en
Feedback
የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር - Ministry of Women and Social Affairs

የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር - Ministry of Women and Social Affairs

Open in Telegram

ይህ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ይፋዊ የቴሌግራም ገጽ ነው!! ስለ ሴቶችና ማሕበራዊ ጉዳዮች ሚኒስቴር ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት ተከታዮቹን ገፆቻችንን ይጎብኙ Follow ministry of Women and Social Affairs pages for more information ***** ድረ ገጽ፦ https://www.mowsa.gov.et/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/Ethio

Show more
1 600
Subscribers
+124 hours
-27 days
+630 days
Posts Archive
የዲጂታል ዘመን ባለቤቶች፡ የሴቶችና ወጣቶች ሁለገብ ስኬት እና የነገ ተስፋ ‎**** ‎የዛሬው ዓለም በቴክኖሎጂ እና በዲጂታል ፈጠራዎች እየተመራ ይገኛል። የኢኮኖሚ፣ የትምህርት እና የማህበራዊ ግንኙነቶች ማዕከላት ወደ ዲጂታል ስርአት እየተሸጋገሩ ባሉበት በዚህ ዘመን፣ ሴቶችና ወጣቶች የዚህ ለውጥ ግንባር ቀደም ተሳታፊና ተጠቃሚ መሆን መቻላቸው የነገዋን የበለጸገች ሀገር እጣ ፈንታ የሚወስን ቁልፍ ጉዳይ ነው። ‎ ‎ዲጂታል መድረኮች ትምህርትን፣ መረጃን እና የፈጠራ ስልጠናዎችን ለሁሉም በእኩል ደረጃ ተደራሽ በማድረግ እኩልነትን ከማስፈን ባለፈ በቴክኖሎጂው ዘርፍ የሚታየውን የክህሎት ክፍተት በመሙላት በእውቀት ላይ የተመሰረተ ማህበረሰብ እንዲፈጠር መንገድ ከፍተዋል። ‎ ‎የሴቶችና ወጣቶች ዲጂታል ሽግግር የግለሰቦችን ህይወት ከመቀየር ባለፈ አካታችና በዲጂታል የለማ ሀገራዊ የኢኮኖሚ ትራንስፎርሜሽንን እውን ለማድረግ ያስችላል። ‎ ‎አሁን ላይ የዲጂታል ሽግግር ለሴቶችና ወጣቶች አዳዲስ ዕድሎችን በመክፈት የኢኮኖሚ ማብቃትን እና የፈጠራ አቅምን እውን እያደረገ ይገኛል። ‎ ‎ወጣቶች የቴክኖሎጂ አዋቂዎችና የዲጂታል ሽግግሩ ዋነኛ ሞተሮች ናቸው። እንደ ቴክኖሎጂ ስታርት-አፕ (Start-ups)፣ አግሮ-ቴክ (Agri-tech)፣ ፊን-ቴክ (Fin-tech) እና የዲጂታል ግብይት መድረኮች ባሉ ዘርፎች ወጣቶች በመሰማራት አዳዲስ መፍትሄዎችን እያመነጩ ይገኛሉ። ‎ ‎የዲጂታል ቴክኖሎጂ መስፋፋት ሴትና ወጣት ሥራ ፈጣሪዎች የዲጂታል ማህበራዊ ሚዲያ መድረኮችን በመጠቀም ምርትና አገልግሎታቸውን ለሰፊው ህብረተሰብ ማስተዋወቅና የገቢ ምንጭ መፍጠር፣ ዲጂታል የክፍያ ስርአቶችን በመጠቀምም የንግድ አድማሳቸውን ማስፋት ችለዋል። ስራ አጥነትን በማቃለል ረገድም ዘርፉ ትልቅ እፎይታን አስገኝቷል። ‎ ‎ዲጂታል ሽግግር የቅንጦት ጉዳይ ሳይሆን የህልውና እና የብልጽግና መሰረት ነው። ሴቶችንና ወጣቶችን በዲጂታል ክህሎት ማብቃት ማለት የሀገርን የነገ ተስፋ በዘላቂነት ማለምለምና ማስቀጠል ማለት ነው። ‎ ‎ወጣቶችና ሴቶች በቴክኖሎጂ የታጠቁበት ሀገራዊ እውነታ የነገውን የዕድገት ምዕራፍ ዘላቂ፣ አስተማማኝና ብሩህ ያደርገዋል። ‎

