ru
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

Открыть в Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

Больше
2 639
Подписчики
+124 часа
+167 дней
+5630 день
Архив постов
🔴#ስንክሳር መጋቢት24 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ አራት በዚች ቀን የኢትዮጵያ ብርሃኗ የሆኑ #አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት የተጸነሱበት ነው፣ በእስክንድርያ ሀምሳ ዘጠነኛ ሊቀ ጳጳሳት የሆነ #ቅዱስ_አባ_መቃርስ አረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት (ጽንሰቱ) መጋቢት ሃያ አራት በዚህች ዕለት ጌታችን በቃሉ ''ሐዲስ ሐዋርያ'' ብሎ የሾማቸው የኢትዮጵያ ብርሃኗ የሆኑ የደብረ ሊባኖሱ አቡነ ተክለ ሃይማኖት የተጸነሱበት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ለኢትዮጵያ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጎ የመረጣቸው ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት በሊቀ መላእክት በቅዱስ ሚካኤል አብሳሪነት ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኀረያ መጋቢት 24 ቀን ተፀንሰው ታኅሣሥ 24 ቀን 1197 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ ጻድቁ በተወለዱ በሦስተኛው ቀን ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው ‹‹አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ›› ማለትም ‹‹አንዱ አብ ቅዱስ ነው አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው›› በማለት የፈጠራቸውን አምላክ አመስግነውታል፡፡ ወላጆቻቸውም ስማቸውን ፍሥሐ ጽዮን አሏቸው፡፡ ይኸውም የጽዮን ተድላዋ ደስታዋ ማለት ነው፡፡ የወላጆቻቸው የቀድሞ ስማቸው ዘርዐ ዮሐንስና ሣራ ይባል ነበር፡፡ ቅዱሳን አባቶቻችን እነ አቡነ ተክለ ሃይማኖትና እነ አቡነ ዜና ማርቆስ ሌሎቹም እነ አቡነ ሳሙኤል ዘወገግ፣ አቡነ ሕፃን ሞዐ፣ አቡነ አኖሪዮስ (ትልቁ)፣ አቡነ ገላውዲዮስ፣ አቡነ ማትያስ ዘፈጠጋርና አቡነ ቀውስጦስ ዘመሐግል የትውልዳቸው መሠረት ኢያሱ ለሌዋውያን ክፍል ትሆን ዘንድ ከለያት ከኢየሩሳሌም ነው፡፡ ስማቸውን የጠቀስኳቸው እነዚህ ቅዱሳን አባቶቻችን የወንድማማቾች ልጆች ሲሆኑ ከአዳም ጀምሮ 61ኛ ትውልድ ናቸው፡፡ ይኸውም እንዴት ነው ቢሉ ትውልዱ ከአዳም ጀምሮ በካህኑ አሮን በኩል የሆነውና የሌዋዊያን ሊቀ ካህን የነበረው የሳዶቅ ልጅ አዛርያስ በንጉሥ ሰሎሞን ዘመን ከታቦተ ጽዮንና ከብዙ ሌዋዊያን ካህናት ጋር ሊቀ ካህን ሆኖ ከኢየሩሳሌም ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ አክሱም ተቀምጦ ኖረ፡፡ የኦሪትንም ሕግ እየዞረ ለኢትዮጵያ ሰዎች አስተማረ:: ትውልዱም በአብርሃ ወአጽብሓና በአባ ሰላማ ዘመን እስከነበረው እንበረም የሚባለው ጻድቅ ድረስ ደረሰ፡፡ የእንበረምም ትውልድ ደገኛው ሕይወት ብነ በጽዮን ድረስ ደረሰ፡፡ ሕይወት ብነ በጽዮንም የደማስቆ ምድር ከሚሏት ከወለቃ ሀገር የመኮንን ልጅ የሆነችውን ወለተ ሳውልን አግብቶ አበይድላን ወለደ፡፡ አበ ይድላም በንጉሡ ድልዓዥን ዘመነ መንግሥት ለ150 ካህናት አለቃ ሆኖ በወለቃ ሀገር የክርስቶስን የወንጌል ሕግ እያስተማረ ብዙዎችን አጠመቀ፡፡ እስከ ሸዋ ምድር ድረስ እያስተማረ መጥቶ በሸዋ ምድር ተቀመጠ፡፡ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትንም አሳነጸ፡፡ እጅግ አስደናቂ ተአምራትንም ያደርግ ነበር፡፡ ‹‹በሸዋ ጽላልሽ ተቀምጦ ሲያስተምርም በአንዲት ቀን እስከ ሁለት መቶ ሺህ ሕዝብ ያጠምቅ ነበር›› በማለት ገድለ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ይመሰክርለታል፡፡ አበይድላ በመጨረሻ በፈቃደ እግዚአብሔር ከሸዋ ጽላልሽ ምድረ ዞረሬ ሚስት አግቶ ሀበነ እግዚእን ወለደ፤ ሀበነ እግዚእም በኩረ ጽዮንን ወለደ፤ በኩረ ጽዮንም ሕዝበ ቀድስን ወለደ፤ እርሱም ነገደ እግዚእ የተባለ ነው፡፡ ሕዝበ ቀድስም ብርሃነ መስቀልን ወለደ፤ እርሱም ዐቃቢነ እግዚእ የተባለ ነው፡፡ ብርሃነ መስቀልም ሕይወት ብነን ወለደ፤ እርሱም ሴትን ወለደ፡፡ ሴትም ወረደ ምሕረትን ወለደ፡፡ ወረደ ምሕረትም ዘካርያስን ወለደ፡፡ ዘካርያስም የእነ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አባት የሆኑ 6 ወንድማማች ልጆችን ወለደ፡፡ እነርሱም እንድርያስ፣ አርከሌድስ፣ ዘርዐ አብርሃም፣ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብ፣ ቀሲስ ዮሐንስና ቀሲስ ዮናስ ናቸው:: እንድርያስም ሳሙኤል ዘወገግን ወለደ፤ አርከሌድስም ሕፃን ሞዐን ወለደ፤ ዘርዐ አብርሃምም ታላቁን አኖርዮስን ወለደ፤ ዘርዐ ዮሐንስ ወይም ጸጋ ዘአብም ተክለ ሃይማኖትን ወለደ፤ ቀሲስ ዮሐንስም ዜና ማርቆስን ወለደ፣ ቀሲስ ዮናስ ደግሞ የፈጠጋሩን ማትያስንና ገላውዲዮስን ወለዳቸው፡፡ ገላውዲዮስም የመሐግሉ ቀውስጦስን ወለደ፡፡ እነዚህ ደጋግ ቅዱሳን በእናታቸውም በኩል እንዲሁ በዝምድና የተሳሰሩ ናቸው፡፡ ማቴዎስ የተባለው ደገኛ ክርስቲያን የሸዋ ገዥ የነበረ ሲሆን አንድ ወንድ ልጅ መድኃኒነ እግዚእንና ሦስት ሴቶች ልጆችን ወለደ፡፡ ሶስቱ ሴቶች ልጆችም እምነ ጽዮን፣ ትቤ ጽዮንና ክርስቶስ ዘመዳ ይባላሉ፡፡ ሦስቱ እኅትማማቾችም ደጋጎቹን አባቶቻችንን ወለዱልን፡፡ እምነ ጽዮን የእነ ዜና ማርቆስን እናት ማርያም ዘመዳንና ወለደች፡፡ ትቤ ጽዮንም ሕፃን ሞዐን ወለደች፡፡ ክርስቶስ ዘመዳ ደግሞ ታላቁን አኖሬዎስን ወለደች፡፡ የፈጠጋሩ ገዥ መድኃኒነ እግዚእ ደግሞ የተክለ ሃይማኖትን እናት እግዚእ ኀረያን ወይም በሌላ ስሟ ሣራን ወለደ፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከልጅነታቸው ጀምሮ በወላጅ አባታቸው በካህኑ ቅዱስ ጸጋ ዘአብ ግብረ ዲቁናን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው በ15 እና በ22 ዓመታቸው ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ከአቡነ ቄርሎስ (ጌርሎስ) ዲቁናንና ቅስናን ተቀብለዋል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አባታችን ቅድስት ቤተክርስቲያንን በወጣትነት ዕድሜያቸው ያገለግሉ እንደነበር በዚህ ይታወቀል፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀን አባታችን ከጓደኞቻቸው ጋር ለአደን ወደ ዱር ሄደው ሳለ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ተገልጦ ታያቸው፡፡ ቅዱስ አባታችንም ‹‹እንደዚህ ባለ ገናንነት የማይህ ጌታዬ ማነህ?›› ባሉት ጊዜ ቅዱስ ሚካኤል ‹‹ዘወትር የምጠብቅህ ካንተ የማልለይ እናትህንና አባትህንም ስላንተ ከውኃ ስጥመትና ከምርኮ ያዳንኳቸው እኔ ሚካኤል ነኝ፡፡ ከእንግዲህ አውሬ አዳኝ አትሁን፤ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ ሰውን በትምህርት የምታድን ሁን እንጂ፡፡ እነሆ እግዚአብሔር ጽኑዕ ሥልጣን ሰጥቶሃልና፤ ሙት ታስነሣለህ፤ ድውያንን ትፈውሳለህ፤ አጋንንትም አንተን በመፍራት ይሸሻሉ፡፡ ስምህ ፍሥሐ ጽዮን አይሁን፤ ተክለ ሃይማኖት ይሁን እንጂ፡፡ ትርጓሜውም ተክለ አብ፥ ተክለ ወልድ፥ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው›› አላቸው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ይህን ሲነግራቸው ጌታችን በሥጋ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር እንደነበር ሆኖ መልከ መልካም ጎልማሳ መስሎ ታያቸው፡፡ ጌታችንም ‹‹ወዳጄ እንዴት ሰነበትክ? ቸር አለህን?›› አላቸው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ‹‹ጌታዬ ሆይ አንተ ማነህ?›› ብለው ሲጠይቁት ጌታችንም ‹‹እኔ የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ነኝ፤ በናትህ ማኅፀን ፈጥሬህ ያከበርኩህ እኔ ነኝ፡፡ በተወለድክ በሦስተኛው ቀን አሐዱ አብ ቅዱስ አሐዱ ወልድ ቅዱስ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ ብለህ ታመሰግነኝ ዘንድ የምስጋና ሀብት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ በርሃብ ዘመን በቤት የሚያሻው ምግብ ሁሉ ቅቤው፣ የስንዴው ዱቄት በእናት በአባትህ ቤት ይመላ ዘንድ በእጅህ ሀብተ በረከት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ ያንን ሰው አንተን በተጣላ ጊዜ በነፋስ አውታር የሰቀለኩት በመዓት ጨንገር የገረፍኩት እኔ ነኝ፡፡ ውኃ ጠምቶህ በለመንከኝ ጊዜ ከደረቅ መሬት የጣፈጠ ውኃ ያመነጨሁልህ እኔ ነኝ፡፡ ከልጅነትህ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ብዙ ተአምራት እያደረግሁ በአንተ እጅ የታመሙትን ያዳንኳቸው እኔ ነኝ፡፡ ወደፊትም አደርግልሃለሁ›› አላቸው፡፡ ይህንን ብሎ በእጆቹ ባረካቸውና ‹‹ንሣእ መንፈስ ቅዱስ›› ብሎ የሹመትን ሀብት አሳደረባቸው፡፡ ዳግመኛም ‹‹በምድር ያሰርከው በሰማይ የታሰረ ይሁን፤

ኒቆዲሞስ የዐቢይ ጾም ሰባተኛው ሳምንት የስያሜው መነሻ ኒቆዲሞስ የተባለው የአይሁድ አለቃ ታሪክ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ በሦስት መንገድ የአይሁድ አለቃ ነበር፤ በሥልጣን፣ በዕውቀትና በሀብት፡፡ ሰው ሥልጣን ቢኖረው ሀብትና ዕውቀት ላይኖረው ይችላል፡፡ ዕውቀት ቢኖረው ደግሞ ሀብትና ሥልጣን ላይኖረው ይችላል፡፡ ሀብት ቢኖረውም ዕውቀትና ሥልጣን ላይኖረው ይችላል፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ሦስቱንም አንድ ላይ አስተባብሮ የያዘ የአይሁድ አለቃ ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ወንጌልን ለመማር ከአይሁድ ዅሉ ቀድሞ በሌሊት ወደ ጌታችን ይሔድ ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ፈሪሳውያን ማመን ባልቻሉበት በዚያን ዘመን ጆሮውን ለቃለ እግዚአብሔር፤ ልቡን ለእምነት የከፈተ ሰው ነው፡፡ ብዙ ሰዎችን እናውቃለን ማለት ከመልካም ነገር ሲከለክላቸው ኒቆዲሞስ ግን ዐዋቂ ሳለ ራሱን ዝቅ አድርጎ፣ እምነት በማጣት የነጠፈችውን የፈሪሳውያንን ኅብረት ጥሎ፣ ሐዋርያትን መስሎ ጌታውን አግኝቶታል፡፡ ጌታችን ዓለምን ለማዳን ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው በለየባት በዚያች አስጨናቂ ሰዓት፤ ሐዋርያት በተበተኑባት አይሁድ በሠለጠኑባት በዕለተ ዓርብ የጌታችንን ቅዱስ ሥጋውን በድርብ በፍታ ገንዞ የቀበረ፣ እሱን ያገኘ ያገኘኛል ሳይል በድፍረት ከእግረ መስቀሉ የተገኘ ሰው ነው – ኒቆዲሞስ፡፡ ስለዚህም ሰባተኛው ሳምንት በእርሱ ስም ተሰይሟል፡፡ ጌታችን መድኃታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ያመነ የተጠመቀ ይድናል፡፡ ያላመነ ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል፤››(ማር.፲፮፥፮) በማለት በሰጠን ቃል ኪዳን መሠረት በአምላክነቱ አምነን የመንግሥቱ ወራሾች እንሆን ዘንድ ይፍቀድልን፤ ለኒቆዲሞስ ምሥጢሩን እንደ ገለጸ ለእኛም ይግለጽልን፤ አሜን፡፡

የዛሬ መደበኛ ጉባኤ ሰዓት ስለምታከብሩ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን።
የዛሬ መደበኛ ጉባኤ ሰዓት ስለምታከብሩ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን።

አባ ሰላማን በአቃሊት ቅበረኝ ብለዋቸው በቃሬዛ አድርጎ ከጌርጌሳ ወደ አቃሊት ወሰዷቸው፤ እዚያም ሐምሌ 28 ቀን በሰላም ዐረፉ፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ሰባት አክሊላት አቀዳጅቷቸዋል፡፡ዐፅማቸውም ከተቀበረ ከ140 ዓመት በኋላ በመጋቢት 23 ቀን ወደ ደብረ ሊባኖስ በክብር መጥቶ ዐርፏል፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

