ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
رفتن به کانال در Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
نمایش بیشتر637
مشترکین
-124 ساعت
-37 روز
-1330 روز
آرشیو پست ها
🌹 እናታቸውንም አረማዊ የሆነ የመርከቡ ሹም በወሰዳት ጊዜ የአታክልቶች ጠባቂ አደረጋት። እግዚአብሔር ከክፉ ነገር ሁሉ በንጽሕና ጠብቋታልና እነዚያ ሁለቱ ልጆቿ እርሷ ወዳለችበት የአታክልት ቦታ ደረሱ እነርሱም የልጅነታቸውን ነገር ይነጋገሩ ነበር። እርሷም ሰምታ ልጆቿ እንደሆኑ አውቃ ያን ጊዜ ጠራቻቸውና እርሷ እናታቸው እንደ ሆነች ነገረቻቸው አንገት ላንገት ተያይዘው አለቀሱና እርስ በርሳቸው ተሳሳሙ ወደ ኤዎስጣቴዎስም ሔደው ከእነርሱ የሆነውን ሁሉ ነገሩት። እርሱም እርሷ ሚስቱ እንደሆነች እነዚያም ልጆቹ እንደ ሆኑ አወቀ እርስ በርሳቸውም ተሳሳሙ ታላቅ ደስታም ደስ አላቸው ምስጉን የሆነ እግዚአብሔርንም አመሰገኑት።
🌹 ከዚህም በኋላ በእነርሱ ላይ ስለ አደረገው በጎ ነገር እያደነቁና እግዚአብሔርን እያመሰገኑ በአንድነት በአንድ ቦታ ኖሩ። ኤዎስጣቴዎስንም የሚወደው ንጉሥ በሞተ ጊዜ በእርሱ ፈንታ ጣዖት የሚያመልክ ሌላ ንጉሥ ነገሠ። ኤዎስጣቴዎስንም ጠርቶ ከሚስቱና ከልጆቹ ጋር ወደርሱ አቅርቦ ለአማልክት ዕጣን አሳርጉ አላቸው። እሊህ ቅዱሳንም እንዲህ ብለው መለሱለት እኛ የረከሱ አማልክትን አናመልክም የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እናመልከዋለን እንጂ። በዚያንም ጊዜ በእነርሱ ላይ ተቆጥቶ እንዲአሠቃዩአቸው አዘዘ ጽኑ ሥቃይንም አሠቃዩአቸው እግዚአብሔርም ያለ ጥፋት አስነሣቸው።
🌹 ሁለተኛም በበሬ አምሳል በተሠራ ነሐስ ውስጥ እንዲጨምሩአቸው አዘዘና በዚያ ጨምረው እሳትን በላያቸው አነደዱ ነፍሳቸውንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጡ። ክብር ይግባውና ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ኤዎስጣቴዎስ በሁለት ልጆቹና በሚስቱ ጸሎት ይማረን በረከታቸው እኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
🌹 #የቀራጮች_አለቃ_የነበረ _ቅዱስ_አንጢላርዮስ፦ ይህም ቅዱስ አስቀድሞ በማንም ላይ ርኅራኄ የሌለው ነበረ በአንዲትም ዕለት ድኆች በአንድ ቦታ እያሉ በአንጻራቸው አልፎ ሲሔድ በአዩት ጊዜ ስለርሱ እንዲህ አሉ። "ይህ ባለጸጋ በድኆች ላይ ምንም ምን ርኅራኄ የሌለው ነው" ከእነርሱም አንዱ "እኔ ሔጄ ከእርሱ ምጽዋት ተቀብዬ ብመጣ ምን ትሰጡኛላችሁ" አላቸው እነርሱም አንተ ከእርሱ ምጽዋትን ካገኘህ ያልከውን እንሰጥሃለን አሉት በዚህም ነገር ከተከራከሩ በኋላ ወደ አንጢላርዮስ ቤት ሒዶ ምጽዋትን ለመነው አንጢላርዮስም ከመሶቡ እግር የደረቀ ለከት ዳቦ አንሥቶ በመበሳጨት ወርውሮ የድኃውን ራስ ፈቃው ድኃውም ወደ ባልንጀሮቹ ተመልሶ ያንን ለከት አሳያቸው።
🌹 በዚያቺም ሌሊት አንጢላርዮስ በሕልሙ ራእይን አየ እርሱ በፍርድ አደባባይ ቁሞ ሳለ የጠቆሩ ሰዎች ስለ ክፋቱ ብዛት ሲከራከሩት ብርሃን የለበሱ ሰዎች ደግሞ ከዚች ለከት ዳቦ በቀር በርሱ ዘንድ ያደረገውን ምጽዋት አላገኘንም ብለው ሲያዝኑ በሚዛንም በመዘኑዋት ጊዜ ከኃጢአቱ ሁሉ ተስተካከለች። በዚያንም ጊዜ ነቃ በልቡም "ሳልወድ የሠራሁት ይህን ያህል ጠቃሚ ከሆነ ወድጄ ብሠራውማ እጥፍ ድርብ የሆነ ዋጋ የማገኝ አይደለምን" አለ።
🌹 ከዚህም በኋላ ተነሥቶ ገንዘቡን ጥሪቱን ሁሉ አውጥቶ ለድኆችና ለችግረኞች መጸወተ። ገንዘቡንም ሁሉ ከጨረሰ በኋላ ከሩቅ ቦታ ድኆች መጥተው ምጽዋትን ለመኑት እርሱም ገንዘቡን ሁሉ እንደ ጨረሰ ነገራችውና እጅግ አዘኑ እንዳዘኑም አይቶ እንዲሸጡት ፈቀደላቸው እነርሱም ሸጡትና የሽያጩን ገንዘብ ተከፋፈሉ። በተሸጠበትም እንደባሪያ እያገለገለ ኖረ የጌታው ባሮችም በሚያሳዝኑት ጊዜ ብርሃናዊ ሰው ተገልጦ "አትዘን የተሸጥክበትን ዋጋ እኔ ተቀብዬዋለሁ እነሆ በእጄ ውስጥ አለና" ይለዋል።
🌹 ከዚህም በኋላ አስቀድሞ ከነበረበት የመጡ ሰዎች ሥራውን በገለጡበት ጊዜ በሥውር ሸሽቶ ወደ ከተማው በር ደረሰ በሩን የሚጠብቀውም ዲዳና ደንቆሮ ነበር። አንጢላርዮስም "በሩን ክፈትልኝ" በአለው ጊዜ ከአፉ በእሳት አምሳል ወጥቶ በረኛውን ነካው ያን ጊዜ አንደበቱ ተፈታ ጆሮዎቹም ሰሙ በሩንም ከፍቶለት ወደ በረሀ ሔደ በዚያም ገድሉን ፈጽሞ መስከረም 27 ቀን ዐረፈ።
🌹 ሰዎችም በአጡት ጊዜ ወደ በሩ መጡ በረኛውም የሆነውን ሁሉ ነገራቸው ከቅድስናውና ከተአምራቱም የተነሣ እጅግ አደነቁ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አንጢላርዮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 27 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
🌹 "#ሰላም_ለአንጢላርዮስ_ጳኵሲማ_ኅብስቱ። ዘይበሌዕ ለሲሲቱ። መድኃኒተ ነፍሱ ኮነቶ ወበቋዒተ ሎቱ። ያብአኒ ቤተ ፃማሁ እንተ ድኅነ ቦቱ። በአንጎግዎ ዘስኂት ኢይጥፋእ በከንቱ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_27።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "አኅለፍከነ ማእከለ እሳት ወማይ። ወአውጻእከነ ውስተ ዕረፍት። እበውእ ቤተከ ምስለ መባእየ"። መዝ65፥12-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 27፥1-26።
✝️ ✝️ ✝️
