ru
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

Открыть в Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

Больше
636
Подписчики
Нет данных24 часа
-47 дней
-1230 день
Архив постов
መስከረም 29 ✝️

🌹 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹         🌹 #መስከረም ፳፱ (29) ቀን። 🌹 እንኳን #ለታላቋ_ሰማዕት_ለቅድስት_አርሴማ #ለእመቤቷ_አጋታና_ለደናግል_ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል፣ ለሐዋርያው ለነባቤ መለኮት ለቅዱስ ዮሐንስ ለፈለሰበተ ሥጋው  መታሰቢያ  በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #ከጌታችንና_መድኃኒታችን_ከኢየሱስ_ክርስቶስ #ከእመቤታችን_ከቅድስት_ድንግል_ማርያም በሥጋ #ከተወለደበት_ከልደቱ_ከበዓለ ወልደ ከወራዊ መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                          ✝ ✝ ✝ 🌹 #ታላቋ_ሰማዕት_ቅድስት_አርሴማ እና #እመምኔቷ_ቅድስት_አጋታና_ደናግል፦ ይህም እንዲህ ነው በከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን እርሱ መልኳ ውብ የሆነ ብላቴና ድንግል ሊአገባ ሽቶ በየሀገሩ ሁሉ ሒደው መርጠው ያመጡለት ዘንድ አሽከሮቹን አዘዘ። ይችንም የሚመስላት የሌለ ቅድስት አርሴማን በሮሜ አገር በአንድ የደናግል ገዳም ውስጥ አገኙዋት። ሥዕሏንም ሥለው ለንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ላኩለት ንጉሡም ሥዕሏን በአየ ጊዜ እጅግ ደስ አለውና ለሠርግ እንዲመጡ ወደ መኳንንቱ ላከ። 🌹 እሊያ ደናግልም ይህን ነገር በአወቁ ጊዜ ይረዳቸው ዘንድ ድንግልናቸውንም ይጠብቅ ዘንድ አልቅሰው ወደ እግዚአብሔር ለመኑ። ከዚህም በኋላ ተነሥተው በሥውር ሸሹ የንጉሥ ድርጣድስ ግዛት ወደ ሆነ ወደ አርማንያ ሀገርም ደርሰው በአንድ ቦታ ተቀመጡ ከእርሳቸውም ጋር የተሰደዱ ቁጥራቸው ሰባ አምስት የሆነ ወንዶች፣ ሴቶችም ሠላሳ ዘጠኝ የሆኑ ከእርሳቸው ጋራ አሉ። ምግባቸውን አያገኙም ነበርና በታላቅ ችግር ውስጥ ኖሩ ከእነርሱም መብራት የምትሠራ አንዲት ሴት ነበረች ከእርሷም የእጅ ሥራ ከሚገኘው በየጥቂቱ ይመገባሉ። 🌹 ንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም የከበረች አርሴማን በፈለጋት ጊዜ አላገኛትም ግን በአርማንያ አገር እንዳለች ስለርሷ ሰማ። ደግሞ ለአርማንያ ንጉሥ ለድርጣድስ ስለርሷ ከዲዮቅልጥያኖስ ሸሽታ እንደ መጣች የአርሴማን ሥራ ነገሩት እርሱም አንዱን የአርማንያ መኰንን ለእኔ ጠብቃት ወደ እኔም ላካት ብሎ አዘዘው። 🌹 ደናግሉም ይህን በሰሙ ጊዜ ወደ ሌላ ቦታ ተሠወሩ ወደ ንጉሥም ወነጀሉአቸው ንጉሡም ቅዱስት አርሴማን በክብር አድርገው ያመጧት ዘንድ አዘዘ እርሷም ወደ እርሱ መምጣትን እምቢ በአለች ጊዜ እየጎተቱ ወስደው ወደርሱ አደረሷት። የቅድስት አርሴማንም ላህይና ደም ግባቷን በአየ ጊዜ ድንግልናዋን ሊያረክስ ሽቶ እናቷ አጋታን አባብላ እሺ ታሰኝለት ዘንድ አዘዛት አጋታም ወደርሷ ሒዳ ልቧን አስጨከነች እንዲህም አለቻት። "ዕወቂ ይህ ርኲስ አረሚ እንዳያረክስሽና ሰማያዊ ሙሽራሽን እንዳትተዪ እርሱም ክብር ይግባውና የእግዚአብሔር ልጅ ሕያው ክርስቶስ ነው"። 🌹 ንጉሡም ይዞ ወደ እልፍኙ ሊአስገባት ከአደባባይ መካከል ተነሥቶ ድንግል አርሴማን ያዛት። በዚያንም ጊዜ በቅድስት አርሴማ ላይ የእግዚአብሔር ኃይል አደረባትና በምድር ላይ ጣለችው እርሱ ግን በጦርነት እጅግ የጸና አርበኛ ስለ ነበር በታናሽ ሴት ብላቴና ስለተሸነፈ ያን ጊዜ አፈረ። ራሷንም በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘና ቆረጧት ከዚህም በኋላ ደናግሉን ሁሉ ከእናታቸው አጋታ ጋር ይገድሏቸው ዘንድ አዘዘ። 🌹 አንዲት የታመመች ድንግል ነበረች በዐልጋዋ ላይም እንደተኛች ወደ ወታደሮች ጮኸች መጥተውም እንደ እኅቶቿ ራሷን ቆረጡ ሁሉም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ እነዚያንም ከሮሜ አገር አብረው የመጡ ወንዶችን ገደሏቸው ቁጥራቸውም ሰባ አምስት ናቸው ሥጋቸውም በተራራ ላይ የተጣለ ሁኖ ቀረ። 🌹 ሰማዕታትም ከተገደሉ በኋላ በንጉሡ ላይ ጋኔን ተጫነበት መልኩም ተለውጦ እንደ እርያ ሆነ። ቅዱስ ጎርጎርዮስ ወደርሱ መጥቶ በላዩ ጸልዮ እስከ አዳነው ድረስ ስለዚህም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ። የቅዱሳን ሰማዕታትንም ሥጋቸውን ከተጣለበት ሰብስበው በአማረ ቦታ አኖሩአቸው ያማረች ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያንም ተሠራችላቸው። ከእነርሱም ታላላቅ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት አርሴማና በቅዱሳን ሰማዕታት ሁሉ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 29 ስንክሳር።                              ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ይትፌሥሐ አድባረ ጽዮን። ወትሐሠያ አዋልደ ይሁዳ። በእንተ ፍትሕከ እግዚኦ"። መዝ 47፥11-12  የሚነበበው ወንጌል ማቴ 25፥1-14 ወይም ሉቃ 21፥21-ፍ.ም።                            ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "እግዚአብሔር ይቤለኒ ወልድየ አንተ። ወአነ ዮም ወለድኩከ። ሰአል እምኔየ እሁበከ አሕዛበ ለርስትከ። መዝ 2፥7-8። የሚነበቡት መልዕክታት ገላ 4፥1-12፣ 1ኛ ዮሐ 1፥1-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 3፥1-12። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 21፥21-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ ቅዳሴ እግዚእነ ነው። መልካም የቅድስት አርሴማ የዕረፍት በዓል፣ የሐዋርያው የቅዱስ ዮሐንስ የፍልሠተ ሥጋው መታሰቢያ በዓል ሁላችንም ይሁንልን።           

