en
Feedback
Mahtot Eshetie / ማኅቶት እሸቴ

Mahtot Eshetie / ማኅቶት እሸቴ

Open in Telegram

መንፈሳዊ የቤተክርስቲያን አስተምህሮና ሙሉ የግእዝ ቋንቋ ሥልጠና ትምህርት ማስተማሪያ የቴሌግራም ገጽ። በመደበኛ መርሐ ግብር የግእዝ ቋንቋ ሥልጠናን መከታተል የምትሹ በኮሜንት መስጫው ጻፉልኝ።

Show more
4 667
Subscribers
+3324 hours
+1987 days
+20530 days
Posts Archive
ሁለቱ ዓለቶች.... መድኅነ ዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ ወደዚህ ምድር የሰውን ልጅ ለማዳን ሲመጣ እርሱ በሄደት ሂደው እርሱ በተጓዘበት ተጉዘው እርሱ ያስተማረውን ወንጌል አስተምረው አሕዛብን አይሁዳውያንን በጥምቀት ወደ እግዚአብሔር ልጅነት የሚመልሱ ሐዋርያትን ሾመልን። ከእነዚህም ሐዋርያት መካከል በጥብዓታቸው ወንጌልን ዙረው ያስተማሩ ለክርስቶስ ካላቸው ፍቅር በመነሣት ደማቸውን በሮም አደባባይ በ67 ዓ.ም በኔሮን ቄሣር ተእዛዝ ደማቸውን ያፈሰሱ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ቀዳሚዎቹ ናቸው። ቅዱስ ጴጥሮስና ጳውሎስ የመጀመሪያዎቹ የቤተክርስቲያን አባቶች እንደ መሆናቸው ብዙ ነገር ያመሳስላቸዋል። ✍️ የቤተክርስቲያን መሠረትነት ➢ ቅዱስ ጴጥሮስ ከጌታ የቀረበለትን ማን ትሉኛላችሁ የሚለውን ጥያቄ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ ብሎ በትክክል በመመለሱ ፤ በቂሣርያ በእርሱ መሠረትነት ክርስቶስ ቤተክርስቲያንን ሠራት። ማቴ 16፥18 ➢ በቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት ከአሕዛብ የተመለሱ ክርስቲያኖች የምንጸልይበት ቤት ሥሩልን በማለታቸው የመጀመሪያዋ ቤተክርስቲያን በፊልጽስዩስ ቂሣርያ በቅዱስ ጳውሎስ አሳሳቢነት ተገነባች። በሁሉቱ ዓለትነትም ቤተክርስቲያን ተሠራች። ✍️ ከክህደት ወደ እምነት መመለስ ➢ በዕለተ ዐርብ አስክዶ ከክርስቶስ ፍቅር የለየውን ሠይጣን በንስሓ ተመልሶ ከሰዎች ልቦና ሲያሳድደው ይኖራል። ➢ ክርስቶስን በመካድ ክርስቲያኖችን እንዲያሳድድ ያበረታውን ሰይጣን በእምነት ተመልሶ ከክርስቲያኖች ልቦና ሲያሳድደው ይኖራል። ✍️ በሞቱ መምሰል ➢ በዕለ ዐርብ የጌታን መሰቀል ያየው ጴጥሮስ በትሕትና ስለ ፍቅሩ ተዘቅዝቆ ተሰቀለ። ➢ በሞቱ እንመስለዋለን እያለ ያስተማረለትን አምላክ መከራ በቀበል መሰለው። ✍️በፍቅር መገለጥ ➢ ፍቅርን ከክርስቶስ የተማረው ቅዱስ ጴጥሮስ " ፍቅር የኃጢአትን ብዛት ይሸፍናልና ከሁሉ በፊት እርስ በርሳችሁ አጥብቃችሁ ተዋደዱ።" በማለት በተግባር አስተማረ። (1ኛ ጴጥ 4:8) ➢ ፍቅረ ክርስቶስ በልቡናው የተሣለበት ጳውሎስ "ከሁሉም ፍቅር ይበልጣል" ብሎ በማስተማሩ የፍቅር ሐዋርያ ተባለ። 1ኛ ቆሮ 13÷13 ✍️ ወንጌልን ዙሮ ማስተማር ➢ ቅዱስ ጴጥሮስ ሊቀ ሐዋርያ እንደ መሆኑ ሌሎቹን ሐዋርያት ወደየ ሀገረ ስብከታቸው እያደረሰ እያበረታ እንዳባትነቱ ወንጌልን እንዲያስተምሩ በጥበብ እየመከረ እርሱም ወንጌልን አስተማረ። ለምእመናንም ያስተማረውን ጻፈላቸው። ➢ ቅዱስ ጳውሎስ እስከ ምድር ዳርቻ በመሄድ የወንጌልን ቃል አስተማረ። ያስተማረውንም ጻፈላቸው። ✍️በጸጋ መገለጥ ➢ ቅዱስ ጴጥሮስ ከጸጋው ብዛት የተነሣ በጥላው ድውያንን ይፈውስ ነበር። ሐዋ 5፥15 ➢ ቅዱስ ጳውሎስም በልብሱ ጫፍ ሕሙማንን ይፈውስ ነበር። ✍️ የእስር ቤት መመሳሰል ➢ ቅዱስ ጴጥሮስ በታሰረ ጊዜ መልአኩ የእርስ ቤቱን በር ከፍቶ አወጣው። ሐዋ 12፥10 ➢ ቅዱስ ጳውሎስ በታሰረ ጊዜ በእርስ ቤቱ ውስጥ ሲዘምር የእስር ቤቱ ደጆች ተከፈቱ። ሐዋ 16 ÷ 26 ✍️ ሁለቱ ዓለቶች ጌታችን በወንጌል "ይህን ቃሌን ሰምቶ የሚያደርገው ሁሉ ቤቱን በዓለት ላይ የሠራ ልባም ሰውን ይመስላል። ዝናብም ወረደ ጎርፍም መጣ ነፋስም ነፈሰ ያንም ቤት ገፋው፥ በዓለት ላይም ስለ ተመሠረተ አልወደቀም።" ብሏል። (ማቴ 7÷ 24-25 ) ይህች ቤት የተሠራባት ዓለት ክርስቶስ የተገለጠባት የጴጥሮስ እና የጳውሎስ ትምህርት እምነት ሥልጣን ናት። ስለዚህ በእነዚህ ሁለት ዓለቶች ላይ ቤቱን የሠራ ቤቱ በንፋስ በዝናም በጎርፍ አይወድቅም። በዓለት ላይ ተሠርቷልና። እንደዚሁም ሁሉ ልቡናውን በጴጥሮስ በጳውሎስ ሃይማኖት ትምህርት ያጸና በክህደት በኑፋቄ አይወሰድም። ልቡናውን በጴጥሮስ በጳውሎስ እምነት ፣ ትምህርት ፣ በእነርሱ ሥልጣን በተገኘ ልጅነት አጽንቷልና። ✍️ የሐዋርያት በረከት ይደርብን። ➜ ሐምሌ / 5 / 2018 ዓ.ም © ማኅቶት እሸቴ 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21 👇👇👇 የፌስቡክ አድራሻ https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1

