fa
Feedback
Ethiopian Human Rights Commission (EHRC) – ኢሰመኮ

Ethiopian Human Rights Commission (EHRC) – ኢሰመኮ

رفتن به کانال در Telegram

EHRC is an independent NHRI tasked with the promotion and protection of human rights in Ethiopia.

نمایش بیشتر
1 505
مشترکین
+524 ساعت
+67 روز
+5730 روز
آرشیو پست ها
የሕፃናት ከጉልበት ብዝበዛ የመጠበቅ መብት ... የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት፣ አንቀጽ 36(1) (መ) ማንኛውም ሕፃን ጉልበቱን ከሚበዘብዙ ልማዶች የመጠበቅ፤ በትምህርቱ፣ በጤናውና በደኅንነቱ ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ሥራዎችን እንዲሠራ ያለመገደድ ወይም ከመሥራት የመጠበቅ መብት አለው። ዓለም አቀፉ የሕፃናት መብቶች ስምምነት፣ አንቀጽ 32(2)(ሀ-ሐ) ተዋዋይ ሀገራት በተለይ፡- - ዝቅተኛ የቅጥር ዕድሜን ወይም ዕድሜዎችን ይወስናሉ፤ - የሥራ ሰዓትንና የቅጥር ሁኔታዎችን በተመለከተ ተገቢውን ደንብ ያወጣሉ፤ - ይህ አንቀጽ በሚገባ በሥራ ላይ መዋሉን ለማረጋገጥ ተገቢ ቅጣቶችን ወይም ሌሎች ክልከላዎችን ያስቀምጣሉ። https://ehrc.org/?p=38110 #Ethiopia #KeepWordSafe #ጤናማቃላት በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

የሳምንቱ #HRConcept: የሕፃናት ከጉልበት ብዝበዛ የመጠበቅ መብት ... የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት፣ አንቀጽ 36(1) (መ) ማንኛውም ሕፃን ጉልበቱን ከሚበዘብዙ ልማዶች የመጠበቅ፤ በትምህርቱ፣ በጤናውና በደኅንነቱ ላይ ጉዳት የሚያደርሱ ሥራዎችን እንዲሠራ ያለመገደድ ወይም ከመሥራት የመጠበቅ መብት አለው። ዓለም አቀፉ የሕፃናት መብቶች ስምምነት፣ አንቀጽ 32(2)(ሀ-ሐ) ተዋዋይ ሀገራት በተለይ፡- - ዝቅተኛ የቅጥር ዕድሜን ወይም ዕድሜዎችን ይወስናሉ፤ - የሥራ ሰዓትንና የቅጥር ሁኔታዎችን በተመለከተ ተገቢውን ደንብ ያወጣሉ፤ - ይህ አንቀጽ በሚገባ በሥራ ላይ መዋሉን ለማረጋገጥ ተገቢ ቅጣቶችን ወይም ሌሎች ክልከላዎችን ያስቀምጣሉ። 🔗 https://ehrc.org/?p=38110 #Ethiopia #KeepWordSafe #ጤናማቃላት በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

የማኅበረ ሥነ-ልቦና ጉዳት ያለባቸው ሰዎች የጤና መብት ላይ የተካሄደ የምክክር መድረክ ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የማኅበረ ሥነ-ልቦና ጉዳት (psychosocial disability) ያለባቸው ሰዎች የጤና መብት ላይ ለመጀመሪያ ጊዜ ባደረገው የሰብአዊ መብቶች ክትትል በተለዩ ግኝቶች እና በቀረቡ ምክረ ሐሳቦች ዙሪያ ከባለድርሻ አካላት ጋር ግንቦት 12 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ የምክክር መድረክ አካሂዷል። ክትትሉ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ በአማራ፣ ኦሮሚያ እና ትግራይ ክልሎች ሥር በሚገኙ 13 የመንግሥት ሆስፒታሎች እና የግል የሕክምና ማእከላት ላይ የተካሄደ ሲሆን፤ ዋና ዓላማውም እንደ ከባድ ድብርት፣ ባይፖላር ዲስኦርደር፣ ስኪዞፌርንያ፣ የጭንቀት ሕመም ባሉ የረዥም ጊዜ የአእምሮ ጤና ጉዳቶች ምክንያት ለተግባር ውስንነቶች (functional limitations) እና ለማኅበራዊ እንቅፋቶች (social barriers) የተጋለጡ ሰዎችን የሕክምና አገልግሎት ሁኔታዎችን ለመለየት እንዲሁም የመፍትሔ ሐሳቦችን ለማመልከት ያለመ ነው። በምክክር መድረኩ ላይ ከሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ፣ ከትምህርት እና ከጤና ሚኒስቴር፤ ክትትሉ ከተካሄደባቸው ክልሎች የጤና፣ የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮዎች፣ ከአካል ጉዳተኞች ማኅበራት እና የጤና ተቋማት የተወከሉ የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች እንዲሁም ሌሎች ባለድርሻዎች ተሳትፈዋል። በመድረኩ ኢሰመኮ በክትትሉ በለያቸው ቁልፍ እመርታዎች፣ አሳሳቢ ጉዳዮች እና ምክረ ሐሳቦች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል። ተሳታፊዎች በማኅበረ ሥነ-ልቦና ጤና አገልግሎት ላይ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን፣ በተቋሞቻቸው እየተወሰዱ ያሉ እርምጃዎችን እና የሚገጥሟቸውን ተግዳሮቶች አቅርበዋል። በክትትሉ ከተለዩ አዎንታዊ ሁኔታዎች መካከል የአእምሮ ሕክምና ቀደም ካሉት ዓመታት በተለየ በአንድ ሆስፒታል ሳይወሰን በተለያዩ ሪፈራል እና የማስተማሪያ ሆስፒታሎች ውስጥ እየተሰጠ መሆኑ፣ ታካሚዎች የአእምሮ ሕክምናን በቅርበት እንዲያገኙ መደረጉ፣ ክትትል በተደረገባቸው ተቋማት የሚገኙ የሕክምና ባለሙያዎች ታካሚዎችን በመልካም ሥነ ምግባር እና አያያዝ የሚያስተናግዱ መሆኑ እንዲሁም በመንግሥት የሕክምና ተቋማት ከሱስ ሕክምና ውጪ ያሉ የአእምሮ ሕክምናዎች እና መድኃኒቶች በጤና መድኅን ሽፋን ለተጠቃሚው እንዲሰጡ መደረጉ ተጠቃሽ ናቸው። በሌላ በኩል ክትትሉ በተከናወነባቸው የመንግሥት የጤና ተቋማት ውስጥ ከፍተኛ የሆነ የመድኃኒት እጥረት መኖሩ፣ እንደ የኤሌክትሪክ ንዝረት ሕክምና (Electroconvulsive therapy) ያሉ አስፈላጊ የሕክምና ዘዴዎችና ቴክኖሎጂዎች በበቂ ያልተሟላ መሆኑ፣ በሀገሪቱ ለአእምሮ ሕክምና ተጠቃሚ ሕፃናት ተብሎ የተዘጋጀ የመድኃኒት መጠን (ዶዝ) እና የመድኃኒቶች እጥረት መኖሩ፣ በግጭት ዐውድ ውስጥ በሚገኙ ክልሎች የማኅበረ ሥነ-ልቦና ሕክምና ፈላጊ ታካሚዎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መጨመሩና አገልግሎት የሚሰጡ ባለሙያዎች ቁጥር ውስን መሆኑ እና በጤና ተቋማት የሚስተዋለው ከፍተኛ የበጀት ውስንነት አሳሳቢ ጉዳዮች መሆናቸው ተጠቅሷል። በምክክሩ ማጠቃለያ ላይ ተሳታፊዎች በኢሰመኮ የቀረቡ ምክረ ሐሳቦችን ለመፈጸም የሚያስችል የድርጊት መርኃ ግብር አዘጋጅተዋል። የኢሰመኮ የአካል ጉዳተኞች እና የአረጋውያን መብቶች ኮሚሽነር መሐመድ አሕመድ፣ ሰዎች ሕይወታቸውን በአግባቡ እንዲመሩ፣ እንዲማሩ፣ እንዲሠሩ እና ለማኅበረሰባቸው የበኩላቸውን አስተዋጽዖ እንዲያበረክቱ የአእምሮ ጤና መሠረታዊ መነሻ መሆኑን ጠቁመው፤ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ለአእምሮ ጤና ሕክምና አገልግሎት ተደራሽነት፣ ተገኝነትና ጥራት ትኩረት ሰጥተው እንዲሠሩ አሳስበዋል። https://ehrc.org/?p=38082 #Ethiopia #humanrightsforall በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

በሽግግር ፍትሕ ዙሪያ የተዘጋጀ የግንዛቤ ማሳደጊያ ዐውደ ጥናት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በሽግግር ፍትሕ ጽንሰ ሐሳቦች ላይ ያተኮረ የግንዛቤ ማሳደጊያ ዐውደ ጥናት ግንቦት 11 እና 12 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ አካሂዷል። በዐውደ ጥናቱ የኢትዮጵያ ብሔራዊ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ፣ የሽግግር ፍትሕ ፍኖተ ካርታ፣ የሽግግር ፍትሕ ሂደቱን ለመተግበር የተዘጋጁ ረቂቅ ሕጎች፣ በሽግግር ፍትሕ ሂደት ብሔራዊ የሰብአዊ መብቶች ተቋማት ስላላቸው ሚና እንዲሁም በዚህ ረገድ ኢሰመኮ እያከናወናቸው ስላሉ ተግባራት ገለጻዎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል። በውይይቱ ወቅት የሽግግር ፍትሕ ዋና ምሰሶዎች የሆኑት ተጠያቂነት፣ እውነትን ማፈላለግ፣ የተጎጂዎች ካሳ እና ተቋማዊ ማሻሻያዎች ለፍትሕ፣ ለእርቅ እና ለዘላቂ ሰላም ያላቸው አስተዋጽዖ ላይ ውይይት ተደርጓል። በተጨማሪም የሽግግር ፍትሕ ሂደቱ ውጤታማ እና ተዓማኒ እንዲሆን ግልጽ የትግበራ ሥርዓቶች፣ የተቋማት ቅንጅት እና ጠንካራ እና ገለልተኛ ተቋማት መኖራቸው ለሽግግር ፍትሕ ውጤታማነት ወሳኝ መሆናቸው፤ ረቂቅ ሕጎቹም ከዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች ሕጎችና መርሖች ጋር ተጣጥመው ሊዘጋጁ እንደሚገባ እንዲሁም ብሔራዊ የሰብአዊ መብቶች ተቋማት በሂደቱ ላይ የሚያከናውኑት የክትትል ሚና ሊጠናከር እንደሚገባ ተገልጿል። የውይይቱ ተሳታፊዎች ዐውደ ጥናቱ በኢትዮጵያ የሽግግር ፍትሕ ሂደት ላይ የተሻለ ግንዛቤ እንዲኖራቸው ማድረጉን ገልጸው ሂደቱን በውጤታማነት ለመደገፍ የሚያስችል ጠንካራ ተቋማዊ ዐቅምን ለመገንባት መሰል ተከታታይ የግንዛቤ ማሳደጊያ ስልጠናዎች አስፈላጊ መሆናቸው ተገልጿል። ኢሰመኮ የሠራተኞቹን ዐቅም ለማጎልበት መሰል የግንዛቤ ማሳደጊያ ስልጠናዎችን በቀጣይነት እንደሚያካሂድ እንዲሁም የኢትዮጵያ የሽግግር ፍትሕ ሂደት ውጤታማ፣ ተዓማኒ እና ሰብአዊ መብቶችን ማዕከል ያደረገ እንዲሆን ለማድርግ አበክሮ እንደሚሠራ አስታውቋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=38024 #Ethiopia #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

