en
Feedback
ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

Open in Telegram
2 837
Subscribers
-124 hours
-37 days
-830 days
Posts Archive
መልእክተ ሰንበት ጴጥሮስ በእምነታቸው አማካኝነት የተበተኑትን እያጽናና በመልካም አኗኗር እንዲኖሩ ያበረታታል። ቀጥሎም ከመዝሙር በመጥቀስ ያሳስባል፤ “ሕይወትን የሚወድድ፣ መልካም ቀኖችን ሊያይ የሚፈልግ፣ ምላሱን ከክፉ፣ ከንፈሮቹንም ተንኰል ከመናገር ይከልክል" (1ጴጥ 3፥10)። መከራ ቢኖርም ተስፋ አለ፤ ስለዚህ ጥንቃቄ ያለበት ዝግጅት ያስፈልጋል። ክፉ ንግግር መልካም ቀንን (ብርሃንን) አያመጣም። የተሻለውን የሚፈልጉም፣ የቀለለውን በመተው ይታወቃሉ።

መልእክተ ቅዳሜ ቃል በእውነት ሲሞላ መልካም ፍሬ ይታያል። በጥበብ ሲሟሽ ደግሞ መድኀኒት (ፍቱን) ይሆናል። ይህም ቃል እንደየአድማጩ ሲቃኝ ነው፤ "ለእያንዳንዱ ሰው እንዴት መልስ መስጠት እንደሚገባችሁ ታውቁ ዘንድ ንግግራችሁ በጨው እንደ ተቀመመ ሁልጊዜ በጸጋ የተሞላ ይሁን" (ቈላ 4፥6)። "እያንዳንዱ" እና "ሁልጊዜ" የሚሉት ቃላት ትኩረት የሚደረግባቸው፣ ለቃል መጠንቀቅም ፈጽሞ ቸል ሊባል የማይችል ለመሆኑ አመልካች ነው። ቃል በጸጋ ሲሞላም፣ ከውጤት አይጎድልም።

የዕለቱ ሐሳብ ቃል ኅይል አለው። ሰዎች በንግግራቸው ይወከላሉ፤ ከዚያም አልፈው ግን ይወሰናሉ፤ የሚናግሩትን ይሆናሉና። ጠቢቡ ሰሎሞን፣ በጥበብ ንግግሩ መካከል እንዲህ አለ፤ "አንደበት የሞትና የሕይወት ኀይል አላት፤ የሚወድዷትም ፍሬዋን ይበላሉ" (ምሳ 18፥21)። ሔዋን በቃል ተሳበች፤ በቃሏም ተያዘች። 'በልብ የሞላ በአፍ' እንደ ተባለ፣ ቃል ልብን እያስከተለና ሕይወትና ሞትን እያማረጠ ኖሯል። አንደበተቻቸውን የሚወድዱም ዝግጅቷን ይከታተላሉ፤ መልካም እርሻ እንደሚታረም ቃላቸውን 'ከአጨዳ' (ከንግግር) በፊት ያርማሉ። የገዛ ቃላቸውን ከቆይታ በኋላ የሚጠሉ እንዳሉ ሁሉ፣ በአንደበታቸው ፍሬ ደስ የሚሰኙ ብዙ ናቸው።

የዕለቱ ቃል "አንደበት የሞትና የሕይወት ኀይል አላት፤ የሚወድዷትም ፍሬዋን ይበላሉ።" (ምሳ 18፥21 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ የሰው ቃል በእግዚአብሔር ቃል ላይ ሲያርፍ፣ በቃሉ ይገራል፤ ይሟሻል፤ ይበለጽጋልም—ያፈራል። የቆሬ ልጆች እንዲህ ብለው ተቀኙ፤ "አፌ የጥበብን ቃል ይናገራል፤ የልቤም ሐሳብ ማስተዋልን ይሰጣል" (መዝ 49፥3)። በከበባ መካከል ቢሆኑም፣ በእግዚአብሔር ስለ ታመኑ ልባቸው አስተዋለ፣ ቃላቸውም ጥበብን ገለጠ። ሕይወት አጭር፣ ባለጠግነትም አላፊ እንደ ሆነ ተቀኙ፤ እግዚአብሔር ደግሞ ከሲዖል የሚታደግ ስለ መሆኑ መሰከሩ። ሰዎች በእግዚአብሔር ካልታመኑ በቀር ልባቸው ይከብዳል፤ ዑደቱ ይቀንሳል፤ አቅም ይከዳል። ያረፈ ልብ ግን ጥበብን ያመነጫል። ልብም ለአንደበት ይቀርባል፤ እርስ በርስ ይስማማል።

