Gurage Zone Government Communication Affairs
Открыть в Telegram
1 568
Подписчики
-324 часа
-47 дней
+630 день
Архив постов
አሲዳማ አፈር በኖራ በማከም የአርሶአደሩ ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ እየሰራ እንደሚገኝ የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል አስታወቀ።
ሰኔ 25/2018 ዓ.ም |ወልቂጤ
ማዕከሉ በጉራጌ ዞን ምሁር አክሊል ወረዳ ውቅየ ቀበሌ አሲዳማ መሬት ሜካናይዜሽን በመጠቀም በኖራ የማከም ስራ እያከናወነ ይገኛል።
የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል ተመራማሪና የማዕከሉ ዳይሬክተር አቶ ቤተል ነክር እንዳሉት ማዕከሉ በጉራጌ ዞን የግብርና ችግሮችን መነሻ በማድረግና ለችግሮቹ መፍትሄ ለመስጠት በምርምር ጥረት እየተደረገ ይገኛል ።
ያለቀላቸውና ሌሎች ቦታዎች ላይ ውጤታማነታቸው የተረጋገጡ የግብርና ቴክኖሎጂዎች በስፋት ለአርሶአደሮች የማስተዋወቅ ስራ እየተሰራ እንደሆነ የተናገሩት አቶ ቤተል አሲዳማ አፈር በኖራ የማከም ስራ እየሰሩ እንደሆነም አመላክተዋል።
ባለፉት አምስት አመታት የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል ኖራን በስፋት በማቅረብ አርሶአደሩን ተጠቃሚ የማድረግ ስራ እየሰሩ እንደሆነም ተናግረው በተለያዩ ቦታዎች ኖራን በእጅ ከመበተን ይልቅ ሜካናይዝድ መሆን እንዳለበት አርሶአደሮች እየጠየቁ ይገኛል ብለው ይህንንም ችግር ለመቅረፍ ቴክኖሎጂውን ለአርሶአደሩ የማስተዋወቅ ስራ እየሰሩ እንደሆነም አመላክተዋል።
አክለውም አቶ ቤተል አሲዳማ አፈር በኖራ የማከሙ ስራ ከጉራጌ ዞን በተጨማሪ በሌሎችም በአጎራባች ዞኖችም እየሰሩ እንደሚገኝም አብራርተዋል።
ከፍተኛ የዝናብ ስርጭት ባለባቸው አካባቢዎች አሲዳማ አፈር ትልቅ ችግር ተደርጎ የሚወሰድ ሲሆን ይህ ደሞ የአርሶአደሩ ምርትና ምርታማነት በከፍተኛ ሁኔታ እንደሚቀንስም ተናግረዋል።
በአፈር ምርመራ የአርሶአደሩ መሬት ኖራ እንደሚፈልግ በጥናት ካረጋገጡ በኋላ ኖራ ለአርሶአደሩ የማቅረብና የማከም ስራም እንደሚሰራም አብራርተዋል።
አሲዳማ አፈር ተቋቁሞ ምርት ሊሰጡ የሚችሉ የተሻሻሉ ምርጥ ዘሮች የማቅረብ ስራ እየሰሩ እንደሆነም አስረድተዉ ምርጥ ዘሩ ከኖራ ጋር በማቀናጀት የአርሶአደሩ ምርት በከፍተኛ ሁኔታ ይጨምራል ብለዋል።
አርሶአደሩ ሲቸገርበት የነበረው ኖራን በብተና ማከናወን ለጤናና ወጥ በሆነ መልኩ ማሳውን ከማዳረስ አንጻር እንዲሁም የማዋሀድ ስራው ትልቅ ችግር የሚፈጥር ሲሆን ከተጨነም ኢንተርፕራይዝ ጋር በመቀናጀት የኖራ መበተኛ ማሽን ለአርሶደሮች የማስተዋወቅ ስራ እየሰሩም እንደሆነ አስረድተዋል።
የምሁር አክሊል ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ብስራት ገብሩ እንዳሉት በተያዘው የመኸር ወቅት የተቀናጀ የግብርና ልማት ስራ ትኩረት ሰጥተው እየሰሩ እንደሚገኝ አመላክተዋል።
በወረዳው ከ11ሺህ በላይ ሄክታር መሬት በተለያዩ ሰብሎች ለመሸፈን እየተሰራ እንደሆነ ተናግረው ከዚህ ውስጥ የአዝርት ሰብሎች ትልቁን ድርሻ የሚይዙ ሲሆን በተለይ በዘንድሮ መኽር በወጣቶች እየተሰሩ ያሉ ማሳዎች በስንዴ ሰብል ለመሸፈን አጽኖት ተሰጥቶት እየተሰራ ይገኛል ብለዋል።
የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል በወረዳ በግብርናው ዘርፍ ለተሰማሩ የአርሶአደሮችና የወጣቶች ማሳ ምርትና ምርታማነት ለመጨመር የሚያስችል ሰፋፊ ስራዎች እየሰራ እንደሚገኝም አመላክተዋል።
በወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል የአፈርና ውሃ አያያዝ ምርምር አስተባባሪ አቶ ተሾመ በቀለ እንዳሉት ባለፉት አምስት አመታት ለጉራጌ ዞን አርሶአደሮች 9 ሺህ ኩንታል የሚሆን ኖራ የማከፋፈል ስራ ተሰርቷል ብለዋል።
በዞኑ በአንዳንድ አካባቢዎች ዝናብ የሚበዛ እንደሆነ ተናግረው በአካባቢው 52 ፐርሰንት የሚሆነው መሬት በአሲዳማ አፈር የተጠቃ እንደሆነም አስረድተዋል።
ከሆለታ ምርምር ማዕከል ጋር በመሆን አሲዳማ አፈርን ተቋቁሞ መብቀል የሚችሉ የተልባና የጎመን ዝርያዎች ለአርሶአደሩ የማዳረስ ስራ መሰራቱም አመላክተው አሲዳማ አፈር ለማከም የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ መዳበሪያ አቀናጅተው በመስራት አሲዳማ አፈር የማከም ስራ እየሰሩ እንደሆነም አብራርተዋል።
በውቅየ ቀበሌ በግብርና ዘርፍ ተደራጅተው እየሰሩ ያሉ የይስሬሸ የወጣቶች ማህበር አባል ወጣት አብድረዛቅ አህመድ እንዳለው በመኽር እርሻ ስንዴ ለማልማት መንግስት 15 ሄክታር ያመቻቸላቸው እንደሆነ ተናግሯዋል።
የወልቂጤ ግብርና ምርምር ማዕከል መሬቱን በኖራ የማከም ስራ በመስራቱ የበለጠ ምርትና ምርታማነታቸው እንደሚጨምር አስረድቶ ማዕከሉ እያደረገላቸው ያለውን ሁለንተናዊ ድጋፍም አመስግነዋል ሲል የዘገበው የጉራጌ ዞን የመንግስት ኮሚኒኬሽን መምሪያ ነው።
በወረዳው በዘንድሮ የመኸር እርሻ ልማት ከ7 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ በማረስ በተለያዩ በአዝዕርትና በጥራጥሬ ሰብሎች ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ ነው:- አቶ አሰበ ካብቱ
በወረዳው መልማት እየቻሉ ከዚህ ቀደም በባህርዛፍ በቁጥቋጦና በሳር የተያዙ ከ1ሺህ 1መቶ ሄክታር መሬት በላይ መታረሱንም ተመላክቷል።
ሰኔ 17/2018 ዓ.ም(ወልቂጤ) በጉራጌ ዞን እኖር ኤነር መገር ወረዳ ወቅታዊና ልዩ ትኩረት ከሚሹ ስራዎች ውስጥ የመኸር የግብርና ልማት ስራዎች ያሉበት ሁኔታ የመስክ ምልከታ ተካሂዷል።
በወረዳው ባለፉት ሁለት ሳምንታት ብቻ ከዚህ ቀደም ታርሶ የማውቅ ከ2መቶ ሄክታር በላይ ማሳ መታረሱንም ተገልጿል።
የእኖር ኤነር መገር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሰበ ካብቱ እንዳሉት ወረዳው ከመልካም ምድራዊ አቀማመጧ ባለፈ ደጋ፣ ወይናና ከፊል ቆላማ የአየር ንብረት ያላት በመሆኑ ለግብርና ልማት ስራ ምቹ አድርጓታል።
በዘንድሮ የመኸር እርሻ ልማት በወረዳው 7 ሺህ 426 ሄክታር መሬት በማረስ በተለያዩ በአዝዕርትና የጥራጥሬ ሰብሎች ለመሸፈን ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው በዚህም በእስካሁኑ 5 ሺህ 335 ሄክታር መሬት መታረሱን ገልጸዋል።
ከዚህ ማሳ 1ሺህ 5 መቶ ሄክታር መሬት በክላስተር ለማልማት ታቅዶ እየተሰራ እንደሚገኝም ጠቁመዋል።
ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ መካናይዜሽን ወሳኝ ነው ያሉት አቶ አሰበ ለዚህም የወረዳው መንግስት 2 ትራክተሮችን ግዢ በመፈጸምና ወደ ተግባር ከማስገባት ባለፈ በወረዳው ማዕከል ያሉ 9 ትራክተሮች በመጠቀም አርሶ አደሩ እንዲያርስ እየተደረገ መሆኑን ተናግረዋል።
በወረዳው መልማት እየቻሉ በባህርዛፍ፣ በቁጥቋጦና በሳር የተያዙ ከ1ሺ 2 መቶ በላይ አዲስ ማሳዎች በማረስ ወደ ሰብል ለመቀየር እየተሰራ መሆኑን ገልጸው በእስካሁኑ 1ሺህ 1መቶ 57 ሄክታር መሬት መታረሱንም አንስተዋል።
በተለይም እንደ ዞን አስተዳደር በ20 ቀናት 2መቶ 85 ሄክታር መሬት አዳዲስ ማሳ ወደ እርሻ ለማስገባት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑን ጠቅሰው፣ በዚህም በእስካሁኑ 2 መቶ ሄክታር መሬት አዳዲስ ማሳዎችን ማረስ ተችላል ብለዋል።
