es
Feedback
HOP Ministry

HOP Ministry

Ir al canal en Telegram

HOP Ministry — Hear. Obey. Practice. A discipleship platform sharing devotionals, revival histories, spiritual biographies, testimonies, and Amharic Christian literature to build Christ-like lives. Based on Luke 11:28.

Mostrar más
El país no está especificadoLa categoría no está especificada
445
Suscriptores
+224 horas
+237 días
+6630 días
Archivo de publicaciones
Chekolebegn_Lebie(128k).m4a7.00 MB

#የእረፍት_ቦታዬ_ኢየሱስ! እመኑኝ ወደ እግዚአብሔር ቅረቡ ታርፋላችሁ፤ በፊቱ ሁኑ ታርፋላችሁ፤ እግሩ ሥር ቆዩ ታርፋላችሁ። የእረፍት መገኛ ኢየሱስ ነው። ወደ እርሱ መጠጋት፣ በእግሩ ሥር መሰየም ደስታና ሐሴትን የምናጭድበት፣ ልባችን በፍጹም የሚያርፍበት ብቸኛው መንገድ ነው። በነፍሳችን ድካም ተሸክመን፣ ጉልበታችን ዝሎ፣ ልባችን የት ሄጄ ልረፍ እያለ በዓለም ሀሩር ከመቃጠሉ የተነሳ ሲያለከልክ፤ እፎይ የሚያስብል፣ የተጠማች ነፍሳችንን የሚያረካ፣ ጥማችንን የሚቆርጥ የሕይወት ውኃ፣ የዘላለም እረፍት፣ የባከነችን ነፍስ አስካኝ መልካሙ እረኛ ኢየሱስ ብቻ ነው። የተቀጠቀጠ ሸንበቆ እንደማይሰበር፣ የሚጤስ የጧፍ ክርም እንደማይጠፋ አምኖ እና ተማምኖ የሚጠጋው ኢየሱስን ብቻ ነው። በድካም ያለከለከች ነፍስ በፊቱ እርፍ! ትላለች፤ ሕመሟ በመድኃኒቷ በእርሱ ይድናል፤ ቁስሏም በፈዋሹ ጌታ ይሽራል። እርሱ ስብራታችንን፣ ድካማችንን ሊሰማ ዘወትር ቅርብ ነው፤ ባንነግረውም ደግሞ ለእርሱ ከመናዘዛችን በፊት አስቀድሞ ያውቀዋል። ለሰው ልጆች የልባችንን ባወራን ጊዜ የንግግራችንን ብዛት መታገስ አቅቶዋቸው ሲያቋርጡን እና በንግግራችን መሃል ጣልቃ ሲገቡ፤ መልሰው ጆሮ እንዲሰጡን፣ ልብ ብለው እንዲያደምጡን እንደምንለው፦ #በቅድሚያ_አስጨርሰኝ የሚባል አይደለም። እርሱ የልባችንን ጥልቀት ያነበዋል፣ ያውቀዋል፣ ይሰማዋል። በኮልታፋ አንደበታችን የምናደርገውን መቃተትም በደስታ ይሰማዋል፤ ኃዘናችን፣ ድካማችንም ይሰማዋል። የእርሱ ጠረን ከሩቅ ይጣራል። መዓዛውን ለምደው፣ የጉያውንም ሙቀት አይተው ልባቸው ወደ ውጪ የሸፈተ፣ ደጅ ደጁን ማለት ያበዙ የቀመሱት ቸርነቱ እየጎተጎተ እርሱን ያስናፍቃቸዋል። ትንሽ ከእርሱ ፈቀቀ ሲሉ ፍቅሩ፣ የቀመሱት ሀልዎቱ የእግር እሳት ሆኖ ዳግም ወደ እርሱ እንዲመለሱ እግሮቻቸውን ያፈጥናል። እርሱን እርሱን አልሽ፤ ምን አተረፍሽ? ለሚሉኝ ሰዎች በድፍረት የምመልሰው መልሴ የአጽናፈ-ዓለሙ ፈጣሪ የልብ ወዳጄ፣ የልብ ጓደኛዬ፣ የምሰማው፣ የሚሰማኝም ቤተኛዬ ነው፤ ከእርሱ ጋር ለመዋል፣ ለመሰንበትም ታድያለሁ የሚል ነው። በዘመናት መካከል፣ በትውልዶች ታሪክ ውስጥ ቸሩ ጌታ ያልጠገበው፣ ያልሰለቸው ነገር ቢኖር ከሚወዳቸው፣ ከሚወዱትም ልጆቹ ጋር ሕብረት ማድረግ ነው። በቅዱስ ቃሉ እደተጠቀሰው፦ " #እግዚአብሔርን_ፈልጉ " ፣ #ፈልጉኝ  ተደጋጋሚ መልዕክቱ ነው። እርሱን የሚፈልግ አስተዋይ ሰው መኖሩንም ለማየት ዘወትር ወደ ምድር ይመለከታል። ታዲያ እርሱ እኛን መፈለግ፣ ከእርሱ ጋር ሕብረት እንድናደርግ መፈለግ ሳይደክመው፣ ሳይሰለች እኛ እንዴት እርሱን መፈለግ ይደክመናል፣ እንሰለቻለንስ? ፍለጋው ለጥቅሙ ሳይሆን ለጥቅማችን፤ ሊኖርበት ሳይሆን እኛ ልንኖርበት፤ ሕይወት ይሆንልን ዘንድ፣ በሕይወትም እንድንኖር እንደሆነ ገብቶን ቸሩን ጌታ እንከተለው፣ እንከታተለው። በፍለጋችን ውስጥ የቀመስነው ቸርነቱ እልፍ ረሃብ ወልዶ በፊቱ ያሰንብተን፤ ያለ እርሱ የማይኖሩ ጥገኞቹ ያድርገን። ኢየሱስ በአንተ የተነካንበትን መነካት ጥለን፣ ንቀን ብንሄድ ከውስጥ ሰውነታችን ወሳኙን ክፍል ጥሎ እንደመሄድ፣ አጥቶ እንደመኖር ነውና በደረስንበት ሁሉ ያላንተ ለመኖር አቅም ያጣ  ሽባ ሆነን እንመላለሳለን። የጎደለን ነገር አለና ተፈተንም መንቀሳቀስ አንችልም። ልባችንን ከረዳኸውና ካነቃኸን ግን የጣልነውን፣ የጎደለንን ነገር ፍለጋ ፈጥነን ወዳንተ መለስ እንላለንና በየሄድንበት ሁሉ እየተከተልኽ ክፍተታችንን አሳየን፤ እንድንራብህ፣ እንድንቀርብህም እርዳን!! አሜን!! ✍️ መክሊት አየለ 📆 June 6, 2026 #HOPMinistry #HearObeyPractice #DailyDevotional

