የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)
Ir al canal en Telegram
ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።
Mostrar más2 638
Suscriptores
+124 horas
+87 días
+5830 días
Archivo de publicaciones
#ቅዱስ_ቆርኔሌዎስ_ሐዋርያዊ
በዚህችም ቀን የጭፍራ አለቃ የሆነ ትሩፋቱና ገድሉም ያማረ ጻድቅ ሰው ቆርኔሌዎስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው እርሱም በቅዱሳን አባቶቻችን ሐዋርያት ዘመን እግዚብሔርን ያገለገለ ነው።
የእግዚአብሔር መልአክም ተገልጦለት ሐዋርያ ጴጥሮስን ይጠሩት ዘንድ ሰዎችን እንዲልክ ጴጥሮስም ወደርሱ እንዲመጣ ሊሠራው የሚገባውን ከእርሱ ከጴጥሮስ እንዲሰማ አዘዘው።
ጴጥሮስም ወደርሱ በደረሰ ጊዜ የእግዚአብሔርን ቃል አስተማረው ለርሱና ከእርሱ ጋር ላሉት ሁሉ ከሁሉ ቤተሰቡ ጋር አምኖ ተጠመቀ። ከዚህ በኋላ ጴጥሮስ ለእስክንድርያ አገር ቅስና ሾመው ወደርሷ በደረሰ ጊዜ የጣዖታትን አምልኮ ተመልታ አገኛትና አስተማራቸው ብዙዎችንም ወደቀናች ሃይማኖት መልሶ አጠመቃቸው መኰንኑ ድሜጥሮስም አምኖ ከወገኖቹ ጋር በእርሱ እጅ ተጠመቀ።
የኑሮውን ዘመንና ሐዋርያዊ ተጋድሎውን አድርሶ በሰላም አረፈ እርሱም ከአሕዛብ አስቀድሞ ያመነ የመጀመሪያ አማኒ ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ታዖድራ
በዚህችም ቀን ከእስክንድርያ አገር በንጉሥ ዘይኑን ዘመን ቅድስት ታዖድራ አረፈች።
ይችንም ቅድስት ሌላ ሰው አስገድዶ ከባሏ ወስዶ ከባሏ ጋር ያላትን አንድነት አበላሸ ያን ጊዜም ታላቅ ኀዘን በማዘን ተጸጸተች መሪር ልቅሶንም አለቀሰች የወንዶችንም ልብስ ለብሳ ወንድ መሰላ ከእስክንድርያ በሥውር ወጣች ስሟንም ቴዎድሮስ ብላ ሰየመችና ወደ ወንዶች ገዳም ገባች የምንኲስና ልብስንና የመላእክትን አስኬማ ለበሰች።
የሚያዩዋት ሁሉ እርሷ እንደ ጃንደረባ የሆነች ወንድ ትመስላቸው ነበር እርሷ ግን በረኃብ፣ በጽምዕ ሌሊት በመትጋት ቀን በመቆም ጸንታ በመጋደል ላይ ታገሠች እንዲህም በመጋደል ተጠምዳ ብዙ ዘመን ኖረች።
በዚያም ወራት እንዲህ ሆነ አንድ ሰው ከአንዲት ብላቴና ጋር አመነዘረ እርሷም ፀንሳ ወንድ ልጅን ወለደች ወላጆቿም ድንግልናሽን ያጠፋው ማነው ብለው ጠየቋት እርሷም በገዳም ውስጥ የሚኖር አባ ቴዎድሮስ እርሱ ደፍሮኝ ከእርሱ ፀነስኩ ብላ በዚች ቅድስት ታኦድራ ላይ በሐሰት ተናገረች።
ወላጆቿም በሰሙ ጊዜ እጅግ አዘኑ ሕፃኑንም ወደዚያ ገዳም አበ ምኔት ወሰዱት እንዲህም አሉት ይህ ሕፃን የልጅህ የመነኵሴው የቴዎድሮስ ልጅ ነው ። ያን ጊዜም አበ ምኔቱ ይቺን ቅድስት ታኦድራን ጠራትና እንዲህ አላት ይህን ክፉ ሥራ ለምን ሠራህ በመነኰሳቱም ሁሉ ላይ ኀፍረትንና ጒስቁልናን አመጣህ እርሷ ሴት መሆኗን አላወቀምና እርሷም አባቴ ሆይ በድያለሁና ይቅር በለኝ አለችው።
አበ ምኔቱም ተቆጥቶ ከገዳሙ አስወጥቶ አባረራት በበረሀ ውስጥ ሰባት ዓመት ኖረች ያም ሕፃን ከእርሷ ጋር ሁኖ ከሰይጣናት በሚመጡባት በብዙ መከራዎች ብዙ መከራዎች ላይ ታገሠች ብዙ ሥቃያትንም ፈጽሞ አሠቃዩዋት።
ከዚህም በኋላ ዳግመኛ ተቀብለው ወደ ገዳም አስገቡአት ጥቂት ቀንም ኖረች መልካም ተጋድሎዋንም ፈጽማ በሰላም አረፈች ነፍሷንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጥታ የዘላለም ሕይወትን አገኘች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_በነፍዝዝ_ሰማዕት
በዚህች ቀን የስሟ ትርጓሜ ጣፋጭ የሆነ የከበረች በነፍዝዝ በሰማዕትነት አረፈች። ይቺም ቅድስት በእድሜዋ ፈጽማ የሸመገለች ነበረች በፋርስ ንጉሥ በሳቦር ዘመንም መከራ ተቀበለች ከዘጠኝ መቶ ክርስቲያን ጋር ማርከው ወስደው አሠሩዋት የሠራዊቱም አለቃ ታላቅ ሥቃይን አሠቃይቶ ከዚያ በኋላ ራሷን በሰይፍ ቆረጠ።
ራሷንም ከአስቆረጣት በኋላ ከአንገቷ የፈሰሰው ደም እስከ ራቀ ድረስ ወደ ላይ ወጣ ከዚያ የተቀመጡ ጠላቶችም ኃይላቸው ደከመ። የፀሐይ ብርሃንም ጨለመ በዚያም ቦታ ደግሞ ጣፋጭ የሆነ መዐዛ ተመላ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሦስቱ_ቅዱሳን_ገበሬዎች
(ሱርስ፣ አጤኬዎስ፣ መስተሐድራ)
በዚህችም ቀን ስማቸው ሱርስ፣ አጤኬዎስ፣ መስተሐድራ የሚባል ሦስት ገበሬዎች የእስና አገር ሰዎች በሰማዕትነት አረፉ ። አርያኖስም ከሀገሪቱ በስተደቡብ ምንም ሳያስቀር ወታደሮቹ እስከ ደከሙ ድረስ ሰይፋቸውንም ወደ አፎቱ መልሰው ነበር የአገር ሰዎችን ጨርሶ ገድሎ ሲመለስ እሊህ ሦስቱ ገበሬዎች ከዱር ሲመለሱ በከተማ መካከል በተገናኙት ጊዜ እኛ ክርስቲያኖች ነን ብለው በግልጥ ጮኹ አርያኖስም ሰምቶ ወታደሮቹን እሊህን ገበሬዎች ትገድሏቸው ዘንድ ይገባል አላቸው።
ወታደሮቹም እኛ ደክመናል ሰይፎቻችንንም ወደ አፎታቸው አስገብተናል አሉት እሊህ ቅዱሳንም ሰምተው እነሆ መቆፈሪያዎች ከእኛ ጋራ አሉ በእነርሱ ግደሉን አሉ ከዚያም አንገታቸውን በደንጊያ ላይ አድርገውላቸው ቆረጡአቸው።
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ሁሉ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር መስከረም_11
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ዐሥራ አንድ በዚህች ቀን #ቅዱስ_ፋሲለደስ በሰማዕትነት አረፈ፣ #ቅዱስ_ቆርኔሌወስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ #ቅድስት_ታዖድራ አረፈች፣ #ቅድስት_በነፍዝዝ የስሟ ትርጓሜ ጣፋጭ የሆነ በሰማዕትነት አረፈች፣ #ሦስቱ_ቅዱሳን_ገበሬዎች (#ሱርስ፣ #አጤኬዎስ፣ #መስተሐድራ) በሰማዕትነት አረፉ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ፋሲለደስ_ሰማዕት
መስከረም ዐሥራ አንድ በዚህች ቀን ለአንጾኪያ ነገሥታት አባታቸውና መካሪያቸው የሆነ ቅዱስ ፋሲለደስ በሰማዕትነት አረፈ።
እርሱም ለሮም ንጉሥ የሠራዊት አለቃ ነው መንግሥቱም ሁለመናዋ በእርሱ ምክር የጸናች ናት። ብዙዎችም ወንዶችና ሴቶች የቤት ውልዶች አገልጋዮች አሉት።
ዝምድናውም እንዲህ ነው ስሙ ኑማርያኖስ የተባለ የሮም ንጉሥ ለቴዎድሮስ በናድሌዎስ እናቱ የሆነች የቅዱስ ፋሲለደስን እኅት አግብቶ ዮስጦስን፣ ገላውዴዎስን፣ አባዲርን ወለደችለት እሊህም ለቅዱስ ፋሲለደስ የእኅቱ ልጆች ናቸው። የቅዱስ ፋሲለደስም ሚስት ለቅዱስ ፊቅጦር እናት እኅት ናት ከእርሷም ስማቸው አውሳብዮስና መቃርስ የተባሉ ሁለት ልጆችን ወለደ።
በዚያም ወራት የቊዝና የፋርስ ሰዎች የሮምን ሰዎች ሊወጓቸው በላያቸው ተነሡ ያን ጊዜ የንጉሥ ልጅ ዮስጦስን የፋሲለደስ ልጅ አውሳብዮስን ከጦር ሠራዊቶቻቸው ጋር ለውጊያ ላኳቸው።
ንጉሡ ኑማርዮስም ሌሎች ጠላቶች በተነሡበት በኩል ለጦርነት ሒዶ በውጊያው ውስጥ ሞተ የሮም መንግሥትም የሚጠብቃትና የሚመራት የሌላት ሆነች።
እንዲህም ሆነ በዚያ ወራት ስለ ጦርነት ለመደራጀት የሮም ሰዎች ከሀገሩ ሁሉ አርበኞች የሆኑ ሰዎችን ሰበሰቡ ከውስጣቸውም ከላይኛው ግብጽ ስሙ አግሪጳዳ የሚባል የፍየሎች እረኛ የሆነ አንድ ሰው አለ። እርሱንም መኳንንቱ ወስደው በመንግሥት ፈረሶች ላይ ባልደራስ አድርገው ሾሙት እርሱም በጠባዩና በሥራው ሁሉ ኃይለኛና ብርቱ ነበር።
ከንጉሥ ኑማርያኖስ ሴቶች ልጆች አንዲቱ ወደርሱ በመስኮት ተመለከተች ወደደችውም መልምላም ወስዳ አገባችው ስሙንም ዲዮቅልጥያኖስ ብላ ሰይማ አነገሠችው። ከጥቂት ቀኖችም በኋላ ሰማይና ምድርን የፈጠረ እግዚአብሔርን ትቶ ጣዖታትን አመለከ ቅዱስ ፋሲለደስም ሰምቶ እጅግ አዘነ የመንግሥትንም አገልግሎት ተወ።
ከዚህም በኋላ የንጉሥ ኑማርያኖስ ልጅ ዮስጦስና የፋሲለደስ ልጅ አውሳብዮስ ጠላቶቻቸውን ድል አድርገው የጠላቶቻቸውንም አገሮች አጥፍተው ደስ ብሏቸው ተመለሱ። ነገር ግን የነገሠው ዲዮቅልጥያኖስ የክብር ባለቤት ክርስቶስን ክዶ አምልኮ ጣዖትን አቁሞ አገኙት እጅግም አዘኑ ተቆጥተውም ተነሡ ሰይፎቻቸውን መዝዘው ዲዮቅልጥያኖስን ገድለው የንጉሥ ኑማርያኖስን ልጅ ዮስጦስን ሊያነግሡ ወደዱ ፋሲለደስም ከዚህ ሥራ ከለከላቸው።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ፋሲለደስ ዘመዶቹን፣ ሠራዊቱን፣ አገልጋዮቹንም ሁሉ ሰበሰባቸውና በክብር ባለቤት በክርስቶስ ስም ደሙን ሊያፈስ እንደፈለገ አስረዳቸው ሁሉም እንዲህ ብለው መለሱለት አንተ በምትሞትበት ሞት እኛ ከአንተ ጋር እንሞታለን በዚህም ምክር በአንድነት ተሰማሙ።
ከዚህም በኋላ በንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስ ፊት ቁመው ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ ከእርሳቸውም ግርማ የተነሣ ታላቅ ፍርሃትን ፈራ እነርሱ የመንግሥት ልጆች ናቸውና።
የቅዱስ ፊቅጦር አባት ኀርማኖስም ወደ ግብጽ አገር ይልካቸው ዘንድ በዚያም እንዲያሠቃዩዋቸው መከረው ሁሉንም እየአንዳንዳቸውን ለብቻቸው አድርጎ ላካቸው አባዲርንና እኀቱ ኢራኒን ወደ አንዲት አገር፣ አውሳብዮስንና ወንድሙ መቃርስን ወደሌላ ቦታ፣ ገላውዴዎስንም እንዲሁ አደረጉ። በናድሌዎስ ቴዎድሮስም እሼ በሚባል ዕንጨት ላይ በመቶ ሃምሳ ሦስት ችንካር ተቸንክሮ ገድሉን ፈጸመ።
ቅዱስ ፋሲለደስን ግን አምስት ከተማዎች ወዳሉበት ወደ አፍሪካ ምድር ወደ መኰንኑ ወደ መጽሩስ ላከው መጽሩስም በአየው ጊዜ መንግሥቱን ክብሩን ስለ ተወ እጅግ አደነቀ።
ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስም መልአኩን ልኮ በመንፈስ ወደ ሰማይ አውጥቶ በብርሃን ያጌጠ መንፈሳዊ ማደሪያን አሳየው ነፍሱም እጅግ ደስ አላት ከዚህም በኋላ ወደነበረበት መለሰው። ባሮቹን ግን ነፃ ያወጣቸው አሉ የቀሩትም ከእርሱ ጋር የሰማዕትነት አክሊልን የተቀበሉ ሰባት ሺህ ሠላሳ ሦስት የሚሆኑ አሉ።
ቅዱስ ፋሲለደስንም ታላቅ ስቃይን አሰቃዩት በመንኰራኲርና በተሣሉ የብረት ዘንጎች ሥጋውን ሰነጣጥቀውት ሞተ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ያለ ጥፋት ከሞት አድኖ አስነሣው አሕዛብም ሁሉ ይህን ድንቅ ተአምር በአዩ ጊዜ አደነቁ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አመኑ መኰንኑንም ረገሙት ጣዖቶቹንም ሰደቡ በእነርሱ ላይም ተቆጥቶ ራሶቻቸውን በሰይፍ ይቆርጧቸው ዘንድ ወታደሮቹን አዘዘ የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበሉ ቊጥራቸውም ዐሥራ አራት ሺህ ሰባት መቶ ወንዶች ሠላሳ ሰባት ሴቶች ናቸው።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ፋሲለደስን ሥጋው ሁሉ ቀልጦ እንደ ውኃ እስከሚሆን በብረት ምጣድ ውስጥ አበሰሉት መኰንኑም በተራራ ላይ ጥልቅ ጒድጓድ ቆፍረው በዚያ እንዲቀብሩት አዘዘ እንዲሁም አደረጉ። ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ፋሲለደስን ከሞት ደግሞ አስነሣው ወደ መኰንኑም መጥቶ እንዲህ ብሎ ጮኸ መኰንን መጽሩስ ሆይ እፈር ከሀዲ ንጉሥህም የረከሱ ጣዖቶችህም ይፈሩ እነሆ ክብር ይግባውና ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ያለ ጉዳት ከሞት ጤነኛ አድርጎ አስነሥቶኛልና።
ሕዝቡም ይህን ተአምር በአዩ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በሰማዕትነት ሞቱ ቁጥራቸውም ሁለት ሺህ ሦስት መቶ ሆነ።
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ፋሲለደስን በውስጧ መጋዝ ካላት መንኰራኲር ላይ አውጥቶ ታላቅ ሥቃይን አሠቃየው ዳግመኛም በብረት ዐልጋ ላይ በሆዱ አስተኝተው ከበታቹ እሳትን አነደዱ ያን ጊዜም ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠለት ከዚያ ስቃይም ውስጥ አንስቶ ያለ ጉዳት ጤነኛ አደረገው እንዲህም ብሎ ቃል ኪዳን ሰጠው ፋሲለደስ ሆይ ዕውቅ መታሰቢያህን ለሚያደርግ ሁሉ ወይም ለድኆች በስምህ ምጽዋትን ለሚሰጥ ወይም ለተራቈተ ልብስን ወይም በመታሰቢያህ ቀን ለቤተ ክርስቲያን መባ ለሚሰጥ በብዙም ቢሆን በጥቂት መታሰቢያህን ለሚያደርጉ ሁሉ እኔ በደላቸውን ሁሉ እተውላቸዋለሁ መኖሪያቸውንም በመንግሥተ ሰማያት ከአንተ ጋራ አደርጋለሁ።
ጌታችንም ይህን ካለው በኋላ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ ቅዱስ ፋሲለደስም በፍጹም ደስታ ደስ ተሰኘ።
ከዚህም በኋላ መጽሩስ መኰንን ከአማካሪዎቹ ጋር ተማከረ እንዲህም አላቸው ስሙ ፋሲለደስ ስለሚባል ስለዚህ ሰው ምን ላድርግ እርሱን ያላሠቃየሁበት የሥቃይ መሣሪያ ምንም የቀረ የለም ከሐሳቡም አልተመለሰም እነርሱም እንዲህ ብለው መከሩት ራሱን በሰይፍ ቆርጠህ ከእርሱ ተገላገል እነሆ የዚች አገር ሰዎች በእርሱ ምክንያት አልቀዋልና።
በዚያንም ጊዜ የቅዱስ ፋሲለደስን ራስ በሰይፍ እንዲቆርጡ መኰንኑ አዘዘና ቆረጡት የድል አክሊልን ተቀበለ ንቆ ሰለ ተዋት ምድራዊት መንግሥት ፈንታም ሰማያዊት መንግሥት አገኘ። ከሥጋውም ድንቆች የሆኑ ታላላቅ ተአምራት ተገለጡ ከእርሱም ጋር ሰማዕት ሁነው የሞቱ ሁሉም ቊጥራቸው ሃያ ሦስት ሺህ ሰባት መቶ ዘጠና ሦስት ሆነ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
በዚችም ቀን የከበረች መጥሮንያ በሰማዕትነት አረፈች። ይቺም የከበረች መጥሮንያ ለአንዲት አይሁዳዊት ሴት አገልጋይዋ ናት ። ይችም አይሁዳዊት እመቤቷ ከክርስትናዋ አፍልሳ ትክክል ወደ አልሆነ ሃይማኖቷ ልታስገባት ትሻ ነበር ስለዚህም ታጉሳቁላታለች በላይዋም የአገልግሎት ሥራንበታከብድባታለች ።
ከዚህም በኃላ በአንዲት ቀን አይሁዳዊት እመቤቷን ተከትላ ወደ አይሁድ ምኩራብ ሔደች ተመልሳም ወደ ከበረች ቤተ ክርስቲያን ገብታ ጸለየች። ወደ ቤት በገቡም ጊዜ ወዴት ሒደሽ ነበር ወደእኛ ምኩራብ ለምን አልገባሽም ብላ ጠየቀቻት ቅድስት መጥሮንያም ከእናንተ ምኩራብ እግዚአብሔር ርቋል እኮን እንዴት ወደርሱ እገባለሁ። በውስጧ ልገባባት የሚገባኝ ቦታዬ ግን ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ በከበረ ደሙ የዋጃት ይህች ቤተ ክርስቲያን ናት ብላ መለሰችላት።