                           ✝ ✝ ✝ 🌹 #ቅዱስ_አባዲርና_ቅድስት_እኅቱ_ኢራኢ፦ ይህም ቅዱስ ለአንጾኪያ መንግሥት የሠራዊት አለቃ ለሆነ ለፋሲለደስ የእኅቱ ልጅ ነው እርሱም በአባቱ መንግሥት የሠራዊት አለቃ ነበር በውስጡም የሚጸልይበት እልፍኝ አለው። ከሌሊቱም እኩሌታ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠለትና እንዲህ አለው "የሰማዕትነት አክሊልን ትቀበል ዘንድ እኅትህ ኢራኢን ይዘህ ወደ ግብጽ አገር ሒድ። ስለ ሥጋችሁም እንዲአስብ ሳሙኤል የሚባለውን አንድ ሰው እኔ አዛለሁ" ከዚህም በኋላ ሰላምታ ሰጥቶት በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ። 🌹 እንዲሁ ለእኅቱ ኢራኢ ተገልጦላት እንዲህ አላት "የወንድምሽን ቃሉን ስሚው ትእዛዙንም አትተላለፊ" ከእንቅልፏም ነቅታ እጅግ ተንቀጠቀጠች ወደ ወንድሟም ሒዳ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ተገለጠላትና እንደ ተናገራት አስረዳችው። እጅግም ደስ አላቸው ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስም ስለ ስሙ ወደ ግብጽ አገር ሒደው ደማቸውን ያፈሱ ዘንድ በዚህ ምክር ተስማሙ። 🌹 የቅዱስ አባዲር እናትም ይህን ነገር በአወቀች ጊዜ ልብሷን ቀዳ አለቀሰች ከባሮቿም ጋር ወደ ቅዱስ አባዲር መጥታ በሰማዕትነት እንዳይሞት ታምለው ጀመር እርሱም ስለ ሰማዕትነት ነገር ዲዮቅልጥያኖስን እንዳይናገረው ማለላት በዚያንም ጊዜ ከልቅሶዋ ታግሣ ጸጥ አለች። ወደ ሌላ ቦታ ሒዶ በሰማዕትነት እንደሚሞት ግን አላሰበችም። ቅዱስ አባዲርም በየሌሊቱ ሁሉ እንዲህ የሚያደርግ ሆነ ልብሱንም ለውጦ ከቤቱ ይወጣል በወህኒ ቤት ላሉ እሥረኞችም ውኃ በመቅዳት ያጥባቸዋል እስከሚነጋም እንዲህ ያደርጋል በር የሚጠብቀውንም እንዲህ ብሎ አዘዘው "ይህን ለማንም አትናገር ይህንንም ሥራ ብትገልጥ እኔ ራስህን በሰይፍ እቆርጣለሁ"። 🌹 ከዚህም በኋላ ቅዱስ አባዲር ተነሣ እኅቱን ኢራኢንም ይዞ ወደ ግብጽ አገር ሒዶ እስክንድርያ ደረሰ። ከወታደሮችም ያወቁት አሉ "አንተ የሠራዊት አለቃ ጌታችን አባዲር አይደለህም እንዴ" አሉት። እርሱም ፈገግ ብሎ "ብዙዎች እንዲሁ ይሉኛል እኔ ግን እመስለው ይሆናል እንጂ እርሱን አይደለሁም" አላቸው ከዚያም ወደ ሌላ ቦታ ሔደ። በዚያም እንደቀድሞው እርሱ አባዲር እንደ ሆነ ተናገሩት እርሱም አይደለሁም ይላቸው ነበር። 🌹 ከዚህም በኋላ ከእስክንድርያ ከተማ ወጥቶ ወደ ታላቋ የምስር ከተማ ሔደ በዚያም ከአባ አበከረዙን ጋር ተገናኝተው ከእርሱ ቡራኬ ተቀበሉ። ከዚያም ወደ እስሙናይን ደርሰው ከዲያቆን ሳሙኤል ጋር ተገናኙ በማግሥቱም ወደ እንጽና ከተማ ሔዱ በመኰንን አርያኖስም ፊት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመኑ። መኰንኑም ጽኑዕ ሥቃይን ሊአሠቃያቸው ጀመረ ቅዱስ አባዲርም በሥቃይ ውስጥ ያጸናቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነ ያን ጊዜ ጌታችን የእርሱን ነፍስና የእኅቱን ነፍስ ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት ወስዶ ሰማዕታት የሚኖሩበትን የብርሃን ቤቶችን አሳያቸውና ከዚህም በኋላ ወደ ሥጋቸው መለሳቸው። 🌹 መኰንኑም ማሠቃየት በሰለቸ ጊዜ ራሳቸውን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። ራሳቸውንም ከሚቆርጧቸው በፊት መኰንኑ አርያኖስ ቅዱስ አባዲርን እንዲህ አለው "አንተ ማን እንደሆንክ ስምህም ማን እንደሆነ አንተም ከወዴት እንደሆንክ ትነግረኝ ዘንድ በፈጣሪህ አምልሃለሁ" አለው። ቅዱስ አባዲርም "በነገርኩህ ጊዜ ራሳችንን እንዲቆርጡ ያዘዝከውን ትእዛዝ እንዳትለውጥ አንተም ማልልኝ" አለው መኰንኑም ማለለት ያን ጊዜም "የሠራዊት አለቃ እኔ አባዲር ነኝ" አለው መኰንኑ አርያኖስም እንዲህ ብሎ ጮኸ "ወዮልኝ ጌታዬ ሆይ በአንተ ፈንታ እኔ ልሞት ይገባኛል ይህን ሁሉ ጽኑ ሥቃይ እስከ አሠቃየሁህ ድረስ አንተ ጌታዬ እንደሆንክ እንዴት አላስረዳኸኝም ቅዱስ አባዲርም አንተም እንደኔ በሰማዕትነት ትሞት ዘንድ አለህና አትዘን አሁንም ምስክርነታችንን በፍጥነት ፈጽም" ብሎ መለሰለት። 🌹 በዚያንም ጊዜ ራሳቸውን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አርያኖስ አዘዘና እርሱንና እኅቱ ኢራኢን ቆረጧቸው። ያማሩ ልብሶችንም ዘርግተው ገነዙአቸው ዲያቆን ሳሙኤልም የመከራው ወራት እስከሚያልፍ ወደ ቤቱ ወስዶ አኖራቸው ከዚያም በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ታነፀችላቸውና ሥጋቸውን በውስጧ አኖሩ ከእርሳቸውም ታላላቅ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳን ሰማዕታት በአባዲርና በእኅቱ ኢራኢ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 28 ስንክሳር።                                                                            ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ዘይሁቦሙ ሲሳዮሙ ለእንስሳ። ወለእጒለ ቋዓት እለ ይጼውዕዎ። ኢይፈቅድ ኃይለ ፈረሰ"። መዝ 146፥9-10 የሚነበበው ወንጌል 12፥22-32።                              ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "እስመ አድኀንካ ለነፍስየ እሞት። ወለአዕይንትየኒ እምአንብዕ። ወለእገርየኒ እምዳኅዕ"። መዝ 55፥13-14። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 11፥8-22፣ 2ኛ ያዕ 4፥11-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 12፥12-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 8፥3-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።

