ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Ir al canal en Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Mostrar más638
Suscriptores
-224 horas
-57 días
-1130 días
Archivo de publicaciones
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ እንኳን #ለትንሣኤ_አምስተኛ_ሳምንት #ለዕለተ_ጥብርያዶስ መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፮ "#አርአየ_ሥልጣኖ_ላዕለ_ሞት አርአየ ሥልጣኖ ላዕለ ሞት #ንጉሠ_ነገሥት_እግዚአ_አጋግእዝት፤ አዝ፣ ዘይቤብሕዎ #ሊቃነ_መላእክት ይሰግዱ ሎቱ ቅድሜሁ በፍርሃት፤ አዝ፣ #ይቤሎሙ_ኢየሱስ_ለአይሁድ አመ ይእኅዝዎ በይእቲ ሌሊት፤ አዝ፣ ተናግሮሙ ወይቤሎሙ ከመ ሠራቂ መጻእክሙ ተአኀዙኒ በመጥባሕት፤ አዝ፣ ኦ ትዕግሥት ወአርምሞት በፍቅረ ዚአነ በጽሐ እስከ ለሞት፤ አዝ፣ ወንህነኒ #ንግበር_ቅድስት_ፋሲካ በሐሤት አርአየ ሥልጣኖ ላዕለ ሞት ገባሬ #ሕይወት_ክርስቶስ። ትርጉም፦ #ሊቃነ_መላእክት_የሚያመሰግኑት በፊቱም በፍርሃት የሚሰግዱለት፤ የነገሥታት ንጉሥ የጌቶች ጌታ #ክርስቶስ_በሞት_ላይ_ሥልጣኑን_አሳየ። #ኢየሱስ በተያዘባት በዚያች ሌሊት አይሁድን እንዲህ አላቸው፤ በሰይፍ ልትይዙኝ እንደ ሌባ ድንገት መጣችሁ አላቸው፤ በእኛ ፍቅር እስከ ሞት ደረሰ፤ ይህ ትዕግሥትና አርምሞ ከሃሊነት ምን ይረቅ ምን ይደንቅ ምን ይጠልቅ ኦ ወዮ እንደምን ያለ ረቂቅ ነው ለዚህ አንክሮ ይገባል፤ እኛም #በታላቅ_ደስታ_የተለየች_ፋሲካን_እናድርግ፤ #የሕይወት_ፈጣሪ_ክርስቶስ_ሥልጣኑን (ኀይሉን) በሞት ላይ ገለጧልና። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ ሰበረ ኆኃተ ብርት። ወቀጥቀጠ መናሥግተ ዘሐፂን። ወተወክፎሙ እምፍኖተ ጌጋዮሙ"። 106፥16-17 ወይም መዝ 77፥29-30። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 6፥1-15 ወይም ሮሜ 1፥14-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 4፥4-12 ወይም ራዕ 20፥1-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 10፥39-44 ወይም 3፥15-22። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 21፥15_ፍ.ም ወይም 21፥1_14። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ቅዳሴ ነው። መልካም ዕለተ ሰንበትና የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፪ (2) ቀን።
❤ እንኳን #ለታላቁ_በመጽሐፍ_ቅዱስ ላይ ለተጠቀሰው #ለትዕግስተኛው_አባት_ለቅዱስ_ኢዮብና ለመንፈሳዊ ማኅበር አባት #ለአባ_ጳኵሚስ_ረድእ ለከበረ አባት #ለአባ_ቴዎድሮስ ለዕረፍታቸው መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #ከአባ_ኤሲ ጋራ #ከሃያ_ሁለት_ሰዎች በሰማዕትነት ከዐረፉ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ኢዮብ፦ ለዚህም ጻድቅ በዘመኑ እንደርሱ ያለ እውነተኛ ደግ ሰው እንደ ሌለ በቅዱሳት መጻሕፍትም ስለርሱ እንተነገረ እግዚአብሔር መሰከረለት። ሰይጣንም ቀንቶበት በገንዘቡና በልጆቹ ላይ ያሠለጥነው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነ። ጻድቅ ኢዮብን ትዕግሥት እግዚአብሔር ስለሚያውቅ አሠለጠነው ለመጪ ትውልድም አርያና ምሳሌ እንዲሆን ፈቀደለት። ስለርሱም ሐዋርያ ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ "እንሆ የጻድቁ ኢዮብን ትዕግሥቱን ሰምታችኋል" አለ።
❤ ከዚህም በኋላም በአንዲት ቀን ገንዘቡ ሁሉ ጠፋ፣ ሥጋውም በደዌ ሥጋ ከራሱ እስከ እግሩ ድረስ ተመታ። በዚህም በአስጨናቂ ደዌ ውስጥ ኖረ እግዚአብሔርንም አመሰገነው። አንዲት ቃልን እንኳ በፈጠረው እግዚአብሔር ላይ አላጒረመረመም ነገር ግን የተወለደባትን ቀን ረገመ። እንስሶቹና ገንዘቡ ሁሉ በጠፋ ጊዜ "እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔርም ነሣ የእግዚአብሔርም ስም የተመሰገነ ይሁን" አለ።
❤ በዚህ መከራ በነበረበት ዘመናት በተራራ ላይ ተጥሎ ሳለ የወዳጆቹና የሚስቱ ዘለፋ በዝቶበት ነበር። እርስዋ እንዲህ ብላ መከረችው "እስከ መቼ ድረስ በሞኝነት ትኖራለህ እንግዲህስ ስደበውና ሙት ዳግመኛ እግዚአብሔርን ደጅ እጠናዋለሁ መከራውንም እታገሣለሁ የቀድሞ ኑሮዬን ተስፋ አደርጋለሁ ትላለህን?" አለችው። "እንዲህስ እንዳትል ከዚህ ዓለም እንሆ ስም አጠራርህ ጠፋ ሴቶች ልጆቼና ወንዶች ልጆቼ ሞቱ እኔም ዘጠኝ ወር ሳረግዝ፣ ሳምጥ፣ ስወልድ ላይረቡኝ ላይጠቅሙኝ በከንቱ ደከምኩ። አንተም በመግል ተውጠህ በትል ተከበህ ትኖራለህ ሌሊትን ሁሉ ስትዛብር ታድራለህ እኔም እየዞርኩ እቀላውጣለሁ ካንዱ አገር ወዳንዱ ቤት እሔዳለሁ ከድካሜ በኔ ላይ ከመጣው ከችግሬም አርፍ ዘንድ ከጧት ጀምሮ ፀሐይ እስቲገባ ድረስ እጠብቃለሁ አሁን ግን እግዚአብሔርን የማይገባ ቃል ተናግረኸው ሙት" አለችው። ኢዮብም ሚስቱን እየተመለከተ ሰማት። "ሥርዓት እንዳልተሠራባቸው ከአሕዛብ ሴቶች እንዳንዲቱ ተናገርሽን ከዚህ ቀድሞ በጎውን ነገር ከእግዚአብሔር እጅ ተቀበልን ከዚህ በኋላ መከራውን አንታገስምን?" አላት። በዚህ ባገኘው መከራ ሁሉ ኢዮብ ጌታን የበደለው በደል የለም። ኢዮብም ወርቅ በእሳት እንዲፈተን ፈጽሞ ተፈተነ።
❤ እግዚአብሔርም በደመና ውስጥ ኢዮብን ተነጋግረው። ከተናገረውም በኋላ ከደዌው ፈወሰው ጥሪቱን ሁሉ ከቀድሞ እጥፍ አደረገለት ሌሎች ልጆችንም ሴቶችና ወንዶችን ሰጠው። ኢዮብም ከደዌው ከተፈወሰ በኋላ መቶ ሰባ ዘመን ኖረ የኖረውም ዘመን ሁሉ ሁለት መቶ አርባ ስምንት ዓመት ነው በበጎ ሽምግልናም እግዚአብሔርን አገልግሎ ግንቦት 2 ቀን በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ ሰው በቅዱስ ኢየብ ጸሎት ይማረን በረከትም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #የአባ_ጳኵሚስ_ረድእ_አባ_ቴዎድሮስ፦ ይህም አባት በገድል የተጠመደ ትሑት ቅን ታዛዥ በበጎ ሥራም ፍጹም ነበረ። ከአባ ጳኵሚስም ዘንድ ከታናሽነቱ ጀምሮ መነኰሰ ለፈጣሪውም እንደሚታዘዝ ይታዘዘው ነበር። ስለዚህም አባ ጳኵሚስ እጅግ ወደደው በላዩም የመንፈስ ቅዱስ ጸጋ አድራበታለችና በአንድነት ለሚኖሩ መነኰሳት ሁሉ አጽናኝና አረጋጊ ሆነ። ጥበቡና ዕውቀት ነበረውና በዕድሜው ሕፃን ሁኖ ሳለ አባ ጳኵሚስ ገሣጭና መካሪ አድርጎ ሾመው።
❤ ከአባ ጳኵሚስ ዕረፍት በኋላ በአባቱ በአባ ጳኵሚስ ፈንታ አበ ምኔት ሁኖ ተሾመ። ይህም አባት ትሕትናው የበዛ ነው ከዚህ ከኃላፊው ዓለም ክብር ይሸሽ ነበር የአገልግሎቱንም በጎ ሥራ ፈጽሞ ወደ ወደደው እግዚአብሔር ግንቦት 2 ቀን ሔደ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ ሰው አባ ቴዎድሮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት 2 ስንክሳር።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፩ (1) ቀን።
❤ እንኳን ለኢትዮጵያዊው ጻድቃን #ለአቡነ_ተክለ_ሃይማኖት_ለአክስት_ልጅ_እንደ_ነቢዩ_ኤልያስ እሳት ከሰማይ አውርደው በሸዋ ክፍለ አገር ፈንታሌ ተራራ ላይ ሰሪቲ ለምትባ ጠንቋይ እየተላላኩ ሕዝቡን የሚያስቱና የሚያሰቃዩ #አራት_መቶ_ሰባ_ሽህ_ሦስት_መቶ_አጋንንት በአንድ ጊዜ ላጠፋ #ለታላቁ_አባት_ለአቡነ_ቀውስጦስ ለልደታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ቀውስጦስ፦ ጻድቁ የተወለዱት ሸዋ ክፍለ አገር በወግዳና ቡልጋ ውስጥ ሲሆን አባታቸው ቅዱስ ገላውዴዎስ እናቸው ቅድስት እምነ ጽዮን ይባላሉ። የጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት እናት እግዚእ ኃርያ እና እምነጽዮን ታናሽና ታላቅ እህትማማቾች ናቸው።
❤ ቅዱስ ገላውዴዎስና ቅድስት እምነ ጽዮን እግዚአብሔር የተባረከ ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ ለዓመታት በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስዕል ፊት ሲጸልዩና ሲለምኑ እመቤታችን በስዕሏ ላይ አድራ አናገረቻቸው፤ እንዲህም አለቻቸው፦ " አንድ ልጅ አስቀድማችሁ ትወልዳላችሁ፤ የሚወለደውም እኔ በተወለድኩበት ግንቦት1 ቀን ዕረፍቱም በእኔ ዕረፍት ቀን ጥር21 ነው እሱም የሰማያዊ ንጉሥ ጭፍራ ይሆናል" አለቻቸው። በቃሏ መሰረትም ግንቦት1 ቀን ጻድቁ አቡነ ቀውስጦስ ተወለዱ።