እመቤቷም ይህ ነገር በሰማች ጊዜ ተቆጣቻት እጅግም ደብደባ በጨለማ ቤት ውስጥ አሠረቻት ያለ መብልና መጠጥም አራት ቀን ኖረች። ከዚህም በኃላ ከእሥር ቤት አውጥታ በጅራፍ ታላቅ ግርፋትን ገርፋ ሁለተኛ ወደ እሥር ቤት መልሳ አሠረቻት በዚያም አረፈች።
እመቤቷም በድኗን አንሥታ ከቤቷ ደርብ ላይ አውጥታ በውጭ ወደታች ጣለቻት። ወድቃ የሚያዩዋት ሰዎች በገዛ ፈቃድዋ እንደወደቀች አድርገው እንዲናገሩ ብላ ነው ስለ መገደሏ ዳኞች እንዳይመራመርዋት ፈርታለች።
በዚያንም ጊዜ በዚያች አይሁዳዊት ሴት ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ወረደ ከደርቧ ላይ ስትወርድም በድንገት ወድቃ ሞተች ወደ ዘላለማዊም እሳት ሔደች ይህች የከበረች መጥሮንያ ግን የሰማዕታትን አክሊል ተቀብላ ወደ ዘላለም ሕይወት ሔደች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ንግሥተ_ሳባ
ይሕቺ ደግ ኢትዮዽያዊት ከ3 ሺ ዘመናት በፊት የነበረች ደግ እናት ናት። በሥጋዊ ደረጃ ከታንዛንያ እስከ የመን ያስተዳደረች ስመ ጥር ንግሥት ስትሆን በመንፈሳዊው ደረጃ ደግሞ እግዚአብሔር የቀባውን ሰው ፍለጋ ወደ ኢየሩሳሌም ተጉዛለች።
ከዚያውም አምልኮተ እግዚአብሔርን ከሥርዓተ ኦሪት ጋር አምጥታለች። ድንግልናዋን ለታላቁ ንጉሥ ሰሎሞን ሰጥታ ምኒልክን ወልዳለች። ይህቺ ንግሥት በጌታችን (በፈጣሪ) አንደበትም ተመስግናለች። (ማቴ. 12:42) በስምም "ሳባ: አዜብና ማክዳ ተብላ ትታወቃለች። ዛሬ ዕለተ ዕረፍቷ ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ተቀጸል_ጽጌ /#አጼ_መስቀል/
'ተቀጸል ጽጌ' ማለት 'መስቀል ሆይ! በአበባ አጊጥ' እንደ ማለት ሲሆን 'አጼ መስቀል' ደግሞ አጼ ገብረ መስቀልን አንድም አፄ ዳዊት ቀዳማዊን ይመለከታል። ይህስ እንደ ምን ነው ቢሉ፦
በሃገራችን ኢትዮዽያ የነገረ መስቀሉ ትምሕርት ከመጣ ጀምሮ መስቀል ይከበራል። በአደበባባይ ግን እንዲከበር ያደረጉት የቅዱስ ካሌብ ልጅ አፄ ገብረ መስቀል ናቸው። በወቅቱ ንጉሡ፣ ሠራዊቱ፣ ዻዻሱና ሕዝቡ በተገኙበት ቅዱስ ያሬድ "መስቀል መልዕልተ ኩሉ ነገር ያድኅነነ እምጸር።" "መስቀል ከሁሉ ነገር በላይ ነው: ከጠላትም ያድነናል።" እያለ ይዘምር ነበር።
የአበባ ጉንጉንም ለመስቀሉና ለንጉሡ ይቀርብ ነበር። ከ800 ዓመታት በሁዋላም አፄ ዳዊት ግማደ መስቀሉን ባስመጡ ጊዜ መስከረም ቀን ተተክሎ ታላቅ በዓልም ሆኖ ተከብሯል።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር መስከረም_10
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ዐሥር በዚች ቀን #ጼዴንያ በምትባል አገር ሥጋ የለበሰች ከምትመስል ሥዕል ከሠሌዳዋ ቅባት እየተንጠፈጠፈ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያም ተአምር ተገለጠ፣ የሜራሪ ልጅ #ቅድስት_ዮዲት እረፍቷ ነው፣ የከበረች #ቅድስት_መጥሮንያ በሰማዕትነት አረፈች፣ #ንግስት_ሳባ እረፍቷ፣ #ተቀጸል_ጽጌ #አጼ_መስቀል ይከበራል።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ጼዴንያ
መስከረም ዐሥር በዚህች ቀን ጼዴንያ በምትባል አገር ሥጋ የለበሰች ከምትመስል ሥዕል ከሠሌዳዋ ቅባት እየተንጠፈጠፈ አምላክን የወለደች የእመቤታችን የድንግል ማርያም ተአምር ተገለጠ።
ይቺንም ሥዕል የሣላት ወንጌላዊ ሉቃስ ነው ይባላል። ወደ ጼዴንያ አገርም የመጣችበት ምክንያት አንዲት ስሟ ማርታ የሚባል መበለት ሴት ነበረችና ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች ናት። አምላክን የወለደች እምቤታችን ድንግል ማርያምንም እጅግ ትወዳት ነበር። በሚቻላትም ሁሉ ታገለግላታለች።
በአንዲት ቀንም ስሙ ቴዎድሮስ የሚባል መነኩሴ ከእርሷ ዘንድ እንግድነት አደረ በመልካም አቀባበልም ተቀበለችው በማግሥቱም ስተሸኘው አባት ሆይ የምትሔደው ወዴት ነው አለችው። እርሱም በከበሩ ቦታዎች ውስጥ ልሰግድ ወደ ኢየሩሳሌም እሔዳለሁ አላት እርሷም ከእኔ ገንዘብ ወስደህ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ግዛልኝና በመመለሻህ ጊዜ አምጣልኝ አለችው። እርሱም በራሴ ገንዘብ ገዝቼ አመጣልሻለሁ አላት።
ከዚህም በኋላ ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ ከቅዱሳት መካናት ተባረከና ሥዕሏን ሳይገዛ ወደ ጎዳናው ተመለሰ። ያን ጊዜም ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰማ ወደ ገቢያም ተመልሶ ላሕይዋና መልኳ ያማረና የተወደደ የሆነ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል አግኝቶ ገዛት በሐርና በንጹሕ ልብስም ጠቀለላት።
በጎዳናውም እየተጓዘ ሳለ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ወንበዴዎች ተነሡበት ሊሸሽም ወደደ ከዚያቺም ሥዕል መንገድህን ሒድ የሚል ቃል ወጣ የተከተለውም ሳይኖር መንገዱን ተጓዘ። ሁለተኛም ነጥቆ ሊበላው አንበሳ ተነሣበት ያን ጊዜም ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረው።
አባ ቴዎድሮስም ይህን ሁሉ ድንቅ ተአምር ባየ ጊዜ ያቺን ሥዕል ወደ አገሩ ሊወስዳት ወደደ ግዛልኝ ላለችው መበለት ይሰጣት ዘንድ አልፈለገም።
ከዚህም በኃላ በመርከብ ተሳፍሮ በሌላ አቅጣጫ ሲጓዝ ታላቅ ነፋስ ተነሣበት ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያም ወሰደው ከመርከቡም ወርዶ ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ሔደ ማንነቱንም አልገለጠላትም እርሷም አላወቀችውም።
በማግሥቱም ተሠውሮ ወጥቶ ወደ አገሩ ሊሔድ በፈለገ ጊዜ የቅጽሩን ደጃፍ አጥቶ ሲያጥመሰምስ ዋለ በመሸ ጊዜም ወደ ማደሪያው ተመለሰ። ያቺም መበለት በአየችው ጊዜ ታደንቃለች እንዲህም ሁኖ እስከ ሦስት ቀን ኖረ በመሸ ጊዜ በሩን ያየዋል ነግቶ መሔድን ሲሻ የበሩ መንገድ ይሠወረዋል። ያቺም መበለት ያዝ አድርጋ አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን ስትቅበዘበዝ አይሀለሁና ምን ሆነህ ነው አለችው።
ከዚህም በኋላ ከዚያች ሥዕል የሆነውን ሁሉ ነገራት ራሱንም ገለጠላት። ያቺንም ሥዕል ሰጣት ተቀብላም የተጠቀለለችበትን ልብስ ፈታች ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች። ከደስታዋም ብዛት የተነሣ የዚያን መነኩሴ እጆቹንና እግሮቹን ሳመች።
ከዚህም በኋላ ያቺን ሥዕል ወደ ጸሎት ቤቷ ወስዳ በታላቅ ክብር የምትቀመጥበትን አዘጋጅታ አኖረቻት ማንም እንዳይዳስሳትም የነሐስ መስኮትን ሠራችላት በቀንና በሌሊትም የሚበሩ መቅረዞችን በፊቷ ሰቀለች ከመቅረዞችም ውጭ የሐር መጋረጃን ጋረደች። ከሥዕሊቱ በታችም ከሥዕሊቱ እየተንጠፈጠፈ የሚወርደው የወዝ ቅባት የሚጠራቀምበት ከዕብነ በረድ የተሠራ ወጭት አኖረች ያም መነኩስ እስከሚሞትበት ቀን ድረስ የእመቤታችንን ድንግል ማርያምን ሥዕል እያገለገለ ኖረ።
የሀገሩም ሊቀ ጳጳሳት የዚያችን ሥዕል ዜና በሰማ ጊዜ ከኤጲስቆጶሳትና ከካህናት ከሕዝቡም ሁሉ ጋር መጣ በሠሌዳውም ውስጥ በአዩዋት ጊዜ ሥጋ የለበሰች ሁና አገኙዋት ከዚህ ከአምላካዊ ግብር የተነሣ አደነቁ ከዚህም ቅባት ቀድተው ለበረከት በተካፈሉ ጊዜ ወዲያውኑ በወጭቱ ውስጥ ይመላል።
ወደ ሌላ ቦታም ሊወስዷት በፈለጉ ጊዜ ንውጽውጽታ ሆኖ ብዙዎች በድንጋጤ ወደቁ ሥዕሊቱም እስከ ዛሬ በዚያች አገር ትኖራለች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ዮዲት
ዳግመኛም በዚህች ቀን ባሏ ምናሴ ሞቶባት፣ ከወንድ ርቃ ንጽሕናዋን ጠብቃ በጾም፣ በቀኖና፣ በትኅርምት፣ በኀዘን፣ በጸሎት ተወስና የምትኖር የሜራሪ ልጅ ቅድስት ዮዲት አረፈች።
ቅድስት ዮዲት ከከሀዲው ሆሎፎርኒስ እጅ በጥበቧ እስራኤልን ያዳነቻቸው ጥበበኛ የከበረች፣ በእግዚአብሔር ኃይል ራሱን እስከ ቆረጠች ድረስ በልቧ ተራቀቀች ወገኖቿንም ያዳነች ናት።
ነገሩም እንዲህ ነው፦ ለፋርስ ንጉሥ ለናቡከደነፆር የጦር አበጋዝ የነበረው ሆሎፎርኒስ ፈቃድ ተሰጥቶት እስራኤልን ለመውረር ሲመጣ በሠራዊቱ (ዮዲ2፣2-7) የእሥራኤል ልጆችም ሆሎፎርኒስ የአሕዛብን አገር እንዳጠፋና ንብረታቸውን እንደዘረፈ ሰምተው ስለ ቤተ መቅደሱ መፍረስና ሰለ ንዋያተ ቅድሳት መርከሰ ማቅ ለብሰው አመድ ነስንሰው ከቤተ መቅደሱ በር ወድቀው አለቀሱ።(ዮዲ4፡2-15) ሆሎፎርኒስ ግን የሚጠጡትን ምንጫቸውን በመያዙ ፣ የእሥራኤል ልጆች በውኃ ጥም ከመቸገርና ከመሞት ይልቅ እጃቸውን ለጠላት ለመስጠት ወሰኑ፡፡ ነገር ግን ዖዝያን የአባቶቻቸው አምላክ መልስ እስኪሰጣቸውና ቸርነቱን እስኪመልስላቸው መከራውን በትዕግሥት እንዲቀበሉ ስለመከራቸው ጸኑ፡፡ ዮዲ 7፥10-32)
በዚህ ጊዜ ዮዲት ማቅ ለብሳ በራስዋ ላይ ትቢያ ነስንሳ፣ ሱባዔ ገባች! አምላክም ሕዝቡን የሚያድንበትን ዕውቀትና ጥበብ ግብር በገባች በሦስተኛ ቀን ገለጸላት፡፡(ዮዲ8፡2) ከዚያም “ወዴት ትሔጃለሽ አትበሉኝ አምላክ እሥራኤል ይከተልሽ ብሉኝ” ብላ የኀዘን ልብሷን ጣለች፡፡ ሰውነቷን ታጠበችና ሽቱ ተቀባች ባሏ በሕይወት ሳለ የምትለብሰውን የክት ልብሷን ለበሰች፣ የጠላት ሰዎች ሁሉ እስኪወዷት ድረስ ፈጽማ አጊጣ ሄደች፡፡ (ዮዲ.10፥2-3) እነርሱም ለእኔ ትገባለች ለእኔ ትገባለች እያሉ ተሻሙባት፡፡ የንጉሥ ጃንደረባ ጋይ የሚባል ይህችስ ለጌታዬ ትገባለች አለ፣ ለምን እንደመጣች ጠይቀዋት ለመልካም ነገር እንደመጣች ሲረዱ ከጦር አበጋዙ አደረሷት፡፡ (ዮዲ10፥12-22)
በአንዲትም ዕለት ሆሎፎርኒስ የአሽከሮች የምሣ ግብዣ አድርጎ ሲያበላ ሲያጠጣ ያችን ዕብራዊት ጥሩ ብሎ አስጠርቶ ከፊቱ አስቀምጦ ሲበላ አብዝቶ ሲጠጣ ውሎ ሰከረ፡፡(ዮዲ12፥1-20) ከዚያም አሽከሮችን ከሁሉ አስወጥቶ ድንኳኑን ቆልፎ እንደተኛ ከባድ እንቅልፍ ያዘው ዮዲትም ከፀለየች በኋላ ከራስጌው ያለውን ሰይፍ አንስታ የራስ ጠጉሩን ይዛ አንገቱን ቆርጣ በድኑን ከመሬት ጥላ ቸብቸቦውን በአቁማዳ ቋጥራ ለብላቴናዋ አሸክማ ግንዱን በታች ገልብጣ ዙፋኑን በላይ አድርጋ ወደ ሃገሯ ተመለሰች፡፡ (ዮዲ13፥1-10) ሕዝበ እሥራኤል በዚህ ድርጊቷ እጅግ ተደነቁ፣ ጠላታቸውን በእጃቸው የጣለላቸውን አግዚአብሔር አምላካቸውንም አመሰገኑ፡፡ በኋላም የሆሎፎርኒስን ራስ በተራራው ላይ ሰቅለው መዋጋት ጀመሩ፡፡ እስከ ዮርዳኖስም እየተከተሉ አጥፍተዋቸዋል፡፡
ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም የዚህችን ቅድስት እናት በዓለ እረፍቷን በዚህች ዕለት አክብራ ትውላለች ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_መጥሮንያ
🔴#ስንክሳር መስከረም_9
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ዘጠኝ በዚህች የመላእክት አለቃ #ቅዱስ_ሚካኤል በሮም አገር ፍሩምያ በምትባል ከተማ ላደረገው ተአምር መታሰቢያ ነው፣ #ቅዱስ_አባት_አባ_ቢሶራ በሰማዕትነት አረፈ፣ #ቅዱስ_ያሳይ_ንጉሥ እረፍቱ ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሊቀ_መላእክት_ቅዱስ_ሚካኤል
መስከረም ዘጠኝ በዚህች ቀን በሮም አገር ፍሩምያ በምትባል ከተማ ለሆነው ተአምር መታሰቢያ ሆነ። ይህም እንዲህ ነው የሰማይ ሠራዊት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ በሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሚታዩ ድንቆችና ተአምራቶች ምክንያት ዮናናውያን ሰዎች ሰይጣናዊ ቅናትን እንደ ቀኑ ከመቅናታቸውም ብዛት የተነሣ በዚያ አካባቢ የሚወርደውን የወንዝ ውኃ በዚያች ቤተ ክርስቲያን ላይ ሊመልሱትና ከሚጠብቃት መጋቢዋ ጋር በውኃ ስጥመት ሊአጠፉአት ፈልገው መለሱት።
የሰማያውያን ሠራዊት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም ለቤተ ክርስቲያኑ መጋቢ ለናርጢኖስ ተገለጠለት ወደርሱም ቀርቦ ጽና አትፍራ አለው ይህንን ብሎ በእጁ ውስጥ ባለ በትር አለቱን መታው አለቱም ተደንጥቆ እንደ በር ሆነ የዚያ ወንዝ ውኃም በውስጡ አልፎ ሔደ።
ይህንንም ያዩ ምስጉን እግዚአብሔርን አመሰገኑት የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልንም አከበሩት። ከዚያች ቀን እስከ ዛሬ የወንዙን ውኃ በዚያች በተሠነጠቀች አለት ውስጥ አልፎ ሲሔድ ያዩታል ወደ መላእክት አለቃ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ከቶ አይቀርብም።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አባት_አባ_ቢሶራ
በዚህችም ቀን መጺል የምትባል አገር ኤጲስቆጶስ ቅዱስ አባት አባ ቢሶራ በሰማዕትነት አረፈ።
ይህም ቅዱስ በግብጽ አገር እግዚአብሔርን በምትወድ መጺል በምትባል ከተማ ኤጲስቆጶስ ሆነ። ዲዮቅልጥያኖስም ነግሦ ክርስቲያኖችን በሚያሠቃያቸው ጊዜ ክብር ይግባውና በክርስቶስ ስም ደሙን ያፈስ ዘንድ ይህ አባት ወደደ።
ሕዝቡንም ሀሉ ሰብስቦ በቤተ መቅደሱ ፊት በዐውደ ምሕረቱ አቆማቸው ሊጠብቁት የሚገባውን ለጽድቅ የሚያበቃቸውን ትእዛዝ ሁሉ አዘዛቸው። ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና በክርስቶስ ስም ደሙን ማፍሰስ እንደሚሻ ነገራቸው ይህንንም በሰሙ ጊዜ ታላቆችም ታናሾችም በላዩ አለቀሱ።
የሙት ልጆች እንሆን ዘንድ የምትተወን ምን ያደርግልሃል እኛስ እንድትሔድ አንለቅህም አሉት ሊይዙትም ቃጡ ግን አልተቻላቸውም ተውትም እርሱም ወደ ክብር ባለቤት ክርስቶስ አደራ አስጠበቃቸውና ሰላምታ ሰጥቷቸው ከእነርሱ ዘንድ ወጥቶ ተጓዘ። እነርሱም መሪር ልቅሶን እያለቀሱ ሸኙት።
ስማቸው ቢስኮስ ፊናቢክስ ቴዎድሮስ የሚባሉ ኤጲስቆጶሳት አብረውት ሔድ መኰንኑ ወደ አለበት አገርም ደርሰው የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ። እርሱም መኰንኑ አሠቃያቸው ኤጲስቆጶሳትም እንደሆኑ አውቆ ሥቃያቸውን አበዛ እሊህ አባቶች ግን በታላቅ ትዕግሥት የጸኑ ናቸው። ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ ያጸናቸዋልና።