ጋዜጣዊ መግለጫ፡ ኦሮሚያ፦ በአርሲ ዞን አሰኮ ወረዳ የደረሰውን የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች በተመለከተ መንግሥት ተገቢውን ምርመራ በማካሄድ ተጠያቂነትን የማረጋገጥ እና ተጎጂዎችን ለመካስና ለማቋቋም የሚያስችሉ እርምጃዎችን ሊወስድ ይገባል . . . . . የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን አሰኮ ወረዳ ግንቦት 23 እና 24 ቀን 2018 ዓ.ም. የተፈጸመውን ጥቃት በተመለከተ ክትትል እና ምርመራ እያከናወነ ይገኛል፡፡ ኢሰመኮ ይህ መግለጫ ይፋ እስከተደረገበት ጊዜ ድረስ በአካባቢው በአካል በመገኘት ከዐይን እማኞች፣ ከተጎጂዎች፣ ከተጎጂ ቤተሰቦች፣ እና ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ባሰባሰባቸው መረጃዎችና ማስረጃዎች ራሱን የኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት ብሎ የሚጠራው “በተለምዶ ኦነግ ሸኔ” ታጣቂ ቡድን በፈጸመው ጥቃት የመንግሥት የጸጥታ ኃይል አባላትና ሲቪል ሰዎች መገደላቸውን፣ ነዋሪዎች መፈናቀላቸውን፣ የንብረት ውድመት እና ቃጠሎ መድረሱን ለማረጋገጥ ችሏል። ኢሰመኮ በምርመራ ሂደቱ እንዳረጋገጠው በአሰኮ ወረዳ ደለተ ጫፋ ቀበሌ አካባቢ ከግንቦት 22 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ የታጣቂዎች እንቅስቃሴ በመስተዋሉ የአካባቢው ሚሊሻዎችና የኦሮሚያ ጸረ ሽምቅ ውጊያ ፖሊስ አባላት በስፍራው በመሰማራታቸው “በተለምዶ ኦነግ ሸኔ” ተብሎ በሚጠራው ታጣቂ ቡድን እና በተሰማሩ የጸጥታ አካላት መካከል ግጭት ተፈጥሯል። ግጭቱን ተከትሎ የአካባቢው ነዋሪ የሆኑ ሰዎች ላይ ታጣቂ ቡድኑ ባደረሰው ጥቃት ከአካባቢው መሸሽ ባልቻሉ ኃይሉ ንጉሴ እና ሰሙ አባይነህ በተባሉ የክርስትና እምነት ተከታዮች እንዲሁም በአካባቢው ከብቶች በመጠበቅ ላይ የነበረ ባቶ ሰፈኖ የተባለ የእስልምና እምነት ተከታይ በአጠቃላይ የሦስት ሲቪል ሰዎች ሕይወት ሊያልፍ ችሏል። በተጨማሪም ቁጥራቸው ለጊዜው በውል ባልታወቁ ቤቶች ላይ ቃጠሎ መድረሱን፣ የጠለታ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን መቃጠሉን፤ ቢዮ ቡጡሌ የሼክ ሙስተፋ መስጅድ አጥር ላይ ጉዳት መድረሱን፣ በድለተ ጫፋ ጤና ጣቢያ፣ በነዋሪዎች መኖሪያ ቤቶችና የንግድ መደብሮች ላይ በመደዳ ዘረፋ መፈጸሙን እንዲሁም ከ2,650 በላይ የሚገመቱ የአካባቢው ነዋሪዎች መፈናቀላቸውን ኢሰመኮ አረጋግጧል። ኢሰመኮ በአርሲ ዞን በሽርካ፣ በአሰኮ፣ በአንቆሎ ዋቤ፣ ጉና እና መርቲ ወረዳዎች ላይ በታጣቂዎቹ ሲፈጸሙ የነበሩ ጥቃቶች ዳግም እንዳይከሰቱ ተገቢው ጥንቃቄ እንዲደረግ እና ጥቃት ፈጻሚዎች ላይ ተጠያቂነት እንዲረጋገጥ በተለያዩ ጊዜያት ማሳሰቡ ይታወሳል። መንግሥት በአካባቢው ላይ በተደጋጋሚ መሰል ጥቃቶች እና የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች መከሰት መቀጠላቸው አሳሳቢ መሆኑን ከግምት በማስገባት ጥቃት በተፈጸመባቸው አካባቢዎች የጀመራቸውን ጥረቶች በማጠናከር በአስቸኳይ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች እንዲሰማሩ እና ሰላምና ደኅንነትን በማረጋገጥ ነዋሪዎችን ወደ ተረጋጋ ሕይወት የመመለስ ኃላፊነቱን ሊወጣ ይገባል። ከዚሁ ጋር በተያያዘም በመንግሥትና በሌሎች አጋር አካላት በጥቃቶቹ ምክንያት ከቀያቸው ለተፈናቀሉ ነዋሪዎች በቂ የሆነ የአስቸኳይ የሰብአዊ ድጋፍ እንዲቀርብና ተፈናቃዮች ወደ ቀያቸው ተመልሰው በዘላቂነት የሚቋቋሙበት ሁኔታ እንዲመቻች ኢሰመኮ ያሳስባል። በሌላ በኩል ኢሰመኮ ጉዳዩን አስመልክቶ ዝርዝር የምርመራ ሪፖርት ይፋ የሚያደርግ መሆኑን እየገለጸ፤ የተፈጸሙ ጥቃቶችን በአግባቡ ሳያረጋግጡ የሚሰነዘሩ ፍረጃዎችና ቅስቀሳዎች ተጨማሪ ግጭት እንዲፈጠር የማነሳሳት ዕድላቸው ሰፊ በመሆኑ ማናቸውም ተቋማትም ሆኑ ግለሰቦች ከዚህ ድርጊታቸው እንዲቆጠቡ ጥሪ ያቀርባል። የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ ኢሰመኮ በዜጎች ላይ ለደረሰው ሞትና ጉዳት ማዘኑን ገልጸው በሲቪል ሰዎች ላይ የተፈጸሙት የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች አሳሳቢ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ አክለውም መንግሥት ሁኔታውን ለማረጋጋት እና ተጠያቂነትን ለማረጋገጥ ያከናወናቸው ተግባራት መቀጠል ያለባቸው መሆኑን ጠቅሰው፤ በማንኛውም ጊዜ የጸጥታ ሥጋት ባለባቸው አካባቢዎች ሁሉ በቂ የጸጥታ ኃይሎች በመመደብና ተመሳሳይ ጥቃቶችን የመከላከል ሥራ በመሥራት የነዋሪዎች በሕይወት የመኖር፣ የአካል ደኅንነት እና የንብረት መብቶች ለአደጋ እንዳይጋለጡ እንዲያደርግ፣ ተገቢውን ምርመራ በማካሄድ ተጠያቂነትን የማረጋገጥ እና ተጎጂዎችን ለመካስና ለማቋቋም የሚያስችሉ እርምጃዎችን እንዲወስድ እንዲሁም ሁሉም አካላት የተፈጠሩ ችግሮችን ከማውገዝ ባሻገር ግጭት ቀስቃሽ ከሆኑ መግለጫዎች እና ድርጊቶች እንዲታቀቡ ጥሪ አቅርበዋል። 🔗https://ehrc.org/?p=37997 hashtag#Ethiopia📷 hashtag#HumanRightsForAll