ልብ ሲፈልግ እጅም ተቀብሎ ቢሰራ፣ አሳብን አካል ለማልበስ ቢተጋ፣ ስንፍናም ጠፍሮ ባይዘን፣ ያሰብነውንና መሆን ያለበትን ነገር ሁሉ ወስነን ወዲያው ብንተገብረው እንዴት አትራፊዎች እንሆን ነበር?! #HOPMinistry #HearObeyPractice #DailyDevotional  📍 Telegram Channel: https://t.me/hopministry10

#ልብን_ከእጅ_ጋር_ማጣመር! ለብዙ መልካም ነገር፣ በተለይም ለእግዚአብሔር ለሆነው ነገር፦ ቃሉን ለማንበብ፣ ለመጸለይ፣ ከቅዱሳን ጋር ሕብረት ለማድረግ፣ ለማገልገል፣.....እልፍ ሲልም እግዚአብሔር ለነገረንና በልባችን ላስቀመጠው ሸክም ለመትጋትና ለመዘርጋት በልባችን ብዙ መሻት ሊኖር ይችላል፤ ለማድረግ ግን አቅም ሊኖረንም ላይኖረንም ይችላል። አብዛኛውን ነገር እየፈለግን ለማድረግ ግን ቁርጥ ያለ ውሳኔ ሳንወስን ቆይ ዛሬ፣ ቆይ ነገ፣ በኋላ ጀምራለሁ እያልን በቀጠሮ ኗሪዎች እንሆናለን። በዚህ ጉዳይ ላይ ያለኝን የራሴን አቋም ሳይ ለነገ ያሳደርኳቸው ብዙ ወረፋ ጠባቂ ነገሮች አሉኝ። ነገ የኔ መሆኑን እና ምን ይዞ ሊመጣ እንደሚችል ሳላውቅ እንኳን ዛሬ መሆንና ተከውነው ባያልቁ እንኳ ቢያንስ መጀመር የሚችሉ በቀጠሮ የተወዃቸው ብዙ ነገሮች አሉኝ። የልቤን አሳብ፣ መሻቴን ከእጄ (ከተግባሬ) ጋር ማጣመር አቅቶኝ ዛሬዬን አባክናለሁ። ልብ ሲፈልግ እጅም ተቀብሎ ቢሰራ፣ አሳብን አካል ለማልበስ ቢተጋ፣ ስንፍናም ጠፍሮ ባይዘን፣ ያሰብነውንና መሆን ያለበትን ነገር ሁሉ ወስነን ወዲያው ብንተገብረው እንዴት አትራፊዎች እንሆን ነበር?! #አንድ_ቀን ከሚለው መጨረሻው በውል ከማይታወቅ ቀጠሮ፣ ከሚያዘናጋም ከንቱ የለውጥ ተስፋ አምልጠን ዛሬን በአግባቡ ለመጠቀም እንዴት ኃይል ይሆንልን ነበር?! ✍️ መክሊት አየለ 📆 March 20, 2026 #HOPMinistry #HearObeyPractice #DailyDevotional  📍 Telegram Channel: https://t.me/hopministry10

