441
Subscribers
-124 hours
+17 days
+430 days
Posts Archive
#1st_John
#Part_3
ሀ. የሕይወት ቃል (1ኛ ዮሐ 1፥1-4)
ጥቅሱን ለማንበብ ይህን ጽሑፍ ይጫኑ!
2. ዞዊ (ζωή)
ዞዊ (ζωή) በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከግሪክ ቋንቋ የተገኘ ጠቃሚ ቃል ነው። ከአስፈላጊነቱም የተነሳ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ብዙ ጊዜ ተጠቅሷል። ዞዊ በግሪክ እና በዕብራይስጥ ትርጉሙ አንድ ነገር ላይ ይጠቁማል፤ እርሱም ሕይወትን ነው።
የዞዊ (ζነωή) ትርጉም
ዞዊ የግሪክ ቃል ሲሆን “ሕይወት” ተብሎም ሊተረጎም ይችላል። በመጽሐፍ ቅዱስ አገባብ መሠረት ትርጉሙም “የእግዚአብሔር ዓይነት ሕይወት” ማለት ነው። በግሪኩ አገላለጽ፣ ዞዊ በቀላሉ ሕይወት ማለት ነው። ቀደም ብዬ እንደገለጽኩት ዞዊ የመጣው ከግሪክ ሲሆን ሔዋን (Chavvah/ חַוָּה) ከሚለው ከዕብራይስጥ ስም ጋር ተመሳሳይነት አለው። ትርጉሙም “ሕይወት” ማለት ነው። የእስክንድርያ አይሁዶች ሔዋን የሚለውን የዕብራይስጥ ስም ወደ ግሪክ ስም ዞዊ ተርጉመውታል። ይህም በጥንት ክርስቲያኖች ዘንድ ታዋቂ ነበረ፤ እሱም ዞዊ የሚለውን ስም ከዘላለም ሕይወት ጋር ያዛምዳል።
ዮሐንስ 3፥16
“በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።”
በዚህ ክፍል ውስጥ ያለው "ሕይወት" ማለት በምድር ላይ ያለሞት ረጅም ዕድሜ መኖር ሳይሆን ከሞት በኋላም የሚቀጥል የማይቋረጥ “ዘላለማዊ ሕይወት” ማለት ነው። በዚህ ዐውደ-ጽሑፍ መሠረት “እንዳይጠፋ” ማለት በክርስቶስ ያመነ በምድር ላይ ረጅም ዕድሜን ይኖራል ማለት አይደለም፤ በኃጢአት ምክንያት የዘላለም ሞት አይይዘንም ማለት እንጂ። ይህ በክርስቶስ ያመነ ሰው የሚያገኘው ሕይወት የዘላለም ሕይወት ነው ትርጉሙም “ዞዊ” ማለት ነው።
ዞዊ የእግዚአብሔርን ባለጠግነት፣ የተትረፈረፈ መለኮታዊ ተፈጥሮ፣ የፍቅር፣ የደስታ፣ የኃይሉ እና የችሎታው ሙላት ያሳያል። ዳግመኛ ስንወለድ፣ ይህ የተትረፈረፈ የእግዚአብሔር ሕይወት በክርስቶስ ወደ መንፈሳችን ተሰጥቷል። ስለዚህ ዞዊ ለደኅንነታችን ዋና ነገር ነው።
ዞዊ (የእግዚአብሔር ዓይነት ሕይወት) ምን ያደርጋል?
