835
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
ስፍራው እዚህ ላይ ነው
( በእውቀቱ ስዩም)
የተገናኘነው
ስፍራው እዚህ ላይ ነው፤
በጋዜጣ ቅዳጅ፥ መታ መታ አድርገን
አቧራውን ጠርገን
ከሰፈ ጀርባው ላይ
የተቀመጥንበት፤ አረጋዊ ድንጋይ
አካሉ በከፊል ፤ ወደ መሬት ሰጥሞ
እንደነበር አለ፤ የሳር ሻሽ ጠምጥሞ
ላልፎ-ሂያጅ ተመልካች፥ ፍቅር ለጎደለው
ምንም ነገር የለው፥
ቀልብን የሚያሸፍት
በሀያል አድናቆት፥ አፍን የሚያስከፍት ፤
በግርማ ሞገሱ ፥ተሪስት የሚጠራ
ጥንታዊ ሰገነት፥ አለት -ለበስ ጣራ
ተምዘግዛጊ ውሀ፤ ረጅጅጅም ተራራ
አቤት የሰው ጥበብ
አቤት የግዜር ስራ
የሚያሰኘ ድንቃድንቅ ፥ የለም ከዚህ ስፍራ፤
ለኔ መሳዩ ግን
ላንድ የፍቅር መናኝ
ወርቅ የሚሆንለት፥ ትቢያውን ቢዘግን
አንዲት የሳር ብናኝ
አንዲት ያፈር ቅንጣት
አመት የሚያወጉት፥ ታሪክ ነው ሚወጣት ፤
በምነት የተመካ
ተጓዥ ያገሬ ሰው
ወደ ኢየሩሳሌም፥ ወይም ወደ መካ
ቀን ቆርጦ ሲሳፈር፥ ወደ ተቀደሰው
እኔ ግን እዚህ ነው የምመላለሰው ::
[ በዕውቀቱ ስዩም ]
@yourpoim
@yourpoim
ባንተ ስም ተጠራሁ
በድፍረትህ ኮራሁ
ግን ልትለየኝ ነው
ብቻዬን ነኝ ፈራሁ ።
ለካ እንዲህ ብርቅ ነው
የአንድ ለሊት እንቅልፍ
ለካ እንዲህ ይሞቃል
የክንዶችህ እቅፍ
አይ የጦርነት ግፍ !
ምን ላ'ገር ቢዘምቱ ፤ ጠላትን ቢመቱ
ለሰንደቅ አላማ በክብር ቢሞቱ
ነገር ሁሉ ከንቱ !
የልብ አያደርስም
የአፍቃሪን ጥያቄ ፥ ጦር ሜዳ አይመልስም ።
መቼስ ልትሄድ ነው
ዝመት የአባትህ ነው
ኢትዮጲያዊ ሆነህ የተለመደ ነው
ግን "እንጋባለን" ብለሀል ለግንቦት
ነገርኩህ ! እንዳትሞት !
[ ሐብታሙ ሃደራ ]
@yourpoim
@yourpoim
[ ሙሃመድ ኢድሪስ ካሳ ]
.
.
.
አህጉር ተሸክሞ እንደሚዞር ቱሪስት ተላላ ታፋዬ ዝሎ
ፈረጠመ
መካን አንጎሌ ላይ መሰረት የሌለው ግፍ ተጠመጠመ፣
በየለት ፣ በየቀን ...
በናፈቀሽኝ ቁጥር ፎቶሽ ላይ ተሰካሁ
ናፍቀሽኝ ሳነባ የተኛሁሽ ያክል በለቅሶዬ ረካሁ።
.
ቢሆንም..
የናፍቆቴ ሽቦ ምናቤን ተብትቦ የትዝታችን ድር ሀሳቤን
ቢገምድም
እመኚኝ አለሜ በኔና አንቺ ማቄም አጀንዳ ለሚያጮኽ እከካም
አዝማሪ አላጎበድድም።
ውዴ ..
ከሰማዩ መሀል ፈራርጠው ሲደቁ ከዋክብት እንደገል
ትንፋሽሸ ይመጣል ራቁት ምናቤን ከህልው ለማግለል።
.
ብዙ እናፍቅለሁ...
ብዙ ዘግባለሁ ...
በቅዱም ትርክቴ ነገዬ ሲንፏቀቅ ዛሬዬ ሲገፈፍ
ሳቅሽን ስላለሁ ከቁዝምት የዳነ መፃዒ ለመግደፍ።
(ከንፈርሽን ስራብ .....)
የመንፈስሽ ጠረን ከርሰ ምድር ፍቆ ስሬን ሊንድ ሲመኝ፣
ውዝፍ አርምሞሽ ነው ልቤን የሚስመኝ።
፩ .