Amen አሜን Intimate Worship Live.mp310.25 MB

" #ረሃቤን_ፈውሰው! " ጭው ያለ በረሃ ላይ ያልቆየ ሰው ጥም ሊያቃጥለው፣ ረሃብም ሊያንገበግበው አይችልም። ሁሉ በተራቆተበት ምድረበዳ ላይ ያለ ሰው ግን እህል ውሃ ጩኸቱ ነው፤ ውስጡን የሚያንሰፈስፈው ጉድለት አለና እስኪያገኘው፣ በልቶት እስኪጠግብ ልቡ እረፍት የለውም። ረሃብተኛ ለመጥገቢያው የማያቋርጥ ፍለጋ አለው፤ እስኪያገኘውም ድረስ ያላሰለሰ ጥረት ያደርጋል። ይሄንን ሁሉ የምለው ስለመብልና ስለመጠጥ፣ አግኝቶ ስለመብላት፣ ስለመጥገብ፣ ሥጋንም ስለማርካት አይደለም። #እግዚአብሔርን_ስለመራብ እንጂ። ወንዝ ሲወስድ እያሳሳቀ እንደሆነ ሁሉ ለእግዚአብሔርና ለነገሩ ፍላጎት ማጣትም በአንዴ ዱብ ብሎ በላያችን የሚከመር ነገር ሳይሆን እግዚአብሔርን ከመልመድ፣ ከፊቱ ርቆ መቆየትን ከማዘውተር ጀምሮ እያለ እያለ እያለ ሄዶ ረሃብ አልባ፣ ለእግዚአብሔር ፍላጎት፣ ናፍቆት፣ ጉጉት የለሽ መሆን ጋር ይደርሳል። በዚህን ጊዜ ቀድሞ እግዚአብሔርን በመናፈቅ፣ እርሱን በመፈለግ የማይከደኑ አይኖች ከእርሱ ውጪ የሆነው ነገር ላይ ለመፍዘዝ በርትተው እርሱ ሲታሰብ እንቅልፍ የሚጫጫናቸው፤ በፊቱ ለመቆየት የበረቱና የማይደክሙ ጉልበቶች ጸሎት ሲታወስ የሚዝሉና የሚብረከረኩ ይሆናሉ። ምርጥ የተባለ ገበታ በፊቱ ተደርድሮ እያለ #Appetite የሌለው፣ የምግብ ፍላጎቱን ያጣ፣ ረሃቡን የተቀማ ሰው ምን ማድረግ ይችላል? ረሃቡ፦ በደስታ፣ ፈልጎ የመብላቱ፣ የመጥገቡ መንስኤ ነውና ምግቡ አስፈላጊ እንደሆነ ሁሉ ረሃቡም አስፈላጊ ነው። ሰው ረሃቡን ያጣ ዕለት ምግብ ባለመፈለግ ጸንቶ መኖሩ አይቀሬ ነው። በክርስትና ሕይወታችንም ወደሚያሳድገን፣ ወደሚያለመልመን ነገር ለመጠጋት፣ በእርሱ ለመረስረስ መራብና መጠማት ቁልፍ ጉዳይ ነው። ጽሁፌን ሳጠልልቃ ከ  #Aster_Abebe የዝማሬ ግጥም ውስጥ የብልህ ጸሎቷን ልዋስ፦ #ጥቂት_አንተን_ቀምሶ_እንደጠገበ_ሰው_መሆኔ_ጤና_አይደለም_ረሃቤን_ፈውሰው! አሜን!! ጌታ እግዚአብሔር ረሃባችንን ይፈውሰው፤ የእርሱ ረሃብተኞች ያድርገን!! ✍️ መክሊት አየለ 📆 March 28, 2025

4_5940473604738127322.mp313.64 MB

ከእግዚአብሔር ጋር የሚያጣብቀው፣ በፊቱም የሚያሰነብተው መንፈስ ቅዱስ የሰውን ልብ ካልነካ፣ ለልባችን ልብ ሰጥቶት እርሱን እንድንፈልግ ካልረዳን፣ ቀድሞ ከወደድነው በላይ በእግዚአብሔር ፍቅር እንድንጠመድ ፍቅሩን በልባችን ካላፈሰሰ፣ እልፍ ረሃብ ካልጨመረልን በራሳችን አንዳች ማድረግ አንችልም። #HOPMinistry #HearObeyPractice #DailyDevotional  📍 Telegram Channel: https://t.me/hopministry10