ይሄ ለዘመናችን ትውልድ የተሰጠ ታላቅ እድል ነው የታሪኩ ባለቤቶች ሁላችንም ነን ተባብሮ መሥራትም የሁላችንም ድርሻ ነው። ሰንፔር የሕክምና መንደር ሁሉም አካውንቶች በጣና ቂርቆስ የአራቱ ትርጓሜ መጻ
ይሄ ለዘመናችን ትውልድ የተሰጠ ታላቅ እድል ነው የታሪኩ ባለቤቶች ሁላችንም ነን ተባብሮ መሥራትም የሁላችንም ድርሻ ነው። ሰንፔር የሕክምና መንደር ሁሉም አካውንቶች በጣና ቂርቆስ የአራቱ ትርጓሜ መጻሕፍት ጉባኤ ቤት ስም ነው።

የዮሐንስ አፈወርቅ ቅዳሴ መጽሐፈ ቅዳሴ ማብራሪያ #ክፍል_ሰባ_ስምንት 💎 አዳምን የፈጠሩ እጆች ተቸነከሩ ✍️ መግቢያ ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ብዙ ድረስት የደረሰ ብዙ ተግሣጽ የጻፈ ሲሆን ከእነዚህም ውስጥ ቅዳሴው አንዱ ነው። አኰቴተ ቍርባን ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጸሎቱ ወበረከቱ የሀሉ ምስለ ኵልነ ሕዝበ ክርስቲያን ለዓለመ ዓለም አሜን። የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የቍርባን ምስጋና ይህ ነው። ጸሎቱና በረከቱ ከሁላችን ሕዝበ ክርስቲያን ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ✍️ ካህኑ በመጀመሪያ ጸሎቱ ይህንን ይጸልያል ➢ ዓለም ሳይፈጠር የነበረው ለዘላለም የሚኖር የአብን አነዋወሩን እነሆ እንናገራለን። ከርሱ አስቀድሞ የለም። ከርሱም በኋላ የለም። እንደ እርሱም ያለ የሚያውቅ የለም። ➢ ሰማያት ሳይዘረጉ ፣ የብሱ ሳይታይ ፣ ተራሮች ሳይዘረጉ ፣ የአየር ርዝመት ሳይከፈት በባሕርዩ የነበረ ነው። ➢ ከቀላያት መፍሰስ ፣ ከነፋሳት መንፈስ ፣ ከብርሃናት መመላለስ ፣ ከደመናት ፣ ከመባርቅት ፣ ከነጎድጓድ ፣ ከፀሐይ ፣ ከጨረቃ ፣ ከከዋክብት በፊት በባሕርዩ የነበረ ነው። ➢ ከጊዜና ከሰዓት ፣ ከመዓልትና ከሌሊት ፣ ከወርና ከዓመት ፣ ከአዝማናትና ከዕለታት አስቀድሞ በባሕርዩ የነበረ ነው። ✍️ ስለ ሕማሙና ስለሞቱ ካህኑ የተሰበሰብን እኛም የማይሞት የርሱን ሞቱን እንናገራለን። የማይታመም የርሱን ሕማሙን እንናገራለን። በማለት ጀምሮ ስለ ሕማሙ ስለ ሞቱ እንዲህ እያለ ይናገራል። ➢ ሁሉን የያዘውን ያዙት ሁሉን የሚገዛውን አሠሩት ፣ የአምላክን ልጅ አሠሩት በቁጣ ጎተቱት በፍቅር ተከተላቸው። በሚሸልተው ፊት እንደማይናገር እንደ የዋሕ በግ በኋላቸው እየተከተለ ወሰዱት። ➢ ሊቀነ መላእክት በፊቱ እየተንቀጠቀጡ የሚቆሙለትን በአደባባይ አቆሙት። ኃጢአትን ይቅር የሚለውን ኃጥእ አሉት። በመኳንንት የሚፈርድባቸውን በርሱ ፈረዱበት። ➢ ለሱራፌል ዘውድ የሚያቀዳጃቸውን የእሾኽ ዘውድ አቀዳጁት። ለኪሩቤል የግርማ ልብስ የሚየለብሳቸውን ለመዘበት ቀይ ግምጃ አለበሱት። ➢ ኪሩቤል በእሳት ክንፍ ተሸፍነው በፊቱ የሚሠወሩለትን ክፉ ባሪያ እጁን አጽንቶ በጥፊ መታው። ➢ የመላእክት ሠራዊት በመደንገጥ ለሚሰግዱለት እየዘበቱበት በፊቱ ተንበረከኩ። ➢ ይህን ያህል ትሕትና እንደምን ያለ ትሕትና ነው። ይህን ያህል ትዕግሥት እንደምን ያለ ትዕግሥት ነው። ይህን ያህል ዝምታ እንደምን ያለ ዝምታ ነው። ➢ ይህን ያህል ቸርነት እንደምን ያለ ቸርነት ነው። ይህን ያህል ሰውን ማፍቀር እንደምን ያለ ሰውን ፍቅር ነው። ➢ ኃያል ወልድን ፍቅር ከዙፋኑ ሳበው እስከ ሞትም አደረሰው። በደል የሌለበትን እንደ በደለኛ ሰቀሉት። ሕይወትን የሠራውን ከበደለኞች ጋራ ቆጠሩት። ➢ አደምን የፈጠሩ እጆች በመስቀል ቀኖት ተቸነከሩ። ወዮ በገነት የተመላለሱ እግሮች በመስቀል ቀኖት ተቸነከሩ። ➢ ወዮ በአዳም ፊት የሕይወት መንፈስን እፍ ያለ አፍ ከሐሞት ጋራ ነተቀላቀለ የኮመጠጠ መጻጻን ጠጣ። ➢ የጌታን መከራውን የሚናገር ምን አንደበት ነው። ➢ የማይሞተው ሞተ ሞትን ይሽረው ዘንድ ሞተ ሙታንን ያድናቸው ዘንድ ሞተ። ይ.ዲ :- የምትወዱት ሰዎች ፈጽሞ አልቅሱለት። #ማጠቃለያ :- ከአሥራ አራቱ ቅዳሴ ውስጥ የጌታን ሕማሙን ሞቱን በሰፊውና በዝርዝር የሚናገር የዮሐንስ አፈወርቅ ቅዳሴ ሲሆን ይኸውም የጌታ ሕማሙ ሞቱ በሚታሰብባቸው ቀናት (በየወሩ በ27) ይቀደሳል። #ተፈጸመ_ቅዳሴ_ዮሐንስ_አፈወርቅ ➢➢ የቀጣይ ትምህርት #ክፍል_ሰባ_ዘጠኝ የቄርሎስ ቅዳሴ ➜ ሐምሌ / 3 / 2018 ዓ.ም © ማኅቶት እሸቴ 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21 👇👇👇 የፌስቡክ አድራሻ https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1