ከዚህም በኋላ መኰንኑ ራሶቻቸውን በሰይፍ ይቆርጧቸው ዘንድ አዘዘ የሕይወት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። የቅዱስ ቢሶራ ሥጋው ግን ንሲል በሚባል አገር እስከ ዛሬ ይኖራል።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ያሳይ_ንጉሥ
በዚችም ቀን ተጋድሎውን በዛፍ ላይ ሆኖ የፈጸመ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘ ንጉሥ ያሳይ አረፈ።
በቀደመው ዘመን መንግስታቸውን ትተው ከመነኑ ነገሥታት አንዱ ቅዱስ ያሳይ ነው። ምናኔ በቁሙ ከባድ ነው። መንግስትን፣ ዙፋንን፣ ክብርን ትቶ መመነንን ደግሞ ከማድነቅ በቀር እንዲህ ብለው ሊገልጹት ይከብዳል።
ቅዱስ ያሳይም መንግስቱን ትቶ ልምላሜ ወደሌለበት ደረቅ በርሃ ሔደ። በዚያም ከአንዲት ዛፍ በቀር ምንም ነገር አላገኘም። በዚያች ደረቅ ዛፍ ላይ ወጥቶ ለዓመታት በጾምና በጸሎት ተጋደለ።
በዘመነ ተጋድሎው ከዛፏ አልወረደም ሰውም አይቶ አያውቅም። በመጨረሻም ስለ ቅድስናው ዛፏ ለምልማለች። እርሱም በዚህች ቀን ዐርፏል።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
ያን ጊዜም የእግዚአብሔር መልአክ ሕፃኑን ዚፈታ ወደሚባል በረሀ ነጥቆ ወሰደው ሕፃኑንም ባላገኙት ጊዜ አባቱን ዘካርያስን ገደሉት። ስለዚህም ጌታችን አይሁድን በቤተ መቅደሰ መካከል የገደላችሁት የዘካርያስ ደም በላያችሁ ይደርሳል አላቸው ለመገደሉ ምክንያት አይሁድ ናቸውና እንዲህ አለ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዲማድዮስ
በዚህች ቀን የከበረ ዲማድዮስ ከግብጽ ደቡብ ደንጡ ከሚባል አውራጃ ደርሰባ ከሚሏት ከተማ በሰማእትነት አረፈ። እርሱ ሁል ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ይገሠግሣል ድኆችንና በሽተኞችን መጐብኘትንም ይወዳል።
ብርሃናዊ ሰውም ተገልጦለት ሒዶ የሰማእትነት አክሊልን እንዲቀበል አዘዘው ሰማያዊ የሆነ ቃል ኪዳንንም ገባለት በዚህም እጅግ ደስ አለው።
አባቱንና እናቱንም ትቶ ከሀረጉ ወጣ ስለ ከበረ ስሙ በሚቀበለው መከራ ውስጥ ርዳታ እንዲሰጠው እንዲአጸናው ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ወደ ሀገር አትሪብም ሔዶ በመኰንኑ ፊት ክብር ይግባውና በጌታችን ክርስቶስ ታመነ።
መኰንኑም ታላቅ ስቃይን አሰቃይቶ የእስክንድርያ አገረ ገዥ ወደ ሆነ ወደ ሉክያኖስ ሰደደው። በመርከብም ውስጥ ሳለ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጠለት በብዙ ደስታም አረጋግቶትና አጽናንቶ ቃል ኪዳንን ሰጠው ልቡናውም ፈጽሞ እጅግ ደስ አላት።
መኰንኑ ሉክያኖስም በጽኑዕ ስቃይ አሰቃይቶ ራሱን በሰይፍ ቆረጠ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግስተ ሰማያት ተቀበለ። የሀገሩ ሰዎችም መጥተው ስጋውን ወሰዱ ታላቅ ክብርንም አከበሩት ከስጋውም ታላላቅ የሆኑ ድንቆችና ተአምራት ተገለጡ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_አሮን_ካህን
በዚህች ቀን የካህኑ አሮን በትሩ ለምልማ የተገኘችበት ነው። በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት የቅዱሱ ካህን የአሮን በትር ሳይተክሏትና ውሃ ሳያጠጧት ለምልማ፣ አብባ፣ አፍርታ የተገኘችው በዚህ ቀን ነው። ዳታን፣ አቤሮንና ቆሬ ከተከታዮቻቸው ጋር በፈጠሩት ሁከት ምድር ተከፍታ ከዋጠቻቸው በሁዋላ እግዚአብሔር የ12ቱን ነገደ እሥራኤል በትር ሰብስቦ ሲጸልይበት እንዲያድር ሙሴን አዞት እንዲሁ ሆነ።
በነጋም ጊዜ ይህቺ ደረቅ የነበረች በትረ አሮን 12 ፍሬ (ለውዝ፣ ገውዝ፣ በኩረ ሎሚ) አፍርታ ተገኘች። (ዘኁ. 17፥1-11) ለጊዜው ክህነት ከቤተ አሮን እንዳይወጣ ምልክት ሆናለች። ለፍጻሜው ግን ምሳሌነቷ ለድንግል
ማርያም ነው። እመ ብርሃን የወንድ ዘር ምክንያት ሳይሆናት አምላክን ወልዳ ተገኝታለችና።
"ጸናጽል ዘውስተ ልብሱ ለአሮን ካህን ወዓዲ በትር እንተ ሠረጸት ወጸገየት ወፈረየት" እንዳለ #አባ_ሕርያቆስ። (#ቅዳሴ_ማርያም)
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር መስከረም_8
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ስምንት በዚህች ቀን የነቢያት አለቃ #ነቢዩ_ቅዱስ_ሙሴ ዕረፍቱ ነው፣ የበራክዩ ልጅ ካህንና ነቢይ የሆነ #ቅዱስ_ዘካርያስ በሰማዕትነት አረፈ፣ የከበረ #ቅዱስ_ዲማድዮስ በሰማእትነት አረፈ፣ የካህኑ #ቅዱስ_አሮን በትሩ ለምልማ የተገኘችበት ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሙሴ_ሊቀ_ነቢያት
መስከረም ስምንት በዚህች ቀን የእግዚአብሔር ሰው የሆነ የዋህ ቅን ጻድቅ የነቢያት አለቃ የሙሴ ዕረፍቱ ነው። ይህ ነቢይ ነፍሱን ስለእሳቸው አሳልፎ እስከ መስጠት ከእግዚአብሔር ወገኖች ጋር የደከመ ነው እርሱም በግብጽ አገር በኤርትራ ባሕርም ድንቆች ተአምራትን ያደረገ ነው።
ይህም ስለ ፈርዖን ትእዛዝ ወላጆቹ በግብጽ ወንዝ ውስጥ በጣሉት ጊዜ አውጥታ ላሳደገችው ለፈርዖን ልጅ ለተርሙት ልጅዋ መባልን አልወደደም። እርሱ ፈርዖን የዕብራውያንን ወንዶች ልጆች ይገድሏቸው ዘንድ አዝዞ ነበርና። በአገኘችውም ጊዜ ለርሷ ልጅ ሊሆናት ወስዳ በመልካም አስተዳደግ አሳደገችው።
አርባ ዓመትም በሆነው ጊዜ አንዱን ዕብራዊ የግብጽ ሰው የሆነ ሲያጠቃው አየ ለዕብራዊውም ተበቅሎ ግብጻዊውን ገደለው። በማግሥቱ ደግሞ ሁለት ዕብራውያን እርስ በርሳቸው ሲጣሉ አያቸው ሊአስታርቃቸውና በመካከላቸው ሰላምን ሊአደርግ ወደደ። አንዱ ዐመፀኛም ትላንት ግብጻዊውን እንደገደልከው ልትገድለኝ ትሻለህን አለው።
ስለዚህም ነገር ሙሴ ፈርቶ ወደ ምድያም አገር ሸሸ በዚያም ሚስት አግብቶ ሁለት ልጆችን ወለደ በዚያም አርባ ዓመት ኖረ በጳጦስ ቍጥቋጦ ውስጥም እሳት እየነደደ ራእይን አየ። አይቶ ሊረዳ በቀረብ ጊዜ ጳጦስ በተባለ ቊጥቋጦ ውስጥ እግዚአብሔር ተናገረው። ወደ ግብጽ አገርም ሒዶ የእስራኤልን ልጆች ከዚያ እንዲአወጣቸው አዘዘው።
ከዚህን በኋላ እግዚአብሔር በሙሴ እጅ በግብጻውያን ላይ ዐሥር መቅሠፍቶችን አመጣ። መጀመሪያው የወንዙን ውኃ ደም ማድረግ የመጨረሻው የግብጻውያንን የበኵር ልጅ መግደል ነው።
ከዚህም በኋላ ሕዝቡን ከግብጽ አገር አወጣቸው የኤርትራንም ባሕር ከፍሎ በውስጡ አሳለፋቸው የባሕሩንም ውኃ በጠላቶቻቸው በፈርዖንና በሠራዊት ላይ ገልብጦ አሠጠማቸው።
ከዚህም በኋላ በምድረ በዳ ውስጥ አርባ ዓመት ሙሉ መና አወረደላቸው ውኃንም ከአለት አፈለቀላቸው ይህን ሁሉ በጎ ሥራ በዚህ በደግ ነቢይ ሙሴ እጅ እግዚአብሔር አደረገላቸው እነርሱ ግን ይዘልፉት ነበር ብዙ ጊዜም በድንጊያ ሊወግሩት ሽተው ነበር።
እርሱ ግን በእነርሱ ላይ ልቡን አስፍቶ በመታገሥ ስለርሳቸው ወደ እግዚአብሔር ይማልዳል። እነርሱንም አብዝቶ ከመውደዱ የተነሣ እግዚአብሔርን አቤቱ የዚህን ሕዝብ በደሉን ይቅር ካላልክ ከሕይወት መጽሐፍህ ሰርዘኝ አለው።
ሰው ከወዳጁ ጋር እንደሚነጋገር አምስት መቶ ሰብዓ ቃላትን ከእግዚአብሔር ጋር እንደተነጋገረ መጽሐፍ ምስክር ሆነ። የእስራኤል ልጆችም በሚያዩት ጊዜ እንዳይሞቱ ፊቱን እስከ ሸፈነ ድረስ በእግዚአብሔር በጌትነቱ ብርሀን ፊቱ በራ።
መቶ ሃያ ዓመት የሆነ ዕድሜውም በተፈጸመለት ጊዜ ለአገልጋዩ ለነዌ ልጅ ለኢያሱ ሕዝቡን እርሱ እንደጠበቃቸው እንዲጠብቃቸው በእጁ ውስጥ እንዲአስረክበው እግዚአብሔር ሙሴን ለኢያሱ አስረክብ ብሎ አዘዘው።
ሙሴም ኢያሱን ጠርቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ አዘዘው ሕጉንም እንዲጠብቅ ሕዝቡንም ለኢያሱ በእጁ አስረከባቸው ወደ ምድረ ርስትም እርሱ እንደ ሚአስገባቸው አረጋገጠለት። ሙሴም እግዚአብሔር እንዳዘዘው በምስክሩ ድንኳን ውስጥ የሚሠራውን ሁሉ ሠርቶ ከአዘጋጀ በኋላ በተራራ ውስጥ አረፈ በዚያም በመላእክት እጅ በሥውር ተቀበረ። የእስራኤል ልጆች ወስደው እንዳያመልኩት እግዚአብሔር የሙሴን ሥጋ ሠወረ።
በእስራኤል ልጆች ውስጥ እንደ ሙሴ ያለ ደግ የዋህ ቅን የሆነ ነቢይ እንደማይነሣ መጽሐፍ ምስክር ሆነ። ሰይጣንም የሙሴን ሥጋ ለእስራኤል ሊገልጥላችው በወደደ ጊዜ ሐዋርያው ይሁዳ በጻፈው መጽሐፉ እንደመሰከረ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ገሠጸው ከዚህም ሥራ ከለከለው የእስራኤል ልጆችም አርባ ቀን አለቀሱለት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዘካርያስ_ካህን_ወነቢይ
በዚህችም ቀን የበራክዩ ልጅ ካህንና ነቢይ የሆነ የከበረ ዘካርያስ በንጉሥ ሄሮድስ እጅ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ካህን ስለ ልጁ ዮሐንስ መወለድ የመላእክት አለቃ ገብርኤል በነገረው ጊዜ ነገሩን አምኖ አልተቀበለም ። ስለዚህም ሕፃኑ እስቲወለድ ዲዳ ትሆናለህ አለው። በተወለደም ጊዜ አንደበቱ ተፈትቶ እግዚአብሔርን አመሰገነው የልጁንም ስም ዮሐንስ ነው ብሎ ጻፈ። እርሱና ሚስቱ በእግዚአብሔር ሕግ ያለ ነቀፋ የጸኑ ደጎች እንደሆኑ የከበረ ወንጌል ስለዚህ ምስክር ሆኗል።
ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስም በተወለደ ጊዜ ሊሰግዱለት የጥበብ ሰዎች መጡ። ሄሮድስም ስለ መንግሥቱ ፈራ ደነገጠም። ስለዚህም ጭፍሮቹን ልኮ በይሁዳ አገር የቤተ ልሔምንና የገሊላን ሁሉንም ሕፃናት ዕድሜያቸው ሁለት ዓመት የሚሆናቸውን ከዚያም የሚያንሱትን ገደላቸው ሰነፍ የሆነ ሄሮድስ ክርስቶስን ከሕፃናት ጋር እንደ ሚገድለው አስቦ ነበርና።
ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ ለዮሴፍ በሕልም ተገልጾለት ስለአዘዘው ጌታችን ሕፃኑንና እናቱን እመቤታችንን ድንግል ማርያምን ይዞ ወደ ግብጽ አገር መጡ። ኤልሳቤጥ ግን ሕፃኗን ዮሐንስን ይዛ ወደ ዱር ወጣች ወደ ሲና በረሃም ሸሸች በዚያም ሕፃኗን እያሳደገች ሰባት ዓመት ኖረች ከዚህም እርሷ አረፈች ሕፃኑም በመምህርነት ለእሥራኤል እስከሚገለጥበት ጊዜ ድረስ በበረሀ ውስጥ ብቻውን ኖረ።
ሕፃናትንም ከገደላቸው በኋላ ዮሐንስ ክርስቶስ እንደሆነ ሄሮድስ አሰበ ተጠራጠረ ከአባቱ ከዘካርያስ ዘንድ ሕፃኑን ይሹ ዘንድ ወታደሮቹን ላከ ዘካርያስም ሕፃኑ ያለበትን ወይም እናቱ ያለችበትን እኔ አላውቅም አለ። ሄሮድስም ልጅህን ካላመጣህልኝ እኔ እገድልሃለሁ አለው። ዘካርያስም ከእርሱ ዛቻ የተነሣ አልፈራም ወታደሮቹንም አዝዞ በቤተ መቅደሱና በመሠዊያው መካከል ገደሉት ክብር ይግባውና እግዚአብሔርም ሥጋውን ሠወረ ደሙ ግን እንደ ደንጊያ ሆነች።
ካህናቱና ሕዝቡ እንደ ልማዳቸው ለጸሎት በመጡ ጊዜ ከካህናት አንዱ ወደ ቤተ መቅደስ ውስጥ ገባ። የረጋ ደምን አገኘ ከመጠዊያውም እንዲህ የሚል ቃልን ሰማ እነሆ የበራክዩ ልጅ ዘካርያስ ተገደለ የሚበቀልም እስሚመጣ ደሙ ስትጮኽ ትኖራለች።
እንዲህ የሚልም አለ ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት የሆነ የበራክዩ ልጅ ዘካርያስ ይህ አይደለም ያ አልተገደለም በዕድሜው ኡረት በሚባል አገር ሞተ እንጂ ሥጋውም በዚያ ያለ ጥፋት ተገኝቶ ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለታል። የዚህ ዘካርያስ ግን ሥጋው አልተገኘም ስለ መገደሉ የደሙ ድምፅ ምስክር ሆነ እንጁ።
ደግሞ እንዲህ ተባለ ሄሮድስ ሕፃናትን በገደላቸው ጊዜ ከአይሁድ አንድ ሰው መጥቶ የእግዚአብሔር መልአክ ትወልዳለህ ብሎ ነግሮት ለዘካርያስ ልጅ ተወልዶለታል ምናልባት እርሱ ክርስቶስን ይሆን አለው። ስለዚህ ሄሮድስ ሕፃኑን ዮሐንስን ይገድሉት ዘንድ ወታደሮችን ላከ።
ዘካርያስም ወታደሮችን እንዲህ አላቸው ሕፃኑን እኔ ወደሌላ ቦታ ወስጄዋለሁ ከእኔ ጋራ መጥታችሁ ራሳችሁ ከዚያ ቦታ ውሰዱት ወደ ቤተ መቅደስም እስከ አስገባቸው ድረስ ወታደሮቹ አብረውት መጡ። እርሱም ሕፃኑን ልጁን በመሠዊያው ጠርዝ ላይ አኑሮ ጸለየበት ይህም የልጁን መወለድ የእግዚአብሔር መልአክ ለእርሱ የነገረበት ነው።
እርሱም ወደ ቅዱስ ሳዊርያኖስ መጥቶ ከእርሱ ጋር ተከራከረ ግን ከቅዱስ ሳዊርያኖስ አንደበት የሚመጣውን ቃል ይሰማ ዘንድ አልተቻለውም።
ከዚህም በሗላ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሲስ ክርስቶስ ለቅዱስ ሳዊርያኖስ በራእይ ተገልጦለት ይህ አይሁዳዊ እርሱ ራሱ ክርስቶስ ከአከበራቸውና ከባረካቸው ወገን ውስጥ ሊሆን እንዳለው አስረዳው።
ያ አይሁዴዊውም ወደ ቤቱ በገባ ጊዜ አስጨናቂዎች የሆኑ የስቃይ ቦታዎች በሕልሙ በማየት እንዲህ የሚለውን ቃል ታላቅ በሆነ የዘላለም ሥቃይ ውስጥ የሚኖሩ እሊህን ከሀዲዎች ዘመዶችህ አይሁድን እነሆ እይ እነርሱም ክብር ይግባውና በክርስቶስ ያላመኑ ናቸው።
በማግሥቱም ያ አይሁዳዊ ወደ ቅዱስ ሳዊርያኖስ መጥቶ ከእግሩ በታች ወድቆ ሰገደለት ክርስቲያንም ያደርገው ዘንድ ለመነው ያን ጊዜም እርሱንና ቤተሰቦቹን የሀገር ሰዎችንም ሁሉ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው።
የቀሩትም አይሁድ ሁሉ አለቃቸው ክርስቲያን እንደሆነ በሰሙ ጊዜ አምነው ተጠምቀው ክርስቲያኖች ሆኑ።
እንዲሁም ኒሞንጦስ የሚባሉ ሌሎች ሥራየኞች ሰዎችን ወደ ክርስቲያን ሃይማኖት እንዲገቡ ቅዱስ ሳዊርያኖስ ለመናቸው እነርሱ ግን በሥራያቸው ስለሚታበዩ ከእርሱ ቃሉን አልሰሙም እነርሱም በዕድ ወደ እነርሱ የመጣ እንደሆነ በፊቱ አረርን ይበትናሉ ምንም ምን ማየት አይችልም።
ቅዱስ ሳዊርያኖስንም ወደ ቀናት ሃይማኖቱ እሊህን ሥራየኞች ሰዎች ያስገባቸው ዘንድ ዕንባን በማፍሰስ ክብር ይግባውና ጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመነው እግዚአብሔርም በእርሱ ላይ ብቻ ጽኑዕ ደዌ አመጣ ወደ ክርስቲያን ወገኖች ግን ምንም ምን አልደረሰም። በግብጽ አገር በፈርዖንና በሠራዊቱ በግብጻውያንም ላይ መቅሠፍት ሲታዘዝ ወደ እስራኤል ወገን እንዳልደረሰ እንዲሁ ሆነ።
በዚያም ወራት እንዚያ ሥራየኞች የቅዱስ ሳዊርያኖስን ቃል ሰምተው ትእዛዙን ስለ አልተቀበሉ ስለዚህም ይህ ጽኑ ደዌ በላያቸው እንደመጣ አወቁ። ወደ ቅዱስ ሳዊርያኖስም መጥተው በደላቸውን ይቅር ይላቸው ዘንድ ክርስቲያኖችም ያደርጋቸው አስተምሮ አጥምቆ ክብር ይግባውና ከክርስቶስ መንጋዎች ጋር አንድ አደረጋቸው።ያቺ አገር ሁለመናዋ አንድ ማኅበር አንድ መንጋ ሆነች።
