uz
Feedback
ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

ቢብሊካ ኢትዮጵያ (Biblica Ethiopia)

Kanalga Telegram’da o‘tish
2 858
Obunachilar
Ma'lumot yo'q24 soatlar
+17 kunlar
+130 kunlar
Postlar arxiv
የዕለቱ ሐሳብ የእግዚአብሔር ምሕረት አቃፊ ነው—ምሕረቱ ያስጠጋል፤ ያስቀርባል። እርሱ 'ይቅር ብዬአቸው እዚያወረ ባሉበት ልገላገላቸው' አይልም፤ "ነገር ግን በምሕረቱ ባለጠጋ የሆነ እግዚአብሔር ለእኛ ካለው ከታላቅ ፍቅሩ የተነሣ፣ በበደላችን ሙታን ሆነን ሳለ፣ በክርስቶስ ሕያዋን አደረገን፤ የዳናችሁት በጸጋ ነው" (ኤፌ 2፥4-5)። ስለ ወደደ ይምራል፤ ፍቅሩ ጥልቅ ስለሆነም ምሕረት በማድረግ አይሰላችም። ፍቅር ሲጎድል መማር ከባድ ይሆናል። እርሱ ራሱ ፍቅር ስልሆነ ግን፣ ከፍቅር ጎድሎ አያውቅም። የምሕረቱ ባለጠግነትም ከርሱ ጋራ አቆይቶናል።

የዕለቱ ቃል "ነገር ግን በምሕረቱ ባለጠጋ የሆነ እግዚአብሔር ለእኛ ካለው ከታላቅ ፍቅሩ የተነሣ፣ በበደላችን ሙታን ሆነን ሳለ፣ በክርስቶስ ሕያዋን አደረገን፤ የዳናችሁት በጸጋ ነው።" (ኤፌ 2፥4-5 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ ምሕረት በነጻ ቢሰጥም ዋጋው ትሕትናና ራስን ማዋረድ ነው። እግዚአብሔር ከልቡ ይናገራል፤ ሰዎችም ከልባቸው እንዲገናኙት ይፈልጋል። ነቢዩ ኢዩኤል እንዲህ አለ፤ "ልባችሁን እንጂ፣ ልብሳችሁን አትቅደዱ፤ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ፤ እርሱ መሓሪና ርኅሩኅ፣ ቍጣው የዘገየና ፍቅሩ የበዛ፣ ክፉ ነገር ከማምጣትም የሚታገሥ ነውና" (ኢዩ 2፥13)። ከቍጣው ይልቅ ፍቅሩን፣ ከቅጣቱ ይልቅም ባርኮቱን የሚፈልጉ የሆኑትን ይዘው መሆን የሚፈልጉትን እንዲሆኑ ራሳቸውን በፊቱ ሊያዋርዱ ይገባል። እርሱ እየራራ ይምራልና።

የዕለቱ ቃል "ልባችሁን እንጂ፣ ልብሳችሁን አትቅደዱ፤ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ፤ እርሱ መሓሪና ርኅሩኅ፣ ቍጣው የዘገየና ፍቅሩ የበዛ፣ ክፉ ነገር ከማምጣትም የሚታገሥ ነውና።" (ኢዩ 2፥13 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ አንዳንድ ሰዎች፣ 'ግሩም እንግዳ ተቀባዮች ናቸው' ይባላሉ። ፊታቸውን ያላቸውን ከማቅረብ ጋራ ያስማማሉ። እንግዶቻቸው ካሰዘኗቸው ግን ፊታቸውን ያጠቁራሉ። እግዚአብሔር ግን ሲያስተናግደን ምሕረቱን አስቀድሞ ነው። ዳዊት ሰው መሆኑንና ታሪኩን እያሰበ እንዲህ አለ፤ "ጌታ ሆይ፤ አንተ ግን መሓሪና ርኅሩኅ አምላክ ነህ፤ ለቍጣ የዘገየህ፣ ምሕረትህና ታማኝነትህ የበዛ" (መዝ 86፥15)። "ለሚጠሩት ሁሉ" ወሰን የሌለውን ምሕረቱን እያሰበ ተቀኘ። 'ፊቱን እንዴት አያለሁ?' ለሚሉ ቁጣውን ከምሕረቱ ኋላ እንደሚያሰልፍ ገለጠ። ጻድቁ አምላክ መሓሪ ሆኖ ቀደመ።