#ካልተራብን_ባላየ_ባልሰማ_ማለፋችን_የግድ_ነው! እግዚአብሔር እረዳኝ እና ውስጤ፣ ልቤ ጸሎት መፈለግ ቻለ። በእግዚአብሔር ተረዳኹና ለመጸለይ፣ እግዚአብሔርንም ለመፈለግ አቅም አገኘው። እርሱን እንዲፈልግ ለልቤ ልብ ሆነለት። ይህ፦ ጸሎት በእኔ አቅም እንዳልሆነ ሲገባኝ፤ እኔ ባቃተኝና ደከመኝ ባልኹ ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ሲረዳኝ፤ በእኔ ሆኖ በማይነገር መቃተት ሲማልድልኝ፣ ሲያስቃትተኝ የጻፍኹት እውነት፣ ለእግዚአብሔርም ያቀረብኹት ምስጋና ነው። ምንጬ እግዚአብሔር ሆይ አንተን ለመፈለግ ልቤ ልብ አገኘ፣ ልቤ ልብ ሆነለት። የሰው ልጅ ጊዜ ስላጣ ብቻ አይደለም እግዚአብሔርን የማይፈልገው፤ ጊዜ ሞልቶ፣ ተርፎት ለመጸለይ ግን ልብ ሊያጣ፤ ረሃቡንም ሊቀማ ይችላል። ከእግዚአብሔር ጋር ባለን ሕብረት ከባዱ ነገር እርሱን ለመፈለግ ጊዜ ማጣት አይደለም፤ ይልቁንም እርሱን ለመፈለግ ልብ፣ ፍላጎት፣ ረሃብ ማጣት ነው። በተለምዶው ከሰው ልጆች ጋር ባለን ወዳጅነት ከእነርሱ ጋር ያለን ግንኙነት ከሻከረና ሕብረታችን ከላላ አንድ ቤት ሆነን እንኳ ትኩረት ልንነፍጋቸውና ልንዘጋቸው እንችላለን፤ በአንድ መንገድ እየሄድን፣ ፊት ለፊት ተገጣጥመን ባላየ፣ ባልሰማ ልናልፋቸው እንችላለን። ችግሩ አለመገጣጠማችን ላይ ሳይሆን ሕብረት ለማድረግ ፍላጎት ማጣታችን ላይ ነው። በጸሎትና እግዚአብሔርን በመፈለግ አጥብቄ የማምን ሰው ብሆንም፣ እርሱን ለመፈለግ አቅም ያገኘሁባቸው፣ በፊቱ ለመቆየት የበረታሁባቸው እልፍ ጊዜዎች ቢኖሩም፤ በተቃራኒው ደግሞ ጊዜ ሞልቶና ተርፎኝ ሳለ እግዚአብሔርን መፈለግ፣ ቃሉን ማጥናት፣ መጸለይ ዳገት ሆኖብኝ ያውቃል። እርሱን መፈለግ እንዳለብኝ አእምሮዬ እያወቀ ልቤና ጉልበቴ ግን አልታዘዝ ብሎኝ፣ ተደላድዬ፣ የለብታን ካባ እንደ ጌጠኛ ልብስ ተጎናጽፌ አውቃለሁ። በዚህ ሁሉ ውስጥ ግን ቸሩ እግዚአብሔር ያስተማረኝ ነገር ቢኖር፦ መንፈሳዊ ግለትን መጠበቅ ወሳኝና ቁልፍ ነገር መሆኑን፣ ረሃብ አብዝቶ ለመብላት መጥቀሙን፣ ያልተራበ ሰው ለምግብ ፍላጎት እንደሚያጣ ሁሉ እግዚአብሔርን አብዝቶ ለመጠጋትም ረሃብ ቁልፍ ነገር መሆኑን ነው። ለእግዚአብሔር ረሃብ የሌለው ሰው እግዚአብሔርን ስለመፈለግ ብዙ እያወቀ፣ እያስተማረ፣ እየበከ እግዚአብሔር ለመፈለግ ግን አቅም አይኖረውም፤ እግዚአብሔርንም ለመፈለግ ልቡ አይበረታም። ችግሩ የእውቀት ጉድለት ቢሆን ኖሮ በብዙ ምክር፣ በብዙ ትምህርት፣ በብዙ ስብከት በተመለሰ፣ እግዚአብሔርንም ለመፈለግ ኃይል በሆነለት ነበር። ነገር ግን ከእግዚአብሔር ጋር የሚያጣብቀው፣ በፊቱም የሚያሰነብተው መንፈስ ቅዱስ የሰውን ልብ ካልነካ፣ ለልባችን ልብ ሰጥቶት እርሱን እንድንፈልግ ካልረዳን፣ ቀድሞ ከወደድነው በላይ በእግዚአብሔር ፍቅር እንድንጠመድ ፍቅሩን በልባችን ካላፈሰሰ፣ እልፍ ረሃብ ካልጨመረልን በራሳችን አንዳች ማድረግ አንችልም። ይሄን ሁሉ ስረዳ ረሃቤን በስስት እያየኹ እግዚአብሔርን እንዲህ ስል አጥብቄ መለመን ጀመርኹ፦ እባክህ ረሃቤን አቆይልኝ፤ ረሃቤን ሊወስዱ በዙሪያዬ ለሚያደቡ ነገሮች አሳልፈህ አትስጠኝ፤ የአንተን እልፍ ረሃብ ጨምርልኝ። ስራብኽ መገኛዬ፣ መሰንበቻዬ እግርህ ሥር ይሆናልና በሰጠኸኝ በመንፈስ ቅዱስ የአንተን ፍቅር የአንተን ረሃብ በልቤ ደግመህ፣ ደጋግመህ አፍስስ!! አሜን!! ✍️ መክሊት አየለ 📆 June 4, 2026 #HOPMinistry #HearObeyPractice #DailyDevotional