[ ከ Sufi ስንኞች የ ኹስሮን ( Amir khusrow AD 1253–1325 ) “I am a Believer of Love” ]
መቁጠሪያ ባልሻ
ባይሰምር ጸሎቴ ፤
ምቱ ይቆጠራል
መላ ውስጥ አንጀቴ ፤
ሌላ እምነት የለኝም
ፍቅር ነው እምነቴ ።
አንተ ማይም ሓኪም
ተወኝ ለእጣዬ !
ወፈፌ ስራህን ሌላ ቦታ እደል !
ያፍቃሪ ከኒናው የፍቅሩ ፊት አይደል ? !
ውሃ የሚያዘንበው
አይመስለኝ ደመና ፤
ደም ነው የማነባው
ዘንድሮም እንዳምና ።
ብታጪ ሽልማት ወደ ፊት ተዋህደሽ
ልቤ ደስ ይብልሽ !
ገደ ቢስ አትባይ - ውበት ከገደለሽ ።
እውነት ነው ይላሉ ..
ይሉኛል ኹስሮ* ይሰግዳል ለጣዖት
ፍጹም ግን አልሄድም ከመንጋ ጋር ብሞት ።
Amir - ትርጉም ሰልሃዲን አሊ
Repost from Esubalew Abera N.
በቅርቡ በሙዚቃ ሳይንቲስቱ ጋሽ ሙላቱ አስታጥቄ “የኢትዮ — ጃዝ የሙዚቃ ፍልስፍና” ላይ በ “https://www.youtube.com/@esubalewabera” የዩቲዩብ ቻነል የማቀርበው መሰናዶ ይኖራል። እስከዚያው እንደ መቆያ፡— በዘነበ ወላ ስብሐት ገብረ እግዚአብሔር ማስታወሻ፣ በበዕውቀቱ ስዩም ስብስብ ግጥሞች፣ በፕሮፌሰር ኃይሌ ገሪማ የፊልም ፍልስፍና ላይ ያቀረብኳቸውን የግል ምልከታዎች እንድትታደሙ እጋብዛለሁ።
ቻነሉን ሰብስክራይብ ቢያደርጉ ሌሎችም መሰል ዝግጅቶች ይደርስዎታል!
ኪዳኑን ያፈረሰላት
ደርዝ ይዞ አልፈጠራትም
ሃምራዊ ሳቋን ታቅፋም
መጠላት አልቀረላትም
አንሷታል ዕንባ መደረብ
ከጠይም ውበታም ፊቷ
ይሄንን ሊያለብሳት ነበር
ማምሻውን የሄደው ቤቷ
ስለ ዕንባው ከጻፈው ግጥም
ሶስት መስመር አነበበላት
ዝም አለች እሷም እንደ እግዜር
ያን ጊዜ ዕንባ ቀለላት።
.
.
ኪዳኑን ያፈረሰላት
ደርዝ ይዞ አልፈጠራትም
መሳቋን እንደታቀፈች
ማልቀስም አላነሳትም
ቀርቶታል ወንድ መታቀፍ
ድንግል ነው ጠይም አካሏ
ይሄንን ስታክም ነበር
ሴሰኛ ውራጅ ማከሏ
ሃረር ናት ዕምባ ያለበሳት
ባቲ ናት ወንድ ያስለቀሳት
ስለ ዕምባ በጻፈው ግጥም
ሃምራዊ ሳቋን ያስረሳት።
.
.
ኪዳኑን ያፈረሰላት
ደርዝ ይዞ አልፈጠራትም
እህ ባይ ሴት አጣች እንጂ
ወንድ እንደው አልጎደላትም
እኔ ጋር አለሽ ሴትነት
እኔ ጋር አለሽ ወንድነት
ማርያምሽ ያበደረችኝ
እኔ ጋር አለሽ መቀነት
አሙሽ ወይ ፣ ሃገር አስታከው
መቅለልሽን ለእግዜርሽ ልከው
ገላሽን ፣ ተኝተው ቀጡሽ
እኔን ባይ ፣ ንሰሐ አሳጡሽ
ባቲ ነሽ ወንድ ያስለቀሳት
ሐረር ነሽ ማቅ ያለበሳት
ግጥም እንኳ ጣዕሙ ሲታደል
ስለ ዕምባ ለሷ የደረሳት።
°°°
ቆንጆ ስዕል ማለት
የልጅ መንገድ እና ፣ የወንድ ዕምባን አዝላ
ላንዱ ያንገት ጌጧን ፣ ላንዱ ነፍሷን ጥላ
አጠር ያለ ቀሚስ
ቀጠን ያለ ወገብ ፣ አስደናሽ መዳፎች
ከሚስሙት እኩል ፣ የሚያጤሱ አፎች
እያሳለመችው
የቀሚሷን ፓሪ ፣ አየኝ እንደማለት
እየሸፈነችው ፣ የተሳለችበት።
ቆንጆ ስዕል ማለት
ስድስት ቦታ ጉንጉን ፣ ሁለት የእጅ አምባር
ከእጇ እንዳጠለቀች
በነጠላዋ አልፋ ፣ ለእግዜር እያነባች
ለሰው እየሳቀች
ከማርያም ደብር ላይ ፣ ቀድማ የወጣች ፀሀይ
እየሸሸችባት
መንገድም እንደ ሰው ፣ በልጆቿ በኩል እየቀለደባት
የተሳለችበት።
ቆንጆ ስዕል ማለት
የልጅ መንገድ እና ፣ የወንድ ዕንባን አዝላ
ከእግዜርም ከወንድም ፣ ከሁለቱም ተጥላ
ወለላ
ወለላ
ብዙ ወንድም ወንዶች ፣ ያረገፏት ሾላ።
ቆንጆ ስዕል ማለት . . .
የሐሙስ ዘፈን
ሙና ነይ ሰውነት
ሙና ነይ ሴትነት
መልክ እንደ ታቀፈች ፣ ወንድ እንደ ሰለቻት
ማልቀስ አልቻለችም ፣ መሳቅ አይመቻት
ኑ እናልቅስ ለሸጋ
ኑ እናልቅስ ለ ፀይም
ስትሳለም እንጂ ፣ ስትወድ አትታይም
አታምንም
አታምርም
« የጫካ ፅጌ ናት »
አጀብ ከ ወጀብ ጋር ያመላልሳታል
ያም አቅፎ ያም ስሞ ፣ ያቆሳስላታል
ያም አቅፎ ያም ስሞ ፣ ዕድሜ ነሽ ይላታል
ዕድሜ ነሽ የከንፈር
ዕድሜ ነሽ የ ዕምባ
ናና ፣ ናና እናቱ ፣ ናና ፣ ናና አበባ
ዕድሜ ነሽ ይላታል ፣ ዕድሜ ነሽ የልኬት
ቢ'ኖር ይታጣል ወይ ፣ የ እሷን ታህል ደስታ
የእሷን ታህል ስሜት
የሐሙስ ዘፈን
እኑር አንሙት ፣ እንሳቅ እናንባ
ጊዜ ያብሰዋል ፣ የሴትን ለቅሶ
የሴትን ዕንባ
ሮዛ
.
.
ማን ነበረ ሳቋን የተሸከመላት
ማን ነበር መስቀሏን የተሳለመላት
ህይወት በ እግዜር መዳፍ
ህይወት በ ጊዜ አክናፍ
አደገች አጣችው
የልጅ ቡረቃዋን ከየት አኖረችው ?
አንዱን ዕድሜ ቢጤ
አንዱን ጊዜ ቢጤ
ምን ምን ይላል ሲሉት
« ያዛኝ ሰው ገላ
ያዛኝ ሰው አንገት
ማዕተብ ማዕተቧን ነው ?
ዕንባ ዕንባዋን ሚሸት ? »
" እሷን እሷን " ያለው
አንቺን አንገትሽ ስር
አንቺን ማዕተብሽ ስር
ቀምሶሽ ነው ? ስሞሽ ነው ?
የቀረፋ ሽታ ፣ አደይ የ ናና ጣዕም
አንቺን ስመው ቢያዩት
አንቺን ቀምሰው ቢያዩት
ጥፍጥናን አያጣም ?
ሮዛ ስንት አካል ፣ ሮዛ ስንት አምሳል
አንድ አንቺን ለመሳል ?
ስን' ቁስል ፣ ስንት ህመም
አንድ አንቺን ለማለም ?
ወደ ሞት መንገድ ላይ
ማን ነበረ ሳቅሽን ፣ የተሸከመልሽ
ማን ነበር መስቀልሽን ፣ የተሳለመልሽ
እንዴት ቻለ አቅሙ ፣
እንዴት ቻለስ መሳም
መስቀሏን ሲጠጉ
ማዕተቧን ያዘለ ፣ አንገቷ አያሳሳም ?
ሮዛ ያ'ደይ ክንፍ ፣ ሮዛ ንጹህ ቃል
እንደው ናፈቅ ናፈቅ
እንደው ወደድ ወደድ ፣ አሰኝቶሽ ያውቃል ?
እኔን ግን አሰኘኝ
እኔን ግን ሞትኩልሽ
ምነው አንገትሽን
ምነው በሳምኩልሽ
ወርቅ አካል አካሏ፣ ወርቅ አካል ነው ስሟ
እሷ ጊዜን ሆና
እሷ እድሜን ሆና ፣ ሳቋን ማሸከሟ
ወርቅ አካል አካሏ ፣ ወርቅ አካል ነው ስሟ
ሮዛ ።
📷 : selfportrait by so_see
ኖሮ ካየሁት የምድር ገላ ፣
ያንተ ይነፃል
የቀራጭ እድፍ ፣ ያ'መንዝራ ዕምባ
ስምክን ያንፃል
የ'ኔን
ልቤን በ ሴት እጅ ፣ ቀድሞ ቢያበጀው
ቶሎ በሰማኝ ፣ ፀሎት ባልፈጀው ።
መልኬን እንደ እናት ፣ ቢያለብስ ጥቅርሽ
መንገር ባላሻ ።
ወንድም አይደልሁ?
