es
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

Ir al canal en Telegram

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

Mostrar más
2 638
Suscriptores
+124 horas
+87 días
+5830 días
Archivo de publicaciones
መልካም አዲስ ዓመት በሰንበት ት/ቤታችን የተዘጋጀ ዝማሬ

አባ ሚልኪም ከመነኰሰ አርባ አምስት ዓመታት ሲሆነው እንዲህ የሚል ቃል ከሰማይ ወደርሱ መጣ እነሆ የምታርፍበት ቀን ቀርቧል ከሦስት ቀን በቀር አልቀረህም ወደ ዘላለምም ተድላ ደስታ ትሔዳለህ። ያን ጊዜም ልጆቹን ሁለ ጠርቶ ሰይጣን ከሚያመጣው ስሕተት እንዲርቁና እንዲጠብቁ በፍርሃትም ሁነው እግዚአብሔርን እንዲአገለግሉ አዘዛቸው።ከሦስት ቀንም በኋላ ቅዱሳን  አባቶች መነኰሳት አባ እንጦንስ አባ መቃርስ አባ ሲኖዳ አባ ብሶይ አባ ጳኵሚስ ወደርሱ መጥተው እንዲህ አሉት ወንድማችን ወደእኛ ና ከእኛ ጋርም ፍጹም ተድላ ደስታ ባለበት በእግዚአብሔር መንግሥት ደስ ይበልህ ይህንንም ሲሉት ነፍሱ ከሥጋው ወጣች።መላእክትም በዓለም ውስጥ በገድል በትሩፋት  የደከመ ለዘላለሙ በሕይወት ይኖራል እያሉ በክብር በምስጋና ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት አወጡት። ከዚህም በኋላ ጳጳሳት ኤጲስቆጶሳት ሁሉም ካህናት ተሰብስበው ገነዙት በቤተ ክርስቲያንም ውስጥ ቀበሩት ከመቃብሩም ቍጥር የሌላቸው ታላላቅ የሆኑ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ።        ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

ከዚህም በኋላ በፈረስ ተቀምጦ ከአባቱ ፊት ወጣ ሎሌዎቹንም እንዲህ አላቸው መቶ የወርቅ ዲናርን ወስዳችሁ በፍጥነት ምሳ አዘጋጁልን ልጆች ባልንጀሮቼን እኔ ብቻዬን ሒጄ እጠራቸዋለሁ። ዘመዶቹም ሰምተው ተመለሱ እርሱም ብቻውን ሒዶ ያንን ወርቅ ለድኖችና ለምስኪኖች በተነ ፈረሱንም ለአንድ ድኃ ሰጠ በላዩ ካለ ልብስ በቀር ምንም ምን አላስቀረም። መምጣቱም በዘገየ ጊዜ ፈለጉት ግን አላገኙትም። እያለቀሱም ተመልሰው ለአባቱና ለእናቱ ነገሩአቸው እነርሱም የመረረ ልቅሶን አለቀሱ ከለቅሶ ብዛትም የተነሣ የእናቱ  ዐይኖቿ ታወሩ ለሞትም አደረሳት። ይህ አባ ሚልኪ ግን ጡር ወደምትባል ገዳም ሔደ ይቺም ስሙ አባ አውጊን ለሚባል ለእናቱ ወንድም ገዳሙ ናት። ይህም አባ አውጊን ብዙ ትሩፋትን የሚሠራ ጻድቅ ሰው ነው በእርሱም ሥር የተመረጡ ሰባ ሁለት መነኰሳት ነዋሪዎች አሉ። አባ ሚልኪም ከእግሩ በታች ሰግዶ አባቴ ሆይ በጥላህ ሥር እንድኖር የምንኲስናንም ልብስ ታለብሰኝ ዘንድ እሻለሁ አለው። አባ አውጊንም ከወዴት አገር ነህ ብሎ ጠየቀው  እርሱ አባ ሚልኪም አገሩ ቊልዝም ለአባ አውጊንም የእኀቱ ልጅ መሆኑን ነገረው ሰምቶም ፈጽሞ ደስ አለው። ሦስት ዓመትም በአመክሮ አቆየው ከዚህም በኋላ የምንኲስናን ልብስ አለበሰው ዜናው በፋርስ አገር ሁሉ እስቲሰማ ትጋትንና ተጋድሎን አበዛ። እግዚአብሔርም የመፈወስን ሀብት ሰጥቶት አጋንንትን ከሰዎች ላይ አሰወጥቶ ይሰዳቸዋል። ከዕለታትም በአንዲቱ ዕለት የዳዊትን መዝሙር እያነበበ ብቻውን ሲጓዝ ታላቅ ጒድጓድ ወዳለበት ደረሰ በአጠገቡም የበለስ ዛፍ አለ ብዙ እረኞችም በዚያ ያለቅሱ ነበር። አባ ሚልኪም ምን ያስለቅሳችኋል አላቸው። እረኞችም እንዲህ ብለው መለሱለት የአገረ ገዢው ልጅ ከእኛ ጋራ ከበለስ ፍሬ ሲበላ ታላቅ ዘንዶ ወጥቶ ልጁን ውጦ ወደ ጒድጓድ ተመለሰ አሉት። እረኞችም እየነገሩት ሳለ የሕፃኑ አባት ልብሱን በመቅደድ ፊቱንም በመጽፋት ከብዙ ሰዎች ጋር መጣ ቅዱስ ሚልኪንም ስለ ልጁ ማለደው። አባ ሚልኪም ልጄ ሆይ በእግዚአብሔር ታመን እንጂ አትፍራ የጌትነቱንም ድንቅ ሥራ ታያለህ አለው። ያን ጊዜም ፈቱን ወደ ምሥራቅ መልሶ ረጅም ጸሎትን ጸለየ ጸሎቱንም በጨርሰ ጊዜ ዘንዶውን ጠርቶ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሕፃኑን ይተፋው ዘንድ አዘዘው ምንም ሕማም ሳይነካው ጒዳትም ከቶ ሳያገኘው ወዲያውኑ ተፋው በከይሲውም አድሮ ያለ ሰይጣን እንዲህ ብሎ ጮኸ የቊልዝም ሰው ሚልኪ ከአንተ የተነሣ ወዴት ልሒድ ይህንንም ብሎ እንደ ጢስ ተበተነ። የሕፃኑም አባት ይህን ድንቅ ሥራ ልጁም እንደ ዳነ በአየ ጊዜ እጅግ ደስ አለው። ለቅዱስ አባ ሚልኪም ብዙ ወርቅትና ብር አመጣ አባ ሚልኪም መቀበልን አይሆንም አለ ግን በጽድቅ ሥራ አንድ እንድንሆን ገዳምን ሥራ አለው:: አገር ገዢው የሕፃኑ አባትም ደስ አለው ሦስት መቶ የመነኰሳት ቤቶችን ሠራ ዙሪያውንም በግንብ አጠረ መዝጊያውንም ከብረት ሠራ:: ቤተክርስቲያንንም ሲሠሩ ሦስት መቶ ሰዎች ሊአንቀሳቅሷት የማይችሉ ለማዕዘን የምትሆን ደንጊያን አገኙ በጻድቁ በአባ ሚልኪ ጸሎትም ራስዋ ተነሥታ እንደሚፈልጓት ሁና ተሠራች:: ከዚህም በኋላ በዚያ ገዳም ሦስት መቶ ሰዎች ተሰብስበው የተመረጡ መነኰሳትን ሆኑ:: የቅዱስ አባ ሚልኪም ዜናው በሀገሩ ሁሉ ተሰምቶ በየዓይነቱ ደዌ ያለባቸውን በክፉዎች አጋንንትም የተያዙትን ወደርሱ የሚያመጡአቸው ሆኑ ሁሉም በጸሎቱ ይፈወሱ ነበር:: በዚሁ ጻድቅ ጸሎትና ምልጃ የፋርስና የሮም ሰዎች ተጠብቀው  የሚኖሩ ሆኑ:: ከዚህም ብኋላ አባ ሚልኪ ከዋሻ ውስጥ ገብቶ የዋሻውን በር ዘጋ በልቡም እስከ ዕድሜዬ ፍጻሜ ከዚህ ዋሻ አልወጣም ብሎ ቃል ገባ:: የበጎ ሥራ ጠላት ሰይጣንም እንዲህ ብሎ ዛተበት ጠብቀኝ እኔ ከዚህ ከበዓትህ አስወጥቼ የተሳልከውን ቃል አፈርሳለሁ ይህንንም ብሎ ሒዶ በሮም ንጉሥ ልጅ ላይ አድሮ አሳበዳት እርሷም እየጮኸች እንዲህ አለች ከቊልዝማዊው ሚልኪ በቀር የሚያድነኝ የለም:: ንጉሥ አባቷም ሰምቶ ከወታደሮቹ ውስጥ አራት መቶ ሰዎችን ላከ እንዲህም ብሎ  አዘዛቸው በሁሉ ቦታ ተግታችሁ አባ ሚልኪን ፈልጋችሁ ወደ እኔ አምጡት እኔም በጎ የሆነ ዋጋችሁን እከፍላችኋለሁ:: ይህ ካልሆነ ግን ራሶቻችሁን በሰይፍ ልቆርጥ ምያለሁ:: የተላኩ ወታደሮችም ፈልገው በጭንቅ አገኙትና ለብፁዕ  አባ ሚልኪ የንጉሡን መልእክት ልጁን ጋኔን እንደአደረባት የምትናገረውንም ነገር ነገሩት። እርሱም እኔ ሽማግሌ ሰው ነኝ ወደ ሮም አገር ለመሔድ አልችልም አላቸው። እነርሱም አባታችን ሆይ አንተ ከእኛ ጋር ካልሔድክ ንጉሥ በሰይፍ ቆርጦ እንደሚገድለን ነግሮናል አሉት።ስምቶም እጅግ አዘነ እንዲህም አላቸው ልጆቼ ሒዱ እኛ እርስ በርሳችን በሮም ከተማ መግቢያ እንገናኛለን። ቃሉንም ሰምተው ሔዱ በዓመቱም ፍጻሜ ከሮሜ ከተማ መግቢያ መድረሳቸውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ ያን ጊዜም ደመና ተሸክማ ከሮሜ ከተማ መግቢያ አደረሰችው።የንጉሥ መልእክተኞችም በአዩት ጊዜ እጅግ ደስ አላቸው።ለንጉሡም የከበረ አባ ሚልኪ መምጣቱን ነገሩት። እርሱም ወጥቶ በክብር ተቀብሎ ወደ እልፍኙ አስገባው ስለ ልጁ ስለ ደዌዋ ነገረው ቅዱስ አባ ሚልኪም አምጧት ብሎ አዘዘ።በአመጧትም ጊዜ ጋኔኑ ጥሎ አረፋ አስደፈቃት ሞተች ብለው እስከሚጠራጠሩ።ያን ጊዜም አባ ሚልኪ ተነሥቶ ጸለየ በፊቷ ላይም ውኃን ረጨ ዘይትንም ቀባት ሰይጣንንም ከርሷ ይወጣ ዘንድ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም አዘዘው። ያን ጊዜም በጥቁር ባርያ አምሳል ከእርሷ ወጣ። ቅዱስ አባ ሚልኪም ሰይጣንን በሥውር ይዞ በቤት ውስጥ ዘጋበት በዚያም አሠረው። ንጉሡም ይህን ድንቅ ሥራ አይቶ ከእግሩ በታች ሰገደ ለገዳሙ ለሚአስፈልገው ነገር እንዲሆነው ብሎ ብዙ ወርቅና ብርን አመጣለት እርሱም መቀበልን እምቢ አለ። ንጉሡም አባቴ ሆይ ከዚህ ተቀመጥ እኔም ገዳም እሠራልሃለሁ አለው አባ ሚልኪም ልጆቼን መተው አይሆንልኝም አለው ግን በሽተኞችን እየፈወሰ በሮሜ ከተማ ጥቂት ቀኖች ተቀመጠ። ወደ አገሩ ይመለስ ዘንድ ተነሥቶ በወጣ ጊዜ ንጉሡም ከመኳንንቱ ጋራ ሊሸኘው ተነሣ። ከንጉሥ ግቢ በስተውጭ የንጉሥ ፈረሶች የሚጠጡበት ታላቅ የደንጊያ ገንዳ የተበሳ ታላቅ የሆነ ደንጊያን አባ ሚልኪ አይቶ ንጉሡን ይህን ገንዳ ይህንንም የተበሳ ታላቅ ደንጊያ ለገዳም አገልግሎት እሻዋለሁና ስጠኝ አለው።ንጉሡም ዐሥራ አራት ሰዎች ከምድር ከፍ ሊአደርጉት የማይቻላቸው ወደ ገዳምህ እንዴት ይደርሳል ተሸክሞ ወደ ፈለግከው ቦታ የሚያደርስ ኃይል ካለህ እኔ ሰጠሁህ አለው። ያን ጊዜም ቅዱስ አባ ሚልኪ ሰይጣንን ከአሠረበት ቦታ አምጥቶ ያንን የተበሳ ደንጊያ በአንገቱ ውስጥ አንጠለጠለ ገንዳውንም ተሸክሞ በፊት በፊቱ ተገልጦ እንዲጓዝ አዘዘው። ሰይጣንም እነዚያን ገንዳዎች የተበሳውንም ደንጊያ ተሸክሞ በፊት በፊቱ ይጓዝ ጀመረ።ንጉሡና የተሰበሰቡት ሕዝብ አይተው እጅግ አደነቁ ለሚፈሩት ለሚያመልኩት ይህን ያህል ጸጋ የሚሰጥ ምስጉን እግዚአብሔርንም አመሰገኑት። የከበረ አባ ሚልኪም እነዚያን ደንጊያዎች ሰይጣንን አሸክሞ ወደ ገዳሙ አደረሰው በገዳሙም ደጃፍ አጠገብ እንዲአስቀምጣቸው አዘዘው እስከዛሬም በዚያ ይኖራሉ። ሰይጣንንም ዳግመኛ ወጥቶ እንዳይፈትነው በዓለት ዋሻ ውስጥ ዘግቶ በመስቀል ምልክት ለዘላለሙ አሸገው።