እግዚአብሔርም መልአኩን ወደ እንባቆም ላከው እርሱም በኢየሩሳሌም ውስጥ ለአጫጅዎች ምሳ ተሸክም ሲሔድ በራስ ጠጉሩ ተሸከመው። ወስዶም ዳንኤል በአለበት ጉድጓድ ውስጥ አኖረው። ዳንኤልም ተመግቦ እግዚአብሔርን አመሰገነው በዕንባቆምም ቃል ተረጋጋ በዚያችም ሰዓት እግዚአብሔር የላከው መልአክ ወደ አገሩ ወደ ኢየሩሳሌም መልሶ አደረሰው። በሰባተኛዪቱ ቀንም ስለ ዳንኤል እያለቀሰ ንጉሡ ወደ ጕድጓድ መጣ ዳንኤል ሙቶ አንበሶች የበሉት መስሎት ነበርና። ወደ ጕድጓዱም ሲመለከት ዳንኤልን አየው አንበሶችም እንደ ድመቶች እግሮቹን እየላሱ ከእግሮቹ በታች እጥፍጥፍ ብለው ተኝተው ነበር። ንጉሡም እግሮቹን እስከሚልሱ እንደ ድመቶች አንበሶችን ያገረመለትና ያሰገዛለት የዳንኤል አምላክ ታላቅ ነው ብሎ ከፍ ባለ ድምፅ ጮኸ። በዚያን ጊዜ ዳንኤልን ከጕድጓድ እንዲያወጡት እነዚያንም የዳንኤልን ጠላቶች ይዘው ለአንበሶች ወደ ጕድጓድ እንዲጥሉአቸው ንጉሥ አዘዘ ወዲያው እነዚያ አንበሶች በንጉሡ ፊት በሏቸው። ዳንኤልም የእስራኤል ልጆች ወደ ኢየሩሳሌም እስከ ሚመለሱበት ጊዜ በባቢሎን ኖረ እርሷም ሰባ ዘመን ናት ከዚያም በኋላ በሰላም በፍቅር አረፈ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_ፊሊጶስ_ዘደብረ_ሊባኖስ ዳግመኛም በዚህች ቀን የአቡነ ፊሊጶስ ፍልሰተ ዐፅማቸው በክብር ተከናወነ፡፡ የደብረ ሊባኖሱ አቡነ ፊሊጶስ በተወለዱ በ15 ዓመታቸው በምናኔ ወደ ደብረ ሊባኖስ ገቡ፡፡ ከብዙ ጊዜ አገልግሎትም በኋላ በአቡነ ተክለሃይማኖት እጅ መንኩሰው ከእርሳቸውም ዕረፍት በኋላ ሦስተኛ አበምኔት ሆነው አገልግለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ከተወለዱት የመጀመሪያ ፓትርያርክ ሆነዋል፡፡ አባታቸው ቅዱስ ተክለሃይማኖትም በመንፈቀ ኢትዮጵያ ጳጳስ ሆነው ነበር፡፡ በመጀመሪያ የአቡነ ፊሊጶስን የጽድቅ ሕይወትና ሹመታቸውን በተመለከተ በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ገድልና በራሳቸው በአቡነ ፊሊጶስ ገድል ላይ የተጻፈውን እንመልከት፡- ‹‹ክቡር አባታችን አቡነ ተክለሃይማኖት ከዚህ ዓለም ተለይቶ የሚሄድበት ጊዜ ሲደርስ ‹ከአንተ በኋላ አንተን ተክቶ በዙፋንህ የሚቀመጥ ማነው?› አሉት፡፡ እርሱም ‹ብዙ ዘመን አይኖርም እንጂ ኤልሳዕ በእኔ ተተክቶ ይቀመጥ› አለ፡፡ ስለ ፊሊጶስ ግን አላነሳም፣ ኤልሳዕ ካረፈ በኋላ በእርሱ ተተክቶ አባት ይሆን ዘንድ ጌታችን የተሸለመ ፊሊጶስን እንደመረጠው ስም አጠራሩ ለልጅ ልጅ ዘመን እንደሚጸና ያውቅ ነበርና ስለዚህ ‹አልሳዕ በእኔ ተተክቶ አባት ይሁናችሁ› አለ፡፡ ክቡር አባታችንም በታላቅ ክብር ዐረፈ፡፡ አንድ ቀን አንድ ዲያቆን ዐረፈና ሬሳውን ገንዘው አጠቡት፣ ይቀብሩትም ዘንድ አስክሬኑን ይዘው ሲሄዱ በአልጋ ላይ ሳለ አስክሬኑ ተንቀሳቀሰ፡፡ የተሸከሙትም ደንግጠው መሬት ላይ አስቀመጡትና ከመግነዙ ፈቱት፡፡ እርሱም ተነሥቶ ሦስት ጊዜ ተነፈሰ፡፡ ወንድሞችም ‹ምን እያልክ ነው?፣ ወዴትስ ነበርክ?› አሉት፡፡ ያ የከበረና የተመረጠ ዲያቆንም ‹ክቡር አባታችን ተክለሃይማኖት ‹ኤልሳዕ ወደኔ ይምጣ፣ ፊሊጶስ ስለ እኔ ተሹሞ በወንበሬ ይቀመጥ እርሱ ለብዙዎች አሕዛብ አባት ይሆናልና የክርስቶስንም መንጋ በጽድቅና በቅን ይጠብቃል› ብሎኛል› ብሎ ይህን ተናግሮ ተመልሶ ዐረፈ፡፡ ወንድሞችም ኤልሳዕ እንደልማዱ ጎኑን ሳያሳርፍ በወንበር ላይ እንደተደገፈ በሞት ማረፉን አላወቁም ነበር፡፡›› ወደ ጻድቁ የልጅነት ገድላቸው እንመለስና አቡነ ፊሊጶስ በእግዚአብሔር ተመርጠው የመንፈስ ቅዱስም ማደሪያ ሆነዋልና ገና በሕፃንነታቸው በተወለዱባት ሰላሌ ክፍለ ሀገር ዝማ በምትባል ልዩ ቦታ ውስጥ ሰይጣን በጠንቋይ ላይ አድሮ በነደደ በእሳት ውስጥ በመግባትና የተለያዩ ተአምራትን በማድረግ በአካባቢው ራሱን ያስመልክ የነበረን ሰይጣን በእሳት ውስጥ እንዳለ በስመ ሥላሴ አማትበውበት አመድ አድርገውታል፡፡ በዚህ በአቡነ ፊሊጶስ ድንቅ ተአምር የጠንቋዩ ቤተሰቦችና የአካባቢው ሰዎችም አምነው ሊጠመቁ ችለዋል፡፡ ይህንንም ያደረገው ገና ሕፃን ሳለ ነው፡፡ መልአከ እግዚአብሔር ተገልጦለት የትውልድ መንደሩን ትቶ ወደ ግራርያ ሀገር ደብረ አስቦ ሄዶ ቅዱስ ተክለሃይማኖትን እንዲያገኝ በነገረው መሠረት አንድ ቀን ያህል ተጉዞ ተክለሃይማኖትን አገኛቸውና ባርከውት ከመነኮሳት ጋር እንዲያርፍ አደረጉት፡፡ ሦስት ዓመት እነርሱን በመልካም ሥራ ፍጹም ሆኖ ሲያገለግላቸው ከቆየ በኋላ ‹‹ሁሉም በአንድነት አሁን ልብሰ ምንኩስና ይገባዋል›› አሉ፡፡ ቅዱስ አባታችን ተክለሃይማኖትም የምንኩስናን ሥራ የሚያሠራ ቅድስናን ሰጠው፡፡ በሌላም ጊዜ ቅስናን ይቀበል ዘንድ ወደ ጳጳሱ ዘንድ ላኩት፡፡ አቡነ ፊሊጶስ በንጉሥ አምደ ፅዮን ዘመነ መንግሥት ሥጋቸው አልቆ አጥንታቸው እስኪቀር ድረስ ሲገረፉ ደማቸው እሳት ሆኖ ገራፊዎቻቸውን ያሳደደ ቅዱስና ጻዲቅ አባት ናቸው፡፡ ንጉሥ አምደ ጽዮን በክፉ ጠንቋዮች ምክር ተታሎ ‹‹ያልወለደችህን የአባትህን ሚስት ብታገባ መንግሥትህ ትፀናለች›› ብለው ክፉ ምክርን መክረውት የእንጀራ እናቱን አገባትና ንግሥት አደረጋት፡፡ አቡነ ፊሊጶስም ይህን ሲሰሙ ነቢዩ ኤልያስ ንጉሡ አክአብንና አልዛቤልን በድፍረት እንደገሠጻቸው እርሳቸውም በቀጥታ ሄደው ንጉሡን ዘልፈው ገሠጹት፡፡ ወደ ንጉሡም ከመሄዳቸውም በፊት በዚህ ምክንያት ሰማዕት እንደሚሆኑ አውቀውት ነበርና ልጆቻቸውን ተሰናብተውና የሚተካቸውን ሰው ነግረዋቸው ነው የሄዱት፡፡ ንጉሡ አምደ ጽዮንም አጥንታቸው እስኪቀር ድረስ አስገረፋቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቶቻቸውም መሬት ላይ እየተቆረሰ የወደቀውን ሥጋቸውን እያነሱ ለበረከት ወሰዱት፡፡ ደማቸውም እንደ እሳት ሆኖ ገራፊዎቻቸውን ያቃጥላቸው ነበር፡፡ 300 አንስራ ውኃ አምጥተው ከደሙ በወጣው እሳት ላይ ቢያፈሱትም የውኃው ብዛት እሳቱን ማጥፋት አልቻለም፡፡ ንጉሡም በፍርሃት ከዙፋኑ ላይ ወርዶ ሸሸ፡፡ የንጉሡ ጭፍሮች ግን በጋለ ማረሻ ጀርባና ግንባራቸውን ደረታቸውንም ተኮሷቸው፡፡ ኃፍረታቸውንም እንዳይሸፍኑ እጆቻቸውን ወደ ኋላ አስረው ራቁታቸውንም በከተማው ሁሉ ሲያዞሯቸው ዋሉ፡፡ ማታም ንጉሡ ‹ታስረው ለኖሩ ኃይለኛ ውሾች ስጡት› ብሎ በማዘዝ ውሾቹ እንዲቦጫጭቋቸው ቢያደርጉም ውሾቹ ግን ከእግራቸው ስር ሰግደዋል፣ እርሳቸውም በእግራቸው ባረኳቸው፡፡ አማካሪዎቹም ንጉሡን ‹‹ከዚህ መነኩሴ ጋር ምን አጨቃጨቀህ በግዞት አርቀህ ስደደው ብለው›› ብለው መክረውት ‹‹እስከ ቆርቆራ አገር አውጥታችሁ ወደ ትግሬ አገር ውሰዱት›› ብሎ አዘዘ፡፡ እርሳቸውም ንጉሡን ከ3 ዓመት በኋላ ትሞታለህ ብለው ትንቢት ነገረውት በወታደሮች ተወሰዱ፡፡ በግርፋት ብዛት የተቆረሰ ሥጋቸው ድውያንን ይፈውስ ነበር፡፡ ደማቸውም አስረው የሚወስዷቸውን የአንዱን ወታደር አንድ ስውር ዐይኑን ፈወሰለትና ወታደሮቹም አምነው ከእርሳቸው ጋር በዚያው ተሰደው መከራን ተቀብለዋል፡፡ እሳቸው በትግራይ ታላላቅ ተአምራትን እያደረጉ ሲያስተምሩ በትንቢታቸው መሠረትም ንጉሡ ከሦስት ዓመት በኋላ ሞተና ልጁ ነገሠ፡፡ ልጁም አባታችንን ከስደት መለሳቸውና ከተክለሃይማኖት መቃብር ደብረ አስቦ ገቡ፡፡ የነገሠውንም ልጅ አንድ ክፉ ሰው ‹‹ከአንድ በላይ ማግባት ትችላለህ፣ በገና ወቅትም ረቡዕና አርብን መጾም ተገቢ አይደለም›› ብሎ ስለመከረው ጳጳሱን ወደ ሀገራቸው ግብፅ እንዲሰደዱ ሲያደርግ አቡነ ፊሊጶስን ደግሞ ‹‹ረቡዕና አርብን በጠዋት ካልቀደስክ›› ብሎ ወደ ደራ ተሰደው እንዲሄዱ አደረገ፡፡ አባታችን በአጠቃላይ አምስት ጊዜ ተሰደው በትግራይ፣ በደራ፣ በዝዋይ ባሕረ ደሴት፣ በዳሞት ገማስቄ እና በወለቃ በስደት ቆይተዋል፡፡ ጳጳሱን