በአካል ጉዳተኞች የተሐድሶ አገልግሎት የማግኘት መብት ላይ የተካሄደ ውይይት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በ4 ክልሎች እና በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውስጥ በሚገኙ 13 የተሐድሶ ማእከላት እና የጤና ተቋማት ላይ የአካል ጉዳተኞች የተሐድሶ አገልግሎት እና አጋዥ መሣሪያዎች የማግኘት መብትን አስመልክቶ ባካሄደው የሰብአዊ መብቶች ክትትል የተለዩ ግኝቶች ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ግንቦት 13 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ውይይት አካሂዷል። ክትትሉ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ በአማራ፣ ኦሮሚያ፣ ደቡብ ኢትዮጵያ እና ትግራይ ክልሎች በሚገኙ የተለያዩ የተሐድሶ ማእከላት እና የሪፈራል ሆስፒታሎች ላይ የተከናወነ ነው፡፡ በውይይቱ ላይ የጤና፣ የትምህርት እና የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች፣ የሕክምና ተቋማት፣ የአካል ተሐድሶ ማእከላት፣ የክልል ጤና ቢሮዎች፣ የአካል ጉዳተኞች ማኅበራት እንዲሁም ሌሎች መንግሥታዊ እና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ተገኝተዋል። በመድረኩም የተሐድሶ አገልግሎት ምንነት እንዲሁም የተሐድሶ አገልግሎትን የተመለከቱ ዓለም አቀፍ እና ሀገራዊ የሕግና የፖሊሲ ማዕቀፎች ላይ ገለጻ ተደርጓል። በተጨማሪም በኢሰመኮ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ክትትል የተለዩ አዎንታዊና አሳሳቢ ሁኔታዎች ቀርበዋል። የተሐድሶ አገልግሎትን የተመለከቱ የሕግ ማዕቀፎች መኖራቸው፣ አንዳንድ አጋዥ መሣሪያዎችና ቁሳቁሶች በሀገር ውስጥ መመረት መጀመራቸው፣ የዘርፉ ባለሙያዎች ሙያዊ ሥነ ምግባርን የተከተለ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑ፣ የኢትዮጵያ አካል ድጋፍ አገልግሎት በንጽጽር የተሻለ የአጋዥ መሣሪያዎች አቅርቦት ያለው መሆኑ በአዎንታዊ ሁኔታ ተጠቅሰዋል። በአንጻሩ የተሐድሶና አጋዥ መሣሪያዎች አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማት አነስተኛ መሆን፤ ሩቅና ለመድረስ አስቸጋሪ በሆኑ የገጠር አካባቢዎች ተደራሽ አለመሆን፤ በዘርፉ ከፍተኛ የሆነ የሰው ኃይል እጥረት መኖር እና የተሐድሶ አገልግሎት ትምህርት በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት አለመሰጠት በአሳሳቢነት የተለዩ ነጥቦች ናቸው። ከዚህ በተጨማሪም የአጋዥ መሣሪያዎች፣ ቴክኖሎጂዎች እና ማሽኖች አቅርቦት እጥረት፤ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙ መሣሪያዎችና ማሽኖች ያረጁና የተበላሹ መሆናቸው፤ የተሐድሶ አገልግሎት መስጫ ቦታዎች ምቹ አለመሆን፤ ለሁሉም የአካል ጉዳት ዓይነቶች አገልግሎት የሚሰጥ ሁሉን አቀፍ (comprhensive) የተሐድሶ አገልግሎት አለመኖር፤ ዘርፉ የሚመራበት የፖሊሲ ማዕቀፍና የድርጊት መርኅ ግብር አለመኖር እና ከፍተኛ የበጀት እጥረት መሻሻል የሚገባቸውና በአሳሳቢነት የተጠቀሱ ጉዳዮች ናቸው። የውይይቱ ተሳታፊዎች የተሐድሶ አገልግሎት የሚፈልገው የሕዝብ ቁጥር ከፍተኛ በመሆኑ የተሐድሶ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማት በመሣሪያና በሰው ኃይል እንዲደራጁ፣ ዘርፉ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሥርዓተ ትምህርት ውስጥ እንዲካተት፣ መንግሥት የተሐድሶ አገልግሎት ፖሊሲ በመቅረጽ ለዘርፉ ትኩረት እንዲሰጥ እና በቂ በጀት እንዲመድብ እንዲሁም የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን በስፋት እንዲያከናውን ጠይቀዋል። የኢሰመኮ የአካል ጉዳተኞች እና የአረጋውያን መብቶች ኮሚሽነር መሐመድ አሕመድ የአካል ጉዳተኞች የተሐድሶ እና አጋዥ መሣሪያዎች አገልግሎት የማግኘት መብት እንዲረጋገጥ ኢሰመኮ የሚያከናውናቸውን የክትትል እና የውትወታ ሥራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል፡፡ አክለውም፣ በክትትል ግኝቶቹ መነሻነት የቀረቡ ምክረ ሐሳቦች እንዲፈጸሙ፣ በዘርፉ እያጋጠመ ያለው የአጋዥ መሣሪያዎችና የሰው ኃይል አቅርቦት እጥረት እንዲቀረፍ፣ የተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥ ደረጃ እንዲሻሻል እንዲሁም ተቋማት ተደራሽ እንዲሆኑ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን አስተዋጽዖ እንዲያበረክቱ እና በትብብር እንዲሠሩ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37923 #Ethiopia #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

በአካል ጉዳተኞች የተሐድሶ አገልግሎት የማግኘት መብት ላይ የተካሄደ ውይይት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በ4 ክልሎች እና በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውስጥ በሚገኙ 13 የተሐድሶ ማእከላት እና የጤና ተቋማት ላይ የአካል ጉዳተኞች የተሐድሶ አገልግሎት እና አጋዥ መሣሪያዎች የማግኘት መብትን አስመልክቶ ባካሄደው የሰብአዊ መብቶች ክትትል የተለዩ ግኝቶች ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ግንቦት 13 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ ውይይት አካሂዷል። ክትትሉ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ በአማራ፣ ኦሮሚያ፣ ደቡብ ኢትዮጵያ እና ትግራይ ክልሎች በሚገኙ የተለያዩ የተሐድሶ ማእከላት እና የሪፈራል ሆስፒታሎች ላይ የተከናወነ ነው፡፡ በውይይቱ ላይ የጤና፣ የትምህርት እና የሴቶች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች፣ የሕክምና ተቋማት፣ የአካል ተሐድሶ ማእከላት፣ የክልል ጤና ቢሮዎች፣ የአካል ጉዳተኞች ማኅበራት እንዲሁም ሌሎች መንግሥታዊ እና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የሥራ ኃላፊዎችና ባለሙያዎች ተገኝተዋል። በመድረኩም የተሐድሶ አገልግሎት ምንነት እንዲሁም የተሐድሶ አገልግሎትን የተመለከቱ ዓለም አቀፍ እና ሀገራዊ የሕግና የፖሊሲ ማዕቀፎች ላይ ገለጻ ተደርጓል። በተጨማሪም በኢሰመኮ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታ ክትትል የተለዩ አዎንታዊና አሳሳቢ ሁኔታዎች ቀርበዋል። የተሐድሶ አገልግሎትን የተመለከቱ የሕግ ማዕቀፎች መኖራቸው፣ አንዳንድ አጋዥ መሣሪያዎችና ቁሳቁሶች በሀገር ውስጥ መመረት መጀመራቸው፣ የዘርፉ ባለሙያዎች ሙያዊ ሥነ ምግባርን የተከተለ አገልግሎት እየሰጡ መሆኑ፣ የኢትዮጵያ አካል ድጋፍ አገልግሎት በንጽጽር የተሻለ የአጋዥ መሣሪያዎች አቅርቦት ያለው መሆኑ በአዎንታዊ ሁኔታ ተጠቅሰዋል። በአንጻሩ የተሐድሶና አጋዥ መሣሪያዎች አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማት አነስተኛ መሆን፤ ሩቅና ለመድረስ አስቸጋሪ በሆኑ የገጠር አካባቢዎች ተደራሽ አለመሆን፤ በዘርፉ ከፍተኛ የሆነ የሰው ኃይል እጥረት መኖር እና የተሐድሶ አገልግሎት ትምህርት በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት አለመሰጠት በአሳሳቢነት የተለዩ ነጥቦች ናቸው። ከዚህ በተጨማሪም የአጋዥ መሣሪያዎች፣ ቴክኖሎጂዎች እና ማሽኖች አቅርቦት እጥረት፤ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙ መሣሪያዎችና ማሽኖች ያረጁና የተበላሹ መሆናቸው፤ የተሐድሶ አገልግሎት መስጫ ቦታዎች ምቹ አለመሆን፤ ለሁሉም የአካል ጉዳት ዓይነቶች አገልግሎት የሚሰጥ ሁሉን አቀፍ (comprhensive) የተሐድሶ አገልግሎት አለመኖር፤ ዘርፉ የሚመራበት የፖሊሲ ማዕቀፍና የድርጊት መርኅ ግብር አለመኖር እና ከፍተኛ የበጀት እጥረት መሻሻል የሚገባቸውና በአሳሳቢነት የተጠቀሱ ጉዳዮች ናቸው። የውይይቱ ተሳታፊዎች የተሐድሶ አገልግሎት የሚፈልገው የሕዝብ ቁጥር ከፍተኛ በመሆኑ የተሐድሶ አገልግሎት የሚሰጡ ተቋማት በመሣሪያና በሰው ኃይል እንዲደራጁ፣ ዘርፉ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሥርዓተ ትምህርት ውስጥ እንዲካተት፣ መንግሥት የተሐድሶ አገልግሎት ፖሊሲ በመቅረጽ ለዘርፉ ትኩረት እንዲሰጥ እና በቂ በጀት እንዲመድብ እንዲሁም የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን በስፋት እንዲያከናውን ጠይቀዋል። የኢሰመኮ የአካል ጉዳተኞች እና የአረጋውያን መብቶች ኮሚሽነር መሐመድ አሕመድ የአካል ጉዳተኞች የተሐድሶ እና አጋዥ መሣሪያዎች አገልግሎት የማግኘት መብት እንዲረጋገጥ ኢሰመኮ የሚያከናውናቸውን የክትትል እና የውትወታ ሥራዎች አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልጸዋል፡፡ አክለውም፣ በክትትል ግኝቶቹ መነሻነት የቀረቡ ምክረ ሐሳቦች እንዲፈጸሙ፣ በዘርፉ እያጋጠመ ያለው የአጋዥ መሣሪያዎችና የሰው ኃይል አቅርቦት እጥረት እንዲቀረፍ፣ የተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥ ደረጃ እንዲሻሻል እንዲሁም ተቋማት ተደራሽ እንዲሆኑ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የበኩላቸውን አስተዋጽዖ እንዲያበረክቱ እና በትብብር እንዲሠሩ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37923 #Ethiopia #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