🌹 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወረከብናሁ ውስተ ኦመ ገዳም። ንበውዕ እንከሰ ውስተ አብያቲሁ ለእግዚአብሔር። ወንሰግድ ውስተ መካን በኃ ቆመ እግረ እግዚእነ"። መዝ 131፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 5፥8-26፣ ያዕ 2፥5-14 እና የሐዋ ሥራ 17፥1-10። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 19፥16-27። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
🌹 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #መስከረም ፳፯ (27) ቀን።
🌹 እንኳን #አስቀድሞ_በማንም_ላይ_ርኅራኄ የሌለው (ንፉግ) ለነበረ፤ በሕልሙ እግዚአብሔር በሳየው ራእይ ተመልሶ ስለ ምጽዋት ሲል ያለው ንብረት በሙሉ ከሰጠ በኋላ እራሱ ለሸጠ ለቀራጭች አለቃ ለነበረ #ለቅዱስ_አንጢላርዮስ_ለዕረፍት_በዓል መታሰቢያ፣ #በሐዋርያው_ቅዱስ_ጳውሎስ ትምህርት አምና ለተጠመቀች ያለ ደም መፍሰሰ ሰማዕት ለሆነች #ለቅድስት_ጤቅላ (ቴክላ) ለዕረፍቷ በዓል መታሰቢያ፣ #ለቅዱስ_ኤዎስጣቴዎስ_ለሁለት_ልጆቹና_ለሚስቱም ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል መታሰቢያ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ከመድኃኒታችን ከስቅለቱ #ከመድኃኔዓለም ከወራዊ ከመታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
🌹 #ሐዋርያዊት_ቅድስት_ጤቅላ፦ የዚች ቅድስት ወላጆቿ ከመቄዶንያ ሰዎች ውስጥ ባለጸጎች ናቸው እርሷንም እንደ ሀገራቸው ባህል በተግሣጽ በምክር አሳደጓት እነርሱ ጣዖትን የሚያመልኩ ናቸውና።
🌹 ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም ወደዚች አገር በደረሰ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲህ እያለ ሊአስተምር ጀመረ "ዐውቀው ድኆች የሆኑ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት ለነርሱ ናትና። ዛሬ የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው እነርሱ ደስ ይላቸዋልና።
ስለ ዕውነት የሚሰደዱ ብፁዓን ናቸው መንግሥተ ሰማያት ለእነርሱ ናትና። ሚስት እያላቸው እንደ ሌላቸው የሚሆኑ ብፁዓን ናቸው። እነርሱ የዘላለም ሕይወትን ይወርሳሉና"። ይህንንና ይህን የመሰለውን በሰማች ጊዜ ቅድስት ጤቅላ ከቤቷ ደርብ ሳትወርድ ያለ መብልና መጠጥ ሦስት ቀን ኖረች። እናቷም "ከቤትሽ ደርብ የማትወርጂ ለምንድን ነው እህልስ ለምን አትበዪም" አለቻት።
🌹 ከዚህም በኋላ በጭልታ ወረደች ለሚጠብቃትም ዘበኛ እንዳይናገርባት የወርቅ ወለባዋን ዋጋ ሰጠችውና ወደ ቅዱስ ሐዋርያ ጳውሎስ ሔደች። እርሱም በደስታ ተቀብሎ የክርስቶስን ሃይማኖት አስተማራት።
🌹 በማግሥቱም እናቷ እየፈለገቻት በመጣች ጊዜ ከቅዱስ ጳውሎስ ዘንድ አብራ ተቀምጣ አገኘቻት ከዚያም ወደ መኰንን ሒዳ ልጇን ክርስቲያን እንደሆነች ከሰሰቻት። መኰንኑም ከቅዱስ ጳውሎስ ጋራ እንዲያመጧት አዘዘ አስቀድመው ቅዱስ ጳውሎስን ወደ እሳት እንዲወረውሩት አዘዘ እግዚአብሔርም አዳነው። መኰንኑም የቅድስት ጤቅላን ቅጣት እንዲያዩ የሀገር ልጆችን ሰበሰበ ከዚህም በኋላ ወደ እሳት እንዲወረውሩዋት አዘዘ። በዚያን ጊዜ በክርስቶስ ማዕተብ ራሷን አማትባ ራስዋን በራስዋ ወደ እሳት ወረወረች ማንም ያያት ሳይኖር ከእሳት ውስጥ ወጥታ ወደ ቅዱስ ጳውሎስ ሔደች የራስዋን ጠጒር ቆርጣ ወገቧንም ታጥቃ ቅዱስ ጳውሎስን ተከተለችው።
🌹 መኰንኑም ደኅንነቷን በሰማ ጊዜ ያዛት ሃይማኖቷንም እንድትተው አስገደዳት አይሆንም ባለችውም ጊዜ አንበሶችና ድብ ከሚያድሩበት እንዲጨምሩዋት አዘዘ። እነርሱም ሰገዱላትና የእግሮቿን ትቢያ ላሱ። ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው መኰንኑና ወገኖቹ አመኑ አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠመቁ በክርስቶስም መንጋዎች ውስጥ ሆኑ።
🌹 እርሷ ቅድስት ጤቅላም ክብር ይግባውና የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌልን በማስተማር ቅዱስ ጳውሎስን እያገለገለችው ኑራ መስከረም 27 ቀን በሰላም ዐረፈች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስ ጤቅላ ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ትሩር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
🌹 #ቅዱስ_ኤዎስጣቴዎስ_ሁለቱ_ልጆቹና ሚስቱም፦ ይህ ቅዱስም ለሮም መንግሥት የጭፍራ አለቆች ከሆኑት ውስጥ ነው የቀድሞ ስሙ ቂዶስ ነው እግዚአብሔርንም አያውቅም ነበር ግን ብዙ ምጽዋትን በመስጠት ለድኆችና ለችግረኞች ይራራል ስለዚህም ክብር ይግባውና ጌታችን ድካሙ ከንቱ ሁኖ እንዲቀር አልወደደም።
🌹 በአንዲት ቀንም አውሬ ሊያድን ኤዎስጣቴዎስ ወደ ዱር ወጣ እርሱ አዳኝ ነውና ዋልያም አግኝቶ በቀስት ሊነድፈው ወደደ ያን ጊዜም በዋልያው በቀንዶቹ መካከል በመስቀል አምሳል ጌታ ተገለጸለት። የመስቀሉም ብርሃን እስከ ደመና ደርሶ ነበር ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በዚያ ብርሃን ውስጥ ተናገረው ስሙንም አስረዳው ከሚስቱና ከልጆቹ ጋር ወደ ኤጲስቆጶስ ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን እንዲጠመቁ አዘዘው።
🌹 ክብር ይግባውና ጌታችንም ከዚህ በኋላ ችግርና ፈተና እንደሚመጣበት በመጨረሻም ስለ ከበረ ስሙ ምስክር ሁኖ ደሙን አፍስሶ እንደሚሞት አስረዳው። ኤዎስጣቴዎስም ሰምቶ ከተራራው ወርዶ ወደ ቤቱ ሔደ። ጌታችን ያዘዘውንም ለሚስቱ ነገራት ከዚህም በኋላ ወደ ኤጲስቆጶሱ ሔደው ከልጆቻቸው ጋራ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቁ የቀድሞ ስሙንም ለውጦ ኤዎስጣቴዎስ ተባለ።
