ስንክሳር (ገድላት) ዘዕለታት
Відкрити в Telegram
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርሥትያን ስንክሣር ውስጥ የተጻፉ የቅዱሳን አባቶቻችንና የቅዱሳት እናቶቻችን ገድላቸውና አስገራሚ ታሪካቸው ዓመቱን ሙሉ ምንም ሳይቋረጥ በየቀኑ ይነገርበታል! ለአሥትያየትዎ @abitago
Показати більше1 210
Підписники
Немає даних24 години
-37 днів
-530 днів
Архів дописів
1 210
በዓለም የምትኖር ሰው ሆይ! ይኽን የምሥራች ነገርንህ፤ በጆሮህ ሰምተህ በልብህ አኑረው፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ይኽንን ኹሉ ተኣምር የምታሳይህ የአማላጅነት ኀይሏን ሰው ኹሉ ታምኖ ይድን ዘንድ ነው እንጂ ለራሷ የምትሻው ሌላ ሐሳብ የላትምና እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ይኽን ማድረግ እንዲቻላት ብታምን በረድኤቷ ትጠበቃለህ፤ ከጥፋትም ኹሉ ትድናለህ፡፡ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎቷና በረከቷ የተወደደ ልጇ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ይቅርታው ከኹላችን ሕዝበ ክርስቲያን ጋራ ይኹን ለዘለዓለሙ አሜን፡፡ (ምንጭ፦ ተኣምረ ማርያም ዘደብረ ዘመዳ ምስለ ገድለ አቡነ በርተሎሜዎስ)
አምላክን የወለደች የክብርት እመቤታችን ከበዓሏ ረድኤት በረከት ትክፈለን!
በጽኑዕ ቃልኪዳኗ ታስምረን!
1 210
እንኳን ለጸዴንያ ማርያም ዓመታዊ መታሰቢያ በዓልና ለበዓለ ሥዕለ አድኅኖ አደረሳችሁ አደረሰን!!!
መስከረም 10 ቀን ይኽች ዕለት በቤተ ክርስቲያን የቅዱሳት ሥዕላት ክብርና ተኣምራት የሚነገርባት ክብርት ዕለት ናትና ስለ እመቤታችን ሥዕል ተኣምራት እንነግራችኋለን፦
በሰው እጅ ከሚሣሉ ኹላቸው ሥዕላት ጋራ ያስመስሏት ዘንድ የማይገባ እግዚአብሔር አምጻኤ ዓለማት ገባሬ መላእክት ነውና ይኽን ያደርግ ዘንድ ስለማይሳነው ይኽች ሥዕል በእግዚአብሔር እጅ የተሣለች ይመስለኛል እንጂ ለእኔስ እንጃ በሰው እጅ የተሣለች አትመስለኝም፡፡ እንደዚኽ አድርጎ ይሥላት ዘንድ ሰው አይቻለውምና፡፡ ነገር ግን ለእግዚአብሔር አይሳነውምና የከተማውና የቤተ መንግሥት ሰዎች በዚኽች በቅድስት ደብረ ዘመዳ ለመስማት እጅግ የምታስደንቅ የውበቷም ለዛ የሚያስደነግጥና ለማየት የሚያስፈራ ቅድስት ሥዕለ አድኅኖን ዜና ሰሙ፡፡
የከተማው ሰዎችም የምታደርገውን ኀይሏን የመልኳ ደም ግባት እጅግ የሚደንቅ እንደኾነ ሰምተው ይኽችን ድንቅ ድንቅ ተኣምራትን የምታደርግ የእመቤታችን የወላዲተ አምላክ የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል ሰርቆ ወደ ከተማቸው የሚወስዳት ሌባን ላኩ፡፡ ሌባውም ወደዚች ቅድስት ደብረ ዘመዳ ደርሶ በሌሊት ወደ ቤተ መቅደሱ ገባ፡፡ ቅድስት ሥዕለ አድኅኖን አግኝቶም ተሸክሞ ይዞ ከቤተ ክርስቲያን አወጣት፡፡ እርሱ በአሰበበት ሠርጥ መንገድም ወደ ከተማው ተጓዘ፡፡
እርሷ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በወደደችው መንገድ መርታ ወደ ሰፊው አደባባይ አደረሰችው፡፡ ያ ሜዳም የዓለም ሰዎች በዕለተ በዓሏ የእርሷን ሥዕል ሊመለከቱ የሚሰበሰቡበት ነበር፡፡ ሰዎች እጅግ ተሰብስበው ጸሎት ሊያደርሱ የዕጣን መባኣቸውንም ሊያቀርቡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብተው ከነበረችበት በአጧት ጊዜ ያን ጊዜ ካህናቱ ጮኹ፡፡ የገዳሙ ሰዎችም ተሰበስብው ዋይ አሉ፡፡ መለከት ነፉ፡፡ የሀገሩም ሰዎች ሰምተው ኹላቸው ተሰበሰቡ፡፡ በፈረሶችና በእግር ፈልገው ሊያገኟት በአራቱም የምድር አቅጣጫ ተበተኑ፡፡
መንፈቀ መዐልት በኾነ ጊዜም አንድ ሰው የልቡን ሐሳብ ይፈጽም ዘንድ ወደ ገዳም ሔዶ ነበር፡፡ የሔደውን ግን እርሷን ሊሻ አይደለም ስለ ራሱ ሐሳብ ነው እንጂ፡፡ የዓለም ሰዎች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም በበዓሏ ዕለት ሥዕሏን ሊመለከቱ ይሰበሰቡበታል ብለን አስቀድመን ወደተናገርነው ሜዳም ደረሰ፡፡
ያ ሰውም ወደ ሜዳውም በደረሰ ጊዜ ሳያስበው ድንገት ሌባው እግሩ በዐይን ሳይታይ ግን ከብረት ሠንሠለት በሚጸና ተኣምራዊ ገመድ ታስሮ የኹላችን እመቤት የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል ተሸክሞ አገኘው፡፡
ሌባውን የአገኘው ይኽ ሰውም ጮኸ፡፡ የገዳሙም ሰዎች ሰምተው የኹላችን እመቤት ሥዕል ወደተገኘው ሜዳ ተሰበሰቡ፡፡ መለከት ተነፋ፤ እልልታም ተሰማ፤ ለቅሶም ተወገደ፡፡ ካህናቱም እግዚአብሔርን እያመሰገኑ የኹላችን እመቤት ቅድስት ድንግል ማርያምን እያከበሩ ስብሐተ ማሕሌትን አደረጉ፡፡
ያን ጊዜም የገዳሙ የከተማው ሰዎችም ሌባውን ይገድሉት ዘንድ ፈለጉ፡፡ ዕኩሌቶቹ ‹‹እግርና እጆቹን እንቍረጠው እንጂ አንግድለው›› አሉ፡፡ ዕኩሌቶቹ ግን ‹‹እንግደለው›› አሉ፡፡ ርኅርኅተ ኅሊና እመቤታችን ወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያም ግን ለአበ ምኔቱ በጎ ፍርድን ገለጠችለት፡፡ አበ ምኔቱም ‹‹እኛ በጥበባችንና በፍለጋችን አላገኘነውምና እንተው፤ መግደል ብትሻ መግደል ስትችል ልትተወው ብትሻም እርሷ ታውቃለችና በተአምራዊ ገመድ አስራ በእጃችን የአስገባችውም እመቤታችን ወላዲተ አምላክ ቅድስት ድንግል ማርያም ናትና እኛስ እንተወው፡፡ ወደወደደውም ይሒድ›› አላቸው፡፡ ይኽንንም መክረው ወደወደደው ሊሔድ ሸኙት፡፡
አባቶቼና ወንድሞቼ ሆይ! መስረቁና እርሷን መፈለጉ ስለዚኽ የፍቅሯ ጽናት ነገር ቢኾን ይኽንን ተኣምር አሳይታ ለሰላም ሰዎች እንጂ ለሌቦች የሚገባ ያይደለ ፍርድን በሌባው ላይ የፈረደች የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል ናት፡፡ ይኽንን ነገር ብንመለከተው በጼዴንያ ሀገር እንደ አደረገችውና ለአፍርንጋዊ ፍርድን እንደፈረደችው ነው፡፡ ያ አፍርንጋዊም በሀገሩ ሳለ ወደ ንግዱ ሲጓዝ በጼዴንያ በቤተ መሪና ወዟ በምድር ላይ እስከሚፈስስ ድረስ የሚወርድ በዚህ ወዟም ሰውን ኹሉ የምታድን የመልኳ ደም ግባትም ለመናገር የሚያስደንቅና ድንቅ ተኣምር የምታደርግ የኹላችን እመቤት የቅድስት ድንግል ማርያምን የሥዕሏን ዜና ሰማ፡፡
የኹላችን እመቤት የቅድስት ድንግል ማርያምን የሥዕሏን ዜና በሰማ ጊዜም ዓለማዊ ሐሳቡን ኹሉ ትቶ ልቡ በፍቅሯ ተቃጥሏልና ወደምትገኝበት ሔደ፡፡ እስከ ዕለተ ሞቱም ስደተኛ እንግዳ ኾኖ እንደሚኖር መስሎም ሊገባ ወደደ፡፡ ይኽንንም የአሰበው ሰርቆ ወደ ሀገሩ እስከሚወስዳት ምክንያት ለማግኘት ነው እንጂ በዚያ ለመኖር አልነበረም፡፡ የቅድስት ማርታ ሰዎች ግን እንግዳን ለመቀበል ለወንድሞች እንደሚገባቸው አድርገው በቅንነት ተቀበሉት፤ ከእነርሱም ጋራ በሰላም አስቀመጡት እንጂ እነርሱ የልቡን ሽንገላ ለመስረቅም እንደመጣ አላወቁም፡፡