ስጮህ ባላየኝ ስማኝ ለማለት
ለ ክንዴ መቻል
ለ ልቤም ዕምባ ፣ ቢያበጃጅለት
እኔም ያ'ዳም ልጅ ፣ አንተ ያ'ዳም ጌታው
ሳቄ ፆም የለው
ልጓም ሁዳዴህ ፣ መች ነው ሚፈታው
አንተም የ'ኔ አባት ፣ እኔም ያንተ ዘር
ዝም አይሻልም ?
የ ወንድ ምሬት ፣ ከሚዘረዘር
ስማኝ ለማለት ፤
ገላም ከ እድሜ ጋር ይገረጅፋል
ወይ እስክሰማኝ ፣ ወይ እስክትጠራኝ
ስንት ቀን ያልፋል ?
አልተው አልኩ እኮ በ እጄ መቁሰል
አልተው አልኩ እኮ እራሴን ማክሰል
ትጠራኝ ይሆን
ይሄም በ ትላንት እስከሚመሰል ?
ይሮጥ የለም ወይ ፣ እድሜ ሳያውቁት
እነ መደሰት ፣ እነ ማመስገን
እስክናረጅ ነው የሚጠብቁት ?
መቼ ሊመጡ?
መቼ ከ ሰው ጋር ሊያንሰላስሉን
አልፈውን ይሆን
ይሉኝታ ጥላ እየመሰሉን ?
ስማኝ ለማለት
ልቤን በ ሴት እጅ ፣ ቀድሞ ቢያበጀው
ፀሎት ባልፈጀው
ሚበርዳቸው ይመስለኛል
ወንዙ ሀይቁ
ውቅያኖሱ
አራዊቱ ለምለም ዛፉ
በኔ በኩል በእቅፍሽ ካልታቀፉ።
ሚበርዳቸው ይመስለኛል
ታሪክና ትንቢታችን
አሁንና ትላንታችን
ጊዜ ስፍራ
ግራቀኙ ደስታው
ዋየይታው
መኖር መሞት ማግኘት ማጣት
ሚበርዳቸው ይመስለኛል
ካልነካሁሽ ካልነካሽኝ በፍቅር ጣት
ለምን?
በደምሽ ውስጥ
በደሜ ውስጥ ሁሉም ነገር አለው ቅንጣት።
ቅዝቃዜሽ፣ የኔ መብረድ
ሲተላለፍ ሲቆላለፍ
ከሚመጣው ከሚሄደው
ከሚወጣው ከሚወርደው
ነይ እቀፊኝ
ነይ ልቀፍሽ
ብሎ ብሎ እግዜራችን እንዳይበርደው።
ትንሽ መሻት
ጥቂት ናፍቆት አንጠልጥለው
ነፍስ አጠገብ ካልተገኙ
ቆፈን አለ እሳት አቅፈው እየተኙ።
[ ያዴል ትዕዛዙ ]
[ከራስ የተሰረቀ ገጽ]
ትገጥማለች...
ቤት ይመታል
ሰው ፊደሉ
ሰግዶላታል....
ጣዖት ናት...
ለቋንቋ ለቃል
ዘላለም...
ስሯ ይወድቃል
በተፋው....
እሳት። ብዕሯ
ኣፍታዬን.....
ለድሜ.. መዳሯ
ጥጓ ነው መሰል ማሰልቸት
ቀኔን ለነፋስ ማመቸት
ግቧ ነው መሰል ጉም ለጉም
መንገዴን ማሳጣት ትርጉም ።
እያየኋት ነው አሁንም
ትናንትም ከትናንት ወዲያ
ኮቴዋን ጠረኑን ናፍቆ
አሸርጋጅ የልቤ ጓዳ
ምን እንደሁ የታጠቀችው
በፊቱ ስትገማሸር
የዘመን ዝናር ድምድሙ
የሚናድ የሚሸረሸር
ምን ኖሮት ያይኗ ጭላንጭል
እንደ ገል ሊሸራርፈኝ
ላስባት ማሰብ ስጀምር
’ካሳቤ የሚያኳርፈኝ ።
(ብቻ.....
እግሯ...
ይራመድ እንዳሻው
ሞቴ ...
ከሆነ። መድረሻው...