🌹 ከጥቂት ቀኖች በኋላ በዚያች አገር ታላቅ ችግር መጣ የኤዎስጣቴዎስም ገንዘቡ ሁሉ አልቆ ወንዶችና ሴቶች ባሮቹ ተበተኑ ወደሌላ አገርም ሊሰደድ ወዶ ልጆቹንና ሚስቱን ይዞ በመርከብ ተጫነ። ወደ ወደቡም በደረሱ ጊዜ መርከበኞች የመርከብ ዋጋ ከእርሱ ፈለጉ የሚሰጣቸው የመርከብ ዋጋ ባላገኘ ጊዜ ስለ መርከብ ዋጋ የመርከቡ ሹም ሚስቱን ወሰዳት የአታክልት ጠባቂም አደረጋት። ከዚያም ኤዎስጣቴዎስ እያዘነና እያለቀሰ ሁለቱን ልጆቹን ይዞ ሔደ ውኃ ወደ መላበትም ወንዝ ደረሰ አንዱንም ልጁን ከእርሱ ጋር ሊአሻግረው ይዞት ገባ አሻግሮትም ከወንዙ ዳር አኖረውና ሁለተኛውን ልጁን ሊአሻግረው ተመለሰ ግን አላገኘውም። ተኵላ ወስዶታልና ያሻገረውንም አንበሳ ነጥቆ ወሰደው ኤዎስጣቴዎስም ከሚስቱና ከልጆቹ ስለ መለየቱ ታላቅ ኀዘንን አዝኖ መሪር ልቅሶን አለቀሰ ምክሩ ታላቅ የሆነ ሥልጣን ያለው እግዚአብሔር ግን ሁሉንም በየአሉበት ያለ ጥፋት ጠበቃቸው።
🌹 ከዚህ በኋላም ኤዎስጣቴዎስ ወደ አንዲት አገር ሒዶ በዚያ የአትክልት ጠባቂ ሁኖ ብዙ ቀኖችን ኖረ። ከእነዚያ ቀኖችም በኋላ የሮም ንጉሥ ሙቶ በርሱ ፈንታ ለኤዎስጣቴዎስ ወዳጁ የሆነ ሰው ነገሠ ኤዎስጣቴዎስንም ፈለገው ግን አላገኘውም ኤዎስጣቴዎስንም ይፈልጉት ዘንድ ወደ ሀገሩ ሁሉ መልእክተኞችን ላከ። ከመልእክተኞችም አንዱ ኤዎስጣቴዎስ ወዳለበት ደርሶ በአታክልቶች ዘንድ አግኝቶት አወቀው እርስ በርሳቸውም ተሳሳሙ ከዚህም በኋላ ወደ ንጉሡ ወሰደው ንጉሡም በበጎ አቀባበል ተቀብሎ የጭፍራ አለቃ አድርጎ ሾመው።
🌹 ከዚህም በኋላ ንጉሡ ከሚገዛቸው አገሮች ሁሉ ወጣቶችን ሰብስቦ የጦር ሠራዊት ጭፍራ ያዘጋጅ ዘንድ ኤዎስጣቴዎስን አዘዘው እነዚያ ተኵላና አንበሳ የወሰዳቸው የኤዎስጣቴዎስ ሁለት ልጆቹ በአንዲት አገር አድገዋል። ግን እርስበርሳቸው አይተዋወቁም ወጣቶችንም የሚመለምሉ መልምለው ወደ አባታቸው ኤዎስጣቴዎስ አቀረቧቸው እርሱም ሳያውቃቸው የመዛግብት ቤት ጠባቂዎች አደረጋቸው።
🌹 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #መስከረም ፳፮ (26) ቀን።
🌹 እንኳን #ለእናታችን_ለእመቤታች_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም ለልጇ ለወዳጇ ለክብር ባለቤት ለጌታችን ለመድኃኒታችን ##ለኢየሱስ_ክርስቶስ ለስደታቸው መታሰቢያ #ለፈቃድ_ጾም_ለጽጌ ጾም (ለዘመነ ጽጌ) እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
🌹 #የዘመነ_ስደት_መታሰቢያ ለምን በዚህ ጊዜ ሆነ?
#ከመስከረም_26_እስከ_ህዳር_5።
🌹 እመቤታችን ከልጅዋ ጋር ስደትን የጀመረችው ጥር 3 ነው፥ አገረ ግብጽ የገባችው ግንቦት 24 ነው፥ በግብፅ እና በኢትዮጵያ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ከቆዩ በኋላ ስደቱ አብቅቶ ተመለሱ ብሎ መልአኩ ሲነግራቸው ካሉበት ተነስተው ቁስቋም ከተባለች ቦታ ኅዳር 6 ደርሰዋል ።
🌹#የስደት_መታሰቢያ_ለምን_በመነሻው_ጥር_3 አልሆነም?
ይህ ወቅት ዘመነ አስተርእዮ የደስታ ጊዜ ነው ታኅሣሥ 29 ልደቱን ጥር 11 ጥምቀቱን የምናከብርበትና በልደቱ እና በጥምቀቱ የተደረገልንን እያሰብን ደስ የምንሰኝበት ጊዜ በመሆኑ ለስደት መታሰቢያ ለማድረግ አይመችም።
🌹 #ግንቦት_24_አገረ_ግብፅ_የገባችበትን ይዘን ለምን ስደትን አናስብም?
🌹 ግንቦት 24 በዓለ ሃምሳን የምናከብርበት እንደመሆኑ በዚህ ወቅት ጌታችን በትንሳኤው የሰጠንን ነጻነት የምናስብብት ደስ የምንሰኝበት ጊዜ ስለሆነ መስገድ መጾም ስለማይፈቀድ የስደት መታሰቢያ ለማድረግ አይመችም።
🌹 ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 5 ዕፅዋት አበባን ፍሬን የሚያሳዩበት ወቅት ነው።
🌹 ወቅቱ ለምሳሌ የተመቸ ነውና።
"ትወጽእ በትረ እምሥርወ እሤይ ወየዓርግ ጽጌ እምኔሃ" ኢሳ 11፥1 እንዲል የዕሤይ የዘር ግንድ ከተባለች ከእመቤታች ጽጌ ጸኣዳ ወቀይህ የተባለ የፍጥረት ሁሉ ጌጥ ጌታችን የተገኘ ነውና በዚህ መስሎ ለማስተማር የሚያመች ወቅት ነውና። በተጨማሪም ጽጌ በእመቤታች ፍሬ በጌታችን ይመሰላል።
🌹 #አንድም፦ ተመለሰ ከማለት በፊት ተሰደደ ማለት ይቀድማል።
🌹 በዓመት ውስጥ ያሉት የወራት ቅድመ ተከተል ኅዳር 6 ከጥር 3 እና ከግንቦት 24 ይቀድማል። ኅዳር ላይ ከስደት ተመለሰ ብለን ካከበርን በኋላ ጥር ተሰደደ ግንቦት ግብፅ ገባ ብንል አመቺ አይደለም።
ስለዚህ ከጥር 3 ወይም ከግንቦት 24 ይልቅ ኅዳር 6 መታሰቢያ ለማድረግ አመቺ በመሆኑ ቤተክርስቲያን በዚህ ወቅት የስደቱን መታሰቢያ ታደርጋለች።
🌹 በቅዱስ ያሬድ አባባል ስደት #ከመስከረም_26_እስከ_ጥቅምት_20 ሲነገር፤ #ከጥቅምት_21_እስከ_ኅዳር_6 ድረስ ሚጠት (መመለሳቸው) ይነገራል። ይኼውም ተመየጢ ተመየጢ ሰላመ ሰጣዊት የሚለው ሰላም እንዲቀርብ በማኅሌት ስለተወሰነ ነው። ምንጭ፦ አምኃ ሥላሴ መኩሪያ ተስፋዬ።
🌹 ጾሙ ከአገራችን ኢትዮጵያ ጦርነትን የሚያጠፋ እና ሰላም፣ ፍቅርን አንድነትንና መተሳሰብ የሚያመጣ ያድርግልን። መልካም ጾም ለሁላችንም ይሁንልን።
@Teamihokidusan
🌹 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌹
🌹 #መስከረም ፳፮ (26) ቀን።
🌹 እንኳን #ለመላእክት_አለቃ_ለቅዱስ_ገብርኤል ወደ በራክዩ ልጅ ወደ #ቅዱስ_ዘካርያስ_ለተላከበት #መጥምቀ_መለኮትን ከእርሱ ስለ መወለዱ ለአበሰረበት፤ ( #ለመጥምቀ_መለኮት #ለቅዱስ_ዮሐንስ_ለጽንሰት_በዓል)ና ለሰማዕቱ #ለቅዱስ_ዮስጦስ_ልጅ_ለቅዱስ_አቦሊ ለሥጋው ፍልሰት በዓል በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከዐሥር_ሽህ_ሰማዕታት፣ #ከቅድስት_አጋታ_ከበርባራ_ከዮልያና፣ #ከአባት_ጊዮርጊስም_ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