ይኽ አፍርንጋዊም እርሷን የሚያገኝበትን ብቻ እንጂ ስርቆት በደል እንደኾነ አላሰበም፡፡ ብዙ ወራትን ቆይቶ ሊያገኛት በአልቻለ ጊዜም ጠላት ዲያብሎስ የሥዕሏ ዕኩሌታ ቀድዶ ይወስድ ዘንድ ሐሳብ አመጣበት፡፡ ወደ ሥዕሏ ማስቀመጫ እጁን ሰድዶ ዕኩሌታዋን በመቍረጫ ቀደደው፡፡ ያን ጊዜም ብዙ ደም ከዚያች ቅድስት ሥዕል ፈሰሰ፡፡ እጆቹና ልብሶቹም በደም ታለሉ፡፡ ይኽን ተኣምር በአየ ጊዜም ፈርቶ ደንግጦ እንዳይገድሉት ሸሸ፡፡ ሲሸሽም አንድ ሰው አግኝቶት ልብሶቹ በደም ተበክሎ አየው፡፡ ‹‹ማንን ጻድቅ ሰው ገድለህ ይኾን?›› አለው፡፡ አፍርንጋዊውም ‹‹የኹላችን እመቤት የቅድስት ድንግል ማርያምን ሥዕል ቀድጄ ነው እንጂ ከሰው ወገንስ ጻድቅም ቢኾን ኀጥእ አልገደል ኹም›› አለው፡፡ ይኽም ሰው ሰምቶ ወደ ሰዎች ዘንድ ወሰደው፡፡ ሰዎችም ኹሉ ሊገድሉት ተሰበሰቡ፡፡
የኹላችን እመቤት ድንግል ማርያምም ‹‹ይኽን የአደረገ እኔን ከመውደዱ ጽናት የተነሣ ነው እንጂ በተንኮልና በዐመፃ አይደለምና አትግደሉት›› አለቻቸው፡፡ ይኽንንም ብላ እንዳይገድሉት አስተወቻቸው፡፡ የዚኸችን የቅድስት ሥዕሏን አካል ዕኩሌታም ወደተቈረጠው እንዲያስጠጉት አዘዘቻቸው፡፡
ወደተቈረጠው በአስጠጉት ጊዜም ያ የተለያየ የነበረው የሥዕሏ አካል ፈጥኖ ተጣበቀ፡፡ የመቍረጫው ምልክትም አልተገኘም፡፡ ደሙ ግን የእመቤታችን ሥዕል አጠገብ ለምልክት በሚቀመጥበት ሥፍራ እንደ ቀላ አለ እንጂ አልጠፋም፡፡ በአምሳለ ደም የሚታየውም ቀለም አይደለም ቀድሞ የሰማነው ደም ነው እንጂ፡፡ በቤተ ማርታ የነበረችው ያቺ ቅድስት ሥዕልም በቅድስት ደብረ ዘመዳ ያለችው ናት፡፡ አፍርንጋዊው የቈረጣት ያቺ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ቅድስት ሥዕልም ይኽች በቅድስት ደብረ ዘመዳ ያለችው ናት፡፡ አፍርንጋዊውን እንዳይገድሉት የአዳነችውም ያቺ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ቅድስት ሥዕል በቅድስት ደብረ ዘመዳ ያለችው ናት፡፡
አስቀድሞ በጼዴንያ አፍርንጋዊውን ከሞት እንደአዳነችውም እንደሰማን በቅድስት ደብረ ዘመዳም ሌባውን እንዳይገድሉት ስታድነው አየን፡፡ የጼዴንያዋ ሥዕልም ይኽቺ በቅድስት ደብረ ዘመዳ ያለችው ናት፡፡ ያን ጊዜም እርሷ ዛሬም በዚኽ ያለች እርሷ የተቈረጠችውም እርሷ ናት፡፡ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕል አጠገብ ከአለው ጋራ የተጣበቀው የተቈረጠውም የሥዕሏ ዕኩሌታ አካል ነው፡፡ ኹለንተናውም በደም እንደታለለ ተመልከተው፡፡
1 210
መስከረም 10 ገበያተኛውን ሕዝብ አስተምረው ሲጨርሱ ድንጋዩን ዳቦ እያደረጉ ሕዝቡን ይመግቡ የነበሩት ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ግርማ ሥሉስ ዕረፍታቸው ነው።
አባታቸው ነገደ ኢየሱስ እናታቸው ትኩና ለጽዮን የሚባሉ ሲሆን ትኩና ለጽዮን የዐፄ ሰይፈ አርእድ ልጅ ናት። ስለዚኸም አቡነ ግርማ ሥሉስ ትውልዳቸው ከመንግሥት ወገን ቢሆንም ‹‹በዓለም ነግሦ መኖርን አልፈልግም›› በማለት የዓለምን ጣዕም ንቀው ገዳም የገቡ ጻድቅ ናቸው። ክቡር ዐፅማቸው ያረፈው በጎንጅ ደብረ ጥበብ ቅዱስ ቴዎድሮስ ገዳም ነው። ገዳሙ በአማራ ክልል ምዕራብ ጎጃም ዞን ጎንጅ ቆለላ ወረዳ ከባሕር ዳር 70 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ከጥንታዊቷ የጎንጅ አነስተኛ የገጠር ከተማ ላይ ይገኛል። በጊዜው አወቃቀር የዞኑ ዋና ከተማ ፍኖተ ሰላም ነው። ምንም እንኳን ጎንጂ ቆላላ ለባሕር ዳርና ለአዴት ቅርብ ቢሆንም በአወቃቀር ደረጃ በምዕራብ ጎጃም ዞን ውስጥ ተካትቷል።
ጎንጅ ቴዎድሮስ ወይም ጎንጅ ደብረ ጥበብ ገዳም ከክርስቶስ ልደት በፊት በ4518 ዓመተ ዓለም በሊቀ ካህናቱ ዘካሪያስ አማካይነት ተመሠረተ። እስከ ልደተ ክርስቶስ ድረስ የኦሪት መሥዋዕት ሲሠዋበት ኖሯል። ደብረ ጥበብ የሚለው ስያሜው ከጠቢቡ ተዋነይ ጠቢብነት ጋር ይያያዛል፤ ይኸውም በአሁኑ አጠራር ጎንጅ ደብረ ጥበብ የተባለበት ምክንያት በገዳሙ ታዋቂ የነበረው የቅኔ ሊቅ ተዋነይ የተባለው ሊቅ መወደስ የተባለውን ቅኔ ከተቀኘ በኋላ በደመና ተጭኖ በተመሳሳይ ሰዓት ጎንደር ከተማ ዕጣነ ሞገር የተባለውን ቅኔ በመቀኘቱ እንደሆነ ታሪክ ያስረዳል። ሊቁ ተዋነይ ከዚኸ ዋርካ ሥር ተደግፎ ለ20 ዓመታት ግስ ገስሶበታል፣ የቅኔ ቀመር ቀምሮበታል፣ መወድስ ዘርፎበታል፣ ተፈላስፎበታል። የአካባቢው ሕዝብ በእምነት የሚኖር አስገራሚና የዋህ ሕዝብ ነው፣ የሀገሬው ሰው አዲስ ልብስ ገዝቶ ከመልበሱ በፊት እሑድ ቀን ወደ ቤተ ክርስትያን ወስዶ አስባርኮ ነው የሚለብሰው።
በገዳሙ ውስጥ 44 ታቦታት የሚገኙ ሲሆን ከእነዚኸ ታቦታት ውስጥ አንዱ የቅዱስ ባስልዮስ ታቦተ ነው። የጎንጅ ደብረ ጥበብ ካህናት ከ44ቱ ታቦታት ቀድመው የሚጠቅሱት ታቦተ ቅዱስ ባስልዮስን ነው። ምክንያቱም ታቦተ ቅዱስ ባስልዮስ በሌላ ቦታ ሳይኖር በጎንጅ ደብረ ጥበብ ብቻ መኖሩን ለማመልከት ነው። ከቤተ ክርስቲያኑ 50 ሜትር ያህል ከቅጽሩ ደግሞ 25 ሜትር ፈቀቅ ብሎ ትልቁ የተዋነይ ዋርካ በሰባት አክናፍ እንደዣንጥላ ተዘርግቶ ይገኛል። በወረዳው ከጎንጅ ደብረ ጥበብ የቅኔ ትምህርት ቤት በተጨማሪ ታዋቂው የቅኔ ትምህርት ቤት ዋሸራ ማርያም በዚኹ ወረዳ ይገኛል።
ጎንጅ ገዳም የሚገኘው ትልቅ ተራራ ሥር ሲሆን ሰይጣን ከተራራው ጫፍ ላይ ወጥቶ ድንጋዩን ገደሉን እየናደ ሲጥለው ድንጋዩ እየተፈነቀለ ሲወርድ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ሊያፈርስ ሲል ጻድቁ በቃላቸው ድንጋዩን እንዳትንቀሳቀስ ብለው ገዝተው አቁመውታል። በዚያ ትልቅ ገደል ላይ የድንጋዮቹ አቋቋም ላያቸው እጅግ ያስደንቃሉ።
የገዳሙ አስተዳዳሪ ቄስ መልካም በዜ ስለገዳሙ አመሠራረት በቃለ መጠይቅና በጽሑፍ በሰጡት ማስረጃ መሠረት የደብረ ጥበብ ጎንጅ ቴዎድሮስ ገዳም የኦሪት መሥዋት ሲሠዋበት የኖረ መሆኑ፣ ከዋሸራና ከጽላሎ በፊት በእነ ጠቢቡ ተዋናኝ ቅኔ የተዘረፈበትና አሁንም ያለበት መሆኑ፣ ጥንታዊ የብራና መጻሕፍትና ዕድሜ ጠገብ የብራና የመቃ ላይ ሥዕላትና በርካታ ቅርሶች የሚገኙበት ከመሆኑም በላይ ጻድቁ አቡነ ግርማ ሥሉስ የጸለዩበትና ዐፅማቸው ያረፈበት በመሆኑ ልዩና ታሪካዊ ገዳም ያደርገዋል።
ጻድቁ አቡነ ግርማ ሥሉስ ለ40 ዓመት ያህል እሙይት በተባለው ወንዝ አካባቢ ሲጸልዩ ከኖሩ በኋላ በራእይ ተነግሯቸው ወደ ጎንጅ ደብረ ጥበብ ቴዎድሮስ ገዳም በሚሔዱበት ጊዜ ድንጋዮች ተከትለዋቸው ሔደዋል። ተከትለዋቸው ከሔዱት ድንጋዮች መካከል አንዱ ግዝት ድንጋይ እየተባለ የሚጠራው በአሁኑ ወቅት ከገዳሙ 200 ሜትር ርቀት ላይ በደቡብ በኩል ይገኛል። ከላይ የተከማቸው ድንጋይ ወደ ገዳሙ ለመውረድ ሲንከባለል ተገዝቶ ቆሞ ላየው ይደንቃል። ድንጋዩ ከከተማው እስከ ገዳሙ ድረስ አልፎ አልፎ ተንጠባጥቦ ይታያል።