በዘርፉ ውጤታማ ስራ ለመስራት ከፍተኛ ንቅናቄ በማድረግና ለአርሶ አደሩ ግንዛቤ በመፍጠር ዜሮ እርሻ በሚል የተጀመረው ኢንሼቲቭን ለማሳካት በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተው ይህም ለማሳካት የበለጠ በማጠናከር እንደሚሰራ አስገንዝበዋል።
የወረዳው ምክትል አስተዳዳሪና የግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ መላኩ ሳህሌ በበኩላቸው በወረዳው በግብርናው ዘርፍ የታቀደውን እቅድ ለማሳካት ለአርሶ አደሩ በአርሶ አደር ማሰልጠኛ ተቋምና በሞዴል ማሳዎች ግንዛቤ መሰጠቱን አመላክተዋል።
ዜሮ እርሻ በሚል እንደ ሀገር በጠቅላይ ሚኒስትሩ የተጀመረው ኢንሼቲቭ ተከትሎ በወረዳው በዘርፉ በትኩረት እየተሰራ መሆኑን አንስተው ይህም ተግባር በቀጣይም ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል።
በመኸር እርሻ አዲስ ከታረሱ ማሳዎች ውስጥ 2መቶ ሄክታር መሬት በባህርዛፍ ተሸፍኖ እንደነበር እንስተው በእስካሁኑ ከ1 መቶ50 ሄክታር መነሳቱና በአመታዊ ሰብል፣ በሙዝና በቡና ለመተካት እየተሰራ መሆኑን አስረድተዋል።
በወረዳው በጤፍ በሄክታር 14 ኩንታል ምርት ለማግኘት መታቀዱን አንስተው ለዚህም የመጀመሪያ ዙር እርሻ በተገቢው መታረሱናመ በቀጣይም ደጋግሞ የማረስ፣ የክስካሶ፣ የማሳ እንክብካቤና መሰል ስራዎች ይሰራል ነው ያሉት።
ለዚህም አስፈላጊውን ግብአት በተለይም ዩሪያ በበቂ ሁኔታ በመጋዘን መኖሩን የገለጹት ኃላፊው ተጨማሪ ዳፕ ለማስገባት ከሚመለከታቸው አካላት እየሰሩ መሆኑን ጠቅሰው ምርጥ ዘር ለአርሶ አደሩ በወቅቱ ተደራሽ ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።
ምርትና ምርታማነት ለማሳደግ ግብአት መጠቀም ብቻ ግብ አይደለም ያሉት አቶ መላኩ ለዚህም የግብርና ባለሙያዎች ከአርሶ ጎን በመሆን ከእርሻ ዝግጅት እስከ ምርት መሰብሰቢ ወቅት ድረስ የተጠናከረ ስራ እንደሚሰራ ገልጸዋል።
የሹሞሮ ቀበሌ ግብርና ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ ተመስገን ሳህሌ በዘንድሮ እርሻ በቀበሌው 384 ሄክታር መሬት ታቅዶ 360 ሄክታር መሬት ማታረሱን ጠቁመው ከዚህም ውስጥ 67 ሄክታር ማሳ አዲስ መሆኑንም ተናግረዋል።
ለአርሶ አደሩ ትራክተሮችን ተጠቅመው እርሻን በወቅቱ እንዲያርሱ፣ በወቅቱ እንዲከሰክሱና በባህርዛፍ የተያዙ ሊለሙ የሚችሉ ማሳዎችን በሰብልና ፍራፍሬ እንዲተኩ ግንዛቤ ከመስጠት ጀምሮ ሙያዊ ድጋፍ እያደረገላቸው እንደሚገኝ አመላክተዋል።
አቶ ክፍሉ አድማሱና አቶ ቀሲስ እርገታ ሀ/ማርያም በወረዳው አግኝተን ያነጋገርናቸው አርሶ አደሮች ሲሆኑ በጋራ በሰጠት አስተያየት በዘንድሮ የመኸር እርሻ በባህርዛፍና በቁጥቋጦ የተያዙ ማሳዎችን በማንሳትና በመመንጠር ወደ እርሻ መቀየራቸውን ገልጸዋል።
ምርትና ምርታማነት እንዲጨምር የግብርና ባለሙያ የሚሰጣቸውን ምክረሃሳብ በመቀበል በትራክተር ማረሳቸውን አንስተው ከዚህም ባለፈ ማሳው በተደጋጋሚ በማረስና በመከስከስ በጤፍ ለመሸፈን እየሰሩ መሆኑን ተናግረዋል።
በዞኑ በ2018 የክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከ9 መቶ 5 ሺህ በላይ የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ለማድረግ ይሰራል:- አቶ ሙራድ ረሻድ