ሰይጣንም ልብሱ በተቀደደ ሽማግሌ አማሳል ሆኖ ፈጽሞ የሚጮህ ሆነ እንዲህም አለ። ከጽንፍ እስከ ጽንፍ በአለው ቦታ ሁሉ ጨነቀኝ በግብጽ አገርም ጠንካሮች መነኰሳት ተመሉባት በሮሜ አገርም ሊቀ ጳጳሳት ዮናክንዲኖስ በውስጧ ይኖራል ደግሞ በቁስጥንጥንያ ዮሐንስ አፈወርቅ አለ ይህ ቦታ ለእኔ ቀረልኝ ብዬ ነበር እነሆ ሳዊርያኖስ ከእጄ ውስጥ ነጠቀኝ አለ።
እንዲህም ሆነ የፋርስ ሰዎች ሊወጉአቸው ሽተው ወደ አኖሬዎስና ወደ አርቃዴዎስ መልእክትን ላኩ እሊህ ደጋጎች ነገሥታትም የፋርስ ሰዎች የላኩትን ደብዳቤ ወደ ቅዱስ ሳዊሮያኖስ ላኩት። እርሱም ያቺን ደብዳቤ በአነበባት ጊዜ የደብዳቤውን መልስ ወደ ነገሥታት አኖሬዎስና አርቃዴዎስ እያስረዳ እንዲህ ብሎ ጻፈ እኛ የክርስቶስ ከሆን መንግሥታችንም የክርስቶስ ነው እንዲህም ከሆነ የጦር መሣሪያን የጦር ሠራዊትንም አንሻም። እግዚአብሔርም ከቀደሙ ነገሥታት ጋር ሁኖ ያደረገውን እንዴት እንዳዳናቸው ጸላቶቻቸውንም እንዴት ድል እንዳደረጓቸው አስታወሳቸው።
ታላቁም ጾም ሳይደርስ የፋርስ ሰዎች አፍረው ከእነርሱ ዘንድ ተመልሰው ሔዱ። ስለ ዮሐንስ አፈወርቅም ከኤጲስቆጶሳት ጋር በአመጡት ጊዜ ንግሥት አውዶክስያን በምክሩ ሁሉ መክሮዋትና ገሥጿት ነበር። ስለ ዮሐንስ መሰደድም እርሱ ምንም ምን ያደረገው ስምምነት የለም ንግሥቲቱም ምክሩን ባልሰማች ጊዜ ወደ አገሩ ተመለሰ።
ብዙዎች ድርሳናትንና ተግሣጻትንም ደረሰ እሊህም ሃይማኖታቸው የቀናች ሰዎች በአሉባቸው አብያተ ክርስቲያናት እስከ ዛሬ ይኖራሉ። ቅዱስ ሳዊርያኖስም ሸመገለ ዕድሜውም መቶ ዓመት ሆነው ከሥጋውም ከመለየቱ በፊት በዐሥር ቀን የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጾለት ከዚህ ዓለም ከድካምም ወደ እረፍት እንደ ሚወጣ ነገረው።
ከዚህም በኃላ ሕዝቡን ጠራቸው ክብር ይግባውና የእግዚአብሔርን ሕግ በመጠበቅ ጸንተው እንዲኖሩ አዘዛቸውና በሰላም በፍቅር አረፈ። ነፍሱንም በፈጣሪው ክርስቶስ እጅ ሰጠ። ዕረፍቱም የቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ ኤጲፋንዮስ በአረፈ በሁለት ዓመት ዮሐንስ አፈወርቅ በአረፈ በአንድ ዓመት ነው። ሥጋውንም እንደ ሚገባ በንጹሕ ልብስ ገነዙ ብዙ መዝሙራትንና ምስጋናዎችን አድርገውለት በክብር ቀበሩት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱሳን_አጋቶን_ዼጥሮስ_ዮሐንስና_አሞን
በዚህች እለት የከበሩ አጋቶንና ጴጥሮስ ዮሀንስና አሞን እናታቸውም ራፈቃ በሰማእትነት አረፉ። እሊህ ቅዱሳንም በላይኛው ግብፅ ቁስ ከሚባል አውራጃ ከቆንያ ከተማ ናቸው። ለእርሳቸውም ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ ተገልፆላቸው። ከእነርሱ የሚሆነውን ስብራ በምትባል ከተማ እርሷም ወደ እስክንድርያ ክፍል ናት በዚያ የምስክርነት አክሊል እንደሚቀበሉ ስጋቸውንም ወደ ግብፅ ደቡብ ነቅራሀ ወደሚባል አገር እንደሚወስዱ አስረዳቸው ቅዱሳኑም በዚች ራእይ ደስ አላቸው።
በማለዳም ተነስተው ገንዘባቸውን ሁሉ ለድሆችና ለችግረኞች ሰጡ ከእነርሱም የሚበልጥ ወንድማቸው አጋቶን በሀረጉ ሹም ነበር በሁሉም ዘንድ የተወደደ ነው ራፊቃ እናታቸውም ክብር ይግባውና ስለ ክርስቶስ በመከራ ስቃይ ላይ የሚፀኑና የሚታገሱ እንዲሆኑ ታበረታታቸው ነበር።
ከዚህም በኃላ ቊስ ወደ ሚባል አገር ሲደርሱ በመኰንኑ በዲዮናሲዮስ ፊት ቁመው ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ። ከእነርሱም አስቀድሞ እናታቸው ራፊቃን አሰቃያት እርሷም በስቃይ ውስጥ በመታገስ ደስተኛ ነበረች ከዚህም በኃላ አራቱን ልጆቿን አሰቃያቸው።
እነርሱንም በማሰቃየት በሰለቸ ጊዜ ወደ እስክንድርያ እንዲልካቸው ወገኖቹ መከሩት በእነርሱ ምክንያት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ህዝቡ እንዳያምን ፈርተዋልና። እነርሱ በሁሉ ዘንድ የተወደዱ ስለሆነ በእርሳቸውም ምክንያት ከዚህ በፊት ብዙዎች ሰዎች በክብር ባለቤት በክርስቶስ አምነው በሰማእትነት ሙተዋልና የሰማእትነት አክሊልንም ተቀብለዋልና።
ወደ እስክንድርያም ገዥ ወደ አርማንዮስ ቅዱሳኑን በአመጡአቸው ጊዜ በዚያን ወቅት ስሟ ስብራ በምትባል አገር በዚያ ነበር። የተጋድሎአቸውንም ፅናት አውቆ ፅኑ ስቃይን አሰቃያቸው ስጋቸውንም ቆራርጦ ከመንኮራኩር ውስጥ ጨመራቸው።
ዳግመኛም ዘቅዝቀው ሰቀሉአቸው በዚህም ሁሉ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መኮንኑና የርሱ ሰዎች ሁሉ እስቲአፍሩ ያለ ምንም ጥፋትና ጉዳት የሚያነሳቸው ሆነ።
ከዚህም በኃላ ራሶቻቸውን ይቆርጡ ዘንድ ስጋቸውንም በባህር ሊጥሉ በታናሽ ታንኳ ጫኑአቸው። በዚያንም ጊዜ ከግብፅ በስተደቡብ መፂል ከሚባል አውራጃ ነቅራሀ ከምትባል መንደር ወደ አንድ ባለ ፀጋ እግዚአብሄር መልአኩን ላከ።
የቅዱሳኑንም ስጋ እንዲወስድ አዘዘው። እርሱም ወሰዳቸው የፃድቃን ማደሪያቸው ይህ ነወወ የሚል ቃልን ሰማ የመከራውም ወራት እስከሚአልፍ በዚያ አኖሩአቸው።
ከዚህም በኃላ ገለጡአቸው ውብ የሆነች ቤተ ክርስቲያንንም ሰርተውላቸው ስጋቸውን በውስጧ አኖሩ። እግዚአብሔርም ከስጋቸው ድንቆች የሆኑ ታላላቅ ተአምራትን ገለጠ በዚያም ወራት ስጋቸውን ስሙንጥያ ወደሚባል አገር አፈለሱ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
ከዚህም በኃላ የተነጨውን ጽሕሙን ያወለቁትንም ጥሩሱን ሰብስቦ ወደ እስክንድርያ አገር ላካቸው እነሆ የቀናች ሃይማኖት ፍሬ ይህ ነው አላቸው። ለጉባኤውም የተሰበሰቡ ኤጲስቆጶሳት በዲዮስቆሮስ ላይ የደረሰውን መከራ በአዩ ጊዜ እጅግ ፈሩ በእርሱ የደረሰ በእነርሱ ላይ እንዳይደርስ ስለዚህም ከመናፍቁ ንጉሥ ከመርቅያኖስ ጋር ተስማሙ።
በሲኦል ውስጥ ይቆርጡት ዘንድ ባለው ምላሳቸውም ለክርስቶስ ሁለት የተለያዩ ባሕርያት አሉት ብለው በንጉሡ መዝገብ ላይ በእጆቻቸው ጽፈው ፈረሙ። ቅዱስ ዲዮስቆሮስም ተመልሶ ያን በውስጡ የጻፉበትን ደብዳቤ ያመጡለት ዘንድ ወደእሳቸው ላከ እነርሱም ላኩለት እነርሱ እንደጻፉ በውስጡ እርሱ የሚጽፍ መስሏቸዋልና።
እርሱ ግን አባቶቻችን ሐዋርያት ከአስተማርዋት ከቀናች ሃይማኖት በኒቅያ የተሰበሰቡ ሃይማኖታቸው የቀና ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ኤጲስቆጲሳት አባቶቻችን ከሠሩት ሕግ የሚወጣውን ሁሉ በደብዳቤው ግርጌ ጽፎ አወገዘ።
መና*ፍቁ ንጉሥም ተቆጥቶ ጋግራ ወደም ትባል ደሴት እንዲአግዙት አዘዘ ወደዚያም ወሰዱት።ከእርሱም ጋር የሀገረ ቃው ኤጲስቆጶስ አባ መቃርስ አብሮ ተሰደደ። ሌሎችም አራት መነኰሳት የሸሹ አሉ።
እሊህም ስድስት መቶ ሠላሳ ስድስት ኤጲስቆጶሳት ተቀምጠው በኬልቄዶን ለራሳቸው መመሪያ የሚሆናቸውን ሥርዓት ሠሩ።
የከበረ ዲዮስቆሮስንም በአጋዙት ጊዜ ከዚያች አገር ኤጲስቆጶስ ጭንቅ የሆነ መከራ ደረሰበት ኤጲስቆጶስ ንስጥሮሳዊ ስለሆነ ታላቅ ጉስቁልናንም አጎሳቁለው በእጆቹ ላይ ድንቆች ታላላቅ ተአምራቶችን እግዚአብሔር እስከገለጠ ድረስ።
የደሴቱም ሰዎች ሁሉ ሰገዱለት አከበሩት ከፍ ከፍም አደረጉት እግዚአብሔርም የመረጣቸውን በቦታው ሁሉ ያከብራቸዋልና።አባ ዲዮስቆሮስም አባ መቃርስን አንተ በእስክንድርያ አገር የሰማዕትነት አክሊልን ትቀበል ዘንድ አለህ አለው። ከዚህም በኃላ ከምእመናን ነጋዴዎች ጋር ወደ እስክንድርያ ላከው በእርሱ ላይ ትንቢት እንደተናገረ ገድሉን በዚያ ፈጸመ።
የከበረ አባት ዲዮስቅሮስ ግን መልካም ተጋድሎውን በፈጸመ ጊዜ ክብር ይግባውና እግዚአብሔርንም አገልግሎ ከዚች ኃላፊት ከሆነች ኑሮው ወጥቶ ሔደ የሃይማኖቱንም ዋጋ አክሊልን ተቀብሎ ወደ ዘላለም ዕረፍት ገባ ያረፈውም በዚያች በደሴተ ጋግራ ነው ሥጋውንም በዚያው አኖሩ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ሳዊርያኖስ
በዚህችም ቀን የገብላ ኤጲስቆጶስ የከበረ አባት ሳዊርያኖስ አረፈ። የዚህም ቅዱስ የአበባቱ ስም አብስርያኖስ ይባላል የሀገረ አቴናንም ፍልስፍና ተማረ ከዚያም ወደ ቂሣርያ ሔዶ አሸወቀታቸውን ሁሉ ተማረ።
ዳግመኛም ወደ ሮሜ ከተማ ተመልሶ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ተማረ ከጥቂት ዘመናት የብሉይንና የሐዲስን መጸሕፍት አጠና።
ከዚህም በሗላ ቁጥር የሌለው ብዙ ገንዘብን ትተውለት ወላጆቹ አረፉ ስለርሱ ፈንታ መቶ ዕጥፍ ይቀበል ዘንድ ወዶ ያንን ገንዘብ ለክብር ባለቤት ለክርስቶስ ሊሰጥ ወደደና ድሆችን መጸተኘኞችን ምስኪኖችን ችግረኞችንም በውስጥ ይቀበል ዘንድ የእንግዳ ረቀበያ ቤትን ሠራ።
አታእልትም ተከለ ፍሬዎችን ተሸክመው የሚያመጡላቸውን ሠራተኞችን አደረገ እነዚያም ስለ ድሆችና ስለ ችግረኞች የተሠሩ ቦታወች እስከ ዛሬ በስሙ የሚጠሩ ሆኑ።
አገረ ገዥ የሆነ አጎቱን በሮሜው ንጉሥ በአኖሬዎስ ዘንድ እንዲህ ሲል ወነጀለው በከበረ ወንጌል ቃል ኪዳን እነደገባ ከእርሱ ዘንድ ስለ ርሱ መቶ እጥፍ እቀበላለሁና እኔ ገንዘቤን ክብር ይግባውና ለክርስቶስ እሰጠዋለሁ በማለት ሳዊርያሮስ ገንዘቡን ሁሉ እንደበተነ ።
ይህም ነገር ለንጉሡ ደስ አሰኘው ፈጸሞም በእርሱ ደስ አለው እጅግም ወደደው ከእርሱም ከቤተ መንግስቱ እንዳይለይ ንጉሡ አኖሬዎስ አዘዘው ከእርሱም ጋር ሁል ጊዜ ወደ ቤተክርስቲያን በመሔድ ሌሊቱን ሁሉ ቁመው ያድራሉ ንጉሥ አኖሬዎስም የመነኰሳትን ስራዎች ስለሚሠራ ከልብሰ መንግሥቱ በታች በሥጋው ላይ ማቅ ይለብስ ነበር።
በዚህም ወራት ለሮሜ አገር ሊቀ ጳጳሳት ሁኖ የነበረ አባ ዮናክንዲኖስ ነው ለእርሱም ሳዊርያኖስ በብዙ ሕዝብ ላይ ኤጲስቆጶስ መሆን እንዲ ገባው እግዚአብሔር ገለጸለት።
ሊቀ ጳጳሳቱም እጅግ የሚወደውና የሚያከብረው ሆነ ከቶ እንድለየውም አይሻም ነበር በሁሉም ዘንድ ተወዳድ ሆነ ዜናውም በቁስጥንያው ንጉሥ በቴዎዶስዮስ ዘንድ ተሰማ።
ሰዎች ሁሉ እንደሚያከብሩት በአየ ጊዜ ድካሙ በውዳሴ ከንቱ እንዳይጠፍ ከዚያች ቦታ በሥውር ሊወጣ ወደደ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክም ተገለጸለት ወደ ሀገረ ገብሪ ሔዶ ለብዙ ነፍሳት የገዳም አባት እንዲሆን አዘዘው አበሌሊትም ወጥቶ ሔደ የምንኰስና ለብስን ከለበሰ በሗላ ደቀመዝሙር ቴዎድሮስ ከእርሱ ገር ነበር ክብር ይግባውና እግዚአብሔር ወደ ገብላ ገዳም እስከሚደርስ በፊቱ የምትሔድና የምትመራው በመኰራኩር አምሰል የብርሃን ሠረገላ ላከለት።
በዚያም ገዳም አበ ምኔት የሆነ ጻድቅ ሰው ነበር የቅዱስ ሳዊርያኖስንም መምጣት ጌታችን በራእይ አስረዳው ወደርሱ መጥቶ ተቀበለው ሰላምታም ሰጠውና ስለእርሱ ጌታችን በራእይ ተገልጾለት እንዳስረዳው ነገረው የጌታንም ቸርነት እጅግ አደነቁ።
ዜናውም በሀገሮች ሁሉ ተሰማ የማይቁጠሩ ብዚ ሰዎች ወደርሱ ተሰበሰቡ። ንጉሥ ቴዎዶስዮስም ለከበረ ሳዊርያኖስ ገዳማትን የሚሠሩለት ብዙዎች ሰዎችን ሹሞችንም ከእርሱ ዘነድ ላከ የእግዚአብሔርም መልአክ በውስጣቸው ገደም የሚሠሩባቸውን ቦታዎች ወሰነላቸው ብዙ መፍሳትን የሚያጽናና የሚያረጋጋ ሆነ።
ክብር ይግባው እና እግዚአብሔርም በእጆቹ ላይ ድንቆች የሆኑ ብዙዎች ተአምራትን አደረገ ከእርሳቸውም በሀገር ገብላ መኰንን ልጅ ሰይጣን እንደደረባትና መኮንኑም ሳዊርያኖስን ከዚህ አገር ካላበረርክ ከልጅህ አልወጣም የለው ነው።መኰንኑም ይህን ገነር በሰማ ጊዜ ተነሥቶ ወደ ከበረ ሳዊርያኖስ ሒዶ ሰይጣን ያለውን ነገረው ደሞም ልጅን ያድናት ዘንድ ለመነው።
ቅዱስ ሳዊርያኖስም እንድህ ብሎ ደብዳቤን ጻፈለት ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሰሱስ ክርስቶስ ስም ከእሷ ወጥተህ ሒድ አባቷም ያንን ደብዳቤ ተቀብሎ ወደልጁ ሱደ ያን ጊዜም ከመኰንኑ ልጅ ሰይጣን ወጥቶ ሔደ ልጅቷም ዳነች።
ዳግመኛም ታላቅ ሠራዊት እስቲሆኑ ድረስ ብዙዎች ወንጀለኞች ሰዎች ተሰበሰቡ ወደ ከበረ ሳዊርያኖስም ገዳም ገብተው ሊያፈረርሱት ፈለጉ ክብር ይግባውና እግዚአብሔርም በላያቸው ጨለማን አመጣ ምንም ምን ሳያዩ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት ኖሩ ቅዱስ ሳዊርያኖስንም ይቅር ይለቸው ዘንድ ብዙ ዕንባ በመፍሰሰ ለመኑት እርሲም ወደ ቦታዎቻቸው መልሶ ሰደዳቸው።
ዳግመኛም በገዳማቱ ውስጥ ያለ በእርሱ የሚተዳደሩ መነኰሳት ሁሉ ከእነርሱ የታመመ ቢኖር በላያቸው በመጸለይ ያድናቸዋው የሚያጸናናቸውና ሁሉም እንደ እግዚአብሔር መላእክት እስቲሆኑ ፈረሀ እግዚአብሔር የሚያስተምራቸው ሆነ።
እንዲህም ሆነ ስሙ ፈላታዎስ የሚባል የዚያች አገር ኤጲስቆጶስ ከእግዚአብሔር ዘንድ የሆነ እራይ ተገልጦለት ቅዱስ ሳዊርያኖስ በእርሱ ፈንታ ኤጲስቆጶስነት ይሾም ዘንድ እንዳለው አወቀ ያን ጊዜም ወደ ሕዝቡ ሁሉ ላከ ቅዱስ ሳዊርያኖስንም ኤጲስቆጶስነት እንዲሾሙት አዘዛቸው ለዚች ሹመት እግዚአብሔር መርጦታና።
ወዲያውኑ ደጋጏች ነገሥታት አኖሬዎስና አርቃዴዎስ ወስደው ገብላ በሚባል አገር ላይ ኢጶስቆጶስነት ሹሙት ስለ መንጋዎቹና ስለ ወገኖቹም አጠባበቅ ታላቅ ተጋድሎ ተጋደለ።
በዚያችም አገር እጅግ አዋቂ የሆነ የሙሴን ሕግ በማወቁ የሚመካ አንድ ስሙ ስቅጣር የሚባል ይሁዳዊ ነበር።
🔴#ሰንክሳር መስከረም7
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ሰባት በዚህች ቀን አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እናት #የቅድስት_ሐና ልደቷ ነው፣ የመጥምቁ ዮሐንስ እናት የከበረች #ቅድስት_ኤልሳቤጥ አረፈች፣ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት #ቅዱስ_ዲዮስቆሮስ አረፈ፣ የከበረ አባት #ቅዱስ_ሳዊርያኖስ አረፈ፣ የከበሩ #አጋቶንና_ጴጥሮስ_ዮሐንስና_አሞን እናታቸውም ራፈቃ በሰማእትነት አረፉ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ሐና_እመ_እግዝእትነ_ማርያም
መስከረም ሰባት በዚህች ቀን አምላክን ለወለደች ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እናቷ የሆነች የተመሰገነች የቅድስት ሐና ልደቷ ነው።
ይችም ቅድስት ከኢየሩሳሌም አገር ከሌዊ ነገድ ከካህኑ አሮን ትውልድ የሌዊ የሜልኪ ልጅ ለሆነ ለማጣት ('ጣ' ጠብቆ ይነበብ) ልጁ ናት። ለማጣትም ሦስት ሴቶች ልጆች አሉት የታላቂቱም ስሟ ማርያም ናት ሁለተኛዋም ስሟ ሶፍያ ሦስተኛዪቱም ስሟ ሐና ናት ታላቂቱ ማርያምም ለባል ተድራ አዋላጅ የሆነች ሰሎሜን ወለደቻት እርሷም መድኃኒታችንን ከወለደችበት ጊዜ ጀምሮ በስደቷም ወራት ከአረጋዊ ዮሴፍ ጋር እመቤታችንን ድንግል ማርያምን ያገለገለቻት ናት።