❤ ጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ የዚህን ዓለም ተድላ፣ ደስታና ጠዐም ንቀው ፈለገ ሐዋርያትን ተከትለው በሸዋ፣ በከፋና በጅማ ዞረው የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል በማስተማር አረማውያን፣ ነገሥታትና ባላባቶች የሚደርስባቸውን መከራና እንግልት በመታገስ በተጋድሎ ፀንተው ብዙውን ሕዝብ ከአምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር ከኃጢያት ወደ ጽድቅ መልሰዋል። በተለይም በሸዋ ክፍለ አገር ፈንታሌ ተራራ ላይ ሰሪቲ ለምትባ ጠንቋይ እየተላላኩ ሕዝቡን የሚያስቱና የሚያሰቃዩ ፬፻፸ሺ፫፻ (አራት መቶ ሰባ ሽህ ሦስት መቶ) አጋንንትን እንደ ነቢዩ ኤልያስ በጸሎታቸው ከሰማይ እሳት አውርደው ተራራውን ደምስሰው አጋንንቱን አቃጥለዋል። ሕዝቡንም ለጣዖትና ለጠንቋይ ከመገዛት አድነውታል።
❤ ጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ በብዙ ተጋድሎ ሲኖሩ በሰማዕትነት ያርፉ ዘንድ ስለ እግዚአብሔር መንግሥትና ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚተጉ እንጂ የዚህን ዓለም መንግሥት ሀብትና ስልጣን የማይሹ እውነተኛ መናኝ ነበሩና የታናሽ ወንድማቸው የአፄ ይኩኖ አምላክ ልጅ አፄ አምደ ጽዮን የአባቱን እቁባት በማግባቲ "ይህንን ልታደርግ አይገባህም"። ብለው እንደ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ቢገስጹት ዐሥራ አንድ አሽከሮቹን በሌሊት ልኮ ከበዩ ወደ እንሳሮ አገር ካስወሰዳቸው በኋላ ኮሶ አረህ ከሚባለው አፋፍ ላይ በእኩለ ሌሊት በጦር ጎናቸውን አስወግቶ ደማቸውን አስፈሰሰ። ደማቸውም እስከ ታላቁ ወንዝ ጀማ ድረስ ሆነ። የፈሰሰው ደማቸውም ቀይ ብርሃን ሲሆን የሌሊቱ ጨለማ ከፀሐይ ሰባት እጅ የሚበልጥ ብርሃን በአውራጃዎቹ ሁሉ ታየ። በዚህ የተነሳ እስከ ዛሬ ድረስ አገሩ ቀን ተብሎ ይጠራል።
❤ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ሳትለይ በስቃይ ላይ ሳሉም በዘመናቸው ሁሉ ስለነበራቸው ተጋድሎ፣ ንፅህናና ምናኔ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምንና ቅዱሳን መላእክትን አሰከትሎ በክበበ ትስብእት በግርማ መለኮት መጣና ቃል ኪዳን ሰጣቸው። እንዲህም አላቸው፦ "እኔ ለአንተ አይን ያላየውን ጆሮ ያልሰማውን መንግሥተ ሰማያትን አዘጋጀውልህ። በዘመንህ ስላሳለፍከው ክርስቲያናዊ ፍፁም ተጋድሎህ ሰባት የብርሃን አክሊል (ዘውዶችን) ያዘጋጀውልህ ሲሆን ሁለቱ እንደ እነ ነቢዩ ኤልያስና ነቢዩ ሳሙኤል ለሆነ ንጽህናህ፣ ሁለቱ እንደ እነ ቅዱስ ጴጥሮስና ጳውሎስ ለሆነ የወንጌል ስብከትህ፣ ሁለቱ እንደ እነ ቅዱስ ጊዮርጊስና ቅዱስ ፊቅጦር በትዕግሥት ስለተጋደልክ፣ አንዷ ስለ ልብህ ርህራኄ ናት ብሎ አጎናፅፏችኋል። እንዲሁም ስለ እኔ ምስክርነት የሞትክባት ምድር እንደ ዳዊት አገር እንደ ኢየሩሳሌም ትሁንል ወደእርሷ የሄደውንም ሁሉ ወደ ኢየሩሳሌም ወደ መቃብሬ ጎልጎታ እንደሄደ እቆጥርለታለሁ። ብዙ ኃጢያት የሥራ ሰው ንስሐ ገብቶ በዚያች አገር በስምህ ጥቂት ምጽዋት ቢሰጥ እኔ ኃጢያቱን እደመስስለታለሁ፤ በጠበልህም ቢጠመቅ በደሉን አጠፋለታለሁ ደምህ በምድሪቱ ፈሷልና፤ በዕረፍትህ ዕለት ለቤተ ክርስቲያንህ ለቅዱስ ቁርባን ስንዴ፣ ወይንና ዕጣን ያቀረበ ኃጢያት የሰራ ተነሳሂ (ንስሃ የገባ) ሰው ቅዱስ ሥጋውንና ክብር ደሙን እንደተቀበለ ንፁህ ሰው አደርገዋለሁ፣ ለስምህ መታሰቢያ በታነጸው ቤተ መቅደስ በንጽህና ቅዱስ ሥጋውንና ክብር ደሙን የሚቀበል (የሚቆርብ) ሰው ራሱን፤ ቤተሰቡንና ባልንጀሮቹን ያድናል"።
❤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ ይህንን ቃል ኪዳን ሰጥቷቸው ዐረገ። ቅዱሳን መላእክትም ነፍሳቸውን ከስጋቸው በክብር ለዩ። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም በሰማይ መካከል ነፍሳቸውን በፈገግታ ተቀበለች። የዕረፍታቸውም ዕለት እመቤታችን ባለፈችበት ጥር 21ቀን በመሆኑ እመቤታችንም "መታሰቢያህን ለሚያደርጉ ሁሉ በልጄ በረከት እበርካቸዋለሁ" ብላ ቃል ኪዳን ገባችላቸው። ጻድቁ አባታችን አቡነ ቀውስጦስ ባረፉበት ዕለትም ብዙዎች ከዴዌአቸው ተፈውሰዋል። የጻድቁ አባታችን በረከትና ፈውስ አሁንም ድረስ ደማቸው በፈሰበትና አፅማቸው ባረፈበት ቦታ ሁሉ እየታየ ብዙ ምዕመናን ፈውስ ነፍስና ፈውሰ ሥጋ እያገኙበት ነው።
❤ ገዳመ ቀውስጦስ የሚገኘው ከአዲስ አበባ በስተሰሜን 120ኪ.ሜ ርቀት ላይ ሲሆን ወደ ደብረ ሊባኖስ በሚወስደው መንገድ ሙከጥሪ ከተማ ሲደርሱ ወደቀኝ በመታጠፍ ሜጤና ባዩ በሚባለው አካባቢ ልዩ ስሙ ተግባሬ (መገንጠያ) ከሚባል ቦታ ነው። ከጻድቁ አቡነ ቀውስጦስ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ አቡነ ቀውስጦስ (በአጭሩ) ከሚለው መጽሐፍ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፩ (1) ቀን።
❤ እንኳን ለመጋቤ ብርሃናት ለሊቀ መላእክት #ለቅዱስ_ራጉኤል እመቤታችን በሊባኖስ ተራራ ስትወለድ ብርሃኑን ለገለጸበትና ለታላቁ አባት ለሄኖክ ምሥጢራትን ለገለጸበት ዓመታዊ በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ቅዱስ_ራጉኤል፦ በእንግሊዘኛ ሲፃፍ Raguel ሲነበብ ‘’ራጉዌል’’; በግሪክ ሲፃፍ: Ῥαγουὴλ ሲነበብ:Rhagouḕl; በዕብራይስጥ ሲፃፍ: רְעוּאֵל ሲነበብ:Rəʿūʾēl እግዚአብሔርን ቃል አስከባሪ(የሕግ መላዕክ) ማለት ነው፡፡ የሰይጣናትን ጥፋት የሚበቀልም ነው.. . ፤ በብርሃናት ላይ የተሾመም መልአክ ነው ፤ በዚህም መጋቤ ብርሃን ይባላል፡፡ የወደቁ መላዕክትን ይቆጣጠራል፡፡
❤ ራጉኤል ሊቀ መላእክት:- ራጉኤል ማለት የብርሃናት አለቃ ማለት ነው። የብርሃናት አለቃ ሲባል ፀሐይን፣ ጨረቃን እና ከዋክብትን በማመላለስና ለሰው ልጆች፣ ለአዝርዕት፣ ለእንስሳት፣ ለአራዊት ሁሉ ብርሃንን የሚመግብ ነው ማለት ነው። አንድም ራጉኤል ማለት የሚበቀል ማለት ነው። የሚበቀል ነው ማለት በቀል የሚገባው ለጠላት ነው የሰው ልጅ ጠላት ደግሞ ዲያብሎስ ነው፤ ስለሆነም ቅዱስ ራጉኤል እግዚአብሔርን አምነው ሕገ እግዚአብሔርን ጠብቀው በፍርሐተ እግዚአብሔር አምልኮቱን ለሚፈጽሙ ሁሉ ጠላት ዲያብሎስን የሚያርቅላቸው ወደ እነርሱም ፈጥኖ በመድረስ የሚታደጋቸው ነው ማለት ነው። ሔኖክ 6:4፡፡ አንድም ራጉኤል ማለት የኃያላን ኃያል እግዚአብሔር ማለት ነው። የኃያላን ኃያል ያለው የእግዚአብሔርን ኃያልነት ከምድር ፍጥረታት ዘንድ ኃያል ከሚባሉት ሁሉ ሊገለጽ የማይችል ኃያልነቱን ለመግለጽ ኃያልነቱም ከ እስከ የሌለው መሆኑን ለመግለጽ የተቀመጠ ነው። ስለዚህ እግዚአብሔር ኃያል የኃያላን ኃያል መሆኑን የሚገልጽ ትርጉም አለው። አንድም ራጉኤል ማለት ጽኑ እግዚአብሔር ማለት ነው። የእግዚአብሔር አምላክን ጽኑነት ለማጉላት ሲል ጽኑ አለው። እግዚአብሔር የማይወላውል የማይዋዥቅ የማይከዳ ነው ለማለትም ሲል ይህ ስያሜ ተሰጠው። የእግዚአብሔርን ጽናት የሚያሳይ ትርጉም ያለው ስያሜ ነው።
❤ የሊቀ መላእክት የቅዱስ ራጉኤል አገልግሎት እና ስልጣን፡- እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከዚህ ዓለም በ64 ዓመቷ ካረፈች በኋላ ሥጋዋ ወደ ዕፀ ሕይወት ሲነጠቅ (ሲያርፍ) አብሮ ለሄደው እና ሥጋዋን በእጣን ሲያጥን ለነበረው ለፍቁረ እግዚ ለቅዱስ ዮሐንስ ኅብስትን የመገበ መልአክ ነው። በብርሃናት ሁሉ ላይ የሰለጠነ መልአክ ነው። ከአዳም ሰባተኛ ትውልድ የሆነ በእግዚአብሔር ፊት ግሩም ያማረ ሥራው የሰመረ እስከዛሬ የሞት ወጥመድ ያልያዘው የሞት ጥላ ያላረፈበት ነብዩ ሄኖክ "ከቅዱሳን መላእክት አንዱ የሆነ ጸላዒ ዲያብሎስን የሚበቀለው ራጉኤል በብርሃናት ላይ የሰለጠነ ነው" ሲል ስለ እርሱ ተናግሯል፡፡ እግዚአብሔር ዓለምን ይቆጣጠር ዘንድ የሾመው ታላቅና ቅዱስ መልአክ ነው። (ድርሳነ ራጉኤል ዘ ጥቅምት ገጽ 23) አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር ለመተካት ዓለምን የመለወጥ ሥልጣን የተሰጠው ቅዱስ መልአክ ነው።
❤ ከእግዚአብሔር የጌትነቱ አዳራሽ ይገባና ይወጣ ዘንድ ስልጣን ያለው ከኪሩቤልና ከሱራፌል ጋር ከፈጣሪ የጌትነት ዙፋን ፊት የሚቆም ነው። ሎጥን ሚስቱንና ልጆቹን ከእሳተ ጎመራ ያዳነ የበለአምን እርግማን ወደ በረከት የለወጠ እርሱ ነው። በቅዱስ ራጉኤል ስነ ሥዕል ላይ የምናየው ይህ ባለ አራት እራስ ንስር ከአርባእቱ ኪሩቤል አንዱ ገጸ ንስር ነው። የሥላሴን የጌትነት ዙፋን የሚሸከሙ አርባዕቱ እንስሳት ናቸው። የሚሸከሙት ሲባል ጫማ የሰውን ልጅ እንደሚሸከመው እንጂ ችለውትስ አይደለም። እነርሱም የሰው ገጽ፣ የእንስሳ ገጽ፣ የንስር ገጽ እና የአንበሳ ገጽ ያላቸው ናቸው። ይህንንም ነብዩ ሕዝቅኤል "ለእያንዳንዱ እንስሳትም የተለያዩ አራት ገጾች ነበሩት። ይህውም በስተቀኝ በኩል የእንስሳ መልክ፣ በስተ ግራ የላም ገጽ፣ በበስተ ኋላም የንስር ገጽ የሚመስሉ ነበሩ" ብሏል ሕዝ 1፡6-13፡፡