🌹 #የየመላእት_አለቃ_ቅዱስ_ገብርኤል #ለቅዱስ_ዘካርያስ_የመጥምቀ_መለኮትን_የቅዱስ_ዮሐንስ_መጸነስ_እዳበሰረው፦ ስሙ የተመሰገነ እግዚአብሔር ልጅን ይሰጠው ዘንድ አስቀድሞ ሁል ጊዜ በመጸለይ ወደ እግዚአብሔር ይማልድ ነበር። ልጅ ያልወለደውን እግዚአብሔር ብዙ ተባዙ ምድርን ምሉዋት ያለውን በረከት ያጣ ነው በማለት እስራኤል ይገዳደሩት ነበርና።
🌹 ልመናውንም ሰማ በቤተ መቅደስም ቁሞ ዕጣንን ሲያሳርግ መልአኩን ላከለት በከበረ ወንጌልም እንደተባለ መንገዱን ይጠርግ ዘንድ በንጉሥ ክርስቶስ ፊት እንደሚሔድ የተነገረለት ታላቅ ነቢይ ዮሐንስ ከእርሱ መወለዱን አበሠረው።
🌹ዘካርያስም የሰውነቱን መድከም የመውለጃውም ዘመን እንዳለፈና ፈጽሞ እንዳረጅ የሚስቱም እንዲሁ ዘመኗ እንዳለፈና ፈጽማ እንዳረጀች መካንም እንደሆነች ያውቃልና ስለዚህ ይህ ነገር እንዴት ይሆንልኛል "እኔ ያረጀሁ ሽማግሌ ነኝ ሚስቴም እንዲሁ ዘመኗ አልፎ መካን ሁናለች" ብሎ የእግዚአብሔርን መልአክ ተከራከረው።
🌹 መልአኩም "እኔ ይህን ልነግርህ ከእግዚአብሔር ዘንድ ወዳንተ ተልኬ ነበር ልትጠራጠር ባልተገባህም ነበር አሁንም ይህ በጊዜው እስቲፈጸም ዲዳ ሁነህ መናገር ይሳንሃል" ብሎ ገሠጸው። ዘካርያስም የወልደ እግዚአብሔርን መንገድ የሚጠርግ ዮሐንስ እስከሚወለድበት ጊዜ ድረስ ዲዳ ሆነ።
🌹 በሚገረዝበትም ቀን የሕፃኑን አባት ዘካርያስን የሕፃኑን ስም ምን ብለው እንደሚሰይሙት ጠየቁት እርሱም ብራና ለምኖ "ስሙ ዮሐንስ ነው" ብሎ ጻፈ በዚያም ጊዜ አንደበቱ ተፈትቶ እግዚአብሔርን አመሰገነው። ስለ ልጁ ዮሐንስም እርሱ የልዑል ነቢይ እንዲባል መንገዱንም ይጠርግ ዘንድ በእግዚአብሔር ፊት እንደሚሔድ ትንቢት ተናገረ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ዘካርያስና በቅድስት ኤልሳቤጥ በልጃቸው በቅዱስ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
🌹 "#ሰላም_ለፅንሰትከ_በሠሌዳ_ከርሣ_ዘተገልፈ። ለኤልሳቤጥ እምከ እምድኅረ ወርኃ ኀለፈ። ዮሐንስ መልአክ እንተ ትኴንን አእላፈ። ከመ እፈጽም ዘወጠንኩ ስብሐቲከ ትሩፈ። በውስተ ዕዝንየ አልኆስስ መጽሐፈ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_26።
✝️ ✝️ ✝️
🌹 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "በቅድመ መላእክቲከ እዜምር ለከ። ወእሰግድ ውስተ ጽርሐ መቅደስከ። ወእገኒ ለስመከ"። መዝ137፥1-2። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 12፥1-11፣ 1ኛ 2፥20-ፍ.ም እና የሐዋ 10፥1-9። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥1-23። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ኤጲፋንዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ገብርኤል በዓልና የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ የጽንሰት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።
🌼 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼
🌼 #መስከረም ፳፬ (24) ቀን።
🌼 እንኳን #ከሰባ_ሁሉቱ_አርድእት ለአንዱ ለሐዋርያው #ለቅዱስ_አድሊጦስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል፣ #ከላይኛው_ግብጽ ለሆኑ ለ#ቅዱስ_አባት_ለመነኰስ_ለአቡነ_ጎርጎርዮስ ለዕረፍት በዓል በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
🌼 #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት_አንዱ_የሆነው #ሐዋርያው_ቅዱስ_አድሊጦስ፦ ይህም ሐዋርያ ትውልዱ ከአቴና አገር ከታላላቆቿና ከምሁራኖቿ ነው እርሱም ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ አገለገለውም።
🌼 አጽናኝ የሆነ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በሃምሳኛው ቀን ከተቀበለ በኋላ ወደ ብዙዎች አገሮች ሒዶ ሕይወት የሆነ ወንጌልን ሰበከ መግኒን ወደሚባልም አገር ደርሶ በውስጧ የከበረ ወንጌልን ሰበከ የብዙዎችንም ልቦና ብሩህ አድርጎላቸው ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ሕይወት የሆኑ የወንጌልንም ትእዛዞች አስተምሮ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው ።
🌼 ከዚህም በኋላ ከእሳቸው ዘንድ ወጥቶ ወደ አቴና አገር ተመለሰ በውስጧም የከበረ ወንጌልን አስተማረ በዚያን ጊዜም በደንጊያ ወገሩት ጽኑዕ የሆነ ሥቃይንም አሠቃዩት። ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ወረወሩትና በዚያ ተጋድሎውንና ምስክርነቱን ፈጽሞ የሕይወት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዱስ አድሊጦስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
🌼 #አቡነ_ጎርጎርዮስ_ዘላዕላይ_ግብጽ፦ የዚህም የቅዱስና የተመሰገነ ጎርጎርዮስ ወላጆቹ ደጎች ናቸው በዚህ ዓለም ገንዘብም እጅግ ባለጸጎች ነበሩ ይህን ልጃቸውን ጎርጎርዮስንም በበጎ አስተዳደግ አሳደጉት። መንፈሳዊ የሆነ የቤተ ክርስቲያን ትምህርትን ሁሉ ሥጋዊም የሆነ ጥበብንና ቋንቋን አስተማሩት።
🌼 ከዚህም በኋላ የሀገራቸው ኤጲስቆጶስ ወደ ሆነ ወደ አባ ይስሐቅ ወሰዱት እርሱም እጁን በላዩ ጭኖ አናጒንስጢስነት ሾመው።