ጻድቁ ወንጌልን ሊያስተምሩ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ሲዘዋወሩ ዛፎችና ድንጋዮች ሁሉ ይከተሏቸው ነበር። አቡነ ግርማ ሥሉስ ገበያተኛውን ሕዝብ አስተምረው ሲጨርሱ ድንጋዩን ዳቦ እያደረጉ ሕዝቡን ይመግቡ የነበሩ ታላቅ አባት ናቸው። ጻድቁ የተወለዱት በተኣምራት በአካላቸው ላይ ማዕተብ አድርገው፣ በእጃቸው መስቀል ይዘው እና ተገዝረው ነው። ከልጅነታቸው ጀምረው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ተምረው ከጨረሱ በኋላ አበምኔትና መምህር በመሆን በገዳሙ ለ40 ዘመን በመምህርነት አገልግለዋል። በተጋድሏቸውም ወቅት እውይት ከተባለው ባሕር ውስጥ ገብተው ሲጸልዩ ያድሩ ነበር። በኋላ ከእሙይት ባሕር ወደገዳማቸው ቦታ ሲመለሱ ድንጋዮች ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ አቡነ ግርማ ሥሉስ›› እያሉ ከእሙይት ባሕር እስከ ጎንጂ ድረስ ተከትለዋቸዋል። በኋላም ወደ ገዳሙ ሊወርዱ ሲሉ አብዛኛው ድንጋይ በጻድቁ ቃለ ግዝት ከአፋፍ በላይ ሲቀር፣ ሦስቱ ድንጋዮች ግን አባታችንን ‹‹ከወደቁበት እንወድቃለን›› ብለው ተከትለዋቸው ሲወርዱ ‹‹አይሆንም ተመለሱ›› ብለው አዘዟቸው። ድንጋዮቹም ካለበት ቦታ ላይ ቆመው በመቅረታቸው ‹‹ግዝት ድንጋዮች›› ተብለው እስከዛሬ ድረስ ይጠራሉ።
ድንጋዮቹ የቆሙበት ቦታ ከታች ቁልቁለታማ ገደል ቢሆንም ምንም ሳይሆኑ በጻድቁ ቃለ ግዝት እንደቆሙ ቀርተዋል። ከአፋፍ በላይ የቀሩት ሌሎቹ ደንጋዮች በአሁኑ ወቅት ከጎንጂ ቆለላ ከተማ ከገበያው መሐል ይገኛሉ። ቦታው ከጊዜ በኋላ ገበያ እንደሚቆምበት የታያቸው አቡነ ግርማ ሥሉስ ከባሕር ውስጥ ወጥተው ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ አቡነ ግርማ ሥሉስ›› እያሉ የተከተሏቸውን ድንጋዮች ባሉበት ቦታ ላይ እንዲቆሙ ጻድቁ በቃላቸው ሲያዟቸው ‹‹ከጊዜ በኋላ ከዚኸ ቦታ ላይ ገበያ ይቆማል፣ የደጋውና የቆላው ወገኔ ለገበያ በሚገናኙበት ጊዜ ማረፊያና የሸቀጣሸቀጡ መቀመጫ ትሆናላችሁ›› ብለው ስላሏቸው በአሁኑ ወቅት በቍጥር ከ60 በላይ የሚሆኑ ድንጋዮች በገበያው ቦታ ላይ በየቦታው በመደዳ ተሰድረው ለገበያተኛው ሕዝብ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ።
አቡነ ግርማ ሥሉስ የትውልድ ሀገራቸው ጎጃም ሲሆን በተወለዱ ጊዜ ብርሃን ከሰማይ ወርዶላቸዋል። አስቀድመን እንደጠቀስነው የዐፄ ሰይፈ አርእድ የልጅ ልጅ ቢሆኑም ንግሥናን ትተው ዓለምን ንቀው ስለመነኑ መጽሐፍ ‹መናኔ መንግሥት ወብእሲት› ይላቸዋል። በአሁኑ ወቅት ከደብረ ጥበብ ገዳም ከፍ ብሎ በአቡነ ግርማ ሥሉስ ስም የተሰየመ ጠበል ፈልቆ ሕሙማን በየጊዜው እየተፈወሱበት ይገኛሉ። መስከረም 10 ቀን በገዳማቸው በዓለ ዕረፍታቸው በደማቅ ሁኔታ ይከበራል። ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን።
1 210
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
መስከረም 10-የጌታችን ቅዱስ መስቀል አገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ የገባበት ዕለት ነው፡፡
+ ጸዴንያ በምትባል አገር ሥጋ የለበሰች ከምትመስል ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ከሣላት ሥዕል ከሠሌዳዋ ቅባት እየተንጠፈጠፈ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያም ተአምር የተገለጠበት ዕለት ነው፡፡
+ ከከሃዲው ከሆሎፎርኒስ እጅ በጥበቧ እስራኤልን ያዳነቻቸው ጥበበኛዋ ዮዲት ዐረፈች፡፡
+ ቅድስት አትናስያና ሦስት ልጆቿ መታሰቢያ በዓላቸው ነው፡፡
+ ዳግመኛም በዚህችም ዕለት የከበረች ቅድስት መጥሮንያ በሰማዕትነት ዐርፋለች፡፡
ሰማዕቷ ቅድስት መጥሮንያ፡- ይህችውም ሰማዕት ቅድስት መጥሮንያ የአንዲት አይሁዳዊት ሴት አገልጋይ ነበረች፡፡ አሠሪዋ አይሁዳዊ ሴትም ቅድስት መጥሮንያን ክርስቲያን በመሆኗ ብቻ ሸክም ታበዛባትና ታንገላታት ነበር፡፡
ከሃይማኖቷም አውጥታ ጌታችንን ማመንን ልታስተዋት ብዙ ሞከረች፡፡ በአንዲት ዕለትም አይሁዳዊቷ ይዛት ወደ ምኩባራባቸው ሄደች፡፡ ቅድስት መጥሮንያ ግን ወደ ምኩራባቸው ሳትጋ ተመልሳ ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ጸሎት አደረገች፡፡ ወደ ቤታቸው ተመልሰው በገቡ ጊዜ አሠሪዋ ‹‹ወደ እኛ ምኩራብ ለምን አልገባሽም?›› ብላ ጠየቀቻች፡፡ ቅድስት ቅድስት መጥሮንያም ‹‹ከእናንተ ምኩራብ እግዚአብሔር ርቋልኮ፣ እንዴት ወደ እርሱ እገባለሁ! በውስጧ ልገባባት የሚገባኝ ቦታዬ ግን ክብር ይግባውና ጌታችን በከበረ ደሙ የዋጃት ይህች ቤተ ክርስቲያን ናት›› አለቻት፡፡ አሠሪዋ አይሁዳዊትም ከቅድስት መጥሮንያ ይህንን በሰማች ጊዜ እጅግ ተቆጥታ በኃይል ደበደበቻት፡፡ በጨለማ ቤት ውስጥ ዘጋችባትና ያለምግብና ያለመጠጥ ለ4 ቀን አሠረቻት፡፡ ከዚህም በኋላ ወደ ውጭ አውጥታ በጅራፍ ታላቅ ግርፋትን ገርፋ ድጋሚ በእሥር ቤት ጣለቻትና በዚያው ተንገላታ ዐረፈች፡፡ ነፍሷንም እግዚአብሔር ተቀብሎ የሰማዕታትን አክሊል አቀዳጃት፡፡ አሠሪዋ ግን ሥጋዋን አውጥታ በመጣል በዚያም መጥሮንያ ራሷን የገደለች አስመሰለች፡፡ ቅድስት መጥሮንያ ራሷን የገደለች ስለመሰለ አይሁዳዊቷን ሴት ግን ማንም የመረመራት የለም፡፡ ነገር ግን ለተገፉ የሚፈርድ፣ ለተበደሉ የሚበቀል እውነተኛ ዳኛ ልዑል እግዚአብሔር ቁጣው በዚያች አይሁዳዊ ሴት ላይ ወረደ፡፡ ከደርቧ ላይ ስትወርድ ድንገት ወድቃ በዚያው ከመቅጽበት ሞተች፡፡ በነፍሷም ወደ ዘላለማዊ እሳት ሄደች፡፡
ረድኤት በረከቷ ይደርብን፣ በጸሎቷ ይማረን፡፡
+ + + + + +
ጼዴንያ ማርያም፡- ጼዴንያ በምትባል ሀገር ማርታ የምትባል ደግ ሴት ነበረች፡፡ ይህች ደግ ሴት በቤቷ ትልቅ አዳራሽ ሠርታ እንግዶችን እንደ አባታችን አብርሃም ተቀብላ አብለታ አጠጥታ ማደሪያ ቦታም ሰጥታ ታስተናግድ ነበር፡፡ አባ ቴዎድሮስ የሚባል ኢትዮጵያዊ መነኩሴ ወደ ኢየሩሳሌም ሲሄድ መሽቶበት ከማርታ ቤት በእንግድነት አደረና ጠዋት ሊሄድ ሲነሣ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሚሄድ ሲነግራት ‹‹የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተህ አምጣልኝ ዋጋውን ልስጥህ›› አለችው፡፡ እርሱም ‹‹ገንዘቡን ሥዕሉን ሳመጣልሽ ትሰጪኛለሽ›› ብሏት ሄደ፡፡ ኢየሩሳሌምም ደርሶ ቅዱሳት መካናትን ተሳልሞ ሥዕሉን ረስቶ ሳይገዛ ሲመለስ «አደራ ጥብቅ አይደለምን? ያቺ ሴት አደራ ያለችህን ለምን ረሳህ» የሚል ድምፅ ሰማ፡፡ በጣም ደንግጦ ተመልሶ ሄዶ ገዝቶ በረሃ በረሃውን መጓዝ ጀመረ፡፡ በመንገድም እየተጓዘ አንበሳ ሊበላው እየሮጠ ወደ እርሱ ሲመጣበት አየ፡፡ መነኩሴው አንበሳውን ከመፍራት የተነሣ ደነገጠ፣ ተንቀጠቀጠ ደንግጦ ቁሞ ሳለ ያች ሥዕል ከአንበሳው ጩኸት ሰባት እጅ በሚበልጥ አስፈሪ ድምፅ ጩሃ ተናገረች፡፡ ያን ጊዜ አንበሳው ደንግጦ ፈጥኖ ሸሸ፡፡ መነኩሴውም መንገዱን ቀጠለ፡፡ በመንገዱም ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ወጥተው ወንበዴዎች ሊቀሙትና ሊገድሉት ከበቡት፡፡ ከሥዕለ ማርያሟም እንደ መብረቅ ያለ ታላቅ ቃል ወጣ፡፡