#አዲስአበባ፡ በትራንስፖርት አገልግሎት የተደራሽነት ሁኔታ ላይ የተካሄደ ውይይት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎቶች ለአካል ጉዳተኞች እና ለአረጋውያን ያላቸውን ተደራሽነት፣ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች እንዲሁም ሊወሰዱ የሚገባቸውን እርምጃዎች አስመልክቶ ግንዛቤ ለመፍጠር እና የባለድርሻ አካላትን ሚና ለመለየት ያለመ የውይይት መድረክ ግንቦት 4 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ አካሂዷል። በመድረኩ ከኢ.ፌ.ዴ.ሪ የትራንስፖርት እና ሎጂስቲክስ ሚኒስቴር፣ ከአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ቢሮ፣ ከትራፊክ ማኔጅመንት ባለሥልጣን፣ ከከተማ አውቶቡስ አገልግሎት ድርጅት፣ ከሴቶች፣ ሕፃናት እና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ እንዲሁም ከታክሲ ማኅበራት እና ከተርሚናል ኢንተርፕራይዝ የተወጣጡ ተወካዮች እና የሥራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል። በውይይቱ የትራንስፖርት አገልግሎትን ለአካል ጉዳተኞች እና ለአረጋውያን ተደራሽ ከማድረግ አንጻር የሚስተዋሉ ተግዳሮቶች እና አዎንታዊ ሁኔታዎች ቀርበው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል። ለሕዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚውሉ ተሽከርካሪዎች ለአካል ጉዳተኞች እና ለአረጋውያን አጠቃቀም ምቹ የሆኑ መሣሪያዎች የሌላቸው መሆኑ፣ መሣሪያዎቹ ባላቸው ጥቂት ተሽከርካሪዎች ላይም በብልሽት ምክንያት አገልግሎት የማይሰጡ መሆኑ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀ እና ተደራሽ የአውቶቡስ ማቆሚያዎች እና የእግረኛ መንገዶች አለመኖር፣ በድምጽ ወይም በምስል የሚተላለፉ መረጃዎች እና ጠቋሚ ምልክቶች አለመሟላት፣ ለአካል ጉዳተኞች እና ለአረጋውያን ቅድሚያ የመስጠት እና ድጋፍ የማድረግ አሠራር ተግባራዊነቱ በግለሰቦች በጎ ፈቃደኝነት ላይ የተመሠረተ መሆኑ እንዲሁም ከአመለካከት ጋር የተያያዙ ክፍተቶች ተግዳሮቶች መሆናቸው ተመላክቷል። በሌላ በኩል የትራንስፖርት አገልግሎት ለአካል ጉዳተኞች እና ለአረጋውያን ተደራሽ እንዲሆን የሚያስችሉ ሕጎች፣ ፖሊሲዎች እና መመሪያዎች መኖራቸው፣ ለአካል ጉዳተኞች የተለዩ የመኪና ማቆሚያ ቦታዎች (ፓርኪንግ) በዝግጅት ላይ መሆናቸው፣ እንዲሁም አዳዲስ ተሽከርካሪዎች ወደ ሀገር ውስጥ ሲገቡ ተገቢውን የተደራሽነት መስፈርት ያሟሉ መሆናቸውን ማረጋገጥ የሚያስችል ፖሊሲ በዝግጅት ላይ መሆኑ በውይይቱ በአዎንታዊነት ከተነሱ ጉዳዮች መካከል ይገኙበታል። በተጨማሪም የውይይቱ ተሳታፊዎች የትራንስፖርት አገልግሎትን ለአካል ጉዳተኞች እና ለአረጋውያን ተደራሽ ለማድረግ የሚመለከታቸው ተቋማት በቅንጅት መሥራት እንዳለባቸው ገልጸዋል። የኢሰመኮ ምርመራ እና ክትትል ሥራ ክፍል የአዲስ አበባ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ ዮሴፍ ግርማ አካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን የትራንስፖርት አገልግሎት እኩል ተጠቃሚ እንዲሆኑ እንዲሁም የአገልግሎቱን ተደራሽነት ለማረጋገጥ ባለድርሻ አካላት ትኩረት ሰጥተው እንዲሠሩ አሳስበዋል። አክለውም አካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን በትራንስፖርት ዘርፍ ለሚያጋጥሟቸው ተግዳሮቶች እልባት ለመስጠት፤ በጅምር ላይ ያሉ የፖሊሲ ዝግጅት እና መሰል ሥራዎች ተጠናቀው ተግባራዊ እንዲደረጉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡ 🔗 https://ehrc.org/?p=37787 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

#አማራ፡- የተጠርጣሪዎች ሰብአዊ መብቶች አያያዝ ላይ የተካሄደ ውይይት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በአማራ ክልል የተለያዩ ዞኖች እና ከተማ አስተዳደሮች ሥር በሚገኙ 32 ፖሊስ ጣቢያዎች ላይ ባካሄደው የክትትል ሥራ ግኝቶች ላይ ከባለድርሻ አካላት ጋር ግንቦት 5 ቀን 2018 ዓ.ም. በባሕር ዳር ከተማ ውይይት አካሂዷል። በውይይቱ የክልሉ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ ምክትል ኮሚሽነርና የወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ፤ የክልሉ ምክር ቤት የሕግ፣ ፍትሕና አስተዳደር ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፣ የክልሉጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ ፍትሕ ቢሮ፣ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ እንዲሁም ሚሊሻ ኮሚሽን፣ የተ.መ.ድ. የሰብአዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር (Office of the High Commissioner for Human Rights / OHCHR) ባሕር ዳር ጽሕፈት ቤት እና የባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ ሕግ ትምህርት ቤት የሥራ ኃላፊዎች እና ተወካዮች እንዲሁም የፖሊስ መምሪያ ኃላፊዎችና የጣቢያ አዛዦች ተሳትፈዋል። በውይይቱ በክትትሉ የተለዩ መልካም ተሞክሮዎችና እና መሻሻል የሚገባቸው አሳሳቢ የሰብአዊ መብቶች ሁኔታዎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል። የኢሰመኮ ክትትልን ተከትሎ በተደረገ ውትወታ በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ለ172 ሰዎች መፍትሔ መሰጠቱ፤ በደቡብ ወሎ ዞን፣ ደሴ እና ኮምቦልቻ ከተሞች በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች አብዛኛዎቹ ተጠርጣሪዎች በተያዙ በ48 ሰዓት ውስጥ ፍርድ ቤት መቅረባቸው፤ በወንጀል የተጠረጠሩ ሰዎች ከትዳር አጋሮቻቸው ወይም ከቤተሰቦቻቸው፣ ከቅርብ ዘመዶቻቸው፣ ከጓደኞቻቸው፣ ከሃይማኖትና ከሕግ አማካሪዎቻቸው ጋር ሳምንቱን በሙሉ የሚገናኙበት የአሠራር ሁኔታ መዘርጋቱ፤ የወንጀል ሥነ ሥርዓት ሕጉን ድንጋጌዎች መሠረት ያደረገ የወንጀል ምርመራ አሠራር መኖሩ እንዲሁም በተወሰኑ ፖሊስ ጣቢያዎች ምቹ የተጠርጣሪዎች ማቆያ ክፍሎች መኖራቸው በመልካም እመርታነት ተጠቅሰዋል። በሌላ በኩል ሰዎች ያለ ፍርድ ቤት ትእዛዝ የሚያዙ እና በ48 ሰዓታት ውስጥ ፍርድ ቤት የማይቀርቡ መሆኑ፤ “ወቅታዊ ጉዳይ’’ በሚል የተያዙ ተጠርጣሪዎች እስከ 7 ወር ድረስ ፍርድ ቤት ሳይቀርቡ ለተራዘመ እስር የተዳረጉበት ሁኔታ መኖሩ፤ በተጠርጣሪዎች ላይ የሚፈጸም አካላዊ ቅጣት መኖሩ፤ የተጠርጣሪዎች የመጎብኘት መብታቸው መነፈጉ፤ አልፎ አልፎ በፖሊሶች የሚፈጸም ማስፈራራት፣ ዛቻ፣ ስድብ እና አካላዊ ቅጣት፤ ለሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ተጋላጭ ለሆኑ የኅብረተሰብ ክፍሎች የሚደረግ የተለየ ድጋፍ አለመኖር፤ ወጥነት ያለው የቅሬታ አቀራርብ ሥርዓት አለመኖር፤ ተጠርጣሪዎች ቀን ላይ ማረፊያ ክፍሎች ውስጥ ተዘግቶባቸው የሚውሉበት አሠራር መኖሩ ትኩረት የሚሹ እና ሊሻሻሉ የሚገባቸው አሳሳቢ ጉዳዮች መሆናቸው ተመላክቷል። የክልሉ ፖሊስ ዋና ጠቅላይ መምሪያ ምክትል ኮሚሽነርና የወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምሪያ አዛዥ ምክትል ኮሚሽነር ታደሰ አያሌው በኢሰመኮ የቀረቡት ግኝቶች ነባራዊ ሁኔታውን የሚያሳዩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም የተጠርጣሪዎች ሰብአዊ መብቶች አያያዝን የማሻሻል ሥራ የሚመለከታቸው አካላትን ድጋፍ የሚሻ መሆኑን እና ጠቅላይ መምሪያው የራሱን መመዘኛ (standard) አዘጋጅቶ ተግባር ላይ እያዋለ መሆኑን ተናግረዋል። የኢሰመኮ የሰብአዊ መብቶች ክትትል እና ምርመራ ሥራ ክፍል የሪጅን ዳይሬክተር ዮናስ ሙሉጌታ በግጭት እና የጸጥታ ችግሮች ዐውድ ውስጥም ፖሊስ ለሕግ የበላይነት እና ለሰብአዊ መብቶች ድንጋጌዎች እና መርሖዎች መከበር ኃላፊነቱን መወጣት እንዳለበት ገልጸው፤ ተጠርጣሪዎች ሰብአዊ ክብራቸው ተጠብቆ መያዛቸውን ለማረጋገጥ እና ለአጠቃላይ የክልሉ ሰብአዊ መብቶች ሁኔታ መሻሻል ኢሰመኮ ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት መሥራቱን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37768 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

