es
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

Ir al canal en Telegram

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

Mostrar más
638
Suscriptores
Sin datos24 horas
-37 días
-1130 días
Archivo de publicaciones
                          ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወበእግዚአብሔር ተወአልኩ ኢይፈርህ ምንተ ይሬስየኒ ዘሥጋ። ወኵሎ አሚረ ያስቈርሩኒ ዘነበብኩ። ወላዕሌየ ይመክሩ ኵሎ እኩየ"። መዝ 55፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 8፥4-10፣ 1ኛ ጴጥ 2፥21-ፍ.ም፣ የሐዋ ሥራ 5፥29-34። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥16-24። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጎድ ቅዳሴ ነው። መልካም የምካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም በዓልና የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችን ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #ሚያዝያ ፳፯ (27) ቀን። ❤ እንኳን #ለምካየ_ኅዙናን_መድኃኔዓለም #ለቅዳሴ_ቤቱ_76ኛ (ሰባ ስድስተኛ) ዓመት ዓመታዊ በዓል (በአፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት ፋሽሽት ጣልያን 1928 በድጋሚ ኢትዮጵያን ወሮ 1933 ድጋሚ ተሸንፎ ለወጣበት፤ #ለ85 (ለሰማንያ አምስኛው ዓመት ለርበኞች ቀን መታሰቢያ) በዓል እግዚአብሔር በሰላም በጤና አደረሰን። ❤ #ምስካዬ_ኅዙናን_መድኃኔ_ዓለም_ገዳም_ታሪክ፦                           + + + ❤ አዲስ አበባ ምስካዬ ኅዙናን መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን፦ የዚህ ቤተ ክርስቲያን ጽላት ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አገራችን ኢትዮጵያ በፋሺስት ኢጣልያ በተወረረች ጊዜ በስደት እንግሊዝ አገር ባዝ በተባለ ከተማ ሲኖሩ፣ ጥር ፲፫ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ/ም በጊዜው በስደት ኢየሩሳሌም ለነበሩት ወደ ብፁዕ እጨጌ ገብረ ጊዮርጊስ (በኋላ አቡነ ባስልዮስ ) አንድ ፅላትና ለአገልግሎት የሚበቁ አምስት መነኮሳትን ወደ እንግሊዝ አገር እንዲልኩላቸው በ አባ ሐና ጅማ በላኩት ደብዳቤ መሠረት ተልኮ በስደት የኖረ ፅላት ነበር። ❤ የጃ ን ሆይ የስደት መልእክት፦ "ሞዓ አንበሳ ዘእምነገደ ይሁዳ ፤ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሥዩመ እግዚአብሔር ንጉሠ ነገሥት ዘ ኢትዮጵያ ይድረስ ከብፁዕ አባቴ እጨጌ ገብረ ጊዮርጊስ እንደምን ሰንብተዋል ፤ እኛ እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነን። እስካሁን ባለነው አኳኋን የምናስበው ለናንተ ነው እንጂ ወደኛ ምንም የሚያሳስብ የለም። ይልቁንም የኛ እዚህ መሆንና በየጊዜው ጀኔቭ በሚደረገው ስብሰባ ፤ ቢፈቀድልን የኛ መሄድ ባይፈቀድልንም መላክተኛችንን መላክ ለመጣንበት ጉዳይ ዋና ረዳታችን ስለሆነ የፈጣሪያችን ፍርድ የ ኢትዮጵያ ን ጉዳይ እስካጠቃለልን ድረስ እዚሁ ሆኖ ማዳመጥ የሚያስፈልግ መሆኑን ስለተረዳነው የፈጣሪያችንን ቁርጥ እስክናውቅ ድረስ በዚሁ በእንግሊዝ አገር ለመቆየት ቆርጠናል። የእግዚአብሔር ቸርነት ፈቅዶልንና አሰናብቶን ወደ ኢየሩሳሌም እስከምንመጣበት ቀን ድረስ የሃይማኖት ችግር እንዳያገኘን የሚያድጉትም ልጆቻችን የሃይማኖታቸውን መሠረት እንዳያጡት አስበን አንድ ጽላትና አምስት መነኮሳት የሚያስፈልጉትን ንዋየ ቅድሳትና መጻሕፍት ሰጥተውት ይዞ እንዲመጣ አባ ሐናን ልኬዋለሁና ከመምህር ገሪማ ጋራ ተማክራችሁ ዐቢይ ጾም ሳይገባ እንዲደርስ አድርጋችሁ እንድትልኩልን ይሁን። በየጠረፋችንም ተሰደው በሰው ግዛት ላሉትም ሰዎቻችን እንደዚሁ ሰው መላክ አስፈላጊ ሳይሆን አይቀርምና እየተመካከራችሁበትና ፈቃዱ የሚሆን መነኩሴ እየመረጣችሁ እስክናስታውቃችሁ ድረስ መጠበቅ ነው። ጥር ፲፫ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ/ም ፣ ሎንዶን"። ❤ እጨጌ ገብረ ጊዮርጊስም ይሄ መልእክት እንደደረሳቸው በ ኢየሩሳሌም ዴር ሡልጣን የ ኢትዮጵያ ገዳም የነበረውን፣ በስመ መድኀኔ ዓለም የተጠራ ጽላት ፤ ለቁርባንና ለጸሎት የሚያስፈልጉትን ንዋየ ቅድሳት እና መጻሕፍት ጭምር በአምስት መነኮሳት እጅ አስይዘው በፍጥነት ወደ እንግሊዝ አገር ላኩ። የተላኩትም መነኮሳት፦ ፩ኛ/ መምህር ገብረ ኢየሱስ - መነኮስ ወቆሞስ ፪ኛ/ አባ ሐና ጅማ - መነኮስ ፫ኛ/ አባ ማርቆስ - መነኮስ ፬ኛ/ አባ ኃይሌ ብሩክ - መነኮስ ፭ኛ/ አባ ገብረ ማርያም - መነኮስ ናቸው። እነዚህ መነኮሳትም እንግሊዝ አገር እንደደረሱ፣ ሚያዝያ ፳፯ ቀን ፲፱፻፳፱ ዓ/ም አንድ መካነ ጸሎት ባርከው እንደ ቤተ ክርስቲያን ሕግ የጸሎትና የቁርባን ሥርዓት ያደርጉ ጀመር። ከዚያም የተነሳ ያች ቤተ ክርስቲያን በስደት ያለች ኦርቶዶክሳዊት የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ተብላ ትጠራ ጀመር። ❤ የፋሺስት ኢጣልያ ኃይል ተደምስሶ የኢትዮጵያ ነጻነት ሲመለስ ይሄ በስደት እንግሊዝ አገር የነበረው የመድኀኔ ዓለም ጽላትም ከግርማዊት እቴጌ መነን ጋር ነሐሴ ፳፫ ቀን ፲፱፻፴፫ ዓ/ም ተመልሶ አገሩ ገባ። ከዚያም በኋላ ሚያዝያ ፳፯ ቀን ፲፱፻፴፭ ዓ/ም በ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ሆስፒታል ቅጽር ግቢ በታነፀው ቤተ ክርስቲያን “ምስካዬ ኅዙናን መድኀኔ ዓለም” ተብሎ ቅዳሴ ቤቱ ተከበረ። ❤ በስደት በነበሩበት ዘመናት ሥርዓተ ቅዳሴ እንደተለመደው በ ግዕዝ ሲዘመር፣ በሥርዓቱ ውስጥ የተካተቱት ጸሎቶችም ሆኑ የቅዱስ ወንጌል ምንባብ፣ ወዘተ. ግን በ አማርኛ ቋንቋ ነበር የሚነበቡት። አሁንም ይሄ ታቦት ተመልሶ ከገባ በኋላ በ አባ ሐና ጅማ እና በአባ ኃይሌ ብሩክ መሪነት ሥርዓቱ ቀጠለ። በአገሪቱም ይሄ አዲስና ምእመኑን የሚያሳትፍ ተራማጅ ሥርዓት በኢትዮጵያ በጊዜው ያልተለመደ ቢሆንም የከተማው ምእመናን ጧት እና ማታ የምስካዬ ኅዙናን መድኀኔ ዓለምን ቤተ ክርስቲያን ማዘውተር ልምድ ሆነ። በተጨማሪም፣ የአጥቢያው ተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት እና እቴጌ መነን ትምህርት ቤት ተማሪዎች እሑድ እሑድ የማይለዩ አስቀዳሾች ነበሩ። በዚህ ዓይነት እስከ ፲፱፻፵ ዓ/ም ቆይቶ በጊዜው የነበረበት የቅዳሴ ቤት መጥበብ ግልጽ ስለሆነ ንጉሠ ነገሥቱ አሁን ቤተ ክርስቲያኑ የሚገኝበትን ቦታ ለአዲስ ቤተ ክርስቲያን ግንባት እንዲሆን አዘዙ። ❤ የቤተ ክርስቲያን ግንባታ ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ የአዲሱን የምስካዬ ኅዙናን መድኀኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን መሠረት ድንጋይ ሚያዝያ ፳፯ ቀን ፲፱፻፵ ዓ/ም ሲያስቀምጡ አትኩሮታቸው ወጣቱ ትውልድ ላይ እንደነበር ያደረጉት ንግግር ያመለክታል። “… በተፈሪ መኮንን ተማሪ ቤት ክበብ ውስጥ ይህን የአዲሱን ቤተ ክርስቲያን መሠረት ስንመሠርት በዚህ ተማሪ ቤት የሚማሩት ክርስቲያናውያን ወጣቶች የኦርቶዶክሳዊት ሃይማኖታቸውን ሥርዓት እንዲጠቀሙበት አስበን ነው። የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው ፤ ሃይማኖቱን የማያከብር ሃይማኖት የሌለው፣ እርሱም የሚያምነው ደገፋ የሌለው፣ እርሱንም ማንም የማያምነው የሁለት ዓለም ስደተኛ ነው። ፍሬውን ለማየት ተስፋችን እርሱ ምስካዬ ኅዙናን መድኀኔ ዓለም ነው።” ❤ የቤተ ክርስቲያኑ ሕንፃ ግንባታ በሚካሄድበት ጊዜ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ በቅርብ እንደተረዳው፣ ንጉሠ ነገሥቱ፣ ልዑላን እና ልዑላት ቤተ ሰቦቻቸው፤ መሳፍንቱ እና መኳንንቱ የሕንፃውን መገንቢያ ድንጋይ በትከሻቸው እያቀረቡ እንደተሳተፉ ተገንዝቧል። በዚህ ዓይነት እርምጃ ተገንብቶ፣ ልክ በሁለት ዓመቱ በ ፲፱፻፵፪ ዓ/ም ግንባታው ተፈጽሞ ቤተ ቅዳሴው ሚያዝያ ፳፯ ቀን ተመረቀ። ዋቢ ምንጭ፦ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ሐዋርያዊ ድርጅት፣ “ትንሣኤ፡ የሃያ አምስት ዓመታት መንፈሳዊ እርምጃ” (፲፱፻፶፱ ዓ/ም) ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ቤት። ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ፤ ሚያዝያ ፳፯ ቀን ፲፱፻፵ ዓ/ም (የምስካዬ ኅዙናን መድኀኔ ዓለም ቤ/ክ መሠረት ሲጥሉ ያደረጉት ንግግር።                           ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ውእተ ጊዜ እቤ ነየ መጻእኩ። ውስተ ርእሰ መጽሐፍ ተጽሕፈ በእንቲአየ። ከመ እንግር ፈቃደከ መከርኩ አምላኪየ"። መዝ 39፥7-8። የሚነበበው ወንጌል ማር 10፥1-12።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤            ❤ #ሚያዝያ ፳፯ (27) ቀን። ❤ እንኳን በአባቱ ትዕዛዝ ሰማዕታት ለተቀበለ #ለታላቁ_ሰማዕት_ለቅዱስ_ፊቅጦር ለዕረፍትና በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #ከቅዱስ_ፊቅጦር እናት #ከቅድስት_ማርታ፣ #ከቅዱሳን_ሲኖዳና_እስጢፋስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                             ✝ ✝ ✝      ❤ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_ፊቅጦር፦ ለዚህ ቅዱስ የአባቱ ስም ኅርማኖስ ነው እርሱም ለዲዮቅልጥያኖስ የአማካሪዎቹና የሠራዊቱ አለቃ ነው ስለ አምልኮ ጣዖት ሥራ ምክሩና ንግግሩ ሁሉ ከእርሱ ጋራ ነበር የእናቱም ስም ማርታ ይባላል በክርስትናዋ የጸናች ብፅዕት ናት። ❤ ቅዱስ ፊቅጦርም በአደገ ጊዜ አባቱ ወደ ንጉሥ አቀረበው ንጉሡም በመንግሥቱ ውስጥ ሦስተኛ ማዕርግ አድርጎ ሾመው በዚያን ጊዜ ዕድሜው ሃያ ዓመት ነበረ። እርሱም የዚህን ዓለም ክብር ናቀ ሥጋ አይባላም ወይን አይጠጣም ዘወትርም ይጾማል ጸሎትንም ባለማቋረጥ በቀንና በሌሊት ይጸልያል። በክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም የታሠሩትን ይጐበኛቸዋል ለድኆችና ለምስኪኖችም ይመጸውታል። ❤ የቅዱስ ቆዝሞስና ድምያኖስ እናት ቅድስት ቴዎዳዳን በገደሉዋት ጊዜ ንጉሡም ስለ መፍራት ሊቀብራት ማንም አልደፈረም። ይህ ቅዱስ ፊቅጦርም መጥቶ ሥጋዋን ወሰደ ከንጉሥ ስለሚመጣው ቅጣት ሳይፈራ ቀበራት። ጣዖት ስለ ማምለኩ አባቱን ዘወትር የሚገሥጸውና ብዙ ጊዜም የሚመክረው ሆነ አባቱም ወደ ንጉሥ ከሰሰው እንጂ አልሰማውም። ተከሶም ወደ ንጉሥ በአቀረቡት ጊዜ "አማልክት ያልሆኑ ርኲሳን ጣዖታትን ለሚያመልክ ሰነፍ ዝንጉ ልብ የለሽ ለሆነ ንጉሥ አላገለግልም። ከዛሬ ጀምሮ ለሕያው ንጉሥ ክርስቶስ እገዛለሁ የሰጠኸኝንም ገንዘብህን ንሣ" ብሎ በፊቱ ትጥቁን ፈትቶ ጣለለት። ❤ አባቱ ኅርማኖስም ወደ እስክንድርያ እንዲልከውና በኄርሜኔዎስ መኰንን ዘንድ በዚያ ፊቅጦር እንዲቀጣ ንጉሡን መከረው። በዚያን ጊዜም ከአደባባይ አወጡት እናቱም በብዙ ልቅሶ ልትሸኘው መጣች። እርሱም ሲመግባቸው ስለ ነበረ የታሠሩ ምዕመናን ስለ ድኆችና ምስኪኖች ስለ ሙት ልጆችና ስለ ባልቴቶች የሚሹትን በመስጠት እንድትጐበኛቸው አዘዛት ከዚያም አፉን ለጉመው ወሰዱት። ❤ በእስክንድርያ አገር ወደ መኰንኑ ኄርሜኔዎስ ዘንድ በደረሰ ጊዜ ታላቅ ሥቃይን አሠቃዩት የእግዚአብሔርም መልአክ ወደ ሰማያት አውጥቶ ስለ ክብራቸው ለመናገር የሚያስጨንቁ የብርሃን ማደሪያዎችን አሳይቶ ወደ መኖሪያው መለሰው። መኰንኑም በእሳት በአፈሉት በዝፍት፣ በዲን ደግሞ አሠቃየው ከዚያም በብረት አልጋ ላይ አስተኝተው ከበታቹ እሳትን አነደዱ። ደግመው ከውሽባ ማንደጃ ውስጥ ጨመሩት በየአይነቱ በሆነ ሥቃይም አሠቃዩት የክብር ባለቤት ጌታችንም ያጸናውና ከሥቃዩ ያስታግሠው መልአኩንም ልኮ ከቊስሉ ይፈውሰው ነበር። ❤ ከዚህም በኋላ ወደ እንዴናው ከተማ ላከው በዚያም ታላቅ ሥቃይን አሠቃዩት ምላሱን ቆረጡ። በእሳት ያጋሉዋቸውን ችንካሮች በጐኖቹ ውስጥ ጨመሩ እግዚአብሔር ግን አጽንቶ አስታግሦ ያለ ጉዳት በደኅና ያነሣዋል። ከዚህም በኋላ በዚያ በረኃብ እንዲሞት ከዱር ባለ ግምብ ውስጥ አሠሩት። እርሱ ግን መጥረብ የሚያውቅ ስለሆነ ላይዳዎችን በመጥረብና በመሸጥ በየጥቂቱ እየተመገበ የቀረውን ለድኆች እየሰጠ ኖረ። አንድ መኰንንም መጥቶ በዚያ ግምብ አቅራቢያ አደረ ስለ ቅዱስ ፊቅጦርም እርሱ የንጉሥ የሠራዊት አለቃ የሆነ የኅርማኖስ ልጅ እንደሆነ ነገሩት። መኰንኑም ወደርሱ አቅርቦ ብዙ ሸነገለው ባልሰማውም ጊዜ ያሠቃዩት ዘንድ አዘዘ ጅማቶቹን መዘዙ አፋን መቱት ቊልቊል ሰቀሉት በእጆቹ ላይ ከባድ ደንጊያ አንጠልጠሉ። ከዚያም ከሚነድ እሳት ውስጥ ጨመሩት ሙጫ፣ አደሮ፣ ማርና ዘይትን አፍልተው በላዩ ደፉበት በማበራያም አበራዩት አፉንም በአሞትና በእሬት አመረሩት ዐይኖቹንም አወለቁት ደግመውም ዘቅዝቀው ሰቀሉት። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾለት አጸናው አረጋጋው። ሥሮቹንም ሕዋሳቶቹን በቦታቸው መለሰለትና አዳነው። ❤ አንዲት ዓሥራ አምስት ዓመት የሆናት ብላቴና ነበረች ቅዱስ ፊቅጦርን ሲአሠቃዩት በቤቷ መስኮት ታየው ነበር። መላእክትም በእጆቻቸው አክሊሎችን ይዘው እነርሱም በቅዱስ ፊቅጦር ራስ ላይ ሲያኖሩአቸው አይታ እንዴት እንዳየች ለአሕዛብ ነገረቻቸው እጅግም አደነቁ ከእርሳቸውም ብዙዎች በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በሰማዕትነት ዐረፉ። ያቺም ብላቴና በጌታችን አመነች መኰንኑም ራሷን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ። የሕይወት አክሊልንም ተቀበለች ሁለተኛም የአመኑትን ሁሉ ራሳቸውን እንዲቆርጡአቸው አዘዘ የሕይወትንም አክሊል ተቀበሉ። ❤ ከዚህም በኋላ የከበረች የቅዱስ ፊቅጦርን ራስ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ተጋድሎውንም ሚያዝያ27 ፈጽሞ የሕይወትና የድል አክሊል ተቀበለ። ምዕመናን ሰዎችም ሥጋውን ወስደው በከበሩ ልብሶች በድርብ በፍታ ገነዙት። እናቱ ማርታም ከአንጾኪያ እስክትመጣ በንጹሕ ቦታ አኖሩት በመጣችም ጊዜ ከዚያ ወሰደችው። ውብ ቤተ ክርስቲያንም ሠርታ ሥጋውን በውስጥዋ አኖረች ከእርሱም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የቅዱስ ፊቅጦር በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 27 ስንክሳር።

"ሁለቱም አንድ አካል ይኾናሉ ፤ ይህ ነገር ጥልቅ ፤ ረቂቅ ምሥጢር ነው ፤ እኔም ለክርስቶስና ለቤተክርስቲያን ምሳሌ አድርጌ እናገረዋለሁ፡፡" ሃይማኖተ አበው ዘስምዓት ✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨ ሚያዚያ
+9