🌼 ከዚህም በኋላ ወላጆቹ ሊአጋቡት አሰቡ እርሱ ግን ይህን ሥራ አልወደደም ሁለተኛም ወደ ጳጳስ ወስደውት ፍጹም ዲቁናን ተሾመ ወደ አባ ጳኲሚስም አዘውትሮ በመሔድ ከእርሱ የእግዚአብሔርን ሕግ የሚማር ሆነ ከወላጆቹም ብዙ ገንዘብን ወስዶ ወደ አባ ጳኲሚስ አቅርቦ በገዳማቱ ለሚሠሩ ሕንፃዎች ሥራ ያደርግለት ዘንድ ብዙ ልመናን ለመነው እርሱም ተሳትፎ እንዲሆንለት ለሕንፃ ቤተ ክርስቲያንና ለመነኰሳት ቤት መሥሪያ አደረገለት ።
🌼 ከዚህም በኋላ ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዓለምን ትቶ ጥሪቱንና ገንዘቡን ሁሉ ንቆ በመተው ወደ ቅዱስ አባ ጳኲሚስም ሒዶ የምንኲስና ልብስን ለብሶ በጾም በጸሎት በመትጋት በመስገድ ከትሕትና፣ ከቅንነት፣ ከፍቅር ጋር ይጋደል ጀመረ አርአያነቱንና ምሳሌነቱን በአዩ ጊዜ ከእርሱ ፈሪሀ እግዚአብሔርን ተምረው አመንዝራዎች የከፋ ሥራቸውን እስከ ተውና ንስሐም ገብተው ንጹሐንም እስከ ሆኑ ድረስ ተጋደሉ። ከአባ ጳኲሚስም ዘንድ ዐሥራ ሦስት ዓመት ኖረ።
🌼 አባ መቃርስም ወደ አባ ጳኲሚስ በመጣ ጊዜ ሰውነቱን በማድከም ታላቅ ተጋድሎን እየተጋደለ ጥቂት ቀኖች ኖረ ከዚያም በኋላ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሊመለስ ወደደ አባ ጳኲሚስም ከአባ መቃርስ ጋር እንዲሔድ አባ ጎርጎርዮስን አዘዘው እርሱም አብሮ ሔደ በእርሱም ዘንድ ብዙ ዘመናት ኖረ ።
🌼 ከዚህም በኋላ በዋሻ ብቻውን ይኖር ዘንድ እንዲአሰናብተው የከበረ አባ መቃርስን ለመነው እርሱም "እንደ ወደድክ አድርግ" አለው። ያን ጊዜ ወደ ተራራ ሒዶ ታናሽ ዋሻ ቆርቁሮ በውስጧ ሰባት ዓመት ኖረ አባ መቃርስም በየዓመቱ ሁለት ጊዜ መጥቶ ይጎበኘዋል አንደኛ ለከበረ የልደት በዓል ሁለተኛ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተነሣባት በትንሣኤ በዓል ቀን ከርሱ ጋርም ሥጋውንና ደሙን ተቀብሎ ወደ ቦታው ይመለሳል። አባ መቃርስም ስለ ሥራው ሁሉ ይጠይቀዋል እርሱም የሚያየውንና በእርሱ የሆነውን ሁሉ ይገልጽለታል አባ መቃርስም ሊሠራው የሚገባውን የምንኲስና ሥራን ይሠራ ዘንድ ያዘዋል ።
🌼 በተጋድሎም ውስጥ ሃያ ሁለት ዓመታት ሲፈጽሙለት ከዚህ የድካም ዓለም ያሳርፈው ዘንድ እግዚአብሔር ፈቅዶ መልአኩን ላከለት እርሱም ከሦስት ቀን በኋላ ከዚህ ከኀላፊው ዓለም ወጥተህ ወደ ዘላለም ሕይወት ትገባለህ አለው።
🌼 አባ ጎርጎርዮስም በአስቄጥስ ገዳም ያሉ አረጋውያንን አስጠራቸውና ተሳለማቸው በጸሎታቸውም እንዲአስቡት ለመናቸው እነርሱም ደግሞ በእግዚአብሔር ዘንድ እንዲአስባቸው ለመኑት ከሦስት ቀንም በኋላ አርፎ ወደ ዘላለም ሕይወት ገባ።
✝ ✝ ✝
🌼 "#ሰላም_ለጎርጎርዮስ ወለደብራጦስ አያዩ። ዘውኂዘ መንፈስ ሰትየ #ከመ_ሐዋርያት_ሰትዩ። ሶበ ገደፈ ቅድሜሁ እስከ ዘዕለት ሲሳዩ። ዘሎቱ ለሊሁ ወዘአበዊሁ አጥረዩ። ሥርዓተ ማኅበር ሐነፀ ጳኵሚስ በንዋዩ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_24።
✝ ✝ ✝
🌼 #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኀይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥16-ፍ.ም።
✝ ✝ ✝
🌼 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አፅናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ። ወውስተ ፀሓይ ሤመ ጽላሎቶ"። መዝ18፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 2፥12-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 2፥20-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 10፥39-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቅዳሴ ነው መልካም የሐዋርያው ቅዱስ አድሊጦስ እና የአቡነ ጎርጎርዮስ የዕረፍታቸው በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
🌼 በአንዲት ዕለትም የጣዖቶቻቸው በዓል በሆነ ጊዜ በሽልማት ሁሉ ሸለሙአቸው በመብራቶችና በሥዕሎችም ዘንባባም አስጌጧቸው በማግሥቱም መጥተው በዓላቸውን ለማክበር በዋዜማው አዘጋጅተው የጣዖታቱን ቤቶች ዘግተው ወደ ቤታቸው ገቡ። ቅዱስ ዮልዮስም ጣዖታቱን ያጠፋቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነ በዚያን ጊዜም ጌታችን መልአኩን ልኮ የጣዖታቱን ራሶቻቸውን ቆረጠ ፊቶቻቸውንም በፍም አጠቆረ ሽልማታቸውንና ዘንባባውን የጣዖቱን ቤት ሥርዓት ሁሉ አቃጥሎ አጠፋ።
🌼 ማግሥትም በሆነ ጊዜ ለአማልክቶቻቸው እንደ ልማዳቸው በዓልን ሊአከብሩላቸው በከበሩ ልብሶች ተሸልመው ሲመጡ ተጐሳቁለው ጠፍተው አዩአቸው የጣዖቶቻቸውን ድካማቸውን አወቁ። እንዲህም አሉ "አማልክቶቻችን ራሳቸውን ማዳን ያልቻሉ እኛን ያድኑ ዘንድ እንዴት ይችላሉ" ይህንንም ተናግረው ከአትሪብ መኰንን ጋር በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድነት አመኑ።
🌼 ከዚያም ደግሞ ቅዱስ ዮልዮስ ጡዋ ወደሚባል አገር ሔደ ከርሱም ጋር የገምኑዲ መኰንንና የአትሪብ መኰንን አሉ የጡዋ መኰንን ወደ ሁነ ወደ እስክንድሮስ ቀርቦ በፊቱ ክብር ይግባውና በጌታችን ስም ታመነና እንዲህ አለው "ገድሌን ፈጽምልኝ ራሴንም እንዲቆርጡ እዘዝና የምስክርነት አክሊልን ተቀብዬ ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እንድሔድ"። እስክንድሮስም "እኔ አላሠቃይህም በአንተ ላይም ምንም ክፉ ነገር አላደርግም" አለው።
🌼 ቅዱስ ዮልዮስም አምስት መቶ የሚሆኑ አገልጋዮቹን ሰይፎቻቸውን መዝዘው እስክንድሮስን እንዲአስፈሩት አዘዛቸው በዚያንም ጊዜ በእስክንድሮስ ላይ ተነሥተው "ለክብር ባለቤት ክርስቶስ ምስክሮቹ እንሆን ዘንድ የሁላችንም ራሶቻችንን እንዲቆርጡ ካላዘዝክ እኛ እንገድልሃለን" አሉት። ዳግመኛም ርኵስ መንፈስ እንዲጫንበት ቅዱስ ዮልዮስ አዘዘው ወዲያውኑ በመኰንኑ በእስክንድሮስ ላይ ተጫነበት በዚያንም ጊዜ ራሶቻቸውን ይቆርጧቸው ዘንድ በጽሑፍ አዘዘ ሁሉንም ቅዱሳን ሰማዕታትን ቆረጧቸው።