የኤጲፋንዮስ ቅዳሴ መጽሐፈ ቅዳሴ ማብራሪያ #ክፍል_ሰባ_ሰባት 💎 የጥበብ አገሯ ወዴት ነው ✍️ ካህኑ በዚህ ጸሎት ➢ ፍጥረታት ሁሉ የእግዚአብሔር ሁሉ እንደሆኑ እሊህም የእጁ ሥራ የሆኑት ፀሐይ ጨረቃ ከዋክብት። ➢ ጠፈር ፣ ደመና ፣ ዝናም ፣ መብረቅ የእርሱ ገንዘቦቹ ናቸው። ➢ እግዚአብሔር ያሰበውን ያደርጋል የወደደውን የምራል። የሚምረውንም ይምራል። #ማብራሪያ :- የሚምረውን ይምራል ማለት በንስሓ ማሰኝ ብሎ የተመለሰውን ለምሕረት የሚያበቃ በጎ ሥራ የሠራውን ይምረዋል ማለት ነው። ✍️ የመፈተት ጸሎት ካህኑ በዚህ ጸሎቱ ይህንን ይጸልያል። ➢ የጥበብ አገሯ ወዴት ነው። ማደሪያዋስ ወዴት ነው። ቦታዋ ወዴት ነው። የጎዳናዋስ ፍለጋ በወዴት ተገኘ። ማነው ከደመናትስ በላይ ወጥቶ ያወረዳት ማነው። መዋቲ ጎዳናዋን አላወቃትም በሰውም ዘንድ የለችም። ➢ ጥበብ ሁሉ ተዘነጋች ከሰማይ አዕዋፍም ሁሉ ተሠወረች እርስዋን የገዙ ከእግዚአብሔር ጋራ ተወዳጁ። እርሷን የሚጠሏት ሞትን ይወዳሉ። ከፀሐይ ይልቅ ታምራለች ከከዋክብትም አኗኗር። እርስዋ ቀዳማዊት እንደ መሆንዋ ከብርሃን ጋራ ስትነጻጸር ትገኛለች። ➢ ጥበብ በእርጅና ሳለች ሁሉን ታድሳለች በየትውልዱም ከጻድቃን ሰውነት ጋራ ትፋለሳለች። ካህኑ ከዚህም በቀጠል የጥበብን ነገር እንዲህ እያለ ይናገራል። ➢ ዋጋዋ ከከበረ ዕንቍ የበለጠ መሆኑ። ➢ ነገሥታት በእርሷ ይነግሣሉ። ➢ ለሚወዷት ባለጸግነትን ትሰጣለች። ➢ ጥበብ ቤቷን ሠራች ሰባት ምሰሶዎችንም አቆመች። ➢ በመጨረሻም ጥበብ ግን መድኃኒታችን ነው በሥጋው መሥዋዕትነት ያዳነን በደሙም ፈሳሽነት የተወዳጀን ለመንግሥቱም የመረጠን ለዘላለሙ። አሜን። #ማብራሪያ :- በጥበብ የተመሰሉ ጥበብ የተባሉ እነዚህ ናቸው። ➢ ሃይማኖት ➢ ፍቅር ➢ ወንጌል ➢ መስቀል ➢ እራሱ ጌታ ነው። ✍️ የሐዳፌ ነፍስ ጸሎት ካህኑ በቅዳሴ መጨረሻ ጸሎቱ ይህንን ይጸልያል ➢ አዎን አቤቱ የሁሉ ጌታ ነህ ፣ የሁሉ አምላክ ነህ ፣ የሁሉ ንጉሥ ነህ ፣ ሁሉን የያዝህ ነህ ፣ ሁሉን የምትገዛ ነህ ፣ ሁሉን የምታድን ነህ ፣ የሁሉ መድኃኒት ነህ ፣ ሁሉን የምትጠብቅ ነህ ፣ ሁሉን የምትመግብ ነህ ፣ በእውነት የሁሉ ገዥ ነህ። ➢ የልጅህን ሥጋ ከእኛ ሥጋ ጋራ አንድ እንዳደረግህ የመሢህንም ደም ከእኛ ደም ጋራ አንድ እንዳደረግህ እንዲሁ አንተን መፍራትን በልቡናችን በጎ አምልኮትህንም በሕሊናችን ጨምር። ➢ ሥጋውያን የምንሆን እኛ ግን የሥጋን ሕግ እናስባለን የሥጋንም ሥራ እንሠራለን በሥጋ መንገድም እንሄዳለን አንተ ግን የመንፈስን ሕግ አስተምረን የመንፈስንም ሥራ አንተ አስረዳን የመንፈስን መንገድ ምራን። ➢ እኛን ኃጥአንን ብትምረን ያን ጊዜ መሐሪ ትባላለህና ጻድቃንን ግን ከሥራቸው የተነሣ ትምራቸዋለህ እንደ ጽድቃቸውም ትሰጣቸዋለህ። ➢ የቀደመ በደላችንን አታስብብን አቤቱ ይቅርታህ ፈጥኖ ይደረግልን። ወደ አንተ እንጮሃለን ወደ አንተ እናለቅሳለን ወደ አንተ እንማለላለን ለዘላለሙ። አሜን። #ተፈጸመ_ቅዳሴ_ኤጲፋንዮስ ➢➢ የቀጣይ ትምህርት #ክፍል_ሰባ_ስምንት የዮሐንስ አፈወርቅ ቅዳሴ ➜ ሐምሌ / 2 / 2018 ዓ.ም © ማኅቶት እሸቴ 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21 👇👇👇 የፌስቡክ አድራሻ https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1