ሶፍያም ለባል ተድራ ለመጥመቁ ዮሐንስ እናቱ የሆነች ቅድስት ኤልሳቤጥን ወለደቻት። ይችንም ቅድስት ሐናን ከይሁዳ ነገድ ለሆነ ጻድቅ ስሙ ኢያቄም ለሚባል አጋቧት። (ሰሎሜና ኤልሳቤጥ ለቅድስት ሐና የእኅትማማች ልጆች ናቸው።)
ቅድስት ሐና ኢያቄምን አግብታ ስትኖር የቴክታና እና የጴጥሪቃ ምክነት በዘር ወርዶ መክና በመኖሯ የዐይኗ ማረፊያ የልቧ ተስፋ የሚሆን ልጅ እንዲስጣት ፈጣሪዋን ስትማጸን ኖራለች።
የነገሩትን የማይረሳ የለመኑትን የማይነሳ አምላክ ልመናዋን ሰምቶ ሐምሌ ፴ ራእይ አየች። ራእዩንም ከባሏ ከኢያቄም ጋር ተወያየተው ምንጣፍ ለይተው ሱባኤ ገቡ።
ከአንድ ሱባኤ በኋላ ነሐሴ ፯ ቀን ጌታ ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ እንደሚወልዱ አበሠራቸው። ከዚያም እመቤታችን ጸንሳ ልዩ ልዩ ተአምራትን አድርጋለች። ሳምናስን ከሞት አስነስታለች። በርሴባን ዐይኗን አብርታለች። ከዚያም በአይሁድ ተንኮልና አሳዳጅነት ወደ ሊባኖስ ተራራ ተሰዳ ድንግል ማርያምን ወልዳለች። በመውለዷም ሕዳሴ አካል አግኝታ ከኖረች በኋላ ዐርፋለች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ኤልሳቤጥ
በዚችም ቀን የመጥምቁ ዮሐንስ እናት የከበረች ኤልሳቤጥ አረፈች። ቅድስት ኤልሳቤጥ ትውልዷ ከነገደ ሌዊ ነው:: ሐረገ ሙላዷም ከቅዱስ አሮን ካህን ወገን ይመዘዛል:: ከአሮን በቴክታና በጥሪቃ ወርዶ ሔርሜላ ላይ ይደርሳል::
ይህቺ ሔርሜላ የምትባል ደግ ሴት ማጣት ("ጣ" ጠብቆ ይነበብ) የሚባል የተባረከ ሰው አግብታ 3 ቡሩካት ልጆችን ወለደች:: የመጀመሪያዋን 'ማርያም' አሏት:: እርሷ ቅድስት ሰሎሜን ወለደች:: ሁለተኛዋን 'ሶፍያ' አሏት:: እርሷ ደግሞ ቅድስት ኤልሳቤጥን ወለደች:: ሦስተኛዋ ግን የተለየች ናት:: 'ሐና' ብለው ሰየሟት:: እርሷም የሰማይና የምድር ንግሥት የሆነችውን ድንግል ማርያምን ወለደች:: በዚህም መሠረት ድንግል ማርያም: ቅድስት ኤልሳቤጥና ቅድስት ሰሎሜ የእህትማማች ልጆች ናቸው::
ቅድስት ኤልሳቤጥ እድሜዋ በደረሰ ጊዜ ስም አጠራሩ የከበረ: ደግ ካህን ለሆነ: ለቅዱስ ዘካርያስ አጋቧት:: እነርሱም ልጅ አልነበራቸውም ነበርና በብስራተ መልአክ ቅድስት ኤልሳቤጥ 90 ካህኑ ዘካርያስ 100 ሳሉ መስከረም 26 ቀን ታላቁን ሰው ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቁን ጸንሰች ለ6 ወራት ራሷን ሠወረች::
ድንግል እመቤታችን የኤልሳቤጥን መጽነስ በሰማች ጊዜ ለሰላምታ ሄዳ ነበር። በዚያም ወቅት ቅድስት ኤልሳቤጥ መንፈስ ቅዱስ ስለ ሞላባት እመ ብርሃንን አመስግናታለች:: በማሕጸኗ ያለ የ6 ወር ጽንስም የእመ አምላክን ድምጽ ቢሰማ በደስታ ዘሏል:: ለፈጣሪውም ስግደተ-ስባሔ አቅርቧል::
ቅዱስ ዮሐንስ ከተወለደ 2 ዓመት ከ6 ወር በሆነው ጊዜ ሰብአ ሰገል በመምጣታቸው በእሥራኤል ምድር የሚገኙ ሕጻናትን ሔሮድስ አስፈጀ:: በዚህ ጊዜም እናቱ ቅድስት ኤልሳቤጥ ይዛው ስትሸሽ ካህኑን ዘካርያስን ግን በቤተ መቅደስ መካከል ገድለውታል:: አረጋይት ኤልሳቤጥም ሕጻኑን እያሳደገች በገዳመ ዚፋታ ቆይታለች:: ቅዱስ ዮሐንስ በልጅነቱ እዚያው በበርሃ እንዳለ በዚህች ቀን አርፋለች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዲዮስቆሮስ_ሊቅ
በዚህችም ቀን የከበረና የተመሰገነ የእስክንድርያ አገር ሊቀ ጳጳሳት አባ ዲዮስቆሮስ አረፈ። እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃያ አምስተኛ ነው።
ስለ ቀናች ሃይማኖትም ታላቅ ተጋድሎን ከተጋደለ በኋላ ዕረፍቱ በተሰደደበት በደሴተ ጋግራ ሆነ። ይህም እንዲህ ነው ንጉሥ መርቅያኖስ ወደ ሰበሰበው ጉባኤ በጠሩት ጊዜ ሲደርስ ብዛታቸው ስደስት መቶ ሠላሳ ስድስት የሆነ ታላቅ ጉባኤን አየ። እንዲህም አለ ይህ ታላቅ ጉባኤ እስቲሰበሰብ ድረስ በሃይማኖት ላይ የተገኘው ጉድለት ምንድን ነው።
ይህ ጉባኤ የተሰበሰበው በንጉሥ ትእዛዝ ነው አሉት። እንዲህም አላቸው ይህ ጉባኤ ስለ ክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቢሆን ኖሮ እኔ ተቀምጬ እግዚአብሔር በሰጠኝ በአንደበቴ እናገር ነበር ግን የዚህ ጉባኤ መሰብሰብ በንጉሥ ትእዛዝ ከሆነ የሰበሰበውን ጉባኤ ንጉሡ እንዳሻው ይምራ።
ከዚህም በኃላ አንዱን ክርስቶስን ከተዋሕዶ በኋላ ሁለት ባሕርይ ሁለት ምክር የሚያደርግ የክህደት ቃል በውስጡ የተጻፈበትን የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ልዮን የላከውን ደብዳቤ የከበረና የተመሰገነ ዲዮስቆሮስ ቀደደ።
በመንፈስ ቅዱስ የሚናገር የከበረ ዲዮስቆሮስም በጉባኤው ፊት እንዲህ ብሎ አስረዳ ሰው እንደመሆኑ ወደ ሠርግ ቤት የጠሩት ጌታችን ክርስቶስ አምላክ እንደመሆኑ ውኃውን ለውጦ ወይን ያደረገው ከሀሊ ስለሆነ ሰውነቱና መለኮቱ በሥራው ሁሉ የማይለይ አንድ ነው።
ደግሞ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቄርሎስ ከተናገረው የአካላዊ ቃል ተዋሕዶ እንደ ነፍስና ሥጋ እንደ እሳትና ብረት ተዋሕዶ ነው ያለውን ቃል ምስክር አድርጎ በማምጣትም አስረዳ። እሌህም የተለያዩ ሁለቱ ጠባዮች ስለ ተዋሕዷቸው አንድ ከሆኑ እንዲሁም የክብር ባለ ቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርሱ አንድ መሲሕ አንድ ጌታ አንድ ባሕርይ አንድ ምክር ነው እንጂ ወደ ሁለት አይከፈልም አላቸው።
ከዚያም ከተሰበሰበው ጉባኤ ውስጥ ማንም ሊከራከረው የደፈረ የለም ከውስጣቸውም የእግዚአብሔር ጠላት ስለሆነው ስለ ከሀዲው ንስጥሮስ በኤፌሶን ጉባኤ አስቀድሞ ተሰብስበው የነበሩ አሉ።
ወደ ንጉሥ መርቅያኖስና ወደ ሚስቱ ንግሥት ብርክልያ ከእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ከአባ ዲዮስቆሮስ በቀር ስለ ሃይማኖት ትእዛዛችሁን የሚቃወም የለም ብለው ነገር ሠሩበት።
ቅዱስ ዲዮስቆሮስንም ወደ ንጉሥ አቀረቡት ከእርሱም ጋር ታላላቅ ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስቆጶሳት ከጉባኤው የሆኑ ነበሩ ከጥዋትም እስከማታ እርስበርሳቸው ሲከራከሩ ዋሉ። የከበረ ዲዮስቆሮስም የቀናች ሃይማኖቱን አልለወጠም ንጉሡና ንግሥቲቱ በእርሱ ተቆጥተው እንዲደበድቡት አዘዙ ስለዚህም ደበደቡት ጽሕሙን ነጩ ጥርሶቹንም ሰበሩ እንዲህም አደረጉበት።
🔴#ስንክሳር መስከረም_6
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ስድስት በዚች ቀን ታላቅ ነቢይ የአሞጽ ልጅ #ቅዱስ_ኢሳይያስ አረፈ፣ #የአቡነ_ሳሙኤል_ዘዋልድባ ዐፅማቸው ከዋልድባ አብረንታንት ወደ ደብረ ዓባይ የፈለሰበት ዕለት ነው፣ #ቅድስት_ሰብልትንያ በዲዮቀልጥያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ሞተች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ነቢዩ_ኢሳይያስ
መስከረም ስድስት በዚች ቀን ታላቅ ነቢይ የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ አረፈ። ይህም ነቢይ ለይሁዳ በነገሡ በአምስቱ ነገሥታት ዘመን አስተማረ ትንቢትም ተናገረ እሊህም አዝያን ኢዮአታም አካዝ ሕዝቅያስና ምናሴ ናቸው።
በአካዝ ዘመንም እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ። እነሆ ስለዚህ እግዚአብሔር ምልክትን ይሰጣችኋል። እነሆ ድንግል ፀንሳ ወንድ ልጅን ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች። ትርጓሜውም እግዚአብሔር ከእኛ ጋራ አንድ ሆነ ማለት ነው።
እርሱም በኃጢአታቸው ከሚመጣባቸው ፍዳ ወገኖቹን የሚያድናቸው ወደ ሃይማኖቱም የሚአስገባቸው እንደሆነ የእስራኤልንም ልጆች መሥዋዕታቸውንና ክህነታቸውን እንደሚሽር ከሐዲስ ወገኖችም የሚያመሰግኑት ካህናትን እንደሚሾም ተናገረ።
የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬምም ኢየሩሳሌምን ከቦ የስድብ ቃልን በክብር ባለቤት በእግዚአብሔር ላይ በተናገረ ጊዜ የፋርስ ንጉሥ ሰናክሬምን ያጠፋው ዘንድ እግዚአብሔር እንዳለው ለሕዝቅያስ ትንቢትን ተናገረ።
በዚያች ሌሊትም እግዚአብሔር የላከው የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ወደ ሠናክሬም ሰፈር መጥቶ ከፋርስ ሠራዊት መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ አርበኞችን ገደለ። የለኪሶ ሰዎች ሲነጋ በተነሡ ጊዜ የሞቱትን ሰዎች ሬሳ ሁሉ አዩ።
ሕዝቅያስም ታሞ ለሞት በተቃረበ ጊዜ የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ ወደርሱ መጥቶ እግዚአብሔር ትሞታለህ እንጂ አትድንም ብሏልና ቤትህን አዘጋጅ አለው። ሕዝቅያስም ፊቱን ወደ ግድግዳው መልሶ ወደ እግዚአብሔር ለመነ ፈጽሞ ጽኑ ልቅሶንም አለቀሰ።
ይህን ከነገረው በኋላ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ነቢዩ ወደ ኢሳይያስ መጣ ሒደህ ለሕዝቅያስ የአባትህ የዳዊት ፈጣሪ እግዚአብሔር ጸሎትህን ሰማሁ ዕንባህንም አየሁ። እነሆ በዘመንህ ላይ ዐሥራ አምስት ዓመት ጨመርኩልህ አለ በለው።
ዳግመኛም ስለ እስራኤል መማረክና ከምርኮ ስለ መመለሳቸው ትንቢት ተናገረ የፈሳሽ ውኃን ምንጭ በማፍሰስ በእጆቹ ላይ እግዚአብሔር ምልክትን ገለጠ።
ክብር ይግባውና ስለ መድኃኒታችን ክርስቶስ መከራ ትንቢት ተናገረ እንዲህም አለ። እርሱም በመከራው ጊዜ ነገርን አልተናገረም እንደ በግ ይታረድ ዘንድ መጣ በግ በሚሸልተው ሰው ፊት እንደ ማይናገር እንዲሁ በመከራው ጊዜ አልተናገረም።
ከዚህም በኋላ ደግሞ በሕዝቅያስ ልጅ በንጉሥ ምናሴ ላይ ትንቢት ተናገር ጣዖትን ስለማቆሙና ስለማምለኩ ገሠጸው። ስለዚህም ንጉሥ ምናሴ ተቆጥቶ በዕንጨት መሰንጠቂያ መጋዝ በራሱና በእግሮቹ መካከል ሠነጠቀው ምስክርነቱንም በዚህ ፈጸመ።
ትንቢት እየተናገረ የኖረበትም ዘመን ሰብዓ ዓመት ከዚያም በላይ ይሆናል። እርሱም ያስተማረው ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ ከመምጣቱ በፊት በዘጠኝ መቶ ዐሥራ ሦስት ዓመት ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ሳሙኤል_ዘዋልድባ
ዳግመኛም በዚህች ቀን የዋልድባው የአቡነ ሳሙኤል ዐፅማቸው ከዋልድባ አብረንታንት ወደ ደብረ ዓባይ የፈለሰበት ዕለት ነው፡፡ አባ ሳሙኤል ዘዋልድባ ትውልዳቸው ከካህናቱ ወገን አክሱም ነው አባታቸው እስጢፋኖስ እናታቸው አመተ ማርያም ይባላሉ። ለመምህር ሰጥተዋቸው ሲማሩ አድገው በኋላም ወላጆቻቸው በሞት ሲለዩአቸው ደብረ በንኰል ገዳም ገብተው ሥርዓተ ምንኩስናን ከአበው እያጠኑ ለትልቁም ለትንሹም በትሕትና እየታዘዙ ውሃ እየቀዱ እንጨት እየሰበሩ በትኅርምት በጽሞና በጸሎት ይኖሩ ነበር።
ሰይጣን በውዳሴ ከንቱ ጾር ቢመጣባቸው ከማሕበረ መነኮሳቱ ተለይተው በተባሕትዎ ለመኖር ሽተው ወጥተው ሲሔዱ ተከዜ ደረሱ። ወንዙ ሞልቶ የማያሻግራቸው ቢሆን ውሃውን በትምህርተ መስቀል ባርከው በአንድ እጃቸው መጽሐፍ በአንድ እጃቸው መብራት እንደያዙ ገብተው መብራቱ ሳይጠፋ መጽሐፉ ሳይበላሽ ተሻግረዋል። ዋልድባ ሲደርሱ ጌታ እዚህ ተቀመጥ ስላላቸው ገዳም መሥርተው ሥርዓተ ምንኩስናን እያስተማሩ ተቀመጡ። ዛሬ በዋልድባ የሚያመሰግኑበት ውዳሴ ማርያም ቅዳሴ ማርያምን ከተከዜ ወዲህ ያመጡ እሳቸው ናቸው። ይህንን እየጸለዩ ሲሔዱ ክንድ ከስንዝር መሬት ለቀው ይታዩ ነበር። አንድ ቀንም ይህንን ጸሎት ደግመው ውኃውን ቢባርኩት ኅብስተ ሕይወት ሆነላቸው ከነደቀ መዛሙርቶቻቸው ተመግበውታል።
እመቤታችንም የፍቅር መግለጫ ዕጣን፣ ወርቅ፣ እንቁ ሰጥታቸዋለች። ውዳሴዬን ከቅዳሴዬ አንድ አድርጎ የደገመውን አንተ ከገባህበት መካነ ሕይወት አስገባዋለሁ ብላ ቃልኪዳን ሰጥታቸዋለች። ጊዜ እረፍታቸው ሲደርስ ጌታን በስብሐተ መላእክት ተገልጦ በስምህ የተማጸነውን በጎ የሰራውን፣ ዜና ገድልህን የጻፈውን፣ ያስጻፈውን፣ ያነበበ፣ የተማረ፣ ያስተማረ፣ እስከ አሥር ትውልድ ድረስ ምሬልሃለሁ። በዚህ ቦታ በዋልድባ የሚሰበሰቡ ልጆችህን ከእዳ ከፍዳ እሰውርልሃለሁ አላቸው። እንኪያስ ቦታዋን ባርክልኝ ብለው እንደ መሶብ አንስተው አስባርከዋታል ጌታችንም እህል አይብቀልብሽ ኃጢአት አይሻገርብሽ ብሎ ቃል ኪዳን ገባላት ለገዳመ ዋሊ። አባታችን አቡነ ሳሙኤል በበዓታቸው ውስጥ ጸንተው ሲኖሩ ታህሣሥ 12 ቀን ያረፉ ሲሆን ዛሬ መስከረም 6 ግን ፍልሰተ አጽማቸው የተከናወነበት እለት ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ሰብልትንያ
በዚህችም ቀን ቅድስት ሰብልትንያ በከ*ሀዲ ንጉሥ ዲዮቀልጥያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ሞተች። ይችንም ቅድስት ዕድሜዋ ዘጠኝ ዓመት ሲሆን ከሀ*ድያን ያዙዋት እጆቿንና እግሮቿንም አሥረው ከሚነድ እሳት ውስጥ ጣሏት የክብር ንጉሥ በሆነ በእግዚአብሔርም ኃይል ከእሳት ዳነች።
ውኃን በተጠማች ጊዜ እግዚአብሔርን ለምናው ውኃን አፈለቀላትና ጠጣች ክብር ምስጉን የሆነ ጌታችንንም አመሰገነችው። ከዚህም በኋላ ነፍሷን በእግዚአብሔር እጅ አደራ ሰጥታ ራሷን ከእሳት ውስጥ ወረወረች ምስክርነቷንም ፈጸመች።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
ከዚህም በኃላ ሁለተኛ ያዙት ወስደውም ከሚነድ እሳት ውስጥ ጨመሩት ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አዳነው። ዳግመኛም ተነጣጥቀው እንዲበሉት አንበሶችን በላዩ ሰደዱ በእግዚአብሔርም ኃይል በአንበሳ ላይ ተቀመጠ።
ከዚህም በኃላ ብዙ አሠቃዩት ሕዋሳቶቹ እስቲለያዩና የሆድ ዕቃው እስቲፈስ ጎተቱት ተጋድሎውንና ምስክርነቱን በዚህ ፈጽሞ የሰማዕትነት አክሊልን በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አፄ_ልብነ_ድንግል
በዚህችም ቀን እግዚአብሔርን የሚወድ ሃይማኖቱ የቀና ደግ ጻድቅ የኢትዮጵያ ንጉሥ ልብነ ድንግል አረፈ።
እኒህ ንጉሥ ኢትዮዽያን ለዓመታት (ከ1500 እስከ 1532 ዓ.ም) ቢያስተዳድሩም 15ቱ ዓመት ያለቀው በስደት ነው። ከደጋጉ አፄ ናዖድና ንግሥት ወለተ ማርያም ተወልደው በሥርዓቱ አድገው ቢነግሡም በክፉ መካሪዎች ጠንቅዋይ ወደ ቤታቸው ገብቶ ሃገሪቱን ለመከራ ዳርጓታል።