በዚህ መከራ በነበረበት ዘመናት በተራራ ላይ ተጥሎ ሳለ የወዳጆቹና የሚስቱ ዘለፋ በዝቶበት ነበረ። እርስዋ እንዲህ ብላ መከረችው እስከ መቼ ድረስ በሞኝነት ትኖራለህ እንግዲህስ ስደበውና ሙት ዳግመኛ እግዚአብሔርን ደጅ እጠናዋለሁ መከራውንም እታገሣለሁ የቀድሞ ኑሮዬን ተስፋ አደርጋለሁ ትላለህን አለችው። እንዲህስ እንዳትል ከዚህ ዓለም እነሆ ስም አጠራርህ ጠፋ ሴቶች ልጆቼና ወንዶች ልጆቼ ሞቱ እኔም ዘጠኝ ወር ሳረግዝ ሳምጥ ስወልድ ላይረቡኝ ላይጠቅሙኝ በከንቱ ደከምኩ ። አንተም በመግል ተውጠህ በትል ተከበህ ትኖራለህ ሌሊቱን ሁሉ ስትዛብር ታድራለህ እኔም እየዞርኩ እቀላውጣለሁ ካንዱ አገር ወዳንዱ አገር ካንዱ ቤት ወዳንዱ ቤት እሔዳለሁ ከድካሜ በኔ ላይ ከመጣው ከችግሬም አርፍ ዘንድ ከጧት ጀምሮ ፀሐይ እስቲገባ ድረስ እጠብቃለሁ አሁን ግን እግዚአብሔርን የማይገባ ቃል ተናግረኸው ሙት አለችው። ኢዮብም ሚስቱን እየተመለከተ ሰማት። ሥርዓት እንዳልተሠራባቸው ከአሕዛብ ሴቶች እንዳንዲቱ ተናገርሽን ከዚህ ቀድሞ በጎውን ነገር ከእግዚአብሔር እጅ ተቀበልን ከዚህ በኋላ መከራውን አንታገሥምን አላት። በዚህ ባገኘው መከራ ሁሉ ኢዮብ ጌታን የበደለው በደል የለም። ኢዮብም ወርቅ በእሳት እንዲፈተን ፈጽሞ ተፈተነ። እግዚአብሔርም በደመና ውስጥ ተነጋገረው። ከተናገረውም በኋላ ከደዌው ፈወሰው ጥሪቱን ሁሉ ከቀድሞ እጥፍ አደረገለት ሌሎች ልጆችንም ሴቶችና ወንዶችን ሰጠው። ኢዮብም ከደዌው ከተፈወሰ በኋላ መቶ ሰባ ዘመን ኖረ የኖረውም ዘመን ሁሉ ሁለት መቶ አርባ ስምንት ዓመት ነው። በበጎ ሽምግልናም እግዚአብሔርን አገልግሎ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሐዋርያው_ቅዱስ_በርቶሎሜዎስ ዳግመኛም በዚህች ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ ሐዋርያ በርቶሎሜዎስ ምስክር ሁኖ አረፈ። ለዚህም ሐዋርያ ሒዶ ያስተምር ዘንድ እልዋህ በሚባል አገር ዕጣው ወጣ። እርሱም ከጴጥሮስ ጋር በአንድነት ሔደ የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም አስተማሩ ልባቸውንም የሚያስደነግጥ ድንቆች ተአምራትን በፊታቸው ከአደረጉ በኋላ እግዚአብሔርን ወደ ማወቅ መለሷቸው። ከዚህም በኋላ ወደ ከተማው ውስጥ ገብቶ ያስተምር ዘንድ ምክንያት አደረገ ቅዱስ ጴጥሮስም እንደ ባሪያ ሸጠው።ባለ ጸጋ ለሆነ መኰንንም በወይን አትክልት ውስጥ የሚያገለግል ሆነ ድንቅ ተአምርን በማድረግ የተቆረጡ የወይን ቅርንጫፎች በሠራተኞች እጅ ላይ ሳሉ አፈሩ። የአገረ ገዥውም ልጅ በሞተ ጊዜ ከሞት አሥነሣው የሀገር ሰዎችም ሁሉ አመኑ እግዚአብሔርንም ወደ ማወቅ ተመለሱ። ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በርበር ወደሚባል አገር ሔዶ ያስተምር ዘንድ ሐዋርያ በርተሎሜዊስን አዘዘው እንዲረዳውም ሐዋርያ እንድርያስን ከደቀ መዝሙሩ ጋር ላከለት። የዚያች አገር ሰዎች ግን እጅግ የከፉ ስለሆኑ በፊታቸው ድንቆች ተአምራቶችን እያደረጉላቸው ሐዋርያትን አልተቀበሏቸውም ። ጌታችንም ሰውን ከሚበሉ አገር አንዱን ገጸ ከልብ ይታዘዝላቸው ዘንድ በሚያዙት ሁሉ ትእዛዛቸውን እንዳይተላለፍ አዘዘው።ሐዋርያትም ወደዚያች አገር ሁለተኛ ይዘውት ገቡ የሀገር ሰዎችም ሐዋርያትን ይበሏቸው ዘንድ ነጣቂዎች የሆኑ አራዊትን አወጡ። ያን ጊዜም ያ ገጸ ከልብ በአራዊቱ ላይ ተነሥቶ እየነጠቀ በላቸው ይህንንም ገጸ ከልብ ከመፍራት የተነሣ ከሰዎች በድንጋጤ የሞቱ ብዙዎች ናቸው። የሀገር ሰዎች ሁሉም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ከሐዋርያትም እግር በታች ሰገዱ የሚሉአቸውን ሁሉ የሚያደርጉ ታዛዦች ሆኑ። ሐዋርያትም ቤተ ክርስቲያን ሠርተውላቸው ካህናትንም ሹመውላቸው ከእነርሱም ዘንድ ወጥተው እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ሔዱ። ሐዋርያ በርቶሎሜዎስም እግዚአብሔርን የማያውቁ ሰዎች ወደሚኖሩት በባሕር ዳርቻ ወዳሉ አገሮች ሔዶ የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሰበከላቸው በፊታቸውም ተአምራትን አደረገ ሁሉም የጌታችን በሆነች በቀናች ሃይማኖት አመኑ። ሐዋርያ በርቶሎሜዎስም ከዝሙት ርቀው ንጹሐን እንዲሆኑ ሰዎችን የሚያዝዝ ሆነ። ንጉሥ አግሪጳም ስለርሱ በሰማ ጊዜ በከበረ ሐዋርያ በርቶሎሜዎስ ላይ እጅግ ተቆጣ። በማቅ ከረጢት ውስጥ እንዲአደርጉትና አሸዋ ሞልተው ከባሕር እንዲጥሉት አዘዘ።እንዲሁም ይህን አደረጉበት ምስክርነቱንና ተጋድሎውንም በዚች ዕለት ፈጸመ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ሜልዮስ በዚህችም ቀን ዳግመኛ የታላቂቱ አገር የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ሜልዮስ አረፈ። እርሱም ለአባታችን ሐዋርያና ወንጌላዊ ለሆነ ማርቆስ ሦስተኛ ነው። ይህም አባት የሮሜ ንጉሥ አስባስያኖስ በነገሠ በዐሥራ አምስት ዓመት ተሾመ ይኸውም የክብር ባለቤት ጌታችን በዐረገ በአርባ ዓመት ነው ክብር ይግባውና የክርስቶስን መንጋዎች በበጎ አጠባበቅ ጠበቃቸው በሹመቱም ዐሥራ ሁለት ዓመት ኖረ። እግዚአብሔርንም አገልግሎ በሰላም በፍቅር አንድነት አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ሚልኪ_ቊልዝማዊ በዚችም ቀን ደግመኛ የቊልዝም ሰው የሆነ ፍጽም ጸድቃ አባ ሚልኪ አረፈ። የዚህም ጻድቅ ወላጆቹ ከቊልዝም አገር ከታላላቆች ወገን ናቸው። እርሷም ከላይኛው ግብጹ አውራጃ ውስጥ ናት እነርሱም በብርና በወርቅ የበለጸጉ ናቸው ለድኖችና ለችግረኞች ምጽዋትን የሚሰጡ እግዚአብሔርንም እጅግ የሚወዱ ናቸው። ነገር ግን ልጅ አልነበራቸውም ከዕለታትም በአንዲቱ ከመምህር ዘንድ የሚማሩ ልጆችን አዩ በእጆቻቸውም ሠሌዳዎችን ይዘዋል። በሠሌዳዎቹም ውስጥ እንዲህ የሚል ጽሑፍ አለ እኛ የሕያው እግዚአብሔር ልጆች እንድንሆን በሕይወታቸው ሳሉ ያስተማሩን አባቶቻችንን አስባቸው አቤቱ ነፍሶቻቸውንም ከተመረጡ ቅዱሳን ጻድቃንና ሰማዕት አሳርፍ። የአባ ሚልኪ አባትም ከልጆች አንደበት ይህን ቃል በሰማ ጊዜ ከዚህ ዓለም ከሔድኩ በኋላ ልጅ የሌለኝ እኔን ማን ያስበኛል ወዮልኝ እያለ እጅግ በማዘን ተከዘ። ከዚህም በኋላ በጾም በጸሎት ምጽዋትንም በመስጠት ከሚስቱ ጋር ምህላ ያዘ። የክብር ባለቤት እግዚአብሔርም ልመናቸውን ሰምቶ ወንድና ሴት ሁለት ልጆችን በአንዲት ጊዜ ሰጣቸው በእነርሱም ፈጽሞ ደስ አላቸው። ወደ ክርስትናም በአስገቧቸው ጊዜ ወንዱን ልጅ ሚልኪ አሉት እኀቱን ስፍና አሏት ትርጓሜዋ ርግብ ማለት ነው በመልካም አስተዳደግ አሳደጓቸው። ለሚልኪ ሰባት ዓመት ሲሆነው አባቱ ወስዶ ለመምህር ሰጠው የብሊያትንና የሐዲሳት መጻሐፍትን ሁሉ ለማረ መንፈስ ቅዱስም አደረበት። ከሕፃናቱም ጋር አይጫወትም አይስቅም በቀንም በሌሊትም አዘውትሮ መጸሕፍትን ያነባል እንጂ። ዕድሜውም ዐሥራ ዘጠኝ ዓመት በሆነው ጊዜ ወላጆቹ ጠርተው ስለ ጋብቻ ሚስት አብግቶ መታሰቢያችው ይሆን ዘንድ ተናገሩት። እርሱም ይህን አልወደደም ነገር ግን በተንኰል እሺ ቃላችሁን ተቀብዬ  ያዘዛችሁኝን ሁሉ አደርጋለሁ አላቸው እርሱ ግን ከዓለም ሸሽቶ ያመልጥ ዘንድ ያስባል። ከዚህም በኋላ አባቱን እንዲህ አለው አባቴ ሆይ ከእኔ ጋራ ለተማሩ ልጆች ለባልንጀሮቼም ምሳ ላደርግላቸው እሻለሁ ምሳንም በባልንጀሮቹ ያዘጋጅላቸው ዘንድ አባቱ አንድ ሺህ የወርቅ ዲናርን ሰጠው። ዳግመኛም ለሚያስፈልገው ሥራ እንዲገለግሉ ወንዶችና ሴቶች አገልጋዮችን አዘዘለት።

🔴#ስንክሳር መስከረም_1 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መስከረም አንድ በዚህች ቀን የከበረ መልአክ #ቅዱስ_ራጉኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው፣ #ጻድቁ_ኢዮብ በፈሳሽ ውኃ ታጥቦ ከደዌው ሁሉ ተፈወሰ፣ ሐዋርያ #ቅዱስ_በርቶሎሜዎስ ምስክር ሁኖ አረፈ፣ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ሜልዮስ አረፈ፣ የቊልዝም ሰው የሆነ ፍጽም ጸድቃ #አባ_ሚልኪ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ራጉኤል_መልአክ መስከረም አንድ በዚህች ቀን ከተስዓቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ የከበረ መልአክ ራጉኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው። ራጉኤል ማለት የብርሃናት አለቃ ማለት ነው። የብርሃናት አለቃ ሲባል ፀሐይን፣ ጨረቃን እና ከዋክብትን በማመላለስና ለሰው ልጆች፣ ለአዝርዕት፣ ለእንስሳት፣ ለአራዊት ሁሉ ብርሃንን የሚመግብ ነው ማለት ነው። አንድም ራጉኤል ማለት የሚበቀል ማለት ነው። የሚበቀል ነው ማለት በቀል የሚገባው ለጠላት ነው የሰው ልጅ ጠላት ደግሞ ዲያብሎስ ነው፤ ስለሆነም ቅዱስ ራጉኤል እግዚአብሔርን አምነው ሕገ እግዚአብሔርን ጠብቀው በፍርሐተ እግዚአብሔር አምልኮቱን ለሚፈጽሙ ሁሉ ጠላት ዲያብሎስን የሚያርቅላቸው ወደ እነርሱም ፈጥኖ በመድረስ የሚታደጋቸው ነው ማለት ነው። ሔኖክ 6:4፡፡ አንድም ራጉኤል ማለት የኃያላን ኃያል እግዚአብሔር ማለት ነው። የኃያላን ኃያል ያለው የእግዚአብሔርን ኃያልነት ከምድር ፍጥረታት ዘንድ ኃያል ከሚባሉት ሁሉ ሊገለጽ የማይችል ኃያልነቱን ለመግለጽ ኃያልነቱም ከ እስከ የሌለው መሆኑን ለመግለጽ የተቀመጠ ነው። ስለዚህ እግዚአብሔር ኃያል የኃያላን ኃያል መሆኑን የሚገልጽ ትርጉም አለው። አንድም ራጉኤል ማለት ጽኑ እግዚአብሔር ማለት ነው። የእግዚአብሔር አምላክን ጽኑነት ለማጉላት ሲል ጽኑ አለው። እግዚአብሔር የማይወላውል የማይዋዥቅ የማይከዳ ነው ለማለትም ሲል ይህ ስያሜ ተሰጠው። የእግዚአብሔርን ጽናት የሚያሳይ ትርጉም ያለው ስያሜ ነው። የሊቀ መላእክት የቅዱስ ራጉኤል አገልግሎት እና ስልጣን፡- እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከዚህ ዓለም በ64 ዓመቷ ካረፈች በኋላ ሥጋዋ ወደ ዕፀ ሕይወት ሲነጠቅ (ሲያርፍ) አብሮ ለሔደው እና ስጋዋን በእጣን ሲያጥን ለነበረው ለፍቁረ እግዚ ለቅዱስ ዮሐንስ ኅብስትን የመገበ መልአክ ነው። በብርሃናት ሁሉ ላይ የሰለጠነ መልአክ ነው። ከአዳም ሰባተኛ ትውልድ የሆነ በእግዚአብሔር ፊት ግሩም ያማረ ሥራው የሰመረ እስከዛሬ የሞት ወጥመድ ያልያዘው የሞት ጥላ ያላረፈበት ነብዩ ሔኖክ "ከቅዱሳን መላእክት አንዱ የሆነ ጸላዒ ዲያብሎስን የሚበቀለው ራጉኤል በብርሃናት ላይ የሰለጠነ ነው" ሲል ስለ እርሱ ተናግሯል፡፡ እግዚአብሔር ዓለምን ይቆጣጠር ዘንድ የሾመው ታላቅና ቅዱስ መልአክ ነው። (ድርሳነ ራጉኤል ዘ ጥቅምት ገጽ 23) አዲስ ሰማይና አዲስ ምድር ለመተካት ዓለምን የመለወጥ ሥልጣን የተሰጠው ቅዱስ መልአክ ነው። ከእግዚአብሔር የጌትነቱ አዳራሽ ይገባና ይወጣ ዘንድ ስልጣን ያለው ከኪሩቤልና ከሱራፌል ጋር ከፈጣሪ የጌትነት ዙፋን ፊት የሚቆም ነው። ሎጥን ሚስቱንና ልጆቹን ከእሳተ ጎመራ ያዳነ የበለአምን እርግማን ወደ በረከት የለወጠ እርሱ ነው። በቅዱስ ራጉኤል ስነ ሥዕል ላይ የምናየው ይህ ባለ አራት እራስ ንስር ከአርባእቱ ኪሩቤል አንዱ ገጸ ንስር ነው። የሥላሴን የጌትነት ዙፋን የሚሸከሙ አርባዕቱ እንስሳት ናቸው። የሚሸከሙት ሲባል ጫማ የሰውን ልጅ እንደሚሸከመው እንጂ ችለውትስ አይደለም። እነርሱም የሰው ገጽ፣ የእንስሳ ገጽ፣ የንስር ገጽ እና የአንበሳ ገጽ ያላቸው ናቸው። ይህንንም ነብዩ ሕዝቅኤል "ለእያንዳንዱ እንስሳትም የተለያዩ አራት ገጾች ነበሩት። ይህውም በስተቀኝ በኩል የእንስሳ መልክ፣ በስተ ግራ የላም ገጽ፣ በበስተ ኋላም የንስር ገጽ የሚመስሉ ነበሩ" ብሏል ሕዝ 1፡6-13፡፡ ከዚህ የምንገነዘበው ነገር ቢኖር አራት ገጽ ካላቸው ኪሩቤል መካከል አንዱ ንስር መሆኑን ነው። ቅዱስ ራጉኤል ደግሞ የእነዚህ ኪሩቤል አለቃቸው (የጌትነቱ ዙፋን ጠባቂ) በመሆኑ በዚህ ምክንያት ማለትም እነርሱ ዙፋኑን ተሸካሚ እርሱ ደግሞ አጠገባቸው መቆሙ መንበሩን ጠባቂ በመሆኑ በዚህ አይነት የአገልግሎት ድርሻ አብረው ሊሳሉ ችለዋል። ቅዱስ ያሬድም በድጓው "አርባእቱ እንስሳ አልቄንጥሩ እንደሚባለው ንስር ፊት ለፊት አይታዩም አንዱም በመራቸው ይሔዳሉ እነርሱም እያንዳንዳቸው አራት ገጽ ሲኖራቸው ሳያርፉና ሳይደክሙ የሚያመሰግኑ ናቸው" በማለት ጽፏል። አንድም መላእክት ነገደ ሱራፌል እና ነገደ ኪሩቤል በመባል ይከፈላሉ። በነገደ ሱራፌል እነ ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ሩፋኤል ወዘተ ሲሆኑ በነገደ ኪሩቤል ደግሞ ቅዱስ ገብርኤል ቅዱስ ራጉኤል ወዘተ ያጠቃልላል። ስለዚህ ቅዱስ ራጉኤል ነገዱ ከነገደ ኪሩቤል ነው በዚህም ላይ የነገደ ኪሩቤል አልቄንጡራ (አራት እራስ ንስር) አለቃቸው ቅዱስ ራጉኤል ነው። በዚህም ምክንያት አብረው ሊሳሉ ችሏል። አንድም መላእክትን ሁሉ እንደ እየስራቸው መለያ ስነ ሥዕላቸውን መሳል ልማድ ነውና። ለምሳሌ ቅዱስ ሚካኤል ከቅድስት አፎምያ ጋር፣ ቅዱስ ገብርኤል ከሠለስቱ ደቂቅ ጋር፣ ቅዱስ ዑራኤል ከእዝራ ሱቱኤል ጋር እንደሚሳሉት ሁሉ ማለት ነው። በዚህም መሰረት ቅዱስ ራጉኤልም ዐቃቤ መንበር ነውና መንበሩን በሚሸከሙት ኪሩቤል ከሚመሰሉት ንስሮች ጋር አብረው ሊሳሉ ችለዋል፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ራጉኤል ከአምላክ የተሰጠው ቃል ኪዳን እግዚአብሔር አምላክ በስሙ ለታመኑት ቅዱሳን፣ ጻድቃን፣ ሰማእታት፣ ሐዋርያት፣ ዘወትር ያለማቋረጥ ስሙን ለሚጠሩት ቅዱሳን መላእክት ሁሉ ቃል ኪዳን ሰጥቷቸዋል። የሰጣቸውም ቃል ኪዳን ዘላለማዊ እና ሊሻር የማይችል ነው። ለመላእክት አለቃ ለቅዱስ ራጉኤልም ይህን ቃል ኪዳን ሰጥቶታል "የራጉኤል አምላክ ይቅር በለኝ በማለት አንዲት ቃልስ እንኳን ቢናገር እንደ ወዳጄ እንደ አብርሃም፣ እንደ ባለሟሌም እንደ ይስሐቅ፣ እንደ አከበርኩትም እንደ ያዕቆብ ክብርን ባለሟልነትን እሰጠዋለሁ በራሱ ላይም አክሊል አቀዳጀዋለሁ እረጅም ዘመናት ሰፊ ወራትም እሰጠዋለሁ" ሲል ቃሉን ሰጥቶታል፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ራጉኤል መስከረም 1 ቀን ከሊቃነ መላእክት በ4ተኛ ደረጃ የተሾመበት ዕለት ነው። ግንቦት 1 ቀን ለታላቁ አባት ለሄኖክ ምሥጢራትን የገለጸበት በዓሉ ነው፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ጻድቁ_ኢዮብ በዚችም ዕለት ኢዮብ በፈሳሽ ውኃ ታጥቦ ከደዌው ሁሉ ተፈወሰ። ይህም ለሰዎች ልማዳቸው ሁኖ ዓመቱ ዙሮ ሲመጣ ፈሳሹ ውኃም በመላ ጊዜ በአዲስ ውኃ ይጠመቃሉ በእርሱም ይባረካሉ። ጻድቁ ኢዮብ በዘመኑ እንደርሱ ያለ ዕውነተኛ ደግ ሰው እንደ ሌለ በቅዱሳት መጻሕፍትም ስለርሱ እንደተነገረ እግዚአብሔር መሰከረለት። ሰይጣንም ቀንቶበት በገንዘቡና በልጆቹ ላይ ያሠለጥነው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር ለመነ። የጻድቅ ኢዮብን ትዕግሥት እግዚአብሔር ስለሚያውቅ አሠለጠነው ለመጪ ትውልድም አርአያና ምሳሌ እንዲሆን ፈቀደለት። ስለርሱም ሐዋርያ ያዕቆብ በመልእክቱ እነሆ የጻድቅ ኢዮብን ትዕግሥቱን ሰምታችኋል አለ። ከዚህ በኋላም በአንዲት ቀን ገንዘቡ ሁሉ ጠፋ ሥጋውም በደዌ ሥጋ ከራሱ እስከ እግሩ ድረስ ተመታ። በዚህም በአስጨናቂ ደዌ ውስጥ ኖረ እግዚአብሔርንም አመሰገነው። አንዲት ቃልን እንኳ በፈጠረው እግዚአብሔር ላይ አላጉረመረመም ነገር ግን የተወለደባትን ቀን ረገመ። እንስሶቹና ገንዘቡ ሁሉ በጠፋ ጊዜ እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔርም ነሣ የእግዚአብሔርም ስም የተመሰገነ ይሁን አለ።