🔴#ስንክሳር መጋቢት_23 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ ሦስት በዚች ቀን ታላቁ_ነቢይ_ዳንኤል አረፈ፣ የደብረ ሊባኖሱ #አቡነ_ፊሊጶስ ፍልሰተ ዐፅማቸው በክብር ተከናወነ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ነቢዩ_ቅዱስ_ዳንኤል መጋቢት ሃያ ሦስት በዚች ቀን የዮናኪር ሴት ልጁ የወለደችው ታላቅ ነቢይ ዳንኤል አረፈ። ናቡከደናጾርም ኢየሩሳሌምን በወረራት ጊዜ አባታቸው ዮናኪር አናንያን አዛርያንና ሚሳኤልን ሦስቱን ልጆቹን የልጁን ልጅ ዳንኤልንም ወሰዳቸው ከእንርሱም ጋር ከእስራኤል ልጆች ብዙ ሰዎች ተማረኩ ። ይህም ዮናኪር የንጉሡ የኢዮአቄም ልጅ ነው። ኢሳይያስ ለሕዝቅያስ ንጉሥ ትንቢት እንደተናገረ የቤተ መንግሥቱንና የቤተ እግዚአብሔርን ዕቃ ሁሉ ናቡከደነጾር ወደ ባቢሎን ወሰደ። ይህ ዳንኤል ያን ጊዜ በዕድሜው ታናሽ ነበር ፍጹም የሆነ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ የእግዚአብሔር መንፈስም አድሮበት በባቢሎን አገር ትንቢት ሲናገር ኖረ። ምርኮ በሆነ በአራተኛው ዓመት ናቡከደነጾር የምታስፈራ ራእይን አየ ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ያቺን ሕልም ረሳት። በባቢሎን የሚኖሩትን ሁሉን ጥበበኞች ሰበሰባቸው ከእርሳቸውም ያቺን ራእይና ትርጓሜዋንም እንዲነግሩት ፈለገ እንርሱ ግን ያቺን ራእይና ትርጓሜዋን ሊያውቋት አልቻሉም። የባቢሎንን ጥበበኞች ሁሉ እርሱንና ባልንጀሮቹ ሠለስቱ ደቂቅን ይገድሏቸው ዘንድ ንጉሥ አዘዘ። ዳንኤልም ይህን ነገር ሰምቶ የዘበኞችን አለቃ ስለ ምን እንዲህ ያለ ትእዛዝ ከንጉሥ ዘንድ ታዘዘ ብሎ ጠየቀው። እርሱም ንጉሥ ስለ አያት ራእይ ነው የባቢሎንና የግብጽ ጠቢባን ሁሉ እርሷን ራእዩን ትርጓሜዋንም ሊነግሩት አልተቻላቸውምና ብሎ መለሰለት። ዳንኤልም የዘበኞቹን አለቃ እኔ ለንጉሥ ሕልሙን እንደምነግረውና ፍቺውንም እንደምተረጕምለት ስለ እኔ ንገርው እሊህንም ተዋቸው አለው ። ከዚህ በኋላም ዳንኤልም ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ባልንጀሮቹ ሠለስቱ ደቂቅም ከእርሱ ጋር የንጉሡን ሕልም ፍቺዋንም ይገለጥላቸው ዘንድ በአንድነት ማለዱ። እግዚአብሔርም ገለጠላቸው ዳንኤልም ወደንጉሥ ገብቶ ሕልሙንና ፍችዋን ነገረው። ከእርሱ በኋላም ስለሚነሡ ነገሥታት ከእንርሱም ከየአንዳንዳቸው የሚሆነውንም ገለጠለት። የዳንኤል ቃል ናቡከደነጾርን ደስ አሰኘው በፊቱም ሰገደ ብዙ እጅ መንሻንም ሰጠው ታላቅ ክብርንም ሰጥቶ በባቢሎን ጠቢባን ሁሉ ላይ አለቃ አድርጎ ሾመው። ከዚህም በኋላ ናቡከደነጾር ሌላ ሕልም አየ ያንንም ተረጐመለት እንዲህም ብሎ አስረዳው ስለታበይክ እግዚአብሔር ከሰው መካከል አውጥቶ ከአራዊት ጋራ በዱር ሰባት ዓመት ያኖርህ ዘንድ አለው። እንደ እንስሳም ሣር ትበላለህ ከሰባት ዓመትም በኋላ ወደ መንግሥትህ ይመልስሃል ፈ በማለት ይህም ተፈጸመበት። ናቡከደነጾር ከሞተ በኋላ መልአክ በግድግዳ ላይ የጻፋትን ለልጁ ለብልጣሶር ተረጐመለት በቤተ እግዚአብሔር ዕቃ በጠጣ ጊዜ ጽሑፉ የተቆጠረ የተመጠነ የተመዘነ እንደሆነ ትርጓሜውም ዙፋኑንና መንግሥቱን እግዚአብሔር ለሌላ የሰጠው መሆኑን ገለጠለት። እንዲህም አለው ቢመዝንህ ጐደሎ ሆነህ አገኘህ መንግሥትህንም ለፋርስ አሳልፎ ሰጠ ትንቢቱም ተፈጸመች። እግዚአብሔርም እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚነግሡትን ነገሥታት በራእይ አሳየው የሐሳዊ መሲሕንም መገለጥ አሳየው። ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔርነቱን ክብር ልዕልናውን ጌትነቱን አሳየው። የክበር ባለቤት ክርስቶስን ወደ ዓለም መምጣቱን ትንቢት ተናገረ ሱባኤዎችንም ወሰነ እንዚያ ሱባኤዎችም በተፈጸሙ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መጣ። ክርስቶስ ይመጣል ይገድሉታልም ለኢየሩሳሌምም መዳኛዋ ይሆናታል ብሎ ትንቢት እንደ ተናገረ። የክብር ባለቤት ከሆነ ከጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ስቅለት በኋላ ኢየሩሳሌም እንደምትጠፋ ቤተ መቅደስም እንደሚፈርስ የተናገረው ትንቢት ሁሉ ተፈጸመ። በባቢሎን አገርም ቤል የሚባል ጣዖት ነበረ ምግብንም ሁልጊዜ ዐሥራ ሁለት ጫን በሚፈጅ ቻል ዐሥራ ሁለት መስፈሪያ ስንዴ አርባ በግ ሰባት ፊቀን የወይን ጠጅ እያወጣጡ ይሰጡት ነበር። ንጉሡም ሁልጊዜ ይሰግድለታል ቤል ጣዖትም ከንጉሡ ቤት የሚሰጡትን የሚበላና የሚጠጣ ይመስለው ነበር ። ንጉሡም ዳንኤልን ለቤል የማትሰግድ ለምንድን ነው አለው። ዳንኤልም ንጉሡን እኔስ ሰማይንና ምድርን ለፈጠረ ፍጥረቱንም ሁሉ በሕያውነት ለሚያኖር አምላክ እንጂ የሰው እጅ ለሠራው ጣዖት አልሰግድም አለው። ንጉሡም ቤል ሕያው ያልሆነ ይመስላሃልን በየነጋታው እንዲበላ እንዲጠጣ አታይምን አለው። ዳንኤልም በንጉሡ ሳቀበት ንጉሥ ሆይ ይበላል ይጠጣል እያሉ አያታሉህ ይህ ውስጡ ጭቃ ላዩ ናስ ነው ምንም ምን አይበላም አይጠጣም አለው። ንጉሡም ተቆጣ የጣዖቱንም ካህናት ጠራቸው እውነት ነውን ቤል አምላክ አይበላም አይጠጣምን አላቸው። ሁልጊዜ የምንሰጠውን በዕውነት ይበላል ይጠጣል አሉት። ከዚህም በኋላ በመሸ ጊዜ ከጣዖቱ ዘንድ መብሉንና መጠጡን ሁሉ ንጉሡ እየተመለከተ ካህናቱ አስቀምጠው ወጡ። የጣዖቱ ካህናትም ከወጡ በኋላ ዳንኤል አመድ አምጡ ብሎ አዘዘ አመጡለትም። ንጉሡም ከዚያ ሁኖ እያየ በጣዖቱ ቤት ውስጥ ነሰነሰው። ንጉሡም በቁልፉ ከዳንኤል ጋር በአንድነት ቈለፉት አተሙትም ወደ ማደሪያቸውም ሔዱ። የጣዖቱ ካህናት ግን ከምድር በታች ውስጥ ለውስጥ መግቢያ ቀዳዳ ነበራቸው ከሚስቶቻቸውና ከልጆቻቸው ጋራ በሌሊት በዚያ ገብተው በሉ ጠጡ በመጡበትም ተመለሱ። በማግሥቱም ንጉሡ መጥቶ የጣዖቱን ቤት ከፈተ ራሱ ከአኖረው መብሎች ምንም አላገኘም ንጉሥም ቤል ሆይ ፈጣሪዬ ዳንኤልን ያሳፈርከው አንተ ገናና ነህ ብሎ ጮኸ። ዳንኤልም ሳቀ ለንጉሡም የወንዶችና የሴቶችን የልጆችንም ፍለጋቸውን በአመድ ላይ አሳየው። ንጉሡም የጣዖቱን ካህናት ይዞ መረመራቸው እነርሱም ውስጥ ለውስጥ ተሠውረው የሚገቡበትንና የሚወጡበትን ለንጉሡ አሳዩት። ያን ጊዜ ንጉሡ ተቆጥቶ የጣዖቱን ካህናት ከሚስቶቻቸውና ከልጆቻቸው ጋራ ገደላቸው ጣዖቱንም ለዳንኤል ሰጠው። ዳንኤልም ሰበረው ምኲራቡንም አፈረሰ። ከዚህ በኋላ ደግሞ የባቢሎን ሰዎች የሚአመልኩትና የሚሰግዱለት ታላቅ ዘንዶ ነበር ንጉሡም ዳንኤልን ይህንንስ አምላክ አይደለም ትለዋለህን እነሆ ሕያው ነው ይበላል ይጠጣል ናስ ነው ትለው ዘንድ አትችልምና ስገድለት እንጂ አለው። ደንኤልም ለንጉሡ እንዲህ ብሎ መለሰለት እኔስ በሕያውነት ከሚኖር ከእግዚአብሔር በቀር ለሌላ አልሰግድም ግን ያለ ሰይፍና ያለ በትር ይህን ከይሲ እገድለው ዘንድ አሰነሰብተኝ አለው። ንጉሥም አሰናበትኩህ አለው። ዳንኤልም ጠጉርና አደሮ ማር ወስዶ እንደ እንቁላልም አድበልብሎ በእሳት አጋለው በሞራም ጠቅልሎ ለከይሲው አጐረሰው በዋጠውም ጊዜ ሆዱ ተሰንጥቆ ሞተ ዳንኤልም የባቢሎን ሰዎች ሆይ አምላካችሁን ተመልከቱ አላቸው። የባቢሎን ሰዎችም በሰሙ ጊዜ እጅግ ተቆጡ ወደ ንጉሡም ተሰብስበው አይሁዳዊው ዳንኤል ነግሦአልን እነሆ ቤልን ሰበረው ካህናቶቹንም ገደላቸው ከዚያም ደግሞ ዘንዶውን ገደለው አሁን እርሱን ዳንኤልን እንድንገድለው ካልሰጠህን አንተን ቤተ ሰብህንም እንገድላለን አሉት። ንጉሡንም እጅግ በአስጨነቁት ጊዜ ስለ ዳንኤል አዘነ ግን ዳንኤልን ሰጣቸው እነርሱም በአንበሶች ጉድጓድ ውስጥ ጣሉት በዚያም ሰባት ቀን ኖረ። ከረኀብ ጽናትም የተነሣ እንዲበሉት በሌላ ጊዜ የሚሰጧቸውን በእነዚያ ቀኖች ምንም ምን አልሰጧቸውም ነበር።

