሞ "መጻተኛ ጰላሞን ሆይ ወዮልህ እንደወፍ ላጠምድህ በአንተ ላይ በርትቻለሁና…" እያለ ሲዘብትብኝ አየሁት፡፡ ነገሩንም ሰምቼ በመስቀል ምልክት በላዩ አማተብኩ፣ ከእኔም ሸሸ፡፡ "አሁንም አባቴ ለትጹን ሆይ በደሌን ይቅር ይለኝ ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንድትለምንልኝ በቅድስናህ ተማፅኛለሁ" አለው፡፡ ቅዱስ አባ ጰላሞንም "አይዞህ እግዚአብሔር ኃጢአትህን ይቅር እንደሚልህ አምናሁ" ብሎ አጽናናው፡፡ ከዚህም በኋላ ተነሥቶ ሦስት መዓልትና ሦስት ሌሊት ጸለየ፡፡ ወደ እነርሱም እንዲህ የሚል ቃል መጣ፡- "የታመናችሁ አገልጋዮቼ አትፍሩ ከእንግዲህ ወዲህ ጠላት በእናንተ ላይ አይበረታታም፡፡ ጰላሞንም የሠራውን ኃጢአት በራሱ በሰይጣን ላይ አደረግሁ፣ የጰላሞንን ኃጢአት ብቻ አይደለም ነገር ግን የሚፈትናቸውን ሰዎች ሁሉ ኃጢአታቸውን በሰይጣን በራሱ ላይ እመልሳለሁ"፡፡ ❤ ከዚህም በኋላ አባ ጰላሞን ከአባ ለትጹን በረከትን ተቀብሎ እግዚአብሔርን እያመሰገነ ወደ በዓቱ ሄደ፡፡ ተጋድሎውንም ፈጽሞ በዚህች ዕለት በሰላም ዐረፈ፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ሁሉ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፡- የሰኔ 17 ስንክሳር።                                              ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ኀይልየኒ ወዝክርየኒ እግዚአብሔር። ወውእቱ ኮነኒ መድኃንየ። ቃለ ትፍሥሕት ውስተ አብያቲሆሙ ለጻድቃን"። መዝ 117፥14። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 17፥5-11።                            ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "አኮ ከመዝ ኃጥአንሰ አኮ ከመዝ። ዳዕሙ ከመ መሬት ዘይግሕፎ ነፋስ እምገጸ ምድር። ወበእንተዝ ኢይትነሥኡ ረሲዓን እምደይን"። መዝ 1፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ጢሞ 1፥1-10፣ ያዕ 5፥14-17 እና የሐዋ ሥራ 13፥44-49። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 6፥20-24። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የአባ ገሪማ ከሞት የተሰወሩበት በዓል፣ ለአባ ለትጹን፣ የአባ ጰላሞን የዕረፍት በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤             ❤ #ሰኔ ፲፯ (17) ቀን። ❤ እንኳን ለታላቁ አባት እናቱን በዝሙት አስረግዞ ፅንሱንም መርዝ አጠጥቶ በማኅፀኗ የገደለውን ርጉም ሰው ከዘላለማዊው ሥቃይና ኩነኔ ለታደጉት #ለአባ_ለትጹንና ፍፁም መናኒ ለሆነ ለመጻተኛ ከሰው ጋር ተነጋግሮ ለማያውቀውና በተራራ ላይ ብቻውን በገድል ተጠምዶ ሲኖር የጌታችንን መከራ እያሰበ ቀንና ሌሊት ያለቅስ ለነበረው ለባሕታዊ #አባ_ጰላሞን ለዕረፍታቸው መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከሰማዕታት #ከነአኮራን፣ #ከበርተሎሜዎስ፣ #ከእለስክንድርያ፣ #ከእለስክንድሮስ፣ #ከዮሴፍና_ከጻድቂቱ_አርሴማ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                           ✝️ ✝️ ✝️ ❤#አባ_ለትጹን፦ ይህም አባት ከብህንሳ አገር ነበር ጎልማሳ በነበረ ጊዜም "ነፍሱን ስለ እኔ የጣላትም ያገኛታል ለዘላለም ሕይወትንም ይጠብቃታል" የሚለውን በቅዱስ ወንጌል ውስጥ የተጻፈውን የሕያው ንጉሥን ቃል ሰማ ወዲያውኑ ልቡ ስለ እግዚአብሔር ፍቅርና ስለ ዘላለማዊ ተድላ እንደ እሳት ነደደ። ቅዱስ ቁርባንንም ተቀብሎ እስዋሕት ወደ ሚባል ገዳም ሔደ በጾም በጸሎትና በስግደት ታላቅ ተጋድሎን ያለ ማቋረጥ ይጋደል ጀመር ሰባት ሰባት ቀንም ይጾም ነበር። ❤ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸለትና የምንኲስና ልብስን ዘንድ ወደ አባ ኤስድሮስ እንዲሔድ አዘዘው እርሱም መልአኩ እንዳዘዘው ሔደ አባ ኤስድሮስም በልብሱና በአስኬማው ላይ አርባ ቀኖች ጸለየ ከዚያም በኋላ ልብሱንና አስኬማውን አለበሰው በገድል መጠመድን ጨመረ። ❤ ከዚያም መምህሩንም አስፈቅዶ ወጥቶ ብቻውን መጋደል ጀመረ፡፡ በአቅራቢያውም አንድ ገዳም ነበረና አንድ ቀን አበ ምኔቱ ታሞ ለሞት ደርሶ አገኘው፡፡ መነኰሳትም ዙሪያውን ከበውት ሲያለቅሱት አገኛቸው፡፡ እንዲሁም የሰይጣን ሠራዊትም አበ ምኔቱን ከበውት ደስ ሲሰኙ አያቸውና ደንግጦ "አባት ሆይ በአንተ ላይ የሆነው ምንድነው?" ብሎ አበ ምኔቱን ጠየቀው፡፡ እርሱም መነኰሳቱን ከእርሱ እንዲርቁ ካደረገ በኋላ የሠራውን በደሉን እንዲህ ብሎ ነገረው "እኔ ካሁን በፊት ማንም ያልሠራውን ኃጢአት ሠርቻለሁና አባቴ ሆይ በጸሎትህ አትርሳኝ፡፡ እኔ ቅስና ልሾም ፈልጌ ባልሾሙኝ ጊዜ ወደ ሌላ ሀገር ሄድኩ፡፡ "ኤጲስቆጶሱም ቅስና ሹሞኛል" ብዬ በድፍረት በቁርባን ላይ የምቀድስ ሆንኩ፡፡ ለጠላሁትም በቁርባኑ መሥዋዕት ውስጥ መርዝ አድርጌ እሰጠዋለሁ እርሱም ይሞታል፡፡ ከእናቴም ጋራ ዓሥር ጊዜ ተኝቻለሁ፣ ከእኔም ፀንሳ ለመውለድ በደረሰች ጊዜ ሥራይ አጠጥቼ ሕፃኑን በሆዷ ውስጥ ገደልኩት፡፡ ኃጢአቴ ብዙ ነውና ተነግሮ አያልቅም፡፡ ከበጎ ሥራም ምንም ምን የሠራሁት የለም፡፡ ነገር ግን በጸሎትህ አትርሳኝ ከዚህ ከኃላፊው ዓለም መውጫዬ ደርሷልና" ብሎ ለአባ ለትጹን ነገረው፡፡ ወዲያውም በክፉ አሟሟት ሞተ፤ ነፍሱንም አጋንንት ሲቀበሏትና በየራሱ በሆነ ሥቃይ ሲያሠቃዩዋት አባ ለትጹን ተመለከታት፡፡ ❤ በዚህም አባ ለትጹን የመረረ ልቅሶን አለቀሰ፡፡ ከዚህም በኋላ አባ ለትጹን "ስለ ወዳጆቹ ነፍሱን አሳልፎ የሚሰጥ ያለ ከሆነ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም" የሚለውን የቅዱስ ወንጌልን ቃል አስቦ ስለዚያ ኃጥእ ሰው ነፍስ ወደ ጌታችን እየለመነ አምስት ጊዜ እስከሚሞት ሰውነቱን ሊያሠቃያት ጀመረ፡፡ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል መትቶ አስነሣውና እንዲህ አለው "ስለዚያ ኃጢአተኛ ነፍስ ነፍስህን አትግደል ምሕረት አይገባውምና፡፡ እግዚአብሔር እውነት ፈራጅ ስለሆነ በደሉ አይሠረይለትም"፡፡ ❤ አባ ለትጹን ግን መሐሪ ይቅር ባይ ወደሆነ እግዚአብሔር ስለዚያ ኃጢአተኛ እየለመነ ራሱን ማሠቃየት አልተወም፡፡ ከዚህም በኋላ ራሱን በባሕር አስጥሞ ሞተ፡፡ ያን ጊዜም ጌታችን መጥቶ በባሕሩ ዳር ተቀመጠና ከባሕሩ ውስጥ አውጥቶ ከሞት ያድነው ዘንድ ሚካኤልን አዘዘው፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም አባ ለትጹንን ከባሕሩ አውጥቶ ከሞት አድኖ ቤታችን ፊት አቆመው፡፡ ክብር ይግባውና ጌታችንም "የመጥኩህ ለትጹን ሆይ ኃጢአቱ እጅግ ብዙ ስለሆነ በደሉም ከኃጢአተኞች ሁሉ በደል ስለሚከፋ ምሕረት ስለማይገባው ስለዚያ ኃጢአተኛ ሰው ብዙ ጊዜ ነፍስህን ለምን ትገድላለህ?" አለው፡፡ አባ ለትጹንም "መሐሪና ይቅር ባይ ጌታዬ ፈጣሪዬ ሆይ ያን ኃጢአተኛ ትምረው ዘንድ እለምንሃለሁ ያለዚያ ግን የእኔንም ነፍሴን ከእርሱ ጋራ ወደ ሥቃይ ውሰዳት" ብሎ ጌታችንን ለመነው፡፡ ❤ ከዚህም በኋላ ጌታችን የዚያን ኃጥእ ነፍስ ያመጣት ዘንድ ቅዱስ ሚካኤልን አዘዘውና አመጣት፡፡ ጌታችንም በከበሩ እጆቹ ዳሰሳትና እንዳልተፈጠረች አደረጋት፡፡ ወዲያውም "ይህቺ ነፍስ አፈር ትሁን እንጂ ለሥቃይ ወይም ለሕይወት አትሁን" አለ፡፡ አባ ለትጹንም ስለይቅርታውና ስለቸርነቱ ገናናነት መድኃኒታችንን ፈጽሞ አመሰገነው፡፡ ❤ ከዚህም በኋላ ጌታችን አባ ለትጹንን "የመጥኩህ ለትጹን ሆይ በእውነት እነግርሃለሁ መታሰቢያህን ለሚያደርግ ሁሉ በስምህ መባ ለሚያስገባ ወይም የተራበ ለሚያበላ የተጠማ ለሚያጠጣ የተራቆተ ለሚያለብስ ገድልህን ለሚጽፍ እኔ የሁሉንም ኃጢአታቸውን ይቅር እላለሁ፣ ስማቸውንም በሕይወት መጽሐፍ እጽፋለሁ፣ በጎ ዋጋቸውንም እሰጣቸዋለሁ" የሚል ቃልኪዳን ሰጥቶት ወደ ሰማያት ዐረገ፡፡ አባ ለትጹንም እጅግ ደስ ብሎት ወደ በዓቱ በመመለስ ብዙ ከተጋደለ በኋላ ገድሉን ፈጽሞ ሰኔ 17 ቀን በሰላም ዐረፈ፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ለትጹን ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትጉር ለዘላለሙ አሜን።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #ባሕታዊ_አባ_ጰላሞን፦ ከተጋድሎው የተነሣ ሰይጣን እስከ ደከመ ድረስ በተራራ ላይ እግዚአብሔርን እያገለገለ በገድል ተጠምዶ ሲኖር ቀንና ሌሊት ያለቅስ ነበር፡፡ ከሰው ጋር ሳይነጋገር ብዙ ዘመን ከኖረ በኋላ ሰይጣን የሚያስቅ ነገርንና ጨዋታን እያመጣበት ይፈትነው ነበር፡፡ ነገር ግን አባ ጰላሞን የጌታችንን መከራ እያሰበ ይተክዝ ያለቅስ ነበር፡፡ ሰይጣንም በዚህ ተቆጥቶ አንበሳ ሚዳቋን እንደሚያድን