ስለ ክብር ባለቤት ስለ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ ስለመቀበሉ በዚያችም ቀን ስለ ፀሐይ መጨለም ከዚያም በኋላ እስራኤልን ስለሚደርስባቸው መከራ፣ ኀዘን፣ ልቅሶ፣ ረድኤትም እንደሚአጡ የእግዚአብሔርንም ቃል መስማትን ከማጣት የተነሣ እንደሚራቡና እንደ ሚጠሙ። በሀገሩ ሁሉ በአሕዛብም መካከል እንደሚበተኑ አሕዛብም እንደ አጃ ሸክሽከው እንደሚአጓልቧቸው ትንቢትን ተናገረ ትንቢቱም በላያቸው ተፈጸመ። ስለኃጢአታቸውና ስለ ክፉ ሥራቸው፣ ስለ ዘለፋቸው እነርሱ እንደ ገደሉት ተነገረ። የትንቢቱም ዘመን ከጌታችን ሥጋዌ በፊት በስምንት መቶ ዓመት ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ያዕቆብ_ዘምስር (ግብፅ) ዳግመኛም በዚህች ቀን ንጹሕ ድንግል አባት የምስር አገር ኤጲስቆጶስ አባ ያዕቆብ አረፈ። ይህም ተጋዳይ የሆነ አባት ገና በታናሽነቱ የምንኵስናን ልብስ ይለብስ ዘንድ ነፍሱ ወደደች። ከሀገሩም ወጥቶ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደና በአባ ዮሐንስ ሐጺር በዓት ውስጥ ኖረ በዚያም ጽኑዕ በሆነ ገድል ብዙ ዘመናት ተጠምዶ ኖረ። ከዚህም በኋላ በአባ ዮሐንስ ሐጺር ቤተ ክርስቲያን ላይ ሊቀ ዲያቆናት አድርገው ሾሙት የደግነቱ፣ የትሩፋቱና የቅድስናውም ዜና ተሰማ። በእግዚአብሔርም ፈቃድ በምስር አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት። በሹመቱ ወንበርም በተቀመጠ ጊዜ ጾምን ጸሎትን ጨመረ ስለ ሹመቱም ተጋድሎውንና አገልግሎቱን ከቀድሞው አበዛ እንጂ ቸልል አላለም። ሕዝቡንም ሁልጊዜ ያስተምራቸዋል መጻሕፍትንም ያነብላቸዋል ከእነርሱ ሥውር የሆነውንም ይተረጒምላቸዋል። ኃጢአትን በመሥራት የሚኖሩትን ይገሥጻቸዋል፤ በንስሐ እስከሚመለሱም ሥጋውንና ደሙን ከመቀበል ያርቃቸዋል ። በጎ ተጋድሎውንም በፈጸመ ጊዜ ጥቂት ታመመ መንጋዎቹንም ጠርቶ በቀናች ሃይማኖት እንዲጸኑ አዘዛቸው ደግሞ ካህናቱን ጠርቶ በጸሎትና በቅዳሴ ጊዜ ቸለል እንዳይሉ አዘዛቸው። ሁለተኛም ሥጋውንና ደሙን ለማክበር በንጽሕና እግዚአብሔርን በመፍራት ሁናችሁ ካላገለገላቸሁ ከደማችሁ ንጹሕ ነኝ አላቸው። ከዚህም በኋላ ፊቱንና ደረቱን በመስቀል ምልክት አማተበ እጆቹንም ዘረጋ ዐይኖቹንም ራሱ ከደነና በሰላም አረፈ በአማሩ ልብሶችም ገነዙት ታላቅ ልቅሶንም አልቅሰው በክብር በምስጋና በማወደስ ቀበሩት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ጳጒሜን_5 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጳጒሜን አምስት በዚህች ቀን #የአባ_በርሱማ፣ #የነቢዩ_አሞጽ እና #የአባ_ያዕቆብ_ዘምስር የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_በርሱማ ጳጒሜን አምስት በዚህች ቀን የከበረ አባት ከልብስ ተራቁቶ የሚኖር የብርቱ ልጅ አባ በርሱማ አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ በምስር አገር እጅግ ባለጸጎች ነበሩ እነርሱም እግዚአብሔርን የሚፈሩ መጻተኞችንም በፍቅር የሚቀበሏቸው በእግዚአብሔርም በሕጉ ሁሉ ጸንተው የሚኖሩ ናቸው። ይህን ቡሩክ በርሱማን በወለዱት ጊዜ በፈሪሀ እግዚአብሔር የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትንም ሁሉ በማስተማር አሳደጉት። ከዚህም በኋላ ወላጆቹ አረፉ የእናቱም ወንድም ወላጆቹ የተውለትን ገንዘብ ሁሉንም ወሰደ አባ በርሱማም አባትና እናቱ የተውለትን ገንዘብ የእናቱ ወንድም እንደ ወሰደ አይቶ የዓለምን ኃላፊነት አሰበ። እንዲህም አለ መድኃኒታችን ነፍሱን ሊያድን የሚወድ ይጣላት ስለእኔም ሰውነቱን የጣላት ያገኛታል ብሏል። ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጠፋ ምን ይጠቅመዋል ወይስ ሰው ስለ ነፍሱ ቤዛ ምን በሰጠ ነበር። የሰው ልጅ በአባቱ ጌትነት ከመላእክቶቹ ጋር ይመጣ ዘንድ አለውና ያን ጊዜም ለሁሉ እንደ ሥራው ይከፍለዋል። ይህንንም ብሎ ከዓለም ወጣ በበጋ ቃጠሎ፣ በክረምት ቅዝቃዜ ልብስ ሳይለብስ በአምስት ኮረብታዎች ላይ ኖረ። ወገቡንም በማቅ መታጠቂያ ይታጠቃል በልቡም እንዲህ ይላል በርሱማ ሆይ በሚያስፈራ ዕውነተኛ ፈራጅ ፊት ትቆም ዘንድ አለህ እኮን። ሁልጊዜም በጾም በጸሎት በስግደት በቀንና በሌሊት ይተጋ ነበር። በሚመገቡም ጊዜ በውኃ የራሰ ደረቅ ቂጣ ይመገባል ቆዳውም ከአጥንቱ ጋር ተጣበቀ። ከዚያም ቦታ ሊሸሽ ወደደ ከንቱ የሆነ የሰውን ምስጋና ፈርቷልና በምስር ወዳለት የቅዱስ መርቆሬዎስ ቤተ ክርስቲያን ደረሰ በዚያም በጾም በጸሎት በስጊድ እየተጋደለ ሃያ አምስት ዓመት ኖረ። በዚያችም ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በዋሻ ውስጥ ታላቅ ዘንዶ አለ ዘንዶውንም ከመፍራት የተነሣ ሰው መብራትን ማብራት የማይችል ነው። እግዚአብሔርም የዚህን ቅዱስ የአባ በርሱማን ደግነቱን ሊገልጥና በእጆቹም ድንቆች ተአምራትን ለማድረግ በወደደ ጊዜ አባ በርሱማ ወደዚያች ዋሻ ገባ ወደ እግዚአብሔርም እንዲህ ብሎ ጸለየ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ እባቡን ጊንጡን እንረግጥ ዘንድ በጠላት ኃይል ላይ ሁሉ ሥልጣንን የሰጠኸን አንተ ነህ። አሁንም በዚች ዋሻ ውስጥ በሚኖር ከይሲ ላይ ታሠለጥነኝ ዘንድ እለምንሃለሁ ላንተም ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ። ከዚህም በኋላ ራሱን በመስቀል ምልክት አማተበ እንዲህም እያለ ዘመረ በተኲላና በእባብ ላይ ትጫማለህ አንበሳውንና ዘንዶውን ትረግጣለህ። ከዚህም በኋላ ያንን ዘንዶ በእጁ ይዞ እንዲህ አለው ከእንግዲህ ገራም ሁን ታጠፋ ዘንድ ሥልጣን አይኑርህ ኃይልም ቢሆን በማንም ላይ ከሰው ወገን በአንዱ ላይ ክፉ ሥራ አታደርግ የሚሉህን ሰምተህ የምትታዘዝ ሁን እንጂ በዚያን ጊዜም አንበሶች ለነቢዩ ዳንኤል እንደተገዙ ያ ዘንዶ ከአባ በርሱማ እግሮች በታች ተገዢ ሆነ። ከዚህም በኋላ አባ በርሱማ በመራብ በመጠማት ተጋድሎውን ጨመረ በየሁለት ቀን፣ በየሦስት ቀን፣ በየሰባት ቀን እያከፈለ ብርሃን በላዩ እስቲወጣ ያለ ማቋረጥ የሚጾም ሆነ። ለጸሎት በሚቆም ጊዜ ከይሲው ከርሱ ይርቃል በሚቀመጥም ጊዜ ሲጠራው ወደርሱ ይመጣል። በዚችም ቤተ ክርስቲያን አካባቢ የውኃ ጒድጓድ አለች ወደርሷ በመውረድ ሁል ጊዜ ከማታ እስከ ንጋት ከውስጧ ገብቶ ያድራል በክረምትም በበጋም እንደዚህ ያደርጋል መላዋን ሌሊትም በውስጥዋ እየጸለየ ያድራል። የሚመገበውም የደረቀና የሻገተ ቂጣ ሲሆን የሚጠጣውም የከረፋ ውኃ ነው። የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን አዘውትሮ ያነባል ይልቁንም የዳዊትን መዝሙር አባቶችም ሥጋቸውን ለማድከም ያደረጓቸውን ትኀርምቶች በማንበብ ስለዚህ ትኀርምትን ንጽሕናን ወደደ ለሰዎችም እንዲህ እያለ ጠቃሚ ሥራዎችን ያስተምራል ያለ ልብ ንጽሕና በቀር አንዱ እንኳን የእግዚአብሔር መንግሥት ማየት አይችልም ኃጢአት ሁሉ ከንስሓ በኋላ ይሠረያልና። ለክርስቲያን ወገኖችም እንዲህ ያስተምራቸዋል ከእግዚአብሔርም ተአምራት የማድረግ ሀብት ተሰጠው ከገድሉም ለሰው የገለጥነው ጥቂቱን ነው። የዚህም አባት አርአያው የሚያምር መልኩም በብርሃን ያሸበረቀ ገጽታው ደስ የሚል ነው። ጥሪት በማጣቱም ደስ ይልዋልና። ከዓለማዊ ልብስ የተራቆተ ዓለምን ከማግኘትም የራቀ ነው። ቀድሞ ከቤቱ ከወጣ ጀምሮ የቀይ ግምጃ ጨርቅ በማገልደም ሥጋውን ይሸፍናል በክረምትም በበጋም የቀን ሐሩርን የሌሊት ቊርን ይታገሣል በጐኑና በምድር መካከል ምንጣፍ አላደረገም ወደ ሕይወት አገር ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት የሚያደርስ ተጋድሎን እንደዚህ ተጋደለ። ከክፉዎች ሰዎችና ከክፉዎች አጋንንት ብዙ ጊዜ ኀዘን ፈተና አግኝቶታል ከዚህም ሁሉ ጋር በዚህ ጭንቅ በሆነ ሥራ የረዳው እግዘሐአብሔርን ፈጽሞ ያመሰግነዋል። ይህንን በጎ የገድል ጒዞ በተጓዘ ጊዜ ሰዎት ዜናውን ሰሙ ሽማግሎችም ጐልማሶችም ከእነርሱ በጽነት የተሰነካከለ ወይም ከጠላት ሰይጣን ፈተና ያገኘው ወይም የመንፈስ ደዌ ያገኘው ሁሉ መሪና አጽናኝ ይሆናቸው ዘንድ ተመኝተውት ፈለጉት ከእርሱ ፈውስ ያገኙ ዘንድ መጡ። ይህ የከበረ አባ በርሱማ በዚህ የጽና ተጋድሎ ሠላሳ ዓመታትን በፈጸመ ጊዜ እግዚአብሔርንም አገልግሎ ከዚህ በኋላ ጳጒሜን አምስት በዚች ቀን በሺህ ሠላሳ ሦስት ዓመተ ሰማዕታት በሰላም በፍቅር አንድነት አረፈ። ከዚህ አስቀድሞ ደቀ መዝሙሩ ቀሲስ ዮሐንስ በልቡ እንዲህ አለ ከአባታችን በርሱማ በኋላ እንግዲህ ስዎችን ማን ያጽናናቸዋል። ደቀ መዝሙሩ ያሰበውን በመንፈስ ቅዱስ አውቆ በንጹሕ አንደበቱ እንዲህ ብሎ መለሰለት። ልጄ ዮሐንስ ሆይ የቶባል ልጅ አባ በርሱማ ብሎ ስሜን የሚጠራኝን ሁሉ ከእሳቸው እንደማልርቅ ዕወቅ እኔ እነሆኝ ብዬ የክብር ባለቤት ከሆነ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ የሚሻውን ሁሉ እፈጽምለታለሁ። ከዚህም በኋላ ወደ ግራው ተመልክቶ እነሆ ፈለጉብን ተመራመሩን ከክፋ ሥራ ምንም ምን በእኛ ላይ አላገኙም አለ። ከዚህም በኋላ ደግሞ ደቀ መዝሙሩ አብርሃምን ቢላዋ ወይም መቊረጭት ስጠኝ አለው መቁረጫውንም ተቀብሎ ምላሱን ቆርጦ ጣላትና እግዚአብሔር ብርሃኔና መድኃኒቴ ነው የሚያስፈራኝ ምንድነው የሚለውን መዝሙር እስከ መጨረሻው ይዘምር ጀመር። ከዚህም በኋላ አዳኝ በሆነ መስቀል ምልክት ፊቱን አማተበ ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ ብርሃናውያን መላእክትም የከበረች ንጽሕት ነፍሱን ተድላ ደስታ ወደ ሚገኝባት ገነት አሳረጓት። መነኰሳቱም ከበግ ጸጒር በተሠራ ንጽሕ በሆነ በነጭ ባና ገነዙት ተሸክመውም ወስደው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት። ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰማንያኛ የሆነ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስ መጣ ከእርሱ ጋርም ኤጲስቆጶሳት ቀሳውስትና ዲያቆናት የምስር አገር ታላላቆችና ብዙ የክርስቲያን ወገኖች በአንድነት ሁነው በመዘመርና በማመስገን በታላቅ ክብር ሥጋውን ገንዘው ቀበሩት። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ነቢዩ_አሞጽ በዚችም ቀን ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ አሞጽ ነቢይ አረፈ። ይህም ዕውነተኛ ነቢይ በእስራኤል ነገሥታት በኢዮአስና በኦዝያ ዘመን አስተማረ የእስራኤልንም ልጆች የእስራኤልንና የይሁዳንም ነገሥታት ይገሥጻቸው ነበር።