በሰብአዊ መብቶች፣ በሽግግር ፍትሕ እና ተያያዥ የሕግ ማዕቀፎች ዙሪያ የተካሄደ ዐውደ ጥናት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)፣ ከፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት እና ከጀርመን ዓለም አቀፍ ትብብር ድርጅት (GIZ) ጋር በመተባበር በሰብአዊ መብቶች እና በሽግግር ፍትሕ ዙሪያ የግንዛቤ ማሳደጊያ ዐውደ ጥናት ሚያዝያ 16 እና 17 ቀን 2018 ዓ.ም. አካሂዷል። ዐውደ ጥናቱ ስለ ሽግግር ፍትሕ ጽንሰ ሐሳቦች፣ መርሖች እና አላባውያን፤ ስለ ኢትዮጵያ የሽግግር ፍትሕ ሂደት፤ የፖሊሲ ይዘት፤ በሽግግር ፍትሕ ሂደት ውስጥ ኢሰመኮ ስላለው ሚና፤ እንዲሁም በአጠቃላይ የሰብአዊ መብቶች ጥበቃን በማረጋገጥ ረገድ የዳኝነት አካላት ግንዛቤን ለማሳደግ ያለመ ነው። በዐውደ ጥናቱ ላይ ነባር እና አዲስ የተሾሙ የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ዳኞች እና የሥራ ኃላፊዎች ተሳትፈዋል። በመድረኩ በሽግግር ፍትሕ ሂደት የዳኝነት አካላት ሚና፣ ስልታዊ የሰብአዊ መብቶች ሙግት፣ የአስተዳደር ሥነ ሥርዓት ሕግ አተገባበር እና ተያያዥ የሰብአዊ መብቶች ጉዳዮችን የተመለከቱ ገለጻዎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል። በውይይቱ ለከባድ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ምላሽ በመስጠት ረገድ የሚያጋጥሙ ተግዳሮቶች፤ በሽግግር ፍትሕ ስልቶች ቀረጻ እና አተገባበር ሂደት የተጎጂዎችን ፍላጎት፣ እይታ እና ቅድሚያ የሚሰጧቸውን ጉዳዮች የማካተት አስፈላጊነት፤ እንዲሁም በሽግግር ፍትሕ ትግበራ ወቅት በመደበኛው የዳኝነት ሥርዓት ውስጥ የሚቋቋሙ ልዩ ችሎትን ጨምሮ ሌሎች አስፈላጊ ተቋማትን ከማቋቋም ጋር ተያይዞ የሚነሱ ስጋቶችን አስቀድሞ በመለየት የመፍትሔ አቅጣጫዎች ማስቀመጥን የተመለከቱ ሐሳቦች በስፋት ተነስተዋል። የውይይቱ ተሳታፊዎች ዐውደ ጥናቱ በሰብአዊ መብቶች ጥበቃ እና በዳኝነት ተግባራት መካከል ባለው መስተጋብር ላይ ግንዛቤ ያገኙበት መሆኑን ገልጸዋል። በተጨማሪም መብቶችን መሠረት ያደረገ የዳኝነት ውሳኔ አሰጣጥን (rights-based adjudication) ለማጠናከር እና የሽግግር ፍትሕ ሂደቱን ውጤታማ በሆነ መንገድ ለመተግበር የዳኝነት አካላት እና የኢሰመኮ ቀጣይነት ያለው አጋርነት አስፈላጊ መሆኑን ጠቁመዋል። የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት ክብርት ወ/ሮ ሌሊሴ ደሳለኝ ፍርድ ቤቶች ተጠያቂነትን በማረጋገጥ፣ መሠረታዊ መብቶችን በማስጠበቅ፣ ገለልተኛ እና ፍትሐዊ ውሳኔ በመስጠት የኢትዮጵያ የሽግግር ፍትሕ ሂደት ውጤታማ አተገባበር ላይ ያላቸውን ቁልፍ ሚና አብራርተዋል። አክለውም፣ በኢትዮጵያ ለተፈጸሙ ከባድ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ተገቢ ምላሽ በመስጠት ዘላቂ ሰላም እና የሕግ የበላይነትን ማስፈን እንደሚገባ ገልጸዋል። ኢሰመኮ አጠቃላይ ለፍትሕ ሥርዓቱ ውጤታማነት እንዲሁም የዳኝነት አካላት በሽግግር ፍትሕ ሂደት የሚያከናውኗቸውን ተግባራት በመደገፍ ረገድ የሚያበረክተውን አስተዋጽዖ አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ 🔗 https://ehrc.org/?p=37740 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

በምርጫ ሂደት የወቅታዊ ሁኔታ መከታተያ ሥርዓት (Situation Room) መደራጀትና ወደ ሥራ መግባት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ለ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ ያደራጀውን የወቅታዊ ሁኔታ መከታተያ ሥርዓት (Situation Room) ግንቦት 14 ቀን 2018 ዓ.ም. አስጀምሯል፡፡ በመርኃ ግብሩ የኢሰመኮ ኮሚሽነሮች፣ የሥራ ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች እንዲሁም የጀርመን ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት (GIZ – Deutsche Gesellschaft für Internationale Zusammenarbeit) ተወካዮች ተገኝተዋል። ኢሰመኮ በተሻሻለው የመቋቋሚያ አዋጁ መሠረት በምርጫ ወቅት የሰብአዊ መብቶች አጠባበቅ ሁኔታን የመከታተል ኃላፊነትና ሥልጣን በግልጽ የተሰጠው ሲሆን፣ የሁኔታ መከታተያው የምርጫው ሂደት ሰብአዊ መብቶችን ያከበረ መሆኑን ለመከታተል የሚያግዙ ስልቶች እና አስፈላጊ የቴክኖሎጂ ግብአቶች የተሟሉለት ነው፡፡ የምርጫ ሂደት ሁኔታ መከታተያውን የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ እና የጀርመን ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት የኢትዮጵያ እና ጅቡቲ ዳይሬክተር ዶሮቴ ሃተር መርቀው ከፍተውታል። የሁኔታዎች መከታተያው የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች እና አሳሳቢ ጉዳዮችን በተመለከተ መረጃዎችን በፍጥነት ለማእከል እንዲደርሱ በማድረግ መፍትሔ ለማሰጠት የሚደረገውን ጥረት የሚያሳልጥ ነው። ይህም የምርጫው ሂደት አግባብነት ባላቸው አዋጆች፣ ደንቦችና መመሪያዎች መሠረት ሰብአዊ መብቶችን አክብሮ መከናወኑን ለማረጋገጥ፣ ማናቸውም ዐይነት የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች እንዳይፈጸሙ አስቀድሞ ለመከላከልና ከተፈጸሙም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር ፈጣን ምላሽ የሚያገኙበትን ሁኔታ ለመፍጠር፤ የሰብአዊ መብቶች አንድምታ ያላቸው ከምርጫ ጋር የተያያዙ የጸጥታ ሁኔታዎችን፣ የቴክኒክ ችግሮችን ወይም ሌሎች እንቅፋቶችን በወቅቱ በመረዳት እልባት ለመስጠት እንደሚጠቅም ተብራርቷል፡፡ የጀርመን ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት የኢትዮጵያ እና የጅቡቲ ዳይሬክተር ዶሮቴ ሀተር የኢሰመኮ የሰብአዊ መብቶች ክትትል ሥራዎች መጠናከር ትልቅ ስኬት መሆኑን ገልጸው፣ ለምርጫው ልዩ ትኩረት መስጠቱን በማድነቅ ተቋማቸው አጋርነቱን አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ ምርጫው ዲሞክራሲያዊ፣ አሳታፊ እና ሰብአዊ መብቶችን ያከበረ መሆኑን ለማረጋገጥ በሚደረገው ጥረት የምርጫ ወቅታዊ ሁኔታ መከታተያው ከፍተኛ ዐቅም በመፍጠር እና በየአካባቢው የሚሰማሩ የክትትል ባለሙያዎች ባሉባቸው ቦታዎች ቀጥታ መረጃ በመስጠት ለውሳኔ የሚረዳ ዐውድ የሚፈጥር መሆኑን ገልጸዋል። አክለውም መሰል የቴክኖሎጂ ዐቅም በመፍጠር ረገድ የጀርመን ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅት ላበረከተው አስተዋጽዖ ምስጋና አቅርበዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37711 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

#ቤኒሻንጉል_ጉሙዝ፦ በፖሊስ ጣቢያዎች ላይ በተከናወኑ የሰብአዊ መብቶች ክትትሎች የተለዩ ግኝቶች ላይ የተካሄደ ውይይት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ውስጥ በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎች ላይ ባከናወናቸው የሰብአዊ መብቶች ክትትሎች የተለዩ ግኝቶች እና የተሰጡ ምክረ ሐሳቦች ላይ ሚያዚያ 29 ቀን 2018 ዓ.ም. በባምባሲ ከተማ ከባለድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሂዷል። በውይይቱ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት የሕግ እና ፍትሕ አስተዳደር ቋሚ ኮሚቴ፣ ከክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን እና ከተለያዩ ዞኖች፣ ወረዳዎች፣ ልዩ ወረዳዎች እና ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያዎች የተወጣጡ ተወካዮች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ በውይይቱ ኢሰመኮ በፖሊስ ጣቢያዎች ላይ ባከናወናቸው ክትትሎች የተለዩ አዎንታዊ እና አሳሳቢ ጉዳዮች እንዲሁም የተሰጡ ምክረ ሐሳቦች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ ከሕግ አግባብ ውጪ የሚደረጉ እስሮች እና የቤተሰብ ጉብኝት ክልከላዎች ላይ መሻሻሎች መኖራቸው፤ በአንዳንድ ቦታዎች ላይ የማቆያ ስፍራዎች እደሳት እና አዲስ የማስፋፊያ ግንባታዎች እየተከናወኑ መሆኑ እንዲሁም የተወሰኑ ፖሊስ ጣቢያዎች በእስር ላይ ለሚገኙ ተጠርጣሪዎች ምግባ የሚውል በጀት መያዝ መጀመራቸው በውይይቱ በአዎንታዊነት ከተነሱ ጉዳዮች መካከል ይገኙበታል፡፡ በሌላ በኩል የተጠርጣሪዎችን መብቶች በማያከብሩና የመብት ጥሰት በሚያደርሱ የፖሊስ አባላት ላይ አስተዳደራዊና ሕጋዊ እርምጃዎችን አለመወሰድ፤ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ ሰዎችን ማሰር፤ በሕግ በተቀመጠው ቀነ ገደብ ፍርድ ቤት አለማቅረብ፤ ከሕግ አግባብ ውጪ የሚደረጉ አፈሳ/ የጅምላ እስሮች መኖር፤ የማቆያ ክፍሎች ጥበትና የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ችግር በክልሉ አንዳንድ ፖሊስ ጣቢያዎች በአሳሳቢነት የቀጠሉ እና ሊሻሻሉ የሚገባቸው ጉዳዮች መሆናቸው ተገልጿል፡፡ የውይይቱ ተሳታፊዎች በአሳሳቢነት የቀጠሉ ችግሮችን ለማሻሻል እና በክልሉ ያለው አጠቃላይ የተጠርጣሪዎች አያያዝ ሁኔታ ሰብአዊ መብቶችን ያከበረ እንዲሆን አበክሮ መሥራት አስፈላጊ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡ የኢሰመኮ የክትትልና ምርመራ ሥራ ክፍል ሪጅናል ዳይሬክተር በጋሻው እሸቱ በጥበቃ ስር ያሉ ሰዎችን ሰብአዊ መብቶች በማክበር፤ በማስከበር እና በማሟላት ረገድ የፖሊስ ተቋማት ትልቅ ኃላፊነት ያለባቸው መሆኑን አንስተው የኢሰመኮ ምክረ ሐሳቦችን ተግባራዊ ማድረግን ጨምሮ በክልሉ ያለው የተጠርጣሪዎች አያያዝ ሁኔታ ሰብአዊ መብቶችን ያከበረ መሆኑን ለማረጋገጥ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቅንጅት መሥራት እንዳለባቸው ገልጸዋል፡፡ 🔗 https://ehrc.org/?p=37684 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