የኤጲፋንዮስ ቅዳሴ መጽሐፈ ቅዳሴ ማብራሪያ #ክፍል_ሰባ_ስድስት 💎 ከባሕር ጥልቀት ይልቅ ጥልቅ ነው ✍️ መግቢያ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ የደሴተ ቆጵሮስ ኤጲስቆጶስ ነው። ይህ ቅዱስ አባቱና እናቱ አይሁዳውያን ናቸው። ቤተሰቦቹ ደሃ ነበሩ። አባቱም በልጅነቱ በመሞቱ በኑሮ ተቸገሩ። ነበራቸውም አንድ አህያ ብቻ ነበር። እናቱ አህያውን እንዲሸጥ ወደ ገቢያ ላከችው። አህያውን ሰዎች ሊገዙት ዋጋ በሚጠይቁት ጊዜ አህያው ተራጋጭ ነበርና አትናቴዎስን ረግጦ ገደለው። በገበያው መካከል የነበረና ይህንን ክስተት ያየ አባ ፊሎጎስ ጸልዮ በክርስቶስ ስም አትናቴዎስን ከሞት አስነሣው አህያውንም ይሞት ዘንድ አዘዘውና ሞተ። አትናቴዎስም እኔን ያስነሣህበት አህያውንም ጸልየህ የገደልክበት የኔ ዘመዶች አይሁዳውን ሩቅ ብእሲ ብለው ሰቅለው የገደሉት ነውን አለው። አዎ አለው። ይህ ነገር በልቡናው ቀረ። ባለጸጋ አይሁዳዊ አጎት ነበረው ሀብቱን አውርሶት ሞተ። በገንዘቡም የነቢያትን መጻሕፍት ገዛ። ከዕለት በአንድ ቀን አባ ሉክያኖስ (አባ ፊላታዎስ) የተባለ መነኵሴ መንገድ ሲሆድ አትናቴዎስ ከወደ ኋላው ይከተለው ነበር። በንገድ የተቀመጠ አንድ ችግረኛ ነዳይ ስመ እግዚአብሔር ጠርቶ አባ ፊላታዎስን ለመነው። አባ ፊላታዎስ የሚሰጠው ገንዘብ የለውም ነበር ነገር ግን ስመ እግዚአብሔር ስለጠራበት የለበሰውን አጽፍ (ፎጣ ወይም ኩታ አይነት) አውልቆ አለበሰው። በዚህ ጊዜ ብርህት አጽፍ (የብርሃን ልብስ) ከሰማይ ወርዳ ፊላታዎስን ስታለብሰው ከኋላ ያለው አትናቴዎስ ይመለከታል። ነገሩ ቢረቅበት ቀርቦ ጠየቀው በማን ስም እንመጸወተ ሲጠይቀው በክርስቶስ ስም እንደ ሆነ ነገረው። ይህ የኔ ዘመዶች አይሁዳውያን የሰቀሉት ነውን አለው አዎ አለው። አጥምቀኝ አለው እስከ እኅቱ አጠመቀው። ኋላም በእግዚአብሔር ትእዛዝ በቆጵሮስ ሀገር ጵጵስና ተሹሟል። የነበረበት ዘመንም ከቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጋር አንድ ነው። ከቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጋርም አንዳቸው ስለ አንዳቸው አሟሟት ተገልጾላቸው ተነጋግረው በአንድ ዘመን ዐርፈዋል። ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ብዙ ድርሳን ደርሷል ብዙ ተግሣጽ ጽፏል ከብዙውም አንዱ ይህ ቅዳሴው ነው። ካህኑ :- አኰቴተ ቍርባን ዘቅዱስ ኤጲፋንዮስ ኤጲስቆጶስ ዘደሴተ ቆጵሮስ ጸሎቱ ወበረከቱ የሀሉ ምስለ ኵልነ ሕዝበ ክርስቲያን ለዓለመ ዓለም አሜን። የቆጵሮስ ደሴት ኤጲስቆጶስ ቅዱስ አትናቴዎስ የተናገረው የቍርባን ምስጋና ይህ ነው። ጸሎቱና በረከቱ ከሁላችን ሕዝበ ክርስቲያን ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ✍️ የመጀመሪያው የጸሎት ይዘት ➢ እግዚአብሔር በገናንነቱ ገናና ነው። ከመቼ ወዲህ የማይሉት ቀዳማዊ ነው። እስከ ዛሬ የማይሉት ማዕከላዊ ነው። እስከዚህ የማይሉት ደኃራዊ ነው። ➢ ለአነዋወሩ ጥንት የለውም ለአኳኋኑም ፍጻሜ የለውም ለዘመኑ ቁጥር የለውም ለዓመታቱም ልክ ቁጥር የለውም ለውርዝውናው ማርጀት የለበትም ለኃይሉም ጽናት ድካም የለበትም ለመልኩ ጥፋት የለበትም። ለፊቱ ብርሃንም ጨለማ የለበትም። ➢ ለጥበቡ ባሕር ድንበር የለውም። ለአገዛዙ ስፋት ወሰን የለውም። ➢ የጥበበኞችን ምክር የሚያጠፋ ጥበበኛ ነው። ➢ ጻድቁን ጽድቅ ሳይሠራ ያውቀዋል። ኃጢአተኛውንም ኃጢአት ሳይሠራ ያውቀዋል። ካህኑ በዚህ ጸሎቱ የእግዚአብሔር ሁሉን ቻይነት ፣ ሁሉን አዋቂነት ፣ ፍጥረታትን ፈጥሮ የሚያዛቸው ፣ ሁሉን ገዥና መጋቢ እንደ ሆነ ይናገራ። ➢➢ የቀጣይ ትምህርት #ክፍል_ሰባ_ስምንት የጥበብ አገሯ ወዴት ነው ➜ ሐምሌ / 1 / 2018 ዓ.ም © ማኅቶት እሸቴ 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21 👇👇👇 የፌስቡክ አድራሻ https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1

"ነዳያን ተርበው እነሱን አልፈህ ለቤተ መቅደስ ሻማ ብታበራ የነዳያን ዕንባ ያጠፋዋል" አፈወርቅ

"እንኳን ሰው መልአክ ይሳሳታል" አባታችን እናመሰግናለን። ክቡር ኮከበ ሊቃውንት አራት ዓይና አባ ገብረ ማርያም ጌጡ ➢ልጆቼን ምእመናንን አደናግሬያለሁ ይቅርታ ፣ ንግግሬ ስሕተት ነው ፣ ይሄ የቤተክ
"እንኳን ሰው መልአክ ይሳሳታል" አባታችን እናመሰግናለን። ክቡር ኮከበ ሊቃውንት አራት ዓይና አባ ገብረ ማርያም ጌጡ ➢ልጆቼን ምእመናንን አደናግሬያለሁ ይቅርታ ፣ ንግግሬ ስሕተት ነው ፣ ይሄ የቤተክርስቲያናችን አስተምህሮ አይደለም። ➢ ለ40 ዘመናት የተማርኩት በአንድ ስሕተት ማጥፋት አልፈልግም ፣ በስሕተት ሲዖል መግባት አልሻም። ➢ እኔ ሰው ነኝ እሳሳታለሁ። ንስሓንምኮ የሰጠን እንደምንሳሳት አውቆ ነው። ➢ ከመድረክ እንደወረድኩ የማስተምራቸው ደቀመዛሙርት አሰንደዚህ እኮ አላስተማሩንም አሉኝ። ➢ ከንባብ (ከዘር) ምሥጢር የያዘ ይሻላል። ትሕትና በተሞላበት መንገድ ሙሉ ገለጻ አድርገዋል። በዋካ ብርሃን ሚዲያ።