🔴#ስንክሳር ጳጒሜን_4 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጳጒሜን አራት በዚህች ቀን #የአባ_ባሞይን (#አባ_ጴሜን)ና #የ6ቱ_ወንድሞቹ እንዲሁም #የሮሜ_ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_ሊባርዮስ የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ባይሞን (#አባ_ጴሜን) ጳጒሜን አራት በዚህች ቀን ተጋዳይ አባ ባይሞን አረፈ። ይህም ቅዱስ ከምስር ሀገር ነው ስማቸው ዮሐንስ፣ ኢዮብ፣ ዮሴፍ፣ ላስልዮስ፣ ያዕቆብ፣ አብርሃም የሚባል ስድስት ወንድሞች አሉት ሁሉም መነኰሳት ሁነዋል። ከእሳቸውም ዮሐንስ ይልቃል ነገር ግን በእውቀትና በጥበብ ባይሞን ይበልጣል። ሁሉም ተስማምተው ከዓለም ወጡ ከሰውም ሩቅ በሆነ ቦታ የሚኖሩ ሆኑ የክብር ባለቤት የሆነ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ቀንበር ተሸክመው ከዘመድም ተለይተው በጠባብ መንገድ ተጓዙ። እናታቸውም ልታያቸው ወዳ ወደ በዓታቸውም ደርሳ በውጭ ቆመች ወደርሷም መጥተው እንድታያቸው ላከችባቸው እነርሱም ወደርሷ እንዲህ ሲሉ ላኩ በዚህ በኃላፊው ዓለም ልታይን ከወደድሽ በወዲያኛው ልታይን አትችይም እርሷም አስተዋለች አልመለሰችላቸውም መንገዷን ተጓዘች። ይህም አባት ባይሞን በአስቄጥስ ገዳም ለሽማግሌዎችም ለጐልማሶችም አረጋጊ ወደብ ሆነ። ከጠላት ሰይጣን ፈተና የሃይማኖት ጥርጥር ወይም ደዌ ያገኘው ሁሉ ወደርሱ ይመጣል ወዲያውኑ ያረጋጋዋል ከደዌውም ይፈውሰዋል። ይህም አባት በምንኲስና ሕግ ስለ መጋደል ስለ አምልኮም ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትን ደረሰ። በትምህርቱም እንዲህ አለ የተሰነካከለ ወንድምን ብታይ ስለርሱ ተስፋ አትቁረጥ ልቡን አንቃለት እንጂ ከወደቀበትም እንዲነሣ አጽናንተህ ሸክሙን አቃልለት። አፍህ የተናገረውን ይሠራ ዘንድ ልብህን አስተምረው አለ። አንድ ወንድም እንዲህ አለው ሥራው መልካም የሆነ ወንድም ያየሁ እንደሆነ ደስ ይለኛል ወደቤቴም አስገብቼ ባለኝ ነገር ደስ አሰኘዋለሁ። ግን ሥራው ብልሹ የሆነ ወንድም ያየሁ እንደሆነ አልፈቅደውም ወደ ቤቴም አላስገባውም። አባ ባይሞንም እንዲህ ብሎ መለሰለት ሥራው በጎ ለሆነው እንዳረግኸው ለዚህም ሥራው ብልሹ ለሆነው ዕጥፍ አድርገህ በመሥራት ደስ አሰኘው ለታመመ መድኃኒት ያደርጉለት ዘንድ ይገባልና። ከዚህም በኋላ ለዚያ ከርሱ ጋር ለሚነጋገር ወንድም እንዲህ ብሎ ነገረው በመነኰሳት ገዳም ስሙ ጢሞቴዎስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ በኃጢአትም ወድቆ አቤቱ ይቅር በለኝ እያለ የሚጮህና የሚያለቅስ ሆነ። ከሰማይም እንዲህ የሚል ቃል መጣ አንተ ወንድምህን በመከራው ጊዜ ቸለል ያልከው ባትሆን እኔ ባልጣልኩህም ነበር። ይህ አባት ደግሞ እንዲህ አለ እኛ የወንድማችን በደል ብንሰውር እግዚአብሔርም በደላችንን ይሠውርልናል። ይህም አባት ዕድሜውን በተጋድሎና በትሩፋት ሥራ ከፈጸመ በኋላ ወደ መልካም ዕርግና ደርሶ እግዚአብሔርን አገልግሎ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሊቀ_ጳጳሳት_አባ_ሊባርዮስ_አረፈ ዳግመኛም በዚችም ቀን የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት አባ ሊባርዮስ አረፈ። ይህም አባት አርዮሳዊ በሆነ በሁለተኛው ቈስጠንጢኖስ ዘመን ተሾመ። የቈስጠንጢኖስም ወንድሙ ቊንስጣ በሮሜ ነግሦ ነበር። ሐዋርያዊ አትናቴዎስንና ጳውሎስን ከመንበረ ሢመታቸው በአሳደዳቸው ጊዜ እነርሱም ወደዚህ አባት ሊባርዮስ መጡ። ይረዳቸውም ዘንድ ለመኑት እርሱም ተቀበላቸው ከደብዳቤ ጋርም ወደ ንጉሥ ቊንስጣ ላካቸው ንጉሡም ደብዳቤያቸውን ተቀብሎ በጎ ነገር እንዲያደርግላቸው ወደ መንበረ ሢመታቸውም እንዲመልሳቸው ወደ ወንድሙ ቈስጠንጢኖስ ደብዳቤ ጻፈላቸው። እርሱም የወንድሙን ደብዳቤ በአነበበ ጊዜ አትናቴዎስን ወደ መንበረ ሢመቱ እስክንድርያ፣ ጳውሎስንም ወደ መንበረ ሢመቱ ቊስጥንጥንያ መለሳቸው። ከዚህም በኋላ ቊንስጣ ንጉሥ በዓመፀኞች በተገደለ ጊዜ ቈስጠንጢኖስ ወደዚህ አባት ሊባርዮስ መልእክት ላከ ሐዋርያዊ አትናቴዎስን ያሳድደው ዘንድ የአርዮስንም ወገን እንዲቀበላቸው ብዙ ቃል ኪዳናትንም ገባለት እርሱ ግን አልተቀበለውም በምክሩም ከእርሱ አልተስማማም። ስለዚህም ይህን አባት ሊባርዮስን ሩቅ አገር አጋዘው። ከዚህም በኋላ ወንዱሙ ቈንስጣን የገደለውን ጭፍራ ልኮ ገደለው። ከዚህም በኋላ ቈስጠንጢኖስ ወደ ሮሜ ከተማ ሔደ ስለዚህ አባት ሊባርዮስም የገዳማትና የአድባራት ሊቃውንት ካህናቱም ሁሉ ወደ መንበረ ሢመቱ ይመልሰው ዘንድ ንጉሡን ለመኑት እርሱም ምልጃቸውን ተቀብሎ ወደ መንበረ ሢመቱ መለሰው። ይህ አባት ወደ መንበሩ በተመለሰ ጊዜ በቀናች ሃይማኖት ይጸኑ ዘንድ ሁልጊዜ መንጋዎቹን ማስተማር ጀመረ ብዙ ድርሳናትንና ተግሣጻትንም ደረሰ የአርዮስ ወገኖችንም እየተቃረናቸው ኖረ ያወግዛቸውና ያሳድዳቸውም ነበር። ከስደት ከተመለሰ በኋላ በሰባት ዓመት በሰላም አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