🌹 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #መስከረም ፳፰ (28) ቀን። 🌹 እንኳን #ከብሉይ_ኪዳን_መጽሐፍ ውስጥ አንዱ በስማ ለተሰየመ #ለታማኟ_ለኬልቅዩስ_ልጅ #ለቅድስት_ሶስና_ለዕረፍት በዓል፣ #ለቅዱስ_አባዲርና_ለእኅቱ_ቅድስት_ኢራኢ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከሰማዕታት #ኢራኢ_ከጳውፍርና_ከሐና_መነኰስ_ሉቃስም ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                    ✝ ✝ ✝ 🌹 #የኬልቅዩስ_ልጅ_ቅድስት_ሶስና፦ ዜናዋም እንዲህ ነው ይችን ቅድስት ሶስናን በባቢሎን የሚኖር ስሙ ኢዮአቄም የሚባል አንድ ሰው አገባት እርሷ እጅግ መልከ መልካም የሆነች ፈጣሪ እግዚአብሔርንም የምትፈራው ነበረች። 🌹 እናትና አባቷም ደጋግ ነበሩ ለልጃቸውም ሙሴ የጻፋትን ኦሪት አስተምረዋት ነበር። ባሏ ኢዮአቄም ግን እጅግ ባለጸጋ ነበር በቤቱም አጠገብ የተክል ቦታ ነበረው ከሁሉ እርሱ ይከብር ነበርና አይሁድ ወደርሱ ይመጡ ነበር። ኃጢአት ከባቢሎን አገር ሕዝቡን እንጠብቃቸዋለን ከሚሉ ከግብዞች ወገኖች እንደ ወጣች እግዚአብሔር ስለነርሱ የተናገረባቸው ግብዞች የሆኑ ሁለት መምህራን በዚያ ወራት ታዩ። 🌹 እነርሱም በኢዮአቄም ቤት የለመዱ የሚአገለግሉም ናቸው። የሚፈራረዱም ሁሉ ወደ እርሱ ይመጡ ነበር። ሕዝቡ ሁሉ ወደ ቤታቸው ከገቡ በኋላ ቀትር በሆነ ጊዜ ሶስና ወደ ባሏተክል ቦታ ገብታ በዚያ ትመላለስ ነበር። ገብታ በተመላለሰች ጊዜ እነዚያ መምህራን ሁልጊዜ ያዩዋት ነበርና ተመኙዋት። ልቡናቸውንም ለወጡ ሰማይንም እንዳያዩ ዐይኖቻቸውን ግልብጥብጥ አደረጉ ሰማያዊ እግዚአብሔርን እንዳያስቡ እውነትኛ ሕግን አላሰቡም። 🌹 ሁለቱም ሁሉ ወደዷት ፈቃዳቸውን መናገር አፍረዋልና እርስበርሳቸው በልቡናቸው ያለውን ነገር አልተነጋገሩም ይደርሱባትም ዘንድ ይወዱ ነበር ያገኟትም ዘንድ ሁልጊዜ ይጠብቋታል። አንዱም አንዱን "የምሳ ጊዜ ነውና ወደ ቤታችን እንግባ" አለው እየራሳቸውም ተለያይተው ሔዱ። ተመልሰውም በጎዳና አንድነት ተገናኙ ሁለቱም ተያዩ ያን ጊዜም ፍላጎታቸውን ተነጋገሩ ብቻ ለብቻ እሷን የሚያገኙበትን ጊዜ ተቃጠሩ። 🌹 ከዚህም በኋላ በቀን ሲጠብቋት ሶስና ሁል ጊዜም ትገባ እንደነበር ከሁለቱ ደንገጡሮቿ ጋር ገባች አልቧታልና በተክል ውስጥ ትታጠብ ዘንድ ወደደች። ተሠውረው ከሚጠብቋት ከሁለቱ ረበናት በቀር በዚያ ማንም ማን አልነበረም። ዘይትና ሽቱ አምጥተው ያጥቧት ዘንድ ልትታጠብ የተክሉንም ደጅ ይዘጉ ዘንድ ደንገጡሮቿን አዘዘቻቸው። እነርሱም እንዳዘዘቻቸው አደረጉ የተክሉን ደጃፍ ዘግተው ያዘዘቻቸውን ያመጡ ዘንድ በስርጥ ጐዳና ወጡ የተሠወሩ እነዚያን ረበናት ግን አላዩአቸውም። 🌹 እነዚያ ደንገጡሮች ከወጡ በኋላ ሁለቱ ረበናት ተነሥተው ወደርሷ ሮጡ "እነሆ የተክሉ ደጃፍ ተዘግቷል የሚያየን የለምና እንደርስብሽ ዘንድ እንወዳለንና እሺ በይን" አሏት። "ይህ ካልሆነ ካንቺ ጋር ሰውን እንዳገኘን ተናግረን እናጣላሻለን ስለዚህም ደንገጡሮችሽን ከአንቺ አሰወጥተሽ ሰደድሽ"። ሶስናም አለቀሰች "በሁሉም ፈጽሞ ተጨነቅሁ ባደርገው እሞታለሁ ባላደርገውም አልድንም ከእጃቸው ማምለጥንም አልችልም በእግዚአብሔር ፊት ከምበድል ኃጢአት ሳልሠራ በእጃችሁ መውደቅ ይሻለኛል" አለች። 🌹 ሶስና ቃሏን አሰምታ ጮኸች። እነዚያም ረበናት ከእርሷ ጋር ጮኹ አንዱ ሩጦ ሒዶ የተክሉን ደጃፍ ከፈተ በቤቷም ያሉ በተክል መካከል ጩኸትን ሰምተው ወጡ ምን እንደሆነ ያዩ ዘንድ በሥርጥ ጐዳናም ሮጡ። እነዚህ ሁለቱ ረበናት ይህንን ነገር በተናገሩ ጊዜ በሶስና ላይ እንዲህ ያለ ነገር ፈጽሞ ተሰምቶ አያውቅም ነበርና ዘመዶቿና አሽከሮቿ እጅግ አፈሩ። 🌹 በማግሥቱም ሕዝቡ በባሏ በኢዮአቄም ዘንድ ተሰበሰቡ እነዚያም ሁለቱ ረበናት ሶስናን ያስገድሏት ዘንድ ከዓመፀኛ ልባቸው ጋራ መጡ በሕዝቡ ሁሉ ፊት ያመጡአት ዘንድ "ወደ ኢዮአቄም ሚስት ወደ ሶስና ላኩ" ብለው አዘዙ ወደርሷም ላኩባት። እርሷም ከእናት ከአባቷ ከወገኖቿ ከዘመዶቿ ከሚያውቋትም ሁሉ ጋር መጣች። 🌹 ሶስና ግን እጅግ ደመ ግቡ ነበረች መልኳም ያማረ ነው። ዓመፀኞች የሆኑ እነዚያ ሁለቱ ረበናት መልኳን ለመጥገብ ይገልጧት ዘንድ አዘዙና ገለጧት። አባቷ፣ እናቷ፣ ቤተሰቦቿ፣ የሚያውቋትም ሁሉ አለቀሱላት። እነዚያም ሁለቱ መምህራን በሕዝቡ መካከል ተነሥተው እጆቻቸውን በራሷ ላይ አኖሩ። እርሷ ግን ልቡናዋ በእግዚአብሔር ታምኗልና እያለቀሰች ወደ ሰማይ ተመለከተች። 🌹 እነዚያም ረበናት "ብቻችንን በተክል ውስጥ ስንመላለስ እርሷ ከሁለቱ ደንገጡሮቿ ጋር ገባች ደንገጡሮቿንም ልካቸዋለችና የተክሉን ደጃፍ ዘግተው ሔዱ ከዚያም በኋላ አንድ ጐልማሳ ከተሠወረበት መጥቶ አብሮዋት ተኛ። እኛ ግን በዚያ ተክል ዳርቻ ሁነን ኃጢአታቸውን አየን ወደነርሱም ሮጥን አንድነት ተኝተውም አገኘናቸው። እኛም እርሱን መያዝ ተሳነን እርሱ በርትቶብናልና አመለጠን የተክሉንም ደጃፍ ከፍቶ ወጣ። እርሷን ግን ይዘን ሰውዬው ማን እንደ ሆነ ጠየቅናት ግን አልነገረችንም ለዚህም ነገር ምስክሩ እኛ ነን" አሉ። 🌹 የሕዝቡ መምህራንና መኳንንትም ነበሩና በአደባባይ የተሰበሰቡ ሰዎች ነገራቸውን አመኑላቸው ትሙት በቃ ብለውም ፈረዱባት። ሶስናም ቃሏን አሰምታ ጮኸች "ዘለዓለም ጸንተህ የምትኖር የተሠወረውን የምታውቅ የሚደረገውን ሁሉ ሳይደረግ የምታውቅ ፈጣሪ ሆይ በሐሰት እንዳጣሉኝ አንተ ታውቃለህ እነዚህ መምህራን ክፉ ነገርን ባደረጉብኝ ገንዘብ የሠራሁት ኃጢአት ሳይኖር እነሆ እሞታለሁ" አለች። እግዚአብሔርም ቃሏን ሰማ። 🌹 ይገድሏት ዘንድ ሲወስዷት እግዚአብሔር ስሙ ዳንኤል በሚባል ልጅ ላይ ልቡናን አነሣሣ "እኔ ከዚች ሴት ደም ንጹሕ ነኝ" ብሎ ቃሉን አሰምቶ ተናገረ። ሕዝቡም ሁሉ ወደርሱ ተመልሰው "አንተ የምትናገረው ይህ ነገር ምንድን ነው" አሉ። ዳንኤልም "በመካከላቸው ቁሞ አላዋቆች የምትሆኑ እናንተ የእስራኤል ልጆች ሳትመረምሩና ነገሩን ሳትረዱ በእስራኤል ልጅ ላይ እንዲህ አድርጋችሁ እንደዚህ ያለ ፍርድን ትፈርዳላችሁን" አለ "እነዚህ መምህራን በሐሰት አጣልተዋታልና ወደ አደባባይ ተመለሱ" አላቸው። 🌹 ሕዝቡም ሁሉ እየሮጡ ወደ አደባባይ ተመለሱ አለቆችም ዳንኤልን "እግዚአብሔር አንተን አልቆሃልና በመካከላችን ተቀምጠህ ተናገር" አሉት። ዳንኤልም "እየራሳቸው አራርቃችሁ አቁሙአቸው እኔም ልመርምራቸው" አላቸውና አንዱንም አንዱን አራርቀው አቆሟቸው። ዳንኤልም ከእርሳቸው አንዱን ጠርቶ "ከዚያ ሰው ጋር በምን ዕንጨት ሥር ሲነጋገሩ አየሃት" አለው "በኮክ ዕንጨት ሥር ሲነጋገሩ አየኋቸው" አለ እርሱንም አርቆ ሁለተኛውን "ሲነጋገሩ ያየህበት ዕንጨት ምንድን ነው?" አለው "ሮማን ከሚባል ዕንጨት ሥር ነው" አለ። ሕዝቡም ሁሉ ቃላቸውን አሰምተው በመጮህ ያመነችበት ሶስናን ያዳናት እግዚአብሔርን አመሰገኑት። 🌹 ለእግዚአብሔርከቃላቸው የተነሣ ዳንኤል አስነቅፏቸዋልና ምስክርነታቸውንም ሐሰት አድርጎባቸዋልና በነዚያ በሁለቱ መምህራን ላይ በጠላትነት ተነሥተው ገደሏቸው። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት ሶስና ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