አባ ጰላሞንን ያድነው ነበር፡፡ በአንዲት ቀንም አባ ጰላሞን የእጅ ሥራውን ሊሸጥ ተነሠቶ ወደ ገበያ ሲጓዝ ሰይጣን ጎዳናውን አሳተው፣ ልቡንም መሰጠው እንጂ የሚያደርገውን ያውቅ ዘንድ አልተወውም፡፡ ❤ ከሰባት ቀኖች በኋላ አባ ጰላሞን ከረኀብና ከውኃ ጥም የተነሣ ከመሬት ላይ ወደቀ፤ ለሞትም የደረሰ ሆነ፡፡ ሰውን ወዳድ የሆነ ጌታችንም እንዲጠፋ አልተወውምና ሰይጣንን ከእርሱ አርቆ አሳደደው፡፡ አባ ጰላሞን በእርሱ ላይ የሆነውን ባወቀ ጊዜ ወደ ጌታን ጮኸ፡፡ ወዲያውም "ጰላሞን ሆይ አትፍራ ከእንግዲህ ወዲህ ጠላት በአንተ ላይ ክፉ ሊሠራ አይልችም፡፡ ነገር ግን ተነሥተህ ወደ ደቡብ ጥቂት ተጓዝ በዚያም በተራራው አጠገብ የሚኖር ስሙ ለትጹን የሚባል ሽማግሌ ጻድቅ ሰው ታገኛለህ፣ እርሱ ስለ ስሜ ብዙ መከራ የተቀበለ ነው፡፡ ያደረከውንም ሁሉ ሰይጣንም እንዴት እንዳሳተህ ንገረው፣ እርሱ ኃጢአትህ እስኪሠረይ ስለ አንተ ይጸልያልና" የሚል ቃልን ሰማ፡፡

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #ሰኔ ፲፯ (17) ቀን። ❤ እንኳን #ከዘጠኙ_ቅዱሳን_አንዱ_ለሆኑት ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ይስሐቅ ባደረጉት ተአምር ስማቸው #አባ_ገሪማ_ለተባሉት ከዚህ ዓለም #ከሞት_ለተሰወሩበት_ዓመታዊ_መታሰቢያ_በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #አቡነ_ይስሐቅ_አባ_ገሪማ፦ የዚህም ቅዱስ አባቱ የሮም ንጉሥ ነበር ስሙም መስፍንያኖስ ይባላል። የንግሥት እናቱ ስምም ሰፍንግያ ነው እርሷም መካን ስለሆነች በእናቱ በቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያም ከማላጅነት በመማፀን ወደ እግዚአብሔር እየለመነች ኖረች። ከዚህ በኋላ ይህን የተባረከ ልጅ ተቀበለች ስሙንም ይስሐቅ ብላ ጠራችው። ጥቂት በከደገ ጊዜም የቤተ ክርስቲያን ትምህርት አስተምረው ዲቁና አሾሙት። ❤ አባቱ በሞተ ጊዜ የሮም ሰዎች በአባቱ ዙፋን ላይ አነገሡት እየፈረደና በቅን እየገዛ ሰባት ዓመት ኖረ። በዋሻ የሚኖረው አባ ጰንጠሌዎንም በሰማ ጊዜ እንዲህ ብሎ ወደርሱ ላከ "ልጄ ይስሐቅ ሆይ ሙታኖቻቸውን ይቀብሩ ዘንድ ሙታኖችን ተዋቸው አንተ ግን ክብር ይግባውና የክርስቶስን የማያልፍ መንግሥት ትሻ ዘንድ ወደ እኔ ና" አባ ገሪማም መልእክቱ ደርሶት በሰማ ጊዜ መንግሥቱን ትቶ በሌሊት ወጥቶ ሔደ ያንጊዜም ጌታ የላከው የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ተገለጠለት ብርሃናውያን በሆኑ ክንፎቹም ተሸክሞ የዐሥር ወር የሚሆነውን መንገድ በሦስት ሰዓት አደረሰው በአባ ጰንጠሌዎንም ደጅ አቆመው ይህም በኢትዮጵያ ንጉሥ በእልአሚድ ዘመን ነበር። ❤ አባ ጰንጠሌዎንም ቅዱስ ይስሐቅን በአየው ጊዜ ደስ ብሎት አቅፎ ሳመው ወደ በዓቱም አስገብቶ የምንኲስና ልብስን አለበሰው። ይስሐቅም በጾም በጸሎትና በስግደት ተጠምዶ ቆዳው ከዐፅሙ እስከሚጣበቅ ሲጋደል