🌼 እሊህም ቅዱስ ዮልዮስ፣ ልጁም ቴዎድሮስ፣ የከበረ ወንድሙ ዮንያስ፣ አምስት መቶ አገልጋዮቹ የገምኑዲና የአትሪብ መኰንኖች ብዙዎች ሕዝቦችም የሁሉም ቁጥራቸው አንድ ሺህ አምስት መቶ ነው። በዚያች ቀን ከቅዱስ ዮልዮስ ጋር በሰማዕትነት የሞቱ ናቸው የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ።
🌼 የቅዱስ ዮልዮስን የልጁንና የወንድሙን ሥጋ አንሥተው ወደ እስክንድርያ አገር አደረሱ እርሱ በውስጧ ነዋሪ ሁኖ ነበርና ትውልዱ ግን አቅፋሐስ ከሚባል አገር ነው በአማረ ቦታ ውስጥም አኖሩአቸው። ከዚያም በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያንን ሠሩላቸው ከእርሳቸው ታላላቅ የሆኑ ድንቆች ተአምራት ተደረጉ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሁሉ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 22 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
🌼 "#ሰላም_ለኮቶሎስ_አኅወ_እክሱ_ብፅዕት። ወፍቁረ ጣጦስ ሰማዕት። ሶበ አተበ በመስቀል ትእምርተ ሕይወት። መጠነ ዐሠርቱ ወክልኤቱ በእመት። እምዐውደ ምኵናን ሰሰለ እሳት"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_22።
✝ ✝ ✝
🌼 #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ አቡየ ገደፉኒ። ወእግዚአብሔር ተወከፈኒ። ምርሀኒ እግዚኦ ፍኖተከ"። መዝ 26፥10-11 ወይም መዝ 33፥19። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 4፥7-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 4፥12-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 19፥8-11። የሚነበበው ወንጌል ማር 13፥9-14። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቅዳሴ። መልካም በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
🌼 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼
🌼 #መስከረም ፳፪ (22) ቀን።
🌼 እንኳን #ለፋርስ_ንጉሥ_ለሳቦር_ልጆች ለከበሩ #ለቅዱስ_ኮቶሎስና_ለእኅቱ_ቅድስት_አክሱ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል፣ ለከበረ #ለቅዱስ_ዮልዮስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል በሰላም አደረሰን። በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ #ከሰማዕት_ከቅዱስ_ባላን ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
🌼 #የፋርስ ንጉሥ የሳቦር ልጆች ሰማዕታት ቅዱስ ኮቶሎስና እኅቱ ቅድስት አክሱ፦ ለቅዱስ ኮቶሎስም ጣጦስ የሚባል ክርስቲያን ወዳጅ አለው ይህም ንጉሥ ሳቦር እሳትን የሚያመልክ ነው ብዙዎች ምእመናንን ስለሚያሠቃያቸው ክብር ይግባውና የክርስቶስን ስም ይጠራ ዘንድ በዚያ ወራት የደፈረ የለም።
🌼 ይህም ጣጦስ በአንዲት አገር ላይ ገዥ ነበር እርሱ ክርስቲያን እንደሆነ በንጉሡ ዘንድ ወነጀሉት። ንጉሡም ስለርሱ የተነገረው እውነት እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ያረጋግጥ ዘንድ ሌላውን መኰንን ወደርሱ ላከ። ሁለተኛም ክርስቲያንን ያገኘ እንደሆነ ጽኑዕ ሥቃይ እንዲያሠቃይ አዘዘው።
🌼 የንጉሥ ልጅ ኮቶሎስም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ወዳጁ ጣጦስ ወደአለባት ወደዚያች አገር ሔደ ያ መኰንንም በደረሰ ጊዜ ጣጦስን በንጉሥ እንደ ወነጀሉት እንዲሁ ክርስቲያን ሁኖ አገኘው በዚያን ጊዜም የእሳት ማንደጃ ሠርተው ጣጦስን እንዲአቃጥሉት አዘዘ ቅዱስ ጣጦስ ግን በመስቀል ምልክት በእሳቱ ላይ አማተበ እሳቱም የኋሊት ተመልሶ ጠፋ።
🌼 ኮቶሎስም ይህን ተአምር በአየ ጊዜ እጅግ አድንቆ ጣጦስን "ወንድሜ ሆይ ይህን ሥራይ እንዴት ተማርክና አወቅህ" አለው። ጣጦስም ይህ "ከሥራይ አይደለም ክብር ይግባውና ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ይህ ድንቅ ተአምር እንጂ" ብሎ መለሰለት። ኮቶሎስም "እኔ በክርስቶስ የማምን ከሆንኩ እንደዚህ ልሠራ እችላለሁን?" አለው ጣጦስም እንዲህ ብሎ መለሰለት "በእርሱ ካመንክበት ከዚህ የሚበልጥ ተአምራት ታደርጋለህ"።
🌼 በዚያንም ጊዜ ቅዱስ ኮቶሎስ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ በዚያን ጊዜም ነበልባሉ እጅግ ከፍ ከፍ እስከሚል እሳቱን አነደዱ ቅዱስ ኮቶሎስም ቀረብ ብሎ በእሳቱ ላይ በመስቀል ምልክት አማተበ እሳቱም ወደ ኋላ ዐሥራ ሁለት ክንድ ተመለሰና ጠፋ።
🌼 ከዚህም በኋላ መኰንኑ ወደ ንጉሥ ሳቦር ከመኰንኑ ከጣጦስና ከልጁ ከኮቶሎስ የሆነውን ሁሉ ጻፈ ንጉሡም ሰምቶ ጭፍራ ልኮ አስቀረባቸው የቅዱስ ጣጦስንም ራሱን በሰይፍ ቆረጠውና የሰማዕትነትን አክሊል ተቀበለ። ልጁን ቅዱስ ኮቶሎስን ግን ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃየውና ደግሞ እንዲአሠቃየው ለሌላ መኰንን ሰጠው እርሱም ብዙ ካሠቃየው በኋላ አሠረው። እኅቱም አክሱ ወደ እሥር ቤት ወደርሱ መጣች ወደ ቀድሞ ሥራው እንዲመለስ ትሸነግለው ዘንድ አባቷ ልኳታልና። እርሱ ግን እኅቱን ገሠጻት መከራት የቀናች ሃይማኖትንም አስተማራት ያን ጊዜም ከስኅተቷ ተመልሳ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነች።