የነገው ቀን፦ የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ሀገራዊ የቴክኖሎጂ ሽግግር መልዕክት ****** ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢትዮጵያ ከወረቀት አሠራር ወደ ዲጂታል፣ እንዲሁም ከቴክኖሎጂ ተጠቃሚነት ወደ ፈጣሪነት የተሸጋገረችበትን ታሪካዊ ምዕራፍ በጳጉሜንን 5 ነገው ቀን አስመልክተው መልዕክት አስተላለፉ። በመልዕክታቸውም ትናንትን በመማርና በማረም፣ ዛሬን ደግሞ በላቀ ትጋት በመገንባት ዲጂታል ትራንስፎርሜሽን የዕለት ተዕለት ባህላችን እየሆነ መምጣቱን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገልጸዋል። ይህ የዲጂታል ሽግግር ንግድና አገልግሎትን የሚያቀላጥፍ፣ መረጃዎችን ተደራሽ የሚያደርግ እና ልዩ ልዩ ዘርፎችን የሚያዘምን እንደሆነም አብራርተዋል። በተጨማሪም የ5 ሚሊዮን ኢትዮጵያ ኮደሮች ንቅናቄ ወጣቶችን የሰው ሰራሽ አስተውሎት ፈጣሪ በማድረግ በአሁኑ ወቅት ወደ 7 ሚሊዮን ግቡ እያመራ እንደሚገኝ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ጠቁመው፣ ይህም የዲጂታል አገልግሎት ተደራሽነትና ጥራትን ማረጋገጡን አስታውቀዋል። በሀገር በቀል አቅም የበለጸገው የሳይበር ሉዓላዊነታችን የማይቆጣጠሯቸው ቴክኖሎጂዎች ጥገኝነትን ማስቀረቱን ያመለከቱት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ፤ አዲሷ ኢትዮጵያ በዲጂታል ኢኮኖሚ በራስ አቅሟ የምትቆምበት ታላቅ ምዕራፍ ላይ መሆኗን አብስረዋል። #AbiyAhmed #DigitalEthiopia

‎ሀገር አቀፉን የኀብር ቀን አስመልክቶ "ብዝኃነት፡ የኢትዮጵያ ጌጥ" በሚል መሪ ሃሳብ የሥዕል እግዚቢሽንና ውድድር ተካሄደ ‎*** ‎የሥዕል እግዚቢሽንና ውድድሩን የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከኢፌዴሪ የመንግስት ኮሚኒኬሽን አገልግሎት፣ ሰላም ሚኒስቴር፣ ፍትህ ሚኒስቴር፣ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና ከባህልና ስፖርት ሚኒስቴር ጋር በትብብር ተዘጋጅቷል። ‎ ‎ምሽቱ ላይ በተካሄደው የኪነ-ጥበብ መርሃ-ግብር የሀገራችንን ህብረ-ብሔራዊነት፣ ባህል፣ ሃይማኖት፣ ታሪክና ተፈጥሮ ተሰናስነው ሀገርን እንዴት እንደሚያቆሙ የሚያሳዩ የተለያዩ የሕብር ኢትዮጵያ የሚያንፀባርቁ የሥዕል ሥራዎች እግዚቢሽን ቀርበው ለዕይታ በቅተዋል። ‎ ‎የሥዕል ውድድሩ የሰሜን፣ ደቡብ፣ ምሥራቅና ምዕራብ ባህላዊ ውበትን፣ የተፈጥሮና መልክአ ምድር ኅብረ-ቀለምን፣ የታሪክና የድል አሻራዎችን (ዓድዋ፣ ሰንደቅ ዓላማ፣ አክሱም፣ ላሊበላ፣ ጎንደር፣ አልነጃሺና ጀጎል) እንዲሁም የነገዋ ኢትዮጵያን የማንሰራራት ተስፋ (ሕዳሴ ግድብና አረንጓዴ አሻራ) ያካተተ ነበር። ‎ ‎የውድድሩ አሸናፊዎችና የሽልማት አሰጣጥ ስነስርዓት የተካሄደ ሲሆን በውድድሩ ተሳታፊ ለሆኑት ሰዓሊያን ለሁሉም ተሳታፊዎች የሰርተፊኬት እውቅና ሽልማት ተሰጥቷል። ‎ ‎በተጨማሪም እንደ የደረጃቸው፦ ‎1ኛ ደረጃ ለወጣው አሸናፊ አንድ ላፕቶፕ (Laptop) እና 50,000 (ሃምሳ ሺህ) ብር፤ ‎2ኛ ደረጃ ለወጣው አሸናፊ፡ 50,000 (ሃምሳ ሺህ) ብር፤ 3ኛ ደረጃ ለወጣው አሸናፊ፡ 40,000 (አርባ ሺህ) ብር ለቀሩት ተሳታፊዎች ደግሞ ለእያንዳንዳቸው የብር 30,000 (ሰላሳ ሺህ) ብር የማበረታቻ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል። ‎ ‎ ‎

‎አቃቂ ቃሊቲ ለሚገኘው ሴቶች ማረፍያ እና ልማት ማኅበር 1.5 ሚሊዮን ብር በላይ የሚያወጣ ድጋፍ ተደረገ ‎***** ‎(አዲስ አበባ፣ ጳጉሜ 4/2018 ዓ.ም) የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ጳጉሜ 4 "የሕብር ቀን" ምክንያት በማድረግ በአቃቂ ቃሊቲ ክ/ከተማ ለማገኘው የሴቶች ማረፍያ እና ልማት ማኅበር ማዕድ አጋርቷል። ‎በዕለቱ የተቋሙ ከፍተኛ አመራሮች በማህበሩ በመገኘት የ2 መቶ ሺ ብር ገንዘብ እንዲሁም የቴምርና የንህጽና መጠበቅያ ፓድ ድጋፉን አበርክተዋል። ‎ ‎በመርሐግብሩ ላይ በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ የክብርት ሚኒስትር አማካሪ ክቡር አቶ ጌታቸው በዳኔ ባስተላለፉት መልዕክት፥ በብሔራዊ ደረጃ የምናከብረው "የሕብር ቀን" ዓላማው እርስ በእርስ የምንደጋገፍበት፣ አብሮነታችንና ማህበራዊ ትስስራችንን የበለጠ የምናጠናክርበትና የኢትዮጵያዊነት እውነተኛ ዕሴትን በተግባር የምናሳይበት መሆኑን ገልፀዋል። ‎ ‎አክለውም የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ለስርዓተ ጾታ እኩልነት መረጋገጥ እና ለማኅበራዊ ጥበቃ ትኩረት ሰጥቶ እየሰራ ይገኛል ብለዋል። ‎ ‎የሴቶችን መብት ለማስጠበቅ ከሚደረገው ጥረት ጎን ለጎን በተለያየ ምክንያት ለጥቃትና ለችግር ለተጋለጡ ሴቶች የማህበራዊና ስነልቦናዊ ድጋፍ ለመስጠትና በዘላቂነት መልሶ ለማቋቋም የሚያግዙ ተግባራትን ከባለድርሻ አካላት ጋር በቅንጅት እያከናወነ እንደሚገኝ ተናግረዋል። ‎ ‎በዛሬው ዕለትም የህብር ቀንን ምክንያት በማድረግ ለጥቃት የደረሰባቸው ሴቶች ማረፍያ እና ልማት ማኅበር 1.5 ሚሊዮን ብር በዓይነትና በገንዘብ ድጋፍ ማድረጉን አስታውቀዋል። ‎ ‎የሴቶች ማረፍያ እና ልማት ማኅበር ዋና ስራ አስኪያጅ እና መስራች ወ/ሮ ማርያ ሙኒር በተደረገው ድጋፍ መደሰታቸውን ገልፀው ለተረገው ድጋፍ በተጠቃሚ ወገኖች ስም ምስጋና አቅርበዋል። ‎

የፕሬስ መግለጫ ብዝኃነታችን የምንደምቅበት ጌጥ፣ የተደመረ ዐቅማችን ማሳያ ነው! ኢትዮጵያ የብዝኃ ማንነቶች ድምር ናት፡፡ ኢትዮጵያውያን ከሚኖሩበት የአየር ንብረት እስከ አመጋገባቸው፤ ከአመራረታቸው እስከ አለባበሳቸው፤ ከሃይማኖታቸው እስከ ፖለቲካዊ አመለካከታቸው በርካታ ብዝኃነቶች ያስጌጧቸዋል፡፡ የእነዚህ ብዝኃነቶች ድምር ደግሞ የኢትዮጵያ የማድረግ ዐቅም ነው፡፡ የኢትዮጵያውያን ብዝኃነት ለዘመናት የማይታረቁ የልዩነትና ግጭት ምንጭ ተደርጎ እንዲታይ ታሪካዊ ጠላቶቻችን ያለመታከት ሠርተዋል፡፡ በዚህም በየዘመኑ የታዩ ስኬታማ ድሎችን በአጭር እየቀጩ ኢትዮጵያን የማይገባት ደረጃ ላይ እንድትገኝ ለማድረግ ጥረዋል፡፡ ይህ ትውልድ ግን የጠላቶቻችን ምኞትና የብዝኃነትን ዐቅም የተረዳ፣ የበለጸገች ኢትዮጵያን እውን የሚያደርግ ባለታሪክ ለመኾን የልዩነት ሰንኮፎቹን በምክክር ለመንቀል ወስኗል፤ የጋራ ዕጣ ፋንታዉን በጋራ ተልሟል፡፡ ዛሬ ላይ ኢትዮጵያውያን የከፍታ ጉዞን ነጠብጣብ እንዳይኾን መሥመር አስይዘነዋል፡፡ ችግሮቻችንን እና የግጭት ምንጭ ኾነዉ ለባዕዳ መግቢያ ቀዳዳ፣ ለባንዳ መሹለኪያ የነበሩ ክፍተቶችን ለመድፈን በጋራ መክረናለ፡፡ ኢትዮጵያውያን በሰላማዊ ትግል ያነበሩት የለውጥ መንግሥት ባለፉት የለውጥ ዓመታት እየደረጀ መጥቶ ኢትዮጵያን በጽኑ መሠረት ላይ መገንባት የሚያስችል ዓውድ ፈጥሯል፡፡ የመልክአ ምድር፣ የአመጋገብ፣ የአለባበስ፣ የቋንቋ፣ የሃይማኖት፣ የፖለቲካዊ አመለካከትና ሌሎች ልዩነቶቻችን የኢትዮጵያ ጌጥ እና ዐቅም እንደኾኑ የጋራ አቋም ወስደናል፡፡ ብዝኃነታችን ውበት እና የካበተ ሥልጣኔያችን ማሳያ፣ ከትናንት እስከ ዛሬ የመቻላችን ምክንያት እንደኾነ በአካታች ሀገራዊ ምክክራችን አረጋግጠናል፤ ታሪኮቻችንም ምሥክሮች ኾነው አሳይተውናል፡፡ የዓለምን ታሪክና ፖለቲካ የለወጠው የዓድዋ ድል፤ የኢትዮጵያን ጂኦ-ፖለቲካዊ ዐቅም ያሳደገዉ ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ፣ የኢትዮጵያን ስም በዓለም በየዓመቱ በበጎ የሚያስጠራዉ አረንጓዴ ዐሻራ ለብዝኃነታችን ዐቅምነት ሕያዉ ምሥክሮች ናቸው፡፡ ለዚህም ነው ጳጒሜን 4ን የኅብር ቀን ብለን ብዝኃነትን የኢትዮጵያ ጌጥ መሆኑን በሚያረጋግጥ መልኩ እያከበርን የምንገኘው፡፡ ኢትዮጵያ የብዙ ብዝኃነቶች ሀገር በመኾኗ የብዙ ዐቅሞች ባለቤትም ናት፡፡ የብዝኃነትን ጌጥነት እና ዐቅምነት እርስ በርስ መረዳዳት እና አንዳችን ለሌላችን ጥላ ከለላ በመኾን እንገልጸዋለን፡፡ ዛሬ እነዚህን እውነቶች ለዓለም የምንገልጽበት ድንቅ ቀን ነው፡፡ እንኳን ለጳጉሜን 4 የኅብር ቀን አደረሳችሁ! ጳጒሜን 04 ቀን 2018 ዓ.ም የኢፌዴሪ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት አዲስ አበባ ለተጨማሪ የመረጃ አማራጮች https://linktr.ee/FDREGovermentCommunication