ዛሬም ድረስ ጠባሳው ያለቀቀው የግራኝ ወረራ ለ15 ዓመታት ሃገሪቱን ያለ ካህንና ቤተ ክርስቲያን አስቀርቷት ነበር። ብዙ ክርስቲያኖችም ሰልመው ቀርተዋል። አፄ ልብነ ድንግል ግን ደብረ ዳሞ ገዳም ውስጥ ገብተው ንስሃ ጀመሩ አለቀሱ ተማለሉ።
እመቤታችን ተገልጣም "ይቅርታን በነፍስህ እንጂ በሥጋህ አታገኝም" አለቻቸው። እርሳቸውም ሱባኤውን ቀጥለው ስብሐተ ፍቁርን፣ መልክአ ኤዶምን የመሰሉ መጻሕፍትን ደርሰው በዚህች ቀን ዐርፈዋል። እኛ ክርስቲያኖችም እናከብራቸዋለን።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር መስከረም_5
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም አምስት በዚች ቀን #ቅድስት_ሶፊያ_ሰማዕት ከሁለት ልጆቿ ጋር በሰማዕትነት አረፈች፣ #አቡነ_አሮን_መንክራዊ እረፍት ነው፣ #ቅዱስ_ማማስ_ሰማዕት በሰማዕትነት አረፈ፣ ኢትዮጵያዊው ጻድቅ #አፄ_ልብነ_ድንግል እረፍቱ ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅድስት_ሶፊያ_ሰማዕት
መስከረም አምስት በዚች ቀን የከበረች ሶፊያ ከሁለት ልጆቿ አክሶስናና በርናባ ከሚባሉት ጋር በሰማዕትነት ሞተች ።
ዘመነ ሰማዕታት በሚል በሚታወቀው 3ኛው መቶ ክ/ዘመን ብዙ ቅዱሳት እናቶቻችን ስለ ፍቅረ ክርስቶስ አንገታቸውን ሰጥተዋል:: አንዳንዶቹ ደግሞ ሕይወታቸው እጅግ የሚያምር ነበር:: ከእነዚህ ቅዱሳት እናቶቻችን አንዷ ዛሬ የምናከብራት ሐጊያ ሶፊያ ናት::
በዚህ ስም ከሚጠሩት አንዷ ስትሆን በቀደመ ሕይወቷ ክርስቶስን አታውቅም ነበር:: ጣዖትን የሚያመልኩ ወላጆቿ አሳድገው አጋቧት:: ከትዳሯም 2 ቡሩካት ሴቶች ልጆች ወልዳለች:: ስማቸውም አክሶስናና በርናባ ይባላል:: ልጆቿ ልብ እያገኙ በሔዱ ጊዜ ቅድስት ሶፍያ ስለ እውነተኛው አምላክ ትመራመር ገባች::
በወቅቱ የነበሩ ብዙ ሃይማኖቶችን መዘነች:: ከክርስትና በቀር ግን ሌሎቹ ሚዛን እንደማይመቱም አስተዋለች:: "እውነኘተኛው አምላክ ሆይ! ምራኝ እርዳኝም" ስትል ጸለየች:: መድኃኔዓለም ለጠሩት አያሳፍርምና ፈጥኖ በጐውን ጐዳና አሳያት።
ድኅነት ለልጆቿም ይሆን ዘንድ ሁለቱንም ጠርታ ስለ ክርስትና አማከረቻቸው:: ደስ ብሏቸው ተቀበሏት:: እርሷም ጊዜ ሳታጠፋ ወደ ዻዻስ ሒዳ ማሕተመ ክርስትና: ሃብተ ውልድናን ትቀበል ዘንድ ከልጆቿ ጋር ተጠመቀች:: በቅድስናና ደስ በሚያሰኝ አኗኗርም እስከ መከራ ቀን ቆየች::
የመከራ ጊዜ ሲደርስም ልጆቿን ጠርታ "ስለ ክርስቶስ ፍቅር እንሙት" አለቻቸው:: ቡሩካቱ አክሶስናና በርናባም ደስ እያላቸው "እሺ" አሏት:: ወዲያውም በመኮንኑ ፊት ቀርበው ክርስቶስን ከመካድና ከስቃይ ሞት የትኛውን እንደሚመርጡ ቢጠየቁ እነርሱ መሞትን መረጡ:: ወደ እሥር ቤትም ከተቷቸው::
ቅድስት ሶፍያ 2 ልጆቿ ይጸኑላት ዘንድ አዘውትራ ገድለ ሰማዕታትን እና ክብራቸውን ትተርክላቸው ነበር:: በተለይ የታላቁዋን አንጌቤናይት (እመቤት) ሶፍያንና የ3 ልጆቿን (ዺስጢስ: አላዺስና አጋዺስ) ተጋድሎ እየነገረች ታጸናቸው ነበር።
ከእሥር በኋላ ግርፋት ታዞባቸው እናት ራቁቷን ስትገረፍ መልአክ ወርዶ ሲጋርዳት ልጆች በማየታቸው ደስ አላቸው:: ቅድስት ሐጊያ ሶፍያና 2 ልጆቿ እጅግ የበዛ ስቃይን ስለ ቀናች እምነት ተቀበሉ:: ምላስ እስከ መቆረጥም ደረሱ:: በመጨረሻ ግን በዚህች ቀን ተገድለው አክሊለ ሰማዕታትን ገንዘብ አደረጉ
የመከራ ዘመን ካለፈ በኋላ ታላቁ ንጉሥ ቅዱስ ቆስጠንጢኖስ የሁሉን ቅዱሳን ቤት ሠርቶ የእርሷን በመዘንጋቱ ለራሱ ባሰራው ቤተ መንግስት ላይ ተአምር ታይቷል። ለ3 ያህል ጊዜ ስሙን ሲያስቀርጽ መልአክ እየወረደ ይፍቀው የሶፍያንም ስም ይጽፈው ነበር።
በመጨረሻም ንጉሡ ልጁን እስከ መገበር ደርሶ ቤተ መንግስቱ የቅድስት ሶፍያና የ2 ልጆቿ ቤተ ክርስቲያን ለመሆን በቅቷል:: ምንም ለ3 ጊዜያት ያህል ሙሉ እድሳት ቢደረግለትም ዛሬ አሕዛብ የያዙትን ይህንን ቅርስ ንጉሡ የሠራው ከ1700 ዓመታት በፊት ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_አሮን_መንክራዊ
በዚህች ቀን አቡነ አሮን መንክራዊ ዕረፍታቸው ነው፡፡ አቡነ አሮን ወላጅ አባታቸው የላስታው ጻድቁ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ናቸው፡፡ እናታቸው አመተ ማርያም ይባላሉ፡፡ የላስታ ነገሥታት የዘር ሐረጋቸው ከንጉሥ ሰሎሞን ዘር ሲያያዝ የመጣ ነው፡፡
ከ10ኛው እስከ 13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን (920-1253 ዓ.ም ገደማ) በላስታ ቡግና ምድር የነገሡ የላስታ ቡግና ተወላጅ የሆኑ የኢትዮጵያ ቅዱሳን ነገሥታት የንግሥናቸው መጠሪያ ‹‹የዛጉዌ ሥርወ መንግሥት›› ወይም ‹‹የላስታ መንግሥት›› በመባል ይታወቃል፡፡ የንጉሥ ሰሎሞን ዘር የሆነው መራ ክርስቶስ 3 ልጆችን ወለደ፡፡ እነርሱም ጠንጠውድም፣ ግርማ ስዩምና ዣን ስዩም ናቸው፡፡ ጠንጠውድም ገብረ መስቀልን ወለደ፣ ገብረ መስቀልም አቡነ አሮንን ወለደ፣ ግርማ ስዩም ይምርሐነ ክርስቶስን ወለደ፣ ዣን ስዩም ደግሞ ገብረ ማርያምንና ላሊበላን ወለደ፡፡ ገብረ ማርያምም ነዓኲቶ ለአብን ወለደ፡፡ እነዚህ ቅዱሳን ነገሥታት እንደ መልከጼዴቅ (ዘፍ14፡18) ክህነትን ከንግሥና፣ ቅድስናን ከንጽሕና ጋር አንድ አድርገው በመያዝ እግዚአብሔርንም ሕዝብንም በቅድስናና በንጽሕና አገልግለው አልፈዋል፡፡
አቡነ አሮን ግን ገና በ7 ዓመታቸው ነው ዓለምን ፍጹም ንቀው በአቡነ በጸሎተ ሚካኤል እጅ የመነኮሱት፡፡ በ16 ዓመታቸውም ዋልድባ ገዳም ገብተዋል፡፡ ነሐሴ 5 ቀን ገና ሲወለዱ ሙት አስነሥተዋል፡፡ በሀገራችን እየተዘዋወሩ ወንጌልን ሲሰብኩ የሸዋው ንጉሥ አንኮበር ድረስ ጠርቷቸው ሲሔዱ አዋሽ ወንዝ ሞልቶባቸው አገኙት፡፡ ሲሻገሩም ዳዊታቸውን ወስደባቸው፡፡ ‹‹ልጆቼን አመነኮስክብኝ›› በሚል ሰበብ ንጉሡ 7 ዓመት በግዞት አስሮ አስቀመጣቸው፡፡ ነገር ግን ከ7 ዓመት በኋላ አቡነ አሮን ተመልሰው በአዋሽ ወንዝ ሲመጡ መልአክ መጣና ‹‹መቋሚያህን ወደ ወንዙ ላክ›› አላቸው፡፡ መቋሚያቸውንም ቢልኩ ከ7 ዓመት በፊት ወደ ወንዙ ገብቶባቸው የነበረውን ዳዊታቸውን ይዘው አወጡ፡፡ ዳዊቱም በውኃው አልራሰም ነበር፣ ይልቁንም አቧራውን አራግፈው ፈጣሪያቸውን አመስግነው ዳዊታቸውን ይዘው ሄደዋል፡፡ ያ ዳዊታቸው ዛሬም ድረስ በጋይንት አበርጉት ቅዱስ ሚካኤል ይገኛል፡፡
ሰሜን ወሎ መቄት ወረዳ ውስጥ የሚገኘው እጅግ አስደናቂ ገዳማቸው ፍልፍል ዋሻ ሲሆን ጣራው ክፍት ነው፣ ክፍት በሆነው ጣራ በኩል ፀሐይ ሲገጣ ስለሚያቃጥል ጥላ ይይዛሉ ነገር ግን የጻድቁ ግዝት ስላለበት ዝናብ ወደ መቅደሱ ፈጽሞ አይገባም፡፡ እጅግ አስደናቂ ነው፡፡ አቡነ አሮን በዋድላ ሜዳ አልፈው ሲሄዱ አንችም ሜዳ ላይ እንደ ኢያሱ ፀሐይን በቃላቸው ገዝተው አቁመዋታል፡፡
ከታች ጋይንት ተነሥተው መንገድ ሲሄዱ በሰንበት ቀን በሬ ጠምዶ ሲያርስ የነበረን ገበሬ ‹‹ለምን በሰንበት ታርሳለህ?›› ቢሉት ‹‹ምቀኛ መነኩሴ›› ብሎ በጅራፉ ቢገርፋቸው በሬዎቹ ግን ፈጽሞ አልንቀሳቀስ ብለው ቆመዋል፡፡ በዚህ የተናደደው ገበሬም አቡነ አሮንን መሬት ላይ ጥሎ ገረፋቸው፡፡ እሳቸውም ተነሥተው ሲሄዱ ዛፎች ተነቅለው እየተከተሏቸው፣ ቃልም አውጥተው በሰው አንደበት አመስግነዋቸዋል።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ማማስ_በሰማዕት
በዚህችም ቀን ቅዱስ ማማስ በሰማዕትነት ሞተ የአባቱ ስም ቴዎዶስዮስ የእናቱም ያኖች ናቸው። በንጉሥ ዑልያኖስ ዘመንም ስለ ሃይማኖታቸው ይዘው አሠሩአቸው በእሥር ቤትም ሳሉ አረፉ።
አንዲት ክርስቲያናዊት ሴት መጥታ ይህን ሕፃን ወስዳ እንደ ልጅዋ አድርጋ አሳደገችው። ስሙንም ማማስ ብላ ሰየመችው ትርጓሜውም። የሙት ልጅ ማለት ነው አባትና እናት የለውምና።
ዐሥራ ስምንት ዓመትም በሆነው ጊዜ ወደ ከሀዲው ገዢ ሒደው ክርስቲያን ነው ብለው ወነጀሉት ይዘውም በበትሮች ደበደቡት በአንገቱም የሚከብድ ሸክም ታላቅ የዓረር ደንጊያ አንጠልጥለው ከባሕር ውስጥ ጣሉት። ክብር ይግባውና በእግዚአብሔር ኃይል ከባሕር ስጥመት ዳነ ወጥቶም በዋሻ ውስጥ ተሠውሮ ከጎሽ ወተትን እየተመገበ ተቀመጠ።
የሐዘን መግለጫ
የእህታችን ቤተልሔም ፀጋዬ አክስት ስላረፉ ነገ ሐሙስ በ05/01/2015 በደብረ አሚን ተክለ ሃይማኖት ቤ/ክ ከቀኑ 9:00 ሰዓት የቀብር ስነ ስርዓታቸው ስለሚፈጸም የቻልን እንድረስ።
ታላቁ ነቢይ ኢያሱ ግን በተወለደ በ120 ዓመቱ ከግብጽ በወጡ በ80ኛ ዓመት መስከረም 4 ቀን በእዚች ዕለት በወገኖቹ መካከል ዐርፎ በያዕቆብ መቃብር ተቀበረ:: እሥራኤልም ለሠላሳ ቀናት አለቀሱለት::
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_መቃርስ_ሊቀ_ዻዻሳት
ዳግመኛም በዚህች ቀን ቅዱስ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ መቃርስ አረፈ። እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ከቍጥራቸው ውስጥ ነው።
ይህም አባት ከታናሽነቱ ጀምሮ በገድል የተጠመደ ሆነ የምንኲስናንም ልብስ ሊለብስ ወዶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ወጣ። በዚያም በመጀመሪያው አባት በአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መነኰሰ በምንኲስና ያለውንም ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ።
እርሱም ሁልጊዜ መጻሕፍትን የሚያነብና ትርጓሜያቸውንም የሚያስረዳ ሁኗልና በትሩፋት ስራ ከፍ ከፍ ባለ ጊዜ ቅስና ተሾመ። ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤልም በአረፈ ጊዜ ኤጲስቆጶሳቱ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔዱ።
ከእርሳቸውም ጋር ሃይማኖታቸው የቀና ብዙዎች አዋቂዎች ካህናት ነበሩ በአስቄጥስ ገዳም ከሚኖሩ ከታላላቅ መነኰሳትም ጋራ ስብሰባ አድርገው ለዚች ለከበረች ሹመት ስለሚገባው ሰው እየመረመሩ ብዙ ቀኖች ተቀመጡ።
ከዚህም በኋላ የተሻለና ለዚች ለከበረች ሹመት የሚገባ ይህን አባ መቃርስን አግኝተው ሊቀ ጵጵስና ሊሾሙት ሁሉም በአንድ ምክር ተስማው። ስለ ትሩፋቱና ስለ ተጋድሎው በአስቄጥስ ገዳም የሚኖሩ ብዙ መነኰሳት ምስክሮች ሁነዋልና ይዘውትም ሊሔዱ ያለ ፍቃዱ ይዘው አሰሩት እርሱ ግን እንዲህ እያለ ይጮህ ነበር።
እኔ ለዚች ለከበረች ሹመት የማልገባ ነኝ እናቴ ሁለት ባሎችን አግብታ ስለነበር ይህንንም ያለው እንዲተዉት እንጂ እናቱ ግን በአንድ ባል ብቻ የኖረች ሌላ የማታውቅ ንጽሕት እንደሆነች ስለርሷ ብዙዎች ምስክሮች ሁነዋልና። ስለዚህ እሊቀ የተናገረውን ምክንያት አልተቀበሉትም።
ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ወስደው ሊቀ ጵጵስና ሾሙት ከዚያም ወደ ምስር አውጥተው በመዓልቃ በሚገኘው አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሹመቱ ደብዳቤ በዮናኒ በቅብጥ በአረብ ቋንቋ ተነበበች።
ከዚህም በኋላ በሹመቱ ወራት በጎ ስራ ትሩፋትን ተጋድሎውን አብዝቶ የሚሰራ ሆነ ። ሁል ጊዜም ለህዝቡ እግዚአብሔርን እንዲፈሩ ያስተምራቸዋል ስለ ነፍሳቸውም ድኀነት ይገሥጻቸው ነበር።
በሹመቱ ወራትም ከራሱ ከሚገባው ከግብሩ ለቤተ ክርስቲያን ይሰጣል ለድኆችና ለችግረኞችም ይመጸውታል እንጂ ከቤተ ክርስቲያን ገንዘብ ምንም ምን አልወሰደም። በሹመቱም ሃያ ሰባት ዓመት ኖረ እግዚአብሔርንም አገልግሎ ደስ አሰኝቶ በሰላም በፍቅር ሳለ አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ለዘላለሙ ከእኛ ጋር ትኑር አሜን።https://t.me/finotebirhan12
"#አቡቀለምሲስ" ተባለ፣ ይህም በግሪክኛ #ባለራእይ ማለት ነው፡፡ የጌታችንን መከራ መስቀሉን እያስታወሰ 70 ዘመን ሙሉ እያለቀሰ ስለኖረና ፊቱም በሀዘን ስለተቋጠረ "#ቁጹረ_ገጽ" ተብሏል፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አቡነ_ሙሴ_ዘድባ
በዚህች ቀን የድባው አቡነ ሙሴ እረፍታቸው ነው። የትውልድ አገራቸው እስራኤል ልዩ ቦታው ቃና ዘገሊላ ነው። ጽንሰታቸውን ቅዱስ ሩፋኤል መጋቢት 8 ቀን ሲያበስር ልደታቸውን ደግሞ ቅዱስ ገብርኤል ታኅሣሥ 8 ቀን የመወለዳቸውን ብሥራት ተናግሯል፡፡ ሲወለዱ ሚካኤል ወገብርኤል በሰው አምሳል ተገልጠው "የእግዚአብሔር ሰው ሙሴ" ብለው ስም አወጡላቸው፡፡
በተወለዱም በ40ኛ ቀናቸው ከተጠመቁ በኋላ ቅዱስ ሚካኤል አቅፎ ይዟቸው ጌታችን በቅዱሳን እጆቹ አቁርቧቸዋል፡፡ በእሳቸውም ምክንያት በዚያች ዕለት በቤተ ክርስቲያን የነበሩት ሰዎች ሁሉ ክቡራን በሆኑ በጌታችን እጆች ቆርበዋል፡፡ የአቡነ ሙሴ አባታቸው ዮስጦስ ለሐዋርያው ናትናኤል አጎቱ ነው፡፡ እናታቸው ጵርስቅላ ጌታችን በሠርግ ቤት ተገኝቶ ውኃውን ወደ ወይን የለወጠለት የዶኪማስ ልጅ ናት፡፡
ጌታችን ወደ ዶኪማስ ቤት ሠርግ ተጠርቶ የሄደው ዶኪማስ ናትናኤልን ‹‹ሠርጌን እንዲባርክልኝ ጌታ ኢየሱስን ከእናቱ ጋር ጥራልኝ›› ብሎት ነው፡፡ ጌታችን በስብከቱ ‹‹ሕፃናትን ወደ እኔ ይመጡ ዘንድ አትከልሏቸው›› ብሎ ብሎ ካቀፋቸውና
ካስተማረባቸው ሕፃናት አንዱ ይኽ አቡነ ሙሴ ናቸው፡፡ ጻድቁ ዋሻዎችን እየፈለፈሉ የቅዱሳን ሐዋርያትን ዐፅም በክብር ያስቀምጡ ነበር፡፡ የተሠወሩ አብያተ ክርስቲያናትን በማነጽ ወንጌልን በማስተማር ብዙ መከራ የተቀበሉ አባት ናቸው፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ በግብፅ "ንጉሥ አንስጣስዮስ" ተብለው 40 ዓመት በንግሥና እና በድንግልና ኖረዋል፡፡
ከዚህም በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ በመልአክም ምክር ዮናኒ የተባለውን ሌላ ሰው አንግሠው ወደ አስቄጥስ ገዳም ገብተው መነኮሱ፡፡ በገዳሙም በታላቅ ተጋድሎ ከኖሩ በኋላ የመጀመሪያው የኢትዮጵያ የእኛ ጳጳስ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ሲያርፉ በቅዱስ አትናቴዎስ ተሹመው 2ኛው የኢትዮጵያ ጳጳስ ሆነው ‹‹አቡነ ሰላማ ካልዕ›› ተብለው ተሾመው ወደ አገራችን መጡ፡፡ ከመሾማቸው በፊት አባቶቻችን አቡነ አትናቴዎስን ‹‹ጳጳስ ይላኩልን›› ብለው መልእክት ሲልኩባቸው አቡነ አትናቴዎስም ወደ አስቄጥስ ገዳም በመሄድ እግዚአብሔርን በጸሎት ቢጠይቁት የታዘዘ መልአክ መጥቶ ‹‹የእግዚአብሔር ሰው ሙሴን ላክላቸው›› አላቸው፡፡ መነኮሳቱም ሁሉ እንዲሁ አሉ፡፡ ከዚህም በኋላ ሲሾሙ ሚካኤልና ገብርኤል በወርቅ ወንበር ላይ አስቀምጠዋቸው ‹‹ይገባዋል ይገባዋል›› ብለው ቅብአ ክህነት ቀብተዋቸዋል (ጵጵስና ሾመዋቸዋል፡፡) አቡነ ሙሴም ከተሾሙ በኋላ 14000 መነኮሳትን አስከትለው ወደ ቅድስት አገራችን መጡ፡፡ አቡነ ሙሴ ንግሥናቸውን ትተው ወደ ኢትዮጵያ መተው 16 ፍልፍል ቤተመቅደሶችን የሠሩ ሲሆን 8ቱ የተሰወሩ ናቸው፡፡