🌹 እናታቸውንም አረማዊ የሆነ የመርከቡ ሹም በወሰዳት ጊዜ የአታክልቶች ጠባቂ አደረጋት። እግዚአብሔር ከክፉ ነገር ሁሉ በንጽሕና ጠብቋታልና እነዚያ ሁለቱ ልጆቿ እርሷ ወዳለችበት የአታክልት ቦታ ደረሱ እነርሱም የልጅነታቸውን ነገር ይነጋገሩ ነበር። እርሷም ሰምታ ልጆቿ እንደሆኑ አውቃ ያን ጊዜ ጠራቻቸውና እርሷ እናታቸው እንደ ሆነች ነገረቻቸው አንገት ላንገት ተያይዘው አለቀሱና እርስ በርሳቸው ተሳሳሙ ወደ ኤዎስጣቴዎስም ሔደው ከእነርሱ የሆነውን ሁሉ ነገሩት። እርሱም እርሷ ሚስቱ እንደሆነች እነዚያም ልጆቹ እንደ ሆኑ አወቀ እርስ በርሳቸውም ተሳሳሙ ታላቅ ደስታም ደስ አላቸው ምስጉን የሆነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት። 🌹 ከዚህም በኋላ በእነርሱ ላይ ስለ አደረገው በጎ ነገር እያደነቁና እግዚአብሔርን እያመሰገኑ በአንድነት በአንድ ቦታ ኖሩ። ኤዎስጣቴዎስንም የሚወደው ንጉሥ በሞተ ጊዜ በእርሱ ፈንታ ጣዖት የሚያመልክ ሌላ ንጉሥ ነገሠ። ኤዎስጣቴዎስንም ጠርቶ ከሚስቱና ከልጆቹ ጋር ወደርሱ አቅርቦ ለአማልክት ዕጣን አሳርጉ አላቸው። እሊህ ቅዱሳንም እንዲህ ብለው መለሱለት እኛ የረከሱ አማልክትን አናመልክም የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እናመልከዋለን እንጂ። በዚያንም ጊዜ በእነርሱ ላይ ተቆጥቶ እንዲአሠቃዩአቸው አዘዘ ጽኑ ሥቃይንም አሠቃዩአቸው እግዚአብሔርም ያለ ጥፋት አስነሣቸው። 🌹 ሁለተኛም በበሬ አምሳል በተሠራ ነሐስ ውስጥ እንዲጨምሩአቸው አዘዘና በዚያ ጨምረው እሳትን በላያቸው አነደዱ ነፍሳቸውንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጡ። ክብር ይግባውና ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ኤዎስጣቴዎስ በሁለት ልጆቹና በሚስቱ ጸሎት ይማረን በረከታቸው እኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                               ✝ ✝ ✝ 🌹 #የቀራጮች_አለቃ_የነበረ _ቅዱስ_አንጢላርዮስ፦ ይህም ቅዱስ አስቀድሞ በማንም ላይ ርኅራኄ የሌለው ነበረ በአንዲትም ዕለት ድኆች በአንድ ቦታ እያሉ በአንጻራቸው አልፎ ሲሔድ በአዩት ጊዜ ስለርሱ እንዲህ አሉ። "ይህ ባለጸጋ በድኆች ላይ ምንም ምን ርኅራኄ የሌለው ነው" ከእነርሱም አንዱ "እኔ ሔጄ ከእርሱ ምጽዋት ተቀብዬ ብመጣ ምን ትሰጡኛላችሁ" አላቸው እነርሱም አንተ ከእርሱ ምጽዋትን ካገኘህ ያልከውን እንሰጥሃለን አሉት በዚህም ነገር ከተከራከሩ በኋላ ወደ አንጢላርዮስ ቤት ሒዶ ምጽዋትን ለመነው አንጢላርዮስም ከመሶቡ እግር የደረቀ ለከት ዳቦ አንሥቶ በመበሳጨት ወርውሮ የድኃውን ራስ ፈቃው ድኃውም ወደ ባልንጀሮቹ ተመልሶ ያንን ለከት አሳያቸው። 🌹 በዚያቺም ሌሊት አንጢላርዮስ በሕልሙ ራእይን አየ እርሱ በፍርድ አደባባይ ቁሞ ሳለ የጠቆሩ ሰዎች ስለ ክፋቱ ብዛት ሲከራከሩት ብርሃን የለበሱ ሰዎች ደግሞ ከዚች ለከት ዳቦ በቀር በርሱ ዘንድ ያደረገውን ምጽዋት አላገኘንም ብለው ሲያዝኑ በሚዛንም በመዘኑዋት ጊዜ ከኃጢአቱ ሁሉ ተስተካከለች። በዚያንም ጊዜ ነቃ በልቡም "ሳልወድ የሠራሁት ይህን ያህል ጠቃሚ ከሆነ ወድጄ ብሠራውማ እጥፍ ድርብ የሆነ ዋጋ የማገኝ አይደለምን" አለ። 🌹 ከዚህም በኋላ ተነሥቶ ገንዘቡን ጥሪቱን ሁሉ አውጥቶ ለድኆችና ለችግረኞች መጸወተ። ገንዘቡንም ሁሉ ከጨረሰ በኋላ ከሩቅ ቦታ ድኆች መጥተው ምጽዋትን ለመኑት እርሱም ገንዘቡን ሁሉ እንደ ጨረሰ ነገራችውና እጅግ አዘኑ እንዳዘኑም አይቶ እንዲሸጡት ፈቀደላቸው እነርሱም ሸጡትና የሽያጩን ገንዘብ ተከፋፈሉ። በተሸጠበትም እንደባሪያ እያገለገለ ኖረ የጌታው ባሮችም በሚያሳዝኑት ጊዜ ብርሃናዊ ሰው ተገልጦ "አትዘን የተሸጥክበትን ዋጋ እኔ ተቀብዬዋለሁ እነሆ በእጄ ውስጥ አለና" ይለዋል። 🌹 ከዚህም በኋላ አስቀድሞ ከነበረበት የመጡ ሰዎች ሥራውን በገለጡበት ጊዜ በሥውር ሸሽቶ ወደ ከተማው በር ደረሰ በሩን የሚጠብቀውም ዲዳና ደንቆሮ ነበር። አንጢላርዮስም "በሩን ክፈትልኝ" በአለው ጊዜ ከአፉ በእሳት አምሳል ወጥቶ በረኛውን ነካው ያን ጊዜ አንደበቱ ተፈታ ጆሮዎቹም ሰሙ በሩንም ከፍቶለት ወደ በረሀ ሔደ በዚያም ገድሉን ፈጽሞ መስከረም 27 ቀን ዐረፈ። 🌹 ሰዎችም በአጡት ጊዜ ወደ በሩ መጡ በረኛውም የሆነውን ሁሉ ነገራቸው ከቅድስናውና ከተአምራቱም የተነሣ እጅግ አደነቁ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አንጢላርዮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 27 ስንክሳር።                            ✝ ✝ ✝ 🌹 "#ሰላም_ለአንጢላርዮስ_ጳኵሲማ_ኅብስቱ። ዘይበሌዕ ለሲሲቱ። መድኃኒተ ነፍሱ ኮነቶ ወበቋዒተ ሎቱ። ያብአኒ ቤተ ፃማሁ እንተ ድኅነ ቦቱ። በአንጎግዎ ዘስኂት ኢይጥፋእ በከንቱ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_27።                           ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "አኅለፍከነ ማእከለ እሳት ወማይ። ወአውጻእከነ ውስተ ዕረፍት። እበውእ ቤተከ ምስለ መባእየ"። መዝ65፥12-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 27፥1-26።                             ✝️ ✝️ ✝️ 🌹 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወረከብናሁ ውስተ ኦመ ገዳም። ንበውዕ እንከሰ ውስተ አብያቲሁ ለእግዚአብሔር። ወንሰግድ ውስተ መካን በኃ ቆመ እግረ እግዚእነ"። መዝ 131፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 5፥8-26፣ ያዕ 2፥5-14 እና የሐዋ ሥራ 17፥1-10። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 19፥16-27። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።               