ወንበዴዎችም እጅግ ፈርተው ሸሽተው ከጫካው ውስጥ ገቡ፡፡ ያም መነኩሴ እነኚህን የሚያስደንቁ ተአምራት በተመለከተ ጊዜ በልቡ «ለእኔ ረዳት ትሆነኝ ዘንድ ወደ ሀገሬ ይዣት እሄዳለሁ እንጂ ለላከችኝ ሴት አልሰጥም» ብሎ ወደ ሀገሩ ሊሄድ በመርከብ ተሳፈረ፡፡ በባሕር ላይም ሳለ ጽኑ ነፋስ ተነስቶ መርከቡን እየገፋ ማርታ ወዳለችበት ሀገር ወደ ጽዴንያ ዳርቻ አደረሰው፡፡ ማደሪያም ስለሌለው ወደ ደጓ ሴት ወደ ማርታ ቤት ከእንግዶች ጋር አብሮ ገብቶ አደረ፡፡ ሲነጋ ወጥቶ ሊሄድ ከደጃፍ ሲደርስ ደጃፉ ጠፍቶት ከአጥሩ ሲታገል ዋለ፡፡ ማርታም «አባቴ ያመመህ የደከመህ ትመስላለህ ዛሬ ደግሞ እዚህ እደርና ነገ ትሄዳለህ» አለችውና አደረ፡፡ በሁለኛውም ዕለት እንደ መጀመሪያው ቀን በሩን አልፎ መሄድ አቃተውና እዚያው ማርታ ቤት አደረ፡፡ በሦስተኛው ቀን መውጣት ፈልጐ አሁንም ከአጥሩ ጋር ሲታገል አይታ «አባቴ የሆንከው ምንድነው? እነሆ ዛሬ ሦስተኛ ቀንህ ነው» አለችው፡፡
መነኩሴውም «ይህችን ተአምረኛ ሥዕል አልሰጥም ብዬ ነው፡፡ እኔኮ ሥዕል ከኢየሩሳሌም ግዛልኝ ያልሽኝ መነኩሴ ነኝ» ብሎ ሥዕለ ማርያምን አውጥቶ ሰጣት፡፡ እርሷም እጅግ በጣም ተደስታ እግዚአብሔርን አመሰገነች፡፡ በሥዕሏም ፊት ሰግዳ ለእመቤታችን ለድንግል ማርያም ምስጋናን አቀረበች፡፡ ተቀብላም ሥዕል ቤት አሠርታ በክብር አስቀመጠቻት፡፡ ይህችም ሥዕል ቅዱስ ሉቃስ የሳላት ናት፡፡ ሥጋ የለበሰች ትመስላለች፡፡ ከፊቷም ወዝ ይንጠባጠባል፡፡ በዚህችም ሥዕል ብዙ ተአምራት ተደረገ ሕሙማን ተፈወሱ፣ ዐይነ ስውራን ማየት ቻሉ፡፡ በዚያ ዘመን የነበረው ሊቀ ጳጳስ ተአምሯን ሰምቶ ሥዕሏ ወደ ማርታ ቤት የገባችበት ዕለት መስከረም 10 ቀን እንዲከበር ሥርዓት ሠራ፡፡ ይህም በዓል በቤተ ክርስቲያናችን ሁልጊዜ ይከበራል፡፡ የብርሃን እናቱ ድንግል ወላዲተ አምላክ ፍቅሯን ጣዕሟን ታሳድርብን፣ ልጇ አምላካችን በጸሎቷ ይማረን፡፡
+ + + + +
ዳግመኛም የጌታችን ቅዱስ መስቀል አገራችን ኢትዮጵያ ውስጥ የገባው በዚህ ዕለት ነው፡፡ አምላካችን ለበዓሉ በሰላም ካደረሰን መስከረም ዓሥራ ሰባት ቀን በዝርዝር እናየዋለን፡፡ የቅዱስ መስቀሉ ፍቅር ይደርብን!
1 210
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
መስከረም 9-ከቅዱስ ፋሲለደስ ጋር ዐሥራ አራት ሺህ ሰባት መቶ ሰላሳ ሰባት (14737) አማኞች በሰማዕትነት ዐረፉ፡፡
+ ‹‹ተጋድሎውን በዛፍ ላይ ሆኖ የፈጸመ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘ ንጉሥ ያሳይ ዕረፍቱ ነው›› በማለት ስንክሳሩ በስም የገለጸው ጻድቁ ንጉሥ ያሳይ ዐረፈ፡፡
+ አባ ቢሶራ በሰማዕትነት ዐረፈ፡፡
+ ዳግመኛም በዚህች ዕለት የመላእክት ሁሉ አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በሮም አገር ታላቅ ተአምር ያደረገባት ዕለት ናት፡፡
ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በሮም አገር ያደረገው ታላቅ ተአምር፡- ይኸውም በሮም አገር ፍሩምያ በምትባል ከተማ የተደረገ ተአምር ነው፡፡ በዚህች ከተማ ውስጥ የቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ነበረች፡፡ በዚህችም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ገናናው መልአክ ብዙ አስደናቂ ተአምራትን ሲሠራ ኖረ፡፡ በዚህም ምክንያት ዮናናውያን ሰዎች ሰይጣናዊ ቅናት ቀንተው በአካባቢው የሚወርደውን የወንዝ ውኃ አቅጣጫውን መልሰው ቤተ ክርስቲያኗን የሚጠባቃትን መጋቢውንም ጭምር በውኃው ሊያሰጥሟት ተነሡ፡፡ በዚህም ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል ለቤተ ክርስቲያኑ መጋቢ ለናርጢኖስ ተገለጠለትና ‹‹አይዞህ ጽና አትፍራ›› አለው፡፡ ይህንንም ብሎ በእጁ ላይ ባለው በትር ዐለቱን መታው፡፡ ዐለቱም ተሰንጥቆ እንደበር ሆነ፡፡ የዚያ ወንዝ ውኃም በውስጡ አልፎ ሄደ፡፡ ይህንንም ያዩ ሁሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ ገናናውን መልአክ ቅዱስ ሚካኤልንም አከበሩት፡፡ ከዚያች ቀን እስከዛሬ የወንዙ ውኃ በዚያች በተሰነጠቀች ዐለት ውስጥ አልፎ ሲሄድ ያዩታል፣ ወደ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ግን ከቶ አይቀርብም፡፡
የሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ጥበቃ አይለየን፡፡
+++
አባ ቢሶራ፡- ይኸውም አባ ቢሶራ በግብጽ አገር መጺል የምትባል ከተማ ኤጲስ ቆጶስ ሲሆን ዲዮቅልጥያኖስ የክርስቲያኖችን ደም እንደ ውኃ ሲያፈስ አባ ቢሶራም በጌታችን ስም ሰማዕት ይሆን ዘንድ ወደደ፡፡ ሕዝቡን ሁሉ ጠርቶ በሃይማኖት እንዲጸኑ ከመከራቸው በኋላ ወደ ከሃዲዎች ዘንድ ሄዶ የጌታችንን ክብር መስክሮ ለመሞት እንደወሰነ ነገራቸው፡፡ ሕዝቡም ሁሉ ታላቁም ታናሹም እያለቀሱ ‹‹ከእኛ ተለይተህ ወደ ሞት አትሄድም፣ እኛንስ እንደሙት ልጆች ለምን ትተወናለህ?›› እያሉ ለመኑት፡፡ ነገር ግን አባ ቢሶራ ሰማዕትነት ዕጣ ክፍሉ መሆኑን ነግሯቸው በሃይማኖት እስከመጨረሻ እንዲጸኑ ከመከራቸው በኋላ ተሰናብቷቸው ወደ ሰማዕትነት ሄደ፡፡ ሕዝቡም መሪር ልቅሶን እያለቀሱ ሸኙት፡፡ ሌሎች ሦስት ኤጲስ ቆጶሳትም ሰማዕት ይሆኑ ዘንድ ተከትለውት ሄዱ፡፡
አባ ቢሶራ እና ሦስት ኤጲስ ቆጶሳትም የክርስቲያኖችን ደም ያፈስ በነበረው መኮንን ፊቱ ቆመው የጌታችንን አምላክነት መሰከሩ፡፡ መኮንኑም ይዞ ጽኑ ሥቃይ አደረሰባቸው፡፡ ይልቁንም ኤጲስቆጶሳት መሆናቸውን ሲያውቅ ሥቃይን አበዛባቸው፡፡ ነገር ግን ጌታችን እያጸናቸው መከራውን በትዕግስት ተቀበሉ፡፡ በመጨረሻም በዚህች ዕለት አባ ቢሶራና ሦስት ኤጲስ ቆጶሳት (ቢስኮስ፣ ፊናቢክስ እና ቴዎድሮስ) አንገታቸውን ተሰይፈው ሰማዕትነታቸውን በድል ፈጽመዋል፡፡
ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!
