es
Feedback
Jura Legal Update

Jura Legal Update

Ir al canal en Telegram

Official Telegram Channel of Jura Legal Update

Mostrar más
1 415
Suscriptores
Sin datos24 horas
+227 días
+9630 días
Archivo de publicaciones
በሕጻናት ቀለብ አወሳሰን መምሪያ ቁጥር 1/2016 የሕጻናት ወርሃዊ የቀለብ አወሳሰን የስሌት ሰንጠረዥ
በሕጻናት ቀለብ አወሳሰን መምሪያ ቁጥር 1/2016 የሕጻናት ወርሃዊ የቀለብ አወሳሰን የስሌት ሰንጠረዥ

የፈቃደኝነት ማረጋገጫ /Declaration of Consent/ የሚያካትታቸው ጉዳዮች እና ለአገልግሎቱ የሚስፈልጉ መስፈርቶች: የፈቃደኝነት ማረጋገጫ ሰነድን ይረጋገጥልኝ አገልግሎት ጥያቄ ከዚህ በታች በተገለጹትና እንደአስፈላጊነቱ በሌሎች ጉዳይች ላይም ተግባራዊ ሊደረግ ይችላል፡፡ በመሆኑም ጉዳዩ፦ 1) የሰውነት አካልን ለመለገስ ሲሆን ለጋሹ እንዲሁም የለጋሹ ፈቃድ ሰጪ ባል/ሚስት ወይም በማስረጃ ሊረጋገጥ የሚችል የሥጋ ዘመድ ፈቃደኛነታቸውን ለማረጋገጥ፣ 2) አካለ መጠን ያላደረሱ ልጆችን የተመለከተ ሲሆን የልጁ ወላጆች ወይም በፍ/ቤት ውሳኔ የሞግዚትነት ሥልጣን የተሰጠው ሰው ፈቃዱን ለማረጋገጥ፣ 3) ከኢትዮጵያ ውጪ የሞተን ሰው አስክሬን እንዲመጣ ወይም በሞተበት አገር ማስቀበርን የተመለከተ ሲሆን የሟች የሚመለከተው ባል/ሚስት ወይም በማስረጃ ሊረጋገጥ የሚችል የሥጋ ዘመድ ፈቃደኛነቱን ለማረጋገጥ፣ 4 ) በሸሪዓ ህግ መሠረት የጋብቻ ፍቃድን የተመለከተ ሲሆን የምታገባዋ ሴት አባት፣ አባት ከሌለ በማስረጃ ሊረጋገጥ የሚችል የሥጋ ዘመድ ፈቃደኛነቱን ለማረጋገጥ ሲባል ነው፡፡ የፍቃደኝነት መግለጫ /Declaration of Consent/ ሰነድ አረጋግጦ ለመመዝገብ መሟላት ያለባቸው መስፈርቶች፣ ሀ. በተቋሙ የአገልግሎት መስጫ ሲስተም ተሞልቶ የጉዳይ መከታተያ ቁጥር የያዘና እና በሕግ አግባብ የተዘጋጀ የፍቃደኝነት ማረጋገጫ ሰነድ መቅረቡን፣ ለ. የፈራሚው መታወቂያ መቅረቡን፣ ሐ. ፈራሚው ከህግ ወይም ከውል የመነጨ ስልጣን ያለው መሆኑን፣ መ. በማረጋገጫ ሰነዱ ውስጥ ማስረጃ የሚጠይቅ ፍሬ ነገር ካለ ይህንኑ የሚያስረዳ ዋና የማስረጃ …ሰነድ መቅረቡን፣ ሠ. ጉዳዩ የሰውነት አካልን ለመለገስ ከሆነ በለጋሹና በተቀባዩ እና በለጋሹና በፍቃድ ሰጪው መካከል ዝምድና መኖሩን እንዲሁም በሃኪሞች ቦርድ የተሰጠ ዋና የሕክምና ማስረጃ ሰነድ መቅረቡን፣ ረ. ጉዳዩ ለአካለ መጠን ያልደረሱ ልጆችን በተመለከተ ከሆነ በፍቃድ ሰጪውና በአካለ መጠን ባልደረሰው እንዲሁም በፍቃድ ተቀባዩና አካለ መጠን ባልደረሰው መካከል ዝምድና መኖሩን፣ ሰ. ጉዳዩ ከኢትዮጵያ ውጪ የሞተን ሰው አስክሬን ለማምጣት ወይም በሞተበት አገር …ማስቀበርን የተመለከተ ከሆነ በፍቃድ ሰጪውና በሟች መካከል ዝምድና መኖሩን፣ ሸ. ጉዳዩ የሸሪዓ ጋብቻ ፍቃድን የተመለከተ ከሆነ በፍቃድ ሰጪውና በምታገባዋ ሴት መካከል ..ዝምድና መኖሩን፣ ቀ. የተዘጋጀው የፈቃደኝነት ማረጋገጫ ይዘት ትክክለኛና እውነት ስለመሆኑ በቃለመሃላ የተደገፈ ..መሆኑን፣ ማጣራትና ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ #የሠነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት

photo content

በኢትዮጵያ የውርስ ሕግ ከጋብቻ ውጭ የተወለደ ልጅ (Child born out of wedlock) በጋብቻ ውስጥ ከተወለደ ልጅ (Child born of wedlock) ጋር እኩል የወራሽነት መብት አለው? ==================== በብዙ ማኅበረሰቦች ዘንድ በሚስተዋሉ ባሕላዊ እሴቶችና ልማዳዊ ድርጊቶች ውስጥ፣ ከጋብቻ ውጭ የተወለዱ ልጆች (Children born out of wedlock) በጋብቻ ውስጥ ከተወለዱ ልጆች (Children born of wedlock) እኩል ማኅበራዊ ተቀባይነት የማግኘት ዕድላቸው ውስን ነው። ይህ ዓይነቱ ማኅበራዊ መገለል (Social stigmatization) ልጆች ራሳቸው ፈቅደውና መርጠው ባልመጡበት ምድራዊ ሕይወት በማኅበረሰቡ ዘንድ ዝቅ ተደርጎ የመታየት፣ አግላይና አጉል ስሞች የመሰጠት እንዲሁም ያነሰ ማኅበራዊ ቦታ የመመደብ ተጽዕኖዎች እንዲያርፉባቸው ያደርጋል። ይህ አይነቱ ማኅበራዊ አድሎአዊ አመለካከት፣ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ የልጆችን ሕጋዊ መብቶችና ጥቅሞች አደጋ ላይ ሲጥል ይስተዋላል። ​በመሆኑም፣ ከሕግ ሙያ ውጪ ያለ ማንኛውም የኅብረተሰብ ክፍል፣ ይህ ዓይነቱ ልጅ ከውርስ አንጻር በሕግ ፊት ያለው መብት ምን እንደሆነ ማወቁ እጅግ አስፈላጊ ነው። ሕጉ በማኅበረሰቡ ውስጥ የሚስተዋለውን እንዲህ ያለውን አጉል አመለካከት እንዴት እንደሚያስተናግድ ግንዛቤ መኖሩ፣ ፍትሕን ለማስፈንና ሰብዓዊ መብትን ለማክበርና ለማስከበር ትልቅ መሠረት ይጥላል። ​የኢትዮጵያ የሕግ ሥርዓት ይህንን አይነት አድሎ ሙሉ በሙሉ ውድቅ በማድረግ፣ በማንኛውም ሁኔታ የተወለደ ልጅ በወላጆቹ የውርስ ሀብት ላይ እኩል መብት እንዳለው በሕግ በግልጽ ደንግጓል። የሀገሪቱ የበላይ ሕግ የሆነው የኢፌዲሪ ሕገ-መንግሥት ለማንኛውም ዓይነት አድሎአዊ አሠራር በር የሚዘጉ መሠረታዊ መርሆችን ያስቀመጠ ሲሆን፣ በተለይም ስለ ሕፃናት መብት በሚደነግገው በአንቀጽ 36 (4) ላይ "ከጋብቻ ውጭ የተወለዱ ሕፃናት በጋብቻ ከተወለዱ ሕፃናት ጋር እኩል መብት አላቸው" በማለት የእኩልነት መርህን በግልጽ አስፍሮታል። ​ይህ ድንጋጌ ከአንድ ወላጅ የተወለዱ ልጆች የትውልድ ሁኔታ (Status of birth) በውርስ መብትም ሆነ በማናቸውም ሕጋዊ መብቶቻቸው ላይ ልዩነት እንዳይፈጠር ሕገ-መንግሥታዊ ዋስትና ይሰጣል። የኢትዮጵያ የፍትሐብሔር ሕግ በውርስ ሕግ ክፍሉ ላይ በልጆች መካከል የወላጆቻቸው ወራሽ ለመሆን ምንም ዓይነት የደረጃ ወይም የድርሻ ልዩነት አላስቀመጠም። በፍትሐብሔር ሕግ አንቀጽ 842 መሠረት፣ የሟች ልጆች የመጀመሪያ ደረጃ ወራሾች ናቸው። ሕጉ በአንቀጽ 836 (1) ላይ በግልጽ እንደደነገገው በጋብቻ ውስጥ መወለድ ወይም አለመወለድ ወራሾችን ሆነ የእያንዳንዳቸውን የውርስ ድርሻ ልክ ለመወሰን ምንም ውጤት ወይም ዋጋ የለውም። ​በመሆኑም በሕግ ረገድ የሟች ልጅ መሆን ብቻውን መብቱን የሚያስገኝ እንጂ፣ ልጁ የተወለደበት የትዳር ሁኔታ በውርስ ድርሻው ላይ የሚያመጣው ምንም ዓይነት ልዩነት የለም። ሟች በሕጋዊ ኑዛዜ አማካኝነት የድርሻ ልዩነት ካላደረገ በስተቀር፣ ሁሉም ልጆች በሕግ በተወሰነው መሠረት በውርሱ ላይ እኩል ድርሻ አላቸው። ​ከጋብቻ ውጪ የተወለደ ልጅ ከሌሎቹ ልጆች እኩል የመውረስ መብቱን ለመጠቀም መሟላት ያለበት ብቸኛው ነገር ተወላጅነቱን (Filiation) በሕግ ፊት መረጋገጡ ብቻ ነው። ​አንዴ በሕግ ፊት ልጅነቱ ከተረጋገጠ በኋላ፣ በትዳር ውስጥ ከተወለደ እና ከትዳር ውጪ ከተወለደ ልጅ መካከል ምንም ዓይነት የቅድሚያ መብት ወይም የድርሻ ልዩነት ሳይደረግ እኩል የወራሽነት መብት ይኖራቸዋል። መልካም ቀን! ==================== ​ማስታወሻ፦ ይህ ጽሑፍ ለአጠቃላይ ግንዛቤ ብቻ የቀረበ ስለሆነ የባለሙያ ምክርን አይተካም። የሕግ ጉዳዮች እንደ ነባራዊ ሁኔታቸው ሊለያዩ ስለሚችሉ፣ ከተጨባጭ ጉዳይ ጋር የተያያዘ ዝርዝር የሕግ ምክር ለማግኘት ከባለሙያ ጋር መማከር አስፈላጊ ነው። ==================== Jura Legal Update ሰኔ 02 ቀን 2018 ዓ.ም አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ ቴሌግራም: https://t.me/JuraLegalUpdate ፌስቡክ:https://www.facebook.com/share/1c2WCxGTV7/