🌹 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #መስከረም ፳፯ (27) ቀን። 🌹 እንኳን #አስቀድሞ_በማንም_ላይ_ርኅራኄ የሌለው (ንፉግ) ለነበረ፤ በሕልሙ እግዚአብሔር በሳየው ራእይ ተመልሶ ስለ ምጽዋት ሲል ያለው ንብረት በሙሉ ከሰጠ በኋላ እራሱ ለሸጠ ለቀራጭች አለቃ ለነበረ #ለቅዱስ_አንጢላርዮስ_ለዕረፍት_በዓል መታሰቢያ፣ #በሐዋርያው_ቅዱስ_ጳውሎስ ትምህርት አምና ለተጠመቀች ያለ ደም መፍሰሰ ሰማዕት ለሆነች #ለቅድስት_ጤቅላ (ቴክላ) ለዕረፍቷ በዓል መታሰቢያ፣ #ለቅዱስ_ኤዎስጣቴዎስ_ለሁለት_ልጆቹና_ለሚስቱም ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል መታሰቢያ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ከመድኃኒታችን ከስቅለቱ  #ከመድኃኔዓለም ከወራዊ ከመታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                          ✝ ✝ ✝ 🌹 #ሐዋርያዊት_ቅድስት_ጤቅላ፦ የዚች ቅድስት ወላጆቿ ከመቄዶንያ ሰዎች ውስጥ ባለጸጎች ናቸው እርሷንም እንደ ሀገራቸው ባህል በተግሣጽ በምክር አሳደጓት እነርሱ ጣዖትን የሚያመልኩ ናቸውና። 🌹 ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም ወደዚች አገር በደረሰ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲህ እያለ ሊአስተምር ጀመረ "ዐውቀው ድኆች የሆኑ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት ለነርሱ ናትና። ዛሬ የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው እነርሱ ደስ ይላቸዋልና። ስለ ዕውነት የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት ለእነርሱ ናትና። ሚስት እያላቸው እንደ ሌላቸው የሚሆኑ ብፁዓን ናቸው። እነርሱ የዘላለም ሕይወትን ይወርሳሉና"። ይህንንና ይህን የመሰለውን በሰማች ጊዜ ቅድስት ጤቅላ ከቤቷ ደርብ ሳትወርድ ያለ መብልና መጠጥ ሦስት ቀን ኖረች። እናቷም "ከቤትሽ ደርብ የማትወርጂ ለምንድን ነው እህልስ ለምን አትበዪም" አለቻት። 🌹 ከዚህም በኋላ በጭልታ ወረደች ለሚጠብቃትም ዘበኛ እንዳይናገርባት የወርቅ ወለባዋን ዋጋ ሰጠችውና ወደ ቅዱስ ሐዋርያ ጳውሎስ ሔደች። እርሱም በደስታ ተቀብሎ የክርስቶስን ሃይማኖት አስተማራት። 🌹 በማግሥቱም እናቷ እየፈለገቻት በመጣች ጊዜ ከቅዱስ ጳውሎስ ዘንድ አብራ ተቀምጣ አገኘቻት ከዚያም ወደ መኰንን ሒዳ ልጇን ክርስቲያን እንደሆነች ከሰሰቻት። መኰንኑም ከቅዱስ ጳውሎስ ጋራ እንዲያመጧት አዘዘ አስቀድመው ቅዱስ ጳውሎስን ወደ እሳት እንዲወረውሩት አዘዘ እግዚአብሔርም አዳነው። መኰንኑም የቅድስት ጤቅላን ቅጣት እንዲያዩ የሀገር ልጆችን ሰበሰበ ከዚህም በኋላ ወደ እሳት እንዲወረውሩዋት አዘዘ። በዚያን ጊዜ በክርስቶስ ማዕተብ ራሷን አማትባ ራስዋን በራስዋ ወደ እሳት ወረወረች ማንም ያያት ሳይኖር ከእሳት ውስጥ ወጥታ ወደ ቅዱስ ጳውሎስ ሔደች የራስዋን ጠጒር ቆርጣ ወገቧንም ታጥቃ ቅዱስ ጳውሎስን ተከተለችው። 🌹 መኰንኑም ደኅንነቷን በሰማ ጊዜ ያዛት ሃይማኖቷንም እንድትተው አስገደዳት አይሆንም ባለችውም ጊዜ አንበሶችና ድብ ከሚያድሩበት እንዲጨምሩዋት አዘዘ። እነርሱም ሰገዱላትና የእግሮቿን ትቢያ ላሱ። ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው መኰንኑና ወገኖቹ አመኑ አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠመቁ በክርስቶስም መንጋዎች ውስጥ ሆኑ። 🌹 እርሷ ቅድስት ጤቅላም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌልን በማስተማር ቅዱስ ጳውሎስን እያገለገለችው ኑራ  መስከረም 27 ቀን በሰላም ዐረፈች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስ ጤቅላ ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ትሩር ለዘላለሙ አሜን።                               ✝ ✝ ✝ 🌹 #ቅዱስ_ኤዎስጣቴዎስ_ሁለቱ_ልጆቹና ሚስቱም፦ ይህ ቅዱስም ለሮም መንግሥት የጭፍራ አለቆች ከሆኑት ውስጥ ነው የቀድሞ ስሙ ቂዶስ ነው እግዚአብሔርንም አያውቅም ነበር ግን ብዙ ምጽዋትን በመስጠት ለድኆችና ለችግረኞች ይራራል ስለዚህም ክብር ይግባውና ጌታችን ድካሙ ከንቱ ሁኖ እንዲቀር አልወደደም። 🌹 በአንዲት ቀንም አውሬ ሊያድን ኤዎስጣቴዎስ ወደ ዱር ወጣ እርሱ አዳኝ ነውና ዋልያም አግኝቶ በቀስት ሊነድፈው ወደደ ያን ጊዜም በዋልያው በቀንዶቹ መካከል በመስቀል አምሳል ጌታ ተገለጸለት። የመስቀሉም ብርሃን እስከ ደመና ደርሶ ነበር ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በዚያ ብርሃን ውስጥ ተናገረው ስሙንም አስረዳው ከሚስቱና ከልጆቹ ጋር ወደ ኤጲስቆጶስ ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን እንዲጠመቁ አዘዘው። 🌹 ክብር ይግባውና ጌታችንም ከዚህ በኋላ ችግርና ፈተና እንደሚመጣበት በመጨረሻም ስለ ከበረ ስሙ ምስክር ሁኖ ደሙን አፍስሶ እንደሚሞት አስረዳው። ኤዎስጣቴዎስም ሰምቶ ከተራራው ወርዶ ወደ ቤቱ ሔደ። ጌታችን ያዘዘውንም ለሚስቱ ነገራት ከዚህም በኋላ ወደ ኤጲስቆጶሱ ሔደው ከልጆቻቸው ጋራ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቁ የቀድሞ ስሙንም ለውጦ ኤዎስጣቴዎስ ተባለ። 🌹 ከጥቂት ቀኖች በኋላ በዚያች አገር ታላቅ ችግር መጣ የኤዎስጣቴዎስም ገንዘቡ ሁሉ አልቆ ወንዶችና ሴቶች ባሮቹ ተበተኑ ወደሌላ አገርም ሊሰደድ ወዶ ልጆቹንና ሚስቱን ይዞ በመርከብ ተጫነ። ወደ ወደቡም በደረሱ ጊዜ መርከበኞች የመርከብ ዋጋ ከእርሱ ፈለጉ የሚሰጣቸው የመርከብ ዋጋ ባላገኘ ጊዜ ስለ መርከብ ዋጋ የመርከቡ ሹም ሚስቱን ወሰዳት የአታክልት ጠባቂም አደረጋት። ከዚያም ኤዎስጣቴዎስ እያዘነና እያለቀሰ ሁለቱን ልጆቹን ይዞ ሔደ ውኃ ወደ መላበትም ወንዝ ደረሰ አንዱንም ልጁን ከእርሱ ጋር ሊአሻግረው ይዞት ገባ አሻግሮትም ከወንዙ ዳር አኖረውና ሁለተኛውን ልጁን ሊአሻግረው ተመለሰ ግን አላገኘውም።  ተኵላ ወስዶታልና ያሻገረውንም አንበሳ ነጥቆ ወሰደው ኤዎስጣቴዎስም ከሚስቱና ከልጆቹ ስለ መለየቱ ታላቅ ኀዘንን አዝኖ መሪር ልቅሶን አለቀሰ ምክሩ ታላቅ የሆነ ሥልጣን ያለው እግዚአብሔር ግን ሁሉንም በየአሉበት ያለ ጥፋት ጠበቃቸው። 🌹 ከዚህ በኋላም ኤዎስጣቴዎስ ወደ አንዲት አገር ሒዶ በዚያ የአትክልት ጠባቂ ሁኖ ብዙ ቀኖችን ኖረ። ከእነዚያ ቀኖችም በኋላ የሮም ንጉሥ ሙቶ በርሱ ፈንታ ለኤዎስጣቴዎስ ወዳጁ የሆነ ሰው ነገሠ ኤዎስጣቴዎስንም ፈለገው ግን አላገኘውም ኤዎስጣቴዎስንም ይፈልጉት ዘንድ ወደ ሀገሩ ሁሉ መልእክተኞችን ላከ። ከመልእክተኞችም አንዱ ኤዎስጣቴዎስ ወዳለበት ደርሶ በአታክልቶች ዘንድ አግኝቶት አወቀው እርስ በርሳቸውም ተሳሳሙ ከዚህም በኋላ ወደ ንጉሡ ወሰደው ንጉሡም በበጎ አቀባበል ተቀብሎ የጭፍራ አለቃ አድርጎ ሾመው። 🌹 ከዚህም በኋላ ንጉሡ ከሚገዛቸው አገሮች ሁሉ ወጣቶችን ሰብስቦ የጦር ሠራዊት ጭፍራ ያዘጋጅ ዘንድ ኤዎስጣቴዎስን አዘዘው እነዚያ ተኵላና አንበሳ የወሰዳቸው የኤዎስጣቴዎስ ሁለት ልጆቹ በአንዲት አገር አድገዋል። ግን እርስበርሳቸው አይተዋወቁም ወጣቶችንም የሚመለምሉ መልምለው ወደ አባታቸው ኤዎስጣቴዎስ አቀረቧቸው እርሱም ሳያውቃቸው የመዛግብት ቤት ጠባቂዎች አደረጋቸው።