ሐዋርያት ሆይ በእግዚአብሔር ፊት እስከምትቆሙ እጠብቃችሁ ዘንድ ከእኔ ርዳታን ሹ። የዚህ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሩፋኤል ተአምራቶቹ ብዙ ናቸው ስለእኛ ይማልድ ዘንድ የበዓሉን መታሰቢያ ልናደርግ ይገባናል። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_መልከጼዴቅ በዚህችም ቀን ለእግዚአብሔር ልጅ ምሳሌው የሆነ የመልከጼዴቅ መታሰቢያው ነው። መልከጼዴቅም ዐሥራ አምስት ዓመት በሆነው ጊዜ ከአዳም ሥጋ ጋር እንዲልከውና በምድር መካከል እንዲያኖረው እግዚአብሔር ኖኅን አዘዘው እርሷም ቀራንዮ ናት። የዓለም መድኃኒት ክርስቶስም መጥቶ በዚያ እንደሚሠዋ አዳምንም ከልጆቹ ሁሉ ጋር እንደሚያድነው አመለከተው። ከዚህም በኋላ በአባቱ በኖኅ ትእዛዝ ሤም መልከጼዴቅን በሥውር ወሰደው የእግዚብሔርም መልአክ እየመራቸው ሔደው ወደ ቀራንዮ ተራራም አደረሳቸው መልከጼዴቅም ክህነትን ተሾመ። ዐሥራ ሁለት ደንጊያዎችንም ወስዶ መሠዊያ ሠራ ከሰማይ የወረደለትንም ኅብስትና ወይን መሠዊያ በሠራቸው ደንጊያዎች ላይ መሥዋዕትን አሳረገ። ምግቡንም መላእክት ያመጡለታል ልብሱም ዳባ ነው በአባታችን አዳም ሥጋ ዘንድ ሲያገለግል ኖረ። አብርሃምም ከጦርነት ነገሥታትን ድል አድርጎ በተመለሰ ጊዜ ኅብስትንና ወይንን አቀረበለት አብርሃምም ከገንዘቡ ሁሉ ከዐሥር አንድ ሰጠው እርሱ ካህንም ንጉሥም ሁኖ ተሹሟልና። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አፄ_ዘርዓ_ያዕቆብ_ጻድቁ በዚህችም ቀን የኢትዮጵያ ንጉሥ መልካም ስም አጠራር ያለው ዘርዐ ያዕቆብ አረፈ። ዘርዐ ያዕቆብ ብሎ ስሙን መልአክ ነው ያወጣለት፡፡ ሲወለድም ብርሃን ቤቱን ሞለቶት ታይቷል፡፡ ግማደ መስቀሉን ከአባቱ ከዐፄ ዳዊት ተረክቦ በማስመጣት በግሸን አስቀምጦታል፡፡ ንግሥቲቱ የዐፄ ዳዊት ሚስት የጻድቁን የደብረ ቢዘኑን የአቡነ ፊሊጶስን እግራቸውን አጥባቸው ስትጨርስ የእግራቸውን እጣቢ ከጠጣችው በኃላ የእምነቷን ጽናትና ጥልቀት አይተው ጻድቁ ባደረባቸው መንፈስ ቅዱስ ትንቢትን በመናገር "ከማኅፀንሽ ፍሬ ታላቅ ጻድቅ ልጅ ይወጣል" ብለው ትንቢት ነገሯት፡፡ በትንቢታቸውም መሠረት ታላቁ ጻድቅ ንጉሥ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ተወልዱ፡፡ ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ለሀገራችንም ሆነ ለቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ ውለታ ውለዋል፡፡ ጣዖት አምልኮን ከሃገራችን ለማጥፋት ብዙ ሺህ ካህናትን አሰልጥነው በመላ አገራችን አሰማርተዋል፡፡ የኑፋቄ ችግሮችን ለመቅረፍ ጉባኤያትን አዘጋጅተዋል፡፡ ተአምረ ማርያምን ጨምሮ ከ11 ያላነሱ መጻሕፍትን በመንፈስ ቅዱስ አጋዥነት ደርሰው ለአገልግሎት አብቅተዋል፡፡ ብዙ መጻሕፍትን ከውጪ አስመጥተው አስተርጉመዋል፡፡ ሰው ሁሉ ለእመ ብርሃንና ለቅዱስ መስቀሉ ፍቅር እንዲገዛ ጥረት አድርገዋል፡፡ እመቤታችንን በፍጹም ልባቸው ከመውደዳቸው የተነሳ ዛሬም ድረስ በሃገራችን ድንግል ማርያም "የዘርዓ ያዕቆብ እመቤት" እየተባለች ትጠራለች፡፡ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አንጸው ብዙ ሥርዓቶችም በሊቃውንት እንዲሠሩ አድርገው ሌሎች ብዙ በጐ ተግባራትንም ፈጽሞ በዚህች ዕለት በሰላም ዐርፈዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ሰራጵዮን_ዘሰንዱን በዚህችም ቀን ሰንዱን ከሚባል አገር ቅዱስ ሰራጵዮን አረፈ። ይህም ቅዱስ ከታናሽነቱ ጀምሮ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን ትርጓሜያቸውንም ተማረ የዚህንም ዓለም ገንዘብ ሁሉ ትቶ ወደ አረሚ አገር ሔደ ራሱንም በሃያ ብር ሸጦ ማገልገል ጀመረ የሽያጩንም ዋጋ ጠበቀው። እንጀራ ሳይበላ ውኃ ሳይጠጣ ከስሕተታቸው ይመልሳቸው ዘንድ ሁል ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ነበር። ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት በሆነ በክርስቶስ አሳመናቸው ሕግንና ሥርዓትንም ሁሉ አስተማራቸው ከዚህም በኋላ ስለርሳቸው ራሱን ባሪያ አድርጎ እንደሸጠ እንጂ እርሱ ባሪያ እንዳልሆነ ነገራቸው ሽያጩንም ለድኆች እንዲሰጡት ሰጣቸው። ከዚህም በኋላ መንካያውያን ወደሚባሉ ሕዝቦች ሒዶ ለነርሱም ራሱን ሸጠ የክብር ባለቤት ወደሆነ ክርስቶስ እምነት እስከመለሳቸው ድረስ ተገዛላቸው። ከዚህም በኋላ ደግሞ ወደ ሮሜ አገር ሒዶ በሰላም እስከ አረፈ ድረስ በጾምና በጸሎት እየተጋደለ ኖረ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በመልአኩና በቅዱሳኑ አማላጅነት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ጳጒሜ_3 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጳጒሜን ሦስት በዚህች ዕለት የሰዎች ሁሉ ጸሎት የሚያርግባት #ርኅወተ_ሰማይ ትባላለች፣ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ #ቅዱስ_ሩፋኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው፣ ለእግዚአብሔር ልጅ ምሳሌው የሆነ #የካህኑ_መልከጼዴቅ መታሰቢያው ነው፣ የኢትዮጵያ ንጉሥ መልካም ስም አጠራር ያለው #ቅዱስ_ዘርዐ_ያዕቆብ አረፈ፣ ሰንዱን ከሚባል አገር #ቅዱስ_ሰራጵዮን አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ርኅወተ_ሰማይ ጳጒሜን ሦስት በዚህች ዕለት የሰዎች ሁሉ ጸሎት የሚያርግባት፣ አራተኛው መጋቢ ኮከብ የሚያልፍባት፣ ለሰው ልጆች ከፈጣሪያቸው ጸጋ በረከት የሚሰጥባት ዕለት ስለሆነች ርኅወተ ሰማይ (ሰማይ የሚከፈትባት) ቀን ትባላለች። አሁን በሰማይ መዘጋት መከፈት ኑሮበት አይደለም። የሰው ልጆችን ልመና ቅዱሳን መላእክት ያለ ከልካይ የሚያሳርጉበት አንድም ቅዱስ ሩፋኤል የዓመቱን የጸሎት መዝገብ የሚከፍትበት ቀን ስለሆነ እንዲህ ተባለ እንጂ። እመቤታችን ድንግል ማርያም ለአጼ ናዖድ እንደ ነገረቻቸው በዚህች ዕለት ሁሉም ቅዱሳን ስለሚታሰቡ፣ የእግዚአብሔር የምሕረት መዝገቡ ስለሚከፈት፣ ዕለቷን ክብርት ያሰኛታል። በቅዱስ ሩፋኤል አበጋዝነት (መሪነት) በዚህች ዕለት ለዓመት የሚበቃ ምሕረት ይገኛል። ስለዚህም አባቶቻችን በዚህች ሌሊት ሦስት መቶ ስልሳ አምስት አቡነ ዘበሰማያትን ሲጸልዩ ያድራሉ። በሌላ ወገን ደግሞ የጌታ ዳግም ምጽዓቱ መታሰቢያ እንደ መሆኗ ትልቅ ትኩረትም ይሰጣታል። ቸሩ ጌታችን ከተከፈተች ገነት ከተነጠፈች ዕረፍት ሁላችንንም ያድርሰን። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ሩፋኤል_ሊቀ_መላእክት በዚህች ቀን የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ የሩፋኤል የበዓሉ መታሰቢያ ነው። እርሱም ከመላእክት አለቆች ሦስተኛ የሆነ ነው። ደግሞም ከእስክንድርያ ውጭ በደሴት የታነፀች ቤተ ክርስቲያኑ በከበረ ሊቀ ጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን በውስጧ ተአምር የተገለጸባት የከበረችበት ነው። ይህም እንዲህ ነው ሀብታም ሴት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ መጥታ ሳለ ከእርሷ ጋርም ብዙ ሰው ነበረ። ከባሏም የወረሰችው ብዙ ገንዘብ አላት በሊቀ ጳጳሳቱ ቤት አንጻር ያለውን ኮረብታ አስቆፈረችው በጥቅምት ወር ዐሥራ ስምንት ቀን እንደጻፍን የወርቅ መዝገብ ተገለጠ። በዚያም ወርቅ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትን አነፀ ከእርሳቸውም አንዲቱ የመላእክት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ ሩፋኤል በስሙ የታነፀች ይህች ናት። ሥራዋንም በፈጸመ ጊዜ እንደዛሬው በዚች ቀን አከበራት። ብዙ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጸች ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና። የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው። ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔርም በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ ያን ጊዜ ይህ የከበረ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ እንዲህ አለው እግዚአብሔር አዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጽ ጸጥ ብለህ ቁም። አንበሪውም ጸጥ ብሎ ቆመ አልታወከም በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆነ። ይቺም ቤተ ክርስቲያን እስላሞች እስከተነሡበት ዘመን ኖረች ከዚህም በኋላ ሁለተኛ ያ አንበሪ ተናወጸ ደሴቲቱም በላይዋ ከሚኖሩ ብዙ ሕዝብ ጋራ ሠጠመች። #ዳግመኛም የቊስጥንጥንያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስ ጻድቅ ለሆነ ንጉሥ አኖሬዎስ ተናገረ። እንዲህም አለው ንጉሥ ሆይ እኛ ወዳንተ ልንመጣ በመርከብ እንደተሳፈርን ዕወቅ በጒዞ ላይ ሳለንም በቀዳሚት ሰንበት ቀን በደሴት ውስጥ ታናሽ ቤተ ክርስቲያን አየን ወደ ወደቡም ደርሰን በዕለተ እሑድ ሥጋውን ደሙን እንቀበል ዘንድ ወደርሷ ሔድን። ለዚያች ቤተ ክርስቲያንም በጐኗ ታናሽ ገዳም አገኘን በውስጧም ወንድሞች መነኰሳት አሉ በክብር ባለቤት ጌታችንም ፈቃድ ወደ ርሳቸው ደረስን ። መነኰሳቱንም በቀደሙ አባቶች ዘመን የተጻፈ አሮጌ መጽሐፍ በእናንተ ዘንድ እንዳለ እጽናናበት ዘንድ እርሱን ሰጡኝ አልኳቸው። እንዲህም ብለው መለሱልኝ እኛ ትርጓሜያቸውን የማናውቀው መጻሕፍቶች በዕቃ ቤት አሉ። እኔም አያቸው ዘንድ ወደዚህ አምጡልኝ አልኳቸው። በአመጡአቸውም ጊዜ መረመርኳቸው ጌታችንም በደቀ መዛሙርቱ ፊት ያደረጋቸውን ኃይሎችና ድንቆች ተአምራቶችን ስለ ሰማይና ምድርም ጥንተ ተፈጥሮ አገኘሁ። ሁለተኛም ስመረምር ስለ ሰባቱ ሊቃነ መላእክት ሹመትና መዐርግ አባቶቻችን ንጹሐን ሐዋርያት የጻፉትን አገኘሁ ይኸውም ጌታችን በደብረ ዘይት ከእሳቸው ጋራ እያለ የመለኮቱን ምሥጢር በገለጠላቸው ጊዜ። ሐዋርያትም እንዲህ ብለው እንደለመኑት ጌታችንና ፈጣሪያችን ሆይ የከበረ የሩፋኤልን ክብሩን ታስረዳን ዘንድ እንለምንሃለን በየትኛው ዕለት በየትኛው ወር ሾምከው። ከባልንጀሮቹ የመላእክት አለቆችም ትክክል ነውን የበዓሉን መታሰቢያ ያደርጉ ዘንድ በዓለም ውስጥ ስለርሱ እንድናስተምር እርሱም በመከራቸው ጊዜ ይረዳቸው ዘንድ በአማላጅነቱም በአንተ ዘንድ ይቅርታን ያገኙ ዘንድ። ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዘዘና ከሦስተኛው ሰማይ ሦስቱ የመላእክት አለቆች ሚካኤል፣ ገብርኤልና ሩፋኤል መጡ በታላቅ ደስታም ለክብር ባለቤት ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰገዱ። ጌታችንም ሩፋኤልን እንዲህ አለው የክብርህን ገናናነት የባልንጀሮችህንም ልዕልናቸውን እንዲያውቁ ለሐዋርያት ንገራቸው። ያን ጊዜም ለጌታችን ሰገደ ይነግራቸውም ዘንድ ጀመረ እንዲህም አላቸው ደገኛው የመላእክት አለቃ ሚካኤል ለሁሉም መላእክት አለቃቸው ነው ስሙም ይቅር ባይ ይባላል። ሁለተኛም የመላእክት አለቃ ገብርኤል የስሙ ትርጓሜ አገልጋይም ጌታም የሆነ የዓለሙ ሁሉ እመቤት የሆነች አምላክን የወለደች ቅድስት ድንግል ማርያምን ያበሠራት ነው። የእኔም ስሜ ሩፋኤል ነው ይህም ደስ የሚያሰኝ ቸር መሐሪ ቅን የዋህ ማለት ነው እኔም ኃጢአተኞችን በእግዚአብሔር ዘንድ አልከሳቸውም ከኃጢአታቸው በንስሓ እስኪመለሱ ስለ ቅንነቴ በእነርሱ ላይ እታገሣለሁ እንጂ። በሃያ ሦስቱ የመላእክት ነገድ ሠራዊት ላይ እግዚአብሔር የሾመኝ እኔ ሩፋኤል ነኝ እግዚአብሔር አብን ይቅር ባይ ልጁን አጽናኝና አዳኝ የሆነ መንፈስ ቅዱስን እናመሰግነው ዘንድ። በደብረ ጽዮን በሚደረገው የሺህ ዓመት ተድላ ደስታ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የክብር ጽዋን በሚሰጣቸው ጊዜ ለቅዱሳኖቹ በጎ ነገርን እንድሰጣቸው እግዚአብሔር ያዘዘኝ ሩፋኤል እኔ ነኝ። ደግሞም በዚች ቀን ከዕፀ ሕይወት ዐጽቅ ወስጄ ለተመረጡ ክርስቲያኖች በእጄ እንድሰጣቸው እግዚአብሔር ያዘዘኝ ሩፋኤል እኔ ነኝ። የሰማያት መዛግብትም ከእጄ በታች ተጠብቀው የሚኖሩ እኔ ሩፋኤል ነኝ። እኔም እግዚአብሔር እንዳዘዘኝ እከፍታቸዋለሁ እዘጋቸዋለሁም። በምድር ሰው ለባልንጀራው ስለ ስሜ በጎ ነገር ቢያደርግ እኔ በመከራው በችግሩ ረዳዋለሁ ወይም የሹመቴን ነገር የሚጽፍ ወይም ከቅዱሳን ጋራ ስሜን የሚያስብ ወይም በስሜ ለቊርባን የሚሆነውን የሚሰጥ ወይም በበዓሌ ቀን ምጽዋትን የሚሰጥ ይኸውም እግዚአብሔር በሊቃነ መላእክት ክብር የሾመኝና ያከበረኝ ጳጕሚን ሦስት ቀን ነው። ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት እስከማስገባው በብርሃን ሠረገላ እኔ እሸከመዋለሁ በምድር ላይ ከቶ እንደርሱ ያለ የማይገኝ መዐዛው እጅግ ጣፋጭ በሆነ ሽቱ ነፍሶቻቸው እርሱን በማሽተት ደስ እንዲላቸው አደርጋለሁ።

ነሐሴ 29/2014 ዓ.ም የፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት ዓመታዊ ጉዞ ወደ አደሬ ደብረ ሰዋ ሰው ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም የማስታወሻ ፎቶ