photo content

የሕግ መሻር (Repeal of Laws)፡ ምንነት፣ አይነቶች እና ውጤቶች አንድ ሕግ በሕግ አውጪው አካል ወይም ሕግ እንዲያወጣ ውክልና በተሰጠው አካል ሲወጣ በቋሚነት እንዲያገለግል ታስቦ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን የማህበረሰቡ ፍላጎት፣ አዳዲስ ፖሊሲዎች ሲቀረጹ ወይም የቀድሞው ሕግ በጊዜው ካለው ሁኔታ ጋር መጣጣም ሲያቅተው አልያም በሌላ ምክንያት ሕጉን በከፊል ወይም ሙሉ በሙሉ ማንሳት አስፈላጊ ይሆናል። ይህ ሂደት የሕግ መሻር (Repeal of Laws) ይባላል። ይህ የሕግ መሻር ሂደት በባህሪው በሁለት ዋና ዋና ክፍሎች ይከፈላል። የመጀመሪያው ግልጽ መሻር (Express Repeal) የሚባለው ሲሆን፣ ይህ የሚሆነው ሕግ አውጪው አካል በአዲስ በሚያወጣው ሕግ ላይ የትኛው የቀድሞ ሕግ ወይም የተወሰነ አንቀጽ ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል እንደተሻረ በግልጽ ስም እና ቁጥር ጠቅሶ ሲደነግግ ነው። ሁለተኛው ደግሞ በተዘዋዋሪ መሻር (Implied Repeal) የሚባለው ሲሆን፣ ይህም አዲሱ ሕግ እና የቀድሞው ሕግ እርስ በርሳቸው ሙሉ በሙሉ የሚጋጩ እና አብረው ሊተገበሩ የማይችሉ በሚሆኑበት ጊዜ ይከሰታል። በእንደዚህ አይነት ሁኔታ ሕግ አውጪው በግልጽ የተሻረውን ሕግ ባይጠቅስም እንኳ፣ የኋለኛው ሕግ የቀድሞውን እንደሚሽረው የሚገልጸው የሕግ መርህ ተፈጻሚ በመሆን የድሮውን ሕግ ህልውና ያበቃለታል። አንድ ሕግ በግልጽም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ሲሻር ሰፊ የሕግ ውጤቶችን ያስከትላል። ዋናው ውጤት የተሻረው ሕግ የወደፊት እጣ ፈንታ ሙሉ በሙሉ የሚያበቃ መሆኑ ነው። ሕጉ ከተሻረበት ቀን ጀምሮ ሕጋዊ አስገዳጅነቱን እና ህልውናውን ስለሚያጣ፣ ከዚያን ጊዜ በኋላ አዳዲስ መብቶችን መፍጠር፣ ግዴታዎችን መጣል ወይም ሕጋዊ ግንኙነቶችን መመስረት አይችልም። ሆኖም ግን ይህ መሻር ወደኋላ ተመልሶ አስቀድሞ የተጠናቀቁ ጉዳዮችን አያፈርስም። ይህም ማለት ሕጉ ሳይሻር በፊት በነበረው መብት መሰረት የተገኙ መብቶች፣ ግንኙነቶች ወይም የተሰጡ ፍርዶች ሕጋዊ ሆነው ጸንተው ይቀጥላሉ። በነገራችን ላይ፣ አንድን ሕግ የሻረው አዲሱ ሕግ ራሱ በሌላ ጊዜ ቢሻር፣ መጀመሪያ የተሻረው የድሮው ሕግ በራሱ ጊዜ ህያው ሆኖ ተመልሶ ሊሰራ አይችልም። የተሻረ ሕግ ተመልሶ እንዲሰራ ከተፈለገ ሕግ አውጪው አካል በግልጽ አዲስ ሕግ ማውጣት ወይም በይፋ ነባሩን ሕግ መልሶ ማጽደቅ ይኖርበታል። ከዚህም በላይ፣ ዋናው ሕግ (አዋጅ) ሲሻር፣ ተፈጻሚነቱን ለማስቀጠል የሚያስችል የማዳኛ ድንጋጌ (Saving Clause) በአዲሱ ሕግ ውስጥ ካልተካተተ በቀር፣ በዚያ በተሻረው ዋና ሕግ መሠረት የወጡ ታችኛ (ንዑስ) ሕጎች (ደንቦችና መመሪያዎች) በሙሉ አብረው ሕጋዊ ውጤት ማጣታቸው ወይም መቅረታቸው አይቀሬ ነው። የሕግ መሻር ከሕግ ማክተም (Expiry of Laws) ጋር በውጤት ደረጃ መመሳሰሎች ቢኖሩትም በባህሪው ግን በእጅጉ ይለያያል። በሁለቱም ሂደቶች የሕጉ ሕጋዊ አስገዳጅነት እና ሕልውና ሙሉ በሙሉ ወይም በከፊል ቢያበቃም የሕግ ማክተም ሕጉ ራሱ አስቀድሞ በውስጡ በያዘው የጊዜ ገደብ ምክንያት በራሱ የሚሞትበት ሂደት ነው። ሕጉን ለመሻር የግድ አዲስ የሕግ አውጪነት ተግባር ወይም አዲስ ሕግ ማውጣት የግድ ይላል። በአንጻሩ የሕግ ማክተም የሚከሰተው አስቀድሞ የተወሰነ የጊዜ ገደብ ባላቸው ጊዜያዊ ሕጎች ላይ ብቻ ነው። እንደዚህ አይነት ሕጎች ሲወጡ አብሯቸው የሚያበቃበት ቀን አብሮ የሚወሰን በመሆኑ፣ የተቀመጠው ጊዜ ሲደርስ ሕጉ ምንም አይነት አዲስ ተጨማሪ ሕግ ሳይፈለግ በራሱ ጊዜ ህልውናው ያበቃል። መልካም ቀን! Jura Legal Update