🌹 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #መስከረም ፳፮ (26) ቀን። 🌹 እንኳን #ለእናታችን_ለእመቤታች_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም ለልጇ ለወዳጇ ለክብር ባለቤት ለጌታችን ለመድኃኒታችን ##ለኢየሱስ_ክርስቶስ ለስደታቸው መታሰቢያ #ለፈቃድ_ጾም_ለጽጌ ጾም (ለዘመነ ጽጌ) እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                                                         ✝ ✝ ✝ 🌹 #የዘመነ_ስደት_መታሰቢያ ለምን በዚህ ጊዜ ሆነ? #ከመስከረም_26_እስከ_ህዳር_5። 🌹  እመቤታችን ከልጅዋ ጋር ስደትን የጀመረችው ጥር 3 ነው፥ አገረ ግብጽ የገባችው ግንቦት 24 ነው፥ በግብፅ እና በኢትዮጵያ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ከቆዩ በኋላ ስደቱ አብቅቶ ተመለሱ ብሎ መልአኩ ሲነግራቸው ካሉበት ተነስተው ቁስቋም ከተባለች ቦታ ኅዳር 6 ደርሰዋል ። 🌹#የስደት_መታሰቢያ_ለምን_በመነሻው_ጥር_3 አልሆነም? ይህ ወቅት ዘመነ አስተርእዮ የደስታ ጊዜ ነው ታኅሣሥ 29 ልደቱን ጥር 11 ጥምቀቱን የምናከብርበትና በልደቱ እና በጥምቀቱ የተደረገልንን እያሰብን ደስ የምንሰኝበት ጊዜ በመሆኑ ለስደት መታሰቢያ ለማድረግ አይመችም። 🌹 #ግንቦት_24_አገረ_ግብፅ_የገባችበትን ይዘን ለምን ስደትን አናስብም? 🌹 ግንቦት 24 በዓለ ሃምሳን የምናከብርበት እንደመሆኑ በዚህ ወቅት ጌታችን በትንሳኤው የሰጠንን ነጻነት የምናስብብት ደስ የምንሰኝበት ጊዜ ስለሆነ መስገድ መጾም ስለማይፈቀድ የስደት መታሰቢያ ለማድረግ አይመችም። 🌹 ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 5 ዕፅዋት አበባን ፍሬን የሚያሳዩበት ወቅት ነው። 🌹 ወቅቱ ለምሳሌ የተመቸ ነውና። "ትወጽእ በትረ እምሥርወ እሤይ ወየዓርግ ጽጌ እምኔሃ"  ኢሳ 11፥1 እንዲል የዕሤይ የዘር ግንድ ከተባለች ከእመቤታች ጽጌ ጸኣዳ ወቀይህ የተባለ የፍጥረት ሁሉ ጌጥ ጌታችን የተገኘ ነውና በዚህ መስሎ ለማስተማር የሚያመች ወቅት ነውና። በተጨማሪም ጽጌ በእመቤታች ፍሬ በጌታችን ይመሰላል። 🌹 #አንድም፦ ተመለሰ ከማለት በፊት ተሰደደ ማለት ይቀድማል። 🌹 በዓመት ውስጥ ያሉት የወራት ቅድመ ተከተል ኅዳር 6 ከጥር 3 እና ከግንቦት 24 ይቀድማል። ኅዳር ላይ ከስደት ተመለሰ ብለን ካከበርን በኋላ ጥር ተሰደደ ግንቦት ግብፅ ገባ ብንል አመቺ አይደለም። ስለዚህ ከጥር 3 ወይም ከግንቦት 24 ይልቅ ኅዳር 6 መታሰቢያ ለማድረግ አመቺ በመሆኑ ቤተክርስቲያን በዚህ ወቅት የስደቱን መታሰቢያ ታደርጋለች። 🌹 በቅዱስ ያሬድ አባባል ስደት #ከመስከረም_26_እስከ_ጥቅምት_20 ሲነገር፤ #ከጥቅምት_21_እስከ_ኅዳር_6 ድረስ ሚጠት (መመለሳቸው) ይነገራል። ይኼውም ተመየጢ ተመየጢ ሰላመ ሰጣዊት የሚለው ሰላም እንዲቀርብ በማኅሌት ስለተወሰነ ነው። ምንጭ፦ አምኃ ሥላሴ መኩሪያ ተስፋዬ። 🌹 ጾሙ ከአገራችን ኢትዮጵያ ጦርነትን የሚያጠፋ እና ሰላም፣ ፍቅርን አንድነትንና መተሳሰብ የሚያመጣ ያድርግልን። መልካም ጾም ለሁላችንም ይሁንልን።               @Teamihokidusan

🌹 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹            🌹 #መስከረም ፳፮ (26) ቀን። 🌹 እንኳን #ለመላእክት_አለቃ_ለቅዱስ_ገብርኤል ወደ በራክዩ ልጅ ወደ #ቅዱስ_ዘካርያስ_ለተላከበት #መጥምቀ_መለኮትን ከእርሱ ስለ መወለዱ ለአበሰረበት፤ ( #ለመጥምቀ_መለኮት #ለቅዱስ_ዮሐንስ_ለጽንሰት_በዓል)ና ለሰማዕቱ #ለቅዱስ_ዮስጦስ_ልጅ_ለቅዱስ_አቦሊ ለሥጋው ፍልሰት በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከዐሥር_ሽህ_ሰማዕታት፣ #ከቅድስት_አጋታ_ከበርባራ_ከዮልያና፣ #ከአባት_ጊዮርጊስም_ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                 ✝ ✝ ✝ 🌹 #የየመላእት_አለቃ_ቅዱስ_ገብርኤል #ለቅዱስ_ዘካርያስ_የመጥምቀ_መለኮትን_የቅዱስ_ዮሐንስ_መጸነስ_እዳበሰረው፦ ስሙ የተመሰገነ እግዚአብሔር ልጅን ይሰጠው ዘንድ አስቀድሞ ሁል ጊዜ በመጸለይ ወደ እግዚአብሔር ይማልድ ነበር። ልጅ ያልወለደውን እግዚአብሔር ብዙ ተባዙ ምድርን ምሉዋት ያለውን በረከት ያጣ ነው በማለት እስራኤል ይገዳደሩት ነበርና። 🌹 ልመናውንም ሰማ በቤተ መቅደስም ቁሞ ዕጣንን ሲያሳርግ መልአኩን ላከለት በከበረ ወንጌልም እንደተባለ መንገዱን ይጠርግ ዘንድ በንጉሥ ክርስቶስ ፊት እንደሚሔድ የተነገረለት ታላቅ ነቢይ ዮሐንስ ከእርሱ መወለዱን አበሠረው። 🌹ዘካርያስም የሰውነቱን መድከም የመውለጃውም ዘመን እንዳለፈና ፈጽሞ እንዳረጅ የሚስቱም እንዲሁ ዘመኗ እንዳለፈና ፈጽማ እንዳረጀች መካንም እንደሆነች ያውቃልና ስለዚህ ይህ ነገር እንዴት ይሆንልኛል "እኔ ያረጀሁ ሽማግሌ ነኝ ሚስቴም እንዲሁ ዘመኗ አልፎ መካን ሁናለች" ብሎ የእግዚአብሔርን መልአክ ተከራከረው። 🌹 መልአኩም "እኔ ይህን ልነግርህ ከእግዚአብሔር ዘንድ ወዳንተ ተልኬ ነበር ልትጠራጠር ባልተገባህም ነበር አሁንም ይህ በጊዜው እስቲፈጸም ዲዳ ሁነህ መናገር ይሳንሃል" ብሎ ገሠጸው። ዘካርያስም የወልደ እግዚአብሔርን መንገድ የሚጠርግ ዮሐንስ እስከሚወለድበት ጊዜ ድረስ ዲዳ ሆነ። 