[ ይስሃቅ ]
_ ሌላ መንገድ _
[
እንደ_ደጋ ቆሎ በኑግ እንደታሸው
እንደ_ጀግና ሂወት ቶሎ እንደሚመሸው
እንደ_ስለት ግልገል
ፈፋ ተባ ሲሉት እንደሚሟሽሸው
ጠቆረ ጊዚያቱ
ሻከረ ወራቱ
ምኑንም ምኑንም እያግበሰበሰ
ሊኮል ነው ሲሉት ጎሼ ደፈረሰ
እቴ ነይ እንግዲህ
ሰጥቸሽ ሰጥተሽኝ ተካፍለን ለማደር
ካይኖችሽ ካይኖቼ እንባ እንበዳደር
እቴ ነይ እንግዲህ
እንስቃለን ብለን
ጥርስሽን ፍቀሽው ጥርሴን ተወቅሬ
የወይራ ማሟጫ ከጉንጬ ሰንቅሬ
እስከመቼ ድረስ
ደስታን እየጠበቅን ከወቅት እንታገል
ተሸርፎ ተሸርፎ
አለቀ አደለምወይ እድሜ'ያችን እንደገል
እቴ ነይ ዝምብለሽ
ካለው እንስማማ
ርሃብ ጥማችንን በሳቅ እንድንገፋው
በባዶው እንቦርቅ በመልካ በፈፋው
አዚሚልኝ ዘፈን ሂወት የዳበሰው
ምጣድ ቃል ንገሪኝ መኖር የዳሰሰው
ምናቤን ዘርግቼ
በፍም የተለካ ላቀብልሽ ግጥም
'ላለም እንናገር
እንባን ወዶ መኖር እንዴት እንደሚጥም
እቴ ነይ ዝምብለሽ
እንዲህ ባለ ጊዜ
ተስፋ ሆኖ ሲቀር
የሂወትን ጀምበር በሳቅ ማገባደድ
ሽክረትን ነው ማፍቀር መከራን ነው መውደድ
[ አማረ ዘውዱ ]
እግዜር ያለልምዱ
እዚህ በረሃ ላይ ዶፍ ዝናቡን ጣለ
ፍጥረት ታዛ ቢያጣ
ከደመናው ግርጌ ሄዶ ተጠለለ።
ለዚህ ምድረ በዳ
እንግዳ ነው ዝናብ ደልቶት ተራመደ
ብቻ በመንገዱ
አንዷን ምስኪን ፅጌ ጎርፍ ጠርጓት ሄደ።
እና ማን ግድ አለው?
ሁሉም ዝም ሁሉም ጭጭ!
ዝናቡ ዶፍ ቢያወርድ ዝናቡ ቢያባራ
እግሮቹ ስር ሳለች
አይተዋወቅም ካንዲት ጽጌ ጋራ።
ደመና ስር ሆኖ አበባ አለማወቅ
ሰማይ ስር ተገኝቶ ሕይወት አለማድመቅ
ተረሳስቶ መኖር
አንዳችን ላንዳችን እንደሆንን ባዳ
ቅጣቱን ሲጀምር
በገዛ ቤታችን አረገን እንግዳ።
[ ያዴል ትዕዛዙ ]
ብቸኝነት
እልፍኝህ እንዳʽብርሀም ቤት፣
አደባባይህ እንደጥምቀት፤
የሰው አሸን ቢወረው፣ ጠጠር መጣያ ቢገድም፤
ለመሀላህ ካስማ ʽሚሆን፣ ሲያነቅፍህ የምʽጠራው ስም፤
ከልቦናህ ሲነጥፍ፣ አንደበትህን ሲያንቀው፤
ብቻህን ነህ፣ ያኔ እወቀው፡፡
[ በድሉ ዋቅጅራ ]
@yourpoim
t.me/yourpoim
እኔ ነኝ ገደቢስ
የእድለ ቢስ አምሳል፣
ሌላው ነገር ቀርቶ...
የፊቴ ገጽታ፣ ግድግዳ ላይ ቢሣል፣
ደቂቃ አይቆይም፤
ግድግዳው ይፈርሳል።
Muhammed Edris Kassa
አንዳንዴ
ጠላት ሲሆን ሳር ቅጠሉ
ተስፋ ሳጣ ሲዞር ሁሉ
በሀዘኔ
በሕመሜ ፣ በድቀቴ በመሀሉ
እየመጣሁ የማርፍባት
የምትቀርበኝ የምቀርባት
ያቺ ድንጋይ
እሷም ጠልታ የሰው ጠረን
እሷም ጠልታ የሰው ገላ
ገደል ገባች ተንከባላ
HEnock Bekele
እግዜርና ዳዊት - አብረው ተቧደኑ
ብቻውን ታጠቀ - ጎልያድ ምስኪኑ
አንዳንዱ ተገዶ - ለሽንፈት ሲፈጠር
በጥቅሻ ይወድቃል - እንኳንስ በጠጠር
Bewketu Seyoum
[ "በሰፊው ሕዝብ ጥያቄ መሰረት የተደገመ" ብለህ እንደ ETV ትሰክሳለህ ግጥም ልትገርብ ስትፈልግ 😂]
➖ Cultic Poetry - A Letter To Thyself ➖
ኮቴህ ደረቅ ነው፣ ዳናህ የለው ገድ
እስኪ አርፈህ ውድቅ፤ አትወላገድ
ምን ልትፈጥር ነው የምትታገል?