- ዞዊ ሰውን አዲስ ፍጥረት ያደርጋል። (2ኛ ቆሮ 5፥17፤ 2ኛ ጴጥ 1፥4)
- ዞዊ እግዚአብሔርን እንድናውቅ እና ከእርሱ ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዲኖረን ያስችለናል። (ዮሐ 17፥3)
- ዞዊ መንፈሳዊ ጨለማን ያስወግዳል። (ዮሐንስ 1፥4፤ 1ኛ ዮሐ 5፥11-12)
- ዞዊ ከዲያብሎስ፣ ከኃጢአት እና ከዘላለማዊ ፍርድ ነፃ ያወጣናል። (ዮሐ 5፥24፤ ሮሜ 8፥2፤ 1ኛ ዮሐ 5፥18)
ማጠቃለያ
ሕይወት = ዞዊ (ζነωή)
ቃል = ሎጎስ (λόγος)
ዮሐንስ በመልዕክቱ የሚጀምረው ኢየሱስን “የሕይወት ቃል” በማለት ነው። ይህም ማለት እናንተ የምታውቁት ሁሉን የፈጠረው ቃል (Logos/ λόγος) የዘላለም ሕይወት (ዞዊ/ζነωή) ነው ማለቱ ነው። ይህንን ሎጎስ (ፈጣሪን ወይም እግዚአብሔርን) እና ዞዊ (የዘላለምን ሕይወት) ሰውን ለማዳን ሰው ሆኖ ተገልጦ እኛ ሰምተነዋል፣ አይተነዋል፣ ተመልክተነዋል፣ ዳስሰነዋልም (ነክተነዋልም) በማለት ምስክርነቱን ያጸናል።
➝ ይህን የምታነቡ ነገር ግን ኢየሱስን እንደ ጌታና አዳኝ አድርጋቹ ያልተቀበላችሁ፣ ጸሎቴ የእግዚአብሔርን የዘላለም ሕይወት ስጦታ ለመቀበል ልባችሁን እንድትከፍቱ ነው። ቀጥሎም በሚኖረን ተከታታይ ጥናት ስለዚህ የዘላለም ሕይወት እንማራለን። በግል መወያየትም እንችላለን።
https://t.me/Theophilus_Terefe
#1st_John
#Part_2
ሀ. የሕይወት ቃል (1ኛ ዮሐ 1፥1-4)
ጥቅሱን ለማንበብ ይህን ጽሑፍ ይጫኑ!
1. ቃል - Logos (λόγος)
ሎጎስ (λόγος) የግሪክ (የጽርዕ) ቃል ሲሆን “ቃል” “ንግግር”፣ “መርህ” ወይም “ሃሳብ” ተብሎ የተተረጎመ ነው። የሎጎስ የቃሉ ሃሳብ ለዮሐንስ እና በዘመኑ ለነበሩት የግሪክ እና የአይሁድ ዓለማት አስፈላጊ ነበር። አይሁዳውያን እግዚአብሔር በቃሉ ውስጥ ራሱን ፍጹም አድርጎ እንደገለጠ ስለሚያውቁ፣ ብዙ ጊዜ ቃል ተብሎ ይጠራ ነበር። በግሪክ ፍልስፍና ደግሞ ዓለም አቀፋዊ፣ መለኮታዊ ምክንያት ወይም የእግዚአብሔርን አእምሮ ያመለክታል። ለግሪኮች፣ ፈላስፋዎቻቸው ስለ ሎጎስ ለዘመናት ሲናገሩ ቆይተዋል።
በአዲስ ኪዳን የዮሐንስ ወንጌል እንዲህ ሲል ይጀምራል፡-
“¹ በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ። ² ይህ በመጀመሪያው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ። ³ ሁሉ በእርሱ ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም። ⁴ በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።” (ዮሐ 1፥1-4)።
እዚህ ላይ “ቃል” ወይም ሎጎስ ኢየሱስ ክርስቶስን የሚያመለክት መሆኑ ግልጽ ነው። ዮሐንስ ኢየሱስ፣ ቃል ወይም ሎጎስ፣ ዘላለማዊ እና አምላክ እንደሆነ ተከራክሯል። በተጨማሪም ፍጥረት ሁሉ የመጣው የሕይወት ምንጭ ሆኖ በቀረበው በኢየሱስ በኩል ነው። በሚያስደንቅ ሁኔታ ይህ ሎጎስ መጥቶ በመካከላችን ኖረ፡- “ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን” (ዮሐ. 1፡14)። .