ይሄ ኅብረት ቤተክርስቲያንን ወደ ወርቃማው የሊቃውንት ዘመን እንደሚመልሳት ተስፋ አለን። 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21
ይሄ ኅብረት ቤተክርስቲያንን ወደ ወርቃማው የሊቃውንት ዘመን እንደሚመልሳት ተስፋ አለን። 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21

ቅኔ በሕፃን አንደበት በጎንደር ፈለገ ጥበብ በዓታ ለማርያም ትምህርት ቤት። የ ፳፻፲፰ ዓ.ም የተማሪዎች ምረቃ 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21

እኒህን አባት በዘመናችን ያስነሣ እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን። ሁሉም ነገር የተሰጣቸው ሊቅ እውቀት ፣ ከሕይወት ፣ ከተግባር ፣ ከአስተዳደር ፣ ከጥበብ ፣ ከፍቅረ ሰብእ ፣ ከትጋት ፣ ከአርቆ አሳቢ
+3
እኒህን አባት በዘመናችን ያስነሣ እግዚአብሔር የተመሰገነ ይሁን። ሁሉም ነገር የተሰጣቸው ሊቅ እውቀት ፣ ከሕይወት ፣ ከተግባር ፣ ከአስተዳደር ፣ ከጥበብ ፣ ከፍቅረ ሰብእ ፣ ከትጋት ፣ ከአርቆ አሳቢነት ፣ ለዓላማ ከመጽናት ወዘተርፈ። ርዕሰ ሊቃውንት አባ ገብረ ኪዳን ግርማ ሰንፔር ጠቅላላ ሆስፒታል ተመጽመሽ እንይሽ። 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21

ሕዝባዊ ጉባኤ በጎንደር በጎንደር በብቸኝነት በሚገኘው በደብረ ልዑላን ድል አምባ ቅዱስ አማኑኤል ቤተክርስቲያን የፊታችን እሑድ ሰኔ 28 ከቅዳሴ በኋላ ሕዝባዊ ጉባኤ በደብሩ ተዘጋጅቷል ታላላቅ መምህራ
ሕዝባዊ ጉባኤ በጎንደር በጎንደር በብቸኝነት በሚገኘው በደብረ ልዑላን ድል አምባ ቅዱስ አማኑኤል ቤተክርስቲያን የፊታችን እሑድ ሰኔ 28 ከቅዳሴ በኋላ ሕዝባዊ ጉባኤ በደብሩ ተዘጋጅቷል ታላላቅ መምህራን እና መዘምራን በቦታው ተገኝተው ሕዝቡን ያስተምራሉ በጎንደር እና አካባቢው ያላችሁ ምእመናን በዕለቱ በቦታው በመገኘት ቃለ ወንጌል ትማሩ ዘንድ ተጠርታችኋል። በከተማዋ ካሉት አብያተክርስቲያናት መካከል በጥቅጥቅ ደኑና በተራራማ ቦታው የተለየ የሆነው ጸጥታ የሰፈነበት የጎንደር ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የሚገለገሉበትና የሚማሩበት ቤተክርስቲያን አሁን ላይ በመገንባት ላይ ነው። በአከባቢው በቂ ምእመናን የሌሉት እንደመሆኑ ግንባታው በተፈለገው መጠን ሊሄድ አልቻለምና የሁላችንም እገዛ ይጠይቃል። የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ የቅዱስ አማኑኤል ቤተክርስቲያን ሕንፃ ማሠሪያ 1000413488242

ለመብላት የመነኰሰ ሰው መብል እስከተገኘበት ድረስ እንኳን ከተማ ሲኦልም ቢሆን ይገባል።
ለመብላት የመነኰሰ ሰው መብል እስከተገኘበት ድረስ እንኳን ከተማ ሲኦልም ቢሆን ይገባል።