🔴#ስንክሳር ጳጒሜን_2 #ቅዱስ_ቲቶ_ሐዋርያ አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጳጒሜን ሁለት በዚህች ቀን ሐዋርያ ጳውሎስ መልእክት የጻፈለት የከበረ ሐዋርያ ቲቶ አረፈ። የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ቀርጤስ ከሚባል አገር ነው። እርሱም ለዮናናውያን ወገን ለሆነ ለአገረ ገዥው እኅት ልጅዋ ነው። ከታናሽነቱም የዮናናውያንን ትምህርትና ፍልስፍና ተምሮ እጅግ አዋቂ ሆነ በጠባዩም ቅን ሥራው ያማረ ለድኆችና ለችግረኞች መራራት የሚወድ ነው። ከሌሊቶችም በአንዲቱ ቲቶ ሆይ ስለ ነፍስህ ድህነት ተጋደል ይህ ዓለም አይጠቅምህምና የሚለውን በሕልሙ አየ። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ደነገጠ ምን እንደሚሠራም አላወቀም። ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት በተሰማ ጊዜ ብዙዎች ሰዎችም ተአምራቱን እርስበርሳቸው ተነጋገሩ የአክራጥስ መኰንንም ሰምቶ አደነቀ ዕውነት እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ወይም የሥራይ እንደሆነ ሊያውቅ ሽቶ የሚልከው ብልህ ሰው ፈለገ የእኅቱንም ልጅ ቲቶንን መረጠው ከእርሱ የሚሻል የለምና። ሲልከውም ታላቅና ጥልቅ የሆነ ምርመራ እንዲመረምር አዘዘው። ቲቶም ከይሁዳ ምድር በደረሰ ጊዜ የመድኃኒታችንን ድንቆች የሆኑ ተአምራቶቹን አየ ሕይወትነት ያላቸው ትምህርቶቹንም ሰማ። ከዮናናውያንም በትምህርታቸውና በሥራቸው መካከል ታላቅ የሆነ መራራቅን አግኝቶ የዮናናውያን ሃይማኖታቸው የቀናች እንዳልሆነች ለይቶ ዐወቀ። ከዚህም በኋላ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ አመነ፤ ደቀ መዝሙሩም ሁኖ ተከተለው። ወደ እናቱ ወንድም ወደ አገረ ገዥውም መልእክትን ላከ የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተምረውና የሚሠራው ዕውነት እንደሆነ ነገረው። ጌታችንም ከሰባ ሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ውስጥ የተቆጠረ አደረገው ከዕርገቱም በኋላ ከሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀብሎ ከእሳቸው ጋር በሀገሮች ሁሉ ዙሮ አስተማረ። ጌታችንም ጳውሎስን ጠርቶ ሐዋርያው በአደረገው ጊዜ ያን ጊዜ ሐዋርያ ጳውሎስን ተከተለው በብዙ አገሮችም ወንጌልን ሰበከ። የከበረ ጳውሎስም በሮሜ ከተማ ምስክር ሆኖ ከሞተ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ወደ ሀገረ አክራጥስ ተመለሰ ቤተ ክርስቲያንም ሠርቶ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው በዙሪያቸው ላሉ አገሮችም እንዲሁ አደረገ። ከዚህም በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደ ወደደው እግዚአብሔር ሔደ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ቲቶ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ጳጒሜን_1 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጳጉሜን አንድ በዚህች ቀን እና #ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ የታሰረበት፣ #የዑቲኮስ_ሐዋርያና #ቀሲስ_አባ_ብሶይ የእረፍታቸው መታሰቢያ ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ዮሐንስ_መጥምቅ ጳጒሜን አንድ ቀን በዚህች ዕለት ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ወደ እሥር ቤት ገብቷል። ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ፦ ንጉሡ ሔሮድስ የወንድሙን የፊልጶስን ሚስት ሔሮድያዳን በማግባቱና በመሰል ክፋቶቹ ቅዱስ ዮሐንስ ይገስጸው ነበር። ቅዱስ ዮሐንስ "መምሕር ወመገስጽ ዘኢያደሉ ለገጽ" "ፊት አይቶ የማያዳላ" ነውና ገሰጸው። ሔሮድስ ቅዱሱን ይፈራው ያከብረውም ነበር። በኋላ ግን ፈቃደ ሥጋው ስላየለበት በተለይ ደግሞ ከሰባት ቀናት በኋላ ልደቱን ሲያከብር እንዳይረብሸው በመስጋት በዚህች ቀን በወታደሮቹ አስይዞ እሥር ቤት ውስጥ ጥሎታል። ለሰባት ቀናት በጨለማ ውስጥ አሥሮ መስከረም 2 ቀን አስቆርጦታል። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ዑቲኮስ_ሐዋርያ በዚህች ቀን የወንጌላዊ ዮሐንስ ረድእ ሐዋርያና ሰማዕት የከበረ ዑቲኮስ አረፈ ። ይህም ቅዱስ ወንጌላዊ ዮሐንስን ሲያገለግለውና ሲታዘዘው ኖረ። ከዚያም ከሐዋርያ ጳውሎስ ጋራ ሔደ እርሱም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰም እንዲሰብክ አዘዘው በአረማውያንና በዮናናውያንም መካከል ሰበከ። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ወደማወቅ ብዙዎችን መለሳቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው። የጣዖታት ቤቶችን አፍርሶ አብያተ ክርስቲያናትን ሠራ። ከከሀድያንም ብዙ መከራ ደረሰበት መታሠርና ብዙ ቀኖች ግርፋቶችን በመቀበል፤ የእግዚአብሔርም መልአክ ወደ እሥር ቤት ከምግብ ጋር መጥቶ ይመግበዋል። ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ጣሉት እሳቱም ከቶ አልነካውም ሁለተኛም ለአንበሶች ጣሉት እነርሱም እንደ በጎች ሆኑለት። ከዚህም በኋላ ወደቍስጥንጥንያ ሀገር ሔደ። ሲሔድም የእግዚአብሔር መልአክ ይመራውና ያጸናናው ነበር ተጋድሎውንም ፈጽሞ በበጎ ሽምግልና ወደ እግዚአብሔር ሔደ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቀሲስ_ብሶይ_ሰማዕት በዚችም ቀን የአባ ሖር ወንድም ቀሲስ ብሶይ በሰማዕትነት ሞተ። ይህም ቅዱስ ከአንፆኪያ አገር ክብር ካላቸው ወገኖች ውስጥ ነው ስለ ዕውቀቱና ስለ ሃይማኖቱ ጽናት ቅስና ተሾመ። ወንድሙ አባ ሖርና እናቱ ወደ ግብጽ አገር ሔደው በሰማዕትነት ከሞቱ በኋላ እርሱም ተነሥቶ ወደ እስክንድርያ ሥጋቸውን ያይ ዘንድ ሔደ። ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች ሰጠ ከሦስት እንጀራና ከሚመረጐዛት ከአንዲት የሰኔል በትር በቀር ምንም አልያዘም ነበር። ወደ እስክንድርያ አገርም በደረሰ ጊዜ የዘመዶቹ በድን ወዳለበት ሰዎች መርተው አደረሱት የእናቱንና የወንድሙንም ሥጋ በአየ ጊዜ ከእርሳቸው ስለ መለየቱ መሪር ልቅሶን አለቀሰ። ከዚህም በኋላ ወደ መኰንኑ ሒዶ በፊቱ ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። ለመኰንኑም የአባ ሖር ወንድም እንደሆነ ነገሩት መኰንኑም ታላቅ የደንጊያ ምሰሶ በሆዱ ላይ እንዲአቆሙበት አዘዘ ይህንንም በአደረጉበት ጊዜ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ውስጥ ሰጠ። ከዚህም በኋላ ደግሞ ሥጋውን ከወንድሙና ከእናቱ ሥጋ ደግሞ ቍጥራቸው ሰማንያ ስምንት ከሆነ ከሌሎች ሰማዕታት ሥጋ ጋር በአንድነት ያቃጥሉ ዘንድ መኰንኑ አዘዘ ወደ እሳት በጨመሩአቸውም ጊዜ ከቶ እሳቱ አልነካቸውም። ምዕመናን ሰዎችም መጥተው የከበሩ የአባ ሖርንና የወንድሙ የአባ ብሶይን የእናታቸውንም ሥጋ ወሰዱ። ሀገሯ ዲብቅያ የሚባል የቅድስት ዳሞንንም ሥጋ፣ ሀገሩ በረሞን የሚባል የቅዱስ ቢማኮስንም ሥጋ፣ ጡልያ ከሚባል አገር የመጣ የውርሱኑፋን ሥጋም፣ አብስላሲ ወደሚባል አገር እስከሚያደርሷቸው በመርከብ ጫኗቸው። የስደቱ ወራት እስከሚፈጸም አክብረው ወስደው በመልካም ቦታ አኖሩዋቸው። ከዚህም በኋላ አብያተ ክርስቲያን ተሠርቶላቸው ሥጋቸውን በውስጣቸው አኖሩ ከእርሳቸውም ተአምራት ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆኑ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእኒህ ቅዱሳን ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