9. ምንም እንኳን አስቀድሞ ከክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስቴር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ እና ክቡር አቶ ሽመልስ አብዲሳ የኦሮምያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝዳንት ጋር በተደረገው ውይይትና ስምምነት መሠረት የታሰሩት ግለሰቦች በሙሉ እንደሚፈቱ ቃል የተገባ ቢሆንም እስካሁን ድረስ በርካታ ሰዎች በእስር ላይ የሚገኙ ስለሆነ መንግስት አስቀድሞ በገባው ቃል መሠረት ሁሉንም እስረኞች እንዲፈታልን ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ ያሳስባል፡፡ 10. በተከሰተው ችግር ከሀገረ ስብከት እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ባሉት የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ላይ በኃላፊነት ተመድበው ሲሰሩ ቆይተው በችግሩ ምክንያት ተፈናቅለው የቆዩት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፣ የሀገረ ስብከትና የወረዳ ቤተ ክህነት ሠራተኞች ያለምንም የፀጥታ ስጋት በምድብ ሥራቸው ላይ እንዲቀጥሉ ከፌዴራል ጀምሮ በየደረጃው ያሉ የመንግስት አካላት ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡   መጋቢት 21 ቀን 2015 ዓ.ም. አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

መ. ቅዱሳን ሐዋርያት ከወሰኗቸው የሕግጋት መጻሕፍት መካከል አንዱ በሆነው በመጽሐፈ ዲድስቅልያ አንቀጽ 1 ንዑስ አንቀጽ 2 ላይ “ወአዘዝነ ከመዝ መዓረገ ሢመታት ለቤተ ክርስቲያን በአርአያ ዘበሰማያት የቤተ ክርስቲያናችን የሹመቶች መዓረግ በሰማያት ባለው አምሳል እንዲሆን አዘዝን” በማለት በንዑስ አንቀጽ 3 ላይ “ወንሕነ ንጌሥጽክሙ ከመ ይንበር ኲሉ ለለ አሐዱ አሐዱ እምኔክሙ ውስተ ዘተጸውዐ እምኀበ እግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ - ከእናንተ ሁሉ እያንዳንዱ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ በተጠራበት ተልእኮ ጸንቶ ይኖር ዘንድ እኛ እንመክራችኋለን በማለት እያንዳንዱ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን በተሰጠው ፀጋና ተልእኮ ጸንቶ ከሚኖር በቀር ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ ባልተሰጠውና ባልተፈቀደለት በሕገወጥ መንገድ ሊሾምም ሆነ ሊሾም እንደማይገባው የሚያስተምረን አምላካዊ ቃል ነው፡፡ ሠ. ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ በመጽሐፈ ዲድስቅልያ አንቀጽ 20 ላይ “በእንተ ዘይሰየም በህልያን እመሂ ኤጲስ ቆጶስ አው ቀሲስ አው ዲያቆን ዘይእኀዝ መዓርገ ሢመት በሕልያን ይሰአር፤ ወይሰዐር ዘሤሞሂ ወይትመተር ለዝሉፉ እምሥርዐተ ክህነት፤ ወኢይሳተፍዎ ወኢበምንትኒ በከመ ረሰይክዎ ለሲሞን መሠርይ እምኀቤየ አነ ጴጥሮስ - መማለጃ በመስጠት ስለሚሾም ኤጲስ ቆጶስ ወይም ቄስ ወይም ዲያቆን ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ የሹመት መዓርግ ቢይዝ ይሻር፣ የሾመውም ይሻር ከክህነት ሥርዓትም እስከ መጨረሻው ይባረር፡፡ እኔ ጴጥሮስ ጠንቋዩ ሲሞንን እንዳደረግሁት በምንም ነገር አያሳትፉት (ሲኖ.ዘሐዋ.ክፍል 3 ቁጥር 20) በማለት ቅዱስ ጴጥሮስ ሥልጣነ ክህነትን ያለአግባብ የሰጠም ሆነ የተቀበለ አካል እስከመጨረሻው ድረስ ከሥርዓተ ክህነት ውጭ እንዲሆን አውግዟል፡፡ በማለትና ሌሎችንም ሕገ ቤተ ክርስቲያንንና ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ዋቢ በማድረግ በሊቃውንት ጉባኤ የቀረበውን የውሳኔ ምክረ ሐሳብ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በአድናቆትና በአክብሮት ተቀብሎ ተወያይቶበታል፡፡         በመሆኑም ከላይ ቀኖና ሕገ ቤተ ክርስቲያን መሠረት አድርጎ ከቀረበው ምክረ ሐሳብና በቤተ ክርስቲያኒቱና በምዕመናን ላይ ከደረሰው ሞት፣ የአካልና የሞራል ጉዳት፣ እስራትና እንግልት አንጻር ውግዘቱ ሊነሣ የማይገባውና በሕግም የሚያስጠይቅ ሕገወጥ አድራጎት ቢሆንም አሁን በተከሰተው ድርጊት በአጭር ጊዜ ውስጥ በእናት ቤተ ክርስቲያን ላይ እና በተከታዮቿ ምዕመናንና አገልጋዮቿ ላይ ከደረሰው ከፍተኛ ጉዳት አንጻር ችግሩን በሆደ ሰፊነትና በይቅር ባይነት መፍታት ካልተቻለ አሁን ያለው መከራና ችግር ይቀጥል ቢባል በቀጣይ በቤተ ክርስቲያኒቱ አንድነትና ሐዋርያዊ ተልዕኮ እንዲሁም በምዕመናንና አገልጋዮቿ ሰላማዊ ኑሮ ላይ የሚያደርሰውን ከፍተኛ የሆነ አደጋ ከግምት ውስጥ በማስገባት እና ካሁን ቀደም ክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ በተገኙበትና በመቀጠልም ክቡር አቶ ሽመልስ አብዲሳ የኦሮምያ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ፕሬዝዳንት በተገኙበት በተደረገው ውይይት በተደረሰው 10ሩ የስምምነት ነጥቦች መሠረት ቅዱስ ሲኖዶስ በስፋት ከተወያየ በኋላ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፏል፡፡  1. የካቲት 8 ቀን 2015 ዓ.ም. በክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚ/ር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ መሪነት ወደ ጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ በመምጣት እስካሁን ድረስ በበዓታቸው ጸንተው የቆዩት 3ቱም የቀድሞ ሊቃነ ጳጳሳት ማለትም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ እና ብፁዕ አቡነ ዜናማርቆስ ላይ አስቀድሞ ጥር 18 ቀን 2015 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተላለፈው ውግዘት ከዛሬ መጋቢት 21 ቀን 2015ዓ.ም. ጀምሮ ተነስቷል፡፡ 2. ውግዘቱ የተነሣላቸው 3ቱም ሊቃነ ጳጳሳት ከዛሬ መጋቢት 21 ቀነ 2015ዓ.ም. ጀምሮ በቀድሞ የሊቀ ጳጳስነት ማዕረጋቸውና ስማቸው ማለትም ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ሊቀጳጳስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤዎስጣቴዎስ ሊቀጳጳስ እና ብፁዕ አቡነ ዜናማርቆስ ሊቀጳጳስ ተብለው እንዲጠሩና አስቀድሞ ተመድበው ይሰሩበት በነበረው የሥራ ኃላፊነታቸው ሥራቸውን እንዲቀጥሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ 3. ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በተገኙበት በተደረገው ውይይት በተደረሰው ስምምነት መሠረት ጥሪውን ተቀብለው ለስምምነቱ ተገዥ በመሆን በጽሑፍ ጥያቄያቸውን ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ያቀረቡት 20ዎቹ የቀድሞ መነኮሳት ጥር 18 ቀን 2015 ዓ.ም. በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ የተላለፈው ውግዘት ከዛሬ መጋቢት 21 ቀን 2015 ዓ.ም. ጀምሮ ተነስቷል፡፡ ቀሪዎቹ 5ቱ ባለው ጊዜ ተጠቅመው ወደቤተ ክርስቲያናቸው እንዲመለሱ ቅዱስ ሲኖዶስ በድጋሚ እያሳሰበ ውግዘቱን በሚመለከት በቋሚ ሲኖዶስ በኩል ታይቶ እንዲፈጸም ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡  4. ውግዘቱ የተነሣላቸው 20ዎቹም የቀድሞ መነኮሳት አስቀድሞ በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት ከዲቁና እስከ ቁምስና ባለው ማዕረገ ክህነታቸው እንዲያገለግሉ እና በምንኩስና ስማቸውም እንዲጠሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡ 5. 20ዎቹ የቀድሞ መነኮሳት የሥራ ምደባን በተመለከተ በተደረሰው ስምምነት መሠረት በቀድሞው የሥራ መደብ ደረጃቸው እንዲመደቡ ቅዱስ ሲኖዶስ በመወሰን ዝርዝር ጉዳዩ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ በኩል እንዲፈጸም ቅዱስ ሲኖዶስ አዟል፡ 6. በተከሰተው ሕገወጥ ድርጊት መነሻነት ለቤተ ክርስቲያናችን ክብርና ልዕልና ሲሉ ለሞት፣ ለአካልና የሞራል ጉዳት፣ ለእስራትና እንግልት እንዲሁም ለስደት የተዳረጉትን ምዕመናን፣ ወጣቶች፣ አገልጋይ ካህትና ከሀገረ ስብከት እስከ አጥቢያ ያሉ የሥራ ኃላፊዎችን ጉዳትና  መከራ እንዲሁም ችግሩን በሕግ አግባብ እንዲፈታና የቤተ ክርስቲያኒቱ መብትና ጥቅም እንዲከበር ሌሊት ከቀን በማገልገል ላይ የሚገኙትን የሕግ ባለሙያዎች ማህበር የሰጡትን ሙያዊ አገልግሎት ቅዱስ ሲኖዶስ ዘወትር በከባድ ሐዘንና ጸሎት ሲያስታውሰው የሚኖርና በቀጣይ በቤተ ክርስቲያኒቱ የታሪክ መዛግብት ተመዘግቦ ለቀጣዩ ትውልድ መማሪያነት እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡  7. ውግዘቱ የተነሣላችሁ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋይ አባቶችም በቀጣይ በፈጸማችሁት ድርጊት የተጎዳውን መላው ሕዝበ ክርስቲያን እና ክብሯ የተደፈረውን እናት ቤተ ክርስቲያናችሁን ሊክስ በሚችል የትሕትና መንፈስ በማገልገልና ዳግመኛ ከእንዲህ ዓይነቱ ሕገወጥ አድራጎት በመራቅ የተጣለባችሁን ከፍተኛ ኃላፊነት በታማኝነት እንድትወጡ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥብቅ ያሳስባል፡፡ 8. በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የደረሰውን ፈተና እንዲወገድና የቤተ ክርስቲያኒቱ መብትና ክብር እንዲጠበቅ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወክላችሁ ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ በመሩት የውይይት መድረክ ላይ በመሳተፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከታችሁ  ሦስቱ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕ አቡነ ናትናኤል፣ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ እና ብፁዕ አቡነ ሩፋኤል እና አቀራራቢ የሀገር ሽማግሌዎች እንዲሁም በፍትሕ አደባባይ ክስ በመመስረት የደከማችሁ የሕግ ባለሙያዎች ማህበር እና ችግሩን ለመላው ዓለም በማዳረስ ሰፊ ሥራ የሠራችሁ የሚዲያ ተቋማትን ቅዱስ ሲኖዶስ ለሰጣችሁት ታሪክ የማይረሳው አገልግሎት በእጅጉ ያመሰግናል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ መጋቢት 21/2015 ዓ.ም ጥር 14 ቀን 2015ዓ.ም. በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሐሮ ባለወልድ ቤተ ክርስቲያን የተፈጸመውን ሕገወጥ የኤጲስ ቆጶሳት ሹመትን ተከትሎ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ጥር 18 ቀን 2015ዓ.ም. ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ የተከናወነው ድርጊት የቤተ ክርስቲያኒቱን ዶግማ፣ ቀኖና አስተዳደራዊ መዋቅር የጣሰ ሕገወጥ አድራጎት መሆኑን አጽንኦት ሰጥቶ በመወያየት ሕገወጡን ሹመት ያከናወኑትና ተሿሚዎችን በቤተ ክርስቲያናችን ቀኖናዊ ሥርዓት ከዲቁና ጀምሮ የነበራቸውን ማዕረገ ክህነት በሙሉ በመሻር ከቤተ ክርስቲያኒቱ አባልነት አውግዞ መለየቱ የሚታወስ ነው፡፡ ምንም እንኳን የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በውሳኔው ውግዘቱ እንደተጠበቀ ሆኖ በድርጊታቸው ተጸጽተው እና ከስህተታቸው ተመልሰው በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓት መሠረት የሚሰጣቸውን ቀኖና ተቀብሎ ለመመለስ ዝግጁ ከሆኑ የቤተ ክርስቲያኒቱ የይቅርታ በር ክፍት መሆኑን በማሳወቅ መግለጫ የሰጠ ቢሆንም ግለሰቦቹ ከስህተታቸው ተምረው በይቅርታ እድሉ ከመጠቀም ይልቅ በሕገወጥ መንገዱ ቀጥለውና ውግዘቱን ጥሰው በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕጋዊ መዋቅራዊ አደረጃጀት መሠረት ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በቅዱስ ሲኖዶስ ተመድበው በሚያገለግሉባቸው አህጉረ ስብከት ላይ እርስ በርሳቸው በመመዳደብ እያደረጉት የነበረውን ሕገወጥ እንቅስቃሴ መንግስት በሕግ የተጠላበትን ሕግን የማስከበር ኃላፊነት በመወጣት የቤተ ክርስቲያናችንን ተቋማዊ ልዕልና እንዲያስከብርልን ከመግለጫም አልፎ በደብዳቤ ያቀረብነው ጥያቄ ተቀባይነት አጥቶ በሕገወጥ መንገድ የተሾሙት ግለሰቦች በመንግሥታዊ የፀጥታ አካላት ታጅበው በኦሮምያ ክልል የሚገኙትን አህጉረ ስብከት፣ ወረዳ ቤተ ክህነት፣ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትን በኃይል ሰብረው ተቋማቱን በመውረር ሀብትና ንብረት የተዘረፈ ሲሆን ይህም ሕገወጥ ድርጊት በሚከናወንበት ወቅት ሕገ ቤተ ክርስቲያናችን አይጣስም፣ ሲኖዶሳችን አይከፈልም፣ ቀኖናችን አይደፈርም በማለት በጽናትና በአንድነት ድርጊቱን የተቃወሙት ምዕመናን፣ ወጣቶችና አገልጋይ ካህናት እንዲሁም በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልዩ ልዩ የሥራ ኃፊዎች በተለይም የሻሸመኔና አካባቢው ምእመናንና አገልጋይ ካህናት ለሞት፣ ለአካልና የሞራል ጉዳት፣ ለእስራትና እንግልት ተዳርገዋል፡፡  በዚህም ምክንያት ቅዱስ ሲኖዶስ ችግሩን እና ፈተናውን የማሳለፍ ሥልጣን ሁሉ ባለቤት የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን በምሕረት አይኑ ተመልክቶ የመጣውን ፈተና ያስወግድልን ዘንድ በጾመ ነነዌ ለ3 ቀናት ሁሉም የቤተ ክርስቲያኒቱ እምነት ተከታዮች ማቅ ለብሰው በጸሎትና በምህላ ወደ እግዚአብሔር እንዲያመለክቱ በወሰነው መሠረት በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ ተፈጽሞ በማያውቅ ሁኔታ እንኳንስ ልጆቿ ምእመናን ይቅርና እራሷ እናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም የሀዘን መገለጫ የሆነውን ጥቁር ማቅ ለብሳ ከሀገር አቀፍም አልፎ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሐዘኗን ገልጣለች፡፡ የእናት ቤተ ክርስቲያንና የልጆቿ ምዕመናን እንባና ጸሎት በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት በማግኘቱ ለውይይት ዝግ የነበረው የመንግስታችን በር ለውይይት ተከፍቷል፡፡ የደረሠብን የጉዳት ከፍተኛነት በሀገራችን መንግስታዊ ሚዲያዎች ዘንድ ቦታ ቢያጣም አለም አቀፍ ሚዲያዎችና የቤተ ክርስቲያናችን የሚዲያ ተቋማት ለአለም አቀፍ ማህበረሰብ እንዲደርስ በማድረጋቸው ችግሩን ከእኛም አልፎ በሁሉም አኃት አብያተ ክርስቲያናት፣ የአለም አብያተ ክርስቲያናት ሕብረት፣ የምሥራቅ ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት እና ሌሎች ሲቪክ ማህበራት ድርጊቱን በማውገዝ ለእናት ቤተ ክርስቲያናችን ያላቸውን አጋርነት ገልጸዋል፡፡ በዚህም በችግራችን ወቅት ከጎናችን ለቆሙት አካላት በሙሉ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አሁንም በድጋሚ ከፍ ያለ ምስጋናዋን ታቀርባለች፡፡ በመጠቀልም ክቡር የኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስቴር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ባመቻቹት የውይይት መድረክ በተወከሉ ብፁዓን አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች በኩል በተደረገው መጠነ ሰፊ ውይይት መሠረት ባለ10 ነጥቦች ላይ የጋራ ስምምነት በተደረሰው መሠረት ሦስቱ የቀድሞ አባቶች የካቲት 8 ቀን 2015 ዓ.ም. ወደ ጽርሐ መንበረ ፓትርያርክ መጥተው በቀድሞ በዓታቸው ተወስነው እስካሁን የቆዩ ሲሆን 20ዎቹ ተሿሟዎች ደግሞ በስምምነቱ መሠረት ለውሳኔው ተገዥ መሆናቸውን በመግለጽ መጋቢት 15 ቀን 2015 ዓ.ም. እያንዳንዳቸው በጽሑፍ ለቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ባቀረቡት መሠረት ውግዘቱ እንዴት ሊፈታ እንደሚገባ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት ጉባኤ የውሳኔ ሐሳብ እንዲያቀርብ በታዘዘው መሠረት የቤተ ክርስቲያኒቱን የቀኖና ቅዱሳት መጻሕፍት ዋቢ በማድረግ የውሳኔ ሐሳቡን ያቀረበ ሲሆን እንደሚከተለው በአጭሩ ተገልጿል፡፡ ሀ. “ኢይክል ሰብእ ነሢአ ፀጋ ለሊሁ ወኢምንተኒ እመ ኢተውህበ ሎቱ እምሰማይ” ሰው ከእግዚአብሔር ካልተሰጠው በስተቀር እርሱ ራሱ ጸጋን ገንዘብ ማድረግ አይችልም” (ዮሐ. 3፣27) በማለት በቅዱስ ወንጌል እንደተነገረው የእግዚአብሔር ጸጋ ከላይ የሚሰጠው በቅንነት፣ በትሕትና፣ በትዕግሥትና በጸሎት በመሳሰለው እንጅ በሥርዓት አልበኝነትና በሕገወጥ የድፍረት መንገድ የሚገኝ የእግዚአብሔር ጸጋ የለም፤ አልኖረም፤ አልነበረም፤ ወደፊትም አይኖርም፡፡ ለ. ብርሃና ለቤተ ክርስቲያን የተባለው ደጉ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም “ወአልቦ ዘይነሥእ ክብረ ለርእሱ ዘእንበለ ዘጸውዖ እግዚአብሔር በከመ አሮን” እንደ አሮን በእግዚአብሔር ከተጠራ በቀር ማንም ክብርን ለራሱ የሚወስድ የለም ሲል ክብረ ክህነትን በሚገባ ገልጿል፡፡ (ዕብ.5፡4) እንዲህም በመሆኑ በአሁኑ ሰዓት ከቅዱስ ሲኖዶሱ ውሳኔ ውጭና ቅዱስ ፓትርያርኩ በሌሉበት በድብቅ የተፈጸመው ሕገወጥ ሢመተ ክህነት ለሿሚውም ሆነ ለተሿሚው የእግዚአብሔርን ጸጋ በራስ ፈቃድ እንደመውሰድ ስለሚቆጠር ከፍተኛ የሆነ የዶግማ ጥሰት ተግባር ነው፡፡ ሐ. ከቅዱስ ቃሉ እንደተማርነው “ቀዳሚሃ ለጥበብ ፈሪሀ እግዚአብሔር - የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው” (መዝ.109፣10 ምሳ.1፣7) ይህንም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል መሠረት በማድረግ ስግዱ ለእግዚአብሔር በፍርሀት - ለእግዚአብሔር በፍርሀት ስገዱ (መዝ.28፣2)    ተቀነዩ ለእግዚአብሔር በፍርሀት - ለእግዚአብሔር በፍርሀት ተገዙ (መዝ.2፣11) ንትነሣእ በፍርሀተ እግዚአብሔር - እግዚአብሔርን በመፍራት እንነሣ (ቅዳ.ማ) በማለት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እስከ እስትንፋሰ ደኃሪት መልእክቷን ዘወትር ታስተላልፋለች፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት ይህ ሆኖ እያለ አሁን የተፈጸመው ድርጊት ግን በከፍተኛ ድፍረትና በሕገወጥ መንገድ ከመፈጸሙና የሥልጣነ ክህነትን ክብር ከማጉደፉም በላይ ከውግዘትም በኋላ ከጥፋቱ ባለመማር ሕገወጥነትን እንደ ሕጋዊነት፣ ጥፋትን እንደ ልማት፣ ሐሰትን እንደ እውነት፣ የነፍስ ጥፋትን እንደ ነፍስ ማዳን ተቆጥሮ በልበሙሉነት የአህጉረ ስብከትና የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት በር በኃይል ተሰብሮ የመውረር ሕገወጥ ተግባር ተፈጽሟል፡፡ ይህም ድርጊት ከውግዘት በኋላ በመሆኑ ሕገ እግዚአብሔርን እያወቁ ወደጎን በመተው የተፈጸመ ድርጊት በመሆኑ የዶግማ ጥሰት ነው፡፡