አውቀህ ተሰበር፤ ድቀቅ እንደ ገል
በቄንጥ አትርገጥ መውደቅ ፍራቻ
መንገድ ዳር ፍሰስ እንዳራሙቻ
እንቅፋት ሆነህ ሌላውንም ጣል
ሌላው ከመውደቅ ለምን ያመልጣል?
ልብህን ሰብረህ በል ቅደማቸው
ደምህን ሲያዪ ይፍላ ደማቸው
ስልክህን ዝጋ፤ ከደጃፍህ ጋር
ሳራህን ተዋት፣ ግባ ወደ አጋር
ማነው ጓደኛ ፤ ወዳጅ ምንድነው?
ስሱ ልብህን በል አደንድነው!
ምን አውራ ቢሆን፣ ዶሮ አይጠመድ
እርባና ቢስ ነው ዘመድና አመድ
በርህ ላይ ጠላት ይንከላወሳል
ሰይፍህን ሞርድ፤ ሻሞላህን ሳል
ግራህን መትቶ፣ ቀኙን ላለ ሰው
ለጥፊው ምላሽ፣ ዐይኑን አፍስሰው
ከእሪያ ተማር፣ ሁን ታጥበህ ጭቃ
የጲጥፋራ ሚስት ትርታህ ጨቅጭቃ
ፍቀድ ልብስህን ታውልቅ መንጭቃ
[
አንቺም
ዳግማዊት ማርያም ፅድቁ ሚርብሽ
የዘመኔ አዳኝ ሲሻ ሊያድርብሽ
ብስራት ያለልሽ ሆኗል ስብራት
ቁርሳችን ሆነ የሻገተ ራት
በሺ ፍለጋ በብዙ ትግል
አገኘኹ ብሎ ንፅኂት ድንግል
መላክ ሲመጣ ዜና ለፋፊው
"ወንድ አውቃለሁ" በይ ቀልቡን ግፈፊው
]
ሙንጨራህን ተው ግጥምህን ቅደድ
የማይወድህን አንተም አትውደድ
ቃል የሰነፍ ነው፣ አፈሙዝ ታጠቅ
ዝረፍ ከደሀው፣ ካለው ላይ ንጠቅ
ማንም አይኑርህ፣ ማንም አትኑረው
እያሪኮህን፤ ብቻህን ዙረው
አታልቅስብን፤ አትነፋረቅ
በዝምታ ውስጥ ከሞትህ ታረቅ
ጎልጎታ ጫፍ ላይ ወጥተህ ተራራ
"ልሞት ነው" ብለህ አታስፈራራ
ምን ይጎዳና አንድ ኃጥዕ ሞቶስ
እንኳን አንተና ሞቷል ክርስቶስ
ኡኡታ ጩኸት አያስፈልግም
ማለት ነው'ንጂ ዝም ብሎ ፍግም!
ቢወዱኝ ብለህ ታግለሀል ብዙ
በልብ ገፉህ ባፍ ቢጋብዙ
አይፈልጉህም፣ አትፈልጋቸው
ለርኩስ አይሆንም ንፁህ አልጋቸው!
ዓለም ገፋችህ ካለም ገንጥላ
ልክ እንደራስህ ሌላውን ጥላ!
እርም እርሙን ብላ፣ ወይንህን ጠጣ
ከቶ አይግደድህ፣ ማንም ቢቆጣ
እንኳን ለነገ፣ ለዛሬ አትስጋ
አርብ፣ 'ሮብ ሳትል አነክት ሥጋ
ተፀየፋቸው ቄሱና ሼኹን
በግነት ሲሹ አንተ ፍየል ኹን
በሾላ ዛፍ ላይ አትንጠላጠል
ትበልጥሀለች አንዲቷ ቅጠል
መርዘሙንማ እረዝመኸዋል
ግን አዳኝህኝ መች አይተኸዋል?
አካልህ የለው የስጋ ሙዳ
ችጋር ወዳጅህ፤ ኪስህ ቤርሙዳ
የያዝከው ሁሉ ዋጋ አልባ ጠጠር
ባርኮቱን ሳይሆን ብጉርህን ቁጠር!
ሲያይህ ይድነቀው፤ ይግረመው እግዜር
አፍርቶ ሲያየው የበተነው ዘር
፨ ፨ ፨
በዚህ ሁሉ ግን ይህን አትርሳ
ታመውት ነበር ያንተ ነቀርሳ
በ'ነሱም ነበር ባንተ ያየነው
የሆንከው ሁሉ የሆኑትን ነው!
[ ዮናታን ጌታቸው ]
@yourpoim
@yourpoim
እንቅልፏ
ውድቅት ሌት ይመስል ይከብዳል
ታዲያ
የሚያበራ ሕልም ይወልዳል።
አሁን ትነቃለች
"ደህና አደርክ" ልትል!