ከዚህ የምንገነዘበው ነገር ቢኖር አራት ገጽ ካላቸው ኪሩቤል መካከል አንዱ ንስር መሆኑን ነው። ቅዱስ ራጉኤል ደግሞ የእነዚህ ኪሩቤል አለቃቸው (የጌትነቱ ዙፋን ጠባቂ) በመሆኑ በዚህ ምክንያት ማለትም እነርሱ ዙፋኑን ተሸካሚ እርሱ ደግሞ አጠገባቸው መቆሙ መንበሩን ጠባቂ በመሆኑ በዚህ አይነት የአገልግሎት ድርሻ አብረው ሊሳሉ ችለዋል።
❤ ቅዱስ ያሬድም በድጓው "አርባእቱ እንስሳ አልቄንጥሩ እንደሚባለው ንስር ፊት ለፊት አይታዩም አንዱም በመራቸው ይሔዳሉ እነርሱም እያንዳንዳቸው አራት ገጽ ሲኖራቸው ሳያርፉና ሳይደክሙ የሚያመሰግኑ ናቸው" በማለት ጽፏል። አንድም መላእክት ነገደ ሱራፌል እና ነገደ ኪሩቤል በመባል ይከፈላሉ። በነገደ ሱራፌል እነ ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ሩፋኤል ወዘተ ሲሆኑ በነገደ ኪሩቤል ደግሞ ቅዱስ ገብርኤል ቅዱስ ራጉኤል ወዘተ ያጠቃልላል። ስለዚህ ቅዱስ ራጉኤል ነገዱ ከነገደ ኪሩቤል ነው በዚህም ላይ የነገደ ኪሩቤል አልቄንጡራ (አራት እራስ ንስር) አለቃቸው ቅዱስ ራጉኤል ነው። በዚህም ምክንያት አብረው ሊሳሉ ችሏል። አንድም መላእክትን ሁሉ እንደ እየስራቸው መለያ ሥነ ሥዕላቸውን መሳል ልማድ ነውና። ለምሳሌ ቅዱስ ሚካኤል ከቅድስት አፎምያ ጋር፣ ቅዱስ ገብርኤል ከሠለስቱ ደቂቅ ጋር፣ ቅዱስ ዑራኤል ከእዝራ ሱቱኤል ጋር እንደሚሳሉት ሁሉ ማለት ነው። በዚህም መሰረት ቅዱስ ራጉኤልም ዐቃቤ መንበር ነውና መንበሩን በሚሸከሙት ኪሩቤል ከሚመሰሉት ንስሮች ጋር አብረው ሊሳሉ ችለዋል፡፡
❤ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ራጉኤል ከአምላክ የተሰጠው ቃል ኪዳን እግዚአብሔር አምላክ በስሙ ለታመኑት ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማዕታት፣ ሐዋርያት፣ ዘወትር ያለማቋረጥ ስሙን ለሚጠሩት ቅዱሳን መላእክት ሁሉ ቃል ኪዳን ሰጥቷቸዋል። የሰጣቸውም ቃል ኪዳን ዘላለማዊ እና ሊሻር የማይችል ነው። ለመላእክት አለቃ ለቅዱስ ራጉኤልም ይህን ቃል ኪዳን ሰጥቶታል "የራጉኤል አምላክ ይቅር በለኝ በማለት አንዲት ቃልስ እንኳን ቢናገር እንደ ወዳጄ እንደ አብርሃም፣ እንደ ባለሟሌም እንደ ይስሐቅ፣ እንደ አከበርኩትም እንደ ያዕቆብ ክብርን ባለሟልነትን እሰጠዋለሁ በራሱ ላይም አክሊል አቀዳጀዋለሁ ዕረጅም ዘመናት ሰፊ ወራትም እሰጠዋለሁ" ሲል ቃሉን ሰጥቶታል፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ራጉኤል መስከረም 1 ቀን ከሊቃነ መላእክት በ4ተኛ ደረጃ የተሾመበት ዕለት ሲሆን ግንቦት 1 ቀን ደግሞ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በሊባኖስ ተራራ ስትወለድ ብርሃኑ የገለጠበትና ለታላቁ አባት ለሄኖክ ምሥጢራትን የገለጸበት በዓሉ ነው፡፡ አምላከ ቅዱሳን ልዑል እግዚአብሔር ከመልአኩ ቅዱስ ራጉኤል ረድኤትና በረከት ያሳትፈን በጸሎቱ ይማረን! አሜን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ የተባረከ #የግንቦት_ወር_መዓልቱ_ዐሥራ_አራት ሰዓት ነው ከዚህም ይጨምራል።
❤ #ግንቦት ፩ (1) ቀን።
❤ እንኳን #አምላክን_ለወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ ለጸናች #ለእናታችን_ለእመቤታችን_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም ለልደቷ መታሰቢያ ዓመታዊ የንግሥ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አምላክን_የወለደች_የእመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም_ልደት፦ እርሷም ለሰው ሁሉ ወገን ድኅነት የሆነባት ናት። ከወንዶች ወገን የከበረ አባቷም ስሙ ቅዱስ ኢያቄም ከሴቶች ወገን የከበረች ሚስቱ ቅድስት ሐና ይባላሉ። ሁለቱም ልጅ በማጣት ሲያዝኑ ኖሩ በዚያ ወራት የመካኖችን መብዓ ካህናቱ አይቀበሉም ነበርና። እርሱም ከሰው የሚደርስባቸውን ሽሙጥና ኀዘናቸውን ያርቅላቸው ዘንድ በቀንና በሌሊት ወደ እግዚአብሔር ፈጽሞ ይማልዱ ነበር። ሰውን የሚወድ እግዚአብሔርም ከዘራቸው ለዓለሙ ሁሉ መድኃኒት ይሆን ዘንድ መልካም የሆነ ኀሳባቸውን ተመለከተ።
❤ ክብር ኢያቄምም አርባ ቀን እስኪፈጸም በተራራ ውስጥ ቁሞ ሲጸልይ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገልጸለትና ለዓለሙ ሁሉ ድኅነት የሚደረግባት ዘር እደሚሰጠው አበሠረው። በፍጹም ልብ አምኖ ከተራራው ወረደ ለተመሰገነች ሚስቱ ለቅድስት ሐናም ከእግዚአብሔር መልአክ የሰማውን ያንን ራእይ ኢያቄምም ለሚስቱ ሐናን እንዲህ አላት "ሰማያት ሲከፈቱ አየሁ፤ ነጭ ወፍ መጣ በራሴ ላይም አረፈ" እንደዚህም ሁሉ ሐናም "ርግብ በራሴ ላይ ስትቀመጥብኝ በማሕፀኔም ስታድር አየሁ ገባች" አለችው። ነገራት ቃሉ እውነት እንደሆነ እርሷም አመነች ልዑል እግዚአብሔርም አመሰገኑት።
❤ የተመሰገነች ቅድስት ሐናም ከእርሷ የሚወለደውን በዘመኑ ሁሉ በቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ ታደርገው ዘንድ ለእግዚአብሔር ስለትን ተሳለች። ከዚህም በኋላ ይቺን የከበረች ሕፃን ነሐሴ ሰባት ቀን ተፀነሰች ከስድስት ወር በኋላም የብፅዕት ሐና መፅነስ ታወቀ። ዘመዶችም ሰሙ ወደ እርሷ መጥተውም "የምንሰማው ይህ ነገር አውነት ነውን? ዘመንሽ ካለፈ በኋላ በአንቺ ላይ የተደረገው ነገር ምንድን ነው?" አሏት። ከሐና ዘመዶች ወገን የአርሳባን ልጅ የምትሆን አንዲት ዐይኗ ማየት የተሳናት አንዲት ሴት ነበረች። "የሰማሁት እውነት ነውን?" ብላ የሐናን ማኅፀን ዳሰሰች። "እህቴ ሆይ ሽማግሌ ስትሆኚ እንዴት ፀነስሽ" አለቻት። ዳግመኛም ማየት የተሳነው ዐይኗን ዳሰሰችው ያን ጊዜም ዐይኗ ተከፈተላት ብርሃንንም አየች። "ብፅዕት ሐና ሆይ ለአንቺ ብፅዓን ይገባሻል ፅንስሽ በማኅፀንሽ እያለ ገና ሳይወለድ በሽተኞችን የፈሰ በግልጽ ከታየ ከማሕፀንሽ ከወጣማ ምን ያህል ይፈውስ ይሆን?" እንደዚሁም ሁሉ ብዙ በሽተኞች መጥተው እየዳሰሱ ከበሽታቸው ይፈወሱ ይድኑም ነበር። ይህ ነገርም በእስራኤል ሽማግሎዎች ሁሉ ዘንድ ዕፁብ ድንቅ ሆነ።
❤ ቅድስት ሐናም የፅንሷ ወራት በተፈጸመ ጊዜ በግንቦት አንድ ቀን ከፀሓይ ይልቅ ፈጽማ የምታበራ ሴት ልጅ በሊባኖስ ተራራ ላይ ወለደች፤ የመልኳም ደም ግባት ከመዓር ከሦከር ይልቅ ደስ ያሰኛል፤ የመዓዛዋም ሽታ ከሽቱ ሁሉ ይበልጣል። ዘመዶቿና ጐረቤቶቿም በሰሙ ጊዜ ፈጽሞ ደስ አላቸውና ተሰብስበው ወደስዋ መጡ ወደሷም መጥተው ልጅዋን ባዩ ጊዜ ፈጽመው አደነቁ እርስ በርሳቸውም "እንደዚች ያለች ብላቴና ከቶ አይተን አናውቅም" ተባባሉ ጸጋ እግዚአብሔር በርሷ ላይ አድሯልና የእግዚአብሔርም ብርሃን በሰውነቷ ሁሉ መልቷልና። ከኢያቄምና ከሚስቱ ከሐና ጋራ ደስ እያላቸው የእግዚአብሔርን ቸርነት እየተናገሩ ሰባት ቀን ተቀመጡ ያችንም ብላቴና ስሟንም ማርያም ብላ ሰየመቻት ትርጓሜውም እመቤት ነው ደግሞም ሀብትና ስጦታ ማለት ነው። በእውነት የዓለሙ ሁሉ እመቤት ናት ሁላችን በእርሷ ሰማያዊ ሀብት ልጅነትን ያገኘንባት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የሥጋና የነፍስ መድኃኒት የሆነች እርሷን እናቱን ለሰጠን በረከቷም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን። ምንጭ፦ ተአምረ ማርያም፣ ድርሳነ ቅድስት ሐና ወኢያቄምና የግንቦት 1 ስንክሳር ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወለገጽኪ ይትመሀለሉ ኵሎሙ አሕዛብ ብዑላነ ምድር። ኵሉ ክብራ ለወለተ ንጉሠ ሐሴቦን። በዘአዝፋረ ወርቅ ዑፅፍት ወኊብርት"። መዝ 44፥12-13። የሚነበቡት ወንጌል ማቴ 1፥1-18።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን። ያበድሮን እግዚአብሔር ለአናቅጸ ጽዮን። እምኵሉ ተዐይኒሁ ለያዕቆብ"። መዝ 86፥1-2። የሚነበቡት መልዕክታት ገላ 4፥1-13፣ 1ኛ ጴጥ 8፥13፣ የሐዋ ሥራ 7፥44-51 ወይም 1፥12-15 የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥39-57። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን ማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የልደታ ለማርያም በዐልና የመልአኩ የቅዱስ ራጉኤል በዐል፡፡ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ ሌሊት ሲሆንም ይገድሉት ዘንድ እስከሚሰበሰቡ ድረስ ወደ እስር ቤት አስገቡት፡፡ መንፈቀ ሌሊት ሲሆንም በሮች ተዘግተው ጠባቂዎችም ተኝተው ሳሉ ታላቅ ንውጽውጽታ ሆነ የእግዚአብሔር መልአክም "የግብጽን አገራት ሁሉ የምታረጋጋ የእግዚአብሔር አገልጋይ ማርቆስ ሆይ ስምህ በሰማይ ባለ የሕይወት መጽሐፍ ተጽፏል ከሐዋርያት ቁጥርም ተቆጥሮአል፤ መታሰቢያህም አይረሳም፤ በምድርም ስፍር ቁጥር የሌላትን ሥልጣን፣ ጸጋ ኃይል እነሆ ሰጥቶሃልና፤ ነፍስህ በሰማይ ይሆናል ሥጋህም በመሬት አይጠፋም" አለው፡፡