‎ሚኒስቴሩ የኀብር ቀንን አስመልክቶ ለተቋሙ ሰራተኞችና ለተለያዩ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ማዕድ አጋራ ‎**** ‎(ጳጉሜ 4/2018 ዓ.ም) የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር አመራሮችና ባለሙያዎች "ብዝኀነት የኢትዮጵያ ጌጥ!" በሚል መሪ ሃሳብ የኀብር ቀንን በተለያዩ መርሐግብሮች በድምቀት እያከበሩ ይገኛል። ‎ ‎ሚኒስቴሩ የህብር ቀንን እንዲሁም መጪውን አዲስ አመት ምክንያት በማድረግ የተቋሙ ሰራተኞች ከነቤተሰባቸው በዓሉን ተደስተው እንዲያሳልፉ አስፈላጊውን የበዓል መዋያ ድጋፍ አድርጓል። ‎ ‎በተጨማሪም አቃቂ ቃሊቲ ለሚገኘውና ጥቃት የደረሰባቸው ሴቶች ማረፊያና የልማት ማህበር የ200 ሺህ ብር እና የቴምር ድጋፍ ተደርጓል። በተመሳሳይ ለ13 የበጎ አድራጎት ተቋማት የቴምር ድጋፍ አበርክቷል። ‎ ‎በሚኒስትር ዴኤታ ማዕረግ የክብርት ሚኒስትር አማካሪ ክቡር አቶ ጌታቸው በዳኔ በዕለቱ ባስተላለፉት መልዕክት፤ ብዝሃነት ለሀገር ጥንካሬ እና ለህዝቦች ማህበራዊ ትስስር የጸና ምሰሶ መሆኑን አንስተዋል። ‎ ‎የኅብረ ብሔራዊ አንድነት እሴቶችን ማጠናከር ሀገርን ከማፅናት ባለፈ የነገዋን የበለጸገች ሀገር ዕጣ ፈንታ የሚወስን ቁልፍ ጉዳይ እንደሆነም ገልጸዋል። ‎ ‎ዛሬ ከምንጊዜውም በላይ በህብረት የመቆሙን አስፈላጊነት ተረድተን ለጋራ ቤታችን በጋራ መትጋት ይገባናል ሲሉም አሳስበዋል። ‎ ‎በልዩነታችን አምሮብን፣ በአንድነታችን ጸንተን፣ ለጋራ ብልጽግናችን በህብር መቆምና በየተሰማራንበት መስክ ጠንክረን መስራት ከሁላችንም ይጠበቅብናል ብለዋል። ‎ ‎#ጳጉሜን4 #የኀብርቀን #ብዝኀነትየኢትዮጵያጌጥ #ኢትዮጵያ ‎ ‎ ‎ ‎ ‎ ‎

‎በተቀናጀ አሰራር የተጋላጭ ወገኖችን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ የሚያስችል የ“GO-NGO” ፎረም በድጋሚ ለማቋቋም የሚያስችል ምክክር ተካሄደ ‎**** ‎ ‎የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር መንግስታዊ እና መንግስታዊ ባልሆኑ ተቋማት መካከል የትብብርና ቅንጅት ሥራዎችን ለማጠናከር፣ የ“GO-NGO” ፎረም ዳግም ምሥረታ መድረክ በአዲስ አበባ አካሂዷል። ‎ ‎በመድረኩ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት ሚኒስቴር ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አሳልፈው አመዲን እንደገለጹት፤ ሴቶች፣ ሕፃናት፣ ወጣቶች፣ አካል ጉዳተኞች፣ አረጋውያን እና ሌሎች ተጋላጭ የማኅበረሰብ ክፍሎችን በባለቤትነትና በተቀናጀ መልኩ ለመደገፍ አሁን ላይ ጠንካራ የትብብር ማዕቀፍ መዘርጋት ወሳኝ ነው። ‎ ‎ቀደም ሲል ተቋቁሞ የነበረው ይህ ፎረም ከተቋማዊ መዋቅር ለውጥ ጋር ተያይዞ ተቋርጦ መቆየቱ ሥራዎች በተበጣጠሰ መልኩ እንዲከናወኑና የሀብት ብክነት እንዲኖር ማድረጉ ተነስቷል። ‎ ‎አሁን ዳግም የተቋቋመው ፎረም ይህንን ክፍተት በመዝጋት የሥራ ድግግሞሽን በማስቀረት፣ ተጠያቂነትን በማጠናከር እና ሀብትን በአግባቡ በማስተባበር ተጨባጭ ውጤት እንደሚያስመዘገብ ታምኖበታል። ‎ ‎ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከተሰጠው ኃላፊነት አንጻር ከሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች እና ከባለድርሻ አካላት ጋር ላደረገው ትብብር ምስጋና ያቀረበ ሲሆን፤ በቀጣይም ለፎረሙ ስኬታማነት የቴክኒክና የፋይናንስ ድጋፍ ላደረገው ዪኤንውመን(UN WOMEN) እና ለተባበሩ አካላት ሁሉ ልባዊ ምስጋና አቅርቧል። ‎ ‎🇪🇹#MoWSA #GONGOForum #Ethiopia #Inclusion #SocialDevelopment #AddisAbaba ‎

ጳጉሜን 4- የኀብር ቀን እንኳን አደረሳችሁ! "ብዝኀነት የኢትዮጵያ ጌጥ!"
ጳጉሜን 4- የኀብር ቀን እንኳን አደረሳችሁ! "ብዝኀነት የኢትዮጵያ ጌጥ!"