photo content

በሕግ ዓለም "ሰው" መሆን (የሕግ ሰውነት) በዕለት ተዕለት ማኅበራዊ መስተጋብራችን ውስጥ "ሰው" የሚለውን ቃል ስንጠቀም በአእምሯችን የሚቀረጸው ስጋና ደም የለበሰውን ተፈጥሯዊ የሰውን ልጅ ብቻ ሊሆን ይችላል። ነገር ግን በሕግ ሳይንስ ውስጥ "ሰው" መሆን ከዚያ የሰፋ፣ የጠለቀና የራሱ የሆነ ታሪካዊ መነሻ ያለው መሠረታዊ ጽንሰ ሀሳብ ነው። ይህ ጽንሰ ሀሳብ በሕግ ቋንቋ የሕግ ሰውነት (Legal Personality) ተብሎ ይጠራል። የሕግ ሰውነትን ምንነትና ያለውን ፋይዳ መረዳት ሕግን ለመረዳት የመጀመሪያውና መሠረታዊው 'ሀ ሁ' ነው። ​የ"ሰው" (Person) ቃል አመጣጥ ታሪካዊ መነሻውን ስናጠና የሚመራን በጥንቱ የግሪክና የሮማውያን የቲያትር ጥበብ ውስጥ ወደነበረው "Persona" ወደሚለው የላቲን ቃል ነው። በጥንቱ ዘመን ይህ ቃል የሚያመለክተው ተዋንያን መድረክ ላይ የሚጫወቱትን ገጸ-ባህሪ ወይም የሚወክሉትን "ሚና" (Role or Part) ለታዳሚው ለመለየት ፊታቸው ላይ የሚያደርጉትን "ጭንብል" ነበር። ታዳሚው ጭንብሉን እንዳየ ተዋናዩ የሚወክለውን ባህሪ ወዲያውኑ ይረዳ ነበር። ሕግም ይህንን ታሪካዊ መነሻ በመውሰድ፣ በሕግ ፊት የመንቀሳቀስ መብትና ግዴታ የተሰጣቸውን አካላት የራሳቸው "ሚና ወይም ጭንብል" ያላቸው አድርጎ በመቁጠር "Persons" (ሰዎች) ያላቸው ሲሆን፣ ይህንን መብት የማግኘት ብቃትን ደግሞ "የሕግ ሰውነት" (Legal Personality) በማለት ሰይሞታል። ​በታሪክ ሂደት ውስጥ "የሰውን ልጅ" (Human Being) እና "በሕግ ፊት ሰው መሆንን" (Person) ሁልጊዜም አንድ አድርጎ የመመልከት ልማድ አልነበረም። በጥንቱ የሮማውያን ሕግ (Roman Law) ሥርዓት ውስጥ ሁሉም ሰዎች በሕግ ፊት እንደ "ሰው" አይቆጠሩም ነበር። ለምሳሌ ባሪያዎች (Slaves) እንደ ዕቃ እንጂ እንደ ሰው ባለመቆጠራቸው በሕግ ፊት ምንም ዓይነት መብትና ግዴታ አልነበራቸውም። ከጊዜ ብዛትና ከሥልጣኔ ዕድገት ጋር ግን ሁሉም የሰው ልጆች በተፈጥሯቸው መብትና ግዴታን ለመሸከም ብቁ የሆኑ የሕግ ባለቤቶች (Subjects of Rights and Duties) ተደርገው ተወሰዱ። በመሆኑም በጥንቱ የሮማውያን ሕግ የነበረው በሰዎች መካከል የሕግ ሰውነትን የመንፈግ ልዩነት በዘመናዊ ሕግ ውስጥ ቦታ የለውም። ​ሆኖም ግን፣ በዘመናዊ ሕግም ቢሆን "የሰው ልጅ" እና "የሕግ ሰው" የሚሉት ቃላት ፍጹም አንድና ተለዋዋጭ (Interchangeable) አይደሉም። ምክንያቱም ሕግ ከተፈጥሯዊ የሰው ልጆች በተጨማሪ ሌሎች አካላትንም የመብትና የግዴታ ባለቤት አድርጎ እውቅና ይሰጣቸዋል። ይህም ማለት "ሰዎች" የሚለው ቃል በአንድ በኩል ፍጡር የሆኑትን ተፈጥሯዊ የሰው ልጆችን (Human Beings) ለማመልከት፣ በሌላ በኩል ደግሞ በሕግ ፊት መብትና ግዴታ ያላቸውን ተቋማትንም (Legal Entities) በአንድነት ለመግለጽ ያገለግላል። ​የኢትዮጵያ የፍትሐብሔር ሕግ ይህንን የሕግ ሰውነት ክፍፍል በግልጽ በሁለት ዋና ዋና ምድቦች ከፍሎ ያስቀምጠዋል። የመጀመሪያው ክፍል ከተፈጥሯዊ ወይም ከአካላዊ ሰዎች (Natural or Physical Persons) ጋር የተያያዘ ሲሆን፣ ከሕጉ አንቀጽ 1 እስከ 393 ያሉት ድንጋጌዎች ስለዚህ ጉዳይ ያብራራሉ። ሁለተኛው ክፍል ደግሞ ከሰው ልጅ ውጭ የሆኑ፣ ነገር ግን በሕግ አማካኝነት ሰውነት የተሰጣቸውን ሰው ሠራሽ ወይም ሕጋዊ ሰዎችን (Juridical or Legal Persons) የሚመለከት ነው። በፍትሐብሔር ሕጉ አንቀጽ 394 እና ተከታዮቹ ላይ እንደተደነገገው እንደ መንግሥት፣ የሀገር ውስጥ አስተዳደራዊ መዋቅሮች፣ ሚኒስቴር መሥሪያ ቤቶች፣ የሕዝብ ማኅበራት፣ የንግድ ማኅበራት (Companies) እና ሽርክናዎች (Partnerships) ያሉ አካላት ከተመሠረቱበት ጊዜ ጀምሮ በሕግ መሠረት ፈርሰው እስከሚጠፉበት ድረስ የሕግ ሰውነት ተሰጥቷቸዋል። ​በአንጻሩ፣ የሕግ ሰውነት የሌላቸው ነገሮች ሁሉ ጥበቃ ሊደርግላቸው የሚችልበት የሕግ ማዕቀፍ ሊኖራቸው ቢችልም፣ ራሳቸውን ችለው መብትና ግዴታ የመሸከም ብቃት የላቸውም። በሌላ አነጋገር፣ አንድ አካል በሕግ ፊት መብት ሊኖረውና ግዴታን ሊሸከም የሚችለው ይህ የሕግ ሰውነት ሲኖረው ብቻ ነው። የሕግ ሰውነት ከሌለ ያ አካል በሕግ ፊት የመብት ባለቤት ሳይሆን ልክ እንደ ዕቃ/ንብረት ነው የሚቆጠረው። ለምሳሌ ያህል የቤት እንስሳት የሕግ ሰውነት ስለሌላቸው በራሳቸው ስም መክሰስም ሆነ መከሰስ አይችሉም። ​አንድ አካል የሕግ ሰውነት ሲኖረው የሚከተሉትን ዋና ዋና የሕግ ውጤቶች ያገኛል። በራሱ ስም ንብረት ማፍራት፣ መሸጥና መለወጥ ይችላል፤ ከሌሎች አካላት ጋር ውል መዋዋል ይችላል፤ መብቱ ሲነካ ፍርድ ቤት ቀርቦ የመክሰስ እንዲሁም ጥፋት ሲያጠፋ የመከሰስ መብትና ግዴታ ይኖረዋል። ​ነገር ግን፣ ሕጋዊ ሰዎች (Juridical Persons) ልክ እንደ ተፈጥሯዊ ሰዎች ውል የመዋዋል፣ የመክሰስና የመከሰስ መብት ቢኖራቸውም፣ ከተፈጥሮአዊ ባሕርያቸው መቅረት የተነሳ ሊያከናውኗቸው የማይችሏቸው እንደ የመምረጥና የመመረጥ መብት (Right to Vote) ያሉ የተወሰኑ የግል መብቶች (Rights of Personality) እንዳሉ ልብ ማለት ያስፈልጋል። መልካም ምሽት! Jura Legal Update ግንቦት 28 ቀን 2018 ዓ.ም አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ ቴሌግራም: https://t.me/JuraLegalUpdate ፌስቡክ:https://www.facebook.com/share/1c2WCxGTV7/