በገዳማቸው በቅድስቱ ውስጥ ጥልቀቱ የማይታወቅ እጅግ ጥልቅ የሆነ ጉድጓድ አለ፡፡ በውስጡም ስውራኑ አብያተ ክርስቲያናት ይገኙበታል፡፡ ከአንድ ወጥ ድንጋይ የተቀረጸውና ፍልፍል የሆነው የገዳማቸው የቤተልሔሙ ስፋት ሜትር ከሃያ ሲሆን ጣራው እንደ አቡነ አሮን ክፍት ሆኖ ሳለ ዝናብ ግን አይገባበትም፡፡ ዝናብ የማያስገባው የቀዳዳው ስፋት አንድ ሜትር በአንድ ሜትር ነው፡፡ ጻድቁ በሀገራችንም ዕፁብ ድንቅ የሆኑ ብዙ ፍልፍል አብያተ ክርስቲያናትን በማነጽና ወንጌልን በማስተማር ብዙ ደክመዋል፡፡ በተለይም በዋናነት የሚታወቁት በሰሜን ወሎ አውራጃ ወልድያ ወረዳ መቄት ልዩ ቦታው ገረገራ የሚገኘው ‹‹አዲስ አንባ ዋሻ መድኃኔዓለም›› እና መጀመሪያ እንደመጡ ያረፉባት ‹‹ድባ ማርያም›› ይጠቀሳሉ፡፡
ይህችውም ድባ ማርያም ገዳም ታላቁ አባት እስትንፋሰ ክርስቶስ የመነኮሱባት ናት፡፡ ጻድቁ አቡነ ሙሴ መስከረም 4 ቀን ጌታችን ቃልኪዳን ሲገባላቸው እነዚህን ሁለት ገዳማቸውን ‹‹እንደ አስቄጥስ ገዳም እንደ አቡነ እንጦንስ ማኅበር ይሁኑልህ›› ብሏቸዋል፡፡ በገዳማቸው ከሚኖሩት ቅዱሳን ውስጥ 400 ወንዶች መነኮሳትና 200 ሴቶች መነኮሳያት እንደተሰወሩ መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል፡፡
ጻድቁ ሌላው ለየት የሚያደርጋቸው ነገር ቢኖር ገና በእናቷ ማኅፀን ሳትፀነስ የቅድስት አርሴማን ጽላት ያሠሩላት መሆናቸው ነው፡፡ ቁመቱ 2 ሜትር ከ70 የሆነ ግሩም ቤተ መቅደስም ፈልፍለው አንጸውላታል፡፡ ጌታችንም የሰማዕቷን ጽናትና ረድኤት ከቦታው እንደማይለይባቸው ቃል ገብቶላቸዋል፡፡ በቃል ኪዳናቸው የታመኑትን ልጆቻቸውን መተትና መርዝ አይጎዳቸውም፡፡ ይህም ጌታችን የሰጣቸው ልዩ ቃልኪዳናቸው ነው፡፡ ጻድቁ እንደ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ 12 ክንፍ የተሰጣቸው ታላቅ የምሕረት አባት ናቸው፡፡
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ነቢይ_ኢያሱ_ወልደ_ነዌ
ኢያሱ ማለት የቃሉ ትርጉም መድኃኒት ማለት ነው፡፡ ኢያሱ መባሉ ስለሁለት ነገር ነው አሜሊቃዊያን ድል አድርጎ እስራኤልን ምድረ ርስት እንዲወርሱ አድርጎልና ሁለተኛው ኢያሱ ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ እንዲሆን አስቀድሞ ጌታ ያውቃልና ይህም ኢያሱ አሕዛብን ድል አድርጎ ምድረ ርስት እንዳስገባቸው የሁላችን ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ዲያቢሎስን ድል አድርጎ መንግስቱን አውርሶናልና ኢያሱ በጌታችን ይመሰላል፡፡
ኢያሱ ነቢይ የተወለደው በምድረ ግብጽ በባርነት ከነበሩ እሥራኤላውያን ሲሆን የቀደመ ስሙ አውሴ ይባላል:: ዘመኑ እግዚአብሔር ሕዝቡን ከ215 ዓመታት ባርነት ሊያወጣ የተቃረበበት ነውናሙሴ ነቢይ ከምድያም ሲመለስ ከመረጣቸው ተከታዮቹ ዋነኛው ኢያሱ ነበር:: እሥራኤል ከባርነት ሲወጡ ሙሴ 80 ዓመቱ ኢያሱ ደግሞ 40 ዓመቱ ነበር። ሕዝቡ ልበ ደንዳና አልታዘዝ ባይ ነበርና ለአርባ ቀናት ብቻ የታሠበላቸውን መንገድ አርባ ዓመታት እንዲሆን አደረጉት:: በዚህ ጊዜ ኢያሱ ከመምህሩ ከሙሴና ከሕዝቡ አልተለየም::
ሊቀ ነቢያት ሙሴ ደብረ ናባው ላይ ባረፈ ጊዜ ሕዝቡን ካህናቱንና ታቦተ ጽዮንን ተረከበ:: በዚህ ወቅትም እድሜው ሠማንያ ዓመት ነበር፡፡ እግዚአብሔርም በእስራኤል ላይ ሾመው፡፡ ሕዝቡንም በትጋት ያገለግል ነበር፡፡ በድንቅ ተዓምራት ዮርዳኖስን ከፍሎ አሻገረ የኢያሪኮን ቅጥር አፈረሰ ጠላቶቹን ድል ነስቶ ምድረ ርስት ከነአንን በእግዚአብሔር በኢያሱ መሪነት እንድወርሱ አድርጎል፡፡
ታላቁ ነቢይ ኢያሱ ግን በተወለደ በ120 ዓመቱ መስከረም 3 ቀን በእዚች ዕለት በወገኖቹ መካከል ዐርፎ በያዕቆብ መቃብር ተቀበረ:: እሥራኤልም ለሠላሳ ቀናት አለቀሱለት:: በረከቱ ይደርብን እኛንም በቅዱሱ ምልጃ ይማረን፡፡ነቢያት_ሙሴ ከምድያም ሲመለስ ከመረጣቸው ተከታዮቹ ዋነኛው ኢያሱ ነበር:: እሥራኤል ከባርነት ሲወጡ ሙሴ 80 ዓመቱ ኢያሱ ደግሞ 40 ዓመቱ ነበር::ሕዝቡ ልበ ደንዳና አልታዘዝ ባይ ነበርና ለአርባ ቀናት ብቻ የታሠበላቸውን መንገድ አርባ ዓመታት እንዲሆን አደረጉት:: በዚህ ጊዜ ኢያሱ ከመምህሩ ከሙሴና ከሕዝቡ አልተለየም::
ሊቀ ነቢያት ሙሴ ደብረ ናባው ላይ ባረፈ ጊዜ ሕዝቡን ካህናቱንና ታቦተ ጽዮንን ተረከበ:: በዚህ ወቅትም እድሜው ሠማንያ ዓመት ነበር፡፡ እግዚአብሔርም በእስራኤል ላይ ሾመው፡፡ ሕዝቡንም በትጋት ያገለግል ነበር፡፡ በድንቅ ተዓምራት ዮርዳኖስን ከፍሎ አሻገረ የኢያሪኮን ቅጥር አፈረሰ ጠላቶቹን ድል ነስቶ ምድረ ርስት ከነአንን በእግዚአብሔር በኢያሱ መሪነት እንድወርሱ አድርጎል፡፡
🔴#ስንክሳር መስከረም4
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም አራት በዚህች ቀን #ወንጌላዊው_ቅዱስ_ዮሐንስ ልደቱ ነው፣ የድባው አቡነ ሙሴ እረፍታቸው ነው፣ #ነቢዩ_ኢያሱ_ወልደ_ነዌ አረፈ፣ #አባ_መቃርስ_ሊቀ_ዻዻሳት አረፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዮሐንስ_ወንጌላዊ
መስከረም አራት በዚህች ዕለት ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ከእናቱ ማርያም ባውፍልያ ከአባቱ ዘበዴዎስ የተወለደበት ዕለት እንደሆነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌልን ለመስበክ ዕጣ የደረሰው እስያ ስለነበር ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን አስከትሎ ሄደ፡፡ ይኽችውም ኤፌሶን በጥንቱ በታናሽ እስያ በዛሬው የቱርክ ግዛት ውስጥ ከተማ ናት፡፡ ዛሬ ኢያዞሎክ ተብላ የጥንት ታሪኳ ጠፍቷል፡፡ አስቀድሞ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን ሰብኮባታል፡፡ ደቀ መዝሙሩን ቅዱስ ጢሞቴዎስንም በከተማዋ ላይ ኤጲስቆጶስ አድርጎ ሾሞት ነበር፡፡ እርሱም በግፍ እስከተገደለበት ጊዜ ድረስ ቅዱስ ዮሐንስን እየረዳው በከተማዋ ብዙ አገልግሏል፡፡ በኋላ ግን በግፍ ገድለውታል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ወደ ኤፌሶን ለመሄድ በመርከብ ሲሳፈር መርከቡ በማዕበል ተሰበረ፡፡ ደቀ መዝሙሩን አብሮኮሮስን መዕበሉ ወደ አንዲት ደሴት አደረሰው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ግን በመርከቡ ስባሪ ተንጠልጥሎ በባሕሩ ማዕበል መካከል 40 ቀንና 40 ሌሊት ከኖረ በኋላ ማዕበሉ ተፍቶ አብሮኮሮስ ካለበት ደሴት አደረሰውና ተያይዘው ኤፌሶን ከተማ ገቡ፡፡ የከተማይቱም ሰዎች እጅግ ክፉዎች ስለነበሩ መጀመሪያ ላይ ቅዱስ ወንጌልን መስበክ አልቻሉም ነበር፡፡ እነርሱም እጅግ ክፉዎች መሆናቸውን ስላወቀ ቅዱስ ዮሐንስ ገና ዕጣው ሲደርሰው በሀዘን አልቅሶ ነበር፡፡ አሁንም ከተማው በገቡ ጊዜ ቅዱስ ዮሐንስ ምክንያት በመፍጠር ሮምና ለምትባል ሴት የውሽባ ቤቷ እሳት አንዳጅ ሆኖ አብሮኮሮስም ዕቃ አጣቢ ሆነው ተቀጠሩ፡፡ የቀጠረቻቸው ሴትም እጅግ ታሠቃያቸው ጀመር፡፡ ባሮቿ እንደሆኑ ተስማምተው ስለጻፉላት ትደበድባቸውም ነበር፡፡
እነርሱም በታላቅ ጉስቁልና ውስጥ እየኖሩ እያለ በአንዲት ዕለት የአገረ ገዥው ልጅ ለመታጠብ ወደ ውሽባው ቤት ገባ፡፡ በውሽባ ቤቱም የሰይጣን ኃይል ስለነበረበት የመኰንኑን ልጅ አንቆ ገደለው፡፡ የአገሪቱም ሰዎች ሁሉ ለሞተው የመኰንን ልጅ ሊያለቅሱ ሲሰበሰቡ ቅዱስ ዮሐንስም አብሮ ቆሞ ሲመለከት ሮምና መጥታ "በጌታዬ ልጅ ሞት ልትደሰት መጣህን" እያለች ረገመችው፡፡ እርሱም "አይዞሽ አትዘኚ" አላትና ወደ ሞተው ልጅ ቀርቦ በመስቀል ምልክት ካማተበበት በኋላ በፊቱ እፍ አለበት፡፡ የሞተውም ልጅ ድኖ ተነሣ፡፡ የሀገሪቱም ሰዎች እጅግ ደነገጡ፡፡ ሮምናም ደንግጣ "እግዚአብሔር የሚሉት አምላክ አንተ ነህን" ብላ ጠየቀችው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም "በፍጹም እኔ አምላክ አይደለሁም፣ እኔ የእርሱ አገልጋዩና ሐዋርያው ነኝ እንጂ" አላት፡፡ ሮምናም ስለበደለቻቸው በደል ሁሉ መሪር ዕንባን እያለቀሰች ይቅር እንዲሏት ለመነቻቸው፡፡ እነርሱም አረጋጉዋት፡፡ ከሕዝቡም ውስጥ ብዙዎቹ በጌታችን አመኑ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ሌሎች ብዙ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን እያደረገ ወንጌልን እየሰበከ ከጣዖት አገልጋዮች በቀር ሁሉንም አሳምኖ አጠመቃቸው፡፡ አገልጋዮችን ኤጲስቆጶሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ከሾመላቸው በኋላ ወደ ሌሎች አቅራቢያ አገሮች ሄደ፡፡
በመጨረሻም በከሃዲውና በጨካኙ በድምጥያኖስ ዘመን በጣዖት አምላኪዎች ተከሶ ለፍርድ ቀረበ፡፡ በፈላ ውኃ ካሠቃዩት በኋለ በፍጥሞ ደሴት አጋዙት፡፡ በዚያም ሳለ ራእዩን ተመልክቶ ጻፈው፡፡ ድምጥያኖስም ከተገደለ በኋላ ከግዞቱ ተመልሶ ሦስቱን መልእክታቱንና ቅዱስ ወንጌሉን ጽፏል፡፡ ጌታችንም አስቀድሞ ሞትን እንደማይቀምስ ለዮሐንስ ቃል ገብቶለት ነበርና (ዮሐ 21፡22) ጥር 4 ቀን እንደ ኤልያስና ሄኖክ ሞትን እንዳያይ ወደ ብሔረ ሕያዋን ወስዶታል።
ጌታችን ለዮሐንስ ያልነገረው እርሱም ያላስተማረው ምሥጢር የለም፡፡ ወንጌሉን መጻፍ ሲጀምር "በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ…" ብሎ የጌታችን ነገር ተመራምሮ ለመድረስ ሲል በመሀል መልአኩን በዮርዳኖስ ባሕር ላይ ሲሄድ አገኘው፡፡ መልአኩም የዮርዳኖስን ባሕር በእንቁላል ቅርፊት እየጨለፈ ወደ ውጭ ሲያፈስ ተመለከተው፡፡ ዮሐንስም ተገርሞ "ምን ማድረግህ ነው" አለው፡፡ መልአኩም "የዮርዳኖስን ባሕር ቀድቼ እየደፋሁ ልጨርሰው ነው" ሲለው ዮሐንስም መልሶ "ታዲያ በእንቁላል ስባሪ ነውን?" አለው፡፡ መልአኩም "አዎን" አለው፡፡ ዮሐንስም "በከንቱ ደከምክ" አለው፡፡ ይህን ጊዜ መልአኩም መልሶ "አንተስ እንጂ ደግሞ የአምላክን መገኘት፣ አኗኗሩንም ተመራምረህ በጥበብ ለማግኘት ብለህ 'በመጀመሪያ ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ..' ብለህ ጀምረህ የለምን? አንተ ጌታን ተመራምረህ ካገኘህና ከደረስክበት እኔም የዮርዳኖስን ወንዝ በዚህ እንቁላል ቅርፊት ቀድቼ እጨርሰዋለሁ" አለው፡፡ ዮሐንስም ይህን ጊዜ ደንግጦ ዝቅ ብሎ "ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ…" ብሎ ሀሳቡን ለወጠና ሌላ ታሪክ ቀጠለ፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ጌታችንን እስከ እግረ መስቀሉ ድረስ በመከተሉ ክርስቲያኖችን ሁሉ ወክሎ እመቤታችንን በአደራ የተቀበለ እርሱም ለመቤታችን በአደራ የተሰጠ ሲሆን እመቤታችንን ከወሰዳት በኋላ ለ16 ዓመት እየተንከባከበ ጠብቋታል፡፡ እናቱም በሕፃንነቱ ስለሞተች እመቤታችን ናት እየተንከባከበች ያሳደገችው፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በመልኩም ከጌታችን ጋር ይመሳል ነበር፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ሥዕል የመሳል ተሰጥኦም ነበረው፡፡ ጌታችን በተሰቀለበት ዘመን የነበረው ጢባርዮስ ቄሳር ልጁ በሽተኛ ነበር፡፡ የጌታችንን የማዳን ሥራ እየሰማ እነ ጲላጦስም ስለጌታችን የሚጽፉለትን ይሰማ ስለነበር ልጁን ከጌታችን መቃብር ላይ እንዲያኖሩለት ላከው፡፡ ልጁም ፈጥኖ ተፈወሰለት፡፡ ጢባርዮስ ቄሳርም በልጁ መዳን ምክንያት የጌታችንን ውለታ ማስቀመጥ ፈልጎ የጌታችንን ሥዕሉን የሚሥልለትን ሲያጠያይቅ ዮሐንስን አገናኙት፡፡ ዮሐንስም ጌታችንን ልክ በዕለተ ዓርብ እንደተሰቀለ አድርጎ በመሣል ለጢባርዮስ ቄሳር ሰጠው፡፡ ሲሥለውም በመጀመሪያ ጌታችንን ልክ እንደተሰቀለ አድርጎ ራቁቱን ነበር የሳለው፡፡ ዮሐንስ የሳለው የጌታችን ሥዕልም አፍ አውጥቶ "በመጀመሪያ አይሁድ በኢየሩሳሌም ራቁቴን ሰቀሉኝ፣ አሁን ደግሞ አንተ ድጋሚ በሮም ራቁቴን ትሰቅለኝን?" ብሎ ተናገረው፡፡ ዮሐንስም እጅግ ደንግጦ "እንዴት አድርጌ ልሳልህ?" ብሎ የሳለውን ሥዕል ቢጠይቀው ሥዕሉም "ከለሜዳ አልብሰህ ሳለኝ" አለው፡፡ ዮሐንስም እንዳለው ከለሜዳ አልብሶ ከሳለው በኋላ ሥዕሉን ትኩር ብሎ ተመልክቶ ቢስመው ከንፈሩ አንድ ቀን ተኩል ያህል ተጣብቆ ቆይቷል፡፡ ዛሬም ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን የምትጠቀምባቸውን የጌታችንን ስነ ስቅለት የሚያሳዩ ሥዕሎች መገኛቸው ይህ ወንጌላዊው ዮሐንስ የሳለው ሥዕል ነው፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በተለያዩ ስሞች ይጠራል፦
በሕይወቱና በኑሮው ሁሉ ጌታችንን ለመምሰል ይጥር ነበርና ጌታችንም እጅግ ይወደው ስለነበር "#ፍቁረ_እግዚእ" ተባለ፣ የታላቁ ያዕቆብ ታናሽ ወንድም ስለሆነና አባቱም ዘብድዮስ ስለሚባል "#ዮሐንስ_ወልደ_ዘብድዮስ" ተባለ፣ ለጌታችን ባለው ቅናትና ከወንድሙ ጋር ሆነው ባሳዩት የኃይል ሥራ እንዲሁም የጌታችንን አምላክነት በመግለጡ "#ወልደ_ነጎድጓድ" ተብሏል፡፡ ነገረ መለኮትን ከሌሎቹ በበለጠ ሁኔታ አስፍቶና አምልቶ በማስተማሩ "#ነባቤ_መነኮት ወይም #ታኦሎጎስ" ተብሏል። ኃላፊውንና መጻዒውን ጊዜ በራእዩ ስለገለጠ
ከቅድስናው የተነሣ ከቦታ ቦታ የሚንቀሳቀሰው በአንበሳ ላይ ተጭኖ ነው፡፡ ተአምራትን በማድረግና ወንጌልን በማስተማር በጾም ጸሎት አብዝቶ የደከመ ሲሆን ስለ ሀገራችን ኢትዮጵያ ሌት ተቀን በጸሎት ይተጋ የነበረ ታላቅ አባት ነው፡፡ አቡነ አንበስ ትውልዱ ትግራይ አድዋ በእንጭጮ ወረዳ ነው፡፡ በስሙ ትግራይ አድዋ "እንጭጮ አቡነ አንበስ ገዳም" እና በትግራይ ሽሬ ሁለት ትላልቅ ገዳማት አሉት፡፡ ቅዱስ ያሬድ በድርሰቱ ደጋግሞ የጠቀሳቸው ሲሆን የያሬድንም የድርሰቱን የአቋቋም ሥርዓት ያመጡት አቡነ አንበስ ናቸው፡፡