‎የሀገር ፅናት - የሰላም ዓምዶች ‎***** ‎የሀገር ጸጥታ፣ ሉዓላዊነት እና የሰላም ዋስትና በደማቸው እና በላባቸው የሚከፈሉ ውድ ዋጋዎች ውጤት ናቸው። የሀገርን ሠላም ለመጠበቅና የሉዓላዊነት ዐምድ ሆኖ ለመቆም ከሚደረገው መስዋዕትነት ጀርባ የሴቶች፣ የወጣቶች እና የሰላም እናቶች ሚና ከፍተኛ ነው። ‎ ‎እነዚህ የህብረተሰብ ክፍሎች በሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ በጸጥታ ተቋማት እና በሰላም ማስከበር ዘርፍ እንዲሁም በባህላዊ የሰላም ግንባታ ግንባር ቀደም በመሆን የከፈሉትና እየከፈሉት ያለው መስዋዕትነት ታሪካዊ ቦታ የሚሰጠው ነው። ‎ ‎የመከላከያ ሰራዊቱ እና የጸጥታ ተቋማት የሀገርን ጸጥታ ለማስጠበቅ በሚያደርጉት ጥረት የሴቶችና የወጣቶች ተሳትፎ ከዕለት ወደ ዕለት እያደገ መጥቷል። ‎ ‎ሴት አባላት በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ ከሎጀስቲክስ እና ከሰላም ሰጪነት ባለፈ በከፍተኛ የውጊያ ስልጠናዎች፣ በአየር ሃይል፣ በምህንድስና እና በቴክኖሎጂ ዘርፎች በብቃት እያገለገሉ ይገኛሉ። ‎ ‎ወጣት ሰራዊት አባላት ለሀገር ሉዓላዊነት ያላቸውን ታማኝነት በውጊያ አውደ-ምድር ብቻ ሳይሆን በድንበር ጥበቃ፣ በህግ ማስከበር እና በሰላም እጦት የተጎዱ አካባቢዎችን በመታደግ ረገድ የፊት መስመር ተሰላፊዎች ናቸው። በአህጉራዊና አለም አቀፍ ተልዕኮ ውስጥ አምባሳደሮቿ የሴት ሰራዊት አባላትና መኮንኖች ሚና ልዩ ትኩረት የሚሰጠው ነው። ‎በጦርነትና ግጭት የተጎዱ አካባቢዎችን ለማረጋጋት በሚደረጉ አለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ዘመቻዎች ሴት አባላት ከጸጥታ ጥበቃ ጎን ለጎን ለተጎዱ ህፃናት፣ ሴቶች፣ አካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን ርህራሄን ከሰብአዊነት ያዋደደ ድጋፍ በማድረግ፣ ስነ-ልቦናዊ ድጋፍ በመስጠት እና ሰላምን በመገንባት ረገድ ከፍተኛ አድናቆትን አትርፈዋል። ‎ ‎የሀገር የሞራል ጀርባ እና የባህላዊ ሰላም አርበኞች የሆኑት የሀገር ሽማግሌዎችና ተእናቶቻችን ተቋማዊ ከሆኑ የጸጥታ መዋቅሮች ጎን ለጎን፣ ማህበረሰቡን ከታች ጀምሮ በሰላም በማስተሳሰርና የሰላም ድምጽ በመሆን ሀገር እንድትፀና ሚና የማይተካ ነው። ልጆቻቸውን ለሀገር ሰላም፣ ፍቅርና አንድነት እያስተማሩ የሚያሳድጉት የሰላም እናቶች የሀገር የሞራል መሰረትና የሰላም ህይወት ችቦዎች ናቸው። ‎ ‎የሀገር ሰላም ሲረጋገጥ እና ሉዓላዊነቷ ሲጠበቅ የፊት መስመር አርበኞቹ የሆኑት የመከላከያና ጸጥታ አባላት፣ እንዲሁም የማህበረሰቡ መሰረት የሆኑት የሰላም እናቶች የከፈሉት መስዋዕትነት ሁልጊዜም በክብር የሚታወስ ነው። ሰላማችን የሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች የጋራ ድካም ውጤት በመሆኑ፣ ለዚህ የቁርጠኝነት ስራ ልዩ ዕውቅና ሊሰጠው ይገባል።