አብርሃም ፍቅሬ (የቅዳስ ልጅ)
رفتن به کانال در Telegram
2 402
مشترکین
اطلاعاتی وجود ندارد24 ساعت
-37 روز
-4030 روز
آرشیو پست ها
2 402
Repost from N/a
2 402
ጓደኛዬ ከሀብታሞች መለስ ከደሀዎች ቀለስ የምትል ከወሽመጧ ጠበብ ብላ ሶስት በሰውነታቸው ጠጪውን የሚያጣብቡ ጋርዶች ባሉበት መሸታ ቤት ውስጥ ሁለት ቢራ ጋብዞ እንዲህ ሲል አበረታታኝ።
"ይኸውልህ አብሬ አንተ እምቅ አቅም አለህ...እምቅ አቅም...ቲክ ቶክ ክፈት"!
ወድያው እኔም ተወጣጥሬ ከፈትኩ ከፍቼም አልቀረሁ ፎቶዬን በዘፈን አቀናብሬ ለጠፍኩ...። ይሄ እስኪሆን ስድስተኛ ቢራ ላይ ነበርኩ።
አንድ ሰው ነው ቪዲዮውን ያየው... እሱም እንዲህ አለና ኮመተ "ሄዋንን ያሳታትን እባብ በትንሳኤው ቀን አየሁ የአለም መጨረሻ ደረሰ" ወሽመጤ ሰባት ቦታ ተከፈለ። ሞቅታዬ ሁሉ ጠፋ። ሞቅታ ነበረ ስካር?....ብቻ መካሪ ጓደኛዬን ካቀረቀርኩበት ስልኬ ቀና ብዬ ፈለኩት። ከአንዷ ጋር ይደንሳል። እሷ ትስቃለች... እሱ በርሃ ላይ ጊንጥ ያስደነበራት ግመል ይመስል በሀይል እየተቀነጣጠሰ ይውረገረጋል። በሳቀች ቁጥር ያበረታታችው እየመሰለው መውረግረጉንና መቀነጣጠሱን በአምስት እጥፍ ያህል ከፍ አደረገው። መቼም ወንድ የሴት ጥርስ አይከፈትለት...የገነት በር ተከፍቶ በደስታ እየዘለልክ ግባ ተብሎ የሚዘል ይመስል ሰው ሁሉ እንዳበደ ይመለከተው ጀመር። 'ይሄ ጊንጥ... እኔን እምቅ ችሎታ አለህ ብሎ ጉድ ይስራኝ። እኔማ ተውም አልለው ይዋረዳት።ምን አገባኝ' ብዬ በውስጤ ዝም ብዬ ማየት ጀመርኩ። ቆየት ብሎ የቤቱ ጋርድ መጣና "ብራዘር...ጀለስህን አረጋጋው የዳንስ ወለሉን እኮ ብቻውን አጨናነቀው።" ብሎ በደረቱ አጨናንቆኝ ሄደ። ለሀጣን የመጣ ለፃድቃን ይተርፋል ነውና ነገሩ
"አንተ ወረታው... አንተ ወረታው ...ወረታው...ወሬ...ና ቁጭ በል" ብዬ ከልጅቷ አላቀኩት። በስካር አንደበቱ "እሙዬ...የኔ እናት..ሌላ ግዜም እምቅ ችሎታዬን አሳይሻለሁ...ተመችቻታለሁ እኮ" እያለ ስልኳን ተቀብሎ ተቀመጠ። እንደተቀመጠ ስልኬን አዙሬ "እምቅ ችሎታ አለህ ብለህ የሰራኸኝን አየኸው?" አልኩት ቆጣ ብዬ
" ፐ...." አለኝ
"ፐ!....ምንድነው ፐ?" አልኩት
"አብርዬ የምር ደስ ብሎኛል።አካውንትህ ሊተኮስ ነው" አለ ጮክ ብሎ... የተኩስ ነገር ያሳሰባቸውና... አካውንት ሲባል ገንዘብ የሚያባንናቸው ገልመጥ ገልመጥ አድርገው ወደ ወንበራችን ተመለከቱ። ጋርዱ ድጋሚ ጠጋ አለኝና " ጀለስህን አረጋጋው....ፖለቲካ ማውራት አይቻልም።" ብሎ ሁለተኛ አስጠነቀቀኝና ዞር አለ።
"ወረታው ድምፅ ቀንስ.... " አልኩት
"ለምን ብዬ በሀገሬ....አንተም በአንድ ጡንቻ ራስ እባብ መባልን..."