🌹 በሚገረዝበትም ቀን የሕፃኑን አባት ዘካርያስን የሕፃኑን ስም ምን ብለው እንደሚሰይሙት ጠየቁት እርሱም ብራና ለምኖ "ስሙ ዮሐንስ ነው" ብሎ ጻፈ በዚያም ጊዜ አንደበቱ ተፈትቶ እግዚአብሔርን አመሰገነው። ስለ ልጁ ዮሐንስም እርሱ የልዑል ነቢይ እንዲባል መንገዱንም ይጠርግ ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት እንደሚሔድ ትንቢት ተናገረ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ዘካርያስና በቅድስት ኤልሳቤጥ በልጃቸው በቅዱስ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                              ✝ ✝ ✝ 🌹 "#ሰላም_ለፅንሰትከ_በሠሌዳ_ከርሣ_ዘተገልፈ። ለኤልሳቤጥ እምከ እምድኅረ ወርኃ ኀለፈ። ዮሐንስ መልአክ እንተ ትኴንን አእላፈ። ከመ እፈጽም ዘወጠንኩ ስብሐቲከ ትሩፈ። በውስተ ዕዝንየ አልኆስስ መጽሐፈ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_26።                            ✝️ ✝️ ✝️ 🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "በቅድመ መላእክቲከ እዜምር ለከ። ወእሰግድ ውስተ ጽርሐ መቅደስከ። ወእገኒ ለስመከ"። መዝ137፥1-2። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 12፥1-11፣ 1ኛ 2፥20-ፍ.ም እና የሐዋ 10፥1-9። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥1-23። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ኤጲፋንዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ገብርኤል በዓልና የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የጽንሰት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼            🌼 #መስከረም ፳፬ (24) ቀን። 🌼 እንኳን #ከሰባ_ሁሉቱ_አርድእት ለአንዱ ለሐዋርያው #ለቅዱስ_አድሊጦስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል፣ #ከላይኛው_ግብጽ ለሆኑ ለ#ቅዱስ_አባት_ለመነኰስ_ለአቡነ_ጎርጎርዮስ ለዕረፍት በዓል በሰላም አደረሰን።                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት_አንዱ_የሆነው #ሐዋርያው_ቅዱስ_አድሊጦስ፦ ይህም ሐዋርያ ትውልዱ ከአቴና አገር ከታላላቆቿና ከምሁራኖቿ ነው እርሱም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ አገለገለውም።                            🌼 አጽናኝ የሆነ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በሃምሳኛው ቀን ከተቀበለ በኋላ ወደ ብዙዎች አገሮች ሒዶ ሕይወት የሆነ ወንጌልን ሰበከ መግኒን ወደሚባልም አገር ደርሶ በውስጧ የከበረ ወንጌልን ሰበከ የብዙዎችንም ልቦና ብሩህ አድርጎላቸው ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ሕይወት የሆኑ የወንጌልንም ትእዛዞች አስተምሮ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው ። 🌼 ከዚህም በኋላ ከእሳቸው ዘንድ ወጥቶ ወደ አቴና አገር ተመለሰ በውስጧም የከበረ ወንጌልን አስተማረ በዚያን ጊዜም በደንጊያ ወገሩት ጽኑዕ የሆነ ሥቃይንም አሠቃዩት። ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ወረወሩትና በዚያ ተጋድሎውንና ምስክርነቱን ፈጽሞ የሕይወት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዱስ አድሊጦስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                               ✝ ✝ ✝ 🌼 #አቡነ_ጎርጎርዮስ_ዘላዕላይ_ግብጽ፦ የዚህም የቅዱስና የተመሰገነ ጎርጎርዮስ ወላጆቹ ደጎች ናቸው በዚህ ዓለም ገንዘብም እጅግ ባለጸጎች ነበሩ ይህን ልጃቸውን ጎርጎርዮስንም በበጎ አስተዳደግ አሳደጉት። መንፈሳዊ የሆነ የቤተ ክርስቲያን ትምህርትን ሁሉ ሥጋዊም የሆነ ጥበብንና ቋንቋን አስተማሩት። 🌼 ከዚህም በኋላ የሀገራቸው ኤጲስቆጶስ ወደ ሆነ ወደ አባ ይስሐቅ ወሰዱት እርሱም እጁን በላዩ ጭኖ አናጒንስጢስነት ሾመው። 🌼 ከዚህም በኋላ ወላጆቹ ሊአጋቡት አሰቡ እርሱ ግን ይህን ሥራ አልወደደም ሁለተኛም ወደ ጳጳስ ወስደውት ፍጹም ዲቁናን ተሾመ ወደ አባ ጳኲሚስም አዘውትሮ በመሔድ ከእርሱ የእግዚአብሔርን ሕግ የሚማር ሆነ ከወላጆቹም ብዙ ገንዘብን ወስዶ ወደ አባ ጳኲሚስ አቅርቦ በገዳማቱ ለሚሠሩ ሕንፃዎች ሥራ ያደርግለት ዘንድ ብዙ ልመናን ለመነው እርሱም ተሳትፎ እንዲሆንለት ለሕንፃ ቤተ ክርስቲያንና ለመነኰሳት ቤት መሥሪያ አደረገለት ። 🌼 ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዓለምን ትቶ ጥሪቱንና ገንዘቡን ሁሉ ንቆ በመተው ወደ ቅዱስ አባ ጳኲሚስም ሒዶ የምንኲስና ልብስን ለብሶ በጾም በጸሎት በመትጋት በመስገድ ከትሕትና፣ ከቅንነት፣ ከፍቅር ጋር ይጋደል ጀመረ አርአያነቱንና ምሳሌነቱን በአዩ ጊዜ ከእርሱ ፈሪሀ እግዚአብሔርን ተምረው አመንዝራዎች የከፋ ሥራቸውን እስከ ተውና ንስሐም ገብተው ንጹሐንም እስከ ሆኑ ድረስ ተጋደሉ። ከአባ ጳኲሚስም ዘንድ ዐሥራ ሦስት ዓመት ኖረ። 🌼 አባ መቃርስም ወደ አባ ጳኲሚስ በመጣ ጊዜ ሰውነቱን በማድከም ታላቅ ተጋድሎን እየተጋደለ ጥቂት ቀኖች ኖረ ከዚያም በኋላ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሊመለስ ወደደ አባ ጳኲሚስም ከአባ መቃርስ ጋር እንዲሔድ አባ ጎርጎርዮስን አዘዘው እርሱም አብሮ ሔደ በእርሱም ዘንድ ብዙ ዘመናት ኖረ ። 🌼 ከዚህም በኋላ በዋሻ ብቻውን ይኖር ዘንድ እንዲአሰናብተው የከበረ አባ መቃርስን ለመነው እርሱም "እንደ ወደድክ አድርግ" አለው። ያን ጊዜ ወደ ተራራ ሒዶ ታናሽ ዋሻ ቆርቁሮ በውስጧ ሰባት ዓመት ኖረ አባ መቃርስም በየዓመቱ ሁለት ጊዜ መጥቶ ይጎበኘዋል አንደኛ ለከበረ የልደት በዓል ሁለተኛ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተነሣባት በትንሣኤ በዓል ቀን ከርሱ ጋርም ሥጋውንና ደሙን ተቀብሎ ወደ ቦታው ይመለሳል። አባ መቃርስም ስለ ሥራው ሁሉ ይጠይቀዋል እርሱም የሚያየውንና በእርሱ የሆነውን ሁሉ ይገልጽለታል አባ መቃርስም ሊሠራው የሚገባውን የምንኲስና ሥራን ይሠራ ዘንድ ያዘዋል ። 