የዕለቱ ቃል "አፌ የጥበብን ቃል ይናገራል፤ የልቤም ሐሳብ ማስተዋልን ይሰጣል።" (መዝ 49፥3 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ አንዳንድ ጸሎት የብዙ ጊዜ ጥረትን ይከተላል። ሞክረው ያልቻሉትን እገዛ ይጠይቁበታል። ዘማሪው የገዛ አንደበትን መቆጣጠር እንደማይቻል ሲገነዘብ፣ አምላኩን ተማጸነ፤ "ዐለቴና አዳኜ እግዚአብሔር ሆይ፤ የአፌ ቃልና የልቤ ሐሳብ፣ በፊትህ ያማረ ይሁን" (መዝ 19፥14)። ልብ አንደበትን ይገራል። ሐሳብ ሲጠል ነገር ያጥራል፤ ይጠላልም። እግዚአብሔር ደግሞ በተጠራበት ሁሉ ይገኛል። ለሚማጸኑትም ዐለትና ረዳት ነው። እነርሱም ባማረላቸው አንደበት ያከብሩታል።

የዕለቱ ቃል "ዐለቴና አዳኜ እግዚአብሔር ሆይ፤ የአፌ ቃልና የልቤ ሐሳብ፣ በፊትህ ያማረ ይሁን።" (መዝ 19፥14 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ ቃልና ምራቅ አንድ ነው፤ ወይ ይዋጣል፣ አልያም ይወጣል። በእግዚአብሔር ወይም ስለ አግዚአብሔር የተናገሩት ሲሆን ደግሞ ወዲያው ይሰማል፤ (ሳይወጣ ገና ታውቋልና፤) ኢዮብ ከጥልቅና ሰፊው መከራ የተነሣ ብዙ ተናገረ፤ የሚያውቀውንም የማያውቀውንም ገለጠ። መስማቱ የማይታወቀውና ሩቅ የሚመስለው እግዚአብሔርም 'ተራው ሲደርስ' መናገር ጀመረ። ከፍጥረቱና ከሥራው አንሥቶም ኅይሉንና ጥበቡን ገለጠ። ኢዮብም እንዲህ አለ፤ "እኔ ከንቱ ሰው፣ ምን እመልስልሃለሁ? እጄን በአፌ ላይ እጭናለሁ። አንድ ጊዜ ተናገርሁ፤ የምመልሰው የለኝም፤ ሁለተኛም ተናገርሁ፤ ከእንግዲህ አንዳች አልጨምርም" (40፥4-5)። ይህ ከንቱነት ከማጣት—ያለውን ሁሉ ስላጣ—ወይም ከጤና ጉድለት የመጣ አይደለም፤ ካለማወቅ፣ ፈጥኖ ከመናገርና ሳይለዩ ከማውራት የሚመጣ እን። ሰው ሁሉም ለዚህ ከንቱነት ተዳርጓል፤ ካልሰማና ካልተማራ ብዙ ይናገራል፤ ያለ ዕውቀትም ቃላት ያበዛል። በእግዚአብሔር ፊት ዝም ማለትም ኩርፊያ አይደለም፤ አዋቂ አድማጭ መሆን፣ አልፎም መቅረብ ነው።

የዕለቱ ቃል "እኔ ከንቱ ሰው፣ ምን እመልስልሃለሁ? እጄን በአፌ ላይ እጭናለሁ። አንድ ጊዜ ተናገርሁ፤ የምመልሰው የለኝም፤ ሁለተኛም ተናገርሁ፤ ከእንግዲህ አንዳች አልጨምርም።" (ኢዮ 40፥4-5 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ የሕጉ ርዝመት ከጆሮ እስከ አንደበት ነው። የሰሙትን የሚያምኑም የሚናገሩትን ይኖራሉ። እግዚአብሔር ብርቱውን ጦረኛ ኢያሱን እንዲህ አለው፤ "ይህ የሕግ መጽሐፍ ከአፍህ አይለይ" (1፥3)። ጌታ አምላክ ቃሉ ላይ አለ። ቃሉን የሚጠሩም የስሙን ያህል በሕልውናው ይገናኙታል። ይህን ቃል 'ከሐሳባቸው የማይለዩም' ክንውናቸውን የሚጀምሩ ብቻ ሳይሆን፣ የሚጨርሱም ናቸው።

የዕለቱ ቃል "ይህ የሕግ መጽሐፍ ከአፍህ አይለይ፤" (ኢያ 1፥8 አመት)።

የዕለቱ ቃል "ይህ የሕግ መጽሐፍ ከአፍህ አይለይ፤ በውስጡ የተጻፈውን ሁሉ በጥንቃቄ እንድትፈጽመውም ቀንም ሆነ ሌት ከሐሳብህ አትለየው፤ ይህን ካደረግህ ያሰብኸው ይቃናል፤ ይሳካልም፤" (ኢያ 1፥8 አመት)

መልእክተ ሰንበት የሚገረዙ ቅርንጫፎች ፍሬ የሚያፈሩ ናቸው። እነዚህም ቅርንጫፎች በተክሉ ላይ የበቀሉ የጌታ ሰዎች ናቸው። አጵሎስ አንዱ ነበር። እርሱም ቅዱሳት መጻሕፍትን ጠንቅቆ የሚያውቅና በመንፈስ ግለት ስለ ጌታ የሚመሰክር ሰው ነበር፤ "እርሱም በምኵራብ በድፍረት ይናገር ጀመር፤ ጵርስቅላና አቂላም በሰሙት ጊዜ፣ ወደ ቤታቸው ወስደው የእግዚአብሔርን መንገድ ይበልጥ አስተካክለው አስረዱት" (ሐሥ 18፥26)። ጵርስቅላ ከባሏ ከአቂላ ጋራ ሆና አቀናችው። የስኬቱ መጠን ለነርሱ የአድናቆት ምክንያት አልሆነም። የሞላውን ያዩትን ያህል፣ የጎደለውንም ተመለከቱ። "የእግዚአብሔርን መንገድ" እንዳያረዝም ወይም ጎርባጣ እንዳያደርግ አቀኑት። ሴቷም ወንዱም "አስረዱት"። እውነት አንድ ምንጭ እንጂ አንድ ፆታ የላትም።