#ወደር_የሌለውን_ጌታ_ክርስቶስ_ኢየሱስን_ከማወቅ_ታላቅነት_ጋር_ሲነጻጸር_የቱም_ነገር_ሚዛን_አይደፋም!
+6
#ወደር_የሌለውን_ጌታ_ክርስቶስ_ኢየሱስን_ከማወቅ_ታላቅነት_ጋር_ሲነጻጸር_የቱም_ነገር_ሚዛን_አይደፋም!

4_5855132003271182648.m4a7.52 MB

#የቱም_ነገር_ሚዛን_አይደፋም! ሐዋርያው ጳውሎስ በሰው መስፈርት ሲታይ አለ የሚባል ብዙ ውድና የከበረ፣ ትምክህት ሊሆን የሚችል ነገር ነበረው። እርሱ ያለው ነገር #መናኛ የሆነውና እዚህ ግባ የማይባል የሆነው #ወደር_የሌለውን_ጌታ_ክርስቶስ_ኢየሱስን_ከማወቅ_ታላቅነት_ጋር_ሲነጻጸር_ነው። ጌታ ኢየሱስን የማወቅ ታላቅነት ሲገባን የቱም ነገር ቢሆን በእኛ ሕይወት ላይ ከኢየሱስ በልጦ ሚዛን አይደፋም። ረሃባችን፣ ጉጉታችን #Passion ናችን ሁሉ ለራሱ ለክርስቶስ ኢየሱስ ይሆናል፤ እርሱ የሰጠን ምድራዊ ነገር ጋር ቆመን በጠፊ በአላፊዊ ስንደነቅ ዘመናችን አይባክንም። ይልቁንም የእግዚአብሔርን ምርጥ፣ የእግዚአብሔርን ውድ ኢየሱስን ለማወቅ ስንተጋና፣ ስለ እርሱ ሁሉን ስንንቅ ዘመናችን ይጠቀለላል። ፊልጵስዩስ 3 (አዲሱ መ.ት) ¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯ ⁷ ነገር ግን ይጠቅመኝ የነበረውን ሁሉ አሁን ለክርስቶስ ስል እንደ ጒድለት ቈጥሬዋለሁ። ⁸ ከዚህም በላይ ለእርሱ ብዬ ሁሉን ነገር የተውሁለትን፣ ወደር የሌለውን ጌታዬን ክርስቶስ ኢየሱስን ከማወቅ ታላቅነት ጋር ሳነጻጽር፣ ሁሉንም ነገር እንደ ጒድለት እቈጥረዋለሁ፤ ለእርሱ ስል ሁሉን አጥቻለሁ፤ ክርስቶስን አገኝ ዘንድ ሁሉን እንደ ጒድፍ እቈጥራለሁ፤ ✍️ መክሊት አየለ 📆 October 25, 2024