የዕለቱ ቃል "ጌታ ሆይ፤ አንተ ግን መሓሪና ርኅሩኅ አምላክ ነህ፤ ለቍጣ የዘገየህ፣ ምሕረትህና ታማኝነትህ የበዛ።" (መዝ 86፥15 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ የእግዚአብሔር ትእዛዝ ባሕርይው ላይ ይመሠረታል። እርሱ ይመክራል፤ ያሳስባል፤ ያስጠነቅቃል። ሕዝቡ ትእዛዙን ከረሳና በደል ከበደለ ግን፣ ይቆጣል። ግን ደግሞ ይመለሳል። ሙሴም ይህንኑ ከነዓን ለሚገባው አዲሱ ትውልድ አሳወቀ፤ "አምላክህ እግዚአብሔር መሓሪ አምላክ ነውና አይተውህም ወይም አያጠፋህም፤ ወይም ደግሞ ለአባቶችህ በመሐላ ያጸናላቸውን ቃል ኪዳን አይረሳም" (ዘዳ 4፣31)። 'በደልን የማይከታተል'—መዝግቦ የማይሰንድ—አምላክ ስለሆነ ምልስ ነው። ይምራል፤ ኪዳኑንም ምሕረቱ ሥር ያስገባል። የኪዳን ተላላፊዎቹን በደልም ያሳልፋል።

የዕለቱ ቃል "አምላክህ እግዚአብሔር መሓሪ አምላክ ነውና አይተውህም ወይም አያጠፋህም፤ ወይም ደግሞ ለአባቶችህ በመሐላ ያጸናላቸውን ቃል ኪዳን አይረሳም።" (ዘዳ 4፣31 አመት)

መልእክተ ሰንበት የእግዚአብሔር ሥራ አያልቅም፣ ተልዕኮ (የተሰፈረ ሥራ) ግን ይጠናቀቃል። ጳውሎስ ያለ ዕውቀት በቅንዐት ብቻ ሮጠ፤ ክርስቲያኖችንም አሳደደ። በከንቱ ሩጫው መካከል በደማስቆም ጌታ አቋረጠው። ከዚያ ጊዜ ጀምሮ ወደ ኋላ አላለም፤ "መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ፤ ሩጫውን ጨርሻለሁ፤ ሃይማኖትንም ጠብቄአለሁ" (2ጢሞ4፥7)። ጌታውን ካወቀ በኋላ የሩጫውን ዐይነት ለወጠ። እስከ ፍጻሜውም ሄደ፤ ተልዕኮውንም ጨርሶ አስረከበ። አክሊሉን እያሰበም ከምድር መለየቱን እንደ ሽኝት ቄጠረ።

መልእክተ ቅዳሜ ምሕረት ያገኙ ዕፎይ ይላሉ። ምንም ሳይገባቸው እንደ ተማሩ የገባቸውም ውለታ የማይረሱ ናቸው። የምሕረት አምላክ የሆነው እግዚአብሔር በራሱ (ሳይገባን) ታረቀን። ዕርቁን ከሰላም ጋራ ቸረን፤ "ስለዚህ እኛ የክርስቶስ እንደራሴዎች ነን፤ እግዚአብሔርም በእኛ አማካይነት ጥሪውን ያቀርባል፤ እኛም ከእግዚአብሔር ጋራ ታረቁ ብለን በክርስቶስ እንለምናችኋለን" (2ቆሮ 5፥20)። ስለዚህም፣ የዕርቁን ተልዕኮ ይዘን እናሰፋለን፤ ሰዎችን ወደ ምሕረት እናቀርባለን።

የዕለቱ ሐሳብ የተላከ የታጠቀ ሲሆን፣ ተልዕኮ ይደርሳል፤ ውጤትም ይመጣል። ጌታ ሁሉን ፈጽሞ ምድርን ሊለቅ ሲል ደቀ መዛሙርቱን እንዲህ አላቸው፤ "ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በሚወርድበት ጊዜ ኀይልን ትቀበላላችሁ፤ በኢየሩሳሌም፣ በይሁዳና በሰማርያ ሁሉ፣ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ" (ሐሥ 1፥8)። ሰማያዊውን ተልዕኮ ሰማያዊው አቅም ያስችለዋል። እግዚአብሔር-መንፈስ ኀይል ብቻ ሳይሆን የሥራው ባለቤትም ነው። አቅም ሆኖም ብቻ ሳይሆን ፈቃድ ይዞ ወርዷል። ያስታጠቃቸውንም ይመራል፤ ይቀድሳል፤ ያስችላል።

የዕለቱ ቃል "ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ በእናንተ ላይ በሚወርድበት ጊዜ ኀይልን ትቀበላላችሁ፤ በኢየሩሳሌም፣ በይሁዳና በሰማርያ ሁሉ፣ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስ ምስክሮቼ ትሆናላችሁ።" (ሐሥ 1፥8 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ ጌታ ኢየሱስ ለሰው ልጆች ከሞተና ከተነሣ በኋላ ተልዕኮውን አጸናው፤ "ሰላም ለእናንተ ይሁን! አብ እኔን እንደ ላከኝ፣ እኔም እናንተን እልካችኋለሁ" (ዮሐ 20፥21)። ተልዕኮው ሰላሙን የተከተለ ነው። የእግዚአብሔር ሕዝብ ሰላሙን ለራሱ ብቻ ይዞ የሚቀመጥ ሊሆን አይገባም። ሌሎችም ይህንን የነፍስ ሰላም ሊያውቁትና ሊካፈሉት ይገባል፤ ያን ጊዜ የሰላም ወሰን ይሰፋል። ዐመፃ ወሰን እያሰፋ ሰላምን እንዳያደፈርስ፣ መለኮታዊው ሰላም በሰማያዊው ተልዕኮ ሁሉን ሊያዳርስ ይገባል። የተላኩም ሰላማቸውን ይዘው ይሄዳሉ፤ ሰላምንም ይካፈላሉ።