+ + +
ዳግመኛም በዚህች ዕለት ከቅዱስ ፋሲለደስ ጋር ዐሥራ አራት ሺህ ሰባት መቶ ሰላሳ ሰባት (14737) አማኞች በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡ (ከሰማዕቱ የዕረፍት ዕለት ጋር መስከረም ዓሥራ አንድን ቀን እንመለከተዋለን፡፡ )
የሰማዕታቱ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣ በጸሎታቸው ይማረን!
1 210
ሙሴ ሰው ከወዳጁ ጋር እንደሚነጋገር ከእግዚአብሐር ጋር 570 ጊዜ ቃል በቃል ተነጋግሯል፡፡ 40 ቀን 40 ሌሊት ከጾመ በኋላ ዓሥሩን ትእዛዛት የተጻፉባቸውን ጽላት ተቀበለ፡፡ እስራኤላውያን ባዩት ጊዜ እንዳይሞቱ ፊቱን እስኪሸፍንላቸው ድረስ ፊቱ እንደ ፀሐይ የሚያበራበት ጊዜም ነበር፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ 120 ዓመት በሆነው ጊዜ እግዚአብሔር ሕዝቡን ለአገልጋዩ ለነዌ ልጅ ለኢያሱ እንዲያስረክበው ስላዘዘው ለኢያሱ አስረክቦታል፡፡ ሙሴም እግዚአብሔር እንዳዘዘው በምስክሩ ድንኳን ውስጥ የሚሠራውን ሁሉ ሠርቶ ካዘጋጀ በኋላ በተራራ ውስጥ ዐረፈ፡፡ በዚያም በመልእክት እጅ በሥውር ተቀበረ፡፡ የእስራኤል ልጆችም ወስደው እንዳያመልኩት እግዚአብሔር የሙሴን ሥጋ ሰወረ፡፡ ሰይጣንም የሙሴን ሥጋ ለእስራኤል ሊገልጥላቸው በወደደ ጊዜ ሐዋርያው ይሁዳ በጻፈው መጽሐፉ ላይ እንደመሰከረ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ገሠጸው፣ ከዚህም ሥራ ከለከለው፡፡ የእስራኤልም ልጆች ለሙሴ 40 ቀን አልቅሰውለታል፡፡ ጌታችን ስለ ሙሴ ሲናገር ከእስራኤል ልጆች ውስጥ እንደ ሙሴ ያለ ደግ የዋህ ቅን ነቢይ እንደማይነሣ መስክሮለታል፡፡
ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን!
+ + +
የመጥምቁ ዮሐንስ አባት የበራክዩ ልጅ ካህኑ ዘካርያስ፡- የበራክዩ ልጅ ካህኑና ነቢዩ ዘካርያስ- ይህም ነቢይ ዘካርያስ በንጉሥ ሄሮድስ እጅ መስከረም 8 ቀን በሰማዕትነት ያረፈ ሲሆን የመጥምቁ ዮሐንስ አባት ነው፡፡ ስለ ልጁ ዮሐንስ መወለድ ቅዱስ ገብርኤል ባበሰረው ጊዜ አምኖ ባለመቀበሉ ልጁ ዮሐንስ እስኪወለድ ድረስ ዲዳ ሆኗል፡፡ ልጁ በተወለደም ጊዜ ‹‹ስሙን ዮሐንስ በሉት›› ብሎ በእጁ ሲጽፍ አንደበቱ ተከፍቶለታል፡፡ እርሱና ሚስቱ በእግዚአብሔር ሕግ ያለነቀፋ የጸኑ ደጎች እንደሆኑ ቅዱስ ወንጌል ይመሰክርላቸዋል፡፡ ‹‹በጌታ ትእዛዝና ሕግጋት ሁሉ ያለ ነቀፋ እየሄዱ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ነበሩ›› ተብሎ ነው በወንጌል ጽድቃቸው የተነገረላቸው፡፡ ሉቃ 1፡5-6፡፡
ንጉሥ ሄሮድስ ጌታችንን የሚያገኝ መስሎት 144 ሺህ ቤቴልሔም ሕፃናትን በግፍ ሲጨፈጭፍ እመቤታችን ልጇን ጌታችንን ይዛ ወደ ግብጽ ስትሰደድ ዮሐንስንም እናቱ ቅድስት አልሳቤጥ ይዛው ወደ ሲና በረሃ ገባች፡፡ ኤልሳቤጥ ከመሄዷ በፊት ግን ከባሏ ከዘካርያስ ጋር ሲሰነባበቱ የሚሆነውንም ሁሉ እርሱ ቀድሞ ያውቅ ነበርና ‹‹ሕፃኑን ልጄን ሲያጡ እኔን ይገድሉኛል፣ አንቺ ግን ወደ በረሃው ይዘሽው ሂጂና በዚያ ሸሽጊው›› ብሎ መክሯታል፡፡ ኤልሳቤጥም ከሄደች በኋላ የርጉም ሄሮድስ ጭፍሮች ዮሐንስን ባጡት ጊዜ ወደ ዘካርያስ መጥተው ‹‹ልጅህን ወዴት አድርሰኸው ነው? ወዴትስ ደበቅኸው? አሁን ከደበቅህበት አምጥተህ ፈጥነህ አስረክበን›› በማለት የፍጥኝ አስረው አሠቃዩት፡፡ ሄሮድስም ዘካርያስ ዘንድ ሄዶ ሕፃኑን ልጅ ዮሐንስን ካልሰጠው እንደሚገድለው ነገረው፡፡ ካህኑ ዘካርያስም የንጉሡን ዛቻ ባለመፍራት አገልግሎቱን ቀጠለ፡፡ በመጨረሻም ንጉሡም ወታደሮቹን ልኮ በቤተ መቅደሱና በመሠዊያው መካከል አስገደለው፡፡
ነገር ግን እግዚአብሔር የቅዱስ ዘካርያስን ሥጋውን ሰወረው፣ ደሙ ግን እንደ ድንጋይ ሆነች፡፡ ሕዝቡም እንደ ልማዳቸው ለጸሎት በመጡ ጊዜ ከካህናት አንዱ ወደ ቤተ መቅደስ ሲገባ የረጋ የዘካርያስን ደም አገኘ፡፡ ከመሠዊያውም እንዲህ የሚል ድምፅ ተሰማ፡- ‹‹እነሆ የበራክዩ ልጅ ዘካርያስ ተገደለ፣ የሚበቀልም እስኪመጣ ድረስ ደሙ ስትጮህ ትኖራለች›› የሚል ድምፅ ተሰማ፡፡ ይህንንም አንዳንዶች በማሳሳት ከ12ቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ስለሆነው ስለ በራክዩ ልጅ ነቢዩ ዘካርያስ የተነገረ ነው ይላሉ ግን አይደለም፡፡ ከ12ቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ የሆነው የበራክዩ ልጅ ነቢዩ ዘካርያስ የእርጅና ዘመኑ ደርሶ ኡረት በሚባል አገር ሞተ፡፡ ሥጋውም ያለጥፋት በዚያ ተገኝቶ ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለታል፡፡
የዚህኛው የካህኑና የመጥምቁ አባት ዘካርያስ ግን ሥጋው አልተገኘም፡፡ ስለመገደሉ የደሙ ድምፅ ምስክር ሆነ እንጂ፡፡ ጌታችንም ለተረገሙ አይሁድ ስለእርሱ ሲናገር ‹‹የገደላችሁት የዘካርያስ ደም በላያችሁ ይደርሳል›› ብሏቸዋል፡፡ የዘካርያስም ደም እስከ ሰባት ዓመት ድረስ እየፈላ ደሙ ሲካሰሳቸው ከኖረ ገዥው ጥጦስ ገዳዮቹን በሰይፍ ሲገድላቸው ደሙ መፍላቱን አቁሟል፡፡ ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን!