ሰኔ 17/2018 ዓ.ም(ወልቂጤ) በዘንድሮ የክረምት ወራት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የማህበረሰቡን የመረዳዳትና የመተጋገዝ የቆየ እሴቱን ይበልጥ በማጎልበት እቅዱ እንዲሳካ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ መወጣት እንዳለበት ተገለጸ።
የጉራጌ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሙራድ ረሻድ የዘንድሮ የክረምት ወራት በጎ ፈቃድ አገልግሎት አስመልክተው በሰጡት መግለጫ በባለፉት 8 አመታት እንደ ሀገር ብሎም በዞኑ ሰው ተኮር ስራዎች በመሰራቱ አበረታች ውጤቶች ተመዝግቧል።
በ2018 በክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት 9 መቶ5 ሺህ 268 የህብረተሰብ ክፍሎች ተጠቃሚ ለማድረግ እንደሚሰራ ገልጸዋል።
በዚህም 4መቶ 40 ሺህ 210 ወጣቶችና ሌሎች በጎ ፈቃደኞች እንደሚሳተፉ ጠቅሰው ከዚህም ውስጥ 50 ፐርሰንቱ ሴቶች ናቸው ብለዋል።
በዚህም በ15 የአገልግሎት ዘርፎች 282 አዲስ ቤቶች፣ 279 የደከሙ ቤቶችን ማደስ፣ 1ሺህ 386 ዩኒት ደም ለማሰባሰብና በችግኝ ተከላ፣ በግብርና፣ በትምህርት፣ በጤናና በሌሎችም የአገልግሎት ዘርፎች ለመስራት ታቅዶ የቅድመ ዝግጅት ስራ እየተሰራ መሆኑን ጠቁመዋል።
ይህም በክረምት ወራት በጎ ፈቃድ አገልግሎት የሚሰራው ስራ በገንዘብ ሲተመን 841 ሚሊዮን 28 ሺህ 146 ብር ማዳን እንደሚችል ኃላፊው ገልፀዋል።
ለዚህም በተለያዩ ዘርፎች ድጋፍ የሚሹ ወገኖችን ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ የመለየት ስራ እየተሰራ ነው ያሉት አቶ ሙራድ እንደ ሀገር ከቤት ግንባታ ጋር ተያይዞ የተቀመጠው ወጥ እስታንዳርድ መነሻ በማድረግ በዞኑ በትኩረት እንደሚሰራበትም ተናግረዋል።
የጉራጌ ማህበረሰብ መተጋገዝና መረዳዳት የቆየ እሴቱ መሆኑን አንስተው ይህ መልካም እሴቱ ይበልጥ በማጠናከር በበጎ ፈቃድ ተግባር በስፋት መሳተፍ እንዳለባቸው አንስተው፣ ይህም ተግባር የህሊና እርካታ ከማስገኙቱም ባሻገር በእምነታችን የምናተርፍበት ነው ያሉት።
በዞኑ በ2017 በክረምት ወራት የበጎ ፈቃድ አገልግሎት ከፍ ያሉ እቅዶችን በማቀድ በዞኑ የፊት አመራርና ፓርቲ በተገቢው እየተገመገመ በመመራቱና ድጋፍ ክትትል በመደረጉና በቅንጅት በተሰሩ ስራዎች ውጤታማ ተግባር ማከናወን ተችሏል ብለዋል።
ከዚህም ባለፈ በዞኑ ዋና አስተዳዳሪ በክቡር አቶ ላጫ ጋሩማ አቅጣጫ መሰረት 6መቶ ከመከላከያ ሰራዊት ተመላሽና ቤተሰቦቻቸው የተለያዩ ድጋፎች እንደተደረገላቸው አንስተዋል።
አምና በክረምት ወቅት የነበረውን ጠንካራ ስራዎችን በማጠናከርና ድክመቶችን በመለየት በቀጣይ ውጤታማ ስራ ለመስራት ማህበረሰቡ፣ ወጣቶችና ባለሀብቶችን በጉልበታቸው፣ በገንዘባቸውና በእውቀታቸው ከዚህ ቀደም ሲያደርጉት የነበረውን እገዛና ተሳትፎ አጠናክረው እንዲያስቀጥሉም አስገንዝበዋል።
የጉራጌ ዞን ቀይ መስቀል ማህበር በበጀት አመቱ 4 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር በማውጣት ዘርፈ ብዙ ድጋፎችን ማድረጉን አስታወቀ።
ሰኔ 17/2018 ዓ.ም (ወልቂጤ)
የዞኑ ቀይ መስቀል ከአደጋ ምላሽ እስከ ቤት ግንባታ ድረስ የህዝብ አለኝታነቱን እያስመሰከረ እንደሚገኝ ተገልጿል።
የጉራጌ ዞን ቀይ መስቀል ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት የፕሮግራም ዘርፍና የቅርንጫፍ ጽህፈት ቤት ሀላፊ ተወካይ አቶ ሻሚል የሲሩ እንዳሉት፤ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቱ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ ማህበረሰቡን የሚጠቅሙ ዘርፈ ብዙ ተግባራት እያከናወነ ይገኛል።