photo content

ዛሬ በሆለታ ወልመራ ወረዳ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ውስጥ በሥራ ገበታቸው ላይ ውሳኔ በማንበብ ላይ በነበሩት ዳኛ ወርቄ ፈካንሳ እና በአንዲት ተከራካሪ ላይ የተፈጸመው አሰቃቂ ጥቃት እና የህይወት
ዛሬ በሆለታ ወልመራ ወረዳ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት ውስጥ በሥራ ገበታቸው ላይ ውሳኔ በማንበብ ላይ በነበሩት ዳኛ ወርቄ ፈካንሳ እና በአንዲት ተከራካሪ ላይ የተፈጸመው አሰቃቂ ጥቃት እና የህይወት ማለፍ ሁላችንንም በጥልቅ አሳዝኖናል። ​ሕግ ባለበት፣ ፍትሕ በሚሰጥበት እና የሁሉ መጠለያ በሆነው የፍርድ ቤት አዳራሽ ውስጥ እንዲህ ዓይነት የጭካኔ ድርጊት መፈጸሙ እጅግ የሚያስደነግጥ እና ልብ የሚሰብር ነው። ይህ ክስተት በሥራ ገበታቸው ላይ ላሉ ዳኞች እና ሌሎች የሕግ ባለሙያዎች አስተማማኝ የደህንነት ጥበቃ ሊደረግላቸው እንደሚገባ ትልቅ ማሳያ ነው። ​ለዳኛ ወርቄ ፈካንሳ ቤተሰቦች፣ ለሟች ተከራካሪ ወዳጅ ዘመዶች መጽናናትን እና ብርታትን እንመኛለን። ​ፈጣሪ ነፍሳቸውን በሰላም ያሳርፍ! Jura Legal Update

ስለ ቅጥር ውል አይነትና የማስረዳት ሸክም ​በአሰሪና ሰራተኛ ህግ መሠረታዊ መርህ መሠረት በማንኛውም ሁኔታ የአንድ ሰራተኛ የቅጥር ውል ላልተወሰነ ጊዜ እንደተደረገ ይቆጠራል። አንድን የቅጥር ውል ለ
ስለ ቅጥር ውል አይነትና የማስረዳት ሸክም ​በአሰሪና ሰራተኛ ህግ መሠረታዊ መርህ መሠረት በማንኛውም ሁኔታ የአንድ ሰራተኛ የቅጥር ውል ላልተወሰነ ጊዜ እንደተደረገ ይቆጠራል። አንድን የቅጥር ውል ለተወሰነ ጊዜ ወይም ለተወሰነ ስራ ነው ለማለት ውሉ በአሰሪና ሠራተኛ አዋጁ ላይ ለተወሰነ ጊዜ ሊደረጉ ይችላሉ ተብለው በተዘረዘሩት የሥራ አይነቶች ስር ሊወድቅና ሊረጋገጥ ይገባል። ​ውሉ ለተወሰነ ጊዜ ነው ብሎ የሚከራከረው አሰሪው በመሆኑ፣ ውሉ በህጉ ስር ከሚጠቀሱት ምክንያቶች በአንዱ መደረጉን የማስረዳት ግዴታው በራሱ በአሰሪው ላይ ይወድቃል። በአንጻሩ ሰራተኛው ውሉ ላልተወሰነ ጊዜ ነው ብሎ ሲከራከር በህጉ ግምት (Presumption) ተጠቃሚ ስለሚሆን አስቀድሞ የማስረዳት ሸክም የለበትም። ​ዋናው ሊታወቅ የሚገባው ነጥብ የቅጥር ውል በጽሁፍ ላይ ለተወሰነ ጊዜ ተብሎ መገለጹ ብቻውን በቂ አለመሆኑ ነው። ይልቁንም የውሉ መሠረት የሆነው የስራ ባህሪ በህጉ ከተዘረዘሩት ልዩ ሁኔታዎች ውስጥ በአንዱ ሊወድቅ ይገባል። ይህንን የህግ ትርጓሜ በተመለከተ ሰፋ ያለ ግንዛቤ ለማግኘት የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር መዝገብ ቁጥር 11924 (ቅጽ 3) እንዲሁም ተመሳሳይ ጭብጥ ያላቸውን ሌሎች የሰበር ውሳኔዎችን እንድታነቡ እጋብዛለሁ። በነዚህ መዝገቦች ላይ የተሰጡት ትንታኔዎች በአሰሪና ሰራተኛ ግንኙነት ውስጥ ለሚነሱ መሰረታዊ የክርክር ነጥቦች ጠቃሚነት ያላቸው ናቸው። መልካም ምሽት! Jura Legal Update ቴሌግራም: https://t.me/JuraLegalUpdate ፌስቡክ:https://www.facebook.com/share/1c2WCxGTV7/