ፓስተር_እንዳለ_ወ_ጊዬርጊስ_ዘላለማዊ_Pastor_Endale_W_Giorgis_Zelalemawi_Lyrics128k.m4a5.10 MB

#የዘላለሙን_በእራፊ_አንለውጥ! እርሱን ለብሰን በርዶን ሙቀት ፍለጋ ሌላ ሸማ ለመደረብ አንሄድም፤ እርሱን ለብሰን እርቃናችን ታየ ብለን ሌላ መደረቢያ፣ መሸፈኛም ፍለጋ አንወጣም፤ እርሱን ለብሰን ውበት አጣን፣ ሞገስም ጎድሎናል ብለን ሌላ መጎናጸፊያ ፍለጋ አንባክንም። ነገር ግን ለዘላለም ለብሰነው ሊያደምቀን፣ ሊያሞቀን፣ ነውራችንንም ሊሸፍን ኢየሱስ ልብስ ሆኖናል፤ መጎናጸፊያችንም ነው። ቀድሞ ስንኖርባቸው ከነበረው፣ አሁን ግን በእርሱ ሥራ ገፍፈን ከጣልናቸው ክፉ ባህሪያት፣ ደግሞም በየዕለቱ ጠልፎ ሊጥለን ከሚያደባው የዓለም የኃጢአት ግብዣ የሚያስመልጥ ፍቱኑ፣ ብቸኛው መድኃኒት ኢየሱስን ለብሶ፣ በየዕለቱ እየለበሱ....እየለበሱ....እየለበሱ....፤ በእርሱ ተጎናጽፎ መኖር ነው። እርቃናችንን ሊጠቁሙ፣ ሊያሸማቅቁንም በሚሹ ነገሮች ፊት በድፍረት መቆም የምንችለው፦ የማያልፈውን፣ የማያድፈውን፣ የማይሻረውን፣ የዘላለም ልብስ ኢየሱስን ስንለብስ ብቻ ነው። ሞገሳሙን የሕይወት ሸማ አስቀምጠን የእኛን መናኛ እራፊ ለማሳየት፣ ምኞቱንም እንዲፈጽም በሐሳባችን ለሥጋ በመመቻቸት አንባክን። ይልቁንም በዘላለሙ፣ በእግዚአብሔር ፊት ሞገስ ባለውና በማያሳፍረው ልብስ በኢየሱስ እንዋብ፤ እንረፍ!! “ከክርስቶስ ጋር አንድ ትሆኑ ዘንድ የተጠመቃችሁ ሁላችሁ ክርስቶስን ለብሳችሁታልና።” — ገላትያ 3፥27 (አዲሱ መ.ት) “ይልቁንም ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን ልበሱት፤ ምኞቱንም ይፈጽም ዘንድ ለሥጋ በሐሳባችሁ አትመቻቹለት።” — ሮሜ 13፥14 (አዲሱ መ.ት) ✍️ መክሊት አየለ 📆 June 4, 2026

🎙 Welcome to our book reading journey! Join us as we explore The Martyr of Catacomb—a powerful story of faith, courage, and devotion to Christ. 📖 Hear. Obey. Practice. 📢 t.me/hopministry10

https://vt.tiktok.com/ZSxop5rMm/ 🔥 A story that shook ancient Rome. 📖 A faith that refused to bow. Join us as we begin reading The Martyr of Catacomb — a powerful journey of faith, courage, and devotion to Christ. 📢 Telegram: t.me/hopministry10 📘 Facebook: facebook.com/hopministry10 🎵 TikTok: @hopministry #HOPMinistry #HearObeyPractice #TheMartyrOfCatacomb

ፓስተር_ታምራት_ኃይሌ_ጌታቸው_በመጣ_ጊዜ_Pastor_Tamirat_Haile_Getachew_Bemeta_Gize.m4a5.07 MB

ስለ ዘመን መጨረሻ፣ ስለ ዓለም ፍጻሜ፣ በመጨረሻ ስለሚሆኑ ነገሮች ከቅዱሱ የእግዚአብሔር ቃል ከተማርን በኋላ፣ አሁን ያለንበት ዘመንም የመጨረሻው ዘመንና ካመንበት ቀን እንዲሁም ከትናንት ይልቅ መዳናችን ወደ እኛ ቅርብ የሆነበት ዘመን መሆኑን ከተረዳን በኋላ ዋና ነገር መሆን ያለበት፦ 👉 በዚህ ሁሉ ውስጥ እኔ እንዴት ዓይነት ሰው መሆን ይገባኛል? 👉 የጌታን ቀን መምጣት በምን ዓይነት ሁኔታ ነው መጠባበቅ ያለብኝ የሚለው ነው። ጌታችን ኢየሱስ ወዶ፣ በፈቃዱ የሚጨምርልን እድሜና ቀናት ሁሉ የእኛን ጥለን የእርሱን ፈቃድ የምንኖርበት፤ እርሱን ማክበርና ማስደሰትም ለምን አልሆነም እያልን ዘወትር የምናሰላስለው፣ የምንተጋለት፣ ልናየው የምንናፍቀው #ዋና ጉዳያችን እንዲሆንልን ጌታ ይርዳን!! በዚህ ወቅት የእኛ ትልቁ ስራ መሆን ያለበት የዘመኑን ክፋት ማውራት፣ በአንደበት የዘመን መጨረሻ ነው እያሉ በተግባር ግን ገና ምንም ያልተነካና እልፍ ቀን እንዳለው ሰው በቸልታና በዳተኝነት መባከን ሳይሆን፤ ሊስተካከል የተገባውን አካሄዳችንን ማስተካከል፣ ወዲህ ወዲያ ከማለት ወጥተን በእግዚአብሔር ጉያ ስር መሸሸግ፣ ሊቀይረንና ሊሰራን ለሚችለው ለመንፈስ ቅዱስ ሁለንተናችንን እያስገዛን #እኛ_ላይ_መስራት ነው። 2ኛ ጴጥሮስ 3 (አዲሱ መ.ት) ¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯ ¹¹ እንግዲህ ሁሉም ነገር በዚህ ሁኔታ የሚጠፋ ከሆነ፣ #እናንተ_እንዴት_ዐይነት_ሰዎች_ልትሆኑ_ይገባችኋል? አዎን፣ በቅድስናና በእውነተኛ መንፈሳዊነት ልትኖሩ ይገባችኋል፤ ¹² ደግሞም የእግዚአብሔርን ቀን እየተጠባበቃችሁ መምጫውን ልታፋጥኑ ይገባል። በዚያን ቀን ሰማያት በእሳት ተቃጥለው ይጠፋሉ፤ የሰማይም ፍጥረት በታላቅ ትኵሳት ይቀልጣል። ✍️ መክሊት አየለ 📆 November 12, 2023