የሰው ልጆች በየትኛውም ቦታ ለሚገጥማቸው የተፈጥሮና ሰው ሰራሽ አደጋዎች ቀድሞ በመድረስ የማገዝና የተለያዩ ድጋፎች እያደረገ እንደሆነም አስረድተዋል።
ማህበሩ ለየት ብሎ በሚታወቅባቸው የገጠር የሳር ቤቶች ቃጠሎ ሲደርስ ፈጥኖ በመድረስ የአልባሳትና የቁሳቁስ ድጋፍ ያደርጋል ብለዋል።
ማህበሩ በዞኑ የመድሃኑት መደብር ተደራሽነት በሌለባቸው ቦታዎችም መደብሮችን በመክፈት እየሰራ እንደሆነ ገልፀዋል
ከማህበረሰቡ የአሰፋፈር ሁኔታ ጋር ተያይዞ ጆፎረን ተከትሎ የሚሰፍሩ ቤቶች ብዛት ያላቸው በመሆኑ፣ በአንዱ ቤት እሳት ከተነሳ ብዙ ቤቶች የሚቃጠሉበት ሁኔታ መኖሩን አቶ ሻሚል ገልጸዋል።
በዚህም በየአመቱ ከሁለት መቶ እስከ ሶስት መቶ ቤቶች በእሳት የሚቃጠሉበት አጋጣሚ የሚኖር ሲሆን፣ ቅርነጫፍ ጽህፈት ቤቱ ፈጥኖ በመድረስ የቁሳቁስና የአልባሳት ድጋፍ እያደረገ እንደሆነም አመላክተዋል።
በተጨማሪም ጧሪና ደጋፊ ለሌላቸው አቅመ ደካሞች በመድረስ ምግብና ምግብ ነክ ነገሮች የማሰራጨት ስራ ይሰራል ያሉት አቶ ሻሚል፤ በየአመቱ ለሁለት አቅመ ደካሞች አዲስ ቤት ገንብቶ የማስረከብ ስራም እንደሚሰራም ጠቁመዋል።
የቀይ መስቀል በጎ ፍቃደኞች ወጣቶች በኢትዮጵያ ደረጃ ታዋቂ የሆኑበትና በየአመቱ "የመስጠት ቀን" በሚል በሚያከናውኑት የበጎ ፍቃድ ስራ ሊስትሮ በመጥረግ የሚያገኙትን ገንዘብ በማስቀመጥ እንዲሁም እግር ኳስ ውድድር ሲኖር የቀይ መስቀል አገልግሎት በመስጠት በሚያገኙት ገቢ ለምስኪኖች ምግብ የሚያበሉ እንደሆነ ተገልጿል።
በተጨማሪም እነዚህ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች በቅርቡ በአጣጥ ሆስፒታል ተኝተው ለሚታከሙ 30 ረዳት ለሌላቸው የማህበረሰብ ክፍሎች ምግብ መመገባቸውን አቶ ሻሚል አስታውሰዋል።
የቀይ መስቀል ዋነኛ የበጀት ምንጩ አባላቱ ሲሆኑ፣ በእነዚህ አባላት በሚገኝ ገንዘብ በርካታ ስራዎች እየተሰሩ እንደሚገኝና በቀጣይም የተጠናከረ የአደጋ ስጋት ምላሽ እንደሚሰጥ ተገልጿል።
በበጀት አመቱ በተለያዩ ወረዳዎች ለተፈጠሩ የእሳት አደጋዎች ማህበሩ በመድረስ ምላሽ መስጠት የቻለ ሲሆን፤ ቅርንጫፍ ጽህፈት ቤቱ ከዞኑ አስተዳደር፣ ከዞኑ አደጋ ስጋት ጽህፈት ቤት፣ ከዞኑ ጤና መምሪያ እንዲሁም ከሌሎች የመንግስት ተቋማት ጋር ተቀናጅቶ እየሰራ መሆኑን አመላክተዋል።
አደጋ ለደረሰባቸው የማህበረሰብ ክፍሎች የሚረዱት ከአባላቱ በሚሰበሰበው ገንዘብ እንደሆነ ያስረዱት አቶ ሻሚል፤ በዚህ በጀት አመት ብቻ ወደ 4 ነጥብ 5 ሚሊየን ብር ለአደጋ ስጋት ምላሽ፣ ለቤት ግንባታ፣ ለምግብና ምግብ ነክ ለሆኑ ነገሮች እንዲሁም ለተለያዩ ቁሳቁሶች ማዋል መቻሉን ገልጸዋል ሲል የዘገበው የጉራጌ ዞን የመንግስት ኮሚኒኬሽን መምሪያ ነው።
በዞኑ ለአረንጓዴ አሻራ ልማት ከፍተኛ ትኩረት በመሰጠቱ ተጨባጭ ውጤቶች እየተመዘገቡ ይገኛል:- አቶ እንዳለ ስጦታው
በእኖር ወረዳ ከዚህ ቀደም ተራቁቶ የነበረ አንድ መቶ ሄክታር መሬት በአረንጓዴ አሻራ ልማት ውጤታማ መሆኑን ተገልጿል።
ሰኔ 13/2018ዓ.ም(ወልቂጤ) በጉራጌ ዞን እኖር ወረዳ ወቅታዊ ያረንጓዴ አሻራ ልማት እንቅስቃሴ የመስክ ምልከታ ተካሂዷል።
የጉራጌ ዞን ደንና አከባቢ ጥበቃ ልማት መምሪያ ኃላፊ አቶ እንዳለ ስጦታው በመስክ ምልከታው ወቅት እንዳሉት እንደ ሀገር ከለውጡ መንግስት ወዲህ ለአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር የተሰጠው ልዩ ትኩረት ተከትሎ በዞኑ በዘርፉ በተሰራው ስራ በተባጭ ዘርፈ ብዙ ውጤቶች ተመዝግቧል ።
ከ2011 ዓ.ም ጀምሮ በዞኑ በአረንጓዴ አሻራ መርሃ ግብር በየአመቱ የደን ሽፋን መጠን እያደገ መምጣቱን የጠቀሱት ኃላፊው አሁን ላይ 26 ነጥብ 6 ፐርሰንት መድረሱንም ተናግረዋል።
መሬት መንከባከብና መጠበቅ እንደሚገባ አንስተው፣ ለዚህም የተጎዱና የተራቆቱ መሬቶችን ላይ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው ችግኞችን እንደሚተከልም ገልጸዋል።
የዞኑን ማህበረሰብ በማሳተፍ ከዚህ ቀደም የተራቆቱና ለልማት የማይውሉ ከ16 ሺህ ሄክታር መሬት በላይ በመለየት የየአካባቢው አግሮኢኮሎጂ በጠበቀ መልኩ የተለያዩ ጠቀሜታ ያላቸው በሚሊየን የሚቆጠሩ ችግኞች በየአመቱ ሲተከሉ መቆየቱን አውስተዋል።
በዚህም በዞኑ የከርሰና ገጸ ምድር ውሃ እንዲጎለብት፣ በተለያዩ ምክንያቶች በጎርፍ ታጥቦ የሚሄደውን ለም መሬት ማዳን ከመቻሉም ባለፈ የዝናብ መጠን ከፍ እንዲልና ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ አስችሏል ብለዋል።
ችግኝ መትከል ብቻ ግብ አይደለም የተተከሉትን ተንከባክቦ እንዲጸድቁ ማድረግ ነው ያሉት ኃላፊው በዚህም በተሰራው ስራ የዞኑ የችግኝ የጽድቀት መጠን 93 ፐርሰንት መድረሱንም አስረድተዋል።
በተለይም በዞኑ በሁሉም መዋቅሮች በአብዛኛው የተራቆቱና ለምርትና ምርታማነት የማይውሉ የተጎዱ መሬቶች ላይ ጥናት በማድረግ በደን የመሸፈን ስራ እየተሰራ መሆኑን አንስተው በእኖር ወረዳ ካሳይና ኮሰድ ቀበሌዎች ላይ በመስክ ምልከታ የታየው የደን ማሳ የዚሁ አንዱ ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል።
በወረዳው በካሳይ ቀበሌ ላይ 100 ሄክታር መሬት በላይ በፓይነስ መሸፈኑ አንስተው ይህም ኢኮኖሚያዊ ጠቀሜታው የጎላ በመሆኑ አርሶ አደሩ ተጠቃሚ መሆናቸውም አመላክተዋል።
በኮሰድ ቀበሌ አርሶ አደሩ ባህርዛፍ እየነቀለ ፓይነስ ፓቹላ እየተከለ መሆኑን ማየታቸውን ጠቁመው፣ ይህም የግንዛቤ ስራ በመሰራቱና ጠቀሜታው በመረዳታቸው በመሆኑ ነው ያሉት።
በቀጣይ በዘርፉ የበለጠ ስራ በመስራት ህብረተሰቡ በሁሉም ዘርፍ ተጠቃሚ እንዲሆን እንደሚሰራም አስገንዝበዋል።
የእኖር ወረዳ ደንና አከባቢ ጥበቃ ልማት ጽህፈት ቤት ኃላፊ አቶ በቀለ በዙ በበኩላቸው፣ በወረዳው በዘርፉ በተሰራው ስራ ከፍተኛ ለውጥ መምጣቱን ጠቅሰው በዚህም የደን ሽፋን 25 ነጥብ 5 መድረሱን አንስተዋል።
በየአመቱ ከ1 ሺህ 4 መቶ በላይ ሄክታር መሬት በተለያዩ ዘርፈ ብዙ ጠቀሜታ ያላቸው የተለያዩ ችግኞችን እንደሚተከል አንስተው በዚህም የጽድቀት መጠናን 91 ፐርሰንት በላይ ማድረስ ተችላል ብለዋል።
በወረዳው በካሳይ ቀበሌ በተራቆቱና በተጎዱ የወል መሬቶች ላይ ፓይነስ ፓቹላ፣ የጽድና የግራቪሊያ በመትከል ለማህበረሰቡ በማስረከብ አርሶ አርሶ በመንከባከብና በመጠበቅ ተጠቃሚ እየሆኑ መሆኑን ተናግረዋል።
ይህም ዝናብ በወቅቱ እንዲዘንብ፣ የገጸና የከርሰ ምድር ውሃ እንዲፈልቅና የአርሶ አደሩን ምርትና ምርታማነት እንዲያድግ ማድረጉንም አመላክተዋል።
አርሶ አደር ባምበታ ወጋደና አርሶ አደር ኧስዊጋ አባተ በእኖር ወረዳ የካሳይ ቀበሌ ነዋሪ ናቸው፣ ነዋሪዎቹ እንዳሉት ስፍራው ችግኝ ሳይተከልበት በፊት መሬቱ በጎርፍ ተጠርጎ በወሰዱ ምንም ጥቅም የማይሰጥ እንደነበር አንስተዋል።
አጠቃላይ ማሳው 50 ሄክታር መሬት መሆኑን አንስተው በዚህም ፓይነስ ፓቹላ፣ ጽድና ሌሎችም ችግኞች ይገኙበታል ብለዋል።
በአካባቢው ችግኝ በመተከሉ የአፈር ለምነቱ ከመጠበቁ የተነሳ ሳር ማብቀል ጀምሯል፣ የአከባቢው የአየር ሁኔታ ከማስተካከሉም ባለፈ ኢኮኖሚያዊ ተጠቃሚ መሆናቸውን አንስተዋል።
ለዚህም ችግኞቹ ከመትከል ባለፈ እንዲጸድቁ ከእንሰሳትና ከሰው ንክኪ ነጻ እንዲሆኑ በአጥር በመከለል ሲጠብቁትና ሲንከባከቡት እንደነበር አንስተው ይህም በቀጣይም አጠናክረው እንዲቀጥሉም ገልጸዋል።