"...ኧረ ወረታው በማርያም ዝምበል" ብዬ ተማፀንኩት
"አብርዬ ሙት....እደግመዋለሁ ...በአንድ ጡንቻ ራስ ኮመንት እባብ መባል ከብረት የጠነከረ አለት ሊያደርግህ ይገባል እንጂ አያስደንብርህ። አብርሽ አለት ነህ....የምር አለት ነህ" ብሎ ጠረጴዛውን በኃይል ደቃው
ጋርዱን ሸረፍ አድርጌ እያየሁት " ወረታው....አዎ አለት ነኝ በቃ....ስለ እምቅ ችሎታችንም ውጪ እንመክርበታለን...ጠጣ ዝም ብለህ.." ጋርዱ ትዕግስቱን እንደጨረሰ ያስታውቃል
" ምክክር .... ወይ ምክክር.... ይሄሄሄ አሁን እራሱ ምክክር ብለው ሊመካከሩ የገቡት ሁላ ስድስቱ ይሄኔ እየተጣሉ ነው። ምንም ምክክር አያስፈልግም...እንደ ሀገር" ጋርዱ መጣና "ኑ እስቲ ውጪ እናውራ" አለ
"ወንድሜ እዚህ ብናወራስ..." አልኩት
ወረታው ከእኔም ከጋርዱም አፍ ቀድሞ "ምንድነው ኧ ፀብ ነው?...እንደ አለት የጠነከርን መሆናችንን አላወቀ። ና ውጣለት..…የወንዱ ልጅ" ብሎ ቀድሞ ወጣ። እኔም ተከተልኩ።
እንግዲህ ይሄን ፅሁፍ ስከትብ 'አለቶቹ' እኔና ወረታው ጥቁር አንበሳ ሆስፒታል በአንድ ክፍል ጎን ለጎን ተኝተን መሆኑ እንዳይረሳ።
Abrham F. Yekedas
@HAKiKA1
2 402
እንዴት እንደዚህ አይነት መዘፈቅ ውስጥ እንደገባሁ አላውቅም። ተገናኝተን እንደተለያየን 'ከዚህ በኃላ ይሄን ነገር አቆማለሁ' እያልኩ ለራሴ መሀላ እንደደረደርኩ ነው።ሳገኘው ግን ሁሉም ነገር በእኔ ብሶ ቁጭ ይላል። ማህሌት እንዲህ
አይነት ሁኔታ ውስጥ ትገባለች ብሎ ማን ያስባል? እንኳን ሌላ ሰው እኔም አላስበውም ነበር። የጠሉት ይወርሳል ሆነና መገኘት ያልፈለኩበት ላይ ተገኘሁ።
አብረን ተኝተን እያለ ስልኩ ጮኸ እያቀበልኩት ጥሪውን ስመለከት "ሚስቴ" ይላል። ማቀበሌን ትቼ ቀዩን ተጭኜ ዘጋሁት።
"ያምሻል እንዴ..." ብሎ በቁጣ ስልኩን ከእጄ ወሰደው። እንደተናደደ "ሳታውቂ የገባሽበት አታስመስይ..." እያለ ድጋሚ ለሚስቱ ሊደውል ስልኩን መነካካት ጀመረ። ቃል ሳላወጣ ተነስቼ መታጠቢያ ቤት ገባሁ። ሻወሩን እስከመጨረሻው ከፍቼ ውሀ ውስጥ ተንሰቅስቄ አለቀስኩ። ያቺ ሀይማኖተኛዋ፣ ትጉዋ፣ በራሷ የምትተማመነዋ፣ ከአቋሟ ዝንፍ የማትለዋ፣ ለክብሯ የማትደራደረዋ ማህሌት በየት ቅያስ አምልጣኝ ዛሬ እዚህ ጋ እንዴት እንደቆምኩ አላውቅም። ሰውነቴን ተጠየፍኩት።