❤ ቅዱስ ማርቆስም ይህን ምሳሌ በተመለከተ ጊዜ እጆቹን ወደ ሰማይ አነሣ "ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ከፊትህ አልጣልኸኝም፣ ከቅዱሳን ማኀበርም ደምረኸኛልና አመሰግንሃለሁ፤ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ እለምንሃለሁ ነፍሴን በሰማይ ተቀበላት፤ ከፊትህም አትተወኝ" አለ፡፡ ይህን በተናገረ ጊዜ ጌታችን አዳኝ ከሆነው ከሕማሙ በፊት በመቃብርም ከመጨመሩ አስቀድሞ በሐዋርያት መካከል እንደነበረ ሆኖ ታየው፡፡ "የመረጥሁህ ማርቆስ ሆየ ሰላሜ ከአንተ ጋር ይሁን፤ በወንጌል አስተማርሁህ፤ እነሆመ መከራን ከመቀበሌ አስቀድሞ ከጓደኞችህ ከሐዋርያት ጋር አንደሆንሁት በአርአያ ተገለጥኩልህ፤ ከእነርሱ ምንም ጉድለት እንዳይኖርብህ" አለው፡፡ ቅዱስ ማርቆስም "ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ከጸጋህ ታላቅነት የተነሣ አመሰግንሃለሁ፤ በሥጋህ አንደነበርህ ሁነህ አንዳይህ የተገባኝ አድርገኸኛልና” አለው "ስለተቀደሰው ስምህ መከራን እቀበል ዘንድ ትዕግሥትን አድለኸኛልና" ጌታችንም ሰላምን ሰጠውና በታላቅ ምስጋና ወደ ሰማይ አረገ ፡፡ ሲነገም የአገሩ ሰዎች ተሰበሰቡ፤ ከእስር ቤትም አወጡት በሰንሰለትም አሰሩት፤ ዳግመኛም በላሞች ቦታ እንደፍየል እንጐትተው እያሉ በከተማው ጐተቱት፡፡
❤ ብፁዕ ማርቆስም ምስጋናን አቀረበ በሰማይ ተገለጠ፡፡ በየአገሩ ከጎተቱት በኋላም ደሙ በየመንገዱና በየአደባባይዋ ሞላ "ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ነፍሴን በእጅህ ሰጠሁ" አለ፡፡ ይህን ከተናገረ በኋላም ሚያዝያ 30 ቀን ዐረፈ፡፡ ሁሉም አረማውያን ቅዱስ ማርቆስ አንዳረፈ በተመለከቱ ጊዜም ሥጋውን በእሳት ያቃጥሉት ዘንድ አውበካልዮን በምትባል ቦታ ጽኑ እሳትን አነደዱ፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድም ጨለማና ቀዝቃዛ ነፋስ ሆነ፤ ፀሐይም ብርሃኑን ሰወረ፡፡ በዚች ዕለትም እስከ ምሽት ድረስ መብረቅ፣ ነጎድጓድ፣ ዝናምና ብርድም ሆነ፤ ከአገሩ ሰዎች ከሽማግሌዎች ብዙዎች ወደቁ ከእነርሱም ብዙዎቹ ሞቱ ያን ጊዜ ፈሩ ሂደወም ከአገሩ ሰዎች የቅዱሱን ሥጋ አኖሩት፤ የተዘባበቱበትም አሉ “ ታላቁ አምላክ ሆይ የዚህን ሰው ነፍስ ተቀበላት በዚች ዕለት የልደቱ ዕለት ናትና” አሉ፡፡ ምዕመናን ወንዶች ደረሱና የቅዱሱን ሥጋ ከእሳቱ ወሰዱት ጸሎት ወደሚጸለይበት ቦተም አደረሱት በእርሱ ላይም ተሳሉ፣ ምስጋናንም አቀረቡ እንደ ሥርዓታቸውም እንደ አገሩ ሰዎች ገነዙት በቆፈሩለት መቃብርም ቀበሩት፡፡ መታሰቢያውንም በደስታ፣ በምሥጋና አብዝተው አደረጉ፣ አበዙ በአገሩ መሠረታዊ ቦታም አስቀመጡት፡፡
❤ የሰማዕታት መጀመሪያ በግብጽ ስለ ጌታችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ደሙን ያፈሰሰ የወንጌላዊው የቅዱስ ማርቆስ ዕረፍቱ በሚያዝያ ወር መጨረሻ በ30 ሠላሳኛው ቀን ዕለቱመ ሰኞ ጠዋት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ በተገለጸ 68 ዓ.ም ወደ ሰማይ ባረገ በ35 ዓ.ም በታላቋ አገር በእስክንድርያ ሆነ ፡፡ ከሐዋርያውና ከወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን፡፡ በጸሎቱ ይማረን!፡፡ ምንጭ፦ ገድለ ሐዋርያት ፤ የሚያዝያ 30 ስንክሳር ፤ ክብረ ቅዱስ ማርቆስ ከሚለው መጽሐፍ።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ክቡር ሞቱ ለጻድቅ በቅድመ እግዚአብሔር። እግዚኦ አነ ገብረከ። ገብረከ ወልደ ዓመትከ"። መዝ 115፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኃይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ጢሞ 4፥1-20፣ 1ኛ 5፥12-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 15፥36-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 10፥1-19። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ማርቆስ የዕረፍት በዓልና የትንሣኤ ሰሞን ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ ቅዱስ ማርቆስ በኢየሩሳሌም የእናቱ የማርያም ቤት የደቀ መዛሙርቱ መገናኛና መሰባሰቢያ ስለነበር ደቀመዛሙርቱን የበለጠ እንዲያውቃቸውና እንዲቀርባቸው ከፍተኛ አስተዋፅኦ ከማድረጉም በላየ በተለይም ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር ባለው የጠበቀ ዝምድናና ቀረቤታ ለቅዱስ ጴጥሮስ የሃይማኖት ልጅ በመሆንና ለአገለግሎቱም ፍጹም መንፈሳዊና እውነተኛ የክርስቶስ ምስክር ለመሆን በቅቷል፡፡ ቅዱስ ማርቆስ በልጅነቱ በኢየሩሳሌም ለመኖር በመታደሉ በዚያም ዘመን ይሰጥ የነበረውን ትምህርት የማግኘት ዕድል ገጥሞት ነበርና የዕብራይስጥ፣ የላቲንና የግሪክ ቋንቋዎችን ያውቅ ነበር፡፡
❤ ቅዱስ ማርቆስ ወንጌልን መስበክ የጀመረው ገና በወጣትነቱ ነበር በመጀመሪያ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር አብሮ ያስተምር ነበር፡፡ በግብረ ሐዋርያት አንደተገለጸው ቅዱስ ማርቆስ ከቅድስ ጳውሎስና ከቅድስ በርናባስ ጋር ይሰበክ ነበር፡፡ ከዚያም በፊት ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር በኢየሩሳሌምና በይሁዳ አስተምሮአል፡፡
❤ ቅዱስ ማርቆስ ንጹሕና ድንግል መሆኑን መልካምነቱንና ትምህርቱን ተመልክቶ ቅዱስ ጴጥሮስ ለግብጽና ለአካባቢዋ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት አድርጎ ሾመው፡፡ በግብጽ አገሮች በሎኒያ፣ በመርቅያ፣ በጣውንቄ፣ በበርቃ ለመጀመሪያ አስተማረ እርሱ ነው፡፡ ወንጌልን አስተማራቸው፡፡ አዳኝ በሆነ በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንንም አስተማራቸው፡፡ ሁሉም የዚያች አገር ሰዎች ልቡናቸው የደነደነ ነበሩ በርኵሰት ሁሉ የተሞሉ አማልክትንም ያመልኩ ነበር፡፡ ሰይጣንን በማምለክም ይኖሩ ነበር፡፡ በየቦታው በየመንገዱም ሁሉ ምኩራቦችን የአማልክትን ቤት ይሠሩ ነበር፡፡ መድኃኒትን፣ ዝሙትንም ያደርጉ ሕጻናትን ይገድሉ በደማቸው መድኃኒትን ያደርጉ ነበር፡፡
❤ ቅዱስ ማርቆስም ወደ ሐዋርያት በሄደ ጊዜ አስቀድሞ በርቃ ደረሰ፡፡ ዘመዶቹ ከእነርሱ ወገን ናቸውና፡፡ እግዚአብሔርን ቃልም አስተማራቸው በመካከላቸው ብዙ ተአምራትን አደረገ፤ በሽተኞችን ፈወሳቸው ለምጻሞችንም አነጻቸው፤ በእርሱ ላይ በአደረው ጸጋም አጋንንትን አስወጣ፤ ብዙዎችም በትምህርቱ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ አምላኮቻቸውንም (ጣዖቶቻቸውንም) ሰባበሩ፤ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስምም አጠመቃቸው፡፡
❤ በዚያ ቦታም ወደ እስክንድርያ ይሄድ ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ተገለጠለት፡፡ በዚያም መልካም ተዘራባት ይኸውም የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ወንጌላዊው ብፁዕ ቅዱስ ማርቆስም ለጦርነት እንደተዘጋጀ ጎልማሳ ሆነ ወንድሞቹንም ሰላም አላቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያ ቦታ ቅዱስ ወንጌልን አስተምር ዘንድ ወደ እስክንድርያ እንድሄድ አዝዞኛል" አላቸው፡፡ እነርሱም ሸኙት በመርከብም ተሳፍሮ ወደ እስክንድርያ ሄደ በደረሰ ጊዜም ወደ ከተማው በር ገባ የጫማው ማሠሪያም ተቆረጠ "በቅንነትም መንገድ ፈጠነች" አለ በዚያም ከከተማው መግቢያ ጫማ ሰፊ ነበር፡፡ ቅዱስ ማርቆስም እንዲሰፋለት ለርሱ ሰጠው ሲሰፋም ጣቱን ወግቶ ሰነጠቀው ከእርሱም ደም ፈሰሰ በዩናኒም ቋንቋ "ኢታስታያስ" አለ ትርጓሜው አንድ እግዚአብሔር ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ማርቆስም "ስሙን የምትጠራው አውቀኸው ነውን" አለው "እንጠራዋለን እንጂ አናውቀውም" አለ፡፡ ቅዱስ ማርቆስ በጣቶቹ ላይ መራቅ ጨመረና አፈር ወሰደ ያን ጫማ ሰፊ ቀባው "በሕያው አግዚአብሔር ልጅ በኢየሱስ ስም አጅህ ትፈወስ" አለው፡፡ ስለዚህም ተፈወሰች ጫማ ሰፊውም በሥልጣኑ በቃሉ ያደረገውን ድንቅ ተአምር በተመለከተ ጊዜ "የቸሩ አምላክ አገልጋይ ሆይ እለምንሃለሁ ዛሬ ውጣና በቤቴ ዕረፍ በአንድነትም እንመገብ መልካም ነገርን አድርገህልኛልና" አለው፡፡