ታላቁ ቴዎዶስዮስም በነገሠ ጊዜ ስለ መቅዶንዮስ ስለ ሰባልዮስና ስለ አቡሊናርዮስ በቊስጥንጥንያ መቶ ሃምሳ ኤጲስቆጶሳትን በአንድነት ሰበሰበ። ይህም አባት በጉባኤው ውስጥ አንዱ እርሱ ነበር መናፍቃንም መመለስን እንቢ በአሉ ጊዜ ከወገኖቹ ጋር ረገማቸው አውግዞም ለያቸው። ሃይማኖትን ያቀኑ ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ በሠሩት በጸሎተ ሃይማኖት ላይ ለመንግሥቱም ፍጻሜ የለውም ከሚለው ቀጥሎ እንዲህ የሚል ጨመረ። "የባሕርይ ገዢ በሚሆን በሚያድን በመንፈስ ቅዱስ እናምናለን። ከአብ የተገኘ ከአብ ከወልድ ጋር እንስገድለት እናመሰግነውም በነቢያት አድሮ የተናገረ። ሐዋርያት ሰብስበው አንድ በአደረጓት ከሁሉ በላይ በምትሆን ክብርት ንጽሕት ጽንዕት ልዩ በምትሆን በአንዲት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን።ኃጢአት በሚሠረይባት በአንዲት ጥምቀት እናምናለን። የሙታንንም መነሣት ተስፋ እናደርጋለን የሚመጣውንም የዘላለም ሕይውት።" ከዚህም በኋላ ይህ አባት በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ። ሁለተኛም ስለ ጸሎተ ሃይማኖትና ስለ ትርጓሜው ሌላ በውስጡ ዐሥራ ስምንት ያህል ድርሳን ያለው መጽሐፍ ደረሰ። እርሱም ጥበብን እውቀትን ሁሉ የተመላ እጅግ የሚጠቅም ነው። በጵጵስናውም መንበር ሠላሳ ሦስት ዓመት ከኖረ በኋላ በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መጋቢት_22 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ ሁለት በዚችም ቀን የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ወደ ኢየሩሳሌም በአህያ ግልገል ተቀምጦ የገባበት #ሆሣዕና እያሉ ያመሰገኑበት ነው፣ የከበረ አባት ኤጲስቆጶስ #ቅዱስ_ቄርሎስ ዘኢየሩሳሌም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #በዓለ_ሆሳዕና መጋቢት ሃያ ሁለት በዚችም ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ ገብቶ ቤተ መቅደሱን በአህያ ግልገል ተቀምጦ በመዞር ሆሣዕና እያሉ እንዲአመሰግኑት አድርጓል። ይህም ስለርሱ እየአንዳንዳቸው በዘመናቸው ነቢያት የተናገሩት ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ነው። ያዕቆብም በክርስቶስ ስለ ተመሰለው ስለ ልጁ ይሁዳ አህያውን በዘይት ዕንጨት ላይ ያሥራል ውርንጫውንም በወይን አረግ አለ። ዘካርያስም የጽዮን ልጅ አትፍሪ እነሆ ንጉሥሽ በአህያ ግልገል ተቀምጦ ይመጣል አለ። ኢሳይያስም ንጉሥሽ ጻድቅ የዋህ የሆነ ይመጣል ዋጋውም ከእርሱ ጋራ ነው ሥራውም በፊቱ የተገለጠ ነው በአህያ ግልገልም ላይ ይቀመጣል አለ። አብርሃምም የሰሌን ዝንጣፊ ይዞ መሠውያውን በዞረ ጊዜ ይቺን ዕለት ተድላ ደስታ የሚደረግባት የእግዚአብሔር በዓል ብሎ ጠራት። ዳዊትም ከሕፃናትና ከልጆች አንደበት ምስጋናን አዘጋጀህ አለ። ሰሎሞንም የሕፃናት አንደበታቸው የተቃናች ሆነች አለ ሁለተኛም ልጆችና ሽማግሌዎች በኢየሩሳሌም ይጫወታሉ ምርጕዛቸውም በእጃቻቸው ውስጥ ነው አለ። ደግሞ መትከያዎችሽን አስፍተሽ ድንኳኖችሽን ዘርጊ ያለም አለ። ይህንንም የትንቢት ነገር ለመፈጸም በከበረ ወንጌል እንደተጻፈ ጌታ በአህያዋና በውርንጭላዋ ላይ ተቀምጦ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ። ወደ ኢየሩሳሌም ሊገባ በቀረበ ጊዜ የደብረ ዘይት አጠገብ ከምትሆን ቤተ ፋጌ ደረሰ ደብረ ዘይት ወደሚባል ቢታንያም በደረሰ ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱ ሁለቱን ላከ። ወደ ፊታችሁ ወዳለ አገር ሒዱ። በገባችሁም ጊዜ ሰው ያልተቀመጠበት ያህያ ግልገል ታገኛላችሁ ፈትታችሁ አምጡልኝ። ለምን ትፈቱታላችሁ የሚል ሰው ቢኖር ጌታው ይሻዋል በሉ። የተላኩትም በሔዱ ጊዜ እንደነገራቸው አገኙ። የአህያውንም ግልገል ፈቱ ጌቶቹም ለምን ትፈቱታላችሁ አሏቸው። ጌታው ይሻዋል አሉ። ወደ ጌታ ኢየሱስም ይዘውት ሔዱ ልብሳቸውንም በአህያው ግልገል ላይ ጐዘጐዙ ጌታንም አስቀመጡት። ቅጠል ቆርጠው በመንገድ ላይ የጐዘጐዙ ብዙዎች ናቸው። ልብሳቸውንም በመንገድ ላይ ያነጠፉ አሉ። በፊትም በኋላ ይሔዱ የነበሩት በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ መድኃኒት ነው ብለው አሰምተው ተናገሩ። በእግዚአብሔር ስን የምትመጣ የአባታችን የዳዊት መንግሥትም የተባረከች ናት። ጌታ ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ገባ ሕዝቡም ሁሉ አዩት በመሸም ጊዜ ከዐሥራ ሁለቱ አርድእት ጋር ወደ ቢታንያ ወጣ። በነጋውም ከቢታንያ በወጣ ጊዜ ተራበ። በሩቅም ቅጠል ያላትን በለስ አየ። በርሷ ፍሬ ያገኝ እንደሆነ ሊያይ ሔደ ወደርሷም በደረሰ ጊዜ ከቅጠል ብቻ በቀር ያገኘው የለም የበለስ ወራቱ አልነበረምና። ለዘላለም ካንቺ ፍሬ የሚበላ አይኑር አላት ደቀ መዛሙርቱም ሰሙ። ወደ ኢየሩሳሌም ደርሶ ወደ ቤተ መቅደስ ገባ በምኲራቡም ግቢ የሚገበያዩትን ያስወጣ ጀመረ የለዋጮችንም ሰደቃቸውን ገለበጠ ርግብ የሚሸጡትንም ወንበራቸውን ። ወደ ምኲራብ ለንግድ ገንዘብ ይዘው እንዳይገቡ ከለከለ። ቤቴ ለአሕዛብ ሁሉ የጸሎት ቤት ይሁን የሚል ጽሑፍ ያለ አይደለምን እናንተ ግን የሌቦችና የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት ብሎ አስተማራቸው። ዮሐንስም እንዲህ አለ አልዓዛርን ከሙታን ለይቶ ካስነሳው በኋላ። በነጋውም እሑድ ለበዓል የመጡ ሰዎች ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ኢየሩሳሌም እንዲመጣ በሰሙ ጊዜ። የሰሌን ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው ከኢየሩሳሌም ፈጥነው ወጡ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ከአርያም የተገኘ መድኃኒት የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው እያሉ እየጮኹ ተቀበሉት። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም የአህያ ግልገል አገኘ። ተቀመጠበትም እንደ ተጻፈ እንዲህ ሲል። የጽዮን ልጅ አትፍሪ እነሆ ንጉሥሽ በአህያ ግልግል ተቀምጦ ይመጣል። አስቀድሞ ግን ደቀ መዛሙርቱ ይህን ነገር አላወቁም ነበር ጌታ ሳይሰቀል ። ጌታ በተሰቀለ ጊዜ ይህ የተጻፈ ስለ እርሱ እንደሆነ ያን ጊዜ አወቁት እንጂ እንዲህም አደረጉለት። አልዓዛር አልዓዛር ብሎ ከሙታን ለይቶ እንዳስነሣው ባስነሣው ጊዜ ከእርሱ ጋር የነበሩ ሰዎች መሰከሩለት። ስለዚህም ሕዝቡ አመኑበት። ያደረገውን ተአምራት ሰምተዋልና የሕፃናቱንም ምስጋና ደግሞ አልዓዛርን ማስነሣቱን። የካህናቱ አለቆችና ፈሪሳውያን ግን እርስ በርሳቸው የምታገኙት ረብሕ ጥቅም እንደሌለ አታውቁምን እነሆ ሰው ሁሉ አመነበት አሉ። ማቴዎስና ማርቆስ የሰሌንን ነገር አላወሱም ሌሎች ከእጨንቶች ቅጠሎችን እየቆረጠ በመንገድ ውስጥ ጐዘጐዙ አሉ እንጂ። ሉቃስም ቅጠልን ወይም ሰሌንን አላወሳም ሲሔዱ ልብሳቸውን በመንገድ ላይ ይጐዘጒዙ ነበር አለ እንጂ። ዮሐንስ ግን ለብቻው ከኢየሩሳሌም ከሰሌን ዛፍ ላይ ዘንባባ ቆርጠው ያዙ አለ። ሰሌንም በኢየሩሳሌም አልነበረም ጌታችን ሕፃን ሁኖ ሳለ ወደ ግብጽ በወረደ ጊዜ ከእናቱ ቡርክት ቅድስት ከሆነች ከእመቤታችን ድንግል ማርያም ጋር እስሙናይን ከሚባል አገር ደረሱ ከዚያም ሰሌን አገኙ። ጌታችንም ከሥርዋ ተነቅላ ሒዳ በደብረ ዘይት ላይ እንድትተከል አዘዛት ያንጊዜ ወደ አየር ወጥታ በረረች ሒዳም በዚያ በደብረ ዘይት ተተከለች ከእርስዋም ወስደው የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ተቀበሉት። ጌታችንም የሆሣዕናን ዑደት በአሳየ ጊዜ የአይሁድ ወገን ቅናት ይዟቸው በሚገድሉት ገንዘብ ምክንያት ፈለጉ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ቄርሎስ_ዘኢየሩሳሌም በዚችም ዕለት የከበረው መንፈሳዊ አባት የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ አባ ቄርሎስ አረፈ። ይህም አባት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመማር ያደገና እጅግ አዋቂ ምሁር ሆነ። ከእርሱ በፊት የነበረ ኤጲስቆጶስ አባ በርኪሶስ በአረፈ ጊዜ ይህን አባት መርጠው ለኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ አድርገው ሾሙት። በተሾመም ጊዜ ከመናንያንና ከአርዮሳውያን ተኵላዎች በመልካም አጠባበቅ ሕዝቡን ጠበቀ። የኤጲስቆጶሳት ጉባኤ በሰርድቄ በተሰበሰበ ጊዜ ይህ አባት ከዚያ ደርሶ አርዮሳውያንን ተከራከራቸው ምላሽ አሳጥቶም አውግዞ አሳደዳቸው አካክዮስንም ከቂሣርያ ሀገረ ስብከቱ መንበር አሳደደው። አካክዮስም ወደ ታናሹ አርዮሳዊ ወደ ሆነው ቆስጠንጢኖስ ሒዶ ከማኀበሩ ስለ ደረሰበት ውግዘትና ስደት ይልቁንም ከዚህ አባት ቄርሎስ የደረሰበትን ሁሉ በመናገር ከሰሰው። ስለዚህም አርዮሳዊ ንጉሥ ይህን አባት ከኢየሩሳሌም አሳደደው ሌሎችንም ብዙዎች ኤጲስቆጶሳትን ከሀገረ ስብከት መንበራቸው አሳደዳቸው። ይህም አባት ቄርሎስ ወደ ተርሴስ ከተማ ሒዶ ከአገሩ ኤጲስቆጶስ ከስልዋኖስ ጋራ ተገናኘ። እርሱም ተራዳው ጥቂት ቀኖችም ከእርሱ ዘንድ አስቀመጠው። በሉክያኖስ ስብሰባ በሆነ ጊዜም ይህ አባት ከተሰበሰቡት ውስጥ አንዱ እርሱ ነው አካክዮስንም ደግመው አወገዙት ረገሙትም፡፡ ዳግመኛ ወደ ንጉሥ ሒዶ በዚህ በቅዱስ ቄርሎስ ነገር ሠራበት ንጉሡም ወታደሮች ልኮ ከዚያም ካለበተረ አሳደደው። ከዚህም በኋላ ይህ መናፍቅ ቈስጠንጢኖስ ሞተ። ልጁ ሦስተኛው ቈስጠንጢኖስ ነገሠ ይህንንም አባት ከተሰደደበት ወደ መንበረ ጵጵስናው መለሰው አባቱ ያሳደዳቸውን ኤጲስቆጶሳት ሁሉንም መለሳቸው። ይህም አባት የተረፈውን ዘመን በሰላምና በጸጥታ ኖረ።

🔴#ስንክሳር መጋቢት_21 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ አንድ በዚችም ዕለት የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ከሙታን ለይቶ ወደ አስንሳው ወደ #አልዓዛር ቤት ከደቀ መዛሙርቱ ጋራ የሔደበት ነው፣ ተአምረኛው አባት #አባ_ሊባኖስ_ዘመጣዕ ዓለምን ፍጹም በመናቅ የመነኑበት ነው፣ የማቱሳላ ልጅ #ጻድቁ_ላሜህ መታሰቢያው ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ቤተሰብ (አልዓዛር፣ ማርያና ማርታ) መጋቢት ሃያ አንድ በዚችም ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ለይቶ ወደ አስንሳው ወደ አልዓዛር ቤት ከደቀ መዛሙርቱ ጋራ ሔደ በዚያም ምሳ አዘጋጂለት ማርታም ምግብ በማቅረብ ታገለግላቸው ነበር። ሁለተኛዋ ማርያም ግን እግሮቹን ሽቱ እየቀባች በጸጕሩዋ ታሸው ነበር። ጌታችንም አመሰገናት እርሷ ከመቀበሪያዬ ጠብቃዋለች በማለት ስለ ቅርብ ሞቱ አመለከተ። ዳግመኛም ድኆች ሁል ጊዜ ከእናንተ ጋር ይኖራሉ እኔ ግን ከእናንተ ጋራ አልኖርም አለ በዚህም ተሰቅሎ የሚሞትበት ጊዜ ቅርብ መሆኑን ያመለክታል፡፡ ዳግመኛም በዚችም ቀን አልዓዛርን ሊገሉት የካህናት አለቆች ተማከሩ ገናና ስለሆነች ምልክት በእርሱ ምክንያት ብዙዎች በጌታችን የሚያምኑ ሁነዋልና። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ሊባኖስ_ዘመጣዕ በዚችም ዕለት ከዐለት ላይ ውኃ እያፈለቁ ድውያንን የሚፈውሱት ተአምረኛውና አባት አባ ሊባኖስ ዘመጣዕ ዓለምን ፍጹም በመናቅ መንነዋል፡፡ እርሳቸውም የአባታችን የተክለ ሃይማኖት ገዳም ‹‹ደብረ ሊባኖስ›› በስማቸው የተሰየመላቸው ናቸው፡፡ አባ ሊባኖስ አባታቸው አብርሃም እናታቸው ንግሥት ይባላሉ፡፡ እነርሱም በወርቅና በብር እጅግ የበለጸጉ ሮማዊ ናቸው፡፡ ልጃቸውን አባ ሊባኖስን በሃይማኖት በምግባር ኮትኩተው ካሳደጓቸው በኋላ ዕድሜያቸው ሲደርስ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ያጋቧቸው ዘንድ ከቁስጥንጥንያ አገር ሚስት ባመጡለት ጊዜ እርሱ ግን ፈጽሞ እምቢ አለ፡፡ ወደጫጉላቤትም መግባትን እምቢ አለ፡፡ በዚህም ጊዜ ነቢዩ ሳሙኤልን እንደጠራው አባታችንንም እግዚአብሔር ሦስት ጊዜ በስማቸው ጠራቸውና ‹‹ከአባትህ ተለይ አንተ የመንግሥተ ሰማያት ሙሽራ ነህ እንጂ የዚህ ምድራዊ ዓለም ሙሽራ አይደለህም›› አላቸው፡፡ አባታችንም ‹‹ወዴት እሄዳለሁ? ምንስ ላድርግ?›› ባሉ ጊዜ ወዲያው የታዘዘ መልአክ በሌሊት መጥቶ ከአባታቸው ቤት አውጥቶ ታላቁ አባት አባ ጳኩሚስ ዘንድ አደረሳቸው፡፡ ታላቁ አባት አባ ጳኩሚስም ለአባ ሊባኖስ በዓት በመስጠት ገዳመ ሥርዓትን፣ አስኬማ መላእክትን፣ ቅናተ ዮሐንስን አስተምረዋቸው አመነኮሷቸውና ከ8ቱ ቅዱሳን ጋር እንዲገናኙ አደረጓቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ያ ከአባታቸው ቤት ወስዶ አባ ጳኩሚስ ገዳም ያደረሳቸው ያ መልአክ ድጋሚ ተገለጠላቸውና ‹‹ወደ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ ሂድና ተጋድለህን በዚያ ፈጽም ዝናህ በስፋት ይነገራል፣ ለብዙዎችም አባት ትሆናቸዋለህ›› አላቸው፡፡ ቀጥሎም ራሱ መልአኩ ወደ ኢትዮጵያ አመጣቸውና በአክሱም ተቀመጡ፡፡ በዚያም ብዙ ከተጋደሉ በኋላ ወደ ሸዋ መጡና ወንጌልን ዞረው አስተምረው ብዙ ድውያንን ፈውሰው ከዓመታት ቆይታ በኋላ ተመልሰው አክሱም ሄዱ፡፡ በአክሱምም 7 የተለያዩ ጸበሎችን ከድንጋይ ላይ በተአምራት አፍልቀው ድውያንን ፈውሰው ዕውራንን አበሩ፡፡ በዓታቸውንም ከአክሱም ጽዮን ፊት ለፊት አድርገው ሲኖሩ ከዕለታት በአንደኛው ቀን አባታችን በተአምራት ከጭንጫ ካፈለቁት ጸበል ‹‹ተራ ውሃ ነው›› ብላ አንዲት ሴት ልጇን አዝላ ልትቀዳ መጣች፡፡ ወዲውም ከቦታው ስትደርስ አድጧት ወደቀችና ልጇም አምልጥጧት ልቡን ድንጋይ መቶት ሞተ፡፡ ሴትዮዋም ስትጮህ አባ ሊባኖስ ፈጥነው ወጡና በልጁ ላይ ጸልየው በመስቀል ምልክት አማትበው ከሞት አስነሥተውታል፡፡ ሕፃኑ ልጅ ከሞት እንደተነሣ ‹‹አምላከ አባ ሊባኖስ›› ብሎ አመሰገነ፡፡ ይህንንም ደግ ሥራቸውንና ተአምራታቸውን ያዩ አንዳንድ እኩይ ካህናት በቅናት ተመልተው ‹‹ምትሃት ነው የሚያሳየው›› ብለው በጻድቁ ላይ ሕዝቡን አሳደሙባቸው፡፡ አባታችንም ካህናቱን ለመምከር ቢሞክሩም አላስቀምጥ አሏቸው፡፡ ይልቁንም ጦር ጦራቸውን ይዘው አሳደዷቸው፡፡ አባታችንም በዚህ እጅግ አዝነው ከአክሱም ተነሥተው ደርቃ ወደምትባል ቦታ ሄዱ፡፡ በዚያም በጾም በጸሎት እየተጋደሉ ሲኖሩ በእነዚያ በጠሏቸውና በክፋት በተነሡባቸው ካህናት አገር ግን ለ3 ዓመት ምንም ዝናብ ሳይዘንብ ቀረ፡፡ አባታችን በተሰደዱባት በደርቃ አገር ግን ብዙ ዝናብ ይዘንብ ነበር፡፡ አባታችን በዚያችም አገር እንደልማዳቸው ከዐለት ላይ ውኃ አፍልቀው በውኃው ብዙ ድውያንን ፈውሰውበታል፡፡ በዚያም ትልቅ በዓት መሥርተው በተጋድሎ ሲኖሩ በክፉ የተነሡባቸው እኩይ የሆኑ ካህናት መጥተው ‹‹አባታችን በከንቱ አምተንሃል በድለንሃልና ይቅር በለን፣ በድርቅ ማለቃችን ነውና ዝናብም እንዲዘንብልን ጸልይን›› ብለው ከእግራቸው ሥር ወደቁ፡፡ አባታችንም ይቅር ብለው ከፈጣሪ አማለዷቸው፡፡ ዝናቡም ወዲያው ዘነበላቸውና በአገሪቱ ጥጋብ ሆነ፡፡ ከዚህም በኋላ አባታችን አስቀድመው ወዳዩአት ወደ ሸዋ ምድር ግራርያ መጡና በዓታቸውን በአሰቦት ጫካ አደረጉ፡፡ ነገር ግን መልአኩ ተገልጦላቸው ‹‹ሊባኖስ ሆይ! ከዚህ ቦታ የአንተ መኖሪያ አይደለም፣ በዚህ ቦታ ላይ እግዚአብሔርንና ሰውን የሚያገናኝ የሚያስታርቅ ታላቅ ጻድቅ ይወጣበታልና ይህ ቦታ የእርሱ ርስት ነው፣ የብዙ መነኮሳትም መንደር ይሆናል ነገር ግን የቦታው ስም በአንተ ስም ይጠራልሃል›› አላቸው፡፡ በኋላ አባታችን ተክለ ሃይማኖት ተወልደው በዓታቸውን በዚያ ቦታ ላይ ሲያጸኑ ቦታው ግን ‹‹ደብረ ሊባኖስ›› ተብሎ በመጀመሪያው አባት ስም ተሰየመ፡፡ መልአኩም በሌሊት እየመራ ወደ አክሱም ወሰዳቸው፡፡ ከዚያም ‹‹ታሪክ ወደምትሠራበት ዕጣ ክፍልህ ወደሆነው ቦታ አደርስሃለሁ›› አላቸውና ወደ ኤርትራ አካለ ጉዛይ አውራጃ ልዩ ስሙ መጣዕ ወደተባለው ቦታ ወሰዳቸው፡፡ በዚያም አባታችን ድውያንን እየፈወሱ፣ ለምፃሞችን እያዳኑ፣ ሙታንን እያስነሡ ብዙ ተአምራትን እያደረጉ ወንጌልን እየሰበኩ ‹‹ሊባኖስ ዘመጣዕ›› የሚባለውን ትልቁን ገዳማቸውን መሠረቱ፡፡ በወቅቱ የነበረው ዐፄ ገብረ መስቀልም የመጀመሪያውን ቤተ ክርስቲያን አሠራላቸው፡፡ ቅዱስ ላሊበላ 23 ዓመት ሙሉ ካነጻቸው እጅግ ድንቅ 11 ቤተ መቅደሶች ውስጥ አንደኛውን በአባ ሊባኖስ ስም ሰይሞላቸዋል፡፡ ዐፄ ገብረ መስቀል ያሠራላቸው ሌላኛው ገዳማቸው ትግራይ ተንቤን ውስጥ ይገኛል፡፡ እጅግ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን በማድረግ የሚታወቁት አባታችን እንደ ተስዓቱ ቅዱሳን ከሮም በመምጣት በሀገራችን ላይ ብርሃንን አብርተዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ጻድቁ_ላሜህ በዚችም ዕለት የማቱሳላ ልጅ የላሜህ መታሰቢያው ነው። እርሱም አንድ መቶ ሰማንያ ሁለት ዓመት ኑሮ ኖኀን ወለደው ከወለደውም በኋላ አምስት መቶ ስልሳ አምስት አመት ኖረ። በድምር ሰባት መቶ አርባ ሰባት ዓመት ኖረ። እግዚአብሔርንም አገልግሎት በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