4_5935872526533003350.MP33.64 MB

#እስከ_ሰባት_ጊዜ_ነውን? ፍቅር ከአንደበት ሲያልፍ፣ በልብ ዘልቆ ከእጅ ጋር ሲጣመር፣ የወደቁትን ሲያይ፣ ለተቸገሩት ሲደርስ፣ ለሚያስፈልጋቸው ያለውን ለማካፈል ንፉግ ሳይሆን ሲቀር፣ አጥር ሰርቶ በራሱ ዛቢያ ከመዞር ይልቅ ወደ ሌሎች ሲፈስ፦ ይህ እውነተኛ አምልኮ ይባላል። ለፍቅራችን፣ ለአወዳደዳችን መለኪያ ሚዛኑ (Standard)  የሰዎች ተግባር፣ የእኛም ባህሪ፣ ለተዋዋልነው ውለታ የምንሰጣጠው ግብረመልስ አለመሆኑ፤ ይልቁንም እርሱ እንደወደደን፣ ስለ እኛም ነፍሱን አሳልፎ እንደሰጠ መሆኑ ፍቅርን እጅጉን ከባድና አይደፈሬ ያደርገዋል። ነገር ግን ከእግዜሩ ከተካፈልነው ባህሪ፣ ደግሞም በመንፈስ ቅዱስ በልባችን ከፈሰሰው ውጪ ወትሮስ ፍቅርን ማን የእኛ እና በእኛ አቅም የሚደፈር አደረገው? ለመውደድ የተለያየ ስሌትና ቀመር ማየት ያስፈልገናል ብዬ አላስብም። ማለትም በዘመናችን የሰዎችን ጫና ለማቅለል፤ አልያም መፍትሄ ሰጪና ጉድለት ሞዪ መስለው የግል ከረጢትና ካዝናን ለመሙላት ትልም እንደያዙት አምስቱ፣ አስርቱ፣ እልፍ ሲልም ሣምሳ የ........ መንገዶች እንደተሰኙት መጻሕፍት አይነት ውኃ የሌለባቸው ደረቅ ምንጮች፣ ዝናብ የሌላቸው ደመናዎች አያስፈልጉንም። ትክክለኛውን የፍቅር፣ የመውደድ ልኬት ቀና ብሎ ማየት፣ መለስ ብሎም ማጤን በቂ ነው። አቤት የእግዚአብሔር ቃል! ሰሚ ጆሮ፣ አስተዋይ ልቦና፣ የሚተገብርም እጅ ስለሌለን እንጂ ሁሉን ነገር ጥንቅቅ አድርጎ፣ ግልጽ አድርጎ፣ ፍንትው አድርጎ አስቀምጦልናልኮ!  እስቲ ቆይ ምን እንደሚል ልስማው በሚል አይነት ስሜት፣ ማረጋገጫ ፈልጎ፣ ደግሞ የራሱን መለኪያ አውጥቶ "እስከ ሰባት ጊዜ ነውን?" ሲል ጌታችን ኢየሱስን ደጋግሞ የሚበድል ወንድሙን ስንት ጊዜ ይቅር ማለት እንዳለበት እንደጠየቀው ጴጥሮስ ቅዱስ ቃሉን በዚህ ጉዳይ ላይ ምን ትላለህ? ብለን ጠጋ ብንለው ከደረጃ በታች (the minimum) የሆነውን ሳይሆን የመጨረሻ፣ ፍጹሙን እርከን (the maximum, the highest & the perfect) የሆነውን እውነት፣ ልኬት (standard) ያሳየናል። ያኔ በፍጹምነቱ ፊት መቆም፣ ለዚያም ዋጋ ከፍሎ ትክክለኛና የእግዚአብሔር የሆነውን ለመያዝ አቅም ካጣን ነገሮችን እያድበሰበስን ወደ ኋላ እናፈገፍጋለን። ከሰዎች ጋር ባለን ሕብረት በዘመነኛው እና በሰሞነኛው ቋንቋ #Red_Flags ተብለው የተቀመጡ (ብለው ያስቀመጡልን) ብዙ ነገሮች አሉ። ማለትም ይሄን፣ ይሄን፣ እነዚህን......