የዮሐንስ ወንጌል የሚጀምረው በጊዜው ከነበሩ አንባቢዎች ጋር ለመገናኘትና ኢየሱስን አምላክ መሆኑን ለማስተዋወቅ “መለኮታዊ ምክንያት” ወይም “የእግዚአብሔር ሐሳብ” የሚለውን የግሪክኛ ሐሳብ በመጠቀም ነው። የግሪክ ፍልስፍና ቃሉን የተጠቀመው መለኮታዊ ምክንያትን ለማመልከት ሊሆን ይችላል፣ነገር ግን ዮሐንስ ቃሉን የተጠቀመው ብዙዎቹን የኢየሱስን ባሕርያት ለማመልከት ነው። በዮሐንስ የሎጎስ ጽንሰ-ሐሳብ አጠቃቀም ስለኢየሱስ የሚከተለውን እናገኛለን፦
- ኢየሱስ ዘላለማዊ ነው (“በመጀመሪያው ቃል ነበረ”)
- ኢየሱስ ወደ ምድር ከመምጣቱ በፊት ከእግዚአብሔር ጋር ነበር (“ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ”)
- ኢየሱስ አምላክ ነው (“ቃልም እግዚአብሔር ነበረ”)
- ኢየሱስ ፈጣሪ ነው (“ሁሉ በእርሱ ሆነ”)
- ኢየሱስ ሕይወት ሰጪ ነው (“በእርሱ ሕይወት ነበረች”)
- ኢየሱስ በመካከላችን እንዲኖር ሰው ሆነ (“ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትን ተመልቶ በእኛ አደረ”)
በተጨማሪም የዮሐንስ ወንጌል መክፈቻ ከዘፍጥረት 1፥1 ጋር ተመሳሳይነት አለው።
“በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ” (ዘፍጥረት 1፡1)።
“በመጀመሪያው ቃል ነበረ፣ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፣ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ። ይህ በመጀመሪያ በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ። ሁሉ በእርሱ ሆነ…” (ዮሐንስ 1፡1-2) ( “ብርሃን” የሚለው ተዛማጅ ጭብጥም በዘፍጥረት 1 እና በዮሐንስ 1 ላይም ጥቅም ላይ ውሏል።)
ሎጎስ በብዙ መንገድ ጥቅም ላይ ይውላል፣ ነገር ግን በዮሐንስ ወንጌልና በመልዕክቱ መሠረት ሎጎስ እኛን የፈጠረንና በመካከላችን ሰው ሆኖ ተገልጦ የኖረውን አምላክ ኢየሱስን በግልጽ ይጠቅሳል። ሎጎስ (λόγος) በቀደመችው ቤተክርስቲያን ላሉ ክርስቲያኖች አስፈላጊ የሆነ ሥነ-መለኮታዊ ቃል ሆኖ አገልግሏል፤ ዛሬም ጉልህ ተጽዕኖ ያለው ጽንሰ-ሐሳብ ሆኖ አለ።
ዮሐንስ ይህን ሎጎስ ወይም ዘላለማዊ ፈጣሪን ከእርሱና ከሌሎች ጋር በአካል የተገኘውን የሕይወት ቃል ነው ብሎ ያቀርብልናል። ዮሐንስ ለሁሉም የሚላቸው “ይህን ለዘመናት ስትናገሩት እና ስትጽፉለት የነበረው ሎጎስን እኛ ሰምተነዋል፣ አይተናል ደግሞም ነክተነዋል፤ አሁን ስለ እርሱ ልንገራችሁ” ነው የሚላቸው።
https://t.me/Theophilus_Terefe
#1st_John
#BS_Verses
1ኛ ዮሐንስ 1፥1-4
¹ ስለ ሕይወት ቃል ከመጀመሪያው የነበረውንና የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን የተመለከትነውንም እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን፤ ² ሕይወትም ተገለጠ አይተንማል እንመሰክርማለን፥ ከአብ ዘንድ የነበረውንም ለእኛም የተገለጠውን የዘላለምን ሕይወት እናወራላችኋለን፤ ³ እናንተ ደግሞ ከእኛ ጋር ኅብረት እንዲኖራችሁ ያየነውንና የሰማነውን ለእናንተ ደግሞ እናወራላችኋለን። ኅብረታችንም ከአባት ጋር ከልጁም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ነው። ⁴ ደስታችሁም እንዲፈጸም ይህን እንጽፍላችኋለን።