በኢትዮጵያ የውርስ ሕግ ባልና ሚስት እርስ በእርስ ይወራረሳሉ? በትዳር ውስጥ አብሮ የኖረ የሕይወት አጋር ሲሞት ከሕግ ሙያ ውጪ ላለ ማኅበረሰብ በሕይወት ያለው ባል ወይም ሚስት የሟቹን ንብረት የሚወርስ ቢመስልም በኢትዮጵያ የውርስ ሕግ ግን ኑዛዜ ከሌለ በቀር ባልና ሚስት እርስ በእርስ አይወራረሱም። ይህ የሆነበት ምክንያት የኢትዮጵያ የውርስ ሕግ ከጉዲፈቻ ግንኙነት ውጭ መሠረት የሚያደርገው የደም ትስስርን ወይም የሥጋ ዝምድናን ብቻ በመሆኑና ትዳር ደግሞ የሕግ እንጂ የደም ትስስር ባለመሆኑ ነው። አንድ ሰው በሕይወት እያለ የንብረቱን ክፍፍል በተመለከተ ያደረገው ኑዛዜ ከሌለ ወይም ኑዛዜው በተለያዩ ምክንያቶች ውጤት አልባ በሚሆንበት ጊዜ፣ የኢትዮጵያ የውርስ ሕግ ውርሱ የሚፈጸምበትን ሥርዓት በግልጽ በደረጃ ያስቀምጣል። በዚህም መሠረት የሟች የሥጋ ዘመዶች በውርስ ሂደት ውስጥ ንብረቱን በቀጥታ ወይም በተተኪነት የመውረስ መብት ያላቸው ሲሆን፣ ሕጉ እነዚህን ወራሾች ከ1ኛ እስከ 4ኛ ደረጃ በቅደም-ተከተል ያስቀምጣቸዋል። በዚህ ሥርዓት መሠረት መጀመሪያ 1ኛ ደረጃ ወራሾች የሆኑት ልጆችና ተተኪዎቻቸው ውርሱን ሙሉ በሙሉ የሚወስዱ ሲሆን፣ እነሱ በሌሉበት ሁኔታ ብቻ ውርሱ ወደ 2ኛ ደረጃ፣ ከዚያም ወደ 3ኛ እና 4ኛ ደረጃ ወራሾች በቅደም ተከተል ይተላለፋል። በሕጉ የተዘረዘሩት አራቱም ደረጃዎች ውስጥ የሚመደብ ምንም ዓይነት የሥጋ ዘመድ በሌለበት ሁኔታ ግን፣ መንግስት የሟችን ንብረት እንደሚወርስ የፍትሐብሔር ሕጉ ይደነግጋል። ምንም እንኳ በአንዳንድ የውጭ ሀገራት ባልና ሚስት እርስ በእርስ የሚወራረሱበትን ሥርዓት ቢኖርም በኢትዮጵያ የውርስ ሕግ ግን ኑዛዜ በሌለበት ሁኔታ ወራሽ መሆን የሚችሉት የሟች የሥጋ ዘመዶች ብቻ በመሆናቸው፣ የትዳር አጋር በቀጥታ ወራሽ የሚሆንበት አግባብ የለም። ይሁን እንጂ በትዳር ውስጥ የተፈራ ንብረት ካለ በሕይወት ያለው የትዳር አጋር ያንን የጋብቻ ግንኙነት መነሻ በማድረግ የጋራ ንብረቱን እኩሌታ የመካፈል ሙሉ ሕጋዊ መብት አለው። ይህ የንብረት ክፍፍል መብት ከትዳር ግንኙነቱ የሚገኝ የንብረት ድርሻ እንጂ ውርስ ባለመሆኑ፣ የተረፈውን የሟች ድርሻ እና የሟችን የግል ንብረቶች ደረጃውን ጠብቀው የደም ትስስር ያላቸው የሥጋ ወራሾች ብቻ ይወስዱታል። ወራሽ ከሌለ መንግስት ይወርሰዋል። ስለዚህ ባልና ሚስት ከጋራ ንብረት ድርሻቸው አልፈው እርስ በእርስ መወራረስ የሚችሉት አስቀድሞ በሕግ ፊት የጸና ኑዛዜ በሟች ተደርጎ ሲገኝ ብቻ ነው። ይህ ከሌለ ባልና ሚስት እርስ በእርስ አይወራረሱም! መልካም ምሽት! Jura Legal Update ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ ቴሌግራም: https://t.me/JuraLegalUpdate ፌስቡክ:https://www.facebook.com/share/1c2WCxGTV7/

photo content

83068.pdf3.09 KB

​የሠራተኛው ስምምነት ሳይኖር ወደ እህት ድርጅት ማዛወር አይቻልም! ​አሰሪ በሥራ ውልም ሆነ በሌላ ሰነድ ላይ ሠራተኛው በግልጽ ስምምነቱን ባልሰጠበት ሁኔታ፣ “እህት ድርጅት” ወደ ሆነ ሌላ ተቋም አዛውሮ የማሰራት መብት የለውም። ​የሰበር መዝገብ ቁጥር 83068 (ቅጽ 14) ​#የሰበር_ውሳኔ #የአሰሪና_ሠራተኛ_ሕግ #Jura_Legal_Update