ዐሥራ አምስት ዓመት በሆናት ጊዜ እናትና አባቷ ምን ያከሣሻል አሏት እርሷም እኔስ ኃጢአቴን ይቅር ይለኝ ዘንድ የክብር ባለቤት ወደሆነ ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እጸልያለሁ አለቻቸው። አባቷም በሰማ ጊዜ ወደ ጢባርዮስ ሒዶ የልጁን ሥራ ነገረው እርሱም ወታደሮች ልኮ ወደ ርሱ አስመጣት። ለጣዖትም እንድትሰግድ መኰንኑ አባበላት እምቢ በአለችም ጊዜ ወደ ወህኒ ቤት አስገቧት እናቷም ክርስቲያናዊት ናት እየመጣች በክብር ባለቤት በክርስቶስ እምነት ታበረታታት ነበር። ከዚህ በኋላ የብረት የሆነ የሰሌዳ ክርታስ ይሠሩላት ዘንድ በእሳትም አግለው ክንዶቿ ከወገቦቿ ጋራ አንድ እስቲሆኑ እንዲአጣብቋት አዘዘ ይህንንም በአደረጉባት ጊዜ ያንን የብረት ክርታስ ሰብራ በደኅና ወጣች ሕዝቡም ይህን አይተው በክብር ባለቤት በክርስቶስ አራት ሺህ ሰባት መቶ ያህል አምነው በሰማዕትነት ሞቱ የሰማዕታትንም አክሊል ተቀበሉ። ሁለተኛም ደግመው ከእሥር ቤት አስገቧት ጥፍሮች ያሉት የብረት በሬ ሠሩላት ሆዷን ያስወጓት ዘንድ ሊሰቅሏትም ወደርሷ አቀረቡት ይህንንም በአደረጉባት ጊዜ በጌታ ኃይል በሬው ወዲያና ወዲህ ተከፈለ ሕዝቡም ይህን በአዩ ጊዜ በክብር ባለቤት በጌታችን ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አምስት ያህል ሰው አምነው በሰማዕትነት አረፉ። ከዚህም በኋላ መርዝን ከተመሉ እባቦች ጉድጓድ ውስጥ ጨመሩዋት በጸለየችም ጊዜ እንደ ትቢያ ሆኑ። ሁለተኛም አራት ሰዎች የሚሸከሙትን ከባድ ደንጊያ አምጥተው በአንገቷ ላይ ሰቀሉ በጸለየችም ጊዜ ደንጊያው ወደ ሦስት ተከፈለ። ብዙዎች አረማውያንም በክርስቶስ አምነው በሰማዕትነት አረፉ። ለቅድስቲቱ ግን የብረት ምንቸት አዘጋጁላት በውስጡ የፈላ እርሳስ በላይዋ ያፈሱባት ዘንድ በነኩት ጊዜ በላያቸው ተሰብሮ የሚያሠቃዩአትን ገደላቸው። ንጉሡም አይቶ ተቆጣ ራሷንም በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ምስክርነቷን ከምትፈጸምበት ቦታም በደረሰች ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጸለየች አስጠራጢኒቃ ሆይ አንቺ ብፅዕት ነሽ ስምሽ በሕይወት መጽሐፍ ተጽፏልና የሚል ቃል መጣላት ከዚያም በኋላ በሰይፍ ተቆረጠች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መጋቢት_20 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ በዚህችም ዕለት የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ #ጻድቅ_አልዓዛር ከሞተ በኋላ በአራተኛው ቀን ከሙታን ለይቶ ላስነሳበት መታሰቢያ ነው፣ የእስክንድርያ  ሃምሳ ሰባተኛ ሊቃነ ጳጳሳት የሆነ #ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_ሚካኤል አረፈ፣የተመሰገነችና የከበረች ተጋዳይም የሆነች #ቅድስት_አስጠራጦኒቃ ስለ ክርስቶስ ምስክር ሁና ሞተች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አልዓዛር_ጻድቅ_ሐዋርያ መጋቢት ሃያ በዚህችም ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጻድቅ ሰው አልዓዛርን ከሞተ በኋላ በአራተኛው ቀን ከሙታን ለይቶ አስነስቶት ነበርና ስለዚች ምልክት ገናናነት ብዙዎች አመኑበት። ይህም ጻድቅ ሰው ከእስራኤል ልጆች ውስጥ ነው ማርያና ማርታ የተባሉ ሁለት እኅቶች አሉት። ማርያም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሸቱ የቀባችው ናት። እነርሱም ለጌታ ደቀመዛሙርቶቹ ናቸው ስለ ምግባራቸውም ጌታችን ይወዳቸዋል ሁሉም ያላገቡ ድናግል ናቸው። በሰው ወገን ሁሉ ላይ የተቆረጠና የተወሰነው ሰዎችም ሊጠጡት ያላቸው የሞት ጻዋን የሚጠጣበትና እጁን ለሞት የሚሰጥበት ለዚህ ጻድቅ ጊዜው ሲደርስ እርሱም እጁን በመስጠት አረፈ። የክብር ባለቤት ጌታችን ግን የሚሠራውን ያውቃልና መጀመርያ ከሞት አላዳነውም ጠርቶ እስከሚአሥነሣው ድረስ ሙቶ በመቃብር አራት ቀን እንዲኖር በዚህ በአራት ቀንም የጻድቃንን ማደሪያዎችንና የኃጥአንን የሥቃይ ቦታዎች እንዲያይ ተወው እንጂ አላዳነውም ያን ጊዜም ታላቅ ምልክት ትሆናለች። ከአራት ቀኖችም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እርሱ መጥቶ አልዓዛር አልዓዛር ና ውጣ ብሎ ከመቃብር ውስጥ ጠራው ያን ጊዜ አጆቹና እግሮቹ እንደታሠሩ ሙታኖችንም እንደሚጠቀልሏቸው በሰበን ፊቱ ተጠቅልሎ ወጣ። እጆቹና እግሮቹ እንደ ተጠቀለሉና እንደ ታሠሩ ከመቃብር የመውጣቱ ምክንያት ሰዎች ሁሉ መሞቱን እንዲረዱ ሌሎችም ይህ በመካከላቸው በስምምነት የሆነ ነው ብለው እንዳያሰቡ። ስለዚህም እንደ ገነዙት ሁኖ እንዲወጣ ጌታችን አዘዘው ይችም ምልክት እንድትሆን። ከሀዲዎችም በመቃብር ውስጥ ሕያው እንደ ነበር ቢያስቡም እጆቹና እግሮቹ ፊቱም እንደ ተጠቀለሉ እንዴት ይወጣ ነበር እኛ የክርስቲያን ወገኖች ግን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአራት ቀኖች በኋላ አልዓዛርን ያስነሣው እርሱ እንደሆነ እናምናለን። እንታመናለንም እርሱ በሥራው ሁሉ ላይ ችሎታ አለውና። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ሚካኤል_ሊቀ_ዻዻሳት በዚህች ቀን በእስክንድርያ ከተሾሙ አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃምሳ ሰባተኛ የሆነ የከበረ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤል አረፈ። ይህም አባት በሹመቱ ወራት ብዙ ኀዘንና መከራ ደረሰበት ጎሕ በሚባል አገር የተሾመ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ክብር የሚወድ አንድ ክፉ ኤጲስቆጶስ ነበረ። በሀገረ ስብከቱም ውስጥ ደነውስር በሚባል አገር ያሉ ምእመናን የቤተ ክርስቲያናቸውን ሕንፃዋን አደሱ ሊአከብሩዋትም በፈለጉ ጊዜ የአገር ታላላቆች ከእርሳቸው ሊባረኩ ወደው ሊቀ ጳጳሳቱና በአገሩ ዙሪያ ያሉትን ኤጲስቆጶሳት ልኮ እንዲአስመጣቸው ይህን ክፉ ኤጲስቆጶስ ለመኑት እርሱ ግን እምቢ አላቸው ልመናቸውን መቀበል አልወደደም። እነርሱም በራሳቸው ፈቃድ ይህ ክፉ ኤጲስቆጶስ ሳይፈቅድ ሊቀ ጳጳሳቱንና ኤጲስቆጶሳቱን ሁሉ ልከው አስመጡአቸው። ሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤልና ኤጲስቆጶሳቱ ሁሉ በመጡ ጊዜ ምሳ አዘጋጅላቸዋለሁ ብሎ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ትቶአቸው ሔደ። ማርታ ማርታ ብዙ በማዘጋጀት ብዙ ትደክሚያለሽ ግን ጥቂቱ ይበቃል ያለውን የጌታችንን ቃል አላሰበም። የቍርባን ጊዜ ሊያልፍ ስለሆነ ሊቃውንቱና ኤጲስቆጶሳቱ የቅዳሴውን ሥርዓት ይጀምር ዘንድ ሊቀ ጳጳሳቱን ለመኑት ግድ ባሉትም ጊዜ በሊቀ ጵጵስና ማዕረግና ክብር ተሠይሞ ተነሣ እርሱ ለሁሉ አባት የሆነ ሥልጣኑም ከሥልጣናቸው በላይ ነውና የቅዳሴውንም ሥርዓት ጀመረ። ያ ክፉ ኤጲስቆጶስም በሰማ ጊዜ በልቡ ሰይጣን አደረበትና ተቆጥቶ መጣ። መሥዋዕቱንም ከመቅደስ ገብቶ ከጻሕሉ ውስጥ ነጥቆ ወደ ምድር ወረወረው ሊቀ ጳጳሳቱም ሌላ መሥዋዕት አምጡ ብሎ አዘዘ አምጥተውለትም ቀድሶ ለሕዝቡ ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸውና አሰናበታቸውም። በማግሥቱም ይህ አባት አባ ሚካኤል ሕዝቡን ሰበሰበ ከእርሱ ጋራ ያሉትንም ኤጲስቆጶሳት ካህናቱንና የምእመናንን አንድነት ሰብስቦ ይህን ክፉ ኤጲስቆጶስ ከሹመቱ ሽረው በእርሱ ፈንታ ሌላ ኤጲስቆጶስ ሾሙ። ይህም ለአስቆሮቱ ሰው ለይሁዳ ሁለተኛው የሆነ የምስርን አገር ወደ ሚገዛ ስሙ አሕመድ ወልደ በጥሎን ወደተባለው ሹም ሔደ ይህን አባት አባ ሚካኤልን እንዲህ ሲል ነገር ሠራበት። በሊቀ ጳጳሳቱ ዘንድ ብዙ የወርቅና የብር ገንዘብ እንዳለ እንዲሁም አብያተ ክርስቲያናት የወርቅና የብር ንዋየ ቅድሳትን የተመሉ እንደሆኑ መኰንን ሆይ ዕወቅ አለው። መኰንኑም ይህን አባት ወደርሱ አስቀርቦ ንዋየ ቅድሳቱን እንዲሰጠው ፈለገ እርሱም ሥጋዬን እንደፈለግህ አድርግ ነፍሴ ግን በእግዚአብሔር እጅ ናት በሎ ከለከለው። እጆቹንና እግሮቹን አሥረው በእሥር ቤት እንዲጥሉት አዘዘ በእሥር ቤትም ከአንድ ዓመት በላይ ኖረ በእሥር ቤት ውስጥ በኖረበት መጠን ከለምለም እንጀራና ከጨው ከበሰለ አተር በቀር ሳይበላ ሁል ጊዜ ይጾም ነበር። ከዚህም በኋላ አንድ ጸሐፊ ምእመን ዮሐንስ የሚባል መጥቶ ለዚህ ለከበረ አባት አባ ሚካኤል ዋስ ሆነው ለመኰንኑ አባ ሚካኤል ሃያ ሽህ የወርቅ ዲናር እንዲሰጠው ሁኖ ከወህኒ ወጥቶ ወደ ቤቱ ሔደ ጥቂት ቀን ተቀመጠ ታላላቆች ምእመናንና የአስቄጥስ ገዳም መነኰሳት ዐሥር ሽህ የወርቅ ዲናር ሰበሰቡ ደግሞ የእስክንድርያ አገር ሰዎች ከምድራቸው አንዱን ለዐሥር ሽህ ዲናር ሸጡ ሃያ ሽህ እስከሚሞላ ሰበሰቡ። ሊቀ ጳጳሳቱም ለመኰንኑ ይህን ሃያ ሽህ የወርቅ ዲናር ሰጠው መኰንኑም ዐሥር ዐሥር ሽህ የወርቅ ዲናር እንደ ግብር ሁኖ በየዓመቱ እንዲከፈል ጽፎ አስፈረመው። ጊዜውም ሲቀርብ ይህ አባት አባ ሚካኤል ከምእመናን ሊለምን ተነሥቶ ወጣ በልበይስ ወደተባለም አገር ደርሶ አንዲት ቀን ዋለ ወደርሱም አንድ ምስኪን ድኃ መነኰሴ ገባ። ከሊቀ ጳጳሳቱም ቡራኬ ተቀብሎ ተመልሶ በበር አጠገብ ከረድኡ ጐን ቆሞ አትዘን በልብህም አትተክዝ ከዛሬዪቱ ዕለት እስከ አርባ ቀኖች ትድናለህ በላይህ ያለውን የዕዳ ደብዳቤ ትቀበላለህና ለመኰንኑ ምንም አትሰጠውም ብለህ ለአባት ሊቀ ጳጳሳት ንገረው አለው ያ ረድኡም እንዳለው ነገረው ድኃውን መነኲሴ ፈለጉት ግን አላገኙትም። አርባ ቀኖችም ሳይፈጸሙ ያ መኰንን በክፉ አሟሟት ሞተ በእርሱ ፈንታም ልጁ ተሾመ ለዚህም አባት ያንን የዕዳ ደብዳቤ መለሰለት ይህም አባት ድኃው መነኰስ ትንቢት እንደ ተናገረ ደብዳቤውን ተቀብሎ ቀደደው ከዕዳም ዳነ። ይህም አባት በታላቅ መከራና በኀዘን በሹመቱ ዘመን ሃያ ዘጠኝ ዓመት ከኖረ በኋላ በፍቅር በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስትና_ሰማዕት_አስጠራጦኒቃ በዚህችም ዕለት የተመሰገነችና የከበረች ተጋዳይም የሆነች አስጠራጦኒቃ ስለ ክርስቶስ ምስክር ሁና ሞተች። የዚች ቅድስት አባቷ ጣዖት አምላኪ ነው እርሷ ግን በክብር ባለቤት በክርስቶስ የምታምን ናት ሥጋዋም እስቲከሣና እስቲደርቅ መልኳም እስቲለወጥ ድረስ በሥውር ትጾማለች ትጸልያለችም።