ኖረ። ❤ ከዚህም በኋላ መደራ ወደተባለ ቦታ ሔደ በዚያም ድንቅና ተአምር እየአደረገ በሽተኞችን በመፈወስና አጋንንትን በማስወጣት ብዙ ዘመን ኖረ። በአንዲት ዕለትም በጥዋት ሥንዴ ዘራ በሠርክም መሥዋትን አሳረገ። በማግሥቱም በግራር ዛፍ ላይ በሮችን አውጥቶ የሥንዴውን ነዶ አበራየ ሰባ ሰባት የእንቅብ መስፈሪያም ሆነ። ሁለተኛም የወይን አረግ በአለት ላይ ተከለ ወዲያውም በቀለች አበበችና አፈራች በእርሷም መሥዋዕትን አሳረገ። አንዲት ቀንም ሲጽፍ መሸና ፀሐይ ሊጠልቅ ተቃረበ በቦታውም እንዲቆም አዘዘው ጽሕፈቱንም እስቲጨርስ ቆመ። ምራቁንም ትፍ ባለበት ዘንድ ጠበል ፈልቆ እስከ ዛሬ ለበሽተኞች ፈውስ ሆኖ ይኖራል። ❤ በአንዲት ዕለትም ሰዎች ወደ አባ ጰንጠሌዎን መጥተው "ቀሲስ ይስሐቅ እኮ ከበላ በኋላ የቁርባን ቅዳሴ ቀደሰ" ብለው ነገሩት አባ ጰንጠሌዎንም ወደርሱ ሒዶ "ልጄ ይስሐቅ ሆይ ምሥጢር ስለ አለኝ ከአጠገባችን ሰዎችን አስገልል" አለው ይስሐቅም "ሰዎችን ተውና ዕንጨቶችና ድንጋዮችም ይገለሉ" አለ። ወዲያውኑም ዕንጨቶችና ድንጋዮች አንድ ምራፍ ያህል ሸሹ። አባ ጰንጠሌዎንም "ልጄ ይስሐቅ ገረምከኝ" አለ ስለዚህም ከዚያች ጊዜ ጀምሮ ገሪማ ተባለ። ❤ መልካም ተጋድሎንና የቀና አካሔዱን በፈፀመ ጊዜ ክብር ይግባውና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠለት "ስሙን ለሚጠራና መታሰቢያው ለሚያደርግ፣ ገድሉንም ለሚጽፍና ለሚያጽፍ፣ ለሚያነበውና ለሚተረጉመው ስማቸውን በሕይወት መጽሐፍ እንደሚጽፍ ቃል ኪዳን ሰጠው ዳግመኛም "የተራበውን ላበላ፣ የተጠማውንም ላጠጣ እኔ የሕይወት እንጀራን እመግበዋለሁ የድኅነት ጽዋንም አጠጣዋለሁ" አለው። በቤተ ክርስቲያንህም በማኅሌት ያመሰገነውንና የፀለየውን እኔ የመላእክትን ምስጋና አሰማዋለሁ የተራቆተውንም ለሚያለብስ የብልህ እጅ ያልሠራው የብርሃን ግምጃን አለብሰዋለሁ ነፍሱም ከሥጋው በምትለይ ጊዜ የጨለማ መላእክት አይቀርቡትም። የብርሃን መላእክትም በዙሪያው አቆማቸዋለሁ። በስምህም ቤተ ክርስቲያን ለሠራ በሰማያት አርባ ሰባት የብርሃን ቦታዎችን እኔ እሰጠዋለ፣ ለቤተ ክርስቲያንህ መባ የሚሰጠውንም እኔ በመንግሥቴ እቀበለዋለሁ፣ ቦታህን የሚያከብረውንም እኔ በመንግሥቴ አከብረዋለሁ፣ ጠላቶች አጋንንትን ረግጦ የሚገዛበትንም እሰጠዋለሁ"። ❤ አባ ገሪማም "ይህን ታላቅ ሀብት በቸርነትህ ብዛት የሰጠኸኝ አቤቱ ስምህ ይክበር ይመስገን ግን ጌታዬ ሆይ መታሰቢያዬን ላደረገ፣ ገድሎንም ለጻፈ እስከ ስንት ትውልድ ትምርልኛለህ" አለ። መድኃኒታችንም "እስከ ዐሥራ ሁለት ትውልድ እምርዋለሁ" አለው አባ ገሪማም መድኃኒታችንን "ልጆች ባይኖሩትስ ምን ታደርግለታለህ" አለው። መድኃኒታችንም "ዐሥራ ሁለት ዕጽፍ ክብር እሰጠዋለሁ" ብሎ መለሰለት። ❤ ዳግመኛም "የሞት ጥላ እንደማያገኝህ ታላቅ የምሥራች እነግርሃለሁ" አለው ይህንንም ተናግሮ ሰላምታ ሰጥቶት በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ። ቅዱስ አባ ገሪማም በልቡ ደስ ተሰኘ ወዲያውኑም ሰኔ 17 ቀን በብርሃን ሠረገላ ተነጥቆ ብሔረ ሕያዋን ገባ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም አባ ገሪማ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 17 ስንክሳር።

❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤               ❤ #ሰኔ ፲፮ (16) ቀን። ❤ እንኳን #የእግዚአብሔር_መልአክ_ለዮሴፍ በሕልም ተገልጦለት #ሕፃኑንና_እናቱንም_ይዞ_ወደ #እስራኤል_አገር_እንዲመለስ_ላአዘዘበት_ዕለትና #መልካም_ሽምግልና_ላለለው ስም አጠራሩ ለከበረ በገዳም ለሚኖርና በገድል ለተጠመደ #ለስልሳ_ዓመት ብቻው ሰው ሳያይ ለኖረ አባት ለላይኛው ግብጽ ሰው #ለአባ_አቡናፍር_ለዕረፍቱ_በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #የአባ_አቡናፍርን_ገድል ከተናገረ #ከአባ_በፍኑትዮስ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                             ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #አባ_አቡናፍር፦ የዚህም አባት ገድል የተናገረ አባ በፍኑትዮስ ነበር እርሱ ቊጥሩ ከገዳማውያን ነውና። አባ በፍኑትዮስም ወደ በረሃ ውስጥ በገባ ጊዜ አንዲት የውኃ ምንጭና አንዲት የሰሌን ዛፍ አግኝቶ በዚያ እየተጋደለ ብዙ ዘመን ኖረ። ❤ በአንዲት ዕለትም አባ በፍኑትዮስ ወደርሱ ሲመጣ አባ አቡናፍርን አየው ፈርቶም ደነገጠ የሰይጣን ምትሐት የሚያይ መስሎታልና ይህም አባት አቡናፍር ልብስ አልነበረውም ጸጒሩና ጽሕሙ ሥጋውን ሁሉ ይሸፍናሉ አባ በፍኑትዮስም በላዩ በመስቀል ምልክት አማትቦ አጽናናው በፊቱም አቡነ ዘበሰማያት ጸለየ ከዚህም በኋላ "አባ በፍኑትዮስ ሆይ መምጣትህ መልካም ነው" አለው ይህንንም በማለት ከእርሱ ፍርሃቱን አራቀለት። ❤ ከዚህ በኋላ ሁለቱም በአንድነት ጸለዩ የእግዚአብሔርንም ገናናነት እየተነጋገሩ ተቀመጡ። ከዚህም በኋላ ወደዚህ በረሀ ከዓለም አወጣጡ እንዴት እንደሆነ በዚያ በረሀ አኗኗሩ እንዴት እንደሆነ ይነግረው ዘንድ አባ በፍኑትዮስ አባ አቡናፍርን ለመነው። አባ አቡናፍርም እንዲህ ብሎ መለሰለት "እኔ ደጋጎች ዕውነተኞች መነኰሳት በሚኖሩበት በአንድ ገዳም እኖር ነበር የገዳማውያንን ልዕልናቸውን ሲናገሩ ሲያመሰግኑአቸውም ሰማሁ "እኔም ከእናንተ የሚሻሉ አሉን?" አልኳቸው እነርሱም "አወን እነርሱ በበረሀ የሚኖሩ በእግዚአብሔር ዘንድ የከበሩ ናቸው እኛ ለዓለም የቀረብን ስለሆን ብንተክዝና ብናዝን የሚያረጋጋን እናገኛለን ብንታመም የሚጠይቀንና የፈለግነውን ሁሉ እናገኛለን በበረሀ የሚኖሩ ግን ከዚህ ሁሉ የራቁ ናቸው" አሉኝ። ይህንንም ነገር በሰማሁ ጊዜ ልቤ እንደ እሳት ነደደ መንፈቀ ሌሊትም በሆነ ጊዜ የፈቀደውን ይመራኝ ዘንድ ወደ ክብር ባለቤት ጌታችን ተነሥቼ ጸለይኩ። ትንሽ እንጀራም ይዤ ተጓዝኩ አንድ ጻድቅ ሰውም አግኝቼ የገዳምውያንን ገድላቸውንና ኑሮአቸውን እያስተማረኝ በእርሱ ዘንድ ኖርኩ። ❤ ከዚህም በኋላ ወደዚህ ደረስኩ እግዚአብሔር ያዘጋጀልኝን ይቺን ሰሌን አገኘኋት በየዓመቱም ዐሥራ ሁለት ዘለላ ታፈራለች ለየወሩም የምመገበው አንዱ ዘለላ ይበቃኛል ውኃም ከዚች ምንጭ እጠጣለሁ በዚች በረሀ እስከ ዛሬ ስልሳ ዓመት ኖርኩ ከቶ ያላንተ የሰው ፊት አላየሁም" አለኝ። ይህንንም ሲነጋገሩ የእግዚአብሔር መልአክ ወደ እነርሱ ወረደ ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋና ደም ሰጣቸው። ከዚያም በኋላ ከሰሌን ፍሬ ጥቂት ምግብ ተመገብን። ያን ጊዜም የቅዱስ አባ አቡናፍር መልኩ ተለወጠ እንደ እሳትም ሆነ በእግዚአብሔር ፊት ተንበርክኮ ሰገደ ለአባ በፍኑትዮስም ሰላምታ ሰጠው ያን ጊዜም ነፍሱን በጌታ እጅ ሰጠ። ቅዱስ በፍኑትዮስም በጸጉር ልብስ ገንዞ በዚያች ቦታ ቀበረው። ❤ ከዚህም በኋላ አባ በፍኑትዮስ በዚያች ቦታ ይኖር ዘንድ አሰበ በዚያን ጊዜ ያቺ የሰሌን ዛፍ ወደቀች የውኃውም ምንጭ ደረቀ። ቅዱስ አባ በፍኑትዮስ ወደ ዓለም ተመልሶ የገዳማውያንን ዜና ይልቁንም የቅዱስ አባ አቡናፍርን ዜና ይሰብክ ዘንድ ይህ በእግዚአብሔር ፈቃድ ሆነ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በእሊህ የከበሩ ገዳማውያን በአባ አቡናፍርና በአባ በፍኑትዮስ በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ 16 ስንክሳር።                                                 ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወአዝማድየኒ ቀብፁኒ ወተናከሩኒ። ወተኀየሉኒ እለ የኀሥሥዋ ለነፍስየ። ወእለኒ ይፈቅዱ ሕማምየ ነበቡ ከንቶ። መዝ37፥11-12። የሚነበበው ወንጌል ማር 3፥20-ፍ.ም።                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወበኀቤየሰ ፈድፋደ ክቡራን አዕርክቲከ እግዚኦ። ወፈድፋደ ፀንዑ እምቀደምቶሙ። እኌልቆሙ እምኆፃ ይበዝኁ"። መዝ 138፥16-17። የሚነበቡት መልዕክታት ኤፌ 6፥14-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 3፥10-15 እና የሐዋ ሥራ 3፥1-12። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 2፥19-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤               ❤ #ሰኔ_፲፭ (15) ቀን። ❤ እንኳን #ለታላቁ_ሰማዕት_ለሰማይ_ጭፍራ ለተባለ #ለቅዱስ_ሚናስ_ቤተ_ ክርስቲያን_መርዩጥ በተባለ አገር #ለከበረችበት_ለቅዳሴ_ቤቱ_በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የቅዱስ_ሚናስ_ቤተ_ክርስቲያን_ቅዳሴ_ቤት፦ ከዚህ አስቀድሞ የቅዱስ ሚናስ ሥጋ ተሠውሮ ይኖር ነበር ጌታችንም ሊገልጠው በወደደ ጊዜ ምክንያት አደረገ ይኸውም እንዲህ ነው ቅዱስ ሚናስ ሥጋው ተደፍኖ በሚኖርበት ኮረብታ አቅራቢያ በጎችን የሚያረባ አንድ ሰው በጎቹን እየጠበሸ ይኖር ነበር። ከዚያ እረኛ በጎች ውስጥ ደዌ ያለበት አንዱ በግ በዚያ በኮረብታው አጠገብ ባለ የጒድጓድ ውኃ ተጠምቆ ወዲያውኑ ከደዌው ዳነ እረኛውም አይቶ አደነቀ ሌሎችንም ደዌ ያለባቸውን አመጣ በዚያ ውኃም በታጠቡ ጊዜ ሁሉም ዳኑ። ❤ ከዚህም በኋላ ይህ በቦታው ሁሉ ታወቀ ደዌ ያለባቸውም ሁሉ እየመጡ አፈሩን ከውኃው ጋራ አንድ አድርገው ለውሰው በመቀባት ወዲያውኑ ይድኑ ነበሩ ምክንያቱን ግን አላወቁም። በዚያ ውኃና በአፈሩ በሽተኞችን እንደሚያድን የዚያ በግ ጠባቂ ወሬው በሮሙ ንጉሥ ዘንድ ተሰማ ለንሡም የቊስል ደዌ የታመመች ልጅ ነበረችው ወደ በግ ጠባቂውም ላካት እርሱም በጎቹን እንደ አዳናቸው አዳናት። እርሷም በተፈወሰች ጊዜ ከዚያ ቦታ ፈውስ የሚደረግበትን ምክንያት ታውቅ ዘንድ ወደደች። ❤ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ሚናስ በሕልም ተገለጸላትና ሥጋዬ በዚህ ቦታ ተደፍኖ ስለሚኖር እነሆ አስቆፍረሽ ታወጪው ዘንድ እግዚአብሔር አዞሻል" አላት። ከእንቅልፍም በነቃች ጊዜ ቅዱስ ሚናስ እንዳዘዛት አደረገች የከበረ ሥጋውንም አወጣች በዚያም ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያን ሠራችለት ንጉሡም በዚያ ቦታ ከተማ እንዲሠሩ መኳንንቱንና ሹሞቹን አዘዛቸው ታላቅ ከተማም ተሠራች ስሟም መርዩጥ ተባለች። ❤ እግዚአብሔር ከቅዱስ ሚናስ ሥጋ ቊጥር የሌላቸው ድንቆችንና ተአምራትን ገለጠ። ሊቀ ጳጳሳቱም ከኤጲስቆጶሳቱ መጥቶ ቤተ ክርስቲያኒቱን በዛሬዋ ሰኔ 15 ዕለት አከበራት በዚያቺም ቦታ የሚሠሩ የድንቆችና የተአምሮች ወሬ በቦታው ሁሉ ተሰማ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሚናስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሰኔ15 ስንክሳር።                                                   ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ውእተ አሚረ ተናገርኮሙ በራእይ ለደቂቅከ። ወትቤ እሬሲ ረድኤተ በላዕለ ኃይል። ወአልዐልኩ ኅሩይየ እምሕዝብየ"። መዝ 88፥19። የሚነበቡት መልዕክታት ኤፌ 7፥10-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 4፥16-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 25፥1-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 13፥44-51። የሚቀደሰው ቅዳሴ የወልደ ነጎድጓድ የቅዱስ ዮሐንስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ሚናስ የቅዳሴ ቤት በዓልና የጾም ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።