በሴክረተሪ ተመርቄ በአንድ ድርጅት ስራ ስቀጠር የድርጅቱ ስራ አስኪያጅ እሱ ነበር። "ኦ አንቺ ነሽ ፀሀፊያችን Welcome welcome...አሮን እባላለሁ" ብሎ ተዋወቀኝ.....ምኑም ደስ ይላል ቁመቱ፣ አለባበሱ፣ ሳቁ፣ ጨዋታ አዋቂነቱ... እንዲህ እያልኩ ብዘረዝርም አይበቃውም። የድርጅቶቹ ባለቤቶች እሱን በሚሰራበት ቦታ ላይ ለማስቀጠል ሲሽቆጠቆጡለት ሳይ ደግሞ ምን ያክል ቁልፍ ሰው እንደሆነ ለመረዳት ቀላል ነበር። በኃላ ስሰማ መኪና እራሱ በስጦታ አበርክተውለታል። በአጠቃላይ የታደለ ነው። ከስራ ወጥቼ መንገድ ላይ "ፀሀፊያችን ግቢ እንጂ..." ብሎ መኪናውን አቆመልኝ ገባሁ።
"ስምሽን አልነገርሽኝም ወይስ ፀሀፊያችን እያልኩ ልቀጥል?" ሳቀ...እየሳቅኩኝ "ማህሌት..." ብዬ እራሴን አስተዋወኩ
"ኧረ ባክሽ... የባለቤቴም ስም ማህሌት ነው። ግን ሚስቴ ቆንጆ ናት " ሳቀ። ምን ማለት እንዳለብኝ ግራ ገባኝና ዝም ስል "አንቺም ቆንጆ ነሽ ስቀልድ ነው" ደግሞ ሳቀ...እየተሽኮረመምኩ ሳቅኩ (በህይወቴ ለመጀመሪያ ግዜ ተሽኮረመምኩ).... የግራ እጅ ጣቱ ላይ ቀለበቱን ለማየት መሪው ከለለኝ። ሸኝቶኝ ከመኪናው ስወርድም ጣቱ በግልፅ ሊታየኝ አልቻለም "እስቲ እጅህን" አልለው ነገር... ጠዋት ቢሮ ስገባ የመጀመሪያ ስራዬ የሆነው ጣቱን ማየት ነበር። ጣቶቹ ዘለግ ብለው ያምራሉ። ያደረገው ቀለበት ጣቱ ላይ ይበልጥ ያምራል። ምንም ነገሩ ላይ ውበት አለ። ከቢሮው ወጣሁ 'ትዳር እንዳለው አወቅሽ አይደል? ምን ይፈጠር ነው የምትይው ፈጣጣ አትሁኚ ማህሌት' እራሴን ወቀስኩ
በሶስተኛ ወር ከንፈሩን ሳምኩት ቢሮ ውስጥ.... ከዛ ሁለታችንም ተፋፈርን። እኔ ስለገፋፋሁት ደሞ ይበልጥ አፈርኩ። በሌላኛው ቀን እሱ ሳመኝ። መሳሳም ኖርማል ሆነ። በ አምስተኛ ወር room ያዝን።ሁኔታችን የእብደት ይመስል ነበር። ደጋገምነው። ከሆነ በኃላ እሱም እኔም እንፀፀታለን ማቆም ግን አልቻልንም። ሁለት ዓመት ይሄ ነገር ቀጠለ ሚስቱን ይወዳታል። ከእሷ ሁለት ልጆች አሉት። እኔን እንዴት እንደሚመለከተኝ አላውቅም.….ብቻ...
ፎጣ ጣል አድርጌ ከሻወር ወጣሁ ልብሱን ለባብሷል ሱፍ ያዘወትራል ተጠጋሁትና ባሏን ወደስራ እንደምትሸኝ ሚስት ከረቫቱን አስተካከልኩለት..…"ቢቀርብንስ" አለኝ። ለ መቶኛ ግዜ እንዲህ ሲለኝ
እኔም ለመቶኛ ጊዜ "ከዚህ በኃላ አይደገምም" አልኩት። ልብሴን ለባብሼ ቤት አድርሶኝ ወደቤቱ ሄደ።
በቀጣይ ቀን ቢሮ ተገናኘን...እንደተነፋፈቅን በዓይናችን አወራን... በድብቅ የምንገናኝበት ቦታ እንድንገናኝ በዓይናችን ተነጋገርን። ተገናኘን ድጋሚ ወደቅን...አበድን። ምን አይነት ሴጣን መሀላችን እንደገባ አላውቅም። ይሄ ሰይጣን ነው እንጂ ሰው እንዴት እንዲ ይሆናል?