ከዚህም በኋላ ጌታችን አባቶችን ወደቦታችሁ ሒዱ አላቸው ወዲያው ተመለሱ ቅርጺቱንም ወደቦታሽ ተመለሽ አላት እርሷም ወደ ቀደመው አኗኗርዋ ተመለሰች ይህንንም አይተው የካህናት አለቆች አላመኑም ሌላም ብዙ አለ ብነግርህ መወሰን አትችልም ነገር ግን ለብልህ ጥቂት ቃል ትበቃዋለች ለሰነፍ ግን ቢነግሩት በቁም ነገር ላይ አይታመንም። ከዚህም በኋላ ጌታችን ማነጋገሩን ገታ ራሱንም እንደሚያንቀላፋ አደረገ እንድርያስም አንቀላፋ እንድርያስንና ደቀ መዛሙርቱን እንዲሸከሙአቸውና ሊገቡበት ወደሚሹት አገር በውጭ እንዲአኖሩዋቸው መላእክትን አዘዛቸው። ከዚህም በኋላ እንድርያስ በነቃ ጊዜ ዐይኖቹን ገለጠ የከተማውንም በር ተመለከተ በየብስም ላይ እንዳለ አውቆ ደነገጠ አደነቀም። ደቀ መዛሙርቱንም አነቃቸውና እንዲህ አላቸው ጌታችንን በባሕር ላይ ሳለን ያላወቅነው ምን አደረገብን ሲፈትነን መልኩን ለውጦ እንደ ሰው ሁኖ ታይቶናልና። ደቀ መዛሙርቱም እንዲህ አሉት እኛም በጌትነቱ ዙፋን ላይ ሁኖ የመላእክት ሠራዊት ሁሉ በዙሪያው ሁነው ጌታችንን አየነው አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣ ያዕቆብንም ቅዱሳንን ሁሉ አየናቸው ንጉሥ ዳዊትም በመሰንቆ ይዘምር ነበር። እናንተንም ዐሥራ ሁለት ሐዋርያት በፊቱ ቁማችሁ ዐሥራ ሁለቱንም የመላእክት አለቆች በፊታችሁ ሌሎች መላእክት በኋላችሁ ሁነው አየናችሁ። እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስንም መላእክትን እንዲህ ብሎ ሲያዛቸው ሰማነው የሚሉአችሁን ሁሉ ሐዋርያትን ስሟቸው። እንድርያስም በሰማ ጊዜ እጅግ ደስ አለው ይህን ድንቅ ምሥጢር ያዩ ዘንድ ደቀ መዛሙርቱ የሚገባቸው ሆነዋልና። ከዚህም በኋላ እንድርያስ ዐይኖቹን ወደ ሰማይ አቅንቶ እንዲህ ብሎ በታላቅ ድምጽ ጮኸ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ከእኛ ከባሮችህ ሩቅ እንዳልሆንክ አወቅሁ። ነገር ግን በመርከብ ላይ እኔ እንደማስተምረው ሰው መስለኸኝ በድፍረት ተናግሬሃለሁና ጌታዬ ይቅር በለኝ ። በዚያንም ጊዜ የክብር ባለቤት መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለእንድርያስ ዳግመኛ ተገለጠለት እንዲህም አለው። አዎን እኔ ነኝ በሊቀ ሐመር አምሳል በባሕር ውስጥ የተገለጥኩልህና መርከቡን የቀዘፍኩልህ። አትፍራ አትደንግጥ እኔ ከአንተ ጋራ እኖራለሁ ይህንንም ብሎ ወደ ሰማያት በክብር ዐረገ እንድርያስም መንገዱን ሄደ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ጻድቋ_ቅድስት_ዜና_ማርያም በዚህች ዕለት የእናታችን ቅድስት ዜና ማርያም የእረፍቷ መታሰቢያ ነው፡፡ ከአባቷ ከገብረ ክርስቶስ ከእናቷ አመተ ማርያም በ11መቶ ክፍለ ዘመን በቅዱስ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት በምድ ነጋሲ በጎጃም ምድር ግንቦት 30 ቀን የተወለደች ሲሆን ለአቅመ ሔዋን በደረሰች ጊዜ በንፅህ ድንግልና በምድረ ሂንፍራንስ ጣራ ገዳም አካባቢ በሚገኘው በአቡነ እንድርያስ ዋሻ ለ25ዓመት በጾም በፀሎት ምንም አይነት የላመ የጣፈጠ እህል ሳትቀምስ በቅል ውስጥ የሚገኘውን መራራ ፍሬ ከኮሶ ጋር በአንድነት ደርጣ (አዋህዳ) በመዘፍዘፍ ከ3 ቀን በኃላ በመመገብ እስከ ሕይወቷ ፍጻሜ ድረስ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቀራንዮ አደባባይ ላይ የቀመሰውን መራራ ሐሞትን በማሰብ ሙሉ ሕይወቶን እየተመገበች ታላቅ ተጋድሎዋን ፈፅማለች፡፡ ከዚህ የተነሳ ሸክላ ማርያም ተብላ ትጠራ የነበረችው ቦታ ስያሜ ተቀይሮ ደሪጣ ዜና ማርያም ዋሻ ተብሎ እስከ አሁን ድረስ በስሞ እየተጠራ ይገኛል፡፡ ከአቡነ እድርያስ ዋሻ በመቀጠል ከአዲስ አበባ ተነስተን ስንጓዝ አዲስ ዘመን ከተማ በስተቀኝ በኩል ተገንጥለን 15ኪሜ ያክል የጥርጊያ መንገድ እንደተጓዝን  በስሞ የተሰየመውን ደሪጣ ጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም ገዳም ላይ ቀሪ ሕይወቶን ምንም አይነት ዋሻ ባልነበረበት በከፍተኛ ተራራ ላይ እጅግ አስቸጋሪ ቀዝቃዛ አየር ባለበት ብርዱን፣ ፀሐዩን፣ ቁሩን፣ ረኃቡንና ጥሙን በመቋቋም ራቁቶን በመሆን መራራ ምግቦችን አዋህዳ በመመገብ በጾም በፀሎት በመትጋት አስቸጋሪ የሆነውን ተጋድሎዋን በመፈፀም በዚሁ በተቀደሰ ስፍራ በዚህች ቀን በታላቅ ክብር አርፋለች፡፡ በዚህም ወቅት ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያምና ከእልፍ አላፋት ቅዱሳ መላዕክት ጋር እንዲሁም ከሐዋርያት ፣ ከሰማዕታት ፣ ከጻድቃን ፣ ከደናግል ጋር በመሆን ከሰማይ በመውረድ በታላቅ ክብር ዕረፍቷን አክብሮላታል ታላቅ ኪዳንም ገብቶላታል፡፡ በዚሁ በተቀደሰ ስፍራ ላይ ወይንም በአሁኑ ሰዓት መቃብሯ በሚገኝበት ዋሻ ቤተመቅደስ አካባቢ በተጋድሎዋ ጊዜ ራቁቷን በሆነች ሰዓት መላ ገላዋን የሸፈነላት ፀጉር በእየ ዛፎቹ ላይ እስከ አሁን ድረስ አለ ፡፡ ይህም የጸጉር አምሳያ ከገዳሙ በመውሰድ ብዙ ሰዎች በቤታቸው በመታጠን ከአስም እንዲሁም ከተለያዩ በሽታዎች እየተፈወሱና እየዳኑ ሲሆን ታላላቅ ታምራትን እያደረገ ይገኛል፡፡ በዚህ ገዳም ከሌሎች ገዳማት ለየት የሚያደርገው ታሪክ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ በመውረድ ራሱ የባረከው ልዩ ታሪክ ያለው ጠበል የሚገኝ ሲሆን ይህም ጠበል በቦታው ላይ ሆኖ የተጠመቀ ፣ የጠጣ ፣ አልያም በአለበት ቦታ ሆኖ የተጠቀመ እስከ አሁን ድረስ መካን የሆኑ ሰዎች በፍጥነት ልጅ የሚያገኙ ከመሆናቸው ባሻገር ከማንኛውም ከተለያዩ በሽታዎች በመፈወስ  ታላላቅ ታምራትን እየሰራ ይገኛል፡፡ በ11ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ቅዱስ ላሊበላ በጌታችን በአምላካችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትዕዛዝ መሰረት ወደዚሁ ታላቅ ስፍራ በመምጣት የጻድቋ ማረፈያ/መታሰቢያ ዋሻ ቤተ መቅደስ በመፈልፈል የሰራላት ሲሆን በመቀጠል አፄ ይስሐቅ በ14ተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ይህን ገዳም በስሟ በመገደም በዚሁ ዋሻ ውስጥም የጻድቋ የቅድስት ዜና ማርያም መቃብሯ እንዲሁም የመታሰቢያዋ ፅላት የሚገኝ ከመሆኑ አንጻር በአካባቢው ያሉት ሕዝበ ክርስትያን ከካህናት ጋር በመሆን ሥርዓተ አምልኮ በመፈፀም እየተገለገሉበት ይገኛሉ፡፡ ይህ ዋሻም አስቀድሞ ሦስቱ ቅዱሳን ማለትም አቡነ እንድርያስ ዘጣራ ገዳም ፣አቡነ ተክለኃይማኖት ዘደብረ ሊባኖስ፣ ጻድቋ ቅድስት ዜናማርያም ዘደሪጣ ውስጥ ለውስጥ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት በፀጋ እግዚአብሔር ይገናኙበት የነበረ ሲሆን በአሁን ሰዓትም እግዚአብሔር የመረጣቸው ቅዱሳን ይመላለሱበታል፡፡ ለጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም የተሰጠ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር አምላክ መርጦና ፈቅዶ በጻድቋ አማላጅነት ካለበት ስፍራ ተነስቶ የጻድቋ ደጃን የረገጠ ለ3 ግመል ጭነት ጤፍ ወይም የሦስት አህያ ጤፍ ያህል ነፍሳትን እምርልሻለሁ፤ ከሲዖልም እሳት ነፍሳትን አወጣልሻለሁ የሚል ቃል ኪዳን ለጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም ተሰቶታል። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በጌቶቻችን ሐዋርያት በጸሎታቸው ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ነሐሴ_30 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነሐሴ ሠላሳ በዚች ቀን ከዐሥራ ስድስቱ ነቢያት አንዱ #ታላቅ_ነቢይ_ሚልክያስ ያረፈበት እና ጌታ ባሕር ውስጥ #ለሐዋርያ_እንድርያስ በሊቀ ሐመር አምሳል ተገልጦ ድንቅ ተአምር ያደረገለት ቀን ነው፣ የእናታችን #ቅድስት_ዜና_ማርያም የእረፍቷ መታሰቢያ ነው፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ነቢዩ_ሚልክያስ ነሐሴ ሠላሳ በዚች ቀን ከዐሥራ ስድስቱ ነቢያት አንዱ ታላቅ ነቢይ ሚልክያስ አረፈ። ይህም ነቢይ የእስራኤል ልጆች ከተሰደዱበት ከባቢሎን ሀገር በተመለሱ ጊዜ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በመተላለፋቸው ገሥጿቸዋል። ሁለተኛም ነቋር ስለሆነ መሥዋዕት ስለ አሥራትና በኵራት ገሥጿቸዋል። በዚህ ነቢይ አንደበት እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ተናግሯልና ርኅራኄ አድርጋችሁ ምጽዋትን መጽውቱ፣ ዐሥራቴንና በኵራቴንም አስገቡና እስቲ ፈትኑኝ እኔ ከሰማይ ዝናሙን ባላወርድላችሁ በረከትንም አስቲበቃችሁ ባልጨምርላችሁ የምድራችሁንም ፍሬ ነቀዝና መሰክ እንዳይበሉት እከለክላለሁ። ዳግመኛም ከክብር ባለቤት መድኃኒታችን ክርስቶስ አስቀድሞ መጥምቁ ዮሐንስ ስለ መምጣቱ ስለ ነቢዩ ኤልያስም ተናገረ። ደግሞ ስለ አይሁድ የሥርዓተ ክህነት ፍጻሜ ተናገረ በአሕዛብም አገር ውስጥ ለእግዚአብሔር የሚቀበላቸውን መሥዋዕት የሚያሳርጉ ዕውነተኞች ንጹሐን ካህናት እንዳሉ ገለጠላቸው። በበጎ ተጋድሎውም እግዚአብሔርን ከአገለገለ በኋላ ከዚህ ዓለም በመፍለስ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሐዋርያው_ቅዱስ_እንድርያስ በዚችም ቀን ጌታችን በባሕር ውስጥ ለሐዋርያ እንድርያስ በሊቀ ሐመር አምሳል ተገልጦ ድንቅ ተአምር አደረገለት። እንድርያስም ጌታችንን በመርከብህ አሳፍረን ነገር ግን የምንከፍልህ የመርከብ ዋጋ የለንም አለው። በሊቀ ሐመር የተመሰለ ጌታችንም ስለምን የላችሁም አለው እንድርያስም በከረጢታችን ወርቅን፣ ብርን እንዳንይዝ ስለአዘዘን ነው አለው። ጌታችንም እንዲህ ከሆነ ወደ መርከቤ ወጥታችሁ ተሳፈሩ አላቸው ያንጊዜም ወደ መርከብ ወጥተው ተሳፈሩ። ከዚህም በኋላ ጌታችን እንድርያስንና ደቀ መዛሙርቱን ከባሕሩ ማዕበል የተነሣ መታገሥ እንድትችሉ ተነሥታችሁ እንጀራ ብሉ አለ። አንድርያስም አድንቆ እንዲህ አለው በመንግሥተ ሰማያት የሕይወት እንጀራ እግዚአብሔር ይስጥህ። ደቀ መዛሙርቱ ግን በባሕር ላይ ጉዞ ስለአልለመዱ ከባሕሩ ማዕበል ፍርሀት የተነሣ መብላት መነጋገርም ተሳናቸው ። ጌታችንም እንድርያስን ደቀ መዛሙርትህን ወደ ምድር እንዲወርዱ እዘዛቸው ሲፈሩ አያቸዋለሁና ይህ ካልሆነ እንዳይፈሩ አንተ የኢየሱስ ደቀ መዝሙሩ ከሆንክ ጣዕም ባለው ቃል አስተምራቸው እነሆ ከየብስ ርቀናልና አለው። ጌታችንም መርከቡን መቅዘፍ ጀመረ እንድርያስም ማስተማርና ማጽናናት ያዘ በልቡም ጸለየ ያን ጊዜም ከባድ እንቅልፍን አንቀላፉ ስለተኙለትም እንድርያስ ደስ አለው። እንድርያስም ወደ ጌታችን ተመልሶ እንዲህ አለው ዐሥራ አራት ጊዜ በባሕር ላይ ጒዞ አድርጌአለሁ እንዳንተ የሚቀዝፍ አላገኘሁም። ጌታም መልሶ እንዲህ አለው እኛስ በባሕር ላይ ስንጓዝ ሁል ጊዜ እንቸገራለን። ነገር ግን አንተ የክብር ባለቤት የኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዝሙር እንደሆንክ ባሕር ስለአወቀችህ ማዕበሏን በአንተ ላይ አላነሣችም እንድርያስም በታላቅ ቃል እንዲህ ብሎ ጮኸ። የክብር ባለቤት ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ አመሰግንሃለሁ ከሚያከብርህ ሰው ጋር ተገናኝቼ ተነጋግሬአለሁና። ከዚህም በኋላ ጌታችን እንድርያስን እንዲህ አለው አንተ የክርስቶስ ደቀ መዝሙሩ ነህና ንገረኝ። አይሁድ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ስለምን አላመኑም የሠራውን ብዙ ድንቅ ተአምርን ሰምተናልና አለው። እንድርያስም እንዲህ አለው አዎን ወንድሜ እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ገልጦልናል አንካሶችንም በትክክል እንዲሔዱ አድርጓልና፣ ደንቆሮዎችንም አሰምቷልና፣ ዲዳዎችንም አናግሮአልና፣ ለምጻሞችንም አንጽቷልና፣ ውኃውንም ወይን አድርጓልና፣ አምስት እንጀራና ሁለት ዓሣን አንሥቶ ያዘ ሕዝቡንም በመስክ ሣር ላይ እንዲቀመጡ አዘዘ ሣሩም እንጀራ እስቲለብስ ድረስ በልተው ጠገቡ የተረፈውንም በብዙ ቅርጫቶች አነሣን ይህም ሁሉ ሲሆን አላመኑም። ጌታ ኢየሱስም እንዲህ አለው ይህን ያደረገ በግልጥ ነው ወይስ በሥውር። እንድርያስም እንዲህ አለው ይህንስ በግልጥ ነው ያደረገ በሥውር ያደረገውም አለ ግን የምትፈትነኝ መሰለኝ ጌታችንም እንዲህ አለው ወንድሜ ሆይ ልቤን ደስ ስለሚላት ነውና ንገረኝ። እንድርያስም እንዲህ አለው ልጄ ሆይ በጎ ሥራህን ሀሉ እግዚአብሔር ይፈጽምልህ አሁንም ስማ ጌታችን ያደረገውን ተአምር እኛ ዐሥራ ሁለታችን ሐዋርያቶቹ ከእርሱ ጋራ ስንጓዝ ከሊቃነ ካህናትና ከሕዝቡ ብዙዎች አሉ። ወደ ምኵራብም ደረስን ጌታችንም እንዲህ አለ በሰማይ ባሉ በኪሩቤልና በሱራፌል አምሳል በምድር ላይ ሰው የሠራትን ይቺን የተቀረጸች ሥዕል ታያላችሁን። ከዚህም በኋላ ወደሥዕሊቱ ተመልሶ ብልህ ሰው የተጠበበብሽ የሰማያውያን መልክን ያደረግሽ አንቺን እላለሁ ከቦታሽ ተነቅለሽ ውረጂ የካህናት አለቆችንም ወቀሻቸው እኔም ዕሩቅ ብእሲ ወይም እግዚአብሔር እንደሆንኩ መስክሪ አላት። ወዲያውኑ ከቦታዋ ተነቅላ ወረደች እንደሰውም በመናገር እንዲህ አለች እናንተ የደነቆራችሁ አይሁድ የራሳችሁ መደንቆር ያልበቃችሁ ሌሎችንም ለማደንቆር የምትሹ ለድኅነታችሁ ሰው የሆነ እግዚአብሔርን እንዴት ዕሩቅ ብእሲ ትሉታላችሁ አስቀድሞ ሰውን የፈጠረው በንፍሐት ልጅነትንም የሰጠው ይህ ነው። አብርሃምን የተናገረው፣ ይስሐቅንም ከመታረድ ያዳነው፣ ያዕቆብንም ወደ አገሩ ያስገባው ይህ ነው ለሚፈሩት በረከትን የሚሰጥ ለማይታዘዙለት ቅጣትን የሚያዘጋጅ ይህ ነው ። እውነት እነግራችኋላሁ እናንተ ስለምትክዱት ሕጉንና ሥርዓቱንም ትለውጣላችሁና ስለዚህ እነሆ መስዋዕታችሁ ይሻራል ምኵራቦቻችሁም በዋሕድ ወልደ እግዚአብሔር ስም አብያተ ክርስቲያናት ይሆናሉ። ይህንንና የሚመስለውን ተናግራ ዝም አለች። እኛም የካህናት አለቆችን መልሰን እንዲህ አልናቸው እነሆ ቅርጺቱ ሥዕል ተናግራ ወቀሰቻችሁ ታምኑ ዘንድ ይገባችኋል። የካህናት አለቆችና አይሁድም እንዲህ አሉን ይህ የሚያናግረው በሥራይ ነው አብርሃምን በወዴት አገኘው ከሞተ ዘመኑ ብዙ ነውና። ጌታ ኢየሱስም ወደ ቅርጺቱ መለስ ብሎ እንዲህ አላት አብርሃምን እንዳነጋገርኩት አላመኑምና ሔደሽ እንዲህ በይው። አስቀድሞ አዳምን የፈጠረው፣ አንተንም ወዳጁ ያደረገህ፣ አንተ ልጆችህ ይስሐቅና ያዕቆብን ይዘህ ተነሥ ከመቃብርም ወጥተህ ወደዚህ ኑ የካህናት አለቆችን ትወቅሱአቸው ዘንድ እኔ የማውቃችሁና የተነጋገርኳችሁ መሆኔን አስረዷቸው። ቅርጺቱም ሥዕል ይህን ሰምታ እያየናት ሔደች ወደ አብርሃምም መቃብር ደርሳ በውጭ ቁማ ጠራቻቸው። ወዲያውኑ ከሦስቱ አርእስተ አበው ጋር ዐሥራ ሁለቱ ወጡ ከእኛ ውስጥ ወደ ማን ነው የተላክሽ አሏት። ቅርጺቱም እንዲህ ብላ መለሰች ወደ ሦስቱ የአባቶች አለቆች ነው እናንተ ግን እስከ ትንሣኤ ሙታን ድረስ ተኙ ያን ጊዜም ወደ መቃብራቸው ተመለሱ። እሊህ ሦስቱ አባቶችም የካህናት አለቆችና እኛ ወደ አለንበት ከቅርጺቱ ሥዕል ጋር መጥተው ወቀሷቸው የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነም ነገሩአቸው።

🔴#ስንክሳር ነሐሴ_29 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ነሐሴ ሃያ ዘጠኝ በዚህች ቀን #የአባ_ዮሐንስ_ሐጺር ወደ አስቄጥስ ገዳም የሥጋው ፍልሰት ሆነ፣ #ቅዱስ_አትናቴዎስ #ገርሲሞስና_ቴዎዶጦስ ከሚባሉ ሁለት አገልጋዮቹ ጋር በሰማዕትነት አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አባ_ዮሐንስ_ሐጺር ነሐሴ ሃያ ዘጠኝ በዚህች ቀን የአባ ዮሐንስ ሐጺር ወደ አስቄጥስ ገዳም የሥጋው ፍልሰት ሆነ። ይህም የአባ እንጦንዮስ በሆነ በቊልዝም ገዳም ከአረፈ በኋላ ነው። ለእስክንድርያ አባ ዮሐንስ ሊቀ ጵጵስና በተሾመ ጊዜ እርሱም ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት አርባ ስምንተኛ የሆነ ነው። እርሱም ወደ አስቄጥስ ገዳም ሔደ የከበሩ መነኰሳትም እንዲህ አሉት የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር ሥጋ በዚህ በቤተ ክርስቲያኑ ቢሆን እኛም ሥጋው በአለበት ለፈጣሪያችን እግዚአብሔር እንሰግድ ዘንድ እንሻ ነበር። ያን ጊዜ የእግዚአብሔር ቸርነት አነሣሣችውና ስሙ ቆዝሞስ ለሚባል ለአንድ አበ ምኔት መልእክትን ጻፈ ከእርሱም ጋር የቊልዝም አገር የሆነ አረጋዊ አለ በደረሱም ጊዜ በዚያን ሰዓት ሥጋውን መውሰድ አልተቻላቸውም። የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር ሥጋ የኬልቄዶንን ጉባኤ በተቀበሉ መለካውያን ዘንድ ይጠበቅ ስለነበረ ነገር ግን ቦታውን አወቁ ተረዱ ወደ ቦታቸውም ተመልሰው ሃይማኖታቸው የቀና ምእመናን ሰዎችን አገኙ እነርሱም በዚያች አገር የሚኖሩ ናቸው ስለርሱ የመጡበትን ነገሩአቸው። ከጥቂት ቀኖች በኋላም ከታላላቅ ዐረቦች ወገን ለቊልዝም አገር መኰንን ተሾመ እርሱም ለኤጲስቆጶስ አባ ሚካኤል ወዳጁ ነው ሊቀ ጳጳሳት አባ ዮሐንስም ስለ ቅዱስ ዮሐንስ ሐጺር ሥጋ ወደ ኤጲስቆጶሱ መልእክትን ጻፈ። በመልእክቱም የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺርን ሥጋ ከከሐድያን መለካውያን እጅ እስከ አፈለሱት ድረስ መልእክተኞች አእሩግ መነኰሳትን ምክንያት ፈልጎ እንዲረዳቸው በማሳሰብ አዘዘው። ኤጲስቆጶሱም በሰማ ጊዜ ፈጽሞ ደስ አለው ሒዶም ወዳጁ ለሆነ ለመኰንኑ ጸሐፊ ነገረው። ጸሐፊውም ለመኰንኑ ነገረው። እነሆ መኰንኑም ከመነኰሳቱ ጋራ ሔደ ጸሐፊውም መነኰሳቱ ወደዚያ ቦታ እንዲገቡ ምክንያት እንዴት እናገኛለን አለ።መኰንኑም በልብሶቻቸው ላይ የዓረቦችን ልብሶች ያልብሱአቸውና ከእኔ ጋራ ወደዚያ ቦታ ይምጡ አለ እንዲሁም እንዳላቸው አደረጉ። ከዚህም በኋላ መኰንኑ ሔደ ከእርሱም ጋራ ብዙ ፈረሰኞች ሰዎች ብዙ ሕዝብም የአስቄጥስ ገዳም የከበሩ አረጋውያን አሉ ወደቊልዝም ገዳምም ደረሱ። መኰንኑም በዚያ የሚኖራውን የመለካውያን ኤጲስቆጶስ እንዲህ ብሎ አዘዘው ያንተን ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ አስወጣቸው በዚች ሌሊት እኔ በውስጧ አድራለሁና ያ መለካዊም መኰንኑ እንዳዘዘው አደረገ። መነኰሳቱም እንስሶቻቸውን ከከተማ ውጭ አዘጋጅተው በሌሊት ወደዚያ ገብተው የቅዱስ ዮሐንስ ሐጺርን ሥጋ ይዘው ወደ ምስር ደረሱ ከዚያም ወደ አስቄጥስ ገዳም ደረሱ የአባ መቃርስ ገዳም መነኰሳትም መስቀሎችን፣ ወንጌሎችን፣ ማዕጠንቶችንና መብራቶችን በመያዝ እየዘመሩና እያመሰገኑ ተቀበሏቸው ወደ አባት መቃርስ ሥጋም አቀረቡትና ከእርሱ ተባረኩ በላዩም ብዙ ሽቱዎችን ነሰነሱ የቊርባን ቅዳሴንም ቀደሱ የከበረ ወንጌልም በሚነበብ ጊዜ ታላቅ ድንቅ ተአምር ተገለጠ ቤተ ክርስቲያኒቱ  ሁለመናዋ በሰማያዊ ብርሃን በራች። ከቶ እንደርሱ ሆኖ የማያውቅ በጎ መዓዛ ሸተተ ታላቅ ደስታም ሆነ በዚያም ቦታ ሰባት ቀን ኖረ። ከዚህም በኋላ ወደ ራሱ ቤተ ክርስቲያን ተሸክመው ወሰዱት ዕብራውያንም በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው እያሉ መድኃኒታችንን እንደተቀበሉት ልጆቹ መነኰሳት ተቀበሉትና ወደ ቦታው አኖሩት ከእርሱም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ከዚህም በኋላ ወደ አስቄጥስ ገዳም ሊቀ ጳጳሳት አባ ማርቆስ በወጣ ጊዜ ወደ አባ ዮሐንስ ሐጺር ቤተ ክርስቲያን ገባ። ከእርሱም ጋር ብዙዎች ኤጲስቆጶሳትና የእስክንድርያ አገር ታላላቆች ከግብጽ አገር ሁሉ አሉ። የአባ ዮሐንስ ሐጺር ሥጋ የተጠቀለለበትን ሰሌን ገልጦ ከእርሱ ተባረከ መሪር ልቅሶንም አለቀሰ ያን ጊዜ ሥጋው ሲገለጥ መብረቅና ነጐድጓድ ሆነ።በቤተ ክርስቲያኑም ውስጥ ያሉት ሁሉም ደንግጠው ወደቁ ሊቀ ጳጳሳቱም ሰሌኑን መልሶ በፍጥነት ሥጋውን ጠቀለለ በሽብሸባ እየዘመሩና እያመሰገኑ እንደቀድሞው ሸፈነው። ከዚህም በኋላ ዳግመኛ እንዲህ እያሉ ሊያመሰግኑ ጀመሩ ፈጣን ደመና ሁነህ የመንፈስ ቅዱስን ዝናም የተሸከምክ ሠለስቱ ደቂቅ ወዳሉበት ወደ ባቢሎን የሔድክ በላይህ በአደረ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ወደ እስከንድርያ አገር የተመለስክ ሁለተኛም ወደ ቊልዝም የሔድክ የጣዖታትን ቤቶች አፍርሰህ ሃይማኖትን የሰበክ በሽተኞችን የፈወስክ አጋንንትን ያስወጣህ ወደርስትህም የተመለስክ አንተ የበረከት ማደሪያ ነህና። የአባ ዮሐንስ ሐጺር የሥጋው ፍልሰት ከንጹሐን ሰማዕታት ዘመን በአምስት መቶ ሃያ ዓመት ሆነ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አትናቴዎስ_ሰማዕት በዚህችም ቀን ኤጲስቆጶስ አትናቴዎስ በሰማዕትነት ሞተ ከእርሱም ጋር ስማቸው ገርሲሞስና ቴዎዶጦስ የሚባል ሁለት አገልጋዮች በሰማዕትነት አረፉ። ይህንንም ቅዱስ አትናቴዎስን የእንጦኒቆስን የጭፍራ አለቃውን ልጅ እርሱ እንዳጠመቃት በንጉሥ ዘንድ ወነጀሉትና ንጉሥ አርስያኖስ ያዘው እርሱም ክርስቲያን እንደሆነ ታመነ ብዙ ሥቃይንም አሠቃየው። በሃይማኖቱም ጸና እንጂ ሃይማኖቱን ባልካደ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ እንዲሁም እሊህን ሁለቱን አገልጋዮች ገርሲሞስንና ቴዎዶጦስን በግርፋትና በስቅላት ከቀጣቸው በኋላ ራሶቻቸውን በሰይፍ አስቆረጠ ሦስቱም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ። አማንያን ሰዎችም መጡ ለወታደሮችም ገንዘብ ሰጥተው የቅዱሳኑን ሥጋቸውን ወሰዱ በአማሩ ልብሶችም ገንዘው በሣጥን ውስጥ አኖሩአቸው ከሥጋቸውም  ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።https://t.me/finotebirhan12