የጎርጎርዮስ ቅዳሴ መጽሐፈ ቅዳሴ ማብራሪያ #ክፍል_ሰባ_አምት 💎 ሆሣዕና በአርያም የጎርጎርዮስ ቅዳሴ በዕለተ ሆሣዕና የሚቀደስ ከሌሎቹ ቅዳሴያት በተለየ ስለ ሆሣዕና በደንብ የሚያብራራና የሚናገር ቅዳሴ ነው። ቀዳስያናኑ ምእመናኑ ነአምን የሚለውን በዜማ ሙሉውን ብለው ከጨረሱ በኋላ ካህኑ ይህንን ይጸልያል ➢ ቃል ቀዳማዊ ነው። ያ ቃል የእግዚአብሔር ቃል ነው። ያ ቃል ሥጋ ሆነ በእኛም አደረ ከእኛም ሠወረው። #ማብራሪያ :- ከእኛ ሠወረው ማለት አካላዊ ቃል ሥጋን ተዋሕዶ በዚህ ዓለም በተመላለሰ ጊዜ በባሕርይው ያየው እና ያወቀው የለም በሥጋ ባሕሪ ተሠውሮ ነበርና። ከእኛ ሠወረው ማለቱም ይህንን መሠወሩን ነው። ➢ የሚጠፋ ሥጋን ለበሰ። የማይጠፋም አደረገው። በዚህች ሥጋ የማይገረፍ አምላክ ተገረፈ። ➢ ግርፋቱን ፣ በሊቃነ ካህናቱ ሸንጎ ራሱን በዘንግ መመታቱን ፣ የእሾህ አክሊል መቀዳጀቱን ታዩ ዘንድ ኑ። ➢ የአምላካችን የፊቱን መጸፋት ባየች ጊዜ ባሕር ተንቀጠቀጠች ማየ ተከዚም ሸሸች። ፀሐይ ጨለመ ጨረቃም ደም ሆነ ከዋክብትም ከብዙ ብርሃናቸው ተራቆቱ፧ ➢ ሞት ፈራ ዲያብሎስም ወደቀ። ሲኦልም ጎሩም የሆነ አምላኳን ለመቀበል ከወገኖችዋ ጋራ ባንድነት ሄደች። ➢ በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ ቡሩክ ነው አንተም የአማልክት አምላክ የእስራኤልም ንጉሥ እግዚአብሔር ቡሩክ ነህ እያሉ ለሚያመሰግኑ ሕፃናት ሁሉ ጌትነቱን አሳየ። ➢ የሆሣዕናን ዑደት ለደቀመዛሙርቱ አሳየ። ቡሩክ እርሱ በታላቅ ቃል እየጮኻችሁ ሆሣዕና በአርያም በሉ አላቸው። ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም። እየዞሩ ይበሉ። ይ.ካ ➢ ከመድኃኒትነቱ የተነሣ ከዚህ አስቀድሞ ያልተደረገ ከዚህም በኋላ የማይደረግ ተአምራትና መንክራትን አሳየ። ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም። እየዞሩ ይበሉ። ➢ ከመድኃኒትነቱ የተነሣ ከቤቱ መሠረት ሳይናወጥ ከልዑል መንበሩ ወርዶ ጸጋንና ኃይልን ሰጠ። ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም። እየዞሩ ይበሉ። ➢ ከመድኃኒትነቱ የተነሣ ለኃጥኣን የዕንባ ምንጭ ሰጠ። የበደሉትን ያጸድቃቸው ዘንድ የረከሱትን ያነጻቸው ዘንድ የሳቱትን ይመልሳቸው ዘንድ። ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም ሆሣዕና በአርያም። እየዞሩ ይበሉ። ➢ ከመድኃኒትነቱ የተነሣ ለዕውራን ዳግመኛ የማይጠፋ ዓለም ሊቀበለው የማይቻለው ብርሃንን ሰጣቸው። ከሕሊና አስቀድሞ ያውቃል ከአሳብም በፊት ይመራመራል የሚሠወረውም የለም። ✍️ የመፈተት ጸሎት በዚህ ጸሎት ካህኑ ከአበው አብርሃምናን መልከጼዴቅን እያነሣ ያመሰግናል። ይኸውም አብርሃም መሥዋዕት ለመሠዋት ወደ ተራራ መውጣቱን እየተናገረ ነው። በዚያም ካህኑ መልከጼዴቅ እንደተገናኘው ያነሣል። በመጨረሻም ካህኑ በአንብሮ እድ ይህንን ይጸልያል። ➢ አምላካችን እግዚአብሔር የጌትነትህ ብዕል ወደሚያድርበት ቤተ መቅደስህ ደክመው የመጡትን ባሮችህን ባርክ። ወንዶቹንና ሴቶቹን ሽማግሌዎቹንና ሕፃናቱን ባርክ። ➢ እኛንም በቅዱሳን መላእክትህ ኃይል አንድ አድርግ። በብርሃንህ መጋረጃ ጋርደን በዕፀ መስቀልህም ሠውረን ከክፉ ሥራም ሁሉ አርቀን። ➢ በጊዜው ሁሉና በሰዓቱ ሁሉ ጸሎትን ከሚያሳርጉ ቅዱሳን መላእክት ማኅበር ውስጥ አሳድረን። ➢ የበላነው ሥጋህ የጠጣነውም ደምህ ለኃጢአት ማስተሠረያና ለዘላለም ሕይወት ይሁነን። ባንድ ልጅህ በርሱ ያለ ክብር ጽንዕ ላንተ ይገባል ከርሱ ጋራ ከመንፈስ ቅዱስም ጋራ ዛሬም ዘወትርም ለዘላለሙ አሜን። #ተፈጸመ_ቅዳሴ_ጎርጎርዮስ ➢➢ የቀጣይ ትምህርት #ክፍል_ሰባ_ስድስት የኤጲፋንዮስ ቅዳሴ ➜ ሰኔ / 25 / 2018 ዓ.ም © ማኅቶት እሸቴ 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21 👇👇👇 የፌስቡክ አድራሻ https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1