#ቤኒሻንጉል_ጉሙዝ፦ በሰብአዊ መብቶች እና ሽግግር ፍትሕ ላይ የተካሄደ የዐቅም ግንባታ ዐውደ ጥናት ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት ጋር በመተባበር በሰብአዊ መብቶች እና በሽግግር ፍትሕ ላይ ያተኮረ የዐቅም ግንባታ ዐውደ ጥናት ሚያዝያ 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም. በአሶሳ ከተማ አካሂዷል፡፡ በዚህ ዐውደ ጥናት የክልሉ ሕግ አውጪ፣ ተርጓሚ እና አስፈጻሚ አካላት፣ የክልሉ ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤን ጨምሮ፣ የጠቅላይ ፍርድ ቤት፣ የፍትሕ ቢሮ፣ የፖሊስ ኮሚሽን፣ የማረሚያ ቤቶች አስተዳደር እና ሌሎች የክልሉ የሥራ ኃላፊዎችና ተወካዮች ተሳትፈዋል። በዐውደ ጥናቱ የሰብአዊ መብቶች ጽንሰ ሐሳቦች እና መሠረታዊ መርሖች፣ ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ የሰብአዊ መብቶች ድንጋጌዎች፣ የኢሰመኮ ሥልጣን፣ ተግባርና ኃላፊነት እንዲሁም ዓለም አቀፍ፣ አህጉራዊ እና ብሔራዊ የሽግግር ፍትሕ መርሖች እና የኢትዮጵያ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ አቅጣጫዎች የተዳሰሱ ሲሆን፣ በእያንዳንዱ ርዕሰ ጉዳይ ላይ የቀረቡ ገለጻዎችን ተከትሎ ተሳታፊዎች በዝርዝር ተወያይተዋል። በውይይቱ የተሳተፉ የክልሉ ልዩ ልዩ ተቋማት ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች የዐቅም ግንባታ ዐውደ ጥናቱ ጠቃሚ መሆኑን ጠቁመው፣ መሰል መድረኮች በተለያዩ ተቋማት ውስጥ ለሚገኙ በርካታ ሠራተኞች ተደራሽ እንዲሆኑ ጠይቀዋል። በተጨማሪም ሰብአዊ መብቶችን ማስከበርና ማስፋፋት የሁሉም ባለድርሻ አካላት የጋራ ኃላፊነት መሆኑንም አጽንዖት ሰጥተዋል። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ምክር ቤት ዋና አፈጉባኤ ክብርት ወ/ሮ አስካል አልቦሮ የሕግ የበላይነትን ለማረጋገጥና ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን የሰብአዊ መብቶች ጥበቃ ጉልህ ሚና እንዳለው ገልጸዋል። አክለውም ምክር ቤቱ በክልሉ ያለው የዴሞክራሲ ሥርዓት ይበልጥ እንዲጎለብትና ሰብአዊ መብቶች እንዲከበሩ ለማስቻል የዴሞክራሲ ተቋማት የጋራ ፎረም ለማቋቋም ከኢሰመኮ ጋር እየሠራ መሆኑን አብራርተዋል፡፡ የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ ባለፉት ዓመታት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ባጋጠሙ የጸጥታ ችግሮች ሳቢያ የተከሰቱ እና የተባባሱ የሰብአዊ መብቶች ጉዳዮችን በመጥቀስ፣ የጥሰት መንስዔዎችን መፍትሔ መስጠት እንደሚገባ በአጽንዖት ገልጸዋል፡፡ ዋና ኮሚሽነሩ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች በመድረኩ ያገኙትን ግንዛቤ ወደ ተግባር በመቀየር በክልሉ ለሚታዩ የሰብአዊ መብቶች ጥበቃ ተግዳሮቶች ተገቢውን ምላሽ እንደሚሰጡ ያላቸውን እምነት ገልጸዋል። ሰላም ለሰብአዊ መብቶች ጥበቃ መሠረታዊ ቅድመ-ሁኔታ መሆኑን በመጥቀስ ለዘላቂ ሰላም ቅድሚያ እንዲሰጥም አሳስበዋል። በመጨረሻም ክልሎች በኢትዮጵያ የሽግግር ፍትሕ ፖሊሲ ሥር የተጣለባቸውን ኃላፊነት መወጣት እንዳለባቸው በመግለጽ፣ በሀገራዊ የሽግግር ፍትሕ ሂደት ውስጥ ንቁ ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37606 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

የሲቪክ ምኅዳርን ማስፋት እና የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃን ማጠናከር ላይ ያተኮረ ምክክር ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከአፍሪካ ብሔራዊ የሰብአዊ መብቶች ተቋማት ትስስር (Network of African National Human Rights Institutions (NANHRI)) ጋር በመተባበር በኢትዮጵያ ያለውን የሲቪክ ምኅዳር ለማስፋት እና የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃን ለማጠናከር ያለመ የምክክር መድረክ ሚያዝያ 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ አካሂዷል። በምክክሩ ከተ.መ.ድ. የሰብአዊ መብቶች ከፍተኛ ኮሚሽነር የምሥራቅ አፍሪካ ቢሮ (Office of the High Commissioner for Human Rights-East African Regional Office (OHCHR-EARO))፣ ከአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን የፖለቲካ፣ የሰላም እና ጸጥታ ክፍል፣ ከዴንማርክ ሰብአዊ መብቶች ኢንስቲትዩት (Danish Human Rights Institution – DHRI)፣ ከኬንያ ሰብአዊ መብቶች ብሔራዊ ኮሚሽን (Kenya National Commission for Human Rights – KNCHR) እና ከተለያዩ የሲቪክ ማኅበረሰብ ድርጅቶች የተውጣጡ ተወካዮች ተሳትፈዋል፡፡ በምክክሩ የሲቪክ ምኅዳርን እና የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃን የተመለከቱ ዓለም አቀፍ እና አህጉራዊ የሕግ ማዕቀፎች እና መመዘኛዎች ላይ ያተኮሩ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል። በተጨማሪም ኢሰመኮ ክትትል፣ ጥናት እና ሕዝባዊ መድረክ (Public Inquiry) በማከናወን እንዲሁም ሞዴል ሕግ በማዘጋጀት የሲቪክ ምኅዳሩን ለማስፋት እና የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች መብቶችን ለማስጠበቅ ሲያከናውን የቆያቸው ተግባራት በመድረኩ ቀርበዋል። የምክክሩ ተሳታፊዎች በኢትዮጵያ የተሻለ የሲቪክ ምኅዳር ለመፍጠር የሕግ ማዕቀፎችን ማሻሻል፣ የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች በአካል እና በበይነመረብ (Online) የመብቶች ጥሰት እንዳይደርስባቸው በቂ ጥበቃ መስጠት እንደሚገባ አጽንዖት ሰጥተዋል። የአፍሪካ ብሔራዊ የሰብአዊ መብቶች ተቋማት ትስስር (Network of African National Human Rights Institutions (NANHRI)) ዋና ዳይሬክተር ጊልበርት ሰቢሆጎ (Gilbert Sebihogo) የሲቪክ ምኅዳርን ለማስፋት እና የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃን ለማጠናከር የመንግሥት ቁርጠኝነት እንዲሁም የኢሰመኮ እና የሲቪክ ማኅበረሰብ ድርጅቶች ትብብር ወሳኝ መሆኑን አስረድተዋል። የኢሰመኮ የሲቪል እና የፖለቲካ መብቶች ሥራ ክፍል ዳይሬክተር መቅደስ አመኑ የመደራጀት፣ሐሳብን በነጻነት የመግለጽ እና የመረጃ ነጻነት መብቶች መከበር የሲቪክ ምኅዳርን ለማስፋት እና የሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ጥበቃን ለማጠናከር ወሳኝ መሆኑን አንስተው የሲቪል ማኅበረብ ድርጅቶችን ጨምሮ ሁሉም ባለድርሻ ለተግባራዊነቱ በቅንጅት እንዲሠሩ ጥሪ አስተላልፈዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37584 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

#ሶማሊ፦ በአርብቶ አደር አካባቢዎች ትምህርት የማግኘት መብት አተገባበርን አስመልክቶ የተካሄደ ምክክር ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በሶማሊ ክልል በተመረጡ የአርብቶ አደር አካባቢዎች የትምህርት መብት አተገባበርን አስመልክቶ ባከናወነው የሰብአዊ መብቶች ክትትል የተለዩ ግኝቶች እና የተሰጡ ምክረ ሐሳቦች ላይ መጋቢት 29 ቀን 2018 ዓ.ም. በጅግጅጋ ከተማ ከባለድርሻ አካላት ጋር ምክክር አካሂዷል። በውይይቱ ከሶማሊ ክልል ትምህርት ቢሮ፣ መስኖና ቆላማ አካባቢዎች፣ ሴቶችና ሕፃናት፣ አደጋ ሥጋት አመራር ቢሮዎች እንዲሁም ከተለያዩ የወረዳ ትምህርት ጽሕፈት ቤቶች የተውጣጡ ተወካዮች ተሳትፈዋል። በመድረኩ ኢሰመኮ የትምህርት መብት በዓለም አቀፍና ሀገራዊ የሕግ ማዕቀፎች የተሰጠውን ጥበቃ ጨምሮ በአርብቶ አደር አካባቢዎች የመብቱ አተገባበር ላይ ባከናወነው ክትትል የተለዩ ግኝቶች ቀርበው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል። በውይይቱ በከፍተኛ ንፋስ ምክንያት ጉዳት የደረሰባቸው ትምህርት ቤቶችን መልሶ መገንባት እና የመሠረተ ልማት ዝርጋታን ማስፋፋት እንዲሁም የመምህራንን ዕውቀት እና ክህሎት ለማሳደግ ቀጣይነት ያለው ስልጠና መስጠት አስፈላጊ መሆኑ ተገልጿል። በተጨማሪም ተንቀሳቃሽ እና አዳሪ ትምህርት ቤቶችን ማስፋፋትን ጨምሮ ከአርብቶ አደሩ የኑሮ ዘይቤ ጋር የሚጣጣሙ የትምህርት ስልቶችን መቀየስ አጽንዖት ሊሰጠው እንደሚገባ ተመላክቷል፡፡ የውይይቱ ተሳታፊዎች አርብቶ አደሮች የሚገጥሟቸውን ተግዳሮቶች በዘላቂነት ለመፍታት በየደረጃው ያሉ የመንግሥት አካላት፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች እና ሌሎች የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በቅንጅት መሥራት እንዳለባቸው ገልጸዋል። የኢሰመኮ የማኅበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ መብቶች ሥራ ክፍል ኃላፊ ሃዊ አስፈው፣ በአርብቶ አደር አካባቢዎች የትምህርት መብትን ለማረጋገጥ ከማኅበረሰቡ የኑሮ ዘይቤ ጋር ማጣጣምና ተደራሽነቱን ማረጋገጥ ወሳኝ መሆኑን ገልጸዋል። አክለውም የመሠረተ ልማት ችግር እና ሌሎች ተግዳሮቶችን ለመቅረፍ ሁሉም ባለድርሻ አካላት የተቀናጀ ጥረት እንዲያደርጉና የመፍትሔ እርምጃዎችን እንዲወስዱ ጥሪ አቅርበዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37559 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