"ሁለቱም አንድ አካል ይኾናሉ ፤ ይህ ነገር ጥልቅ ፤ ረቂቅ ምሥጢር ነው ፤ እኔም ለክርስቶስና ለቤተክርስቲያን ምሳሌ አድርጌ እናገረዋለሁ፡፡" ሃይማኖተ አበው ዘስምዓት ✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨ ሚያዚያ 24 ቀን 2018 ዓ.ም በግራር ደብረ አባይ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን  ከወንድማችን ሀብተ ሚካኤል ጋር  የጋብቻ ሥነ ሥርዓትሽን የፈጸምሽው የሰንበት ት/ቤታችን አገልጋይ ዳናዊት( ወለተ ትንሳኤ ) እንኳን ደስ ያለሽ እንኳን ደስ ያላችሁ ። የአብርሃምንና የሣራን ፤ የይሰሐቅንና የርብቃን ጋብቻ የባረከ አምላክ አንድነታችሁን  ይባርክ እመብርሃን በአማላጅነቷ አትለያችሁ ፤ ቅዱስ ሚካኤል ከፊት ይምራችሁ ከኋላ ይከተላችሁ እያለች ፍኖተ ብርሃን  ሰ/ት/ቤት መልካም የትዳር ሕይወት ትመኝላችኃለች። " ጋብቻ ንጹሕ ነው የወንድና የሴት አንድ መሆንንም እግዚአብሔር አክብሮታል "                           መጽሐፈ ዲድስቅልያ

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤         ❤ #ሚያዝያ ፳፮ (26) ቀን። ❤ እንኳን በአባቱ እጅ በመጥረብያ አንገቱን ተመቶ ሰማዕትነት ለተቀበለ፤ አባቱን ከዐረፈ በኋላ ለፈወሰው #ለጠራቢ_ልጅ_ለቅዱስ_ዮሐንስ ለዕረፍቱ በዓልና #ለሱሴ_ልጅ_ለቅዱስ_ሱስንዮስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #ከቅዱሳን_ስብስጥራስ_ከአባ_ሠርጋና፣ #ከይድራስ ከምስክርነታቸው መታሰቢያና #ከቅዱስ_ሱስንዮስ ጋራ ሰማዕትነት ከተቀበሉ #ከአንድ_ሺህ_አንድ_መቶ_ዘጠኝ_ሰማዕታት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                     ✝ ✝ ✝  ❤ #ቅዱስ_ዮሐንስ፦ ይህም ቅዱስ ከነነዌ አገር ነው አባቱ ጣዖትን የሚጠርብና የሚያመልክ ነው። እናቱ ግን ክርስቲያናዊት ናት ልጅ በአጣችም ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ለመነች ጌታም ልመናዋን ተቀብሎ ይህን የተባረከ ልጅ ሰጣት ስሙንም በሥውር ዮሐንስ ብላ ጠራችው። ስምንት ዓመትም በሆነው ጊዜ የጠረበውን ጣዖት እየሸጠለት አባቱን ያገለግል ነበር። ❤ በአንዲት ዕለትም ጣዖቱን ሊሸጥ ሲሔድ የእግዚአብሔር መልአክ ተገናኘውና "ጣዖት የሰይጣን ማደሪያ እንደሆነ ነገረው ጣዖቱንም ከእጁ እንዲጥለው አዘዘው በክብር ባለቤት በክርስቶስ ማመን አስተማረው" ወደ አባቱም በተመለሰም ጊዜ "ሰማይና ምድርን በውስጣቸውም ያለውን ሁሉ ከፈጠረ ከክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ሌላ አምላክ የለም እኔ ለሰው እጅ ሥራ አልሰግድም" አለው። አባቱም ሰምቶ በእሥር ቤት አሰረው እናቱም መጥታ በክብር ባለቤት ክርስቶስ ስም ደሙን ያፈስ ዘንድ አጸናችው። ❤ ከዚህም በኋላ በነገራቸው ሊሸነግሉት የአገር ሰዎች መጥተው "የአባትህ አምላኮች ለምን ተውክ" አሉት እርሱም "እኔ የሰው እጅ ለሰራቸው ጣዖቶች አልሰግድም እነርሱም የእርኵሳን አጋንንት ማደርያዎች ናቸውንና" አላቸው። አባቱም ይህንን በሰማ ጊዜ ምሳር አንስቶ አንገቱ ቆረጠው በድኑም አልወደቀም በደሙም እስከተጠመቀ ድረስ በእግሮቹ ቆመ እጅ። ❤ እናቱም በደሞ ተጠምቃ "አቤቱ የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የአቤል መስዋዕት በምድረ በዳ የተቀበልክ ይህንን መስዋዕት ከእኔ ተቀበል" አለች። በዚያ ጊዜ አባቱ ሰይጣን አደረበትና አበደ ሚስቱን ወደ ልጇ መቃብር ወስዳው ስለ እርሱ ጸለየች ቅዱስ ዮሐንስም በሌሊት ወደ እርሱ መጥቶ አባቱ በጦር ወጋው ሰይጣኑም ከእርሱ ወጣ ከዚህ በኋላ በክብር ባለቤት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመነና በስሙ ተጠመቀ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር አሜን።                            ✝ ✝ ✝  ❤ #ቅዱስ_ሱስንዮስ፦ ይህም ከሀዲው ከዲዮቅልጥያኖስ ወዳጁ ነበረ የእግዚአብሔር መልአክም ተገለጠለትና ሰማዕት እንደሚሆን ነገረው ይህም ነገር በልብ አደረ። ❤ከዚህም በኋላ አምልኮ ጣዖትን እንዲያስፋፋና እንዲያድሱ ከሹመት ደብዳቤ ጋራ ንጉሡ ወደ ኒቆድምያ ላከው ቅዱሱም አይቶ እጅግ አዘነ ወደ እርሱ አንድ ቄስ አምትቶ ክርስትናንን ተምሮ ተጠመቀ። ከዚህ በኋላ ወደ አንጾኪያ ተመለሰ ፍጥረቱ ልዩ የሆነ ልጅ ወልዳ እቱን አገኛት ከዚህ በፊት ሴት ልጅ ወልዳ ገድላ ደሙን ጠጥታለች ሰይጣን አድሮባታልና በወፍና ከይሲ አምሳልም ይገለጣል በአገር ውስጥም ልጅ በሚወለድ ጊዜ ወደርሱ ወርዳ በሥራይም ገድላ ደሙን ትጠጣለች። ❤ ቅዱስ ሱስንዮስም ይህን በአየ ጊዜ ጦሩን አንስቶ ከልጅዋ ጋራ እኅቱን ገደላት ልጅዋ የሰይጣን ልጅ ነውና ሁለተኛም ሥራየኞች ሲሆኑ ባሏንና የባሏን አባቱን ገደላቸው እነርሱ በሥራያቸው ሰውን እያሳመሙ ይድላሉና። ❤ ከዚህም በኋላ ወደ ኒቆድምያ ተመለሰ ወደዚያ ወደ አጠመቀው ቄስ ደርሶ ያደረገውን ሁሉ ነገረው። ወደ አገሩ አንጾኪያም በተመለሰም ጊዜ ከእርሱ የሆነውን አባቱ ሱሲ አወቀ መገደሉንም ወዶ ከንጉሥ ዘንድ ነገር ሠራበት። ያንጊዜም ቅዱስ ሱስንዮስ ወደ ጣዖታት ቤት ሒዶ ወደ ሲዖል ይወልዱ ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አዘዘቸው ያን ጊዜም ምድር አፋን ከፍታ ዋጠቻቸው። አባቱ ዳግመኛ በንጉሡ ዘንድ ከሰሰው ታላቅ ሥቃይም ያሰቃዩት ዘንድ ንጉሥ አዘዘ በብረት ዘንጎችም ደበደቡት፣ በመንኰራኵር አበራዩት፣ በመዶሻም ቀጥቅጠው ሁለተኛ ደግሞ እህል በሚያበራዩበት መሳርያ አበራዩት፣ ከዚያም በከተማ ውስጥ ጎተቱት የክብር ባለቤት ጌታችንም ያጸናውና በስቃዩም ውስጥ ያስታግሰዋል ከቊስሉም የሚፈውሰውን መልአኩንም ልኮ ያለምንም ጉዳት አነሳው ብዙ ሰዎችም አይተው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በእርሱ ምክንያት ሰማዕት ሆኑ። ንጉሡም ከማሠቃየት በደከመ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ። በሥቃዩም ወራት በሰማዕትነት የሞቱት ቊጥራቸው አንድ ሺህ አንድ መቶ ዘጠኝ ሆነ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 26 ስንክሳር።                           ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "አኀዝከኒ እዴየ ዘየማን። በምክረ ዚአከ ዘየማን። ወምስለ ስብሐት ተወአፍከኒ"። መዝ 72፥23-24። የሚነበቡት መልዕክታት ኤፌ 5፥1-15፣ 1ኛ ዮሐ 3፥7-13 እና የሐዋ ሥራ 17፥16- 21። የሚነበበው ወንጌል ማር 13፥9-14። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችን ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤ ❤ እንኳን #ለትንሣኤ_አራተኛ_ሳምንት በሰላምና በጤና እግዚአብሔር አምላክ አደረሰን።                          ✝ ✝ ✝ ❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፫ "#ተንሥአ_ወአንሥአ_ኵሎ_ሙታን ተንሥአ ወአንሥአ ኵሎ ሙታን ወፈትሖሙ ለሙቁሐን፤ አዝ፣ በዐቢይ ኀይል ወሥልጣን ወአግዐዘ ነፍሰ ጻድቃን፤ አዝ፣ ለአልዓዛር ተንሥእ ዘይቤሎ ወዕውርኒ ዘፈወሶ በቃሉ፤ አዝ፣ #ትንሣኤሁ_ገብረ_በሰንበት_በሣልስት_ዕለት ተንሥአ ወአንሥአ ኵሎ ሙታን ተንሥአ ወፈትሖሙ ለሙቁሐን"። ትርጉም፦ #ተነሣ_ሙታንንም_አስነሣ እስረኞችን ፈታቸው፤ በታላቅ ኀይልና ሥልጣን ተነሣ፤ የጻድቃንን ነፍስ ነጻ አወጣ፤ አልዓዛርን ተነሥ ያለው፤ ዕውሩንም በቃሉ የፈወሰው አምላክ በታላቅ ኀይልና ሥልጣን ተነሣ፤ #ትንሣኤውንም_በሰንበት_አደረገ፤ በሦስተኛው ቀን ከሞት ተነሣ፤ ሙታንንም አስነሣ፤ እስረኞችንም ፈታ። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።                                                     ✝ ✝ ✝ ❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "አንሰ ሰከብኩ ወኖምኩ። ወተንሣእኩ እስመ እግዚአብሔር አንሥአኒ"። ኢይፈርህ እምአእላፍ አሕዛብ። መዝ 3፥5-6። የሚነበቡት መልዕክታት ቆላ 3፥1-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 3፥15-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 11፥1-19። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 24፥33-45። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ነው። መልካም ዕለተ ሰንበትና የበዐለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤          ❤ #ሚያዝያ ፳፭ (25) ቀን። ❤ እንኳን በጡቶቿ ደም ልጆቿን ላጠመቀች #ለቅድስት_ሣራና_ከሁለት+ልጆቿ ጋራ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍት በዓላቸው እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #ከባሕታዊ_አባ_በብኑዳ፣ ከተጋዳዩ #ቅዱስ_ቴዎድሮስ_ከአባ ዮሐንስ ሊቀ ጳጳሳት በፋርስ መከራን ከመቶ ሰማዕታትና #ከዶራም ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                            ✝ ✝ ✝  ❤ #ቅድስት_ሣራና_ሁለት_ልጆቿ፦ ይቺም ቅድስት ከአንጾኪያ አገር ናት እርስዋም ከዲዮቅልጥያኖስ መኳንንት ለአንዱ ስሙ ስቅራጥስ ለሚባል ሚስቱ ናት እርሱም በፊት ክርስቲያን ነበረ በኋላ ንጉሡን በመፍራት ካደ እርስዋ ግን በክርስትናዋ ጸንታ ኖረች። ባልዋ ስቅራጥስም "እኔ የክርስቲያንን ሃይማኖት እወዳለሁ የንጉሡን ሥቃይ ከመፍራት በቀር ክርስቶስን በልቤ አልካድኩትም" ይላት ነበር። እንደዚህም ስትኖር ሁለት ልጆችንም ወለደች በአንጾኪያም አገር የክርስትና ጥምቀትን ልታስጠምቃቸው አልተቻላትም። አብያተ ክርስቲያናት ተዘግተዋልና ጠፍተዋልምና ሰውን ወዳድ ክርስቶስን ብዙ ስለመውደዷ ልጆቿን ታስጠምቃቸው ዘንድ ታላቅ ተጋድ አደረች ወደ እስክንድርያ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጴጥሮስ ልትሔድ ወዳ አሽከሮቿን አስከትላ ሁለቱን ልጆቿን ይዛ በመርከብ ተሳፈረች። ❤ የክብር ባለቤት ጌታችንም የሃይማኖቷን ልዕልና ለመጪው ትውልድ ሊገልጥ ወዶ ያቺ መርከብ ለመሥጠም እስከምትደርስ በባሕር መካከል ጥልቅ ነፋስን አስነሣ። ይቺ ቅድስትም ልጆቿ ሳይጠመቁ እንዳይሞቱ ፈራች ተነሥታም ጸለየች ከዚያም ምላጭ አንሥታ ጡቷን የቀኙን በጣች ከደሟም ወስዳ ፊታቸውን በመስቀል ምልክት ቀባች በደረታቸውና በጀርባቸውም ላይ እንዲሁ አደረገች በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስም ስም በባሕሩ ውስጥ አጠመቀቻቸው ያን ጊዜም ታላቅ ጸጥታ ሆነ። ❤ ወደ እስክንድርያ አገርም በደረሰች ጊዜ ከአገር ልጆች ጋራ ያጠምቃቸው ዘንድ ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጴጥሮስ ልጆቿን አቀረበች በዚያን ጊዜም ከአገር ልጆች አጠመቀ። ወደልጆቿም ደርሶ ሊአጠምቃቸው ወሰዳቸው ያን ጊዜ ውኃው ረጋ እነርሱን ትቶ ከአገር ልጆች አጠመቀ ውኃውም ተፈትቶ ወረደ ደግሞ ሊአጠምቃቸው ወደ ልጆቿ ተመለሰ አሁንም እንደቀድሞው ውኃው ረጋ እንዲሁም ሦስት ጊዜ አደረገ ውኃውም ይረጋል አደነቀ። እናታቸውን አቅርቦ ጠየቃት እርሷም የሆነውን "በባሕር መካከል ዐውሎ ነፋስ እንደተነሣባት ጡቷን በጥታ ደሟን እንደ ቀባቻቸውና በባሕር ውስጥ እንዳጠመቀቻቸው ነገረችው ስለ አደረገችውም በድፍረት በፊቱ ሰግዳ ይቅር ይላት ዘንድ ለመነችው"። አባ ጴጥሮስም " ሴትዮ አትፍሪ ሃይማኖትሽ ፍጹም ነው አንቺ በባሕር ውስጥ በአጠመቅሻቸው ጊዜ በመለኮታዊት እጁ ያጠመቃቸው ባለቤቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና አይዞሽ" አላት። ማጥመቁን በፈጸመ ጊዜ ሥጋውን ደሙን አቀበላቸው። ❤ ይቺም ቅድስት ወደ አንጾኪያ ቤቷ ተመለሰች። ባሏም በአያት ጊዜ ይህን በማድረጓ ተቆጥቶ ወደ ንጉሡ ሒዶ ከሰሳት ያደረገችውንም ነገረው። ንጉሡም ወደርሱ ያቀርቧት ዘንድ አዘዘ ስትቀርብም ወደ "እስክንድርያ ለምን ሔድሽ ከክርስቲያን ወገኖች ጋራ ልታመነዝሪ ነውን" አላት። እርሷም እንዲህ ብላ መለሰችለት "ክርስቲያኖች አያመነዝሩም እንደናንተ የረከሰ ጣዖትን አያመልኩም ከእንግዲህ ደግሞ ከእኔ ቃልን አትሰማም የወደድከውን አድርግ" ሁለተኛም "በእስክንድርያ ካንቺ የሆነውን ንገሪኝ ብሎ ጠየቃት ምንም ምን አልመለሰችለትም። ❤ ንጉሥ ከዲዮቅልጥያኖስም እጆቿን የኋሊት አሥረው ሁለቱን ልጆቿን በሆድዋ ላይ አድርገው ሦስቱንም በእሳት ያቃጥሉአቸው ዘንድ አዘዘ። ፊቷንም ወደ ምሥራቅ መልሳ ወደ ክብር ባለቤት ጌታችን ጸለየች ከዚያም ከልጆቿ ጋራ ሚያዝያ25 አቃጠሉዋት የድልና የሕይወት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቷ ለዘላለም ይማረን አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 25 ስንክሳር።         

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤        ❤ #ሚያዝያ ፳፬ (24) ቀን። ❤ እንኳን #ለቅዱስ_ኤስድሮስ ባልንጀራ #ለቅዱስ_ፃና ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓልና ለእስክንድርያ ስልሳ አምስተኛ ሊቀ ጳጳሳት ብዙ ተዓምራት ላደረገ #ለአባ_ስንትዮ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #ደብረ_ሲና_ከከበረችበት_ከአባ_ይድራ መታሰቢያው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያስትፈን።                             ✝ ✝ ✝  ❤ #ቅዱስ_ፃና፦ ይህም እንዲህ ነው ባልንጀራው ከኤስድሮስ ጋራ ከአሠቃዩት በኋላ ባልጀራው ኤስድሮስ በሰማዕትነት ሞተ። ቅዱስ ፃናም በእሥር ቤት ቀረ ከአገረ ፈርማ መኰንንም ታሠረ በእርሱም ፈንታ ሌላ መኰንን ተሾመ። ያንን መኰንንም የክብር ባለቤት የሆነ የኢየሱስ ክርስቶስ ስም የሚጠራ ክርስቲያንን ሁሉ እንዳያስቀር ከሀዲው ንጉሥ አዘዘው። ስለ ቅዱስ ፃናም እርሱ ከጭፍሮች ውስጥ እንደሆነ ጽኑዕ ሥቃይም እንዳሠቃዩትና ከአላማውም እንዳልተመለሰ በነገሩ ጊዜ የከበረች ራሱን ይቆርጡት ዘንድ አዘዘና ቆረጡት የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበለ። ❤ የቅዱስ ፃና እናቱም ቅዱስ ኤስድሮስ ሰማዕት በሆነ ጊዜ አስቀድማ እንዳየች አሁንም ብርሃናውያን መላእክትን የቅዱስ ፃናን ነፍስ ሲያሳርጓት አይታ ለሰው ነገረች። ምዕመናንም ሥጋውን ወስደው ገንዘው ሰምኑድ በሚባል አገር ከባልንጀራው ከኤስድሮስ ሥጋ ጋር አኖሩት። በውስጥዋም እስከ ዛሬ በዓል ይደረግላቸዋል። ወደ እርሳቸው በእምነት ለሚመጣም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ይታያል። በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን።                            ✝ ✝ ✝  ❤ #አባ_ስንትዩ፦ ይህም ከታናሽነቱ ጀምሮ መንፈሳዊ ነው። በአስቄጥስም ገዳም በአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን በበጎ ሥራ በገድል ተጠምዶ አድጎ በዚያው ገዳም አበምኔት ሁኖ ተሾመ። ከዚህም በኋላም ሕዝቡና ኤጲስቆጶሳቱ መርጠውት በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት። ነገር ግን በዘመኑ ሁሉ ከእስላሞች ነገሥታት ታላቅ ችግርና ኀዘን ደረሰበት። ይኸውም በእርሱ ዘንድ ምንም ምን ያልኖረውን ሊሰጣቸው የሌለውን ብዙ ገንዘብ ይሰጣቸው ዘንድ ፈልገው ይዘውታልና። እግዚአብሔር በእጆቹ ብዙ ድንቆች ተአምራቶችን አደረገ ብዙዎችን ጭንቅ ከሆነ ደዌያቸው አድኖቸዋልና ከሰዎችም ላይ ሰይጣናትና አስወጥቷልና በአገረ መርዩጥ ላይ በጸሎቱ ዝናምን አዝንሞአልና። እርሱም ዝናምን ከማጣት የተነሣ ወንዞቻቸው ጉድጓዶቻቸው ሁሉ ደርቀው ከረኃብና ከውኃ ጥም የተነሣ ለሞት ተቃርበው በታላቅ ረኃብ ሦስት ዓመት ኑረዋልና። ❤ በሰማዕት ቅዱስ ሚናስ ቤተ ክርስቲያን በዓልን ሊያከብር ወደርሳቸው በደረሰ ጊዜ የዚያች አገር ሰዎች ወደ ርሱ ተሰብስበው ውኃ በማጣት እንደ ተቸገሩ ነገሩት እርሱሙ ፈጽሞ አጽናናቸው። የቅዳሴውንም ሥርዓት ከፈጸመ በኋላ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ወዲያውኑ ታላቅ ነጐድጓዶችና ኩሬዎች ሁሉ ሞሉ የተክል ቦታዎች ሁሉ ረኩ። ረኃብ በሆነባቸው በእነዚህ ሦስት ዓመት እንደመላ ኖረ። ❤ አራተኛውም በአስቄጥስ አረቦች በተሰበሰቡ ጊዜ በዚያ የሚኖሩትን መነኰሳት ይገድሉአቸው ዘንድ ከበቡአቸው ይህም አባት መስቀሉን ይዞ ወደእርሳቸው ወጣ መስቀሉንም በአዩ ጊዜ ወደኋላቸው ተመልሰው ሸሹ በማንም ላይ ከቶ ጉዳት አላደረሱም። ደግሞ በትምርቱ ከአገሩና ከመንጋው ውስጥ ክህደትንና ኑፋቄን አስወገደ በዚያን ጊዜ ስለእኛ መከራ የተቀበለው ትብስእት ብቻውን ነው አምላክ አይደለም የሚሉ ነበሩና። ❤ ይህም አባት ስንትዩ በከበረ በታላቁ ጾም ወራት መልክትን ጽፎ ለአገሩ ሁሉ ላከ በውስጥዋም እንዲህ የሚል እያስተማረ "ስለእኛ መከራ የተቀበለ እግዚአብሔር ቃል በሥጋ ነው ከተዋሕዶ በፊት ሁለት የነበሩ በተዋሕዶ አንድ ባሕርይ ስለሆነ አንዲት ሰዓት ወይም የዐይን ጥቅሻ ያህል ከቶ አልተለያዩም በመከራ ጊዜ ወይም በሞት ከመለኮቱ ያልተለየ እርሱ አካላዊ ቃል በሥጋው ስለ እኛ መከራን ተቀበለ"። ይቺም መልእክት በአገሩ ሁሉ በአነበቡአት ጊዜ የክርስቲያን ወገኖች ታላቅ ደስታ ደስ አላቸው እሊያ የሳቱትም ተመልሰው ንስሓ ገቡ። ሁለኛም ደግሞ ምላሳቸውን መቆረጥ የሚገባቸው የተሳሳቱ የመለኮት ባሕርይ ሞተች የሚሉ ሰዎች ተገለጡ እሊህም የብልንያ አገር ሰዎችና ኤጲስቆጶሳቸውም ነው። ❤ ይህም አባት ይህን የእብደትና የስንፍና ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ አዝኖ መልእክትን በውስጡ እንዲህ ጻፈ "እግዚአብሔር ባሕርዩ አትመረመርም የማትዳሠሥ የማትታመም ናት እግዚአብሔር ቃል ከእኛ ነሥቶ ያለ መለያየትና ያለ መቀላቀል ከመለኮቱ አዋሐደው ከሰውነቱ ባህርይ በቀር ሕማምን አታስገባም" ሁለተኛም በውስጥዋ እንዲህ አለ "እኛ መከራ ከሚቀበል ከሥጋው እግዚአብሔር ቃልን አንለየውም በመከራውም በሥራው ሁሉ አንድ እንደሆነ እናምናለን እንጂ ሁለተኛም መለኮቱ በባሕርዩ የማይታመም የማይሞት እንደሆነ ከመለኮት ሳይለይ ስለእኛ መከራ ተቀብሎ ሞተ እንጂ"። የመልእክቱም ደብዳቤዎች ወደእነዚህ ሰዎች ደርሰው በአነበቡአቸው ጊዜ ከስሕተታቸው ተመልሰው በእውተኛዪቱ በቀናች ሃይኖት አመኑ። ኤጲስቆጶሳቸውም ጋራ ወደዚህ አባት ወደ ሊቀ ጳጳሳት ስንትዩ ፊት ቀርበው የቀናውን እምነት ተቀብለው አመኑ ታላቅ ስሕተታቸውንና በደላቸውንም ይተውላቸው ዘንድ ለመኑት እርሱም ስሕተታቸውን እያመኑ በኤጲስቆጶሳቱ ሁሉ በካህናቱ በሕዝቡም ፊት እንዲሰግዱ አዘዛቸው እንዳዘዛቸው አደረጉ በደላቸውንም ተወላቸው። ❤ ይህም አባት አብያተ ክርስቲያናትን ስለማነፅ የስደተኞችንም ቦታዎች ስለማዘጋጀት ብዙ የሚአስብ ነው ከዚህ የሚተርፈውንም ለድኆችና ለምስኪኖች ይሰጣል። መልካም ጉዞንም በመጓዝ እግዚአብሔርን አገለገለው ሚያዝያ24 በሰላምም ዐረፈ። የሹመቱም ዘመን ዐሥራ አምስት ዓመት ሆነ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ በአባት ስንትዩ ጸሎት ለዘላለሙ ይማረን አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 24 ስንክሳር።                           ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወወሀብኮሙ ትእምርተ ለእለ ይፈርሁከ። ከመ ያምሥጡ እምገጸ ቅስት። ወይድኀኑ ፍቁራኒከ"። መዝ 59፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 12፥1-12፣ 2ኛ ጴጥ 3፥16-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 16፥27-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 21፥28-33። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ በዚያም ጊዜ ስለ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሥራ ነገሥታቱ ሁሉም ደነገጡ ኀፍረት ደግሞ እንዳይጨምርባቸው ከእርሱም እንዲአርፍ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ እንዲጽፍ ንጉሥ ዱድያኖስን መከሩት። ያን ጊዜም የክብር ቅዱስ ጊዮርጊስን ራስ በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ ድል አድራጊ ቅዱስ ጊዮርጊስም እጅግ ደስ አለው እሳት ከሰማይ አውርዶ ሰባውን ነገሥታትን ያቃጥላቸው ዘንድ መከራውም ከክርስቲያን ወገን ጸጥ ይል ዘንድ ጌታችንን ለመነው። ወዲያው እሳት ወርዶ ከሠራዊታቸው ጋራ ሰባውን ነገሥታት አቃጠላቸው። ❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ተገልጾ ብዙ ቃል ኪዳን ሰጠው። በምድር መታሰቢያህን ለሚያደርግ ሁሉ እኔ ኃጢአቱን ሁሉ እደመስሳለሁ በመከራም ውስጥ ሁኖ በባሕርም ሆነ፣ በየብስ ወይም በደዌ በስምህ የሚለምነኝን እኔ ፈጥኜ ከመከራው አድነዋለሁ ይህንንም ጌታችን ተናግሮ በክብር ወደ ሰማይ ወጣ። ❤ ከዚህም በኋላ ወታደሮቹ የቅዱሳን የከበረች ራሱን ቈረጡት ደም፣ ውኃና ወተት ፈሰሰው፤ ጌታም ቅዱስ ሚካኤልን በብርሃን ልብስ ደሙን እንዲቀበለው አዘዘ። ጌታችንም የኃያሉ የቅዱስ ጊዮርጊስን ነፍስ በእጁ ተቀብሎ ሳማት፤ በሰማያዊ ልብስም አጐናጥፎ ከእርሱ ጋራ ወደ ሰማይ አሳረጋት። አየር በሙሉ ቅዱሳን መላእክትን ተሞላ። ለቸር አባቱና ለመንፈስ ቅዱስ ቊርባን አድርጎ እስኪያቀርበው ድረስ ቅዱሳን ሁሉ በየወገናቸው ያመሰግኑ ነበር። የብርሃን ልብስ አለበሰው። በዕንቈ ባሕርይ ያጌጠ ከጽሩ ወርቅ የተሠሩ መከራ በተቀበለባቸው ሰባት ዓመታት ልክ ከዕፀ ሕይወት አበቦች የተሠሩ አክሊሎች ያሉበትን ዘውድ አቀዳጀው ለዘላለም ከማኅበረ በኵር ጋራ ስሙን ጻፈው። ሰማያውያን መላእክትና ቅዱሳንንም ሁሉ በየወገናቸው በመንበሩ ላይ እንዲአስቀምጡት፤ በኢየሩሳሌም ሰማያዊት በዓል እንዲ ያደርጉለት አዘዛቸው። ❤ ከዚህም በኋላ ከመብረቁ፣ ከነጐድጓድ፣ ከንውጽውጽታው ጽናት፣ ከዝናሙ ብዛት የተነሳ በምድር ላይ ትልቅ ድንጋፄ ሆነ። ምድርም ሦስት ጊዜ ተናወጸች ከዚያ ቆመው የነበሩ ሰዎች ሁሉ ሸሹ ወደ ከተማም ሔዱ ጭፍሮችም ይህንን በአዩ ጊዜ በቅዱስ ጊዮርጊስ አምላክ አመኑ። ነፍሱም ወደ ሰማይ በዐረገች ጊዜ በእግዚአብሔር ፊት ሰገደች። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምታምን ነፍስ ከሥጋዋ በተለየች ጊዜ አስቀድሞ ለሥሉስ ቅዱስ ትስገድ ከዚህ በኋላ ወደ ወዳጄ ወደ ጊዮርጊስ ይወሰዷት እና ለርሱ እጅ ትንሣ ብሎ አዘዘ፤ በዚህ ሁኔታ የቅዱስ ጊዮርጊስ ምስክርነቱ ሚያዝያ በባተ በሃያ ሦስት ቀን በዕተ ዓርብ ዘጠኝ ሰዓት ተፈጸመ። አገልጋዮቹም ሥጋውን ወስደው በልብስ ጠቀለሉት ወደ ሀገሩ ልዳም ወስደው ቤተክርስቲያን ሰርተው በውስጡ አኖሩት፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የቅዱስ ጊዮርጊስም በረከትቱ ረድኤቱ ሁላችን የክርስቲያን ወገኖችን ከሥጋና ከነፍስ መከራ ይጠብቀን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ ገድለ ጊዮርጊስ እና የሚያዚያ 23 ስንክሳር።                               ✝ ✝ ✝   ❤ #ቅዱስ_ሮቆ፦ በአንዲት ዕለትም በጸሎት ቁሞ ሳለ የንዳድ ትንኝ ነደፈው ቊስሉን እያሳየ በብዙ ልቅሶ ወደ ጌታችን ለመነ። ያን ጊዜም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደመና ላይ ተገለጠለት በአንጻሩም ቁሞ "ወዳጄ ሮቆ አትፍራ ላድንህ ወደ አንተ መጥቻለሁና ደግሞም የሮቆ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ከንዳድ በሽታ አድነኝ ብሎ በስምህ ለሚለምነኝ የንዳድ በሽታ በላዩ ላላመጣበት ከአንተ ጋራ ቃል ኪዳንን ላጸና መጣሁ" አለው። ይህንንም ብሎ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ። ❤ ቅዱስ ሮቆም በብዙ ገድል ተጠምዶ ኑሮ ሚያዝያ23 በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ ልመና ይማረን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 23 ስንክሳር።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ይቀጠቅጦሙ ለነገሥት በዕለተ መዐቱ። ወይኴንኖሙ ለአሕዛብ ወያበዝኅ አብድንተ። ወይሰብር አርእስተ ብዙኃን በዲበ ምድር"። መዝ 109፥5-6። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 12፥1-12።                         ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #ዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወይርአዩ አሕዛብ በቅድመ አይንቲነ። በቀለ ደሞሙ ለአግብርቲከ ዘተክዕወ። ይባእ ቅድሜከ ገዓሮሙ ለሙቁሓን"። መዝ 78፥10-11። የሚነበቡት መልዕክታት 2ቆሮ 1፥1-12፣ 1ኛ ጴጥ 1፥6-10 እና የሐዋ ሥራ 14፥1-23። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥16-34። የሚቀደሰው የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ወይም የቅዱስ ዲዮስቆሮ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ጊዮርጊስ የዕረፍት በዐልና የበዐለ ሃምሳ ሶሞን። ለሁላችንም ይሁንልን።

❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤             ❤ #ሚያዝያ ፳፫ (23) ቀን። ❤ እንኳን ፀሐይና የአጥብያ ኮከብ ለተባለ #ለፀሐየ_ልዳ_ለኮከበ_ፋርስ ለታላቁና ክቡር ለሆነ #ለሰማዕታት_አለቃ_ለቅዱስ_ጊዮርጊስ ለምስክርነቱ (ለዕረፍቱ) ፍፃሜ ለ1713ኛ ዓመታዊ መታሰቢያ በዓልና ስሙን ለጠራ ጌታችን በንዳድ (በወባ) በሽታ የተያዛ ሰው እንደሚያድነው ቃልኪዳን ለገባለት ተአምራት እሰከ አሳየ ድረስ ለተጋደለ #ቅዱስ_ሮቆ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                                                    ✝ ✝ ✝   ❤ #ሊቀ_ሰማዕታት_ቅዱስ_ጊዮርጊስ፦ የዚህም ቅዱስ አባቱ መስፍን ነው ስሙም አንስጣስዮስ ይባላል ከቀጰዶቅያ አገር ነው የእናቱም ስም ቴዎብስታ ይባላል ከፍስጥዓዔም አገር ናት ታናሽ ሆኖ ሳለ አባቱ ዐረፈ። ሃያ ዓመትም በሆነው ጊዜ የአባቱን ሹመት ሊቀበል ወደ ንጉሥ ዱድያኖስ ዘንድ ሔደ። ንጉሡም ጣዖት አቁሞ ጣዖትን እንዲአመልኩ ሰዎችን ሁሉ ሲያስገድዳቸው አገኘው። ይህንንም አይቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ እጅግ አዘነ በእርሱ ዘንድ ያለውን ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች ለምስኪኖች ሰጠ ባሮቹንም ነፃ አወጣቸው። ❤ ከዚህ በኋላ በንጉሥ ፊት ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። ንጉሡም አባበለው ብዙ ቃል ኪዳንም ገባለት እርሱ ግን አልተቀበለውም። ለመስማት እንኳ የሚያስጨንቅ ሥቃይን አሠቃየው ጌታችን ግን ያጸናዋል ቊስሉንም ያድነዋል ሦስት ጊዜም እንደ ሚሞት እርሱም እንደሚአስነሣው በአራተኛውም የምስክርነት አክሊል እንደሚቀበል ነገረው። ቃል ኪዳንም ሰጠው ስሙ በዓለሙ ሁሉ የተገለጠ ይሆን ዘንድ በተጋድሎና መከራ በመቀበልም ጽኑዕ በሆነ ሥቃይም ሰባት ዓመት እንደሚኖር መላእክትም እንደሚአገለግሉት ነገረው። ❤ ንጉሡም ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለመታዘዙና ባለመመለሱ እጅግ አዘነ ስለዚህም አትናስዮስ የሚባል ታላቅ ሥራየኛ አመጣ እርሱም መርዝን ቀምሞ በጽዋ መልቶ አስማት ደግሞ እንዲጠጣ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሰጠው። ወዲያውኑ የሚሞት መስሎት ነበር። ቅዱሱም ያንን ጽዋ በመስቀል መልክት አማትቦ ጠጣው ምንም ጉዳት አልደረሰበትም። ያ መሠርይም በክብር ባለቤት በጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አምኖ በሰማዕትነት ሞተ። ከእርሱ ጋራ ሌሎች ብዙዎች ሰዎች በሰማዕትነት ሙተው የሕይወት አክሊል ተቀበሉ ቊጥራቸውም ሠላሳ ሺህ ሰባት መቶ ነፍስ ነው። ❤ ቅዱስ ጊዮርጊስ በዱድያኖስና በሰባ ነገሥታት ፊት በቆመ ጊዜ በዚያም የተቀመጡባቸው የዕንጨት ወንበሮች ነበሩ። ቅዱሱንም "እሊህን የተቀመጥንባቸውን ወንበሮች እንዲበቅሉ እንዲአብቡና እንዲአፈሩ ታደርጋቸው ዘንድ ከአንተ እንሻለን" አሉት። በዚያን ጊዜ ጸለየ እንዳሉትም አደረጋቸው ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው ቊጥር የሌላቸው ብዙ አሕዛብ በጌታችን አመኑ። ❤ ከዚህም በኋላ ቅዱሱን ወስደው በጐድጓዳ ብረት ምጣድ ውስጥ አበሰሉት። አቃጥለው አሳርረው ሥጋውንና ዐጥንቱን ፈጭተው አመድ አድርገው ከረጅም ይድራስ ከተባለ ተራራላይ በተኑት። ጌታችንም ነፍሱን ወደ ሥጋው መልሷት ደግሞ አስነሣው። ወደ ነገሥታቱም ተመልሶ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ስም ሰበከ። ቊጥር የሌላቸው አሕዛብ አይተው አደነቁ በጌታችንም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ። ❤ ነገሥታቱም ደግመው ሙታኖችን ብታስነሳ አምላክህ ዕውነተኛ አምላክ እንደሆነ እናውቃለን በእርሱም እናምናለን" አሉት። ቅዱሱም ጸለየ ከመቃብር ጒድጓድም ውስጥ ወንዶችና ሴቶችን ጐልማሶችንም አስነሣላቸው እነዚያም በክብር ባለቤት በጌታችን ስም አስተማሩ የገሀነምንም ወሬ ተናገሩ ጥምቀትንም ተቀብለው ተመልሰው ዐረፉ። ከሀድያን ነገሥታት ግን ሙታንን ያስነሣህ አይደለም የረቀቁ ሰይጣናትን አሳየህ እንጂ ብለው ተከራከሩ። ከዚያም ከጭንቀታቸው ብዛት የተነሣ ከአንዲት ድኃ ሴት ዘንድ አስጠበቁት እርሷም እንጀራ ልትለምንለት ወጣች የእግዚአብሔርም መልአክ በላዩ ከበጎ ነገር ሁሉ የተመላ ማዕድን አቀረበለት። የዚያች መበለትም ቤቷ ምሰሶ ቅርጫፍን አበቀለ ታላቅ ዛፍም ሆነ። ያቺም መበለት በተመሰለች ጊዜ የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍ አብቅሎ ታላቅ ዛፍ እንደሆነ ስለ ማዕዱም ይህን ታላቅ ምልክት አይታ "የክርስቲያኖች አምላክ ሰው ተመስሎ ወደእኔ መጣ" አለች። ቅዱሱም "እኔ አምላክ አይደለሁም የአምላክ ባሪያ ነኝ እንጂ" አላት። እርሷም እንዲህ ብላ ለመነችው "የአምላክ አገልጋይ ከሆንክ ቸርነትህ እንድትደርሰኝ እለምንሃለሁ። ዕውር፣ ደንቆሮ፣ ዲዳ፣ ጐባጣ የሆነ ልጅ አለኝና ታድንልኝ ዘንድ እለምህሃለሁ"። ስለ ጌታችን እምነትም አስተማራትና በመስቀል ምልክት አማተበው ያንጊዜም አየ። ቅዱስም "በሌላ ጊዜ እንዲሰማ እንዲናገርና እንዲሔድ እንዲአገለግለኝም እኔ እሻለሁ" አላት። በዚያን ጊዜ ንጉሡ በአገሩ ሜዳ ውስጥ ሲዘዋወር ያቺን ዛፍ አይቶ አደነቀ ስለ እርሷም ጠየቀ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከእርሷ ዘንድ የተቀመጠባት የዚያች መበለት የቤቷ ምሰሶ እንደሆነ ነገሩት። ንጉሡም ተቆጣ ቅዱሱንም ከዚያ ወስዶ አስገረፈው በመንኰራኵር አበራዩት ሙቶም በከተማ ውጭ ጣሉት ጌታም ከሞት አስነሣው ወደ ነገሥታቱም ተመለሰ ንጉሡም አይቶ ደነገጠ ስለ ሕይወቱም አደነቀ። ❤ ከዚህም በኋላ ይሸነግለው ዘንድ ጀመረ በመንግሥቱ ላይም ሁለተኛ ያደርገው ዘንድ ቃል ገባለት ቅዱስ ጊዮርጊስም እየዘበተበት "ነገ በጥዋት ለአማልክቶችህ መሥዋዕትን አቀርባለሁ አንተም ሕዝቡ እንዲሰበሰቡ እዘዝ እኔ ስሠዋ እንዲአዩ" አለው። ንጉሡም ዕውነት የሚሠዋ መስሎት ደስ አለው ወደ ቤተ መንግሥቱም እልፍኝ አስገብቶ አሳደረው። ለጸሎትም ተነሣ የዳዊትንም መዝሙር አነበበ የዱድያኖስ ሚስቱ እለእስክንድርያ ንግሥት ሰምታ ቃሉ ደስ አሰኛት የሚያነበውንም ይተረጒምላት ዘንድ ለመነችው እርሱም እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ሰው እንደሆነበት ጊዜ የሆነውን ሁሉ ሊያስረዳትና ሊያስገነዝባት ጀምረ ትምህርቱም በልቡዋ ተቀርጾ በክብር ባለቤት በጌታችን አመነች። ❤ በማግሥቱም ቅዱስ ጊዮርጊስ ለአማልክት ሲሠዋ ለማየት ሰው ሁሉ እንዲሰበሰብ ዐዋጅ ነጋሪ ዞረ የቤቷን ምሰሶ ያበቀለላት ያቺ መበለት ሰምታ ዕውነት መስሏት እጅግ እያዘነች ልጅዋን ተሸክማ እያለቀሰችም ወጣች። ❤ ቅዱስ ጊዮርጊስ በአያት ጊዜ ፈገግ አለ "ልጅሽን በምድር ላይ አኑሪው" አላት ከዚያም ልጅዋን ጠርቶ "ወደ አጵሎን ሒድ ወደእኔም ይመጣ ዘንድ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም እዘዘው" አለው። ያን ጊዜ ያ ልጅ ድኖ ቅዱስ ጊዮርጊስ እንዳዘዘው ወደ ጣዖቱ ቦታ ሒዶ አዘዘው። በጣዖቱ ያደረ ያ ርኵስ መንፈስም ከማደሪያው ወጥቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አለበት መጥቶ "እኔ ሰውን ሁሉ የማስት እንጂ አምላክ አይደለሁም" ብሎ በሕዝቡ ሁሉ ፊት አመነ። ቅዱሱም ትውጠው ዘንድ ምድርን አዘዛትና ወዲያውኑ ዋጠችው ጣዖታቱም ከአገልጋዮቻቸው ጋራ አጠፋቸው ከወገኖቹ ጋራ ዐፈረ። ብስጭትና ቁጣንም እንደተመላ ወደ ንግሥት ሚስቱ ዘንድ ገባ። እርሷም "አምላካቸው ጽኑዕና ኃያል ነውና ክርስቲያኖች አትጣላቸው አላልኩህምን" አለችው። ይህንንም ከእርስዋ ሰምቶ በእርሷ ላይ እጅ ተቆጣ ወደ ክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ እምነት ቅዱስ ጊዮርጊስ እንደአስገባት አወቀ። ከዚህም በኋላ ከከተማ ውጭ እንዲጐትቷትና በመጋዝም እንዲሰነጥቋት አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች።

በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።                             ✝ ✝ ✝  ❤ #ሐዲስ_አባ_ማርቆስ፦ እርሱም በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች አርባ ዘጠነኛ ነው። ይህም አባት ከእስክንድርያ አገር ነው እርሱም በሥራው ሁሉ ቅድስናውን ጠብቆ ኖረ የተማረም ዐዋቂ ሆነ ለወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ በስም ሁለተኛ ነው። አባ ዮሐንስም ዲቁና ሾመው እጅግ መልካም ካህን ሆነ መጻሕፍትን በሚያነብ ጊዜ በአንደበቱ ቅልጥፍና በነገሩ ጣዕም የሚሰሙት ሁሉ ደስ የሚላቸው ሆነ። ከዚያም አባ ዮሐንስ ከእርሱ ጋራ አኖረው በሊቀ ጵጵስናው ሥራ ሁሉ ሥልጣን ሰጠው ያለ እርሱም ምክር አባ ዮሐንስ ምንም ምን አየሰሠራም። ❤ ከዚህ በኋላ በአባ መቃርስ ገዳም የምንኵስና ልብስ አለበሰው በዚያች የምንኵስና ልብስ በለበሰባትም ቀን ቅዱሳን አረጋውያን አንድ ጻድቅ ሰው መጥቶ በእርሱ ላይ እንዲህ ብሎ በሕዝብ ፊት "ይህ ስሙ ማርቆስ የሚባል ዲያቆን በአባቱ በወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ወንበር ሊሸመጥ አለው" ብሎ ትንቢት ተናገረለት። አባ ዮሐንስም የሚሞትበት ጊዜ ሲቀርብ አባ ማርቆስን ሊቀ ጵጵስና እንዲሾሙት ኤጲስቆጶሳቱን አዘዛቸው በእርሱ መሾምም ደስ አላቸው። ከአባ ዮሐንስ ዕረፍት በኋላም ያለ ፈቃዱ ሾሙት እርሱ ግን ከእርሳቸው ሸሽቶ ወደ በአስቄጥስ ሔደ ሰዎችንም ልከው አሥረው ወደ መንበረ ሢመቱ አመጡት። ከዚህ በኋላም ጸጥ ብሎ ስለ አብያተ ክርስቲያን የሚያስብ ሆኖ የፈረሰውን አነፀ ጠገነ። ❤ በዘመኑም መ*ና*ፍ*ቃ*ን*ን ጠባይ ከሕዝቡ ውስጥ አስወገደ ይኸውም በግብጽ አገር የተገለጡ ለብቻቸውም ቤተ ክርስቲያን ሠርተው የሚኖሩ ናቸው እርሱም አስተምህሮ መክሮ መልሶ ከመንጋዎቹ ጋራ አንድ አደረጋቸው። እግዚአብሔር በዚህ አባት እጅ ድውያንን በመፈወስ አጋንንትን በማስወጣት ብዙ ድንቆች ምልክቶችን ገለጠላቸው። ከእርስቸው አንዱን "አስተውል አንተ ያለ ፍርሀት በድፍረት ሥጋውንና ደሙን የምትቀበል ባትሆን ይህ ባላገኘህም ነበር ከእግዲህ ከክፉ ሥራና ከአንደበትህ ከሚወጣ ከከንቱ ነገርም ሰውነትህን ጠብቅ" አለው። ❤ በዘመኑም በምዕራብ ያሉ እስላሞች ይሸጡአቸው ዘንድ ብዙ ክርስቲያኖችን ከሮም ግዛት ውስጥ ማርከው ወደ እስክንድርያ አመጡአቸው ይህም አባት እጅግ አዘነ ከየገዳማቱና ከምእመናን ብዙ ገንዘብ ለምኖ ከእስላሞች እጅ በሠላሳ ሽህ የወርቅ ዲናር ዋጃቸው የነፃነትም ደብዳቤ ጽፎ ነፃ አወጣቸው። እንዲህም አላቸው "ወደ አገሩ መመለስ የሚሻ እኔ ስንቅ ሰጥቼ አሰናብተዋለሁ ከእኔ ጋራ መኖር የሚሻም ካለ እኔ እጠብቀዋለሁ" አላቸው። የተመለሱ አሉ ከእርሱ ዘንድ የቀሩትንም ጠበቃቸው አጋባቸውም። ❤ ከዚህም በኋላ ስለ መድኃኒታችን ቤተ ክርስቲያን አሰበ አደሳትም ሰይጣንም በአገር ውስጥ ሁከት አስነሥቶ በእሳት አቃጠላት ይህም አባት መልሶ ዳግመኛ አደሳት። ❤ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሊአሳርፈው በወደደ ጊዜ ጥቂት ታመመ በፋሲካ በዓል በእሑድ ቀንም ወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ተገለጠለት "ለሚወዱት እግዚአብሔር ስለ አዘጋጀው ተድላ ደስታ ነገረውና ሥጋውንና ደሙን ከተቀበልክ በኋላ ታርፋለህ" አለው። በነቃ ጊዜም እንዴት እንዳየ ከእርሱ ዘንድ ላሉ ኤጲስቆጶሳት ነገራቸው። ከዚያም የቅዳሴውን ሥርዓት ጀምሮ ቀድሶ ሥጋውን ደሙን ተቀበለ በዚያን ጊዜም ሚያዝያ 22 ዐረፈ። የሹመቱም ዘመን ሃያ ዓመት ሆነ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።                             ✝ ✝ ✝     ❤ በዚችም ቀን #አባታችን_አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም ወርዶ ከከበሩ ቦታዎችና ከሊቀ ጳጳሳት ከባ ሚካኤል በረከትን ተቀበለ። የሁለቱ ቅዱሳን በረከትም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የሚያዝያ 22 ስንክሳር።                            ✝️ ✝️ ✝️ ❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ካህናቲከ ይለብሱ ጽድቀ። ወጻድቃኒከ ትፍሥሕተ ይትፌሥሑ። በእንተ ዳዊት ገብርከ"። መዝ 131፥9-10። የሚነበቡት መልክታት 1ኛ ጢሞ 1፥1-12፣ 1ኛ ዮሐ 2፥22-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 12፥12-18። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 18፥15-21። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችን ይሁንልን።