ካየህ/ካየሽ፣ እንዳትታገሺ/ እንዳትታገስ፣ ሽሺ/ሽሽ ብለው ያሰመሩልን መስመር፣ ያስቀመጡልን ገደብ ሞልቷል። እንደ እውነቱ ከሆነ የሰው ልጅ ልብ ከመነሾውም ክፉና ተንኮለኛ ነውና በደንብ ብንመረመር #ሬድ_ፍላጋም ያልሆነ አንድም አይገኝም። ታዲያ እውነታው ይህ ከሆነ ማን ኮናኝ፣ ማንስ ተኮናኝ ሊሆን ነው?! መቼም ከአንዱ ከእግዚአብሔር በቀር አይነቀፌ፣ ፍጹም ጽድቁን በድፍረት ሊያሳይና ኃጢአትን ሊኮንን የሚችል አንድም የለም። ታዲያ ይሄ ሁሉ እውነት ሆኖ ባለበት የሆነች ለራሳችን የምትመች አይነት አጥር ሰርተን፦ ይሄን ካደረገ/ች ይቅር ልል እችላለሁ፣ ይሄም ቢሆን በይቅርታ ይታለፋል፣ እንደዚህ ቢሆን ግን ይቅር ለማለት ይከብደኛል። ለማለት ማን መብቱን ሰጠን?! እስከ ሰባት ጊዜ ነውን? የሚለው የእኛ ጥያቄና ያስቀመጥነው ገደብ እንጂ የእግዜሩ፦ #እስከ_ሰባ_ጊዜ_ሰባት መሆኑን መች አስተዋልን?! ነፍስ ተሰጥቶት ፍቅርን ያወቀ፤ ቁስና፣ ከነፍስ አንጻር ሲታይ ቀላሉን ይቅርታ መስጠት እንዴት ትግል ይሆንበታል? ሲሆን ሲሆን፤ ቢሆንልን ጥሪያችን እኮ ነፍሳችንን እንድንሰጥ፣ ነፍሳችንንም እስከመስጠት እንድንዋደድ ነው። በሥራና በእውነት ለመዋደድ፣ የግብዝነትና የአንደበትን ፍቅር ከላያችን ገፍፎ ለመጣል ጸጋ ይብዛልን፤ መንፈስ ቅዱስ ያግዘን!! 1ኛ ዮሐንስ 3 (አዲሱ መ.ት) ¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯ ¹⁶ ኢየሱስ ክርስቶስ ሕይወቱን ስለ እኛ አሳልፎ ስለ ሰጠ፣ ፍቅር ምን እንደሆነ በዚህ እናውቃለን፤ እኛም ሕይወታችንን ስለ ወንድሞቻችን አሳልፈን ልንሰጥ ይገባናል። ¹⁷ ማንም ሀብት እያለው፣ ወንድሙ ሲቸገር አይቶ ባይራራለት፣ የእግዚአብሔር ፍቅር እንዴት በእርሱ ይኖራል? ¹⁸ ልጆች ሆይ፤ በተግባርና በእውነት እንጂ በቃልና በአንደበት ብቻ አንዋደድ። ማቴዎስ 18 (አዲሱ መ.ት) ¯¯¯¯¯¯¯¯¯¯ ²¹ በዚህ ጊዜ ጴጥሮስ ወደ ኢየሱስ ቀርቦ፣ “ጌታ ሆይ፤ ወንድሜ ቢበድለኝ ስንት ጊዜ ይቅር ልበለው? እስከ ሰባት ጊዜ ነውን?” አለው። ²² ኢየሱስም “እስከ ሰባ ጊዜ ሰባት እንጂ እስከ ሰባት ጊዜ ብቻ አልልህም” አለው። ✍️ መክሊት አየለ ከመጀሪያይቱ የሐዋርያው የዮሐንስ መልዕክት ጥናቴና ከጥሞና ጊዜዬ የተቀዳ። 📆 June 1, 2026