የአዳዲስ ኮሚሽነሮች የትውውቅ እና የመልካም ምኞት መግለጫ መርኃ ግብር ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በቅርቡ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የተሾሙለትን ምክትል ዋና ኮሚሽነር እና የዘርፍ ኮሚሽነሮች ከሠራተኞች እና ከአጋር አካላት ጋር የማስተዋወቂያ መርኃ ግብር ሚያዚያ 22 ቀን 2018 ዓ.ም. አዲስ አበባ በሚገኘው ዋና መሥሪያ ቤት አካሂዷል። በመርኃ ግብሩ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ እና አባላትን ጨምሮ የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል የኑስ ሙሉ፣ ጥሪ የተደረገላቸው አጋር አካላት እና የኢሰመኮ ሠራተኞች ተገኝተዋል። በመርኃ ግብሩ ላይ የኢሰመኮ ምክትል ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ሚዛኔ አባተ፣ የሴቶች እና የሕፃናት መብቶች ኮሚሽነር አሸነፈች አበበ፣ የሰብአዊ መብቶች ትምህርት እና ስልጠና ኮሚሽነር በዳሳ ለሜሳ፣ እንዲሁም የአካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን መብቶች ኮሚሽነር አቶ መሀመድ አህመድ ዝርዝር የሙያ፣ የክህሎት እና የትምህርት መግለጫ ቀርቧል። ተሳታፊዎች በበኩላቸው በገለልተኛ አስመራጭ ኮሚቴ አማካኝነት ግልጽ የሆነ የሕዝብ ጥቆማና የመመልመያ ሂደትን ተከትሎ ለተሾሙ ኮሚሽነሮች ደስታቸውን ገልጸው ውጤታማ የሥራ ዘመን እንዲሆንላቸው መልካም ምኞታቸውን አስተላልፈዋል። በተጨማሪም በተባበሩት መንግሥታት የኢኮኖሚ፣ ማኅበራዊ እና ባህላዊ መብቶች ኮሚቴ (CESCR) እና በአፍሪካ የሕፃናት መብቶችና ደኅንነት የባለሙያዎች ኮሚቴ (ACERWC) አባልነት ተመርጠው ለሀገራቸውና ለኢሰመኮ ኩራት ለሆኑት የሥራ ባልደረቦች ዶ/ር አብዲ ጅብሪል እና አልባብ ተስፋዬ የእውቅና እና የእንኳን ደስ አላችሁ መርኃ ግብር ተከናውኗል። የፌዴራል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን ኮሚሽነር ጀነራል የኑስ ሙሉ ክፍት የነበሩ የአመራር ቦታዎች ዘርፉን በአግባቡ በሚረዱ ባለሙያዎች መሞላታቸው ኢሰመኮ በተሟላ ዐቅሙ ተቋማዊ ተልዕኮውን እንዲወጣ ያስችለዋል ብለዋል። አክለውም የሰብአዊ መብቶችን የማክበርና የማስከበር ሥራ በአንድ ተቋም ብቻ የሚሳካ ባለመሆኑ፣ በማረሚያ ቤት የሚገኙ ሰዎችን መብቶች በተሟላ ሁኔታ ለማረጋገጥ ከኢሰመኮ ጋር በቅርበት እንደሚሠሩ ጠቁመዋል። የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የዴሞክራሲ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ የተከበሩ አቶ እውነቱ አለነ፣ ተሿሚዎቹ መስፈርቱን ካሟሉ 72 ዕጩዎች መካከል በከፍተኛ ውድድር እንደተመረጡ አስረድተዋል። የሰብአዊ መብቶችን መጠበቅ እና ማስፋፋት “ለራሳችን ስንል የምንሠራው ሥራ ነው” ያሉት ሰብሳቢው፤ ምክር ቤቱ የኢሰመኮን ተቋማዊ ነጻነት እና ገለልተኝነት ጠብቆ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ገልጸዋል። ተሿሚዎቹም የሕዝብ እና የመንግሥትን አደራ በሕግ እና በመርሕ ላይ በመጽናት እንዲወጡ አሳስበዋል። የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ብርሃኑ አዴሎ አብዛኛዎቹ ተሿሚዎች በኢሰመኮ ውስጥ በተለያዩ ኃላፊነቶች ሲያገለግሉ የነበሩ መሆናቸው ለተቋሙ ተጨማሪ ዐቅም እንደሚፈጥር ገልጸዋል። ይህም ተቋሙ በሰብአዊ መብቶች ዘርፍ ለበርካታ አመራሮችና ባለሙያዎች መፍለቂያ እየሆነ መምጣቱን የሚያሳይ ተስፋ ሰጪ እርምጃ መሆኑን ጠቅሰዋል። ዋና ኮሚሽነሩ አክለውም፤ በሥራ ዘመናቸው ኢሰመኮ ነጻነቱን ጠብቆ፣ የሰብአዊ መብቶች ማስከበር ተግባሩ ተጠናክሮ እና የሚሰጣቸው ምክረ ሐሳቦች ተፈጻሚነት ተሻሽሎ ማየት ዋነኛ ዓላማቸው መሆኑን ገልጸው፣ ተሿሚ ኮሚሽነሮች ይህንን እውን ለማድረግ የሚጠበቅባቸውን ኃላፊነት እንዲወጡ መክረዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37496 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

ሰብአዊ መብቶችን ማስፋፋት:- በ2018 በጀት ዓመት በ3ኛው ሩብ ዓመት የተሰጡ ስልጠናዎች ... የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከጥር 1 ቀን 2018 ዓ.ም. እስከ መጋቢት 30 ቀን 2018 ዓ.ም. ባለው የበጀት ዓመቱ 3ኛ ሩብ ዓመት በሰብአዊ መብቶች እና በሽግግር ፍትሕ ላይ ያተኮሩ ተከታታይ የአሰልጣኞች ስልጠናዎችን በተለያዩ ከተሞች ሰጥቷል። የአረጋውያን ሰብአዊ መብቶች እንዲሁም መብቶቹን ለማስከበርና ለማስፋፋት የሚያስችሉ ክህሎቶችን በተመለከተ ከየካቲት 2 እስከ 6 ቀን 2018 ዓ.ም. ከሲዳማ እና ከደቡብ ኢትዮጵያ ክልሎች ለተውጣጡ የአረጋውያን እና የጡረተኞች ማኅበራት አመራሮችና አባላት በሃዋሳ እና በአርባ ምንጭ ከተሞች፤ ከመጋቢት 14 እስከ 17 ቀን 2018 ዓ.ም. ለትግራይ አረጋውያን ማኅበር አባላት በመቀሌ ከተማ፤ እንዲሁም ከመጋቢት 21 እስከ 24 ቀን 2018 ዓ.ም. ለሐረሪ ክልል አረጋውያን እና ጡረተኞች ማኅበራት አባላት በሐረር ከተማ ስልጠናዎች ተሰጥተዋል። ስልጠናዎቹ የስልጠናው ተሳታፊዎች አረጋውያን ላይ የሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶችን ሪፖርት እና ውትወታ የማድረግ ክህሎታቸውን እንዲያዳብሩ የሚያስችሉ ተግባራዊ ልምምዶችን ያካተቱ ናቸው። በተጨማሪም ኢሰመኮ በሕፃናት መብቶች ጥበቃ ዙሪያ ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፖሊስ አባላት እና የሥራ ኃላፊዎች ከየካቲት 10 እስከ 13 ቀን 2018 ዓ.ም. በቢሾፍቱ ከተማ ስልጠና ሰጥቷል። ይህ ስልጠና ሕፃናት በወንጀል ድርጊት ተሳታፊ ወይም ተጎጂ በሚሆኑበት ጊዜ ሊከበሩላቸው የሚገቡ መብቶችን በተመለከተ በስልጠናው የተሳተፉ አካላትን ግንዛቤ ለማሳደግ ያለመ ሲሆን፣ ተሳታፊዎች በቡድን ውይይት አማካኝነት ልምድ ተለዋውጠዋል። በሌላ በኩል፣ ከባሌ ዞን እና ከሮቤ ከተማ የሴቶች እና የሕፃናት ጽሕፈት ቤቶች ለተውጣጡ ባለሙያዎች ከየካቲት 30 እስከ መጋቢት 4 ቀን 2018 ዓ.ም. የሴቶች መብቶች ላይ ያተኮረ ስልጠና በሮቤ ከተማ ተሰጥቷል። የታራሚዎችን አያያዝ በተመለከተ፣ ከማእከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተለያዩ ማረሚያ ቤቶች እና ከፍትሕ ቢሮ ለተውጣጡ የሥራ ኃላፊዎች ከየካቲት 9 እስከ 13 ቀን 2018 ዓ.ም. በሆሳዕና ከተማ፤ እንዲሁም ከአማራ ክልል ማረሚያ ቤት ኮሚሽን እና ከስድስት ማረሚያ ቤቶች ለተውጣጡ የማረሚያ ቤት ፖሊስ አባላት ከመጋቢት 21 እስከ 25 ቀን 2018 ዓ.ም. በባሕር ዳር እና ኮምቦልቻ ከተሞች ስልጠና ተሰጥቷል። በተጨማሪም የፖሊስ አባላት ሰብአዊ መብቶችን የማክበርና የማስከበር ዐቅም ለመገንባት ያለመ ስልጠና በወንጀል መከላከልና ምርመራ ዘርፍ ለተሰማሩ የፖሊስ አባላት ከየካቲት 9 እስከ 13 ቀን 2018 ዓ.ም. በሆሳዕና ከተማ፤ ከየካቲት 16 እስከ 20 ቀን 2018 ዓ.ም. በደሴ ከተማ እና ከመጋቢት 14 እስከ 17 ቀን 2018 ዓ.ም. በቢሾፍቱ ከተማ ስልጠናዎች ተሰጥተዋል። ስልጠናዎቹ የታራሚዎች እና ተጠርጣሪዎች ሰብአዊ መብቶች አያያዝን በተመለከተ ዕውቀት፣ አመለካከት እና ክህሎትን ለመገንባት የሚያግዙ ናቸው። በሌላ በኩል ኢሰመኮ በሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች መብቶች ዙሪያ ከሐረሪ እና ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልሎች የተውጣጡ ለሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች አገልግሎት ለሚሰጡ ተቋማት የሥራ ኃላፊዎች ከየካቲት 30 እስከ መጋቢት 4 ቀን 2018 ዓ.ም. በሐረር እና በአሶሳ ከተሞች ስልጠና ሰጥቷል፡፡ የስልጠናው ተሳታፊዎችም በስልጠናው ያገኙትን የሰብአዊ መብቶች ዕውቀት፣ እና ክህሎት በመጠቀም ተግባራዊ እርምጃ ለመውሰድ ያላቸውን ተነሳሽነት ገልጸዋል፡፡   በሌላ በኩል ኢሰመኮ ከፕሮጀክት ኤክስፒዳይት ጀስቲስ (Project Expedite Justice) ጋር በመተባበር የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጀቶች በሽግግር ፍትሕ ሂደት ውስጥ ያላቸውን ሚና እንዲወጡ ለማስቻልና የሽግግር ፍትሕ ሂደትን ለማጠናከር ከአማራ ክልል ለተውጣጡ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ከጥር 4 እስከ 8 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዳማ ከተማ ስልጠና ሰጥቷል። በተመሳሳይ የኪነ ጥበብ እና ሥነ ጥበብ ባለሙያዎች በሽግግር ፍትሕ ትግበራ ወቅት ያላቸውን ሚና በተመለከተ ከድሬዳዋ እና ከሐረር ለተውጣጡ ባለሙያዎች ከጥር 26 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም. በድሬዳዋ፣ እንዲሁም ከጅማ እና ከአጋሮ ለተውጣጡ ባለሙያዎች ከየካቲት 16 እስከ 20 ቀን 2018 ዓ.ም. ስልጠናዎች ተሰጥተዋል። በተጨማሪም በሰብአዊ መብቶች እና በሽግግር ፍትሕ ዙሪያ የወጣቶችን ሚና ለማሳደግ ቀደም ሲል የአሰልጣኞች ስልጠና የወሰዱ የሶዶ ከተማ የወጣቶች ማኅበራት አመራሮች፣ ከጥር 28 እስከ 30 ቀን 2018 ዓ.ም. ለ40 አባላቶቻቸው በሶዶ ከተማ ስልጠና ሰጥተዋል፡፡ ኢሰመኮ የሰብአዊ መብቶች እሴቶች እና መርሖች እንዲሁም ዓለም አቀፍ እና ሀገራዊ የአካል ጉዳተኞች መብቶችን በተመለከተ ከመጋቢት 22 እስከ 24 ቀን 2018 ዓ.ም. ለአካል ጉዳተኞች ማኅበራት አመራሮች እና አባላት በጋምቤላ ከተማ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ሰጥቷል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37391 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።