መልእክተ ቅዳሜ የጳውሎስ የአውሮጳ ጉዞ የተለያዩ ቦታዎችን ያካለለበት ብቻ ሳይሆን ብዙ ዐይነት ሰዎችንም ያገኘበት ነበር። በፊልጵስዪስ ከተማ በገበያ ስፍራ በተገኙ ጊዜ፣ "ከሚያዳምጡትም ሴቶች መካከል ልድያ የምትባል አንዲት ሴት ነበረች፤ እርሷም እግዚአብሔርን የምታመልክና ከትያጥሮን ከተማ የመጣች የቀይ ሐር ነጋዴ ነበረች። ጌታም፣ ጳውሎስ የሚናገረውን በማስተዋል ትሰማ ዘንድ ልቧን ከፈተላት" (ሐሥ 16፥14)። ከዚያም በቤትዋ ተቀብላ አስተናገደቻቸው። ልቧ ለቃሉ ሲከፈት ቤቷ (ኑሮዋ) ለቃሉ አገልጋዮች ተከፈተ። የልቧ ዝግጁ መሆንም ለተማው ተጽዕኖ ፈጣሪ አደረጋት።

የዕለቱ ሐሳብ ማርታና ማርያም የቅርበታቸውን ያህል ስለ ጌታ የነበራቸው መረዳት አንድ ዐይነት አልነበረም። ማርታ አቀባበሏና መስተንግዶዋ ግሩም ቢሆንም፣ ምርጫዋ ግን እንከን ነበረበት። ጌታን አስቀምጣ የስሜት መደፍረስ ውስጥ በገባች ጊዜ እንዲህ ተባለች፤ "የሚያስፈልገው ግን አንድ ነገር ብቻ ነው፤ ማርያም እኮ መልካሙን ድርሻ መርጣለች፤ ይህም ከርሷ አይወሰድም” (ሉቃ10፥42)። እርሷ ለሥራ ስትርቅ፣ ማርያም ግን ለመስማት ቀረበች። ድርሻዋ "መልካም" ብቻ ሳይሆን ዘላቂም ሆነ። መስማት መስጠትን (መሰጠትንም) ሲቀድም፣ ግሩም መሥዋዕት ይሆናል!

የዕለቱ ቃል "የሚያስፈልገው ግን አንድ ነገር ብቻ ነው፤ ማርያም እኮ መልካሙን ድርሻ መርጣለች፤ ይህም ከርሷ አይወሰድም።” (ሉቃ10፥42 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ እግዚአብሔር ኀያል፣ ስሙም ቅዱስ ነው። የቀረቡት ይህንን ይረዳሉ፤ ይቀኙለታልም። ማርያም በውዳሴዋ ይህንኑ አቀረበች፤ "ኀያል የሆነው እርሱ ታላቅ ነገር አድርጎልኛልና፤ ስሙም ቅዱስ ነው፤ ምሕረቱም ለሚፈሩት ከትውልድ እስከ ትውልድ ይኖራል" (ሉቃ 1፥49-50)። አምላኳን ይዛ (በማሕፀኗ)፣ አምላኳን ባረከች። እግዚአብሔርን ከሚፈራ ትውልድ ወጥታ የጽድቅ ትውልድ አስቀጠለች። የምሕረቱን ስፋት አስቀጠለች።

የዕለቱ ቃል "ኀያል የሆነው እርሱ ታላቅ ነገር አድርጎልኛልና፤ ስሙም ቅዱስ ነው፤ ምሕረቱም ለሚፈሩት ከትውልድ እስከ ትውልድ ይኖራል።" (ሉቃ 1፥49-50 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ በእግዚአብሔር የታሰቡ፣ እግዚአብሔርን ያስባሉ። መክበር ለማክበር፣ መጎብኘትም ለውዳሴ ያበቃል። ኤልዛቤል ማርያምን ለመገናኘት በቀረበች ጊዜና ድምፅዋን ስትሰማ በሆዷ የነበረው ጽንስ ዘለለ፤ በመንፈስም ተሞላች። ማርያምም ቀጥላ እንዲህ አለች፤ "ነፍሴ ጌታን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች፤ መንፈሴም በመድኀኒቴ በእግዚአብሔር ደስ ትሠኛለች" (ሉቃ 1፥46-47)። ከነፍስ የሆነ ምስጋና፣ ከመንፈስም የሆነ አምልኮ አቀረበች። በመድኀኒቷ ደስ ስለ ተሰች ምስጋና አቀረበች። በውዳሴዋ ደስታዋን አበዛች።