በጉራጌ ዞን ለሁለት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የነበረው የዘንድሮ የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በሰላማዊ መልኩ ተጠናቀቀ።
ፈተናቸው ያጠናቀቁ ተማሪዎችም የአረንጓዴ አሻራቸውን በማኖር በሌሎች የክረምት በጎ አድራጎት ስራዎችም ተሳትፈዋል።
ሰኔ 12/2018ዓ.ም (ወልቂጤ) በዞኑ ክልል አቀፍ ፈተናው በስኬት እንዲጠናቀቅ በቅንጅት በተሰራው ስራ ያለምንም ችግር በሰላማዊ መልኩ መጠናቀቁን የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ገለጸ።
የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ መብራቴ ወልደማርያም የፈተናው መጠናቀቅ አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ የዘንድሮ የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ያለምንም ችግር በሰላማዊ መልኩ ተጠናቋል።
ፈተናው በ3መቶ 28 ትምህርት ቤቶችና በጉድኝት ማዕከላት 19 ሺህ 580 ተማሪዎች ፈተናው መውሰዳቸውን ጠቅሰው 2መቶ 91 ተማሪዎች ደግሞ በተለያዩ ምክንያቶች በፈተና ያልተቀመጡ መሆኑንም አቶ መብራቴ ገልጸዋል።
በዞኑ የዘንድሮ የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በሰላማዊ መልኩ ለማጠናቀቅ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት በማድረግ በቅንጅት በተሰራው ስራ ፈተናው ያለምንም ኩረጃ በስኬት ማጠናቀቅ መቻሉንም አስረድተዋል።
ክልል አቀፍ የ8ኛ ክፍል ፈተና በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላደረጉ በየደረጃው ላሉ አመራሮች፣ ለፈተና አስፈጻሚዎች፣ ለትምህርት መምሪያና ጽህፈት ቤት የማኔጅመንት አካላትና ባለሙያዎች፣ ለወላጆች፣ ለተማሪዎች እና ለጸጥታ አካላት አቶ መብራቴ ምስጋና አቅርበዋል።
በፈተና መጨረሻ ተማሪዎቹ በተፈተኑባቸው ጣቢያዎች ግቢ የማፅዳት፣ ችግኝ የመትከል፣ የችግኝ መትከያ ጉድጓዶች የማዘጋጀት ስራዎች ያከናወኑ ሲሆን ዩኒፎርምና የተለያዩ ለፈተና የተጠቀሟቸው ቁሳቁሶችን ለቀጣይ ድጋፍ ለሚፈልጉ ተማሪዎች አበርክተዋል።
በዞኑ ለሁለት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ የነበረው የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በሰላማዊ መልኩ መጠናቀቁን የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ገለጸ።
ሰኔ 9/2018ዓ.ም (ወልቂጤ) በዞኑ የዘንድሮ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በስኬት እንዲጠናቀቅ በቅንጅት የተሰራው ስራ በቀጣይም በ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ላይ መድገም እንደሚገባም ተመላክቷል።
የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ መብራቴ ወልደማርያም የፈተናው መጠናቀቅ አስመልክቶ በሰጡት መግለጫ በዞኑ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ያለምንም ችግር በሰላማዊ መልኩ መጠናቀቁን ገልጸዋል።
በዞኑ በ3መቶ 80 አስፈታኝ ትምህርት ቤቶችና በጉድኝት ማእከላት በማደራጀት 18 ሺህ 3 መቶ 90 ተማሪዎች ክልል አቀፍ ፈተናው መውሰዳቸው ገልፀዋል።
በዞኑ የዘንድሮ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በሰላማዊ መልኩ ለማጠናቀቅ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት በማድረግ በቅንጅት በተሰራው ስራ ፈተናው በስኬት ማጠናቀቅ መቻሉንም አስረድተዋል።