የባስልዮስ ቅዳሴ መጽሐፈ ቅዳሴ ማብራሪያ #ክፍል_ሰባ_አራት 💎 ማርያም ዘወትር ድንግል ናት ካህኑ ይህንን ይጸልያል ➢ መሥዋዕት ያቀረቡትን በሰማይ ያለ ዋጋቸውን ስጣቸው። ከጥንት ጀምሮ ያለገሉህ ቅዱሳንህን እናስብ ዘንድ። ➢ ቅዱሳን አባቶቻችንን ፣ ሉቃነ ጳጳሳትን ኤጲስቆጶሳትን ፣ ነቢያትንና ሐዋርያትን ፣ ሰማዕታትንም ፣ ምእመናንን የቤተክርስቲያንህን ወገኖችን ወንጌልን የሚሰብኩ ፣በሃይማኖት ፍጹማን የሆኑ የጻድቃንን ነፍሳት ሁሉ እናስብ ዘንድ። ➢ ይልቁንም ሁልጊዜ ምሕረትን የተመላች ቅድስት ንጽሕት አምላክን የወለደች ድንግል ማርያምን እናስብ ዘንድ። ይ.ሕ :- ወትረ ድንግል ማርያም ፤ ማርያም ዘወትር ድንግል ናት። ሦስት ጊዜ ደጋግመው ይላሉ። ከዚህም በመቀጠል ካህኑ ከአበው ጀምሮ ነቢያትን ፣ ሐዋርያትን ፣ ሰማዕታትን ፣ ጻድቃን መነኰሳትን ስማቸውን እየጠራ ይጸልያል። ስለ እነዚህ ቅዱሳንም ሲል እንዲምረን ይቅር እንዲለን ኃጢአታችንን ያስተሠርይልን ዘንድም ይማጸናል። ✍️ የዓለሙን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ ካህኑ ሠራዊት ከተባለ በኋላ ይህንን ይጸልያል ➢ የዓለሙን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ አማኑኤል ዛሬ ከኛ ጋራ በዚህች ማዕድ ላይ እነሆ አለ። ➢ የሰማይ መላእክት ፣ ዙፋኑን የሚሸከሙ አርባዕቱ እንስሳ ያመሰግኑታል። ሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ዕጣንን በተመሉ የወርቅ ማዕጠንት ከቅዱሳን ጸሎት ጋራ በፊቱ መሥዋዕት አድርገው ያሳርጋሉ። ➢ በበጉ ደም ልብሶቻቸውን ያጠቡ ንጹሓን ደናግል እሊኸውም ዐሥራ አራት እልፍ ከአራት ሺሕ አሸናፊ እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል ያከብሩታልም እንዲህ እያሉ። ➢ አሜን ሃሉ ሉያ እግዚአብሔር አብ ቅዱስ ነው። ➢ ሃሌ ሉያ ጌታችን ወልድ ዋሕድ ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ነው። ➢ ሃሌ ሉያ መጽኛ የሚሆን ጰራቅሊጦስ መንፈስ ቅዱስ ነው። አሜን። ➢ ሃሌ ሉያ አምላክን የወለደች ድንግል ማርያም የተቀደሰችና የተመረጠች ናት። አሜን። ➢ ሃሌ ሉያ ዳግመኛ ይህች መሥዋዕት የነጻች የተመረጠች ናት። አሜን። ➢ ስለዚህ መድኃኒታችን ይጮሃል እንዲህ እያለ ሥጋዬ እውነተኛ የጽድቅ መብል ነው። ደሜም እውነተኛ የሕይወት መጠጥ ነውና። ሥጋዬን የበላ ደሜንም የጠጣ ከእኔ ጋራ ይኖራል ዳግመኛም ከእርሱ ጋራ እኖራለሁ። ➢ በንጹሕ ልቡና ብርሃን በተመላች ነፍስ እንጠራህ ዘንድ ደፍረን በባለሟልነት ቅዱስ እግዚአብሔር አብ ሆይ በሰማይ ያለህ አባታችን እንበል። ✍️ ካህኑ በአንብሮ እድ የሚጸልየው ➢ አቤቱ እሊህ ባሮችህ የሚገዙልህ ቅዱስ ስምህን የሚጠሩ ራሳቸውንም በፊትህ ዝቅ ዝቅ ያደረጉ ናቸው። አቤቱ በነርሱ ላይ እደር ከነርሱም ጋራ ሂድ። በበጎውም ሥራ ሁሉ እርዳቸው ልቡናቸውንም ምድራዊ ከሚሆን ከክፉ ሥራ ሁሉ አንጻላቸው። ➢ ይኖሩ ዘንድ መኖርን ስጣቸው። የዘላለም ሕይወትንም ያስቁ ዘንድ ደስ የሚያሰኙህንም ያውቁ ዘንድ። በዚህ በአንድ ልጅህ በጌታችንና በአምላካችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ እኛ ሁላችን ሕዝብህም ሁሉም መድኃኒታችን እግዚአብሔር ይቅር በለን ብለን ወደሱ የምንጮህለት እርሱ ነው ለዘላለሙ አሜን። #የባስልዮስ_ቅዳሴ_ተፈጸመ። ➢➢ የቀጣይ ትምህርት #ክፍል_ሰባ_አምስት ሆሳዕና በአርያም ➜ ሰኔ / 23 / 2018 ዓ.ም © ማኅቶት እሸቴ 👇👇👇 የቴሌግራም ሊንክ https://t.me/MEBspiritualtraining21 👇👇👇 የፌስቡክ አድራሻ https://www.facebook.com/mebrie.eshetie.1