ዜማ ይፈልቃታል
ከወፍ፣ ከዛፍ፣ ከነፋስ፣ ከጅረቶች ያልተቀዳ
ትወልዳለች
አዲስ ሰማይ አዲስ ምድር
አዲስ ዳገት አዲስ ሜዳ
ወደ ሀሴት ወደ ነፍሷ መራመጃ
ሲለው ለሰው ማምለኪያ
ሲለው ለሰው መስገጃ
ወደ ቂብላ ወደ ናዝሬት
ወደሰማይ ወደመሬት
መዳረሻ እንዲሆነኝ
ደህና አደርክ ትለኛለች ነቅታ
ስንት ሰዓት ነው አሁን? 3:00 ሰዓት ማታ።
አሁን ትነቃለች ደህና አደርክ ልትል!
ወፎች ይበራሉ
ወፎች ያዜማሉ ከናፍሯ ግርጌ
ንቦች ያሰማሉ ማህሌተ ጽጌ።
ባነቃቋ ወሰን
ታቀራርባለች የዐለምን ጥጋት
ድንገት ትተፋለች ባለቀለም ንጋት።
ልዩ ልዩ ቀለም ያለው ቢራቢሮ
ቀስተ ደመናውን ክንፎቹ ላይ ቋጥሮ
ነፍስ ይዘራል ባፏ
ነፍስ ይነሳል ካፏ
ከንጋት ከብስራት
ከቁርስ ከእራት
ሁሉም ጋር ነው ሰልፏ።
በልሳኗ በኩል
ይፈልቃል ቅዱስ ማይ ነፍስ የሚያፈረጥም
እቆርጥበታለሁ ያደረበኝን ጥም።
ቸስስስስስ ጉረሮዬን
ራስስስስስ ... የነፍሴን ሀሩር
የሆነ ስፍራዬ
ቅዝቅዝ እርጥብ ይላል እንደሸማ ፈትል
መቼ? ደህና አደርክ ስትል።
እስኪ ስንት ሰዓት ሆነ? 3:01 ማታ።
አሁን ትነቃለች ደህና አደርክ ልትል!
ጥርሶቿ ድንበር ላይ መንገድ ይዘረጋል
ፍጥረት ተጠራርቶ ወዳሻው ይሄዳል
በደህና አደርኳ ላይ
ደልቶት ይራመዳል ልክ እንደስጋጃ
እሷ ካልነቃች ግን አኳዃኑን እንጃ።
ማወቅ ይጀምራል ነፍሴ አቅጣጫውን
መውረጃ መውጫውን!
አነቃቋ ብቻ ከግብ ያገናኛል
ከሕልም ያገናኛል
ተራመድ ይለኛል
ያደርገኛል ፈቀቅ
ዐለም አይታይም
ዐይኖቿን ሳትገልጥ አፏ ሳይላቀቅ።
(ስትገልጥ ብርሀን ስትጨፍን ጨለማ
ዐይኔን አስሮ ካደው ካይኖቿ ከተማ)
በፍጥነት መራመድ ያምረዋል ጉልበቴ
ከንፈሮቿ ግርጌ ካሉት ጎዳናዎች
ካሉት ኮረብታዎች መመላለስ ባንዱ
እንዲህ ያጎብዛል
ደህና አደርክ ስትል የመንቃቷ ክንዱ።
እስኪ አሁን ስንት ሰዓት ነው? 3:02 ማታ።
አሁን ትነቃለች ደህና አደርክ ልትል!
ከርቤ ይሸተኛል
እጣን ይሸተኛል ቀረፋ ቀረፋ
መልካሙን መአዛ ደርድራለች ባፏ።
ካፏ ይመነጫል ውብ ሽቱ ውብ ጠረን
ሎሚ ሎሚ የሚል ያስመራ የከረን
ሮዝ ሮዝ የሚል አጸድ እንደሳሮን
ማእጠንት አላት ባፏ የሚያሳምር ኑሮን
አደይ አደይ የሚል መስከረም መስከረም
እሱን አንዴ አሽትቶ ለዘላለም መክረም።
ምን ያለች ጽህና ናት!
የአበባ መደብ
የሽቱ ሸለቆ የሽቱ ኮረብታ
መአዛ ምትለግስ ቃል ብቻ ቀብታ!
በከንፈሯ ፍሬ አምሮ የታነጸው
ገላዬ ያውዳል የንጋትን መጸው!
መቼ? ደህና አደርክ ስትል!
ሰዐቱ ስንት ሆነ? 3:03 ማታ!
ግዴለም!
አሁን ትነቃለች ደህና አደርክ ልትል!