photo content

የመንግስት ጽንሰ-ሀሳብ አመጣጥ መንግስት ማለት በአንድ በተወሰነ ጂኦግራፊያዊ ወሰን (ግዛት) ውስጥ የሚኖርን ማህበረሰብ የሚያስተዳድር፣ ሕግ የሚያወጣ፣ የሚያስፈጽምና የሚያስከብር ከፍተኛው የሥልጣን አካል ነው። ​የመንግስት መኖር የዜጎችን ሰላምና ደህንነት ለመጠበቅ፣ በሰዎች መካከል የሚፈጠሩ ግጭቶች በሕግ አግባብ ሥርዓት እንዲይዙ ለማድረግ፣ እንደ ትምህርት፣ ጤና እና መንገድ ያሉ መሠረተ ልማቶችን ለመገንባት፣ እንዲሁም የሀገሪቱን የኢኮኖሚና የንግድ ሥርዓት በባለቤትነት ለመምራትና ለመቆጣጠር እጅግ አስፈላጊ ነው። እነዚህን ዘርፈ-ብዙ ኃላፊነቶች ለመወጣት ደግሞ፣ እንደየሀገራቱ ተጨባጭ ሁኔታና የፖለቲካ ሥርዓት መንግስታት በተለያዩ ቅርጾችና ዓይነቶች ሊዋቀሩ ይችላሉ። ይሁን እንጂ፣ ዛሬ ላይ የምናየው የተደራጀና የገዘፈ የመንግስት መዋቅር በአንድ ጀምበር የተፈጠረ አይደለም። 'ሰው ማህበራዊ እንስሳ ነው' እንደሚባለው፣ የሰው ልጅ በማህበር መኖር ከጀመረበት ጊዜ አንስቶ ራሱን የሚያስተዳድርበትን የጋራ ሥልጣን ለመፍጠር ረጅም ታሪካዊ ሂደቶችን አልፏል። ይህ የመንግስት አመጣጥና ምስረታ ሂደት እንዴት ሊጀመርና ሊሳካ ቻለ? የሚለው ጥያቄ በፖለቲካ ሳይንስ፣ በታሪክና በሕግ ፍልስፍና ሊቃውንት ዘንድ ለዘመናት በርካታ ክርክሮችን ሲያስነሳ የቆየ ጉዳይ ነው። በዚህም ምክንያት፣ የመንግስትን መከሰትና የሉዓላዊነትን ምንጭ ከተለያዩ እይታዎች አንጻር የሚያብራሩ የተለያዩ ቀደምትና ዘመናዊ ቲዎሪዎች ተቀርጸዋል። ከእነዚህ ዋነኛ ቲዎሪዎች መካከል የዝግመተ ለውጥ እይታ (Evolutionary Theory) አንዱ ነው። ​ይህ እይታ መንግስት በአንድ ጀምበር የተፈጠረ ሳይሆን፣ ከቤተሰብ አወቃቀር ቀስ በቀስ እያደገ የመጣ ነው ይላል። መጀመሪያ የቤተሰብ መሪዎች ነበሩ፤ ቤተሰቦች እየበዙ ሲሄዱ ወደ ጎሳ፣ ከዚያም ወደ ሰፊ ማህበረሰብ ተቀየሩ። ማህበረሰቡ እየሰፋ ሲመጣ ግጭቶችን ለመፍታትና ደህንነትን ለመጠበቅ ቋሚ አመራርና ህጎች አስፈለጉ። ይህ ሂደት የመንግስት መፈጠር መሠረት ሆነ ይላሉ። እንደ ሰር ሄነሪ ሜይን (Sir Henry Maine) እና ኤድዋርድ ጄንክስ (Edward Jenks) ያሉ የታሪክና የሕግ ምሁራን ይህንን ቲዎሪ በስፋት የሚደግፉ ሲሆን፣ በተለይም ሰር ሄነሪ ሜይን በጥንታዊ ማህበረሰቦች ውስጥ የነበረው የአባት የበላይነት የቤተሰብ መዋቅር እንዴት ወደ መንግስትነት እንደተሸጋገረ በጥናት አሳይተዋል። ​ሁለተኛውና እጅግ ተፅዕኖ ፈጣሪው እይታ የማህበራዊ ውል ጽንሰ-ሀሳብ (Social Contract Theory) ሲሆን፣ ይህ በ17ኛውና በ18ኛው ክፍለ ዘመን በአውሮፓ የነበሩ ታዋቂ ፈላስፎች (እንደ ቶማስ ሆብስ፣ ጆን ሎክ እና ዣን ዣክ ሩሶ) ያዳበሩት ሀሳብ ነው። መሠረታዊ ሀሳቡ ሰዎች ከመንግስት መመስረት በፊት "የተፈጥሮ ሁኔታ" (State of Nature) በሚባል፣ ምንም ዓይነት መደበኛ ህግና መንግስት በሌለበት ሁኔታ ውስጥ ይኖሩ ነበር የሚል ነው። ይሁን እንጂ ይህ ሁኔታ ዘላቂ ሰላም ስላልነበረው፣ ሰዎች በሰላም ለመኖርና መብቶቻቸውን ለማስከበር ሲሉ የጋራ ውል በመፈራረም የተወሰነ ነፃነታቸውን ትተው ለጋራ የበላይ አካል ለመገዛት ተስማሙ። መንግስትም በምላሹ ሰላምና ደህንነትን የመጠበቅ ግዴታ ገባ ይላሉ። በዚህ ጽንሰ-ሀሳብ ውስጥ ቶማስ ሆብስ የተፈጥሮ ሁኔታን ሁሉም በሁሉም ላይ የሚነሳበትና ፍርሃት የነገሰበት አድርጎ ስለሚስለው ሰዎች ፍጹም ስልጣን ላለው መንግስት መገዛት አለባቸው ሲል ይከራከራል። በአንጻሩ ጆን ሎክ በተፈጥሮ ሁኔታ ውስጥ ሰዎች የህይወት፣ የነፃነትና የንብረት መብት እንደነበራቸው ገልጾ፣ እነዚህን መብቶች ይበልጥ በተደራጀ መንገድ ለመጠበቅ ሲሉ ውል እንደመሰረቱና መንግስት እነዚህን መብቶች ካላከበረ ህዝቡ የመቀየር መብት እንዳለው ያምናል። ዣን ዣክ ሩሶ ደግሞ ውሉ የተመሰረተው በግለሰቦች ፍላጎት ሳይሆን በህዝባዊ የጋራ ፍላጎት ላይ በመሆኑ እውነተኛ ሉዓላዊነት የህዝብ ነው የሚል እይታ አለው። በ​ሦስተኛ ደረጃ የሚጠቀሰው የኃይል ጽንሰ-ሀሳብ (Force Theory) ሲሆን ​ይህ ፅንሰ-ሀሳብ መንግስት የተመሠረተው በአሸናፊነት፣ በጉልበትና በጦርነት ነው ይላል። ​አንድ ጠንካራ ግለሰብ ወይም ቡድን በሌላው ላይ የበላይነትን ተቀዳጅቶ ግዛቱን ሲያስከብርና ህግጋትን ሲጭን የመንግስት መዋቅር ተጀመረ። ስለሆነም መንግስት የኃይል ውጤት ነው ይላል። እንደ ዴቪድ ሂዩም (David Hume) ያሉ ፈላስፎች እና እንደ ፍራንዝ ኦፐንሃይመር (Franz Oppenheimer) ያሉ የሶሺዮሎጂ ምሁራን ይህንን ሀሳብ ያነሳሉ። ኦፐንሃይመር "The State" በተሰኘ መጽሐፉ ላይ መንግስት የተፈጠረው አሸናፊ የሆኑ ተሸናፊዎችን በሃይል አስገብረው የራሳቸውን ጥቅም ለማስጠበቅ ካደረጉት ወረራ ነው ይላል። አራተኛው መለኮታዊ መብት (Divine Right Theory) ቲዎሪ ሲሆን ​በጥንታዊና በመካከለኛው ዘመን በስፋት ይሠራበት የነበረ ሀሳብ ነው። ​መንግስት ወይም ንጉሥ የተሾመው በቀጥታ በፈጣሪ ነው ተብሎ ይታመን ነበር። ስለዚህ ለመንግስት መገዛት ለፈጣሪ እንደመገዛት ይቆጠር ነበር። ይህ ጽንሰ-ሀሳብ መንግስት ሃይማኖታዊ ቅቡልነት እንዲኖረው አድርጓል። በአውሮፓ ታሪክ ይህንን ሀሳብ በጽሑፎቻቸው የደገፉት እንደ ሰር ሮበርት ፊልመር (Sir Robert Filmer) እና ፈረንሳዊው ጳጳስ ዣክ ቦሱዌ (Jacques-Bénigne Bossuet) ናቸው። ንጉሡ ተጠያቂነቱ ለፈጣሪ ብቻ እንደሆነ ይከራከሩ ነበር። በመጨረሻም፣ ​አምስተኛው የማርክሲስት ቲዎሪ (Marxist Theory) ሲሆን ​ይህ ቲዎሪ መንግስትን የሚያየው በኢኮኖሚ የበላይነት ያለውን ክፍል ጥቅም ለማስጠበቅ እንደተፈጠረ መሣሪያ አድርጎ ነው። እንደ ካርል ማርክስ እና ፍሬድሪክ ኤንግልስ የመሰሉ ፈላስፎች መንግስት የተፈጠረው የሀብት ክፍፍል ሲመጣ ነው ይላሉ። ​የግል ንብረት ሲጀመር፣ ሀብታሞች ንብረታቸውን ከደሃው ለመጠበቅና ጥቅማቸውን ለማስከበር የመንግስትን መዋቅርና ህጎችን እንደ መሣሪያ ፈጠሩ የሚል እይታ አለው። ከእነዚህ አምስት መሠረታዊ ቲዎሪዎች በተጨማሪ፣ ጉዳዩን በሌላ መነፅር የሚያዩ ተጨማሪ እይታዎች አሉ። ​የስነ-ልቦና ቲዎሪ (Psychological Theory) የሚባለው የሰው ልጅ በተፈጥሮው መሪ የመፈለግ፣ የመታዘዝ እና በስርዓት ውስጥ የመኖር ስነ-ልቦናዊ ዝንባሌ ስላለው መንግስት ተፈጠረ ይላል። በሌላ በኩል፣ ​የታሪካዊ/ሶሺዮሎጂካል ቲዎሪ (Historical or Sociological Theory) መንግስት በሃይል ብቻ ወይም በውል ብቻ ሳይሆን የደም ትስስር፣ ሃይማኖት፣ የሃይል የበላይነት እና የምጣኔ ሀብት ፍላጎቶች በአንድ ላይ ተጋምደው የፈጠሩት የረጅም ዘመን ታሪካዊ ውጤት ነው ይላል። እነዚህ ሁሉ ቲዎሪዎች የመንግስትን አመጣጥ ከተለያዩ ማህበራዊ፣ ታሪካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ስነ-ልቦናዊ አቅጣጫዎች ይቃኛሉ። አንዳቸውም በራሳቸው ሙሉ በሙሉ ስህተት ወይም ሙሉ በሙሉ ትክክል ናቸው ሊባሉ አይችሉም። ይልቁንም፣ ዛሬ ላይ የምናየው ዘመናዊ መንግስት የእነዚህ ሁሉ ታሪካዊ ክስተቶች (የሃይል፣ የጋራ ስምምነት፣ የኢኮኖሚ ፍላጎት፣ የረጅም ጊዜ የዝግመተ ለውጥ ሂደት) ድምር ውጤት ነው ማለት ይቻላል። መልካም ቅዳሜ! Jura Legal Update ግንቦት 22 ቀን 2018 ዓ.ም አዲስ አበባ፥ ኢትዮጵያ ቴሌግራም: https://t.me/JuraLegalUpdate ፌስቡክ:https://www.facebook.com/share/1c2WCxGTV7/

የፈተና ውጤት ማስታወቂያ
+4
የፈተና ውጤት ማስታወቂያ

WSU Law School Secures €300,000 International Grant ==================== ​Wolaita Sodo University’s (WSU) School of Law has s
+3
WSU Law School Secures €300,000 International Grant ==================== ​Wolaita Sodo University’s (WSU) School of Law has secured a prestigious VLIR-UOS TEAM 2026 Grant valued at EUR 300,000 for a five-year collaborative project. ​The initiative, "Durable Solutions Through a Human Rights-Based Approach for Displaced Women and Children in the Omo-Gibe River Basin, Southern Ethiopia", is led locally by Associate Professor and Dean of the School of Law, Dr. Kidus Meskele, in partnership with Belgian counterparts led by Professor Wouter Vandenhole. ​WSU leadership hailed the landmark award as a major strategic milestone that significantly elevates the university's international research visibility and community legal engagement. Congratulations to the WSU School of Law team on this major international win!

225144.pdf8.58 KB