https://t.me/Theophilus_Terefe
#1st_John
#Outline
የመልዕክቱ አከፋፈል
በዶ/ር ቶማስ ሐሌ የተፃፈው የአዲስ ኪዳን ማብራሪያ (The Applied New Testament Commentary) ቀላልና ግልጽ አከፋፈል ስላለው ቀጥታ ራሱን የምጠቀም ይሆናል።
አስተዋጽኦ
ሀ. ብርሃን ከሆነው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግ። (1፥1-2፥29)
1. የሕይወት ቃል (1፥1-4)
2. በብርሃን መመላለስ (1፥5-10)
3. ለእግዚአብሔር መታዘዝ (2፥1-6)
4. አዲስ ትእዛዝ (2፥7-17)
5. ስለ ክርስቶስ ተቃዋሚዎች የተሰጠ ማስጠንቀቂያ (2፥18-29)
ለ. ጻድቅ ከሆነው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግ (3፥1-4፥1-6)
1. መልካም የሆነውን ማድረግ (3፥1-10)
2. እርስ በርስ መዋደድ (3፥11-24)
3. ስለ ሐሰተኛ መናፍስት የተሰጠ ማስጠንቀቂያ (4፥1-6)
ሐ. ፍቅር ከሆነው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት ማድረግ (4፥7-5፥21)
1. ስለ ፍቅር ማስተማር (4፥7–21)
2. እምነትን በልጁ ላይ ማድረግ (5፥1-12)
3. የመደምደሚያ ማሳሰቢያዎች (5፥13-21)
https://t.me/Theophilus_Terefe
#1st_John
#Questions
የመጀመሪያውን የሐዋሪያው ዮሐንስን መልዕክት ዘልቀን ገብተን ከማየታችን በፊት በመልዕክቱ ዙሪያና በተለይም በመጀመሪያው ምዕራፍ ላይ ጥያቄ ያላችሁ ወገኖች ጥያቄዎቻችሁን በአስተያየት (Comment) መስጫ ስር እንድታስቀምጡልኝ እጠይቃችኋለሁ። በውስጥ መስመርም መጠየቅ ይቻላል።
https://t.me/Theophilus_Terefe
#1st_John
#Part_1_1
በመጀመሪያው በሐዋርያው ዮሐንስ መልእክት ውስጥ የምናገኛቸው የስሕተት አስተምህሮ ጎራዎችና የትምህርታቸው ጭብጥ እንደሚከተለው ነው።
1.ፍልስፍናዊ ኑፋቄ
ግኖስቲሳውያን/ኖስቲሳውያን (Gnosticism)፦ እንደ ሀይማኖት ፍልስፍና ቁስ አካል ሁሉ ክፉ ነው መንፈሳዊ የሆነ ሁሉ ጥሩ ነው የሚል አቋም ነበረው። በነዚህ በሁለቱ (በቁሳዊውና በመንፈሳዊው) መካከል ላለው ውጥረት መፍትሔው ሰው ከአለማዊነት ወደ መንፈሳዊነት ያደገበት እውቀት ወይም ግኖሲስ (Gnosis) ነው ይላሉ። ይህም በሁለተኛው ክፍለ ዘመን ለቤተክርስቲያን የበለጠ ችግር ሆኗል።
2.የክርስቶስን ማንነት በሚመለከት የቀረበ ኑፋቄ
ዶሴታውያን (Docetism)፦ ሰው ሆኖ የተገለጠውን ኢየሱስን እንደ መንፈስ አድርገው ያቀርባሉ። ወይም የኢሱስን ሰውነት ይክዳሉ።
ሴሪንታውያን (Cerinthianism)፦ ኢየሱስን ባለሁለት ስብዕና እንደሆነ ያስተምሩ ነበረ። ይህም በትምህርታቸው የኢየሱስ ማንነት አንዳንድ ጊዜ ሰው እና አንዳንዴም መለኮት እንደሆነ በማስተማራቸው ምዕመናን ስለማንነቱ የተዛባ ምልከታ እንዲኖራቸው አድርጓል።
https://t.me/Theophilus_Terefe
#1st_John
#Part_1
የመጀመሪያው የዮሐንስ መልዕክት
መግቢያ
የመጀመርያው የዮሐንስ መልእክት ለክርስቲያን አንባቢዎች የተላከ በጣም ተግባራዊ ደብዳቤ ነው። ከሐሰት ትምህርት አደጋዎች ያስጠነቅቃል፤ አማኞች እግዚአብሔርን በመታዘዝ እና ወንድሞቻቸውን እና እህቶቻቸውን እንዲወዱ ይመክራል።
የመልዕክቱ ጸሐፊ ማነው?