#ሰይጣን:- "አልቀረብሽም....ምን አባሽ ላድርግሽ ስሜን እንዳትጠሪ። አሁንስ አልበዛም እንዴ... እዛው በፀበላችሁ...ሰበበኛ"
Abrham F. Yekedas
2 402
የቀሬናው ስምዖን ድንገት በመንገዱ
ከክፉ ቀን ግማሽ ከደግ ቀን በአንዱ
ሄዶ ተረማምዶ መንገዱን ሳይጨርስ
ተብሎ ተጎተተ "ና... ይሄን ሰው አግዝ"
አቅማምቶ ተጠጋ
ከአንድ ምስኪን ገላ ደም ከለዋወሰው
በአዳናቸው ሳይሆን
በሚገርፉት ብቻ በተከበበ ሰው
ግማደ መስቀሉን
እንደቻለው አቅም አብሮ ተሸክሞ
ከባለ ፍዳው ጋር
ገፍቶ ያንን ዳገት... ወጣ ቀራንዮ
ተመልከት
እንዲ ነው አንዳዴ የህይወት ጎዳና
የግድ ተጎትተህ
ድንገት ከመከራው ገፈት ትቀምስና
ካሰብከው ዘግየተክ
ከአለምከው አርፍደህ መድረሻህ ይርቃል
ለፅድቅ መታጨትን
አንተ አትረዳውም የእግዜር ልብ ግን ያውቃል።
እንግዲህ
ለባለ መንገዱ ለቀሬናው ስምዖን
በገጠመው ሲሳይ በስቃይ እንዲያ መሆን
ምን ይሆን ምላሹ ለዚህ ኩነት ምንዳ?
አምላኩን ለረዳ...
Abrham F. Yekedas
@HAKiKA1
2 402
2 402
እንዲ ነበር እንዴ? የእሷነቷ ፊደል
ውስጥ ሀሳቧ ሁሉ ያውቅ ነበር ወይ በደል
እንዲ ነበር እንዴ? ስቀምሰው የእሷ ጣ'ም
(... ገረመቺኝ በጣም)
ከሰቀልኳት ሰማይ አራሷን ፈጥፍጣ
ከውሸቷ ጭብጥ እውነት ተፈልቅቃ
እንዳላሰብን በፍቅር የነገን ጎዳና
እንዳላወጋነው ስንቱን ቀና ቀና
እንዳልታየን ሁሉ የተስፋችን ፋና
ዛሬ ሲሆን ባዶ ደርሶ ሲሆን ወና
ነገሯ ሲገባኝ.....
ከቅኔ ህብረቃል ሰም ወርቋ ሲረዳኝ
እኔና እሷ ብዬ ስንቱን እያሰብኩኝ
ልብ ልቧን ታይቶኝ
እጅግ ተደንቄ ታዝቤያት አበድኩኝ።
Abrham F. Yekedas
@HAKiKA1
2 402
አሁን በቀደም ለት
ማጣት አስከፍቶኝ
ጭምት ትክዝ አርጎ
ከጎዳና ጥሎኝ...
አላፊ አግዳሚውን
ቁጭ ብዬ እየታዘብኩ
አልፎ አልፎ ሲበላኝ
ጀርባዬን እያከኩ
እንደተኮራመትኩ
በተቀመጥኩበት
ደስታ ባጣ አርኪ
ሀዘን እንደገባኝ
ፊቴ መጣ ድንገት ልጅ እግር ሰባኪ
አቋሙን በሚያስንቅ
በአስገምጋሚ ድምፁ
ፀሀይ በዋለበት
በጠቆረ ገፁ
መንፈሳዊ ሞራል
ባጀገነው አቅም
"ገንዘብ ደስታ አይገዛም
ንዋይ አያስቅም፤
አታልቅስ በችግር
አትሳቅ በጥቅም!"