❤ ብፁዕ ቅዱስ ማርቆስም ተደሰተ፡፡ "እግዚአብሔር ሰማያዊት የምትሆን ሕይወት ኀብስትን ይስጥህም" አለው፡፡ ጫማ ሰፊውም ሐዋርያውም እየተደሰተ ወደ ቤቱ አስገባው፡፡ ሐዋርያውም እየተደሰተ ወደ ቤቱ ገባለት። "የእግዚአብሔር በረከት በዚህ ቤት ይኑር" አለ፡፡ ወንድሞች በአንድነት ጸለዩ ከጸሎት በኋላም ተቀመጡና ደስ እያላቸው ተመገቡ፡፡ ጫማ ሰፊውም ቅዱስ ማርቆስን "አባት ሆይ እለምንሃለሁ ይህንን የምትለው እንዴት ነው፤ ይህ ስምስ ምንድን ነው ይህ እንደዚህ የሚቻለው ነው" አለው፡፡ ቅዱስ ማርቆስም "እኔ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ ነኝ" አለው፡፡ ጫማ ሰፊውም "እኔ ላየው እሻለሁ" አለው፡፡ ቅዱስ ማርቆስም "እኔ አሳይሃለሁ" አለው፡፡ ቅዱስ ማርቆስም የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የዳዊት ልጅ፣ የአብርሃም ልጅ ነው እያለ የወንጌሉን መጀመሪያ አስተማረው፡፡ በትንቢት ስለ እርሱ የተናገሩትንም ከመጻሕፍት ተናገረ፡፡ ጫማ ሰፊውም "እኔ የምትለውን ይህን መጽሐፍ እለምንሃለሁ ከረጅም ዘመን ጀምሮ የግብጻውያን ልጆች እንደማይማሩበት አልሰማህምን" አለው ቅዱስ ማርቆስ እንዲህ በማለት የእግዚአብሔርን ነገር ይነግረው ዘንድ አስቀደመ "የዓለም ጥበብ በእግዚአብሔር ዘንድ ናት" አለው ጫማ ሰፊውም የቅዱስን ነገር በሰማ ጊዜ በእግዚአብሔር አመነ ለእርሱም አመለከተው ከእርሱም ኃይላትን ተአምራትን አየ እርሱ ቤተሰቡ፣ ከአገሩ ሰዎችም ብዙዎቹ ተጠመቁ፡፡ የጫማ ሰፊው ስምም አንያኖስ ይባላል፡፡ ያን ጊዜም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ምዕመናን በዙ፡፡ የአገሩ ሰዎች በሰሙ ጊዜም "ይህ የገሊላ ሰው ከዚህ አገር ደርሷል፤ የአማልክትን እጅ መንሻ ለውጧል፤ እንዳይመለኩ ከልክሏል" አሉ ሊገሉትም ፈለጉት ይጥሉት ዘንድም በእርሱ ላይ ፍለጋን አበዙ ብፁዕ ማርቆስ ይህን በተረዳ ጊዜ አስተማራቸውና አንኖስንም ኤጲስ ቆጾስነት ሾመላቸው ሦስት ካህናትንም ሾመላቸው ስማቸውም ወልዮስ፣ መሪደስና በሪሞስ ይባላል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን ተልእኮም ሰባት ዲያቆናትን አንድ ላይ አሥራ አንድ ሰዎችን ሾመላቸው፡፡
❤ ቅዱስ ማርቆስም ወደ ብርቃ ወጣ ለዓመታትም በእርሷ ተቀመጠ፡፡ በሁሉም አገራት ኤጲስቆጶሳትን፣ ካህናትን ሾሞላቸው ወደ እስክንድርያም ተመለሰ፡፡ በእግዚአብሔር በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስምም ጸጋና ማመን በዛባት የላም ቦታ በሚባለው በባሕሩ ዳር ካለው ቦታም ቤተ ክርስቲያን ሠሩ ከዚያ ቦታ ከዓለቱ ሥርም ታላቅ ድንጋይ ቁራጭ ነበር፡፡ ጻድቁም ስለ ምዕመናን መልካም ሃይማኖት እግዚአብሔርን አመሰገነ ብዙ ዘመን በቆየ ጊዜም ክርስቲያኖች በዙ አማልክትንም ተዘባበቱባቸው፤ አረማውያንንም ናቋቸው፡፡ አረማውያንም ቅዱስ ማርቆስ እንደሆነ ወደ አገራቸው እንደ ደረሰ ተረዱ፡፡ ከሰሙት ተአምራት ብዛት የተነሳ ልቡናቸው በቁጣ ተሞላ እርሱ ሕመምተኞችን ይፈውስ፣ ለምጻሞችንም ያነጻ፣ ደንቆሮዎችንም እንዲሰሙ፣ እውራንንም እንዲያዩ ያደርጋል መልካም ተስፋንም ያስተምራቸው ነበር ይይዙት ዘንድም ፈለጉት፤ በየቤታቸውም ጥርሳቸውን ያፋጩ ነበር፤ በአማልክቱ ምኵራብም "እኛ ለዚህ ጠንቋይ ተሸነፍን" እያሉ ጮኹ፡፡ ምዕመናን የሚያከብሩት ዕለት ሰንበት የተባረከው የፋሲካ በዓልም በሰንበት ቀን ሆነ፤ ይህም ዕለት ሚያዝያ 17 ቀን ነው፡፡
❤ በዚያች ዕለትም በእነርሱ ዘንድ የሰራቢስ የልደቱ ቀን ነበር፡፡ ያማረች ዕለትን አገኙ ሰላዮችን ላኩና ያዙት፡፡ እርሱን የቅዳሴ ጸሎት ሳይፈጽምም በሰንሰለት አሠሩት በላሞች ቦታ እንጐትተው እያሉም እንደ አውራ ፍየል በየመንገዱ ጐተቱት፡፡ ቅዱስ ማርቆስም በጐተቱት ጊዜ አግዚአብሔርን አመሰገነው፡፡ "ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በተቀደሰው ስምህ መከራን እንድቀበለ አዘጋጅተኸኛልና አመሰግንሃለሁ” አለ፡፡ ሥጋውም በየመሬቱ ተቆራረጠ ደሙም በየዐለቱ ፈሰሰ፡፡
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሚያዝያ ፴ (30) ቀን።
❤ እንኳን #ለሐዋርያው_ለወንጌላዊው ለእስክንድርያ ሊቃነ ጳጳሳት አለቃ (መጀመርያ) ከሰባ ሁለቱ አርድእት ለአንዱ ለሆነው #ለቅዱስ_ማርቆስ_ዘአንበሳ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሐዋርያው_ወንጌላዊው_ቅዱስ_ማርቆስ ዘአንበሳ፦ የቅዱስ ማርቆስ ወላጆች ስም የአባቱ ስም ቅዱስ አርሰጡጳውሎስ ሲሆን የእናቱ ስም ቅድስት ማርያም ይባላል፡፡ አባቱ ባለፀጋና ያላገባ ነበር የአባቱ ስም ስምዖን ይባል ነበር፡፡ ስምዖንም አርስጡጳውሎስን እንዲያገባ ይገፋፋው ነበር፡፡ አንድ ቀን ወደ ኢየሩሳሌም ሲሄድ በቤቷ እንግዶችን የምትቀበልና የምታስተናግድ ማርያም የተባለችውን የወንጌላዊ የቅዱስ ማርቆስ እናት አገኘ ፡፡ እሱም እሷም ሳያስቡት ባዩት ሕልምና በመፈክረ ሕልም (በሕልም ፈቺዎች) በተነገራቸው መሠረት ተገናኝተው የትዳር ሕይወትን መሠረቱ፡፡
❤ አርስጡጳውሎስ ከከበረውና በባለጸግነቱ ከታወቀው ከአባቱ ካገኘው ሀብት ለነዳያን የሚመጸውት፣ ዐሥራት በኩራት የሚያወጣና ወደ እግዚአብሔርም ዘወትር የሚጸልይ ደግ አባት ነበር፡፡ እሱም የሐዋርያው የቅዱስ ጴጥሮስ ዘመድ የአክስት ልጅ እንደሆነና ቅዱስ ጳውሎስም በመልአክቱ የጠቀሰው እሱን እንደሆነ አንዳንድ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ "አብሮ ከእኔ ጋር የታሰረ አርስጥሮኮስ የበርናባስም የወንድሙ ልጅ ማርቆስ ኢዮስጦስም የተባለ ኢያሱ ሰላምታ ያቀርቡላችኋል" ቈላስይስ 4፥10 ነገር ግን አንዳንድ የግሪክ፣ የላቲን፣ የግእዝና የኮኘት ትርጉሞች "የበርናባስ የወንድሙ ልጅ" የሚለውን ሐረግ አይጠቅሱም ይህም ምንአልባት አንዳንድ የግሪክ ቃላት ከአንድ በላይ ትርጉም ስላላቸው ይሆናል፡፡
❤ የቅዱስ ማርቆስ እናት ማርያም ተብለው ከተጠሩት ብዙ ቅዱሳት አንስት መካከል አንዷ ናት፡፡ ቤቷ በኢየሩሳሌም እንደነበረና ምዕመናንም በቤቷ በጸሎት ይሰበሰቡ እንደነበር በሐዋ 12-12-17 በሰፊው ተገልጾአል፡፡ ይህም በጥንት ወይም በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ከክርስቶስ ልደት በኋላ ካሉት መንፈሳውያኑ ሴቶች (ቅዱሳት አንስት) ከፈተኛ ቦታ ያላት እንደነበር ያመለክታል። በዚያን ጊዜ የነበሩ ምዕመናን በአንድነት በክርስቶስ ስም ይሰባሰቡ ስለነበር ክርስቲያን የሚለውን ስም ያገኙትም በዚሁ ወቅት ነበር፡፡ "በቤተ ክርስቲያንም አንድ ዓመት ሙሉ ተሰበሰቡ፤ ብዙ ሕዝብንም አስተማሩ፤ ደቀ መዛሙርቱም መጀመሪያ በአንጾኪያ ክርስቲያን ተባሉ"፡፡ ሐዋ 11-26
❤ የቅዱስ ማርቆስ እናት የማርያም ቤት የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ለጸሎት የሚሰበሰቡበት ነበር፡፡ በማርቆስ እናት በማርያም ቤት በጽርሐ ጽዮን ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ እንደተገለጸላቸውና መንፈስ ቅዱስን እንደላከላቸው በቅዳሴ ዲዮስቆሮስ እንዲህ ተጽፏል "አመ ሣልስት ዕለት ተንሥአ እሙታን ወቦአ ኀበ ሀለው አርዳኢሁ ጉቡአን ወአስተርእዮሙ በጽርሐ ጽዮን … ወበ ፶ ዕለት ፈነወሎሙ መንፈሰ ቅዱስ ከመ ዘእሳት ወተናገሩ በነገረ ኩሉ በሐውርት … በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ የተሰበሰቡ ደቀ መዛሙርት ባሉበት ገባ በጽርሐ ጽዮንም ታያቸው …በ50ኛው ቀንም በእሳት አምሳል መንፈስ ቅዱስን ሰደደላቸው በአገሩ ቋንቋ ሁሉ ተናገሩ"
❤ በኢየሩሳሌም ውስጥ የማርያም ቤት የሐዋርያት መገናኛና መሰባሰቢያ ነበር፡፡ ስለዚህም የማርቆስ እናት የማርያም ቤት የመጀመሪያዎቹ ክርስቲያኖች ኀብረት መለያ ሆኖ ይታወቃል፡፡
❤ ቅዱስ ማርቆስ የተወለደው በአባቱ ወገን ከነገደ ይሁዳ ሲሆን የተወለደበት ቦታ ከአምስቱ የምዕራብ ከተሞች አንዷ በሆነችው በሊቢያ በሲርኔ ይኸውም አብራይሮሎስ በተባለች ትንሽ መንደር ተወለደ፡፡ ትውልዱ ዕብራዊ ቤተሰቦቹም ይኖሩበት የነበረው በሰሜን አፍሪካ በጥንታዊቱ ፔንዲፓሊስ ሲሪኒካ (ቀሪና) በተባለችው በዛሬው ሊቢያ ምዕራባዊ ጠረፍ በተቆረቆረችው ደማቅ ከተማ ስለነበር ቅዱስ ማርቆስ አፍሪካዊ ነው የሚባለውም ለዚህ ነው የሚሉ አሉ፡፡ ሉሌ መላኩ ቤተክርስቲያንህን እወቅ።