ክልል አቀፍ ፈተናው በስኬት እንዲጠናቀቅ አስተዋጽኦ ላደረጉ በየደረጃው ላሉ አመራሮች፣ አስፈጻሚዎች፣ ለትምህርት አመራሮች እና ለጸጥታ አካላት አቶ መብራቴ ምስጋና አቅርበውዋል።
ይህ ውጤታማነትና ቅንጅት በቀጣይ ከሰኔ 11 እስከ 12 በሚሰጠው የ8ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና ላይ መድገም እንደሚገባም አስገንዝበዋል።
የዘንድሮ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተናው ከኩረጃ ነጻና በሰላማዊ መልኩ በመስጠት በስኬት ለማጠናቀቅ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ ሊወጣ እንደሚገባ ተገለጸ።
ሰኔ 8/2018ዓ.ም (ወልቂጤ) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ምክትል ርዕሰ መስተዳድር፣ የማህበራዊ ክላስተር አስተባባሪ እና የትምህርት ቢሮ ኃላፊ አቶ አንተነህ ፈቃዱ በዛሬው እለት እየተሰጠ ያለውን ክልል አቀፍ ፈተና አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሀን ማብራሪያ ሰጥተዋል
በአዲሱ ትምህርት እና ስልጠና ፖሊሲ በ6ኛ፣በ8ኛ እና በ12 ኛ ክፍል በተለያዩ እርከኖች ተማሪዎች ክልል አቀፍ እና ሀገር አቀፍ ፈተና ይወስዳሉ በማለት ርዕሰ መስተዳድሩ አብራርተዋል።
በተያዘው የትምህርት ዘመን የ6 ኛ ክፍል ተማሪዎች ለፈተና በቂ ዝግጅት እንዲያደርጉ በትኩረት መሰራቱን ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ አመላክተዋል።
ምክትል ርዕሰ መስተዳድሩ እንዳሉት በክልሉ 91ሺህ 9መቶ 18 የ6ኛ ክፍል ተማሪዎች ክልላዊ ፈተናውን እየወሰዱ ይገኛሉ።
ቢሮው በዘንድሮ ዓመት ለሚሰጠው ሀገራዊና ክልላዊ ፈተና ተማሪዎች የማዘጋጀት ስራ ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል።
የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተናው ከሰኔ 8 እስከ 9 ከኩረጃ ነጻ በሆነ መልኩ እንደሚሰጥ የጠቀሱት አቶ አንተነህ በቀጣይ ከሰኔ 10 ጀምሮ በክልሉ የ8ኛ ክፍል ክልላዊ ፈተና ይሰጣል ብለዋል።
የጉራጌ ዞን ትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ መብራቴ ወልደማርያም በበኩላቸው ፈተናው በዞኑ በ3መቶ 80 አስፈታኝ ትምህርት ቤቶችና በ2 መቶ 24 የፈተና ማዕከላት 18 ሺህ 4መቶ 60 ተማሪዎች እንደሚወስዱ አንስተው ከነዚህም ውስጥ 8ሺህ 9መቶ 71 ተማሪዎች ሴቶች መሆናቸውንም ተገልጿል።
ለፈተናው ከአመቱ መጀመሪያ ጀምሮ ተማሪዎች የማብቃትና የመደገፍ ስራ መሰራቱን ያነሱት አቶ መብራቴ ከዚህም ባለፈ ለፈታኞች፣ ለሱፐርቫይዘሮች፣ ለጣቢያ ኃላፊዎች፣ ለፈተና ማዕከላትና ለጸጥታ አካላት ልየታና ኦረንቴሽን የመስጠት ስራ ሲሰራ መቆየቱንም ተናግረዋል።
በዞኑ የዘንድሮ የ6ኛ ክፍል ክልል አቀፍ ፈተና በስኬት ለማጠናቀቅ አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት ሲደረግ መቆየቱንም አንስተዋል።
ፈተናው ከአዲስ አበባ ከህትመት ማዕከል በሰላማዊ መልኩ ወደ ዞኑ በማስገባት ከዞኑ ወደ ሁሉም ወረዳና ከተማ አስተዳደሮችና ፈተና ጣቢያዎች በሰላማዊ መልኩ እንዲሰራጭ መደረጉንም አመላክተዋል።
ክልል አቀፍ ፈተናው በሰላማዊ መልኩና ከኩረጃ ነጻ በመስጠት በስኬት እንዲጠናቀቅ ወላጆች፣ ፈታኝ መምህራን፣ ፈተና አስፈጻሚዎች፣ ቤተሰብና የጸጥታ አካላት ጨምሮ ሁሉም የበኩሉን ድርሻ መወጣት እንዳለበትም አስገንዝበዋል።