🔴#ስንክሳር መጋቢት_19 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ዐሥራ ዘጠኝ በዚች እለት #ሐዋርያ_አርስጥቦሎስ ሐዋርያ አረፈ፣ #ቅዱስ_አስከናፍርና የሚስቱ ማርታ የልጆቹ አርቃድዮስና ዮሐንስ የዕረፍታቸው መታሰቢያ ሆነ፣ #የሰባቱ_ሰማዕታት መታሰቢያቸው ሆነ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አርስጦቦሎስ_ሐዋርያ መጋቢት ዐሥራ ዘጠኝ በዚች እለት የሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ደቀ መዝሙር አርስጥቦሎስ ሐዋርያ አረፈ። እርሱም ጌታችን ከመረጣቸውና ከመከራው በፊት እንዲሰብኩ ከላካቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የተቆጠረ ነው። በሃምሳኛው ቀን በዓልም መንፈስ ቅዱስ በላዮ በወረደ ጊዜ ከሐዋርያት ጋራ ጸጋንና ኃይልን ተመልቶ ሕይወት በሚገኝበት በወንጌል ትምህርት ሐዋርያትን ተከትሎ በመሔድ አገለገላቸው። ብዙዎችንም ወደ ድኀነት መንገድ መልሶ የክብር ባለቤት ወደ ሆነ ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት አስገባቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጥምቆ የአምላክን ሕግና ትእዛዝ ከማስጠበቁ የተነሣ ነፍሳቸውን አዳነ። አባቶቻችን ሐዋርያትም ይህን ቅዱስ አብራጣብያስ በሚባል አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት። ወደርሷም ሒዶ በውስጥዋ ወንጌልን ሰበከ ብዙዎቹንም በቀናች ሃይማኖት እግዚአብሔርን ወደ ማወቅ መለሳቸው። በፊታቸውም ድንቆች ተአምራትን በማድረግ በሃይማኖት አጸናቸው ነገር ግን ከአይሁድና ከዮናናውያን ብዙ መከራ ደረሰበት። ብዙ ጊዜም ወደ ፈረጆች አደባባይ ወስደው በደንጊያ ወገሩት ጌታችንም ከመከራው ሁሉ ጠብቆ አዳ ነው መልካም ተጋድሎውንም በፈጸመ ጊዜ በሰላም በፍቅር አረፈ። እነሆ ለሮሜ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ ሐዋርያ ጳውሎስ አስታውሶታል። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አስከናፍር በዚህችም ቀን ደግሞ ቅዱስ አስከናፍርና የሚስቱ ማርታ የልጆቹ አርቃድዮስና ዮሐንስ የዕረፍታቸው መታሰቢያ ሆነ። ይህም አስከናፍር ብዙ ገንዘብ ያለው ባለጠጋ ነው ለእግዚአብሔርም ሕግ የሚጠነቀቅ ነበር ልጆቹንም መንፈሳዊ ምክርና ተግሣጽ በማስተማር አሳደጋቸው። በአደጉም ጊዜ የጥበብንና የተግሣጽን ትምህርት እንዲማሩ ተይሩት ወደምትባል አገር ሰደዳቸውና ትምህርታቸውን በፈጸሙ ጊዜ ሊድራቸውና በሰርጋቸው ደስ ሊለው ሽቶ ያመጡአቸው ዘንድ ላከ በመርከብም ሁነው ሲመጡ ማዕበል ተነሥቶ መርከቡ ተሰበረ። እግዚአብሔርም ከስጥመት አድኖ በየብስ አወጣቸው ዮሐንስ የተባለውን በአንድ ቦታ ማዕበሉ አውጥቶ ጣለው። ዮሐንስም ተስፋ በቆረጠ ጊዜ ወደ ቅዱሳን ገዳም ሒዶ መነኰሰ። ስለ ወንድሙ ስለአርቃድዮስም እንደሞተ ተጠራጥሮ በጸም በጸሎትና በስግደትም ሥጋውን አደከመ። አርቃድዮስም ወደ ዮርዳኖስ ገዳም ገብቶ ከአንድ ቅዱስ አረጋዊ ሰው ዘንድ መንኲሶ እየተጋደለ ሦስት ዓመት ኖረ። አስከናፍር ግን ልጆቹ በማዕበል እንደሰጠሙ በሰማ ጊዜ ከሚስቱ ጋራ ማቅ ለብሰው አመድ አንጥፈው እያለቀሱ ተቀመጡ። በአንዲት ሌሊትም አስከናፍር በሕልሙ ልጁ ዮሐንስን በራሱ ላይ ከዕንቊ የተሠራ አክሊል ተቀዳጅቶ መስቀል ይዞ አየው። አርቃድዮስንም በኮከብ አምሳል የሆነ አክሊል በራሱ ላይ ደፍቶ አየ ከእንቅልፉም ነቅቶ ለሚስቱ ያየውን ነገራት። ከዚያም በኋላ በየአድባራቱና በየገዳማቱ የልጆቻችንን ወሬ እንመረምር ዘንድ ተነሺ እንሒድ አላትና ወደ ዮርዳኖስ ሒደው ከመጥምቁ ዮሐንስ ገዳም ደረሱ። ልጃቸውን አርቃዴዎስን ያመነኰሰውን አረጋዊ አባትን አገኙት ችግራቸውን ነገሩት እርሱም የክርስቶስ ወዳጆች አትዘኑ ወደ ቤተ መቅደስ ስትመለሱ ልጆቻችሁን በሕይወት ታገኛላችሁ አላቸው ደስ እያላቸውም ተመለሱ። ዮሐንስም በመስቀል በዓል ሊሳለም መጣ አረጋዊውም ጠርቶ ከአርቃድዮስ ከወንድሙ አገናኘው ተያይዘውም አለቀሱ። ደግሞ አስከናፍርን ከሚስቱ ጋራ ጠርቶ ከልጆቻቸው ጋራ አገናኛቸውና በላያቸው ወድቀው እየሳሟቸው አለቀሱ። ከዚህ በኋላ ከዚያ አረጋዊ ዘንድ የምንኲስና ልብስ ለበሱ ሚስቱን ማርታንም ከሴቶች ገዳም አስገባት አገልጋዮችንም ነፃ አውጥቶ አሰናበተ። ገንዘቡንም ለድኆችና ለችግረኞች በተነ ከገዳምም ገብቶ በጾም በጸሎት ተወሰነ እንዲሁም የተባረኩ ልጆቹ በገደል በትሩፋት የተጠመዱ ሁነው ኖሩ ጌታችንንም ደስ አሰኙት በፍቅር አንድነትም አረፉ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሰባቱ_ቅዱሳን_ሰማዕታት በዚህችም ቀን ደግሞ የሰባቱ ሰማዕታት መታሰቢያቸው ሆነ፡፡ እንርሱም የግብጽ ሰው እለእስክንድሮስና እስክንድሮስ ከጋዛ መንደር አጋብዮስ ከቡንጥስ ከተማ ኒሞላስ ከጠራልብስ ዲዮናስዮስ ሮሜሎስና ተላስዮስ ከግብጽ አውራጃዎች የሆኑ ናቸው። እነርሱም በመንፈሳዊ ፍቅር ጸንተው ስለ ሃይማኖት ምስክሮች ሊሆኑ ተስማሙ። በፍልስጥዔም ውስጥ ወደ አለው ቂሣርያ ደርሰው በመኰንኑ ፍት ቆሙ። በከሀዲው ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማመናቸውን ገለጡ መኰንኑም በጽኑዕ ሥቃይ አሠቃይቶ ገደላቸው። የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

ንስሀ ሳይገባ አይሞትም፣ ልጅ መውለድ ባይችል እኔ ልጅ እሰጠዋለሁ፤ ገድልህን በቤትህ ያስቀመጠ እርኩስ መንፈስ፣ ክፉ አጋንንት ቸነፈር ወባ መልአከ ጽልመት አይነካውም፡፡ በገዳምህ መነኩሴ ቢቀበር በሰማይ ክንፍ አበቅልለታለሁ፤ አይሁድም አረማዊም ያላመነ ያልተጠመቀ በገዳምህ መጥቶ ቢያርፍ ይቅር እልልሃለሁ፣ እንደ መቃብሬ ጎልጎታ እንደተቀበረ አድርጌ እቆጥርልሃለሁ›› የሚል ቃል ኪዳን ከሰጣቸው በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ቅዱስ አባታችንም በ500 ዓመታቸው ሐምሌ 29 ቀን ዐርፈው በጎንድ ተክለ ሃይማኖት ተቀብረዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር የሚገኘውን ይህንን ገዳም ጻድቁ ራሳቸው ናቸው የመሠረቱት፡፡ ነገር ግን የገዳሙን ስያሜ በአባታቸው በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ስም አድርገውታል፡፡ አቡነ ዮሐንስ ካረፉ በኋላ በእርግማናቸው መሠረት በመንዝና በይፋት ብርዱ ድርቁ ስለበዛባቸው አንድ ብቁ ባሕታዊ ከበዓታቸው ወጥተው ‹‹በሐሜታችሁ ምክንያት እጨ ዮሐንስ ስለረገማችሁ ነው የእርሱን ዐፅም ካላመጣችሁ ብርዱ ውርጩ ድርቁም አይጠፋላችሁም›› አሏቸው፡፡ ሕዝቡም አባታችን በጉንድ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከተቀበሩ ከ134 ዓመት በኃላ በቅዱሳን እየተመሩ ሄደው በሌሊት ግማሽ ዐፅማቸውን አምጥተው በሀገራቸው አምጥተው ስላስቀመጡ ብርዱና ውርጩ በመንዝ እየቀነሰላቸው መጥቷል፡፡ ዛሬም በሀገሩ ብርዱና ውርጭ ሲበዛ የጻድቁን ታቦት ሲያወጡ ውርጩ ይጠፋል፡፡ ጠገሮ በሚባለው ገዳማቸው ውስጥ የሚገኘው ጠበላቸው እጅግ አስደናቂ ነው፡፡ ግማሽ ዐፅማቸውን ከጉንደ ተክለሃይማኖት አምጥተው አርባ ሐራ መድኃኔዓለም አጠገብ በላይ በፍሩክታ ኪዳነምሕረት መጋቢት 18 ፍልሰተ ዐፅማቸው ተከናወነ፡፡ ምድሪቷም ተባረከች፣ የዘሩትንም አበቀለች፣ ውርጩም ብርዱም ቀነሰ፣ ዝናብ አልዘንብ ሲል ወይም ሰብል የሚጨርስ አንበጣ ሲመጣ ታቦታቸው ወጥቶ ምህላ ይያዛል ወድያውም መቅሰፍት ይርቃል፣ ዝናብም ይዘንባል፡፡ ጻድቁ ደመናን፣ ጨረቃንና ፀሐይን በእጃቸው እየያዙ ይጸልዩ ነበር፡፡ በጠገሮ፣ በአዘሎ፣ በፍርኩታና በሌሎቹም ታላላቅ ቦታቦዎች ላይ በእያንዳንዱ ገዳም ሃምሳ ሃምሳ ዓመት በጸሎት ኖረው በአጠቃላይ በ500 ዓመታቸው ነው ያረፉት፡፡ ዐፅማቸው መንዝ ከአርባ ሐራ መድኃኔዓለም አጠገብ ፍርኩታ ኪዳነ ምሕረት ገዳም ውስጥ ይገኛል፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን ።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መጋቢት_18 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ዐሥራ ስምንት በዚች ቀን #ቅዱስ_ኤስድሮስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የጻድቁ አባታችን #አቡነ_እጨጌ_ዮሐንስ_ዘጠገሮ ፍልሰተ ዐፅማቸው ተከናወነ፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ኤስድሮስ_ሰማዕት መጋቢት ዐሥራ ስምንት በዚች ቀን የሰማዕት ቅዱስ ፃና ጓደኛው የከበረ ኤስድሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ፃና ግን ፈርማ በሚባል አገር ለአገረ ገዥው ከጦር ሠራዊቱ ውስጥ ወታደር ነበር እርሱም ከደቅስያ ሰዎች ወገን ነው ከበግ ጸጕር ልብሶችን ለሚሠራ ለኤስድሮስ ወዳጁ ነው። ሁለቱም ሠርተው ከሚያገኙት ለድሆችና ለችግረኞች ይመጸውታሉ። በአንዱት ሌሊትም ከእርሷ ጋር አክሊሎች ያሉ ድንግል ሴት በራሳቸው ላይ ስታኖረው ሁለቱም ራእይን አዩ። ከእንቅልፋቸውም በነቁ ጊዜ ያዩትን እንዴት እንዳዩ ተነጋገሩ። ምስክሮቹ ሊሆኑ የጠራቸው እግዚአብሔር እንደሆነ አውቀው እጅግ ደስ አላቸው። ከዚያም ተነሥተው ሒደው ወደ መኰንኑ ደረሱ ቅዱስ ፃናም ትጥቁን ፈትቶ በመኰንኑ ፊት ጣለው ሁለቱም በጌታችን በክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ማመናቸውን ገለጡ። መኰንኑም ነገራቸውን ሰምቶ አሥረው ይደበድቧቸው ዘንድ አዘዘ እግዚአብሔርም መልአኩን ልኮ አዳናቸው። ከዚህም በኋላ መኰንኑ ወደእስክንድርያ ቅዱስ ፃናን ላከው ቅዱስ ኤስድሮስን ግን በዚያው ተወው ከጥቂት ቀኖችም በኋላ የእስክንድርያው መኰንን ቅዱስ ፃናን ወደ ፊርማ ከተማ መለሰው። ሁለቱ ቅዱሳንም ተገናኙ በመገናኘታቸውም ደስ ብሎአቸው በላያቸው በየአንዳንዳቸው የደረሰውን መከራ ተነጋገሩ። ዳግመኛን በቅዱስ ኤስድሮስ ዐዘቅትን ይቆፍሩለት ዘንድ በዐዘቅቱም ውስጥ እሳትን አንድደው ቅዱስ ኤስድሮስን እንዲጨምሩት መኰንኑ አዘዘ። ቅዱሱም ጥቂት እስቲጸልይ ይታገሡት ዘንድ ወታደሮቹን ለመናቸው ወደ ጌታችንም ነፍሱን ይቀበል ዘንድ ለሥጋውም ያስብ ዘንድ ጸለየ። ከዚያም ወደ እሳቱ ጕድጓድ ቀረበ ወደ እሳቱም ውስጥ ጨመሩት ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ በሥጋውም ላይ ምንም ጕዳት አልደረሰም መልኩም አልተለወጠም። የቅዱስ ፃና እናትም ከሚወደው ጓደኛው ስለመለየቱ ታለቅስለት ነበር በዚያም ሥጋውን ተሸክመው ወሰዱ የስደቱም ወራት እስቲፈጸም በመልካም ቦታ አኖሩት። ቅዱስ ኤስድሮስም ምስክር ሁኖ በሞተ ጊዜ የቅዱስ ፃና እናት ብዙ መላእክት የቅዱስ ኤስድሮስን ነፍስ ይዘው በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ሲያሳርጓት አየች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አቡነ_እጨጌ_ዮሐንስ_ዘጠገሮ (ፍልሰተ ዐፅማቸው) ዳግመኛም በዚህች ቀን የጻድቁ አባታችን አቡነ እጨጌ ዮሐንስ ዘጠገሮ ፍልሰተ ዐፅማቸው ተከናወነ፡፡ ጻድቁ አባታችን የተወለዱት በኢየሩሳሌም አውራጃ ልዩ ስሙ ሳሬራ በሚባል ቦታ ነው፡፡ የካቲት 28 ቀን ተፀንሰው ህዳር 29 ተወለዱ፡፡ አባታቸው ድላሶር እናታቸው እምነ ጽዮን ይባላሉ፡፡ ሲወለዱ በወላጆቻቸው ቤት ውስጥ ብርሃን ወርዷል፡፡ ወላጆቻቸውም እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ አባታችን ገና በተወለዱ በ5 ዓመታቸው ወላጆቻቸው ወደ እግዚአብሔር ቤት ይዘዋቸው የእመቤታችንን ሥዕል ተመልክተው በደስታ ተመልተው ሳቁ፡፡ አምላክን የወለደች የብርሃን እናቱ እመቤታችንም ከምሥሉ ወጥታ ‹‹በምን አውቀኸኝ ነው?›› ብላ አቅፋ ሳመችውና ‹‹ከእንግዲ ወዲህ የልጄ አገልጋይ ትሆናለህ ኑሮህም እንደ መላእክት ይሆናል በአንተ ምክንያት ብዙ ሰዎች ይድናሉ በምድር ላይም  500 ትኖራለህ›› ብላ ባርካው ተሰወረች፡፡ ከዚያችም ቀን ጀምሮ አባ ዮሐንስ ለክርስቶስ ተላልፎ ተሰጠ፡፡ 50 ዓመትም በበረሃ ሲጋደል ኖሮ ከ50 ዓመት በኃላ በደመና ተጭኖ በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል መሪነት ወደ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ መጡ፡፡ ጻድቁ አባታችን በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘመን መጨረሻ የመጡ ሲሆን ምንኩስና ከደብረ ሊባኖስ ገዳም ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ተቀብለው በዚያው በድብረ ሊባኖስ ገዳም ለ50 ዓመት በጾምና በጸሎት በተጋድሎ ኖዋል፡፡ ከዚኽም በኋላ አባ ዩሐንስ ወደ ተዘጋቸላቸው ምድር በቅዱስ ገብርኤል አሳሳቢነት ወደ ጠገሮ መጡ፡፡ ይኽም ጠገሮ ያለው ገዳማቸው በሰሜን ሸዋ በመንዝና ይፋት ክልል መዘዞ በሚባል ቦታ ሲደርሱ በእግር አንድ ሰዓት ከተጓዙ በኃላ ይገኛል፡፡ ሕዝቡ በተለምዶ እጨ ዮሐንስ እያለ ይጠራቸዋል እንጂ ስማቸው እጨጌ ዮሐንስ ነው፡፡ አቡነ እጨጌ ዮሐንስ መስቀል ከሰማይ የወረደላቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ መስቀሉም ሁልጊዜ ተአምር ይሠራል፡፡ በልደታቸው ቀን ኅዳር 29 ቀን መስቀሉ ከመቅደሱ ወጥቶ በካህናቱ ታጅቦ ወደ ጸበሉ ሲወርድ ከየት እንደመጣ ሳይታሰብ ደመና መጥቶ ከመስቀሉ ላይ ብቻ እረቦና እንደ ጃንጥላ ተዘርግቶ አብሮ ወደ ጸበሉ ይወርዳል፡፡ እዛው ቆይቶ መስቀሉ ሲመለስም አብሮ አጅቦ ይመለስና መስቀሉ ቤተ መቅደስ ውስጥ ሲገባ ደመናው ወዴት እንደተበተነ ሳይታወቅ ይጠፋል። ይህ በዘመናችንም ጭምር እየታየ ያለ ታላቅ ተአምር ነው፡፡ አባታችን በታላቀ ተጋድሎ ሣሉ ሰይጣን የሀገሩን ሰዎች በጠላትነት እንዲነሡባቸው አደረገ፡፡ ሰዎቹም አባታችንን እንዴት እንደሚያጠፏቸው ይማከሩ ጀመር፡፡ ሊገድሏቸው ፈልገው ቅድስናቸው በሁሉ ዘንድ የታወቀ ነውና ፈሩ፡፡ ከዚኽም በኋላ ‹‹ለምን ከመንደራችን ከወንድ ያረገዘች ሴት ፈልገን እሳቸው አስረገዟት ብለን በሐሰት እንከሳቸው?›› ብለው ተማከሩ፡፡ ብዙ ወርቅና ብርም ለአንዲት ሴት ሰጥተው በሐሰት ከእርሱ አርግዣለሁ ብላ እንድትመሰክር አደረጓት፡፡ አባታችንም በሕዝብ ፊት በሐሰት ተከሰሱ፡፡ ጻድቁም ‹‹አንቺ ሴት ከእኔ ነው ያረገሽው?›› አሏት እርሷም ‹‹አዎ ከአንተ ነው ልትክድ ነው እንዴ?›› አለቻቸው፡፡ አባታችንም በዚህ አዝነው ‹‹በአንቺና በእኔ መካከል እግዚአብሔር ይፍረድ›› ሲሉ ያች ሴት ወዲያው ለሁለት ተሰንጥቃ ሞተች፡፡ የአገሩ ሰዎችም እጅግ ፈሩ፡፡ አባታችንም ምድሪቱን እረገሟት፡፡ ‹‹የተዘራው ዘር አይብቀልብሽ፣ የተተከለው አይፅደቅ፣ ብርድና ውርጭ ይፈራረቅብሽ›› ብለው እረግመዋት በደመና ተጭነው ወደ ሰሜን ጎንደር እስቴ ጉንደ ተክለተሃማኖት ሔዱ፡፡ አቡነ ዮሐንስ በመላው ኢትዮጵያ ወንጌልን እየተዘዋወሩ ያስተማሩ ሲሆን ከቅድስናቸው የተነሣ በፀሐይ ላይ 50 ዓመት፣ በጨረቃ ላይ 50 ዓመት፣ በደመና ላይ 50 እንዲሁም ዓለምን በክንፋቸው በመዞር በደመና ላይ 50 የኖሩ ከሰው ተወልደው ከመላእክት የተደመሩ ታላቅ ጻድቅ ናቸው፡፡ በይፋት ጠገሮ በዓለ ወልድ፣ በአፋር አዘሎ፣ በመንዝ ፍርኩታ ኪዳነምሕረት፣ በደብረ ሊባኖስ፣ በጉንደ ተክለ ሃይማኖት በሌሎችም ቦታዎች በመዘዋወር በታላቅ ተጋድሎ ኖረዋል፡፡ አባታችን ከሰማይ መስቀል የወረደላቸው ሲሆን ዛሬም በገዳማቸው የሔደ ሰው በወረደው በእጃቸው መስቀል እየተዳበሰ ቆመው በጸለዩበት ባሕር በጠበላቸው ይጠመቃል፡፡ በተጨማሪም ይይዙት በነበረውም መቋሚያቸው በመዳበር በረከትን ማግኘት ይቻላል፡፡ ቆመው ከጸለዩበት ባሕር ውስጥ ደረቅ አሸዋ ይወጣል፡፡ አባ ዮሐንስ 500 ዓመት ከኖሩ በኋላ እረፍተ ዘመናቸው ሲደርስ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከ15 ነቢያት፣ ከ12 ሐዋሪያት፣ ሄሮድስ ያስፈጃቸው ከመቶ አርባ አራት ሺ ሕፃናት፣ ከአብርሃም ከይስሐቅ፣ ከያዕቆብ ጋር ሁሉንም ነገደ መላእክትን፣ ጻድቃን ሰማዕታትን ሁሉ አስከትሎ መጥቶ ታላቅ ቃልኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ‹‹ስምህን የጠራ ገዳምህን የረገጠ፣ መባ የሰጠ፣ ቤተ ክርስትያንህን የሠራ ያሠራ የረዳ፣ ገድልህን የሰማ ያሰማ ያስተረጎመ፣ መታሰቢያን ያደረገ እስከ 10 ትውልድ እምርልሀለው፤