የዕለቱ ቃል "ኢየሱስም እንደ ገና፣ 'ሰላም ለእናንተ ይሁን! አብ እኔን እንደ ላከኝ፣ እኔም እናንተን እልካችኋለሁ' አላቸው።" (ዮሐ 20፥21 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ የተላኩ ስፍራ አይመርጡም፤ ተልዕኮው ነው ስፍራቸውን የሚውስንላቸው። ጌታ ወደ ዘኬዎስ በቀረበ ጊዜ፣ "ዛሬ አንተ ቤት መዋል ይገባኛልና ፈጥነህ ውረድ" አለው። የቀራጮች (ኅጢአተኞች) "ዋና" ሰው ነበር። ከሰበሰበው ገንዘብ በላይ የሚሆን ሕይወት እንዳለ ስለ ተረዳ ፍለጋውን አሳደገ—ዛፉ ላይ ወጣ። ጌታም በርሱ ቤት መዋል ስለ ተገባው 'አስወረደው'። እርሱም ከሀብቱና በደሉ ወረደ፤ ተግባራዊ ጸጸት ገለጠ። ጌታም እንዲህ አለ፤ "ይህ ሰው ደግሞ የአብርሃም ልጅ ስለ ሆነ፣ ዛሬ መዳን ወደዚህ ቤት መጥቷል፤ ምክንያቱም የሰው ልጅ የመጣው የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን ነው" (ሉቃ 19፥9-10)። ጠፍተው የተገኙቱ መሰማሪያ ሲያገኙ ደግሞ፣ ፍለጋውን ይቀላቀላሉ፤ እነርሱ መድኃኒታቸው በሆነው ጌታቸው እንዳረፉ ሌሎችን 'ዕረፉ!' ይላሉ።

የዕለቱ ቃል "...ይህ ሰው ደግሞ የአብርሃም ልጅ ስለ ሆነ፣ ዛሬ መዳን ወደዚህ ቤት መጥቷል፤ ምክንያቱም የሰው ልጅ የመጣው የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን ነው።" (ሉቃ 19፥9-10 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ ነቢዪ ኢሳይያስ የእግዘብሔርን ቃል እየተናገረ በነበረበት ጊዜ ራእይ አየ። የሚያገለግለውን አምላክ ክብር ከተመለከተ በኋላ ራሱን አዋረደ፤ "ወዮልኝ" አለ፤ "ከዚያም የጌታ ድምፅ፣ 'ማንን እልካለሁ? ማንስ ይሄድልናል?' ሲል ሰማሁት። እኔም፣ 'እነሆኝ፤ እኔን ላከኝ!' አልሁ" (ኢሳ 6፥8)። ጥሪው ከመለኮት ክብር በኋላ እንደ ገና መጣ። ኢሳይያስም "እነሆኝ" አለ። አሁንም፣ "ማንስ ይሄድልናል?" የሚለው ድምፅ ያስተጋባል።

የዕለቱ ቃል "ከዚያም የጌታ ድምፅ፣ 'ማንን እልካለሁ? ማንስ ይሄድልናል?' ሲል ሰማሁት። እኔም፣ 'እነሆኝ፤ እኔን ላከኝ!' አልሁ።" (ኢሳ 6፥8 አመት)

የዕለቱ ሐሳብ ሰማያዊ ጥሪ ሰማይን እንጂ ምድርን አያማክልም። እግዚአብሔር አብራምን በ75 ዓመቱ ጠራው፤ ሕዝብም እንደሚያደርገው ነገረው፤ "ከአገርህ ከወገንህ ተለይተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ። ታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁ፤ ደግሞም እባርክሃለሁ፤ ስምህን ገናና አደርገዋለሁ፤ ለሌሎች በረከት ትሆናለህ" (ዘፍ 12፥1-2)። አብራም ገና ያለ ልጅ ቢሆንም፣ "ታላቅ ሕዝብ" ትሆናለህ ተባለ። ጠሪው ሲጠራ፣ ራሱን እንጂ ተጠሪውን አያይም። ጥሪውም ከተጠሪው ይልቅ ጠሪውን ይመስላል።

የዕለቱ ቃል "እግዚአብሔር አብራምን እንዲህ አለው፤ 'ከአገርህ ከወገንህ ተለይተህ እኔ ወደማሳይህ ምድር ሂድ። ታላቅ ሕዝብ አደርግሃለሁ፤ ደግሞም እባርክሃለሁ፤ ስምህን ገናና አደርገዋለሁ፤ ለሌሎች በረከት ትሆናለህ።'" (ዘፍ 12፥1-2 አመት)