መልእክቱ በተለምዶ ለሐዋርያው ዮሐንስ ተሰጥቷል። የጸሐፊው ስም ግን በደብዳቤው ውስጥ የለም። ሆኖም ጸሐፊው ሐዋሪያዊ የሆነ መንፈሳዊ ሥልጣን እንደነበረው በአጠቃላይ ከደብዳቤው መረዳት ይቻላል። ከዚህም በላይ ጸሐፊው ራሱን የጌታ ኢየሱስ ከአይን ምስክሮች መካከል አስቀምጦ ጽፏል (1፥1-2)። ኢራኔዎስ፣ የአሌክሳንደሪያው ቀለሜንጦስ እና ጠርጡሊያንን ጨምሮ የጥንት የክርስትና ጸሐፍትና የቤተክርስቲያን አበው መልእክቱን የዮሐንስ ብለው ጠቅሰውታል። በሌላ መልኩም የመልዕክቱ ፍሰትና አፃፃፉ ከዮሐንስ ወንጌል ጋር በጣም የሚመሳሰል መሆኑ ጸሐፊው ዮሐንስ ስለመሆኑ ወሳኝ ማስረጃ ነው።
የመልዕክቱ ተቀባዮች
መልዕክቱ ስለ አንባቢዎቹ ማንነት እና ቦታ ክርስቲያን ከመሆናቸው በቀር ምንም ፍንጭ አይሰጥም። የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት ዮሐንስን ከእስያ የሮም ግዛት (በምእራብ ቱርክ) ጋር ስለሚያገናኘው ብዙ ጊዜ አንባቢዎቹ እዚያ ይኖሩ እንደነበር ይታሰባል። ይህ ኅብረት በራዕይ 2 እና 3 የተረጋገጠ በመሆኑ እውነት ሊሆን ይችላል።
የመልዕክቱ ተቀባዮች ዮሐንስ የክርስቶስ ተቃዋሚ ብሎ ከጠራቸው ከሐሰተኛ አስተማሪዎች ጋር ተገናኝተው ነበር (1ኛ ዮሐንስ 2፥18-26)። የእነዚህን የሐሰኛ መምህራን ትክክለኛ ባህሪ ዮሐንስ በመልዕክቱ በሰፊው ያነሳል ። ብዙዎች እነዚህን ሰዎች መንፈሳዊ እና ቁሳዊ ነገሮች በደንብ የሚለዩበት ጥብቅ ምንታዌነትን (Dualism) የያዙ ግኖስቲኮች (Gnostics) እንደሆኑ አድርገው ያስባሉ። ሌሎች ደግሞ ደብዳቤው የዶሴታውያንን (Docetism) የኢየሱስ ሰብአዊነት እውን እንዳልሆነ እና እሱ ሥጋዊ አካል ያለው ብቻ ነው የሚለውን እምነት በመመከት እንደጻፈው ያስባሉ። ሌሎች ደግሞ መልዕክቱ ብዙውን ጊዜ የሴሪንተስን ምንፍቅና ውድቅ ያደርገዋል ብለውም ያስባሉ። በቤተ ክርስቲያን ትውፊት መሠረት ሴሪንተስ በሮም እስያ ይኖር የነበረ ሲሆን ኢየሱስ ሰው ብቻ እንደነበረ እና መለኮታዊው ክርስቶስ በጥምቀቱ በኢየሱስ ላይ እንደወረደ እና ከስቅለቱ በፊት እንደተወው ያስተማረና ሐዋርያው ዮሐንስም አጥብቆ የተቃወመው ሰው ነበረ።
ዮሐንስ በመልእክቱ የተቃወመውን የሐሰት ትምህርት ትክክለኛ ባሕርይ በትክክል መናገር አይቻልም። የተወሰነው መረጃ በራሱ በመልእክቱ ውስጥ የሚገኘው ብቻ ነው። የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ አይደለም ብለው እንደካዱ ግልጽ ነው (2፥22)። ያም ሆነ ይህ ደብዳቤው የተላከበት ቤተ ክርስቲያን ወይም አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ለማስጠንቀቅ እና ለማስተማር የታሰበ መሆኑ አያጠራጥርም። እውነቶቹም በእያንዳንዱ ክርስቲያን ልምምድ ላይ በብዛት ይሠራሉ።
ቁልፍ ጥቅሶች
-1ኛ ዮሐንስ 1፥9፦ “በኃጢአታችን ብንናዘዝ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ከዓመፃም ሁሉ ሊያነጻን የታመነና ጻድቅ ነው።”
-1ኛ ዮሐንስ 3፥6፦ “በእርሱ የሚኖር ሁሉ ኃጢአትን አያደርግም፤ ኃጢአትን የሚያደርግ ሁሉ አላየውም አላወቀውምም።”
-1ኛ ዮሐንስ 4፥4፦ “ልጆች ሆይ፥ እናንተ ከእግዚአብሔር ናችሁ አሸንፋችኋቸውማል፥ በዓለም ካለው ይልቅ በእናንተ ያለው ታላቅ ነውና።”
-1ኛ ዮሐንስ 5፥13፦ “የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ታውቁ ዘንድ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ለምታምኑ ይህን ጽፌላችኋለሁ።”
ቁልፉ ቃላት
"ሕይወት፣ ብርሃን፣ ጨለማ፣ እውነት፣ ውሸት፣ ሐሰት፣ እውቀት"
https://t.me/Theophilus_Terefe
ኢየሱስ መሲሕ (ክርስቶስ) ነውን?
መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል?
ስለ መሲሑ የተነገሩት ትንቢቶች ኢየሱስ መሲሕ እንደሆነ ያረጋግጣሉ?
አዎ፣ ያረጋግጣሉ! ኢየሱስ ምድር ላይ በኖረበት ወቅት “የዓለም አዳኝ ስለሚሆነው” ወይም “መሪ ስለሆነው መሲሕ” የተነገሩ በርካታ ትንቢቶች እንዲፈጸሙ አድርጓል። (ዳንኤል 9:25፤ 1 ዮሐንስ 4:14) ኢየሱስ፣ ከሞተ በኋላም እንኳ ስለ መሲሑ የተነገሩ ትንቢቶች እንዲፈጸሙ ማድረጉን ቀጥሎ ነበር። መዝሙር 110:1፤ የሐዋርያት ሥራ 2:34-36
“መሲሕ” የሚለው ቃል ምን ትርጉም አለው?
ማሺያክ (מָשִׁיחַ) ወይም መሲሕ የሚለው የዕብራይስጥ ቃል እንዲሁም ክርስቶስ (Χριστός) የሚለው የግሪክኛ ቃል ተመሳሳይ ፍቺ ያላቸው ሲሆን ሁለቱም “የተቀባ” የሚል ትርጉም አላቸው። በመሆኑም “ኢየሱስ ክርስቶስ” ማለት “የተቀባው ኢየሱስ” አሊያም “መሲሑ ኢየሱስ” ማለት ነው።
በጥንት ዘመን አንድ ሰው ለአንድ ልዩ ሥልጣን ሲሾም ብዙውን ጊዜ በራሱ ላይ ዘይት በማፍሰስ ይቀባ ነበር። (ዘሌዋውያን 8:12፤ 1 ሳሙኤል 16:13) ኢየሱስን መሲሕ አድርጎ በመሾም ከፍተኛ ሥልጣን የሰጠው አምላክ ነው። (የሐዋርያት ሥራ 2:36) ሆኖም አምላክ ኢየሱስን የቀባው በዘይት ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ ነው። (ማቴዎስ 3:16) ይህም አባባል ኢየሱስ አምላክ የሆነ ሰው ነው ማለት እንዳልሆነ ግልፅ ነው። እርሱ በስጋ የተገለጠ አምላክ ነውና። (አሪዮሳውያን ወይም የዘመናችን የይሖዋ ምስክሮች (Jehovah's Wittiness) ብለው ራሳቸውን የሚጠሩ ቡድኖች ይህንን ክፍል ኢየሱስ ፍጡር ነው ለማለት ይጠቀማሉ። ሆኖም ግን መጽሐፍ ቅዱስ የማያውቀው ኑፋቄ ነው። በሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ)
https://t.me/Theophilus_Terefe
#Prayer
«...ትጸልያላችሁ?»
ለነገ ሕይወታችሁ ትጸልያላችሁ? ትጸልያላችሁ? ራሳችሁን ትልቅ እናትና አባት አድርጋችሁ አስባችሁ፣ ቀጣይ “Generation” እንደምትሰሩ አስባችሁ ለራሳችሁ ትጸልያላችሁ? ነገ ስለሚገጥማችሁ ሕይወት፣ ስለቤታችሁ ትጸልያላችሁ? ስለምትሠሩት ሥራ ትጸልያላችሁ? ስለምታገለግሉት ስለምትመሩት ሕዝብ፣ ስለምትመሩት መስሪያ ቤት፣ ስለምትመሩት አከባቢ፣ ስለምትመሩት ሀገር ትጸልያላችሁ? እሱ ነው ነገ ላይ አቅም 'ሚሆንላችሁ። ሌሎች አቅም አተው ሲንገዳገዱ፤ አቅም ሆኖ 'ሚያቆማችሁ ዛሬ 'ምትጸልዩት፣ ዛሬ 'ምታነቡት ቃል፣ ዛሬ በቤቱ 'ምታሳልት ጊዜና እርሱን በመፈለግ 'ምትጨርሱት ዕድሜአችሁ ወሳኝ ነው።
ከ2014 ዓ/ም ማሕደር።
https://t.me/Theophilus_Terefe
#1st_John
#General_Introduction
1ኛ የዮሐንስ መልዕክት
ጸሐፊ፦ ሐዋርያው ዮሐንስ ዘብዴዎስ
ተቀባዮች፦ የእስያ አብያተ ክርስቲያናት (ምናልባትም የራዕይ 2፥3-7 አብያተ ክርስቲያናት)
የተጻፈበት ግዜ፦ 85-100 ዓ.ም
የተጻፈበት ቦታ፦ ኤፌሶን (?)