አቡነ አንበስ በአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና በአቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ ጊዜ የነበሩ ሲሆን እሳቸውንም አንበሶች ያገለግሏቸው ነበር፡፡ ጻድቁ አቡነ አንበስ ከአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጋር የተገናኘ ትልቅ ታሪክ አላቸው፡፡ የላዕላይ ግብጹ አባ ብንያም፣ በአቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ እና የሐዘሎው አቡነ አንበስ እነዚህ 3ቱ ቅዱሳን ከየአሉበት በአንበሳቸው ተጭነው ዝቋላ አቡዬ ዘንድ እንደደረሱ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንበሶች የ3ቱንም ቅዱሳን አንበሶች ዋጡዋቸው፣ አቡዬም በዚህ አዝነው ከበዓታቸው ወጥተው አንበሶቻቸውን ‹ትፉ› ብለው የበሉአቸውን አንበሶቻቸውን አስተፍተዋቸው ለ3ቱም ቅዱሳን የተበሉባቸውን አንበሶቻቸውን መልሰውላቸዋል፡፡ ይኸውም የሆነው እኝዲህ ነው፡- አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ በዝቋላ 7ቱ ሊቃነ መላእክት እየረዷቸው 70 ሺህ እልፍ አጋንንትን በእሳት ሰይፍ ፈጅተው ካጠፏቸው በኋላ ወደ ምድረ ከብድ ተመለሱ፡፡ ከዚህም በኀላ መንፈስ ቅዱስ የጠራቸው ሦስቱ ቅዱሳን አቡነ ሳሙኤል ዘዋልድባ አቡነ አንበስ ዘሐዘሎ እና የላዕላይ ግብጹ አቡነ ብንያም በአንበሶቻቸው ሆነው ወደ ጻድቁ አባት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ዘንድ ምድረ ከብድ ገዳም መጡ፡፡
አባታችን ግን ስለተሰወራቸው እስከ 7 ቀን ድረስ በምህላ ሰነበቱ፡፡ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንበሶችም መጥተው የ3ቱን ቅዱሳን አንበሶች በልተውባቸው ተሰወሩ፡፡ 3ቱም ቅዱሳን ፈጽመው ደነገጡ፡፡ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስም የቅዱሳኑን ሀዘንና ድንጋጤ ተመልክተው በታላቅና በሚያስፈራ ግርማ ሆነው ስልሳ ነብሮችንና ስልሳ አንበሶችን አስከትለው ተገለጡላቸው፡፡ ቅዱሳኑም ከአቡነ ገብረ መንፈስቅዱስ ግርማ የተነሣ ስለደነገጡ እንዳይፈሩም አረጋጉአቸው፡፡
ከዚህም በኃላ አባታችን "በምን ምክንያት ወደዚህ ገዳም ወደ እኔ መጣችሁ?" አሏቸው፡፡ ሦስቱ ቅዱሳን እንዲህ አሉ፡- "ጸሎትህ ቅድስት እንደሆነች ባወቅን ጊዜ ወደ አንተ መጣን፤ አንተ በሁሉ ርእሰ ባሕታውያን ነህና የእግዚአብሔርን ሥራ ትነግረን ዘንድ መጣን፤ ባላገኘንህም ጊዜ እስከ 7ቀን አለቀስን" አሉት፡፡
ዳግመኛም "አንበሶችህ መጥተው አንበሶቻችንን ደማቸውን ጠጡ ቆዳቸውንም በጥፍራቸው በጣጠሱ" ብለው ነገሯቸው፡፡ አባታችንም ይህንን ሲሰሙ አንበሶቻቸውን "እስከ ዕለቴ ሞቴ ድረስ በእግሬ ከረገጥኩት ትቢያ በቀር ምንም እንዳትበሉ ታዛችሁ የለምን? እግዚአብሔር ያላዘዛችሁትን ለምን በላችሁ? በሉ አሁንም የበላችሁትን ትፉ" አላቸው፡፡ እነዚያም አንበሶች አፋቸውን ከፍተው አንዳች ሳያስቀሩ አጥንታቸውን ሥጋቸውን በሙሉ ተፉአቸው፡፡ ጻዲቁ አባታችንም ወደ ምሥራቅ ተሠልሰው እግዚአብሔርን ከለመኑ በኃላ በአንበሶቹ ሥጋ ላይ ባረኩና "በኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል ተነሡ" አሏቸው፡፡ አንበሶቹም እንደ ዐይን ፈጥነው ተነሥተው እንደ ቀድሞው ሆኑ፡፡
ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ለዘላለሙ ከእኛ ጋር ትኑር አሜን።https://t.me/finotebirhan12
🔴#ስንክሳር መስከረም_3
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ሦስት በዚች ቀን #ሊቀ_ጳጳስ_አባ_ዲዮናስዮስ የተሾመበት፣ #አባ_ሙሴ_ዘገዳመ_ሲሐት አረፈ፣ #አባ_አንበስ_ኢትዮጵያዊ ዕረፍታቸው ነው
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_ዲዮናስዮስ
መስከረም ሦስት በዚች ቀን የከበረ አባት ሊቀ ጳጳሳት አባ ዲዮናስዮስ ከተሾመ በሁለተኛው ዓመት በእስክንድርያ ከተማ የኤጲስቆጶሳት የአንድነት ጉባዔ ተደረገ።
ይኸውም አባት የትንሣኤ ሙታንን ድርሳን የደረሰው ነው፡፡ ይህም ጉባዔ የሆነው ነፍስ ከሥጋዋ ጋር ትሞታለች በዕለተ ትንሣኤም ከሥጋዋ ጋር አብራ ትነሣለች ስለሚሉ ክፉዎች በዐረቢያ አገር ስለ ተነሡ ሰዎች ነው። እነርሱም ለከፋችና ብልሹ ለሆነች ሃይማኖታቸው የፈጠራ ድርሰትን ደርሰው በእስክንድርያ ከተማ ወደሚኖሩ ሰዎች ላኩ።
አባታችን ሊቀ ጳጳሳት አባ ዲዮስናስዮስም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ አዘነ ከዚህ ከክፉ ሥራም እንዲመለሱ አስተማራቸው ገሠጻቸውም እነርሱ ግን አልሰሙትም አልተመለሱም። ስለዚህም በእነርሱ ላይ ይህን ጉባዔ ሰብሰቦ ተከራከራቸው ስሕተታቸውንም ገልጾ አስረዳቸው እነርሱ ግን ሰይጣን አሳውሮአቸዋልና ተጸጽተው አልተመለሱም ይህም ጉባኤ ረግሞ ከቤተ ክርስቲያን አንድነት ለይቶ አሳደዳቸው። ይህም አባት ዲዮናስዮስ ስለርሳቸው ድርሳናትን ደረሰ በውስጣቸውም እንዲህ የሚል እንጂ በቸርነቱ ስጦታ ውስጥ የእግዚአብሔር ፍቅር የጎላ የተረዳ ሆነ ነፍስ ረቂቅ ስለሆነች እንደ መላእክት በሕይወት እንድትኖር እንጂ እንዳትሞት እንዳትጠፋ ማድረጉ ነው።
ከሥጋዋም በምትወጣ ጊዜ ስለ በጎ ሥራዋ እንደሚገባት መጠን ወደ ሕይወት ቦታዋ ይወስዷታል ወይም እንደ ሥራዋ ክፉነት ወደ ሥቃይ ይወስዷታል። በትንሣኤ ቀንም ንቃሕ መዋቲ ተብሎ ዓዋጅ ሲነገር በፈጣሪያቸው ትእዛዝ የሙታን በድኖች ሲነሡ ነፍሳት እንዲህ ይሆናሉ እያንዳንዲቱ ነፍስ ከሥጋዋ ተዋሕዳ አብራ ትነሣለች።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_ሙሴ_ዘገዳመ_ሲሐት
በዚህችም ቀን የገዳመ ሲሐት አባ ሙሴ አረፈ ። ይህም ቅዱስ ከመነኰሰ ጀምሮ ዓለምን ትቶ ከበረሀ ገብቶ በጾም በጸሎት በመጠመድ ተጋደለ ። እግዚአብሔር ዘይቶንና የተምር አትክልት ያለባትን የአትክልት ቦታ በማየት ልቡን ብሩህ እስከ አደረገለት ድረስ በወሩ መባቻም ከዘንባባ ዕንጨትና ከዘይቶን የወደቀውን ፍሬ ወስዶ ይበላል ።
ምግቡም ታናሽ ወፍ በሚመገበው መጠን ልክ ነው ልብሱም ከዘንባባ ቅጠል የተሠራ ሰሌን ነው ። ስለዚህ ለሚያስጨንቅ ለክረምት ቅዝቃዜና ለበጋ ቃጠሎ የተጋለጠ ከዚህም ጋር በጾምና በጸሎት የተጠመደ ነው ።
ነገር ግን መጻሕፍትን የሚያውቅ አይደለም የዱር አራዊትም በየወገናቸው ወደርሱ ይመጡ ነበር እርሱም ያረጋጋቸዋል ። የጸሎት ጊዜም ሲደርስ በእጁ ሲጠቅሳቸው ይሔዳሉ ። ድርቅ የሆነ እንደሆነም ሊያነጋግሩት እንደሚሹ ሁነው መጥተው በፊቱ ይቆማሉ እርሱም የሚሹትን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ በጸሎቱ ዝናብን ያወርድላቸዋል ። እንዲሁም እያደረገ ከእርሳቸው ጋር አርባ አምስት ዓመት ኖረ ።
ሰይጣንም ቀናበት ዘመኑ በአለፈና እጅግ በአረጀ ሽማግሌ አምሳል በጥቂት በጥቂት ሲያዘግም ከበዓቱ ውስጥ ሁኖ አየው ለዚህ ቅዱስ አባ ሙሴም ገዳማዊ መናኒ መስሎት ወደርሱ ሒዶ አምጥቶ ወደ በዓቱ አስገባው አራዊት ግን በሽማግሌ የተመሰለውን ሰይጣን በአዩት ጊዜ ከእርሱ ሸሹ።
ከዚህ በኋላ አባ ሙሴን አገሩንና ሃይማኖቱን ጠየቀው እርሱም ሁሉን ነገረው ደግሞ አባ ሙሴ ኑሮው እንዴት እንደሆነ ሽማግሌውን ጠየቀው ። በሽማግሌ የተመለሰ ሰይጣንም እንዲህ ብሎ መለሰለት እኔ በዓለም ኃጢአት በመሥራት ብዙ ዘመናት ኖርኩ አንዲት ሴት ልጅንም ወለድኩ ። ከዚያም የዓለምን ኃላፊነትና ጠፊነት አሰብኩ ከዓለምም ወጥቼ በበረሀ ውስጥ አርባ ዓመት ኖርኩ ።
ልጄን ያገባት እንደሌለ በአሰብኩ ጊዜ በዚህ ነገር ምክንያት ወዳንተ መጣሁ ከአንተ በቀር የሚያገባት የለምና በሞትኩም ጊዜ የምትቀብረኝ አንተ ነህ ብዙ ስፍራዎችና የአታክልት ቦታዎችም ስላሉኝ ሁሉንም እንተ ትወርሳለህ ።
አባ ሙሴም ሰምቶ ደነገጠ እኔ መነኲሴ ስሆን ይህን እንዴት አደርጋለሁ አለ የተመረጡ ጻድቃን ሲሆኑ ሚስቶች የነበሩአቸው አብርሃምን ሙሴን ዳዊትን ከብሉያት መጻሕፍት ምስክር ማስረጃ አድርጎ አመጣለት በዚህም ወደ ተንኰሉ ልቡን አዘነበለው ።
በውስጡ ያጌጠች ሴት ልጅ ያለችበትን የተሸለመ አዳራሽ አሳየውና ከዚያም በኋላ እንደሞተ ሆነ አባ ሙሴም አይቶ በለዩ አለቀሰ ገንዞም ቀበረው ።
ልጅቷ ወዳለችበት ለመግባት በፈለገ ጊዜ ጥቅል ነፋስ ነፍሶ የኋሊት ጣለው ከዚህ በኋላ ልቡ ሲመለስለት አዳራሹንም ልጅቷንም የአትክልት ቦታዎችንም አጣ ፈጽሞ እያደነቀ ወደ ማደሪያው ተመለሰ ከዕንጨቱም ፍሬ ምግቡን ሊመገብ ፈለገ በአፉም ውስጥ መራራ ሆነበት በረኃብም ስለ ተጨነቀ ወደ ዱር ወጥቶ ሔደ ።
ከዚህም በኋላ በአህያው ላይ ተቀምጦ ወደ እስክንድርያ በሚሔድ በሽማግሌ ነጋዴ አምሳል ሰይጣን ተገናኝው መብልና መጠጥም ይዞ ነበር አባ ሙሴንም ከርሱ ጋር ወሰደው ወዳንድ አገርም አድርሶ በዚያሴት ተወው ።
ዳግመኛም በገዳማዊት በመናኒነት በምትኖር አምሳል ሰይጣን ታየው እርሷም ውኃ የምትቀዳ መስላ ነው ሥራውን ጠየቀችው ሰይጣን እንደ ፈተነው ሁሉን ነገራት በልቧም ሳቀችበት ወደ ቤቷም ወስዳው አብልታ አጠጥታ ከዚያ በኋላ የጋብቻን ነገር አሳሰበትው ብዙ ገንዘብም እንዳላት እርሷም የሟች ንጉሥ እንደ ሆነት ነገረችው ።
ልቡም እንደአዘነበለ አይታ እኔ አይሁዳዊት ነኝ እኛም ብዙዎች ነን ሃይማኖቱንም እስከካደ ድረስ በብዙ ተንኰል ተስፍ አስደረገችው ።
ዳግመኛም እንዲህ አለችው ና ወደ በረሀ እንውጣና ያኖርኩትን ገንዘብ እንውሰድ ብላ ውኃ ወደሌለበት በረሀ ወሰደችው ከተራራ በላይም ወጥታ ተለወጠችበት እንዲህም አለችው እኔ ብዙዎችን ያሳትኩ ሰይጣን ዚህ አንተነንም ከገዳምህ አስመጣሁህ ሃይማኖትህንም አስካድኩህ እነሆ በዚህ በረሀም ሙተህ ነፍስህ ወደገሃነም ትወርዳለች ይህንንም ብሎ ሰይጣን ከርሱ ተሠወረ ። ን
በተመለሰም ጊዜ በቀኝም በግራም መንገድ አጣ የሚጠጣውም ውኃን አላገኘም ምድር ጠበበችው በምድር ላይም ወድቆ በፊቱ ውስጥም አፈርን በተነ ነፍሱም ከሥጋው ለመለየት እስከደረሰች ደረስ ተንከባለለ ጭኸ መሐሪና ይቅር ባይ ሰውን የሚወድ እግዚአብሔር ራራለት ያጽናናው ዘንድ መልአኩን ላከለት እርሱም ኃጢአትህ ተሠረየልህ እስከ ሰባት ቀንም ታርፍለህ የእግዚአብሔር አገልጋይ ሳሙኤልም ይቀብርሃል ብሎ አጽናናው ሰላምታም ሰጥቶት ዐረገ ።
ያን ጊዜም ሳሙኤል መጣ ንጉስ ኢጋቦም በበረሃ ውስጥ ወደአነፃት ቤተ ክርስታያን ወሰደው እርሷም ገዳማውያን የሚሰበሰቡባት ተሰውራ የምትትኖር ናት ወደርሷም በደረሱ ጊዜ ቅዱሳን ተሰብስበው መሥዋዕትን ሲያሳርጉ አገኙና በአንድነት ሥጋውንና ደሙን ተቀበሉ ሰንብትም ከሆን በኋላ ከቅዱሳን መቃብር በረከትን ሊቀበሉ ከአባ ሰሙኤል ጋራ አብረው ሔዱ ዘኪያም ደርሶ አባ ሙሴ ሰገደ ወዲያውም አረፈ አባ ሳሙኤልም ቀበረው ገድሉንም ጻፈ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#አባ_አንበስ_ኢትዮዽያዊ
🔴#ስንክሳር መስከረም_2
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም
መስከረም ሁለት በዚህች ቀን #ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ ሰማዕት ሆነ፣ #ቅዱስ_ዳስያ_ሰማዕት ሰማዕት ሆነ፣
#ቅዱስ_ዲዲሞስና_የቅድስት_መሪና መታሰቢያቸው ነው።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ
መስከረም ሁለት በዚህች ቀን የካህኑ የዘካርያስ ልጅ የከበረ አጥማቂው ዮሐንስ ሕግን አፍራሽ በሆነ በንጉሥ ሄሮድስ እጅ ሰማዕት ሆነ።
ይህም እንዲህ ነው በፊልጶስ ሚስት በሄሮድያዳ ምክንያት ነቢዩ ዮሐንስ በገሠጸው ጊዜ ፊልጶስ ወንድሙ ስለሆነ ቅዱስ ዮሐንስም የወንድምህን ሚስት ልታገባ አይገባህም ይለው ነበርና።
ቅዱስ ዮሐንስም ሄሮድስን የወንድሙን የፊልጶስን ሚስት ሄሮድያዳን ስለማግባቱና ሌላም ያደርገው ስለነበረ ክፉ ሥራ ሁሉ ይገሥጸው ነበር። ደግሞም በተግሣጽ ላይ ተግሣጽን ጨመረ። ስለዚህም ዮሐንስን ተቀየመውና በግዞት ቤት አኖረው።
ሄሮድስም ዮሐንስን ይፈራው ነበር ጻድቅ ቅዱስ ሰው እንደሆነ ያውቅ ነበርና ብዙ ይጠባበቀውም ነበር። ሄሮድስ የተወለደባትን ቀን በዓል የሚያከብርባት ዕለት ነበረች መኳንንቱን አለቆቹን መሣፍንቱን ሹሞቹን በገሊላ አገር ያሉትን ታላላቅ ሰዎች ግብር አገባ።
የሄሮድያዳ ልጅም ወደ አዳራሹ ገብታ ዘፈነች ሄሮድስንም ደስ አሰኘችው ከእርሱ ጋር በማዕድ የነበሩትንም ንጉሡም ያቺን ብላቴና የምትሺውን ለምኚኝ እሰጥሻለሁ አላት። እስከ መንግሥቱ እኩሌታ ድረስም ቢሆን የለመነችውን ሊሰጣት ማለላት።
ወጥታም እናቷን ምን ልለምነው አለቻት እናቷም የመጥምቁ ዮሐንስን ራስ አለቻት። ያን ጊዜም እየሮጠች ወደ ንጉሡ ገብታ የመጥምቁ ዮሐንስን ራስ በወጭት አሁን እንድትሰጠኝ እሻለሁ ብላ ለመነችው። ንጉሡም ስለ መሐላው አብረውት ስለ ነበሩትም ሰዎች አዘነ እምቢ ሊላት ግን አልወደደም።
ያን ጊዜም ባለወጎችን ላከ በእሥር ቤትም ሳለ የዮሐንስን ራስ ቆረጡ ራሱንም በወጭት አምጥተው ለዚያች ብላቴና ሰጡአት እርሷም ወስዳ ለእናቷ ሰጠች። በዚያችም ቀን የቅዱስ ዮሐንስ ራስ ከሄሮድያዳ ከእጆቿ ላይ ወደ አየር ስለ በረረች ታላቅ ድንጋፄ ሆነ።
ደግሞም ሄሮድስ ሆይ የወንድምህን ሚስት ልታገባ አይገባህም እያለች በመጮኽ ዘልፋዋለችና። ደቀ መዛሙርቱም በሰሙ ጊዜ መጥተው በድኑን ወስደው ቀበሩት።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዳስያ_ሰማዕት
በዚችም ቀን በግብጽ ውስጥ ታዕዳ ከሚባል አገር ዳስያ ሰማዕት ሆነ። ይህንንም ቅዱስ የእንዴናው አገረ ገዥ አርያኖስ አሠቃየው ጽኑ ሥቃይንም ከአሠቃየው በኋላ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ።
✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞
#ቅዱስ_ዲዲሞስና_የቅድስት_መሪና_ሰማዕት
በዚህችም ቀን የሰማዕት ዲዲሞስና የቅድስት መሪና መታሰቢያቸው ነው።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12
¡Ya disponible! Investigación de Telegram 2025 — los principales insights del año 