ብሎ አዥጎደጎደው
ሰበካውን ሁሉ በቆንጆ ቆንጆ ቃል፤
ሰማሁ ሰማሁና
እኔ ምርር ብሎኝ
ጮሄ ተናገርኩኝ የራሴን አባባል...
"ስሙኝ ወገኖቼ
ከፊሉ ስህተት ነው የዚህ ሰባኪ ቃል፤
በመኖር ኡደት ውስጥ
ህይወት ተዘርቶበት
ሰው ለምድር ሲጣል፤
ገንዘብ ደስታ አይገዛም
ነገር ግን...ማጣት ደስታ የሳጣል።
አይጣል...
(ይሄ ነው እውነታው...)
(ስማኝ)
ቃሌ "እህ..." አስብሎ
ሰሚ ባገኝ ጆሮ
ተቸግሬም የሰው
ዓይን ባይርቀኝ ኖሮ
ስለሌለኝ ብስቅ
ማጣት ቢያስደስተኝ
እዚ ጎዳና ጥግ ምን አኮራመተኝ?
በዝምታ ልኑር
አሁን በቃ ተወኝ!
...ተወኝ"
Abrham F.Yekedas
@HAKiKA1
2 402
"ታውቂያለሽ? ለመጀመሪያ ግዜ ስመለከትሽ የወደድኩልሽ አይንሽን ነው" ፀጉሯን እየነካካሁ ስላት
"እኔ ደግሞ ፈለግህን..." አለችኝ።
"ፈለግ...ማለት ...?"
"ማለትማ የኔ ካጠገቤ ተቀምጠህ እኔ ጎንበስ ብዬ መፅሀፍ እያነበብኩ አልነበር። ወደአንተ ለማየት ዓይኔ ሂደቱን ሲጀምር ከማርያም ጣትህ ነበር፤እዛች ጣትህ ላይ ፈለግ ነበረች..ከጥፍርህ ስር ሆና ከጣትህ ህይወት ተነጥላ ገንጠል ያለች ልውደቅ አልውደቅ የምትል ፈለግ ከዛ ወደድኳትና አንተን ማየት ትቼ ብዕሬን አውጥቼ 'ፈለግ' የሚል ሶስት ገፅ ግጥም ፃፍኩ።"
"አይ በጣም ጎበዝ.... ያኔ ጨምድደሽ ስትጥይው ያቀበልኩሽ ወረቀት ስለፈለጌ የፃፍሽው ነው?"
" አዎ አንጓው አልጥም ስላለኝ ጣልኩትና ሌላ ጀመርኩ....አቀብለኸኝ በዛው ተግባባኸኝ....ነፍስህ ጥበባዊ ስለሆነ ደስ አልከኝ። ማን አጎንብሶ የወደቀ ያቀብላል?" ምን ማለት እንዳለብኝ ግራ ገብቶኝ... ዝም አልኩ።
"ቆይማ ላንብብልህ...?"
"ምን..?"
"ፈለግን ...."
"ፈለግ?...እ ግጥሙን አይ ይቅር እማ ተይ ..... ስንጋባ" ተማፀንኩ።
"ውይ ትንሽ እኮ ነው....አስፋፍቼው ስድስት ገፅ ሆኗል እንጂ..." ቦርሳዋን ከፍታ ቀይ አጀንዳዋን ብቅ አደረገችው። እንግዲህ የተቀመጥንበት ካፌ ሊበጠበጥ ነው።
"ተይ እማ....ሌላ ቀን ተይ....ይሄን ቀይ አጀንዳ መልሺው ....እያጥወለወለኝ ነው"
"አይ እንግዲህ አነብልሃለው... ።...የግጥሜ ርዕስ ፈለግ....
አንቺ የጣት ፈለግ ተበጠሽ ከጣቴ፤
ዝርፍፍ አትበዪ ከማርያሟ ጣቴ፤
ጥፊልኝ ከፊቴ....ከወጣትነቴ..."
''ወይኔ በላቸውውውው.... ምን ብበድል ነው ያንቺ መጫወቻ ያረገኝ።" ከገጣሚ ጋ መፋቀር ትርፉ ይሄ ይሁን በቃ?😒
Abrham F.Yekedas
@HAKiKA1