የተጻፈበት አጋጣሚ፦ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ በመጣው ግኖስቲሲዝም (ኖስቲሲዝም) ፍልስፍና የሚመጣ ቀውስ፣ መናፍቅነት እና ግጭት።
የመልዕክቱ ዓላማዎች፦
1. ለእግዚአብሔር ልጆች እውነተኛ ደስታን ማስተዋወቅ (1፥4)
2. የእግዚአብሔር ልጆች ኃጢአት እንዳይሠሩ ለመከላከል (2፥1)
3. የእግዚአብሔርን ልጆች ከሚያስቱት ለመጠበቅ (2፥26)
4. ለእግዚአብሔር ልጆች የዘላለም ሕይወትን ለማረጋገጥ (5፥13)
https://t.me/Theophilus_Terefe
#1st_John
#PollVote
በሰጠሁት ምርጫ መሠረት 1ኛ የዮሐንስ መልዕክት አብላጫውን ድምጽ ስላገኘ፥ ሰኞ፣ ረቡዕ እና ቅዳሜ ወደእናንተ በተለያየ አማራጭ አቀርባለሁ (በብዛት በጽሑፍ ነው)። ስለተሳተፋችሁ አመሰግናለሁ።
የማስተላልፈውን መልዕክት ለሌሎችም በማጋራትና ወደ ቻናሉ እንዲቀላቀሉ በማድረግ እንድትተባበሩኝ በትሕትና እጠይቃለሁ።
https://t.me/Theophilus_Terefe
#በእምነት_ብቻ
በመዝሙር 32 ዳዊት ከእግዚአብሔር ስለ ተቀበለው ነጻ የሆነ ይቅርታ ሐሴትን ያደርጋል። ኃጢአትን አድርጎ ስለነበረ፥ ኃጢአቱን ለእግዚአብሔር ይናዘዛል፤ እግዚአብሔርም በታላቅነቱ ኃጢአቱን ይቅር ይለዋል። በመዝሙር 32 ዳዊት የተቀበለው ምሕረት ፈልጎ ያገኘው ነገር እንዳልነበር ጳውሎስ ተገንዝቦ ነበር። (ሮሜ 4፥6-8) በዚህ መዝሙር ዳዊት ያደረገው ነገር ኃጢአቱን ለእግዚአብሔር መናዘዝና በእግዚአብሔር ምሕረት መደገፍ ነበር። እግዚአብሔር በነጻ ይቅር አለው። እግዚአብሔር ኃጢአትን ይቅር እንደሚልና ሰዎችን ጻድቅ እንደሚል ይህ ግልጽ የሆነ ተጨማሪ ማረጋገጫ ነው። መልካም ሥራን ስለሠሩ ወይም ኃጢአትን መሥራት ስላቆሙ ሳይሆን በእግዚአብሔር ስለታመኑ ብቻ ነው። (መዝ 32፥9)
https://t.me/Theophilus_Terefe
እግዚአብሔር በሚናገርበት ግዜ የሚሰሙትን ሲናገሩ ይሰማቸዋል። "የሚሰማኝ ግን..." ብሎ መጀመሩ ከዚህ ቀደም የተብራራው የዚህ ዓረፍተ ነገር ተቃራኒ መሆኑን ያሳያል። እነርሱም ደግሞ "የማይሰሙት" ናቸው።