6ኛው ዓመታዊ ሀገር አቀፍ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የሰብአዊ መብቶች ምስለ-ችሎት (Human Rights Moot Court) ውድድር ተጠናቀቀ ... በኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) አዘጋጅነት ሲካሄድ የነበረው 6ኛው ዓመታዊ ሀገር አቀፍ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የሰብአዊ መብቶች ምስለ-ችሎት (6th National High Schools Human Rights Moot Court Competition) ውድድር ሚያዝያ 16 ቀን 2018 ዓ.ም. በአዲስ አበባ በተካሄደ የፍጻሜ ውድድር ተጠናቋል፡፡ ውድድሩ ከጥር 23 ቀን 2018 ዓ.ም. ጀምሮ በክልሎች እና በሀገር አቀፍ ደረጃ ሲካሄድ የቆየ ሲሆን በ12 ክልሎች እና 2 ከተማ አስተዳደሮች ከሚገኙ 91 ትምህርት ቤቶች የተውጣጡ 182 ተወዳዳሪ ተማሪዎች ተሳትፈውበታል። በክልሎች እና በከተማ አስተዳደር ደረጃ በተካሄደው የምስለ ችሎት ውድድር ከፍተኛ ነጥብ ያስመዘገቡ 8 ቡድኖች ወደ አዲስ አበባ ከተማ በመምጣት የሩብ እና የግማሽ ፍጻሜ ሀገር አቀፍ የቃል ክርክር ውድድር ከሚያዝያ 12 እስከ 16 ቀን 2018 ዓ.ም. ሲያደርጉ ቆይተው የፍጻሜ ውድድር አድርገዋል፡፡ በፍጻሜ ውድድሩ ተማሪ መርስን ተፈራ እና ተማሪ ቦንቱ ታደሰ ከአዲስ አበባ ከተማ እቴጌ መነን የሴቶች አዳሪ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እንዲሁም ተማሪ ይዲድያ ብሩክ እና አናቤል ነብዩ ከደብረብርሃን ከተማ ሀይሌ ማናስ አካዳሚ አመልካችና ተጠሪን ወክለው የቃል ክርክራቸውን አካሂደዋል። በዚሁ መሠረት:- ተማሪ መርሰን ተፈራ እና ቦንቱ ታደሰ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እቴጌ መነን የሴቶች አዳሪ ትምህርት ቤት የፍጻሜ ውድድሩ አሸናፊዎች ሆነዋል፡፡ ተማሪ አናቤል ነብዩ ከደብረብርሃን ከተማ ሀይሌ ማናስ አካዳሚ የውድድሩ ምርጥ የቃል ተከራካሪ በመሆን ያሸነፈች ሲሆን፤ ተማሪ ኪብሮን ነጻነት እና ተማሪ ዲኒያ ናስር ከሸገር ከተማ ሒል ቶፕስ አካዳሚ በምርጥ የጽሑፍ ክርክር አሸናፊዎች ሆነዋል፡፡ የዘንድሮው ውድድር ምናባዊ ጉዳይ ትኩረቱን ያደረገው “የመማር መብት በግጭት ዐውድ ውስጥ” (The Right   to Education in the Context of Armed Conflict) ላይ ሲሆን፣ የትምህርት መብትን በተለይም የትምህርት ተገኝነትን (availability) ተደራሽነትን (accessibility)፣ ተቀባይነትን (acceptability) እና ተላማጅነትን (adaptability)፤ በግጭት ዐወድ ውስጥ የትምህርት መብት መርሖችን እንዲሁም የትምህርት መብትን ከማክበር፣ ማስከበር እና ማሟላት አኳያ የመንግሥት መሠረታዊ ግዴታዎችን የተመለከቱ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ የሰብአዊ መብቶች መመዘኛዎች ላይ ተመሥርቷል።  ይህም በግጭት ዐውድ ውስጥ የትምህርት ቀጣይነትን የተመለከቱ የሰብአዊ መብቶች መመዘኛዎችን በማንሳት ተወዳዳሪ ተማሪዎች በመብቶቹ ዙሪያ ጥልቅ ውይይትና ንባብ እንዲያደርጉ እና ዕውቀት እንዲያካብቱ አጋጣሚ ፈጥሯል። የምስለ ችሎት ውድድሩ በሕግና ሰብአዊ መብቶች ባለሙያዎች የተዳኘ እና የመደበኛ ፍርድ ቤት ክርክር ሥርዓትን የተከተለ ሲሆን፤ ተወዳዳሪ ተማሪዎች ተገቢው ገለጻና አጭር ስልጠና ከተሰጣቸው በኋላ ለውድድሩ በተመረጠው ምናባዊ የሰብአዊ መብቶች ጉዳይ (hypothetical case) ላይ አመልካች እና ተጠሪን በመወከል የጽሑፍ እና የቃል ክርክር ያደረጉበትም ነው። በዚህ የፍጻሜ ውድድር ላይ የኢሰመኮ ኮሚሽነሮችን ጨምሮ ጥሪ የተደረገላቸው ከፍተኛ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎች፣ የክልል ትምህርት ቢሮዎች ተወካዮች፣ መንግሥታዊ እና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተወካዮች፣ የተወዳዳሪ ተማሪዎች ቤተሰቦች እንዲሁም ተማሪዎች ተገኝተዋል፡፡ የኢሰመኮ ምክትል ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ሚዛኔ አባተ ኢሰመኮ የወጣቶችን የሰብአዊ መብቶች ግንዛቤና ክህሎት ለማሰደግ እንዲሁም አመለካከት ለመቀየር ከሚጠቀምባቸው ስልቶች መካከል የምስለ ችሎት ውድድር አንዱ መሆኑን ጠቅሰው፣ በግጭት ዐውድ ውስጥ የትምህርት ቀጣይነትን ማረጋገጥ ሀገር ተረካቢ ትውልድ በመፍጠር ሀገራት ከግጭት ዐውድ ውስጥና ከሰብአዊ መብቶች ጥሰተቶች አዙሪት ሊወጡ የሚችሉበት የተሻለ አማራጭ መሆኑን ተረድተው፣ ይህንኑ በውድድሩ የተለያዩ ዙሮች ላይ ለተሳተፉ ተማሪዎች፣ የትምህርት ቤት ማኅበረሰብ አባላት፣ ወላጆች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ማስገንዘብ እንደቻሉ ገልጸዋል። አክለውም “6ኛው ሀገር አቀፍ የሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች የሰብአዊ መብቶች ምስለ ችሎት ውድድር ወቅታዊ እና ሀገራዊ የሰብአዊ መብቶች አጀንዳዎችን ተገንዘቦ አስተዋጽዖ የማድረግ ዐቅም ያለው ትውልድ በማፍራት ሰብአዊ መብቶች ባህል የሆኑባት ኢትዮጵያን እውን ማድረግ እንድንችል ዕድል የሠጠን ነው” ብለዋል። 🔗 https://ehrc.org/?p=37324 #Ethiopia🇪🇹 #HumanRightsForAll #mootcourt በነጻ የስልክ መስመራችን 7307 ላይ በመደወል የሰብአዊ መብቶች ጥሰት አቤቱታ ማቅረብ ወይም ጥቆማ መስጠት ይችላሉ።