በቅርቡ በተቋቋመው በኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ አስተዳደር ውስጥ በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፤ በአገልጋዮቿ እና በምእመናን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ግፍ እና በደል አስመልክቶ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የተሰጠ መግለጫ ። ++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++ ክርስትና ወደ ኢትዮጵያ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ  የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ከሰሜን እስከ ደቡብ፣ ከምዕራብ እስከ ምስራቅ በተለያየ ዘመን በተነሱ ቅዱሳን ክርስትና እንዲሰበክ በማድረግ ለሺህ ዓመታት የሀገሪቱ የሃይማኖት፣ የታሪክ እና የሞራል ምንጭ ሆና ኖራለች፡፡ ቤተ ክርስቲያን ራሷ የሆነው ክርስቶስን በመስበክ ያላመኑትን ከማሳመን፣ ያመኑትን ከማፅናት እና የፀኑትን ከመቀደስ ውጪ ሌላ ምድራዊ ዓላማ ሳይኖራት ነገስታቱንም ሆነ ምዕመኑን እኩል ንስሀ አባት መድባ አና ንስሀ አቀብላ፣ ቀድሳ አቁርባ እና ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩም ለሁሉም እኩል ፍትሃት አድርጋ የምትሸኝ ሰውን በፆታው፣ በቋንቋው፣ በነገዱ እና በማንነቱ አድሎ ሳታደርግ የኖረች ናት። ሆኖም ግን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ በሀገራችን ውስጥ ያለአንዳች ማስረጃ የተፈጠሩ የሀሰት ትርክቶች እና እነዚህን ትርክቶች መሠረት ተደርገው በሰፊው ሲነዙ የነበሩ ሀሰተኛ መረጃዎች ቤተ ክርስቲያንን ዋጋ እያስከፈላት ይገኛል፡፡ አሁን አሁን የቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች እና ምእመናን በሃይማኖታቸው ብቻ ተለይተው በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ባሉ አካላት ካህናት አባቶቻችን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስ ስጋና ደሙን ቀድሰውና አክብረው ለሰዎች ድህነት ይሆኑ ዘንድ በተሰጣቸው ስልጣነ ክህነት ምእመናን ለርስት መንግሥተ ሰማያት የሚያበቁ ሁነው ሳለ በተለያዩ ጊዜ ለሞት እና ለእንግልት እንዲሁም ለስደት እና ለእስራት ሲዳረጉ ማዬት የእለት ተእለት ተግባር ከሆነ ሰንበትበት ብሏል፡፡ በአዲሱ መንግስታዊ መዋቅራዊ አደረጃጀት በአዲስ አበባ ዙርያ በኦሮሚያ ክልላዊ መንግስት ሸገር ከተማ በሜጢ ሆርሲሳ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ካህን የነበሩት ቄስ አባይ መለሰ በመጋቢት ፲ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ከቅዳሴ ወጥተው ወደ መኖሪያ ቤታቸው ሲሄዱ ለጊዜው ማንነታቸው ባልታወቁ ግለሰቦች በተፈጸመባቸው ድብደባ ሕይወታቸው ሊያልፍ መቻሉን ተረድተናል፡፡ መንግሥት የዜጎችን በሰላም ወጥቶ የመግባት ደህንነት የማስጠበቅ እና ዋስትና የመስጠት እንዲሁም ጭካኔ እና አረመኔያዊ ከሆኑ ጥቃቶች የመጠበቅ መንግሥታዊ ኃላፊነት ሊኖርበት ይህንን ባለመወጣቱ ምክንያት የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች እና ዜጎች በሕይወት የመኖር መብት በየእለቱ እየተሸረሸረ ይገኛል፡፡ በመሆኑም ሀገረ ስብከታችን በቀሲስ አብይ መለስ ሞት የተሰማንን መሪር ኃዘን እየገለጽን የሚመለከተው የፌዴራል፤ የአዲስ አበባ ከተማ እና የኦሮሚያ ክልል ፖሊስ እና የፍትህ አካል ጉዳዩን ልዩ ትኩረት በመስጠት ተገቢውን ምርምራ በማድረግ ይህንን አስነዋሪ እና ጭካኔ የተሞላበትን የግድያ ወንጀል የፈጸሙ ወንጀለኞችን ለፍርድ እንዲያቀርብ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በንፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ስር የሚተዳደሩ ቁጥራቸው ከዐሥራ ሦስት በላይ የሆኑ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት በአዲሱ የከተማ ድንበር ማካለል ወደ ኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ ክልል ውስጥ የተካለሉ ቢሆኑም ለዓመታት ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ገንብተው መንፈሳዊ አገልግሎት ሲሰጡ ከቆዩ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ፩ የኤርቱ ሞጀ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ እና የቅዱስ ጊዮርጊስ አብያተ ክርስቲያናትን ለማፍረስ ተሞክሮ ከእነዚህ ውስጥ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ሙሉ በመሉ በአፍራሽ ግብረ ሀይል እንዲፈርስ ከመደረጉም በላይ የፈረሰውን ቤተ ክርስቲያን በውስጡ ከሚገኙ ንዋያተ ቅድሳት ጋር በሙሉ እንዲቃጠሉ እና እንዲወድሙ ተደርጓል፡፡ ፪. በኤርቱ ሞጆ ደብረ ሰላም መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያንን አጥሩን ማፍረስ ተጀምሮ ምእመናን እና የቤተ ክርስቲያኒቱ አባቶች ባደረጉት ርብርብ የማፍረስ : ሒደቱ ለጊዜው ቢቆምም አሁንም ይህን ቤተ ክርስቲያንም ሆነ በሸገር ከተማ ውስጥ ያሉ አብያተ ክርስቲያናት በከፍተኛ ስጋት ውስጥ እንደሚገኙ ለመረዳት ተችሏል፡፡ ስለሆነም ለሀገር ባለውለታ የሆነችን ቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በማሳደድ እና በማውደም ታሪካዊ መሠረቷን ለመናድ እና ከሌሎች ቤተ እምነቶች በመነጠል በቤተ ክርስቲያናችን ላይ እየተፈጸመ ያለው አድሏዊ እና ኢ-ሕገ መንግስታዊ የሆነው ድርጊት በአስቸኳይ እንዲቆም እንዲደረግ እያሳሰብን የፌዴራል እና የክልሉ መንግሥትም የድርጊቱን ፈጻሚ አካላት ላይ ተገቢውን እርምት እንዲወስድ ስንል እንጠይቃለን፤ በመጨረሻም የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እና የሚመለከተው ባለስልጣን አካል በየካቲት ፳፫ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም በገነተ ጽጌ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ የተፈጸመውን እና ሕገ ወጥ ተግባርን በተመለከተ የድርጊቱን ፈጻሚ አካላትን በ፭ ቀናት ጊዜ ውስጥ ተለይተው በሕግ ተጠያቂ በማድረግ ለሕዝብ እንዲያሳጡት ጥሪ ያስተላለፈች ቢሆንም ይህ መግለጫ  አስከሚሰጥ ድረስ ለድርጊቱ ተጠያቂ የሆኑ አካላት ተለይተው ተጠያቂ አለመሆናቸው ቤተ ክርስቲያናችንን በእጅጉ ያሳዘነ ተግባር ነው፡፡ በመሆኑም መንግሥት ቤተ ክርስቲያን ያቀረበችውን ጥያቄ ምላሽ ሊሰጥ ያልቻለ በመሆኑ የድርጊቱን መነሻ ምክንያት የደረሰውን ጉዳት እና የድርጊቱን ፈጻሚዎች ለይቶ ለሕዝብ ይፋ የሚያደርግ የሕግ ባለሙያዎች ኮሚቴ በማዋቀር ወደሥራ የተገባ መሆኑን እያሳወቅን ኮሚቴው የደረሰበትን ጥቅል መረጃ በአጭር ቀናት ጊዜ ውስጥ ለሕዝብ ሪፖርቱን የሚያቀርብ እና የድርጊቱ ፈጻሚዎች ቤተ ክርስቲያንን በይፋ ይቅርታ እንዲጠይቁ እና አጥፊዎችም ለድርጊታቸው ተገቢውን ሕጋዊ ቅጣት እንዲያገኙ እየሠራን መሆኑን እናሳውቃለን። በመሆኑም፡ ፩. መንግሥት የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ በመሆናቸው ምክንያት በአሰቃቂ ሁኔታ በመንገድ ላይ ተደብድበው ሕይወታቸው እንዲያልፍ የተደረጉት የቄስ ዐብይ መለሰ ገዳዮችን ተከታትሎ ለፍርድ እንዲያቀርብ እና ችግሩን ከሥር ከመሠረቱ በመፍታት የአገልጋዮችንና የምእመናን መብት እንዲያስከብር ፪. በሸገር ከተማ አስተዳደር እየተፈፀመ ያለው አብያተ ክርስቲያናትን የማፍረስ ድርጊት በአስቸኴይ እንዲቆም እንዲደረግ፣ ፫. የፈረሱትን አብያተ ክርስቲያናት ቦታ ተመላሽ እንዲያደርግ እና የፈረሰውን ቤተ ክርስቲያንም በራሱ ወጪ እንዲያሠራ እንዲደረግ እንጠይቃለን። የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናን እና ምእመናት እንዲሁም የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ አባቶች ዘመነ ቤተ ክርስቲያንን በጉልበታችን፤ በዕውቀታችን እና በገንዘባችን የምናገለግልበት ብቻ ሳይሆን በአካላችን፣ በጤናችን እና በሕይወታችንም መስዋዕትነትን የምንከፍልበት የሰማዕትነት ዘመን ነው፡፡ ይህ የሰማዕትነት መከራም በሀገራችንና በየቤታችን እየመጣ ያለ የመከራ ዘመን በመሆኑ አብዝቶ ወደ እግዚአብሔር በመጸለይ፤ ሥጋችንን በጾም እና በስግደት በመግራት ከአባቶቻችሁ አባታዊ መመሪያ በመቀበል በሃይማኖታችሁ ጸንታችሁ እንድትቆሙ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡ እግዚአብሔር ሀገራችንን እና ህዝቦቿን ይባርክ መጋቢት ፲፯ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ምንጭ :- Eotc