# ምልክታቸውስ ምንድርነው?
1. ዓላዋቅነትን፣ ፌዝንና ስንፍናን መውደድ ወይም እውቀትን መጥላት። (ምሣሌ 1:22)
2. ለእግዚአብሔር ጥሪ እምቢተኛ መሆን ወይም አለመቀበል። (ምሣሌ 1:24)
3. የእግዚአብሔርን ምክርና ዘለፋ ቸል ማለት ወይም መናቅ። (ምሣሌ 1:25)
# ይህን ሁሉ አድርገው ወይም እምቢ ብለው ግን እግዚአብሔርን ይፈልጋሉ? መቼ?
-አዎን ይፈልጋሉ፤ የሚፈልጉትም፦
1. ድንጋጤ ሲደርስባቸው። (ምሣሌ 1:27)
2. ጥፋት ሲመጣባቸው። (ምሣሌ 1:27)
3. ጭንቅ ሲወርድባቸው። (ምሣሌ 1:27)
# የእግዚአብሔርስ ምላሽ ምንድርነው?
1. መከራ፣ መዓትና ሲቃይ ሲወርድባቸው ያለምላሽ ማየት። (ምሣሌ 1:26-27)
2. ሲጠሩና አጥብቀው ሲፈልጉት አለመገኘት። (ምሣሌ 1:28)
3. ላደረጉት ነገር ፍሬውን መስጠት። (ምሣሌ 1:31)
፨ስለዚህ፦ እግዚአብሔር ሲናገር እንስማው፤ በጭንቅ ግዜ ይሰማናል፣ በሰላምም ያኖረናል፤ ከመከራ አሳርፎ ክፉ ሳያስፈራን ያኖረናል፤ ከመዓትም ያድነናል።
https://t.me/Theophilus_Terefe
ጳውሎስ በደረሱበት አካላዊ መከራዎች እና እጦቶች የተሰማውን ሥቃይ ለመረዳት አስቸጋሪ ነው። ነገር ግን የአገልግሎቱ መንፈሳዊ ተጋድሎዎች የበለጠ ሸክም ነበራቸው። ይህ ክፍል የአገልግሎቱን ሥቃይ ያጠቃልላል። ለራሱ ሳይሆን ለሌሎች መቆርቆሩን ይነግረናል። (በ1ኛ ቆሮንቶስ 12፡25) ጳውሎስ ስለ ቤተ ክርስቲያን የተለያዩ አባላትን ያቀፈ አካል እርስ በርስ በመተሳሰብ አንድ ላይ እንደተዋቀረች በሰፊው ጽፏል። እዚህ ላይ ለቆሮንቶስ ቤተ ክርስቲያን ደኅንነት ብቻ ሳይሆን፣ ከሁሉ የሚበልጠውን መንፈስ የሚገሥጽበትን፣ ነገር ግን በአገልግሎቱ ለተቋቋሙት አብያተ ክርስቲያናት ሁሉ ደህንነት የሚጨነቅበትን የዕለት ተዕለት ሸክም ይገልጣል።
©TBKC
https://t.me/Theophilus_Terefe
በምንም አሳብ አትጨነቁ። ይህ ትእዛዝ ነው። መጨነቅ ኃጢአት ነው፤ ምክንያቱም ጭንቀት የእምነት መጉደል ምልክት ስለሆነ (ሮሜ 14፥23)። እግዚአብሔር የሚወደንና ሁሉን የሚችል ሰማያዊ አባታችን ነው። ስለዚህ ልጆቹን ይጠብቃል (1ጴጥ. 5፥7)። ልንጨነቅ አይገባንም (ማቴ 6:25-34)
ነገር ግን የሚያስፈልገንን ነገር እግዚአብሔርን ልንጠይቀው ይገባል (ማቴ. 6፥11፤ 7፥7-8)። የምንፈልገውን ነገር ሳንጠይቅ እግዚአብሔር ያውቃል። ሆኖም የሥጋ አባታችን የልጆቹን ጥያቄ መስማት እንደሚፈልግ ሰማያዊ አባታችንም የእኛን ጥያቄ መስማት ይፈልጋል። ስለዚህ እርሱን በእምነት ልንጠይቀው ይገባል (ያዕ. 1፥6-8)። ይህም ብቻ ሳይሆን እርሱን እያመሰገንን ልንጠይቀው ያስፈልጋል (ኤፌ 5፥20፤ ፊል 1፥3)። እግዚአብሔር ሁልጊዜ ጸሎታችንን ይሰማል፤ መልስም ይሰጠናል። ስለዚህ በጸሎት እየጠየቅነው ስለሚሰጠን መልስ ማመስገን እንችላለን (1ዮሐ 5፥14-15)።
©NTC
https://t.me/Theophilus_Terefe