❤ ቅዱስ ማርቆስ ሰኔ 3 ቀን በዕለተ ረቡዕ ተጸንሶ መጋቢት 3 ቀን በዕለተ ዐርብ ፀሐይ ከመውጣቷ በፊት ተወለደ፡፡
❤ የቅዱስ ማርቆስ የስሙ ትርጓሜ ማርቆስ ማለት ንህብ ማለት ነው ንብ ከሁሉ እንዲቀስም አስቀድሞ ከክርስቶስ በኋላም ከሐዋርያት ተምሮአልና፡፡ አንድም አንበሳ ማለት ነው አንበሳ ለላሕም ጌታው እንደሆነ እንዲሰብረው እርሱም አምልኮተ ላሕምን ከግብጽ አጥፍቷልና፡፡ አንድም ካህን ልዑክ ማለት ነው፡፡ ብሥራተ ማሪ ማርቆስ ይላል የተደራረበ ቀለም ነው፡፡ ሁሉም ካህን ማለት ነው፡፡ እመልአክተ ሲኖዲቆስ ባለ ጊዜ መልእክትም ሲኖዲቆስም ክታብ ማለት እንደሆነ ….።
❤ የቅዱስ ማርቆስ ሁለተኛ ስሙ ዮሐንስ ይባላል። "ባስተዋለም ጊዜ እጅግ ሰዎች ተከማችተው ይጸልዩበት ወደ ነበረው ማርቆስ ወደ ተባለ ወደ ዮሐንስ እናት ወደ ማርያም ቤት መጣ" ሐዋ12፥12
❤ የቅዱስ ማርቆስ ተክለ ቁመናና መልክ
እንዲሁም አለባበሱን እንዲህ በማለት ተጠቅሷል፡፡ "የግብጽና የኢትዮጵያ ኮከብ ብፁዕና ቅዱስ ማርቆስ መልኩ ቀይ ቅንድቦቹም ከበድ ያሉ ዓይኖቹም እንደሰማያዊ ኀብር የጠሩ ቁመቱ ረጅም ከአንገቱም ስር ስርጉድ የሆነ እንደ ነቢዩ ኤልሳዕ ራሰ በራህ የሆነ ቀሚስ (ልባልባውም) በወገቡ የሆነ የግብጽና የኢትዮጵያ አባት የቅዱስ ማርቆስ ምልክቱ ይኸ ነበር፡፡
❤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዘመነ ሥጋዊ በሚሰብክበት ጊዜ ቅዱስ ማርቆስ ወጣት ነበር፡፡ ልቦናው የቀና እንደሆነም አውቆ ከሰባ ሁለቱ አርድእት የመጀመሪያ አድርጐ መረጠው ከዚህ በኋላ የክርስቶስ ደቀመዝሙር ሆኖ ጌታ ወንጌልን ሲያስተምር፤ ተአምራት ሲያደርግ ያስተውል ነበር ፡፡ በምሴተ ሐሙስ በአይሁድ ሲያዝና መከራን ሲቀበል ቅዱስ ማርቆስ በኢየሩሳሌም መንገድ ላየ ሆኖ በርቀት ድርጊቱን ይከታተለ ነበር፡፡ በወንጌሉም እንዲህ ተብሎ የተጻፈው ስለ አርሱ እንደሆነ ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ "ዕርቃኑን በነጠላ የሸፈነ አንድ ጐበዝ ይከተለው ነበር ጎበዛዝቱም ያዙት፤ እርሱ ግን ነጠላውን ትቶ ዕራቁቱን ሸሸ"፡፡ ማር14-51-52
❤ ቅዱስ ማርቆስ በቤቱ መጻፊያ ይዞ የጌታን ተአምራት ይጽፍ ነበር፡፡ የግሞ ሊናሮስ የሚባል አገልጋዩን ጌታን እንዲከተልና የሚያደርገውንም ተአምራት እንዲጽፍ ያደርግ ነበር ፡፡ "ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በዓለ ፋሲካን ሲያከብር ተከተሉት" የተባለውም ቅዱስ ማርቆስን እንደሆነ እንዲህ ተጽፍል፤ "ከደቀ መዛሙርቱም ሁለት ላከ እነዲህም አላቸው ወደ ከተማ ሂዱ ማድጋ ውሃ የተሸከመ ሰውም ያገኛችኋል ተከተሉት የሚገባበትንም የቤቱን ጌታ መምህሩ፣ ከደቀመዛሙርቴ ጋር ፋሲካን የምበላበት የእንግዳ ቤት ወዴት ነው ይላል በሉት፡፡ እርሱም በደርብ ላይ ያለውነ የተሰናዳና የተነጠፈ ታላቅ አዳራሽ ያሳያችኋል፣ በዚህም አሰናዱልን፡፡ ደቀ መዛሙርቱም ወጡ ወደ ከተማም ሄደው እንዳላቸው አገኙ ፋሲካም አሰናዱ” ማር 14፥13-15፤ ሉቃ 22፥10-12።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሚያዝያ ፳፱ (29) ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት ለአንዱ መራራ የሆኑ ውኃዎችን ለውጦ ጣፋጮች ላደረጋቸው፤ የደረቁ ዕንጨቶችንም ላለመለመና በደዌ የተጨነቁ ብዙ በሽተኞችንም ላዳነ #ለሐዋርያ_ለቅዱስ_አርስጦስ ዕረፍት በዓልና ለንጹሕ ደግ ቅን ለሆነ ለኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ #ለአባ_አካክዮስ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ ከክብር ባለቤት #ከጌታችን_ከኢየሱስ_ክርስቶስ_ከልደቱ (በዓለ ወልድ) ከወራዊ መታሰቢያ በዓል፣ #ከአባ_ገምሶና ከእርሱ ጋራ ከሆኑ ከብዙ ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_አርስጦስ፦ ይህም ቅዱስ ከሐዋርያት ጋራ በጽርሐ ጽዮን የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ከተቀበለ በኋላ ከአገሩ ሁሉ ቋንቋ ተናገረ። ሐዋርያትንም እያገለገለ ከእሳቸው ጋራ ሲሰብክ ብዙ ጊዜ መከራ ተቀበለ።
❤ ከዚህም በኋላ ሐዋርያት መርጠው ለኢየሩሳሌም ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ሾሙት። በዚችም አገልግሎት ጥቂት ቆይቶ ብስጥስ በሚባል አገር ላይ ሁለተኛ ኤጲስቆሰነት ሾሙት። በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በውስጥዋ አስተምሮ አንድነትንና ሦስትነትን በማሳወቅ የሰዎቿን ልቡና ብሩህ አደረገ። የጣዖታትንም ቤቶች አፍርሶ አብያተ ክርስቲያንን ሠራ በክብር ባለቤት በጌታችንም ስም አጸናቸው።
❤ ታላላቅ አስደናቂ ተአምራትን በማድረግ መራራ የሆኑ ውኃዎችን ለውጦ ጣፋጮች አደረጋቸው፣ የደረቁ ዕንጨቶችንም እንዲያለመለመልሙና እንዲአፈሩ አደረጋቸው፣ በደዌ የተጨነቁ ብዙ በሽተኞችንም አዳነ ወደ በጎ እርጅና ደርሶ እግዚአብሔር አገልግሎ ሚያዝያ29 በሰላም ዐረፈ። እንሆ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመልክቱ አስታውሶታል። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ሐዋርያ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_አካክዮስ፦ ይህ አባት ንጹሕ ደግ ቅን የሆነ የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ ነው። ይህንንም ቅዱስ ከሀድያን ብዙ ቀኖች አሠቃዩት እግዚአብሔር በእጆቹ ብዙ ተአምራትን አደረገ ከዚህም በኋላ ሚያዝያ29 በፍቅር አንድነት ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዠላለሙ ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 29 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ዕብል_አርስጦስሃ_ፍጹም። ኤጲስቆጶስና በእደ ሐዋርያት ተሠይመ። ለሀገረ ብናጥስ ሕዝብ እንዘ ያርኢ መድምመ። ገብረ በጸሎቱ ይቡስ ዕፅ ልምሉመ። ወምረረ ማይ ረሰየ ጥዑመ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_29።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ምስሌከ ቀዳማዊ በዕለተ ኃይል። ወብርሃኖሙ ለቅዱሳን። ወለድኩከ እምከርሥ እምቅድመ ኮከበ ጽባሕ"። መዝ 109፥3 ወይም 2፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 2፥1-8 ወይም ሉቃ 1፥26-39።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "አልቦ ነገር ወአልቦ ነቢብ ዘኢተሰምዐ ቃሎሙ። ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አጽናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ"። መዝ 18፥3-4 ወይም 101፥25-26። የሚነበቡት መልዕክታት ቈላ 4፥10-14፣ 1ኛ ዮሐ 4፥918 እና የሐዋ ሥራ 13፥4-16። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12 ወይም ዮሐ 1፥1-15። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይሞ ቅዳሴ የእመቤታችን ማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም በዓልና የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦፦ "ካህናቲከ ይለብሱ ጽድቀ። ወጻድቃኒከ ትፍሥሕተ ይትፌሥሑ። በእንተ ዳዊት ገብርከ"። መዝ 131፥9-10 የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 5፥1-ፍ.ም፣ 3ኛ ዮሐ 1፥8-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 15፥22-37። የሚነበበው ወንጌል 18፥18-23። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የርክበ ካህና (የቅዱስ ሲኖዶስ) ስብሰባና የበዓለ ሃምሳ ጊዜ። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ እንኳን #ለትንሣኤ_ሃያ_አምስተኛ (፳፭) ቀን #ርክበ_ካህናት (ዕለተ ጥብርያዶስ) እግዚአብሔር አምላክ በሰላም በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ርክበ_ካህናት (ዕለተ ጥብርያዶስ)፦ የሀገራችን የቅዱስ ሲኖዶስ መሰብሰቢያ ቀን ርክበ ካህናት፣ ዕለተ ጥብርያዶስ፣ ዳግሚት ዕለት አግብኦተ ግብር ምንድን ነው?