🌼 በተጋድሎም ውስጥ ሃያ ሁለት ዓመታት ሲፈጽሙለት ከዚህ የድካም ዓለም ያሳርፈው ዘንድ እግዚአብሔር ፈቅዶ መልአኩን ላከለት እርሱም ከሦስት ቀን በኋላ ከዚህ ከኀላፊው ዓለም ወጥተህ ወደ ዘላለም ሕይወት ትገባለህ አለው። 🌼 አባ ጎርጎርዮስም በአስቄጥስ ገዳም ያሉ አረጋውያንን አስጠራቸውና ተሳለማቸው በጸሎታቸውም እንዲአስቡት ለመናቸው እነርሱም ደግሞ በእግዚአብሔር ዘንድ እንዲአስባቸው ለመኑት ከሦስት ቀንም በኋላ አርፎ ወደ ዘላለም ሕይወት ገባ።                                                        ✝ ✝ ✝ 🌼 "#ሰላም_ለጎርጎርዮስ ወለደብራጦስ አያዩ። ዘውኂዘ መንፈስ ሰትየ #ከመ_ሐዋርያት_ሰትዩ። ሶበ ገደፈ ቅድሜሁ እስከ ዘዕለት ሲሳዩ። ዘሎቱ ለሊሁ ወዘአበዊሁ አጥረዩ። ሥርዓተ ማኅበር ሐነፀ ጳኵሚስ በንዋዩ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_24።                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኀይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥16-ፍ.ም።                             ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አፅናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ። ወውስተ ፀሓይ ሤመ ጽላሎቶ"። መዝ18፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 2፥12-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 2፥20-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 10፥39-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቅዳሴ ነው መልካም የሐዋርያው ቅዱስ አድሊጦስ እና የአቡነ ጎርጎርዮስ የዕረፍታቸው በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።         

🌼 በአንዲት ዕለትም የጣዖቶቻቸው በዓል በሆነ ጊዜ በሽልማት ሁሉ ሸለሙአቸው በመብራቶችና በሥዕሎችም ዘንባባም አስጌጧቸው በማግሥቱም መጥተው በዓላቸውን ለማክበር በዋዜማው አዘጋጅተው የጣዖታቱን ቤቶች ዘግተው ወደ ቤታቸው ገቡ። ቅዱስ ዮልዮስም ጣዖታቱን ያጠፋቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነ በዚያን ጊዜም ጌታችን መልአኩን ልኮ የጣዖታቱን ራሶቻቸውን ቆረጠ ፊቶቻቸውንም በፍም አጠቆረ ሽልማታቸውንና ዘንባባውን የጣዖቱን ቤት ሥርዓት ሁሉ አቃጥሎ አጠፋ። 🌼 ማግሥትም በሆነ ጊዜ ለአማልክቶቻቸው እንደ ልማዳቸው በዓልን ሊአከብሩላቸው በከበሩ ልብሶች ተሸልመው ሲመጡ ተጐሳቁለው ጠፍተው አዩአቸው የጣዖቶቻቸውን ድካማቸውን አወቁ። እንዲህም አሉ "አማልክቶቻችን ራሳቸውን ማዳን ያልቻሉ እኛን ያድኑ ዘንድ እንዴት ይችላሉ" ይህንንም ተናግረው ከአትሪብ መኰንን ጋር በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድነት አመኑ። 🌼 ከዚያም ደግሞ ቅዱስ ዮልዮስ ጡዋ ወደሚባል አገር ሔደ ከርሱም ጋር የገምኑዲ መኰንንና የአትሪብ መኰንን አሉ የጡዋ መኰንን ወደ ሁነ ወደ እስክንድሮስ ቀርቦ በፊቱ ክብር ይግባውና በጌታችን ስም ታመነና እንዲህ አለው "ገድሌን ፈጽምልኝ ራሴንም እንዲቆርጡ እዘዝና የምስክርነት አክሊልን ተቀብዬ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እንድሔድ"። እስክንድሮስም "እኔ አላሠቃይህም በአንተ ላይም ምንም ክፉ ነገር አላደርግም" አለው። 🌼 ቅዱስ ዮልዮስም አምስት መቶ የሚሆኑ አገልጋዮቹን ሰይፎቻቸውን መዝዘው እስክንድሮስን እንዲአስፈሩት አዘዛቸው በዚያንም ጊዜ በእስክንድሮስ ላይ ተነሥተው "ለክብር ባለቤት ክርስቶስ ምስክሮቹ እንሆን ዘንድ የሁላችንም ራሶቻችንን እንዲቆርጡ ካላዘዝክ እኛ እንገድልሃለን" አሉት። ዳግመኛም ርኵስ መንፈስ እንዲጫንበት ቅዱስ ዮልዮስ አዘዘው ወዲያውኑ በመኰንኑ በእስክንድሮስ ላይ ተጫነበት በዚያንም ጊዜ ራሶቻቸውን ይቆርጧቸው ዘንድ በጽሑፍ አዘዘ ሁሉንም ቅዱሳን ሰማዕታትን ቆረጧቸው። 🌼 እሊህም ቅዱስ ዮልዮስ፣ ልጁም ቴዎድሮስ፣ የከበረ ወንድሙ ዮንያስ፣ አምስት መቶ አገልጋዮቹ የገምኑዲና የአትሪብ መኰንኖች ብዙዎች ሕዝቦችም የሁሉም ቁጥራቸው አንድ ሺህ አምስት መቶ ነው። በዚያች ቀን ከቅዱስ ዮልዮስ ጋር በሰማዕትነት የሞቱ ናቸው የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። 🌼 የቅዱስ ዮልዮስን የልጁንና የወንድሙን ሥጋ አንሥተው ወደ እስክንድርያ አገር አደረሱ እርሱ በውስጧ ነዋሪ ሁኖ ነበርና ትውልዱ ግን አቅፋሐስ ከሚባል አገር ነው በአማረ ቦታ ውስጥም አኖሩአቸው። ከዚያም በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያንን ሠሩላቸው ከእርሳቸው ታላላቅ የሆኑ ድንቆች ተአምራት ተደረጉ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሁሉ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 22 ስንክሳር።                             ✝ ✝ ✝ 🌼 "#ሰላም_ለኮቶሎስ_አኅወ_እክሱ_ብፅዕት። ወፍቁረ ጣጦስ ሰማዕት። ሶበ አተበ በመስቀል  ትእምርተ ሕይወት። መጠነ ዐሠርቱ ወክልኤቱ በእመት። እምዐውደ ምኵናን ሰሰለ እሳት"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_22።                             ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ አቡየ ገደፉኒ። ወእግዚአብሔር ተወከፈኒ። ምርሀኒ እግዚኦ ፍኖተከ"። መዝ 26፥10-11 ወይም መዝ 33፥19። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 4፥7-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 4፥12-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 19፥8-11። የሚነበበው ወንጌል ማር 13፥9-14። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቅዳሴ። መልካም በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።