እንዲህም ብሎ መረቀው ከሰማይ ጠል ከምድር ስብ ይስጥህ ሥንዴህን ወይንህንና ዘይትህን ያብዛልህ አሕዛብም ይገዙልህ አለቆችም ይስገዱልህ ለወንድሞችህም ጌታ ሁን የአባትህም ልጆች ይስገዱልህ። የሚረግምህም የተረገመ ይሁን ይህም በእግዚአብሔር ፈቃድ ሆነ። ይህም አባት ይስሐቅ ወደ መቶ ሰማንያ ዘመን ደረሰ አባታችን ይስሐቅም እንዲህ ብሎ ተናገረ ከዚህም በኃላ መልአክ ወደ  ሰማይ ወሰደኝ አባቴ አብርሃምን አየሁትና ሰገድሁለት እርሱም ሳመኝ ንጹሕን ሁሉ ስለ አባቴ ተሰበሰቡና ወደ ውስጠኛው የአብ መጋረጃ ከበውኝ ከእኔ ጋራ ሔዱ እኔም ወድቄ ከአባቴ ጋራ ሰገድኩ። የሚያመሰግኑ መላእክት ሁሉ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብሎ የሚመሰገን አሸናፊ እግዘአአብሔር ምስጋናው በሰማይና በምድር የመላ ነው እያሉ ጮኹ። አባቴ አብርሃምን እኔ በቦታዬ ልዩ ነኝ ሰው ሁሉ ልጁን በወዳጄ ይስሐቅ ስም ቢሰይም በቤቱ ውስጥ በረከቴ ለዘላለም ይኖራል የቡሩክ ወገን የሆንክ አንተ ቡሩክ አብርሃም ሆይ መምጣትህ መልካም ነው።አሁንም  በወዳጄ በልጅህ ይስሐቅ ስም የሚለምን ሁሉ በረከቴ በቤቱ ውስጥ ለዘላለም እንዲኖር ቃል ኪዳኔን አጸናለታለሁ አለው። ትሩፋቱን ቅንነቱን ገድሉን የሚጽፍ ካለ ወይም በስሙ የተራበ የሚያጠግብ በመታሰቡያው ቀን የተራቆተ የሚያለብስ እኔ የማያልፈውን መንግሥት እሰጠዋለሁ። አብርሃምም እንዲህ አለ አቤቱ ዓለሙን ሁሉ የያዝክ አብ ሆይ ቃል ኪዳኑን ገድሉን ይጽፍ ዘንድ ካልተቻለው ቸርነትህ ትገናኘው አንተ ቸር መሐሪ ነህና አንጀራ የሌለው ችግረኛ ቢሆንም። ጌታም እንዲህ ብሎ መለሰለት በወዳጄ በይስሐቅ በመታሰቢያው ዕለት ከሌሊት ጀምሮ በጸሎት ይትጋ አይተኛ እኔም መንግሥቴን ከሚወርሱ ጋራ ከበረከቴ እሰጠዋለሁ። አባቴ አብርሃምም ሁለተኛ እንዲህ አለ በሽተኛ ድውይ ከሆነ ቸርነትህ ታግኘው ጌታም እንዲህ አለ ጥቂት ዕጣን ያግባ ዕጣንን ካላገኘ የቃል ኪዳኑን መጽሐፍ ፈልጎ በልጅህ በወዳጄ በይስሐቅ መታሰቢያ ቀን ያንብበው። ማንበብም የማያውቅ ከሆነ ወደሚያነቡለት ሒዶ እሷን አስነብቦ ይስማ። ከእነዚህም ይህን ማድረግ ካልቻለ ወደ ቤቱ ገብቶ ደጁን ይዝጋ እየጸለየ መቶ ስግደቶችን ይስገድ እኔም የሰማይ የመንግሥት ልጅ አደረገዋለሁ። ለቁርባን የሚሆነውንና መብራትን ያገባ እኔ ያልኩትን ሁሉ የሚያደርግ እርሱ የመንግሥተ ሰማያትን ርስት ይቀበላል።ቃል ኪደሰኑንና ገድሉን ትሩፋቱን ለመጻፍ ልቡን ያበረታውን እኔ ስሙን በሕይወት መጽሐፍ እጽፋለሁ በሺው ዓመት ምሳ ላይም ይገኛል። እግዚአብሔርም ይህን ብዙ ነገርን በተናገረ ጊዜ ያዕቆብ አይቶ በመደንገጥ ነፍሱ ተመሠጠች ይስሐቅም ያዕቆብን አንሥቶ ልጄ ሆይ ዝም በል አትደንግጥ ብሎ ጠቀሰው ከዚህም በኃላ ሳመውና በሰላም አረፈ።ከኤሞር ልጆች በገዛው እናቱ ሣራ በተቀበረችበት በአብርሃም መቃብር ተቀበረ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ያዕቆብ በዚችም ቀን ደግሞ እግዚአብሔር እስራኤል ብሎ ስም ያወጣለትን የአባቶች አለቃ የሆነ የያዕቆብን የዕረፍቱን መታሰቢያ እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አባቶቻችን አዘዙን። ይህም ቅዱስ በበጎ ሥራ ሁሉ በመራራት በቅንነት በትሕትና በለጋስነት የአባቶቹን የአብርሃምንና የይስሐቅን መንገድ የተከተለ ሆነ። ወንዱሙ ኤሳውም ብኩርናውን በምስር ንፍሮ ደግሞ በረከቱን ስለወሰደበት አብዝቶ ስለጠላው ሊገድለው ይፈልግ ነበር ስለዚህም አባቱ ይስሐቅና እናቱ ርብቃ ያዕቆብን ወደ ርብቃ ወንድም ወደ ላባ ሰደዱት። እየተጓዘም ሳለ በአደረበት በረሀ ከምድር እስከ ሰማይ የሚደርስ መሰላል የእግዚአብሔርም መላእክት በውስጡ ሲወርዱ ሲወጡ በሕልሙ አየ እንዲህም አለ ይህ የሰማይ ደጅ ነው ከዚህም የእግዚአብሔር ቤት ይሠራል። በሶርያ ምድር ወደሚኖር ወደእናቱ ወንድም ወደ ላባ በደረሰ ጊዜ ሁለቱን ልጆቹን ልያንና ራሔልን አጋባው በዚያም የላባን በጎች እየጠበቀ ሃያ አንድ ዓመት ያህል ኖረ። ላባም የምሰጥህ ምንድን ነው አለው ያዕቆብም ምንም የምትሰጠኝ የለም አሁን ወደፉት የምነግርህን ነገር ካደረግህልኝ ዳግመኛ በጎችህን ፈጽሜ እጠብቃለሁ። አሁን በጎችህ በፊት ይለፉና ከበጎችህ ሁሉ ጠጉራቸው ነጫጭ የሆኑትንና መልካቸው ዝንጉርጉር የሆነውንም ስለዋጋዬ ለይልኝ አለው። ዓይነቱ ዝንጉርጉር ያልሆነውና መልኩ ነጭ ያልሆነው  ሁሉ ግን ላንተ ይሁን አለው። ላባም እንዳልክ ይሁን አለ። በዚያችም ቀን ነጩንም ቀዩንም ዝንጉርጉሩንም መልኩ ዳንግሌ የሆነውንም የፍየሉንም አውራ ለይቶ ለልጂቹ ሰጠ። በእነርሱና በያዕቆብ መካከል ሦስት ቀን የሚያስኬድ ጎዳና ርቀው ሔዱ ያዕቆብ ግን የቀሩትን የላባን በጎች ይጠብቅ ነበር። ያዕቆብም የልምጭ በትርንና ታላቅ የሎሚ በትርን ወስዶ ቅረፍቱን ልጦ ጣለው ያዕቆብ የላጣቸው በትሮች ነጫጭ ሁነው ታዩ። እነዚያንም በትሮች በጎች ከሚጠጡበት ገንዳ ላይ ጣላቸው በጎች ውኃ ሊጠጡ በመጡ ጊዜ እነዚያ በትሮች በፊታቸው ሁነው ይታዩ ዘንድ። መጥተውም በጠጡ ጊዜ እነዚያን በትሮች አስመስለው ፀንሰው ነጩንና ሐመደ ክቦውን ዝንጉርጉሩን ወለዱ። ያዕቅብም አውራ አውራዎቹን በጎች ለየ አውራ አውራውን ከለየ በኃላ እንስት እንስቶቹን በጎች ለይቶ ዝንጉርጉር ሐመደ ክቦና ነጭ በሆኑ አውራዎች ፊት አቆማቸው የራሱንም በጎች ለያቸው እንጂ ከላባ በጎች ጋራ አልቀላቀላቸውም። ያዕቆብም እጅግ ፈጽሞ ባለጸጋ ሆነ ሴቶችንም ወንዶችንም አገልጋዩችን ገዛ ብዙ ከብት ላሞችን በጎችን ግመሎችንና አህዮችን ገዛ። ያዕቆብም ወደአገሩ በተመለሰ ጊዜ እስከ ንጋት ድረስ አንድ ሰው ሲታገለው አደረ ከእርሱም ጋራ ሲታገል እንዳልቻለው ባየ ጊዜ እርም የሚሆንበት ሹልዳውን ያዘው ጎህ ቀድዷልና ልቀቀኝ አለው ካልመረቅከኝ አልለቅህም አለው። ስምህ ማን ይባላል ቢለው ስሜ ያዕቆብ ነው አለው እንግዲህ ስምህ ያዕቆብ አይባል እስራኤል ይባል እንጂ አለው ከእግዚአብሔርና ከሰው ጋራ መታገልን ችለሃልና። ከዚህም በኃላ ስለ ልጁ ዮሴፍ ብዙ ኀዘን አገኘው ወንድሞቹ ወደ ግብጽ ሸጠውታልና በጠየቃቸውም ጊዜ ክፉ አውሬ በልቶታል አሉት ከልቅሶውም ብዛት የተነሣ ዐይኖቹ ታወሩ። ከዚህም በኃላ ታላቅ ረሀብ ሆነ በግብጽ አገር እህል የሚሸጥ መሆኑን ያዕቆብ ሰማ ሥንዴ ይሸምቱ ዘንድ ልጆቹን ላካቸውና ወደ ዮሴፍ ደረሱ ንጉሥ ሆኖም አግኘተውት ሰገዱለት ወንድማቸው እንደሆነም አላወቁትም እርሱ ግን አውቋቸዋል ሥንዴውንም ሰጥቶ አስናበታቸው ሁለተኛም በተመለሱ ጊዜ ራሱን ገለጠላቸውና ወደዚህ ስለ ሸጣችሁኝ አትፍሩ እመግባችሁ ዘንድ በፊታችሁ እግዚአብሔር ለሕይወት ልኮኛልና አላቸው። አሁንም ፈጥናችሁ ሒዱና ለአባቴ ንገሩት ልጅህ ዮሴፍ እንዲህ ይላል በሉት ለግብጽ አገር ሁሉ እግዚአብሔር ጌታ አድርጎኛል ፈጥነህ ና በዚያ ልኑር አትበል። ስለዚህም እስራኤል ወደግብጽ አገር ከቤተሰቡ ሁሉና ከጓዙ ከገንዘቡ ጋር ወርዶ በዚያ የሚኖር ሆነ። ዕረፍቱም በቀረበ ጊዜ ልጆቹን ጠርቶ እየአንዳንዳቸውን መረቃቸው ትንቢትንም ተናገረላቸው የዮሴፍንም ልጆች ኤፍሬምንና ምናሴን እጆቹን አመሳቅሎ ባረካቸው መረቃቸውም። ከዚህም በኃላ በመቶ ሠላሳ ሰባት ዕድሜው በሰላም በፍቅር አረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባቶቻችን በአብርሃም፣ በይስሐቅ እና በያዕቆብ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን ።https://t.me/finotebirhan12