🌼 ከዚህም በኋላ ወንድሟ ቅዱስ ኮቶሎስ ወደ አንድ ቄስ ላካት እርሱም የክርስትና ጥምቀትን በሥውር አጠመቃት። ወደ አባትዋም ተመልሳ እንዲህ አለችው "አባቴ ሆይ ለእኔና ለወንድሜ ለኮቶሎስ የሆነው ላንተ ቢደረግልህ ይሻልሃል ክብር ይግባውና ሰማይና ምድርን በውስጣቸውም ያለውን ሁሉ ከፈጠረ ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለምና"። ይህንንም ነገር አባቷ ከእርሷ በሰማ ጊዜ በእርሷ ላይ እጅግ ተቆጥቶ ነፍሷን በእግዚአብሔር እጅ እስከ ሰጠች ድረስ ጽኑዕ ሥቃይን እንዲአሠቃዩአት አዘዘ በዚህም ምስክርነቷን ፈጽማ የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለች።
🌼 ወንድሟን ቅዱስ ኮቶሎስን ግን በፈረሶች ጅራት ውስጥ አሥረው በተራራዎች ላይ አስሮጧቸው ሥጋውም ተቆራርጦ ተበተነ ነፍሱንም በፈጣሪው እጅ ሰጠ። የቀረ ሥጋውንም ወደ ሦስት ቆራርጠው የሰማይ ወፎች ይበሉት ዘንድ በተራራ ላይ ጣሉት በእንደዚህም ሁኔታ ምስክርነቱን ፈጽሞ የሕይወት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።
🌼 ወታደሮችም ሲመለሱ የሰማዕታትን ሥጋ ይወስዱ ዘንድ በሀገር አቅራቢያ ያሉ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን እግዚአብሔር አዘዛቸው እነርሱም በሌሊት ሔደው የቅዱሳን ሰማዕታትን ሥጋቸውን ወስደው በታላቅ ክብር ገነዙአቸው እንደ በረዶም ነጭ ሁነው አግኝተዋቸዋልና። የመከራው ወራትም እስቲፈጸም ድረስ በመልካም ቦታ አኖሩአቸው።
🌼 ከዚያም በኋላ ያማረች ቤተ ክርስቲያን ተሠርታላቸው የቅዱሳን ሥጋቸውን በዚያ አኖሩ ከሥጋቸውም ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
🌼 #ሰማዕቱ ቅዱስ ዮልዮስ፦ ይህም ቅዱስ አቅፋሐስ ከሚባል አገር ነው ክብር ይግባውና ጌታችንም ስለ ቅዱሳን ሰማዕታት ለሥጋቸው እንዲአስብ ገድላቸውንም እንዲጽፍ ሥጋቸውንም ገንዞ እየአንዳንዱን ወደ ሀገራቸው እንዲልክ ያቆመው ነው።
🌼 እግዚአብሔርም በመኳንንቱ ልብ መታወርን ስለ አመጣ ለሰማዕታት ይህን ያህል በጎ ሥራ ሲሠራ ምንም ነገር አይናገሩትም ስለ ጣዖት አምልኮም አያስገድዱትም ነበር። ጽሕፈትም የሚያውቁ ሦስት መቶ አገልጋዮች አሉት እነርሱም የሰማዕታትን ገድላቸውን እየተከታተሉ ይጽፋሉ። በመሠቃየትም ሳሉ ሰማዕታትን ያገለግላቸዋል በቊስላቸውም ውስጥ መድኃኒት ያደርግላቸዋል ሰማዕታትም ይመርቁታል እንዲህ ብለውም ትንቢት ይናገሩለት ነበር። "አንተም ክብር ይግባውና ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ደምህ ይፈስ ዘንድ አለህ" ከቅዱሳን ሰማዕታትም ጋራ ትቈጠራለህ።
🌼 የከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ የግዛቱ ዘመን በተፈጸመ ጊዜ ዮልዮስን ከቅዱሳን ሰማዕታት ከቁጥራቸው አንድ ሊአደርገው ወዶ ቅዱሳን ሰማዕታትም ትንቢት እንደተናገሩለት በመኰንኑ ፊት ስለ ከበረ ስሙ ይታመን ዘንድ ለግብጽ አገር ደቡብ ወደሆነች ወደ ገምኑዲ ወደ መኰንኑ አርማንዮስ እንዲሔድ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዘዘው።
ወዲያውኑ ተነሥቶ ሔደ ከዚያም ደርሶ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ መኰንኑም ታላቅ ሥቃይን ብዙ ጊዜ አሠቃየው እግዚአብሔርም ያለ ጥፋት በጤና ያነሣው ነበር። ከዚህም በኋላ ምድር አፍዋን ከፍታ ጣዖታቱን ትውጣቸው ዘንድ ቅዱስ ዮልዮስ ክብር ይግባውና ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ወዲያውኑ አፍዋን ከፍታ ሰብዓ ጣዖታትን መቶ ሠላሳ የሆኑ ካህናቶቻቸውን ዋጠቻቸው።
🌼 በዚያንም ጊዜ ቅዱስ ዮልዮስን አምጥተው ለአማልክት በግድ እንዲአሰግዱት መኰንኑ አዘዘ ጣዖታቱን ግን ከካህናቶቻቸው ጋር ጠፍተው አገኙአቸው በዚያ ያሉ ሕዝቦችም ይህን አይተው እጅግ አደነቁ። ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አመኑ መኰንኑ አርማንዮስም ጣዖታቱ ከካህናቶቻቸው ጋር እንደ ጠፉ በአየ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ። ከቅዱስ ዮልዮስም ጋር ወደ አትሪብ ሔደው በመኰንኑ ፊት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመኑ የአትሪብ መኰንን ግን ቅዱስ ዮልዮስን እጅግ ጭንቅ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው ክብር ይግባውና ጌታችንም ያለ ጥፋት ያነሣው ነበር።
+1
#EOTC🕯
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በምንጃር ወረዳ በአረርቲ ከተማ በደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በተከሰተውና ከ30 በላይ ለሚሆኑ ምዕመናን ህልፈት ምክንያት በሆነው አደጋ የተሰማቸውን ጥልቅ ሃዘን ገልጸዋል።
ቅዱስነታቸው ፥ " በአደጋው በሞተ ሥጋ ለተለዩን ወገኖቻችን ዕረፍተ ነፍስን በአደጋው የአካል ጉዳት ለደረሰባቸው ሁሉ ምሕረትን በመለመን ለተጎጂ ቤተሰቦችና ለመላው ምዕመናን መጽናናትን ይስጥልን " በማለት አባታዊ የኃዘን መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን
የቀድሞ አባላችን ናትናኤል ጉልማህ ድንገተኛ የኤሌክትሪክ አደጋ ደርሶበት በአለርት ሆስፒታል ተኝቶ ሰርጀሪ ሊሠራለት ስለሆነ ሁላችንም 50 ብር አዋተን እሑድ ጥቅምት 2 ከቅዳሴ በኃላ 03:00 አብረን እንሄዳለን ላልሰሙት በማሠማት እንድንገኝ በልዑል እግዚአብሔር ስም መልዕክት እናስተላልፋለን ወንድማችንን እግዚአብሔር ይማርልን አሜን!!!
+2
" ኃዘኑ የአረርቲ ደብረ ገነት ማርያም አገልጋይ ካህናትና የከተማዋ ምእመናንን ብቻ ሳይሆን የመላው ኦርቶዶክሳዊያን ኃዘን ነው " - ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ
የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ በአረርቲ ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ርብራብ የእንጨት ተደርሞሶ ሕይወታቸውን ባጡ ምእመናን የተሰማቸውን ጥልቅ ኃዘን ገለጹ።
" የቤተ ክርስቲያኑ ግንባታ ተጠናቆ ምርቃቱን በጉጉት እየጠብቀን ባለንበት ይህ አስከፊ ኀዘን በመከሰቱ ጥልቅ ኃዘን ተሰምቶናል " ብለዋል።
" ኀዘኑ የአረርቲ ደብረ ገነት ማርያም አገልጋይ ካህናትና የከተማዋ ምእመናንን ብቻ ሳይሆ የመላው ኦርቶዶክሳዊያን ኃዘን ነው በደረሰው ጉዳትም ልባችን ተሰብሯል " ያሉት ብፁዕነታቸው ለካህናቱና ለሕዝበ ክርስቲያኑ መጽናናትን ተመኝተዋል።
" በአደጋው ሕይወታቸውን ያጡ ወገኖቻችን የቅዱሳን አምላክ ነፍሳቸውን በደጋጎቹ ቅዱሳን አባቶቻችን አጠገብ ያሳርፍልን ጉዳት ደርሶባቸው በጤና በሆስፒታል በሕክምና ለሚገኙ ወገኖቻችን ፈጣሪ በምሕረቱ እንዲጎበኛቸው እንጸልያለን " ብለዋል። #EOTCTV
🌼 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼
🌼 #መስከረም ፳፩ (21) ቀን።
🌼 እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት ለአንዱ ለሐዋርያው #ለቅዱስ_ጢባርዮስ_ለዕረፍቱ መታሰቢያ በዓል፣ #ለቅዱስ_ቆጵርያኖስና_ለድንግሊቱ #ቅድስት_ዮስቴና ሰማዕትናት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
🌼 #በዚችም_ቀን_ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት የአንዱ ሐዋርያ #የቅዱስ_ጢባርዮስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው። የሐዋርያው ቅዱስ ጢባርዮስ በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
🌼 #ቅዱስ_ቆጵርያኖስና_ድንግሊቱ_ቅድስት_ዮስቴና፦ ይህም ቅዱስ ቆጵርያኖስ አስቀድሞ ከሀዲና ሥራየኛ ነበር እርሱም ለሥራየኞች ሁሉ አለቃቸው ነው። በሥራዩም ሥራ ከመመካቱ ብዛት የተነሣ በሥራይ የሚበልጠው ካለ ሊያይና ከዚያ ሊማር ከሌለ ግን በእነርሱ ላይ ሊመካባቸው ወደ አንጾኪያ አገር ሔደ።
🌼 ቆጵርያኖስም ወደ አንጾኪያ ከተማ በደረሰ ጊዜ ወሬው ተሰማ በአንጾኪያም ከተማ ከሀገር ታላላቆች ተወላጅ የሆነ አንድ ጐልማሳ አለ እርሱም ላህይዋ የሚያምር አንዲቷን ድንግል ብላቴና ተመኛት ወደ ቤተ ክርስቲያን በምትሔድ ጊዜ እያያት በእርሷ ፍቅር ልቡ እንደ እሳት ተቃጠለ በምንም በምን ሊአገኛት አልተቻለውም ገንዘብ በመስጠትም ቢሆን ወይም በማስፈራራት ወይም በሥራይ ሥራ አልሆነለትም።
🌼 የቆጵርያኖስም ወሬው በተሰማ ጊዜ እርሱ ከሥራየኞች ሁሉ እንደሚበልጥ ስለርሱ ተነግሮአልና ያም ድንግል ዮስቴናን የተመኛት ጐልማሳ ወደ ቆጵርያኖስ ሒዶ በልቡ ያለውን ጉዳዩን ድንግሊቱን ዮስቴናን እንደተመኛትና እርሷን ማግኘት እንደተሳነው ነገረው ቆጵርያኖስም እኔ የልብህን ፍላጎት እፈጽምልሃለሁ አትዘን አለው።
🌼 ከዚያም በኋላ ያን ጊዜ ዮስቴናን ወደርሱ ያመጧት ዘንድ በሥራዩ የአጋንንትን ሠራዊት ወደርሷ ላከ እነዚያም አጋንንት ወደርሷ በቀረቡ ጊዜ እርሷን መውሰድ አልቻሉም ከጸሎቷ የተነሣ ይቃጠላሉና እንዲህም ብዙ ጊዜ ላካቸው ግን ወደርሱ ሊያመጧት አልቻሉም ቆጵርያኖስም ሁሉንም አጋንንት ጠርቶ ድንግል ዮስቴናን ካላመጣችሁልኝ እኔ ከእናንተ ተለይቼ ክርስቲያን እሆናለሁ አላቸው።
🌼 ከዚህም በኋላ የሰይጣናት አለቃ ሊሸነግለው አሰበ አንዱንም ሰይጣን ከሰይጣናት ውስጥ በዮስቴና አምሳል ተመስሎ ለቆጵርያኖስ እንዲታየው አደረገ። ሰይጣኑም አለቃው እንዳዘዘው እንዲህ አድርጎ ተዘጋጀ እነሆ አሁን የዮስቴናን መምጣት ለቆጵርያኖስ ነገረው እርሱም እውነት መስሎት እጅግ ደስ አለው ሊቀበላትም ተነሣ። በእርሷ አርአያ የተመሰለውንም ምትሐት በአየ ጊዜ "የሴቶች እመቤት ዮስቴና መምጣትሽ መልካም ሆነ" አለ ይህንንም ስሟን በጠራ ጊዜ ያ በእርሷ አምሳል የተመሰለ ሰይጣን እንደ ጢስ ሁኖ ተበተነ።
🌼 በዚያንም ጊዜ የሽንገላው ምክንያት ምትሐቱም ከንቱ እንደሆነ ቆጵርያኖስ አወቀ አስተዋለም በልቡም እንዲህ አለ። "ስሟን በጠሩበት ቦታ እንደ ጢስ የሚበተኑ ከሆነ በፊቷ ሊቆሙ ሊሸነገሏትስ እንዴት ይቻላቸዋል" ይህንንም ብሎ ወዲያውኑ የጥንቆላ መጻሕፍቶቹን አቃጠለ።
🌼 ከዚህም በኋላ ወደ አንጾኪያ ሊቀ ጳጳሳት ሒዶ የክርስትና ጥምቀትን ተጠምቆ የምንኲስና ልብስን ለበሰ ከጥቂት ቀኖችም በኋላ ዲቁና ሾመው። ዳግመኛም ቅስና ሾመው በትሩፋት ሥራና በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ከፍ ከፍ ባለ ጊዜ ለሀገሩ ምዕራብ ለሆነች ቅርጣግና ለምትባል አገር ኤጲስቆጶስ ይሆን ዘንድ ተገባው ያን ጊዜም ቅድስት ዮስቴናን ወስዶ ለደናግል ገዳም እመ ምኔት አደረጋት።
በቅርጣግናም የቅዱሳን የአንድነት ስብሰባ በሆነ ጊዜ ከጉባኤው አባላት እርሱ አንዱ ነው።
🌼 ከብዙ ወራት በኋላም ከሀዲው ንጉሥ ዳኬዎስ ስለእነርሱ ሰማ ወደርሱም አስቀረባቸውና የክብር ባለቤት ክርስቶስን ክደው ለጣዖቶቹ እንዲሰግዱ አዘዛቸው። ትእዛዙንም ባልሰሙ ጊዜ ታላቅ ሥቃይን አሠቃያቸው ብዙ ሥቃይንም ከአሠቃያቸው በኋላ የቅዱስ ቆጵርያኖስንና የቅድስት ደንግል ዮስቴናን የሦስት ወንዶችንም ራሳቸውን አስቆረጠ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም ቅዱስ ቆጵርያኖስና ድንግሊቱ ቅድስት ዮስቴና በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 21 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
🌼 "#ሰላም_ሰላም_ለጢባርዮስ_ስንዕ። ምስለ ፸ወ፪ቱ አርድእተ እግዚእ። በዕለተ ዕረፍትከ ዮም ብሔረ ተድላ ወፍግዕ። ባርከነ ለደቂቅከ በውስተ ዛቲ ምሥዋዕ። እስመ ለመምህር ቡራኬ ሥሩዕ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_21።