1 210
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
መስከረም 8-ግብጻዊው ዕብራዊውን ሲገድለው አይቶት ለወገኑ ተበቅሎ ግብጻዊውን ገድሎ ወደ ምድያም አገር ማለትም ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ የካህኑን የዮቶርን ልጅ አግብቶ ሁለት ልጆችን ወለዶ በኢትዮጵያ 40 ዓመት ከኖረ በኃላ የዮቶርን በጎች እየተበቀ ሳለ እግዚአብሔር በቁጥቋጦ ውስጥ በታላቅ ራእይ ተገልጦለት እስራኤልን ከግብጽ እንዲያወጣ ነግሮት ሄዶ በ10 መቅሰፍታት እስራኤላውያንን ነጻ ያወጣቸው ሊቀ ነቢያት ሙሴ ዕረፍቱ ነው፡፡
+ የመጥምቁ ዮሐንስ አባት የበራክዩ ልጅ ካህኑ ዘካርያስ በሰማዕትነት ዐረፈ፡፡
+ ከሃዲው መኮንን በእጅጉ ካሠቃየው በኋላ አንገቱን በሰይፍ የሰየፈው ሰማዕቱ ቅዱስ ሉክዮስ ዕረፍቱ መሆኑን ስንክሳሩ በስም ይጠቅሰዋል፡፡
+ ሰማዕቱ ቅዱስ ዲማድዮስ ዕረፍቱ ነው፡፡
+ ምግቡ የአጋዘን ወተት የሆነ በዕረፍቱም ጊዜ ብዙ ተአምራትን ያደረገ የከበረ ገዳማዊ ቂርቆስ ዕረፍቱ መሆኑን ስንክሳሩ በስም ይጠቅሰዋል፡፡
ሰማዕቱ ቅዱስ ዲማድዮስ፡- ይኸውም በሃይማኖትና በምግባር ያጌጠ ስለነበር ጌታችን ተገልጦለት ሄዶ በስሙ ሰማዕት ይሆን ዘንድ አዘዘው፡፡ ከደቡባዊ ግብጽ ተነሥቶ እናት አባቱን ትቶ ወጥቶ ወደ አትሪብ በመሄድ በከሃዲው መኮንን ፊት ስለ ጌታችን መሰከረ፡፡ ከሃዲውም ገዥ ጽኑ ሥቃይ ካደረሰበት በኋላ ወደ እስክንድርያ ላከው፡፡ የእስክንድርያም መኮንን ሉክያኖስ በተራው አሠቃየው፡፡ ነገር ግን ጌታችን ዲማድዮስ ተገልጦለት አረጋጋው፡፡ በኋላም መኮንኑ ዲማድዮስን ማሠቃየት በሰለቸው ጊዜ ራሱን በሰይፍ አስቆረጠውና የሰማዕትነቱ ፍጻሜ ሆነ፡፡ረድኤት በረከቱ ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን!
+ + +
ሊቀ ነቢያት ሙሴ፡- የፈርዖን ሴት ልጅ ‹‹ከውኃ አውጥቼዋለሁና›› ስትል ሕፃኑን ሙሴ ብላ ጠርታዋለች፡፡ ዘጸ 2፡10፡፡ እስራኤላውን በግብፅ ባርነት እየተገዙ ባለበት ወቅት ፈርዖን እስራኤላውያን ወንድ ልጅ ሲወልዱ እንዲገደል በአዋጅ አስነገረ፡፡ የሙሴም እናት ልጇ በፈርዖን ትእዛዝ መሠረት እንዳይገደልባት ስለ ፈርዖን ትእዛዝ ፍራቻ ልጇን በቅርጫት አድርጋ ወንዝ ውስጥ ጣለችው፡፡ ተርሙት የምትባለው የፈርዖን ሴት ልጅ በወንዝ ገላዋን ልትታጠብ ወርዳ ሳለ በዚያ ቅርጫት አግኝታ ብትከፍተው የሚያሳሳ ውብ ልጅ አገኘት፡፡ ‹‹ይህንንስ አሳድገዋለሁ›› ብላ ወደ ቤቷ ወሰደችውና ሙሴ በንጉሡ በፈርዖን ቤት አደገ፡፡ የሙሴም እናት ተንከባካቢ ሞግዚቱ ሆና ተጥሎ የተገኘውን ልጇን እንድታሳድግ ከፈርዖን ሴት ልጅ ጋር በድብቅ ተስማምታ በንጉሡ ቤት ገባች፡፡ እናቱም ልጇን ሙሴ የፈርዖን ልጅ እንዳይባል ሃይማኖቱን፣ ማንነቱን፣ ታሪኩን፣ ባሕሉን ጠንቅቃ እያስተማረች አሳደገችው፡፡
ሙሴ 40 ዓመት በሆነው ጊዜ አንዱ ግብፃዊ ዕብራዊውን ሲገድለው አይቶት ለወገኑ ተበቅሎ ግብፃዊውን ገደለው፡፡ በማግስቱ ደግሞ ሁለት ዕብራውያን እርስ በእርሳቸው ሲጣሉ አያቸው፡፡ ሊያስታርቃቸው ፈልጎ ወደ እነርሱ ጠጋ ቢል አንደኛው ዐመፀኛ ዕብራዊ ‹‹ትናንት ግብፃዊውን እንደገደልከው ልትገድለን ትሻለህን?›› አለው፡፡ ሙሴም ‹‹በድብቅ አደረኩት ያልኩት ለካ ታውቆብኛል›› ብሎ ፈርዖንን ፈርቶ ወደ ምድያም አገር ሸሽቶ ሄደ፡፡ የምድያም አገር ካህን የሆነውን የዮቶርን (በሌላ ስሙ ራጉኤል ይባላል) ሴት ልጁን ሲፓራን አግብቶ 40 ዓመት በምድያም ተቀምጦ ሁለት ልጆችንም ወለደ፡፡ ይህችውም ምድያም የተባለች አገር ቅድስት ኢትዮጵያ ናት፡፡ የዚህም ምስክሩ መጽሐፍ ቅዱስ ነው፡፡ ዘጸ 2፡1-25፣ ኦሪት ዘኁልቅ 12፡1-12፡፡ ሕዝበ እስራኤል ከግብፅ ሳይወጡ በኋለኛውም ዘመን ጌታችን ከመወለዱም ከብዙ ዘመን በፊት በቅድስት አገር ኢትዮጵያ ውስጥ እግዚአብሔርን የሚያገለግል ካህን እንደነበረ መጽሐፍ ቅዱስ የሚመሰክረው ሐቅ ነው፡፡
ሙሴ በምድያም አገር ማለትም በኢትዮጵያ በዱር ሆኖ የኢትዮጵያዊውን ካሁን የዮቶርን በጎች እየጠበቀ ሳለ በቁጥቋጦ ውስጥ ታላቅ ራእይ አየ፡፡ ነበልባል ከሐመልማል ጋር ሐመልማልም ከነበልባል ጋር ተዋሕዶ ነበልባሉ ሐመልማሉን ሳያቃጥለው፣ ሐመልማሉም ነበልባሉን ሳያጠፋው ተመልክቷል፡፡ ይህንንም ምሥጢር ለመረዳት ጠጋ ሲል ከቁጥቋጦው ውስጥ እግዚአብሔር ድምፅ አውጥቶ ጠራው፡፡ የቆመባት ስፍራ የተቀደሰች ስለሆነች ጫማውንም ከእግሩ እንዲያወልቅ ነገረው፡፡ ዘጸ 3፡5፣ ሐዋ 7፡30-34፡፡ ለጊዜው ሐመልማል የእስራኤል፣ ነበልባሉ ደግሞ የመከራቸው ምሳሌ ነው፡፡ ሐመልማሉ ነበልባሉን ያለመጥፋቱ እስራኤልም መከራውን ግብር ገብተን ቀኖና ይዘን እናርቀው ያለማለታቸው ምሳሌ ሲሆን ነበልባሉ ሐመልማሉን ሳያቃጥል ማየቱ የግብጽ መከራ እስራኤልን ጨርሶ ያለማጥፋቱ ምሳሌ ነው፡፡ ፍጻሜው ግን ሙሴ ያየው የነበልባልና የሐመልማል ተዋሕዶ የመለኮትና የትስብእት ተዋሕዶ ምሳሌ ነው፡፡ ነበልባሉ ሐመልማሉን እንዳላቃጠለው ሁሉ ሐመልማሉም ነበልባሉን እንዳላጠፋው ሁሉ መለኮት ምልአቱን ስፋቱን ርቀቱን ሳይተው ሥጋም ግዙፍነቱን ሳይተው የመዋሐዳቸው አንድ አካል አንድ ባሕርይ የመሆናቸው ምሳሌ ነው፡፡
እንዲሁም ነበልባሉ የጌታችን ምሳሌ ሲሆን ሐመልማሉ ደግሞ የእመቤታችን ምሳሌ ነው፡፡ ይኸውም ነበልባሉ ሐመልማሉን እንዳላቃጠለው ሁሉ እሳተ መለኮት ጌታችንም 9 ወር ከ5 ቀን በማኅፀኗ ባደረ ጊዜ እመቤታችንን ባሕርየ መለኮቱ አላቃጠላትም፤ ሐመልማሉም ነበልባሉን እንዳላጠፋው ሁሉ ጌታችንም ከእመቤታችን ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ ሰው ቢሆንም ባሕርየ መለኮቱ አልተለወጠም፡፡ ይህንንም ቅዱስ ኤፍሬም በሐሙስ ምስጋናው ላይ እንዲህ ሲል ገልጾታል፡- ‹‹መለወጥ የሌለባት ድንግል ማርያም ሙሴ በበረሐ በነደ እሳት ጫፎቿ ሳይቃጠሉ ያያት ዕፅን ትመስላለች፣ የአብ ቃል በእርሷ ሰው ሆኗልና እሳተ መለኮቱ አላቃጠላትምና፤ ከወለደችው በኋላ ድንግልንናዋ አልተለወጠምና፤ ሰውም ቢሆን መለኮቱ አልተለወጠም በእውነት አምላክ ነውና፣ በእውነት አምላክ የሆነ እርሱ መጥቶ አዳነን፡፡››
የደማስቆው ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹ዕፀ ጳጦስ የአምላክ እናት አምሳል ነበረች፤ ሙሴ ወደ እርሷ በተጠጋ ጊዜ እግዚአብሔር ‹አንተ የቆምክባት ስፍራ የተቀደሰች መሬት ናትና ጫማህን ከእግርህ አውልቅ› አለው፡፡ እንግዲህ ሙሴ የወላዲተ አምላክን ምሳሌ ያየባት መሬት የተቀደሰች ከሆነች ምሳሌዋ ራሷ ምን ያህል የተቀደሰች ትሆን? እርሷ ቅድስት ብቻ ሳትሆን ቅድስተ ቅዱሳን ናት›› በማለት ስለ እመቤታችን አስተምሯል፡፡
ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር ሙሴን ሕዝበ እስራኤልን ከግብፅ ባርነት እንዲያወጣቸው ላከው፡፡ ሙሴም ወደ ግብፅ አገር ሄዶ 10 የተለያዩ መቅሰፍቶች አመጣ፡፡ መጀመሪያ ውኃውን ወደ ደምንት ለወጠው፡፡ 10ኛው የበኩር ልጆቻቸው ሞቱ፡፡ በተአምራቱም ሕዝቡን ይዞ ከግብፅ ወጣ፡፡ የኤርትራን ባሕር በበትሩ ለሁለት ከፍሎ አሻገራቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ሕዝበ እስራኤልን በምድረ በዳ 40 ዓመት ሙሉ መና ከሰማይ እያወረደ መገባቸው፣ ከአለትም ላይ ውኃ እያፈለቀ አጠጣቸው፡፡ እራኤል ግን እጅግ ክፉዎች ነበሩና በክፋ ይነሱበት ነበር፡፡ በድንጋይ ሊወግሩት ያሉበት ጊዜም ነበር፡፡ እርሱ ግን ፍጹም በመታገስ በኃጢአታቸው እንዳይሞቱ ወደ እግዚአብሔር ይማልድላቸው ነበር፡፡
1 210
ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም፡፡በጣም ብዙ ድርሳናትን ደርሰዋል፡፡100 ዓመት በሆናቸው ጊዜ የታዘዘ መልአክ መጥቶ ከ10 ቀን በኋላ በሞት እንደሚያርፉ ነገራቸው፡፡ ሕዝቡንም ጠርተው በሃይማኖት እንዲጸኑ ከመከሯቸውና
ከተሰናበቷቸው በኋላ መስከረም 7 ቀን በሰላም ዐርፈዋል፡፡ይኸውም ዕረፍታቸው የተከናወነው ኤጲፋንዮስ ባረፈ በ2ኛ ዓመቱ ዮሐንስ አፈወርቅ ባረፈ በዓመቱ ነው፡፡ጌታችን የብርሃን ሰረገላ ሰጥቷቸዋል፡፡ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣በጸሎታቸው ይማረን፡፡
+ + + + + + + + + + + + + + +
ሰማዕታቱ ቅድስት ራፊቃ እና አራት ልጆቿ፡- ለቅድስት ራፊቃ እና ለአራት ልጆቿ ማለትም ለአጋቶን፣ ለጴጥሮስ፣ ለዮሐንስና ለአሞን ጌታችን ለሁሉም በራእይ ተገልጦላቸው በስሙ መስክረው ሰማዕት እንሚሆኑ ነገራቸው፡፡አስቀድሞም
ታላቁ አጋቶን በአገሩ ተሹሞ በሥልጣን ሆኖ ነበር። የጌታችንንም የሰማዕትነት ጥሪ ተቀብለው ከላይኛው ግብጽ ከቁስ አውራጃ ተነሥተው በከሃዲው መኮንን በዲዮናስዮስ ፊት ስለ ጌታችን አምላክነት መሰከሩ፡፡መኮንኑም ብዙ ሥቃዮችን አደረሰባቸው፡፡ጌታችንም በተአምራት ከመከራቸው ሲያድናቸው ያየ ብዙ ሰዎች ሲያምኑ መኮንኑ እጅግ ተቆጥቶ ጽኑ ሥቃይ አደረሰባቸው፡፡ማሠቃየትም
በሰለቸው ጊዜ ወደ እስክንድርያው ገዥ አርማንዮስ ዘንድ ላካቸው፡፡ከሃዲው አርማንዮስም ሥጋቸውን ቆራርጦ በመንኮራኩር ውስጥ ጨመራቸው፡፡ነገር ግን ጌታችን ጤነኛ አድርጎ ፈወሳቸው፡፡ዳግመኛም ዘቅዝቀውም ሰቀሏቸው፡፡
አሁንም ጌታችን አዳናቸው፡፡በተአምራተቸውም ብዙዎች በጌታችን አመኑ፡፡በመጨረሻም ራሶቻቸውንም በሰይፍ ቆርጠው ሥጋቸውን ወደ ባሕር ጣሉት፡፡ቅድስት ራፊቃና
አራት ልጆቿም ሰማዕትነታቸውን በዚሁ ፈጸሙ፡፡የታዘዘ መልአክም መጥቶ ለአንዱ ባለጸጋ የቅዱሳኑን ሥጋ ያለበትን ነግሮት እንዲያወጣውና በክብር እንዲያስቀምጠው አዘዘው፡፡ባለጸጋውም የቅዱሳኑን ሥጋቸውን ከባሕሩ
አወጥቶ የመከራ ዘመን እስኪያልፍ በክብር አኖረው፡፡ ከሥጋቸውም ብዙ ተአምራት ተገልጠው ታዩ፡፡ የሰማዕታቱ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፣በጸሎታቸው ይማረን፡፡
+ + + + + + + + + + + + + + +
+ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት እመቤታችን ድንግል ማርያም ወላዲተ አምላክን የወለደቻት ቅድስት ሐና ልደቷ ነው፡፡ሐና ማለት ‹‹ጸጋ›› ማለት ነው፡፡አምላክን የወለደች የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም እናት ናት፡፡እርሷም ከኢየሩሳሌም አገር ከሌዊ ነገድ ከካህኑ አሮን ትውልድ የሌዊ የሜልኪ ልጅ
ለሆነ ለማጣት ልጁ ናት፡፡የቅድስት ሐና አባት ማጣትና እናቷ ሄርሜላ ከእርሷ በተጨማሪ ሶፍያና ማርያም የሚባሉ ሌሎች ሁለት ሴት ልጆችን ወልደዋል፡፡ቅድስት ሐና ከይሁዳ ነገድ የሆነውን ጻድቅ ኢያቄምን አግብታ ቅድስት ድንግል ማርያምን ወለደች፣ ድንግል ማርያምም መድኃኔዓለም ክርስቶስን ወለደች፡፡ሶፍያ ኤልሳቤጥን ወለደች፣ ኤልሳቤጥም መጥምቁ ዮሐንስን ወለደች፡፡ከሦስቱም ታናሽ የሆነችው ‹‹ማርያም›› የተባለችው የማጣትና የሄርሜላ ልጅ
ደግሞ ሰሎሜን ወለደቻት፡፡ይኽችም ታላቅ እናት ቅድስት ሐና አምላክን በድንግልና ሆና በሥጋ ለወለደችው ለቅድስት ድንግል ማርያም ወላጇ ትሆን ዘንድ የተገባት ሆናለችና ከሴቶች ሁሉ እንደምትበልጥና እንደምትከብር እንረዳ፡፡ ለዓለም ሁሉ ድኅነት የተደረገባትን ልዩ ስጦታ የሆነች ድንግል ማርያምን እርሷ አስገኘቻት፡፡ለክብር ባለቤት ለጌታችን ለአምላችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ አያቱ ሆናለችና ምን ያህል ክብርት እንደሆነችና እግዚአብሔር የመረጣት ንጽሕት ቅድስት እንደሆነች በዚህ ይታወቃል፡፡
ረድኤት በረከቷ ይደርብን፣ በጸሎቷ ይማረን፡፡
1 210
አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አሜን
መስከረም 7-የብርሃን እናቱ የሆነች ድንግል ወላዲተ አምላክን የወለደቻት ቅድስት ሐና ልደቷ ነው፡፡
+ በ451 ዓ.ም በጉባዔ ኬልቄዶን ላይ ተገኝቶ ልዮንን የረታውና ያወገዘው ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ በዓለ ልደቱና ዕረፍቱ ነው፡፡
+ በአካል መሄድ ሳያስፈልጋቸው ደብዳቤ በመጻፍ ብቻ በንጉሡ ልጅ ላይ ያደረውን ሰይጣን ያስወጡትና በሀገርም ላይ የመጣውን የጠላትን ጦር በመርታት ድል ያደርጉ የነበሩት አቡነ ሳዊርያኖስ ዕረፍታቸው ነው፡፡
+ ቅድስት ራፊቃ እና 4 ልጆቿ ቁልቁል ተሰቅለውና አንገታቸውን በመሰየፍ ሰማዕትነታቸውን በድል ፈጸሙ፡፡
+ ዳግመኛም በዚኽች ዕለት ከቅዱስ ፋሲለደስ ጋር ማኅበርተኞቹ የሆኑ ሁለት ሺህ ሰባት ሰዎችም በሰማዕትነት ዐርፈዋል፡፡
+ የመጥምቁ ዮሐንስ እናት የቅድስት ኤልሳቤጥም የመታሰቢያዋ በዓል ነው፡፡ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፣
በጸሎቷ ይማረን፡፡
+ + + + + + + + + + + + + + +
ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ፡- ቅዱስ ዲዮስቆሮስ ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት 25ኛው ነው፡፡ስለ ቀናች ሃይማኖት ታላቅ ተጋድሎን ከፈጸመ በኋላ በተሰደደበት በደሴተ ጋግራ መስክረም 7 ቀን ዐርፏል፡፡ንጉሡ መርቅያኖስ በጠራው ጉባዔ በጠሩት ጊዜ በቦታው ሲገኝ 636 ጉባኤተኞች ተሰብስበው ደረሰ፡፡‹‹ምን ጉድለት ተገኝቶ ነው ይህ ሁሉ የተጠራው?›› ሲላቸው ‹‹በንጉሡ ትእዛዝ ተጠርተን ነው››
አሉት፡፡ቅዱስ ዲዮስቆሮስም ‹‹ይህ ጉባኤ ስለ ጌታችን ክብር ቢሆን ኖሮ እኔ ተቀምጨ እግዚአብሔር በሰጠኝ በአንደበቴ እናገር ነበር ነገር ግን የጉኤው መሰብሰብ በንጉሡ ትእዛዝ ከሆነ ንጉሡ እንዳሻው ይምራው›› አላቸው፡፡ከዚህም በኋላ የክርስቶስን ባሕርይ ለሁለት የሚከፍለው የክህደትን ቃል በውስጡ የያዘውን የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ልዮን የላከውን ደብዳቤ ቀደደው፡፡ለጉባኤውም ርትእት የሆነች ሃይማኖትን ገለጸ፡፡የተዋሕዶንም ምሥጢር በነፍስና በሥጋ እንዲሁም በእሳትና ብረት እየመሰለ አስዳ፡፡ጌታችን ሰው እንደመሆኑ ወደ ሠርግ ቤት ተጠርቶ ሄደ፣ አምላክ እንደመሆኑ ውኃውን ለውጦ ወይን አደረገው›› እያለም በብዙ ምሳሌዎች ሲያስረዳቸው ከጉባኤው ሊከራከረው የደፈረ ማንም አልነበረው፡፡ነገር ግን ክፉዎች ጉባኤውን በከሃዲው በልዮን ምክር ወዳዘጋጀው ንጉሡ መርቅያንና ወደ ሚስቱ ንግሥት ብርክያል መልዕክት ልከው ከዲዮስቆሮስ በቀር እነርሱ ያዘዙትን ሃይማኖትንና ትእዛዝ የሚቃወም እንደሌለ በመናገር ነገር ሠሩበት፡፡ነገር ግን በጉባኤው ውስጥ ንስጥሮስን ያወገዙ አባቶችም ነበሩበት፡፡ንጉሡም ቅዱስ ዲዮስቆሮስን አስጠርቶት ከሌሎች ሊቃነ ጳጳሳት ጋር እስከ ማታ ድረስ ሲከራከሩ ዋሉ፡፡ቅዱስ ዲዮስቆሮስ እንዳልተመለሰላቸው ባዩ ጊዜ ንግሥቲቷና ንጉሡ በእርሱ ተቆጥተው ክፉኛ አስደበደቡት፡፡ጽሕሙን ነጭተው ጥርሱንም አስወለቁት፡፡ ቅዱስ ዲዮስቆሮስም የተነጨ ጽሕሙንና የወለቀ ጥርሱን ሰብስቦ ወደ እስክንድርያ በመላክ ‹‹እነሆ የቀናች ሃይማኖት ፍሬ ይህ ነው›› አላቸው፡፡ለጉበኤው የተሰበሰቡ ኤጲስ ቆጶሳትም በቅዱስ ዲዮስቆሮስ ላይ የደረሰውን ዐይተው ፈሩና ከከሃዲው ንጉሥ መርቅያኖስ ጋር ተስማሙ፡፡ክብር ይግባውና ‹‹ለክርስቶስ ሁለት የተለያዩ ባሕርያት አሉት›› ብለው በንጉሡ መዝገብ ላይ በእጆቻቸው ጽፈው ፈረሙ፡፡ቅዱስ ዲዮስቆሮስም እነርሱ የጻፉለትን መዝገብ እንዲልኩለት ሲጠይቃቸው ላኩለት እርሱም ጽፎ የሚፈርምበት መስሎአቸው ነበርና፡፡እርሱ ግን አባቶቻችን ሐዋርያት ካስተማሯት ከቀናች ሃይማኖት በኒቅያ የተሰበሰቡ ሃይማኖታቸው የቀና የ318 ኤጲስ ቆጶሳት አባቶቻችን ከሠሯት ሕግ የሚወጣውን ሁሉ በደብዳቤው ግርጌ ጽፎ አወገዘ፡፡መና*ፍቁ ንጉሥም ይህን ጊዜ እጅግ ተናዶ ጋግራ ወደምትባል ደሴት እንዲያግዙት አዘዘ፡፡የሀገረ ቃው ኤጲስ ቆጶስ አባ መቃርስ አብሮት ተሰደደ፡፡ሌሎቹ ግን ሸሹ። ከዚህም በኋላ እነዚያ የካዱ 636 ኤጲስ ቆጶሳት ተቀምጠው በኬልቄዶን ለራሳቸው መመሪያ የሚሆናቸውን ሥርዓት ሠሩ፡፡በጋግራ ደሴት ያለው ኤጲስ ቆጶስም ከንጉሡ ጋር የተባበረ ነበርና አቡነ ዲዮስቆሮስ ላይ ብዙ መከራ አደረሰበት፡፡የደሴቱ ሰዎች ግን በቅዱስ ዲዮስቆሮስ እጅ የሚፈጸሙ ተአምራትን
እያዩ እጅግ ያከብሩት ነበር፡፡ከዚህም በኋላ ቅዱስ ዲዮስቆሮስ አባ መቃርስን ወደ እስክንድርያ ሄዶ ሰማዕት እንደሚሆን ትንቢት ነገረውና ከነጋዴዎች ጋር ላከው፡፡እንደተናገረውም አባ መቃርስ በእስክንደርያ ሰማዕት ሆኖ ዐረፈ፡፡አቡነ ዲዮስቆሮስ ግን በዚያቹ በጋግራ ደሴት ሰማዕትነቱን ፈጽሞ በክብር ዐርፏል፡፡ምእመናንም ሥጋውን በዚያው አኖሩት፡፡የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ረድኤት በረከቱ
ይደርብን፣ በጸሎቱ ይማረን፡፡
+ + + + + + + + + + + + + + +
አቡነ ሳዊርያኖስ፡- የግሪክ አቴናን ፍልስፍናና ጥበብ ጠንቅቀው የተማሩ ናቸው፡፡ምግባር ሃይማኖታቸው የሰመረ፣ ትሩፋት ተጋድሏቸው የቀና ነው፡፡ብሉይን ከሐዲስም አጠናቀው ተምረዋል፡፡ወላጆቻቸው ያወረሷቸውን እጅግ የተትረፈረፈ ንብረት ሸጠውና ለጦም አዳሪዎች መጽውተው ለድኆች ማደሪያና ለእንግዶች ማሪፊያ ቤት ሠርተው ነዳያንን ይንከባከቡ ጀመር፡፡ይህንንም የጽድቅ ሥራቸውን የሮሜው ጻድቁ ንጉሥ አኖሬዎስ ሲሰማ እጅግ ደስ ተደስቶ አስመጥቶ ከእርሱ ጋር በቤተ መንግሥቱ አማካሪና አባቱ አድርጎ አኖራቸው፡፡ከንጉሡም ጋር አብረው ሁልጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ሌሊቱን በሙሉ ለጸሎት ቆመው ያድራሉ፡ጻድቁ የገብላው አገር ንጉሥ ሴት ልጁን ሰይጣን ይዟት ሳለ ደብዳቤ በመጻፍ ልከው በልጅቷ ላይ ያደረውን ሰይጣን በደብዳቤአቸው ብቻ አስወጥተውታል፡፡አቡነ ሳዊርያኖስ ደብዳቤ በመጻፍ ብቻ በሀገር ላይ የመጣ የጠላትንም ጦር
እያሸበሩ ድል ያደርጉ ነበር፡፡ይኸውም የቍስጥንጥንያው ንጉሥ አርቃዴዎስና አኖርዮስ በገብላ አገር ኤጲስቆጶስነት ከሾሟቸው በኋላ የፋርስ ሰዎች እነዚህን ደጋግ ነገሥታት ሊወጓቸው ሽተው በኃይል በመጡባቸው ጊዜ ወደ አባ
ሳዊርያኖስ መልአክትን ላኩ፡፡አባታችንም ለቅዱሳን ነገሥታቱ ‹‹እኛ የክርስቶስ ከሆንን መንግሥታችንም የክርስቶስ ነው፣ እንዲህም ከሆነ የጦር መሣርያ የጦር ሠራዊትም አንሻም…››ብለው ደብዳቤ ጽፈው እንደላኩ ነገሥታቱ ያለ ምንም ጦርነት የፋርስን ሀገር ሰዎች አሸንፈው ወደ ሀገራቸው መልሰዋቸዋል፡፡አቡነ ሳዊርያኖስ በገብላ አገር ኤጲስቆጶስነት ከተሾሙ በኋላ የሙሴን ሕግ በማወቁ የሚመካ አንድ ስሙ ስቅጣር የሚባል አይሁዳዊ ወደ እርሳቸው መጥቶ ተከራከራቸው፡፡የጻድቁንም ቃላቸውን ሊሰማቸው አልቻለም ነበር፡፡በዚህም ጊዜ ጌታችን ለአቡነ ሳዊርያኖስ ተለጠላቸውና ‹‹እኔ ካከበርኳቸው ወገኖች ይሆናል›› በማለት እንደሚያምን ነገራቸው፡፡ያም አይሁዳዊ ወደቤቱ በገባ ጊዜ ወገኖቹ አይሁድ ሲኦል ውስጥ ሆነው ሲሠቃዩ በራእይ ተመለከተ፡፡‹‹ከሃዲዎች ዘመዶችህን እነሆ እይ›› የሚል ድምንም ሰማ፡፡በማግሥቱም ይህ አይሁዳዊ ወደ አቡነ ሳዊርያኖስ መጥቶ ከእግራቸው ሥር ወድቆ እንዲያስተምሩትና የክርስቶስ ወገን እንዲያደርጉት ለመናቸው፡፡እርሳቸውም አስተምረው ከሀገሩ ሰዎች ጋር አንድ ላይ አጠመቋቸው፡፡የቀሩት ብዙ አይሁድም በጌታችን አምነው ተጠመቁ፡፡አቡነ ሳዊርያኖስ ሥራየኛ ጠንቋዮችን ሁሉ እያሳመኑ አስተምረው አስጠምቀዋቸዋል፡፡አቡነ ሳዊርያኖስ ስለ ዮሐንስ አፈወርቅ ስደትና እንግልት ያለችበት ድረስ ሄደው ንግሥት አውዶክስያን ቢመክሯትና ቢገሥጹዋትም በክፋቷ ጸንታ አልሰማቸው ብትል ተመልሰው ወደ አገራቸው ሄደዋል፡፡አቡነ ሳዊርያኖስ ተአምራታቸው