ጨረቃና ጸሐይ
የምን መጋፋት ነው በሉ ስርአት ያዙ
ጨለማና ብርሃን
ሚሸጋገርበት አፏ ላይ ነው ጠርዙ።
እሷ ሳታወራ እሷ ሳትናገር
ምሽቱ ተሸኘ ነጋ ብሎ ነገር
ውሸት ነው ሀሰት ነው!
ስትነቃ ስትነቃ
አዲስ አዲስ ፀሐይ አዲስ አዲስ ጀንበር
ባፏ በር በቃል በር
ይወጣል ቀን በቀን
እሷ ናት አፏ ነው የተፈጥሮ ሕጓ
ማለዳ ይባላል የመናገር ጥጓ።
ብዙ ብርሃን አላት
ደህና አደርክ ስትል ምናለ ሚደበቅ
ብቻ የኔ ሥራ
ሺህ ፀሐይ ለማየት አንድ አፏን መጠበቅ!
ሰዓቱ ስንት ሆነ? 3:04 ማታ!
አሁን ትነቃለች ደህና አደርክ ልትል!
እውቀት ጥበብ ብልሃት
ከሰሎሞን አፏ ባንድ ሐረግ ይጎርፋል
አላዋቂ አካል
አዋቂ ከንፈሯን መ'ቶ ይደገፋል።
ይሰብካል ሰባኪ ትርጉም በመዘርዘር
ያዜማል ዜመኛ
ይሥላል ሠዐሊ
ገጣሚው ይቀኛል ነክቶት የጥበብ ዘር።
ደህና አደርክ ባይ አጥቶ
ያገኘውን ሁሉ
"ከንቱ ነው" ይል ነበር ጠቢብ አንድ ሰሞን
እውነተኛ ጥበብ
እውነተኛ ጠቢብ አፏ ነው ሰሎሞን።
ደርሶ በጥበብ ስም
እንዴትም ቢጠበብ
ፈራጅ ነው ተብሎ ምን ባይከሰስም
ዐለም የሆነ አፏ ዐለም አያረክስም።
ስሙን እየጠራሁ
በያንዳንዱ ነገር ያሰኘኛል መማል
ደህና አደርክ ስትል
የረከሰው ሁሉ ውድ ሆኖ ይቆማል።
አሁን ስንት ሰዓት ነው? 3:05 ማታ!
አሁን ትነቃለች ደህና አደርክ ልትል!
ንጋት ግን ቅርብ ነው
እሷን እያለሙ እሷን እያሰቡ
ባቆመችው ዐለም በቁም ካሸለቡ።
ደህና አደርክ ስትል
ምን እውቀት
ምን ጥበብ ምን ግጥም ይተርፈኝ?
ቅዠቷ ብቻ አይደል ይኼንን ያጻፈኝ?!
[ ያዴል ትዕዛዙ ]
@yourpoim
@yourpoim
ሙዚቃ ቤት ጀርባ
ግማሽ የደረሰ ሲጃራ እንደያዘች
.
ተክዛ አገኘኋት
ምን ሁነሽ ነው ሳልል ፤ አብሬያት ተከዝኩኝ ፤
ሃዘን ተርፏት ነበር ፣ እንባ ተበደርኩኝ ፣
እናልቅስ አለችኝ
«እሺ» እናልቅስ አልኳት
ጭኗን አንተርሳኝ
እንባዋን አጉርሳኝ
ዝም ብየ አለቀስኩኝ
ዝም ብላ አለቀሰች
እኔም ሃዘን ነካኝ ፣ እሷም ሰው መሰለች ።
ትንሽ እንዳለቀስን
የተበደርኩትን እንባ ሳልጨርሰው
ፊቴን አደራርቃ
ጉንጨ ጫፍ ሳመችኝ ፣
በቃ ተው አታልቅስ ፣ ብላ አባበለችኝ ፣
እንዝፈን አለችኝ ?
እንደንስ አለችኝ ?
ቢራ እንጠጣ አለችኝ ?
«እሺ» እንዝፈን አለኳት
«እሺ» እንደንስ አልኳት
እኔን የትም ትቼ ፣ እሷን ተከተልኳት ፣
.
አብረን ያለቀስነው ፣ እንባ እስከሚጎድል ፣
ተቃቅፈን ዘፈነው
የሕይወትን እጣ ፣ የሕይወትን ዕድል ።
.
ሃዘኑ ሲበቃት
ዘፈኑ ሲበቃኝ
ደህና እደሪ ብያት ፣ ከሄድኩኝ በኋላ ፣
ሃዘን እወዳለሁ ፣ ደስታ ነው 'ምጠላ ፣
.
አሁን ላይ ብቻየን
እኔም ልክ እንደ እርሷ ...!
ሃዘን በሹል ጥፍሩ
እንባ በእሳት ጅራፍ ፣ ሲገርፈኝ እንደሰው ፣
የተበደርኩትን ፣ እንባ ነው ማለቅሰው ።
[ ሶሎሞን ሽፈራው ]
@yourpoim
@yourpoim