❤ ርክበ ካህናት የሁለት ቃላት ጥምረት ሲኾን እነዚህም፤
፩ኛ. ረክብ የሚለው ቃል ተራከበ ተገናኘ ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲሆን ትርጕሙም ማግኛ፣ መገኛ፣ መገናኛ ማለት ነው፡፡ /ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፰፴፩/፡፡
፪ኛ. ክህነት የሚለው ቃል ከዲቁና ጀምሮ እስከ ከጵጵስና ድረስ ያሉትን መዓርጋት (በጥቅሉ ዲያቆናትን፣ ቀሳውስትንም ኾነ ጳጳሳትን) የሚያጠቃልል ስያሜ ነው፤ ካህን (ነጠላ ቍጥር) ሲኾን ካህናት ደግሞ (ብዙ ቍጥር) ነው፤ ብዙ ጊዜ ግን ይህን ባለማወቅ ካህናት የሚለውን ለቀሳውስት ብቻ መጠሪያ ሲኾን እናያለን፤ አለማወቅ ነው! (ለምሳሌ በቅዳሴ መጨረሻ ላይ ዲያቆኑ በእደ …… ካህን ይባርከነ ቢል ለኹሉም ያስኬዳል፥ ሰዋስዉም ያዛል፥ ሥርዐቱም ይኸው ነው፤ ነገር ግን ዛሬ ዛሬ በእደ … ካህን ይባርከነ በማለት ፈንታ በእደ ብፁዕ ፓትርያርክ፣ በእደ ብፁዕ ሊቀ ጳጳስ፣ በእደ ቆሞስ …. ሲባል ይታያል፤ መስተካከል ያለበት ጉዳይ ነው፡፡)
❤ ርክበ ካህናት ማለትም የአባቶች ካህናት (ማለትም በጵጵስና ማዕረግ ያሉ፦ ኤጲስ ቆጶሳት፣ ጳጳሳት፣ ሊቃነ ጳጳሳትና ርዕሰ ሊቃነ ጳጳስን ያጠቃለለ (የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት) ጕባኤ፤ የካህናት መገኛ፥ መገናኛ ጉባኤ (መሰባሰቢያ፣ መወያያ) ማለት ነው፡፡
❤ በዓሉ በየዓመቱ የትንሣኤ በዓል በዋለ በ፳፭ኛው ቀን ሁልጊዜ በዕለተ ረቡዕ ይውላል፤ ወሩና የሚውልበት ቀን ግን በኢየዓርግና በኢይወርድ (በባሕረ ሓሳብ የበዓላትንና የአጽዋማትን) ቀመር ተከትሎ የሚወጣ ስለኾነ ከፍና ዝቅ ይላል፡፡ የአጽዋማትና የበዓላት ቀመር በቅዱስ ድሜጥሮስ አማካኝነት ከመዘጋጀቱ በፊት (ዐቢይ ጾም ሰኞ፣ ስቅለት ዓርብ፣ ትንሣኤ እሑድ፣ ርክበ ካህናት ረቡዕ፣ ዕርገት ሐሙስ፣ ጰራቅሊጦስ እሑድ እንዲሆን ከመደረጉ በፊት) ርክበ ካህናት በየዓመቱ ግንቦት ፳፩ ቀን ይውል ነበር /መጽሐፈ ግጻዌ ግንቦት ፳፩/፡፡
❤ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል አድርጐ ከተነሳ በኋላ ለደቀ መዛሙርቱ በየጸጋቸው መጠን እየተገለጠ ያጽናናቸው፥ ያጸናቸው፥ ያስተምራቸው፥ ይባርካቸውም ነበር፤ ጌታችን እስከ ዕርገቱ ባሉ ፵ ቀናትም መጽሐፈ ኪዳንን፣ ትምህርተ ኅቡዓትን፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን አስተምሯቸዋል፤ በልቡናቸውም አሳድርድሮባቸዋል፡፡
❤ በመጽሐፍ ቅዱስ በዮሐንስ ወንጌል፤ ከዕርገቱ አስቀድሞ ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ ፫ ጊዜ በጕባኤ መገለጡ ተዘግቦ ይገኛል፡፡ እነዚህም፤
1ኛ. የትንሣኤ (ዮሐ. 20፥19)
2ኛ. የአግብኦተ ግብር (ዳግም ትንሣኤ) /ዮሐ. 20፥:26/
3ኛ. የጥብርያዶስ፤ (ዮሐ. 21፥1)
ለድንግል ማርያም ግን በኹሉም እለታት መገለጡን አበው ያስተምራሉ፡፡
❤ በጥብርያዶስ ባሕርም ከዐሥራ አንዱ ቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ምሳ በልቷል፡፡ የርክበ ካህናት በዓል መነሻም ጌታችን ለሦስተኛ ጊዜ ከተገለጠበት ከጥብርያዶስ ባሕር ካለው ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡
በዚህች ዕለት በቅዱስ ዼጥሮስ መሪነት ሐዋርያቱ ወደ ጥብርያዶስ ባሕር ሔዱ፡፡ አሶችን ሊያጠምዱም በብዙ ደከሙ፤ ነገር ግን ጌታችን በረድኤት አብሯቸው አልነበረምና አንዳች አሣ በመረባቸው ሊገባ አልቻለም፡፡ ማጥመድ (አስተምሮ ከክህደት ወደ ሃይማኖት፤ ከኀጢአት ወደ ጽድቅ መመለስ) የሚቻለው በረድኤተ እግዚአብሔር እንጂ በእውቀት ብዛት ወይም በአንደበተ ርቱዕነት ብቻ አይደለምና፡፡
❤ ሲነጋ ግን መድኀኒታችን ወደ ቅዱሳን ደቀ መዛሙርቱ መጣ፤ በጥብርያዶስ ባሕር ዳርቻም ቆሞ ታያቸው፤ ከሚወደው ደቀ መዝሙሩ ከቅዱስ ዮሐንስ በቀር ጌታችን መሆኑን ያወቀው ግን አልነበረም፡፡ ቸሩ አባት "ልጆቼ! አንዳች የሚበላ ነገር አላችሁ?" ሲል ጠየቀ፤ "ጌታ ሆይ! የለም" አሉት፡፡ "የለንም" ብሎ የሌለንን ነገር በጌታ ፊት ማመኑ እጅግ መልካም ነው፤ ምክንያቱም ያጣነውን ነገር ሊሰጠን፥ የጎደለንን ሊሞላልን፥ የጠፋብንን ሊጠቁመን ቸርነቱ ብዙ ነውና፡፡ ያን ጊዜ ሐዋርያቱን መረባቸው በመርከብ ቀኝ እንዲጥሉ አዘዛቸው፡፡ እነርሱም በደስታ ጣሉ፤ በአግራሞት እስኪሞሉ ድረስ መረባቸውን መሳብ አቅቷቸው ሊቀደድ እስኪደርስ ድረስ 153 ዓሦች ተያዙላቸው፡፡
❤ ያን ጊዜም የሚወደው ደቀ መዝሙሩ ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችን መኾኑን ለቅዱስ ዼጥሮስ "ጌታ እኮ ነው" አለው፤ ሽማግሌው ቅዱስ ግን ራቁቱን ነበርና ወደ ባሕሩ ተወረወረ፡፡ ከአፍታ በኋላም ጌታችን ከሐዋርያቱ ጋር በድጋሚ (ለ፪ኛ ጊዜ) ለምሳ ተቀመጠ፤ ባርኮ ሰጥቶ ልባቸውን ሊያጸና አብሯቸው በላ፡፡
በዚያች ሰዓት ቅዱስ ዼጥሮስን ፫ ጊዜ "ትወደኛለህን?" ሲል ጠየቀው፤ ቅዱሱ አረጋዊም እየደጋገመ "ለሊከ ተአምር ከመ አነ አፈቅረከ (እንድወድህ አንተ ታውቃለህ" ሲል መለሰ፡፡ ጌታም በበጐች ሐዋርያት (ካህናት)፤ በጠቦቶች አርድእት (ዲያቆናት)፤ በአባግዕት ፴፮ቱ ቅዱሳት አንስት (ምዕመናን ወምዕመናት) ላይ ሁሉ እረኛ እንዲሆን ሾመው፡፡
❤ ይህ ምሥጢር ለጊዜው ጌታችን ሐዋርያትን፣ ሰብዐ አርድእትንና ሠላሳ ስድስቱን ቅዱሳት አንስት በአጠቃላይ መቶ ሃያውን ቤተሰብእ እንዲጠብቅና እንዲከባከብ ቅዱስ ጴጥሮስን ማስጠንቀቁን፤ ፍጻሜው ግን የቤተ ክርስቲያን አባቶች (ጳጳሳት) መምህራንንና መላው ሕዝበ ክርስቲያንን እንዲጠብቁና እንዲያስተዳድሩ በእግዚአብሔር መሾማቸውን የሚያስረዳ ትርጕም አለው ዮሐ ፳፩፥፩-፲፯ (አንድምታ ትርጓሜ)፡፡ ቀጥሎም የቅዱስ ጴጥሮስን የሰማዕትነቱን ምሥጢር ገልጦለት "ተከተለኝ" (ለጊዜው በእግር፤ በኋላ ግን በግብር ምሰለኝ) ብሎታል፡፡ ወልደ ነጐድጓድ ወፍቊረ እግዚእ ቅዱስ ዮሐንስም ሞትን እንደማይቀምስ እንዲሁ ተናግሮለታል።
❤ ጌታ ለሐዋርያት በአንድነት የተገለጠባትን ይህች ቀን እነዚህ ሁሉ ተግባራት የተከናወኑባት ናትና (የትንሣኤ በዓል ፳፭ኛ ቀን) መሠረት በማድረግ፤ የኋላ ሊቃውንት በየዓመቱ የትንሣኤ በዓል በዋለ በ፳፭ኛው ቀን ዐራቱ ሊቃነ ጳጳሳት የሚሰበሰቡበት የካህናት መገናኛ ቀን ርክበ ካህናት ይሁን ብለው ወስነዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ርክበ ካህናት በዓለ ትንሣኤ በዋለ በ፳፭ኛው ቀን፣ በበዓለ ሃምሳ እኩሌታ በዕለተ ረቡዕ ይዘከራል፤ በያዝነው ዓመት በ፳፻፲፰ (2018) ዓ.ም የትንሣኤ በዓል ከተከበረበት ዕለት (ሚያዝያ ፬ (4) ቀን) ጀምሮ ብንቆጥር ፳፭ (25) ኛው ቀን ሚያዝያ ፳፰ (28) ቀን ይኾናል፡፡ በመኾኑም የዘንድሮው ርክበ ካህናት ሚያዝያ ፳፰ (28) ቀን በዕለተ ረቡዕ ይውላል ማለት ነው፡፡
❤ ይህ በዓል ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሲያስተዳድሩ የቆዩ አባቶቻችን ጌታንና ደቀ መዛሙርቱን አብነት በማድረግ በጋራ በመሰባሰብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተቀላጠፈ አገልግሎት እንደዚሁም ለምእመናን አንድነትና መንፈሳዊ ዕድገት የሚበጁ መንፈሳውያን መመሪያዎችን የሚያስተላልፉበት እለት ነው፡፡
❤ "በአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ሚያዝያ ፳፰ (28) ቀን።
❤ እንኳን በኮራሳት ተራራ በገድል ተጠምዶ ለሚኖር በሐሰት ሰው ገድለሃል ብለውት የሞተውን ሰው አስነስቶ ላስመሰከረ #ለቅዱስ_አባት_ለአባ_ሜልዮስና መቅሱር ለሚባል አገር ለሆነ #ለቅዱስ_ብስጣውሮስ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #ከዋሲሊኮስና ከብዙ ሰማዕታት ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ሜልዮስ፦ ይህም አባት ኮራሳት በሚባል አገር በተራራ ባሉ ዋሻዎች ከሁለት አርድእቱ ጋራ ይኖር ነበር። የኮራሳት ንጉሥ ሁለት ልጆቹ ወደዚያ ወጡ ከእርሳቸውም ጋራ አገልጋዮች አሉ አራዊትን አጥምደው በፍላፃዎች ይገሉ ዘንድ መረባቸውን ተክለው አርባ ምዕራፍ ያህል ሔዱ። መረቡን በጠቀለሉት ጊዜ ይህን ቅዱስ አባት ማቅ ለብሶ ጠጉሩም የረዘመ ሁኖ አገኙት።
❤ የንጉሥ ልጆችም በአዩት ጊዜ ፈሩ አንተ ሰው ነህን ወይም መንፈስ ብለው ጠየቁት እርሱም "በዚህ ተራራ ውስጥ የምኖር ለሕያው እግዚአብሔር ልጅ ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የምሰግድ ሰው ነኝ" ብሎ መለሰላቸው። እነርሱም "ከእሳትና ከፀሐይ በቀር አምላክ የለም እንዳንገድልህ ሠዋላቸው" አሉት። እርሱም "እሳትና ፀሐይ የተፈጠሩ ናቸው እናንተም ተሳስታችኋል ፍጥረቶችን በፈጠረ በእውነተኛ አምላክ ታምኑ ዘንድ እኔ እለምናችኋለሁ" ብሎ መለሰላቸው። በዚያን ጊዜ ይህን አባት ሁለቱን አርድእትም ይዘው ጽኑ ሥቃይ አሠቃዩአቸው በዚህ ወር በዐሥራ ሦስት የሁለቱን አርድእት ራሳቸውን ቆረጡአቸው የሰማዕትነት አክሊል ተቀበሉ።
❤ አረጋዊ ቅዱስ ሜልዮስን ግን ዐሥራ አምስት ቀን ያህል ሲአሠቃዩት ኖሩ ከዚህ በኋላ በመካከላቸው አቆሙት አንዱ በፊት አንዱ በኋላ ሁነው በፍላፃ ይነድፉት ጀመር። እርሱም "በእናንተ ላይ ክፉ ያልሠራውን ለመግደል ሁለታችሁ ስለተስማማችሁ እንዲሁ እንደሥራችሁ በፍላፃችሁ ነገ ትሞታላችሁ" አላቸው። ሰምተውም አልፈሩም ነፍሱን እስከሚአሳልፍና ምስክርም ሆኖ የሰማዕትነት አክሊል እስከሚቀበል ነደፉት እንጂ። በማግሥቱም እንደልማቸው ለአደን ወጡ የዱር አህያም አገኙ ተከትለውም ቀስታቸውን አስፈነጠሩ እግዚአብሔር ፍላፃቸውን ወደልባቸው መለሰ ቅዱስ ሜልዮስም እንደተናገረባቸው ሞቱ።
❤ በዚህ ቅዱስም እጅ ጌታችን ተአምራትን ገለጠ በአንዲት ዕለትም አልፎ ሲሔድ በመንገድ ላይ የሞተ ሰው አገኘ የአገር ሰዎች ግን አንዱን መነኰስ አንተ ነህ የገደልከው ብለው ያዙት። ቅዱስ ሜልዮስም ጸለየ "የሞተውም በውኑ የገደለህ ይህ መነኵሴ ነውን?" አለው ያን ጊዜ የሞተው ተነሥቶ "እርሱስ አልገደለኝም ነገር ግን ብዙ ገንዘቤን ከአንድ ቄስ ዘንድ አደራ አስጠበቅሁ ስለዚህ ገደለኝ ከዚህም ጣለኝ" አለ ደግሞ እንዲህ ብሎ ለመነው "ዕገሌ ወደሚባል ወደዚያ ቄስ ሒደህ ገንዘቤን ከርሱ ተቀብለህ ለልጆቼ ስጥ" አለው። ቅዱስ ሜልዮስም "እስከ ትንሣኤ ቀን በሰላም ዐርፈህ ተኛ እኔ ገንዘብ አከፋፋይ ዳኛ አይደለሁም" አለው ያንጊዜም ተኛ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ በቅዱስ ሜልዮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ብስጣውሮስ፦ የዚህም ቅዱስ አባቱ ጻድቅ ሰው ነው እናቱን ግን ሰይጣን አስቷት ወደ እስልምና ገባች እርሱም ፈሪሀ እግዚአብሔርን እየተማረ እስከሚጐለምስ አደገ አካለ መጠንም አድርሶ ሚስት አገባ ከርሷም ልጆችን ወለደ።
❤ ብዙ ዘመናትም በአለፉ ጊዜ አንገተ ደንዳና በቀለኛ ሰው በእርሱ ላይ ተነሥቶበት ወደ እስላሞች መኳንንት ሒዶ ሰው ወደ እኛ ሕግ ቢገባ ልጆቹም ሃይማኖቱን ይከተላሉ ይህ ብስጣውሮስ ግን ከሕጋችን የተለየ ነው ብሎ ነገር ሠራበት። የእስላሞች ዳኞችም በሰሙ ጊዜ መልክተኞች ልከው ወደርሳቸው ወደ ሸንጎ አቀረቡት ስለ ሃይማኖቱም ጠየቁት ክርስቲያን እንደሆነ ያለ ፍርሀት ክርስቲያን ነኝ ብሎ ታመነ። ዳኛው ግን ይሸነግረው ዘንድ በፍቅር ይናገረው ጀመር ከከበረችና ከቀናች ሃይማኖቱ ይመለሰው ዘንድ ብዙ ስጦታዎችን እንደሚሰጠው ቃል ገባለት ቅዱሱ ግን ከቶ አልተመለሰም ወደ ስጦታውም ከቶ ልቡ አላዘነበለም።
❤ ከዚህ በኋላ ወደ ግዞት ቤት ወስደው በእግረሙቅ እንዲአሥሩት በአንገቱም የተበሳ ታላቅ ግንድ አሥረው በግንባሩ ደፍተው በኵስ ላይ እንዲጥሉት መኰንኑ አዘዘ። እንዲሁም አደረጉበት እስከ ሦስት ቀን በእሥር ቤትም ሳለ ፀዐዳ ርግብ መጥቶ ጋረደው ስለዚህም የእሥር ቤቱ ጠባቂ ምስክር ሆነ።
❤ ከዚህም በኋላ ዳኞች ወደ ሸንጎ አስቀርበው "ከእንዲህ አንታገሥህም ወደ ሃይማኖታችን ከምትገባና ወይም በእሳት ከምናቃጥልህ ምረጥ" አሉት። እርሱም እኔ ከእናንተ ጋራ ለዘላለሙ ዕድል ፈንታ የለኝምና የወደዳችሁን አድርጉ" ብሎ መለሰላቸው። በዚያን ጊዜም እጅግ ተቆጡ ያለ ርኅራኄ ይደበድቡት ዘንድ አዘዙ ያገር ሰዎችም በጫማቸው መቱት አንዲት ሴትም መጥታ በጫማዋ መታችው ወዲያውኑ እጆቿ ደረቁ። ከዚህም በኋላ ባለ ሰይፍ ከመኰንኑ ታዝዞ ወጣ ሰይፉንም መዝዞ ሳያቋርጥ መላልሶ አንገቱን መታው። ምቱም ወደ ጐን ሒዶ ጀሮውን ቆረጠው አመታቱ ክፉ ስለ ሆነ ከሥሮቿ ብዙ ደም ፈሰሰ። ከዚህም ደግሞ ተዉት እምነታቸው ሊአስገቡት እምቢ በአላቸውም ጊዜ ሁለተኛ ሰይፉን መዝዞ ሰያፊው የከበረች አንገቱን ሚያዝያ28 ቆረጠው በመንግሥተ ሰማያትም የምስክርነት አክሊልን ተቀበለ። ሥጋውንም ከእሳት ጨመሩ ግን አልተቃጠለም። ዘመዶቹም መጥተው በድኑን ወደአገሩ ወሰዱ። በቅዱስ ዮሐንስ ዘሐራቅሊ ጐን ቀበሩት። የክብር ባለቤት ጌታችንም ብዙ ድንቆች ተአምራትን ከሥጋው ገለጠ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ በከበረ ሰማዕት ጸሎት ለዘለዓለሙ ይቅር ይበለን አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 28 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ዕብል_ለሚልዮስ_ጻድቅ። እምፍትወተ ሥጋ ርኁቅ። እንዘ ይነድፍዎ ሎቱ በአሕፃሆሙ ውሱቅ። እፎ ኢያኅዘኖሙ ለነዐውተ አርዌ ደቂቅ። ሥእርተ ርእሱ ነዊኀ ወልብሱ ዘሠቅ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የሚያዝያ_28።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ዕቀበኒ እምሥገርት እንተ ኀብኡ ሊተ። ወእማዕቀፎሙ ለገብርተ ዓመፃ። ለይደቁ ውስተ መሥገርቶሙ ኃጥአን"። መዝ 140፥9-10። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 4፥1-14፣ ያዕ 2፥19-ፍ.ም፣ የሐዋ ሥራ 7፥1-9። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 12፥8-17። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