❤ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። ❤            ❤ #ሚያዝያ ፳፪ (22) ቀን። ❤ እንኳን #በኒቅያ_ጉባኤ_ሊቀ+መንበር+ለነበረው አርዮስ ለአወገዘው ለእስክንድርያ ዐሥራ ዘጠኛ ሊቀ ጳጳሳት ለታላቁ አባት #ለአባ_እለእስክንድሮስ ለዕረፍት በዓል፣#ለሐዲስ_ሐዋርያ_ለታላቁ_አባት_ለአቡነ_ተክለ_ሃይማኖት ከኢትዮጵያ ወደ ኢየሩሳሌም ከከበሩ ቦታዎች ለመባረክ ለሆዱበት መታሰቢያ ቀንና ከግብጽ ደቡብ ከእብክ አውራጃ ከሆሪን ከተማ ለሆነ ለከበረ አባት #ለአባ_ይስሐቅ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ  በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከእስክንድርያ አርባ ዘጠነኛ ሊቀ ጳጳሳት #ከአባ_ማርቆስና ሃምሳ ሦስተኛ ሊቀ ጳጳሳት ከከበረ አባት #ከአባ_ሚካኤል ከዕረፍታቸው መታሰቢያ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                            ✝ ✝ ✝  ❤ #አባ_እለእስክድሮስ፦ ይህ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳትም ዐሥራ ዘጠነኛ የሆነ ነው። ❤ ስለርሱም ሐዋርያዊ አባት አትናቴዎስ እንዲህ አለ "አባቴ እለእስክንድሮስ ተቀምጦ ወንጌልን አያነብም ቁሞ ያነባል እንጂ ከርሱ ጋራም ብርሃን አለ"። ሁለተኛም ስለርሱ ሲናገር "ወደርሱ እመምኔቶች መጥተው በእኛ ዘንድ ሰባት ሰባት ቀን የሚጾሙ ደናግል አሉ። በእጅዎቻቸውም ምንም ምን ሥራ አይሠሩም" ብለው ነገሩት። እርሱም "እኅቶቼ ሆይ እኔ ሁለት ቀን እንኳ ከቶ አልጾምኩም ፀሐይ እስኪገባም ቆይቼ አልበላሁም በልክ እበላለሁ በልክም እጾማለሁ በሌክ በመጠንም እሠራለሁ በልክ ይበሉ ዘንድ በልክም ይጾሙ ዘንድ በልክም ሥራ ይሠሩ ዘንድ ንገሩአቸው በበጎ ሥራ ሁሉ ይሰለፉ" አለ። ❤ የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ ደጎች ምዕመናን ናቸው እርሱም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ ሁኖ ከታናሽነቱ ጀምሮ በውስጥዋ አደገ። አባ መክሲሞስ አናጒንስጢስነት አባ ቴዎናስ ዲቁና፤ ተፍጻሜተ ሰማዕት ጴጥሮስም ቅስና ሹመውታልና እርሱም ከታናሽነቱ ጀምሮ ንጹሕ ድንግል ነው። ❤ አባ ጴጥሮስ በሰማዕትነት የሚሞትበት ጊዜ ሲቀርብ በግዞት ቤት ሳለ ይህ እለእስክንድሮስና አኪላስ ወደርሱ ገብተው ለመኑት ስለርሱ አባ ጴጥሮስ ይማልዱለት ዘንድ ሁለቱን ለምኖአቸዋልና። አባት ጴጥሮስ ግን በውግዘት ላይ ውግዘትን ጨመረበት እንዲህም ብሎ ነገራቸው "የክብር ባለቤት ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የተቀደደ ልብስ ለብሶ ተገለጸልኝ ልብሴን አርዮስ ቀደዳት አለኝ። ይህም የባሕርይ አንድነቴን ለያት ማለት ነው ውግዘቱንም እንድጨምርበት እርሱ አዘዘኝ"። ደግሞ እንዲህ ገለጠላቸው አኪላስ ሊቀ ጵጵስና እንዲሾም ከርሱም በኋላም እለእስክንድሮስ እንደሚሾም አርዮስ እንዳይቀበሉት በምንም ሥራው እንዳይተባበሩት አዘዛቸው። አባ ጴጥሮስም ምስክርነቱን በፈጸመ ጊዜ አኪላስ ሊቀ ጵጵስና ተሾመ የአባት ጴጥሮስንም ትእዛዝ ተላልፎ አርዮስን ከውግዘቱ ፈታው። ቅስናም ሾመው ስለዚህ አኪላስ በመንበረ ሢመቱ ያለ ስድስት ወር አልኖረም በድንገት ሞተ። ❤ ከዚህ በኋላ ይህ አባት እለእስክድሮስ ሊቀ ጵጵስና ተሹሞ በመንበረ ሢመቱ ላይ ተቀምጠ አርዮስንም ከወገኖቹ ጋራ አውግዞ አሰሠደደው። የአገር ታላላቆችም ከሕዝቡ መጡ ከውግዘቱ እንዲፈታውም ለመኑት። በውግዘት ላይ ውግዘትን እንዲጨምር እንጂ እንዳይፈተሠው አባት ጴጥሮስ እንደአዘዘው ነገራቸው። ❤ ከዚህም በኋላ አርዮስ ወደ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሒዶ በግፍ አወገዘኝ ብሎ እለእስክድሮስን ከሰሰው። ስለዚህም ንጉሥ ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት የከበሩ አባቶችን በኒቅያ ከተማ ሰበሰበ። ይህም አባት እለእስክድሮስ ተመርጦ ለጉባኤው ሊቀ መንበር ሆነ አትናቴዎስም ጸሐፊ ነበር። አርዮስንም ተከራክረው ክህደቱን ግልጽ አደረጉ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከአባቱ ከአብ ጋራ ከሕይወቱ መንፈስ ቅዱስም ጋራ በመለኮቱ ትክክል እንደሆነ አስረዱት። ከክህደቱ ባልተመለሰ ጊዜ አውግዘው ለይተው ከቤተ ክርስቲያን አሳደዱት። በአንድ ቃልም ጸሎተ ሃይማኖትን ከአባቶች ጋራ ሠሩልን ደግሞ በእርሳቸው ቤተ ክርስቲያን ለዘላለም የምትመራባቸው ሃያ ቀኖናን ሠርተው ወሰኑ። ❤ ከዚህም በኋላም ይህ አባት እለእስክንድሮስ ወደ መንበረ ሢመቱ ከድል ጋራ ተመለሰ። በበጎ አጠባበቅም መንጋውን ጠበቀ በወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ መንበርም ዐሥራ ሰባት ዓመት ኖረ ሚያዝያ22 በሰላም ዐረፈ። በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን አሜን።                           ✝ ✝ ✝                       ❤ #አባ_ይስሐቅ፦ ይህ አባት ከግብጽ አገሩ ደቡብ ከእብክ አውራጃ ከሆሪን ከተማ የሆነ ነው። የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም አብርሃም የእናቱም ስም ሶስና ነው ታናሽም ሁኖ ሳለ እናቱ ሙታ ብቻውን ያለእናት አባቱ እያሳደገው ኖረ። ❤ ጥቂት በአደገም ጊዜ የአባቱን በጎች የሚጠብቅ ሆነ አባቱም ሌላ ሚስት አገባ በዚያ ወራትም ታላቅ ረኃብ ሆነ የአባቱም ሚስት ትጠላው ነበረ ከጥቂትም በቀር እንጀራ አትሰጠውም ያንኑም ሁልጊዜ ለእረኞች ሰጥቶ እርሱ ግን እስከምሽት ይፈጸማል። ምሳውን ለእረኞች እንደሚሰጥና ሁልጊዜ እስከምሽት እንደሚጾም አባቱ ሰምቶ እውነት እንደሆነ ሊያይ ወደርሱ ሔደ። ቅዱሱም ሕፃን አባቱን መምጣት ዐውቆ በልብሱ ሦስት ጭቃ አድበልብሎ አሠረ እንደ ታሠረ በሚያየው ጊዜ ለአባቱ አምባሻ እንዲመስለው ብሎ። አባቱም በመጣ ጊዜ የልጁን ልብስ ፈትቶ አየ አምባሻም ሁነው አገኛቸው። የነገውንም ሰው ምግቡን ለእረኞች ከሰጠ በዛሬዪቱ ቀን ይህ አምባሻ ከወዴት ተገኘለት" ብሎ ጠየቀው እርሱም "በእውነት ሰጥቷል" አለ ሌሎችም ብዙዎች መጥተው በዚህ ነገር ምስክሮች ሆኑ አባቱም አደነቀ እግዚአብሔርንም አመሰገነ። ❤ ይህም አባት በአደገ ጊዜ አባ ኤልያስ ወደሚባል ሰው ሔዶ መንኵሶ በዚያ እየተጋደለ ብዙ ዓመታት ኖረ። አባ ኤልያስም በዐረፈ ጊዜ በርኑግ ወደሚባል ገዳም ሔዶ ስሙ ዘካርያስ ከሚባል አረጋዊ ዘንድ በታላቅ ገድል ተጠምዶ ኖረ። አባቱም ያገኘው ዘንድ በአገሮች ሁሉ ይዞር ነበር በዚህ በበርኑግ ገዳምም በአገኘው ጊዜ ከእርሱ ጋራ እንዲመለስ አባቱ ለመነው አይሆንም አለ አባ ዘካርያስም ከአባቱ ጋራ ይሔድ ዘንድ እስከሚዐርፍም ከእርሱ ዘንድ እንዲኖር አዘዘው ይህ ቅዱስም ከአባቱ ጋራ ሔዶ እስከሚዐርፍ ድረስ ከእርሱ ዘንድ ኖረ። ❤ አባቱም በዐረፈ ጊዜ አባቱ የተወውን ገንዘብ ሁሉንም ለድኆችና ለምስኪኆች ሰጠ ከከተማውም ጥቂት ራቅ ብሎ ለራሱ ታናሽ ማደሪያ ሠራ በሰላም እስከሚዐርፍባት ቀን በጾም በጸሎት በስግደት ኖረ በዐረፈ ጊዜም በመልካም ቦታ አኖሩት ከዚያም ተሠወረ። ከብዙ ዘመናትም በኋላ እግዚአብሔር ሊገልጠው ወዶ በመቃብሩ ላይ መብራት ሲበራ እህል ለሚዐጭዱ ሰዎች ሦስት ቀን ያህል ታየ ሊያዩትም ወደቦታው ሲደርሱ ያ መብራት ከእርሳቸው ይሠወራል በሁሉ ዘንድ እስቲሰማም እንዲህ ሁኖ ኖረ። ❤ ከዚህም በኋላ በመቃብሩ ላይ እያበራ ያ መብራት ደግሞ ታያቸው ሥጋውም በዚያ እንዳለ ሁለተኛ በሕልም ነገራቸው ምዕመናንም አክብረው በግመል ጭነው ወደ አገሩ መካከል ወደ ሆሪን ወሰዱት ነስሪን ከሚባል አገር መካከል ሲደርሱ ግመሉ በዚያ ተንበረከከ እንዲነሣም መቱት መነሣትንም እምቢ አለ መኖሪያው በዚያ ይሆን ዘንድ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንደሆነ አወቁ። በዚያም በስሙ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ሥጋውን በውስጥዋ አኖሩ ከእርሱም ብዙ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን