ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Open in Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Show more637
Subscribers
-124 hours
-47 days
-1230 days
Posts Archive
❤ ሌሎችም ከአገረ ፍዩም የጎልማሳውን ሥጋ ሰርቀው ወደ ፍዩም አገር ሲአደርሱት የእግዚአብሔር መልአክ ነጥቆ ወደ አባቱ ሥጋ መለሰው መነኰሳቱም ብዙ ጊዜ ፈተኑት የወጣቱን ሥጋ ከአባቱ ሥጋ የሚለዩት ሁነው ነበር። በጥዋትም በአንድነት ያገኙአቸዋል ከመነኰሳቱም አንዱ እንዲህ የሚለውን እስኪያይና እስከሚሰማ ድረስ። "ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛ በሕይወተ ሥጋ ሳለን እርስበርሳችን አልተለያየንም በጌታችን ክርስቶስም ዘንድ አልተለያየንም እናንተ እርስ በርሳችን ለምን ትለያዩናላችሁ" ከዚያችም ቀን ወዲህ የለያቸው የለም።
❤ አረማውያንም የአስቄጥስን ገዳም በአጠፉ ጊዜ ስለ ቅዱሳን ሰማዕታት ሥጋ መነኰሳቱ ፈሩ ከቦታቸውም አፍልሰው ወስደው በከበረ አባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን ጎን አኖሩዋቸው የመቃብር ቦታም ሠሩላቸው በላዩም ሊቀ ጳጳሳት ታውዳስዮስ ዘመን በስማቸው ቤተ ክርስቲያን ሠሩላቸው። ሊቀ ጳጳሳት አባ ብንያሚንም ወደ አስቄጥስ ገዳም በመጣ ጊዜ የካቲት አምስት ቀን እንዲከበር በዓልን ሠራላቸው ይኸውም ሥጋቸው የተገለጠበት ነው ቤተ ክርስቲያናቸውም እስከ ዛሬ አለች በቅብጢ ቋንቋ ብህም ብሲት በመባል የታወቀች ናት ይህም አርባ ዘጠኝ ማለት ነው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 26 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ "#ሰላም_ለክሙ_ሱቱፋነ_ፃማ_ወሕማም። አርብዓ ወተሰዓቱ አእሩገ ገዳም። ምስለ ላእከ ንጉሥ ወወልዱ ዘተከልክሙ ዮም። #ለአንስጣስያ_ቅድስት ዓዲ ሰላም። ጽንዐ ወራዙት ዘሞዐት በድካም"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥር_26።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወፈርሀ ኵሉ ሰብእ። ወነገሩ ግብረ ለእግዚአብሔር። ወአእምሩ ምግባሮ"። መዝ 63፥9-10። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ቆሮ 4፥1-6፣ 1ኛ ጴጥ 1፥10-13 እና የሐዋ ሥራ 8፥18-25። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 11፥29-33። የሚቀደሰው ቅዳሴ ቅዳሴ እግዚእነ ወይም የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ። መልካም የጾም፣ የጸሎትና የምህላ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤
❤ #ጥር ፳፮ (26) ቀን።
❤ እንኳን #ከቁስጥንጥንያ_ቤተ_መንግሥት ታላላቆች ለአንዱ ልጅ ለሆነች በዋሻ ውስጥ ለብቻዋ ወንድ መስላ በመኖር ለ28 ዓመታት በታላቅ ተጋድሎ ለተጋደለች #ለታላቋ_ጻድቅ_ለቅድስት_አንስጣስያ ለዕረፍት በዓልና #ለጻድቅ_አርቃዴዎስ_ልጅ በሆነ በጻድቁ ቴዎዶስዮስ ዘመነ መንግስት #አርባ_ዘጠኝ_ለሆኑ_ለከበሩ_አረጋውያን_መነኰሳት_ከንጉሥ_መልክተኛ_ከልጁም_ጋር_ሰማዕትነት_ለተቀበሉበት_ለዕረፍታቸው በዓላቸው እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚችን ከሚታሰቡ፦ #ከከበሩ_መጥረያስ_ከስርስንዮስ ሰማዕትና #ከመፍቀሬ+ነዳያን_ከዮሴፍ ከመታሰቢያቸው ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ቅድስት_አንስጣስያ፦ ይቺም ቅድስት ከቊስጥንጥንያ ቤተ መንግሥት ታላላቆች የአንዱ ልጅ ናት። እርሷም በላይዋ በደም ግባቷ እጅግ ያማረች ናት ንጉሥ ብስጥያኖስም ሊአገባት ፈለገ እርሷ ግን ይህን በልቧ አልወደደችም የንጉሡም ሚስቱ በሕይወት ነበረች ንጉሡ እንደሚሻትም ለንግሥት ሚስቱ አስረዳቻት በዚያንም ጊዜ ንግሥቲቱ ወደ ግብጽ በመርከብ አሳፍራ በሥውር ሸኘቻት ከእስክንድርያም ከተማ ውጭ ገዳም አሠራችላት በዚያም ኖረች ያም ገዳም በስሟ ተጠራ።
❤ የከበረች አንስጣስያም በግብጽ አገር እንዳለች ንጉሥ በአወቀ ጊዜ ፈልገው ወደርሱ ያመጡአት ዘንድ መልክተኞችን ላከ ይህንንም ነገር ተረድታ ተነሣች የወንዶችንም ልብስ ለብሳ መስፍንን መሰለች ወደ አስቆጥስ ገዳም ሔዳ ወደ አበ ምኔቱ ወደ አባ ዳንኤል ገባች ምሥጢርዋን ሁሉ ገለጠችለት። እርሱም ወስዶ በዋሻ ውስጥ ለብቻዋ አኖራት እርሷም ሴት እንደሆነች ማንም አላወቀም በየሳምንቱም በእንስራ ውኃ ቀድቶ ከዚያ ዋሻ ደጃፍ እንዲያኖር አንዱን ደግ አረጋዊ አባ ዳንኤል አዘዘው ያም ሽማግሌ አያውቅም ይችም ቅድስት አንስጣስያ በጸሎት በጾምና በመስገድ በመትጋትም እየተጋደለች ሃያ ስምንት ዓመት ኖረች። ውኃ ሲቀዳላት የነበረ ያ ሽማግሌ በዐረፈ ጊዜ አባ ዳንኤልም ያ ሽማግሌ ሲሠራ እንደ ነበር ይሠራ ዘንድ ረዳቱን አዘዘው ቅድስት አንስጣስያም ሀሳቧን በገል ላይ እየጻፈች በበዓቷ ደጃፍ ታኖረው ነበር ረድኡም ወደ መምህሩ ወደ አባ ዳንኤል ይወስደዋል። የምትጽፈውንም ምን እንደሆነ አያውቅም።
❤ በአንዲት ዕለትም የጻፈችበትን ገል አመጣ አባ ዳንኤልም በአነበባት ጊዜ አለቀሰ ረድኡንም "ልጄ ሆይ ተነሥ የዚያን ቅዱስ ሰው ሥጋ ሒደን እንቅበር እርሱ ከዚህ ዓለም ይለያልና" አለው። በሔዱም ጊዜ ወደ በዓቷ ገብተው ከእርሷ ተባረኩ እርሷም አባ ዳንኤልን "አባቴ ሆይ ስለ እግዚአብሔር ብለህ በላዬ ካለው በቀር በምንም ልብስ እንዳትገንዘኝ" አለችው ከዚህም በኋላ የከበረች አንስጣስያ ተነሥታ ጸለየች "እኔ በእግዚአብሔር ዘንድ አደራ አስጠበቅኋችሁ" አለችና በምድር ላይ ተቀምጣ ዐረፈች በላይዋም አለቀሱ ሊቀብሩዋትም አስበው ረድኡ ይገንዛት ዘንድ ሲቀርብ እንደ በለስ ቅጠሎች ደርቀው ጡቶቿን ተመለከተ። ከተጋድሎ ብዛትም የተነሣ እንዲህ ሁኗልና አባ ዳንኤልም አይቶ በማድነቅ ዝም አለ።
❤ ከቀበርዋትም በኋላ ወደ በዓታቸው ተመለሱ ረድኡም ወደ አባ ዳንኤል ቀርቦ ሰገደለትና እንዲህ ሲል ለመነው "ስለ እግዚአብሔር ብለህ የዚችን ቅድስት ዜናዋን ንገረኝ ሴት እንደሆነች አይቻለሁ"። አባ ዳንኤልም የገድሏን ዜና ሊነግረው ጀመረ እንዲህም አለው "እርሷ ከቊስጥንጥንያ አገር ከመንግሥት ታላላቅ ወገኖች ውስጥ የሆነች ስትሆን ሰውነቷን ለክርስቶስ ሰጥታ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ክብር ሁሉ ተወች። ሰይጣንን ተዋጋችበት ከዚህ ከታላቅ ተጋድሎዋ ለእኛ ለወንዶች መመከሪያ ሊሆነን ይገባል ከእርሷም የሴቶችን ደካማነት አርቃ የኃይለኞች ወንዶችን ብርታት ገንዘብ እስከማድረግ ደርሳ እግዚአብሔርን አገልግለችው" አለው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት አንስጣስያ በጸሎቷ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #በጻድቁ_ንጉሥ_በቴዎዶስዮስ ዘመን #የከበሩ_አርባ_ዘጠኝ_አረጋውያን_መነኰሳትና ከንጉሥ መልክተኞች ከልጁም ጋር ሰማዕት መሆጋቸው፦ የሰማዕትነታቸው ምክንያት ቴዎዶስዮስ ልጅ አልነበረውም በአስቄጥስ ገዳም ወደ ሚኖሩ አረጋውያን መነኰሳት ልጅን ይሰጠው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እንዲማልዱለት እየለመናቸው መልእክትን ላከ ከውስጣቸውም ስሙ ቢስዱራ የሚባል አንድ ታላቅ አረጋዊ ስለ እርሱም ወደ ንጉሥ እንዲህ ብሎ ጻፈ "ከአንተ በኋላ ከሚነሡ መናፍቃን ጋር አንድ እንዳይሆን ልጅን ይሰጥህ ዘንድ እግዚአብሔር አልወደደም"። መልእክቱን በአነበበ ጊዜ ንጉሥ ደስ ብሎት እግዚአብሔርን አመሰገነው ሃሳቡንም አሳረፈ።
❤ ዳግመኛም ግብዞች ሰዎች ሌላ ሚስት አግብቶ ከእርሱ በኋላ በዙፋኑ የሚቀመጥ ልጅን ይወልድ ዘንድ መከሩት እርሱም "የትሩፋታቸው ዜና በዓለም ዳርቻ ሁሉ ደርሷልና በአስቄጥስ ገዳም ከሚኖሩ ቅዱሳን አረጋውያን ትእዛዝ በቀር ምን ምንም አላደርግም" ብሎ መለሰላቸው። ስለዚህም አረጋውያንን ይጠይቅ ዘንድ ንጉሥ መልክተኛውን ዳግመኛ ላከ ለንጉሡም መልእክተኛ ልጅ ነበረው ልጁም በረከታቸውን ይቀበል ዘንድ ከእርሱ ጋራ ወደ አረጋውያን እንዲወስደው አባቱን ለመነው መልክእተኛው ከልጁ ወደ አረጋውያን በደረሰ ጊዜ የንጉሥ ደብዳቤ ሰጣቸው እርሱንም አነበቧት ያን ጊዜ ግን አባ ቢስዱራ ስለሞተ አልተገኘም አረጋውያንም የንጉሡን መልእክተኛ የአባ ቢስዱራ ሥጋ ወዳለበት ወሰዱትና አደረሱት ሥጋውንም "አባታችን ሆይ እነሆ የንጉሥ መልክት ወደ እኛ ደረሰ እኛም የምንመልስለትን አናውቅም" አሉት። በዚያንም ጊዜ አረጋዊ አባ ቢስዱራ ተነሥቶ "እግዚአብሔር ልጅን ሊሰጥህ አልፈቀድም አላልኩህምን አለ በሉት ለንጉሥ አሁንም ከዓላውያን ጋር አንድ ሁኖ እንዳይረክስ ሌሎች ሴቶችንም ቢአገባ ልጅን አይሰጠውም" ይህንንም ተናግሮ ተመልሶ ተኛ።
❤ አረጋውያንም ይህን ቃል በክርታስ ጽፈው ለንጉሥ መልእክተኛ ስጡት እርሱም ወደ አገሩ ሊመለስ በተነሣ ጊዜ እነሆ የበርበር አረማውያን ደረሱ አባ ዮሐንስ የሚባል አረጋዊም ቁሞ ወገኖቹን እንዲህ አላቸው "እነሆ የበርበር ሰዎች ይገድሉን ዘንድ መጡ ምስክርነት የሚሻ ከእኔ ጋር ይቁም የሚፈራ ግን ወደ ግንብ ሒዶ ይሠወር" አለ። የሸሹም አሉ ከአባ ዮሐንስም ጋር የቀሩ አርባ ዘጠኝ አረጋውያን መነኰሳት የንጉሥ መልእክተኛም ልጅ ከጎዳና ጒዞ ላይ ዘወር ሲል በአረጋውያን ሰማዕታት ራሶች አክሊላትን ሲያኖሩ መላእክትን አያቸው የዚያም ጎልማሳ ስሙ ድያስ ነው አባቱንም "እነሆ በአረጋውያን ራሶች ላይ አክሊላትን ሲያኖሩ ረቂቃን መላእክትን አያለሁ አሁንም እንደርሳቸው አክሊልን ለመበቀል እኔ እሔዳለሁ" አለው አባቱም "ልጄ ሆይ እኔም ከአንተ ጋር እሔዳለሁ" አለው። በዚያችም ጊዜ አረጋውያን መነኰሳት ለአረማውያን ተገለጡላቸው አረማውያንም ገደሏቸው የምስክርነት አክሊልንም ተቀበሉ።
❤ አረማውያንም ከሔዱ በኋላ መነኰሳቱ ከተሠወሩበት ግምብ ወርደው የሰማዕታትን ሥጋቸውን ሰበሰቡ ገንዘውም በበዓት ውስጥ አኖሩዋቸውም በእርሳቸውም ዘንድ ሌሊቱን ሁሉ የሚጸልዩና የሚዘምሩ ከእርሳቸውም የሚባረኩ ሆኑ የአባ ዮሐንስንም ሥጋ ሰዎች ሰርቀው ባታኑን ወደሚባል አገር ወሰዱት ከእርሳቸውም ዘንድ ጥቂት ቀኖች ኖረ ከዚህም በኋላ ቅዱሳን ወደቦታው መለሱት።
❤ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን። ❤
❤ እንኳን #ከሰባቱ_አጿማት_አንዱ ለሆነ #ለነነዌ_ጾም እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። #ጥር_25_እስከ_ጥር_27_ቀን 2018 ዓ.ም።
✝️ ✝️ ✝️
❤ ጾም ሙሽሪትን ትመስላለች፤ ሙሽሪትን በሠርግ አዳራሽ ኾነው የሚቀበሏት ሰዎች ቤቱን ያስጌጡታል፤ ይሸልሙታል፡፡ ወደ ሠርጉ አዳራሽ የሚገባውን ሰው የሠርግ ልብስ ለብሶ እንደኾነ፣ የቆሸሸ እንዳልኾነ አይተው ያስገቡታል፡፡ እኛም እንዲኽ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡
❤ ልቡናችንን በማንጻት፣ ልል ዘሊል ከመኾን በመራቅ፣ የክፋት እርሾን በማስወገድ፣ ከጾም ጋር አብረው የሚመጡትን የሚያጅቧትን መልካም ምግባራትንም ለመቀበል የልቡናችንን ውሳጤ በመክፈት የምግባር እናት፣ የማስተዋል እንዲኹሉም ለሌሎች ምግባራት ኹሉ ንግሥት የምትኾን ጾምን ልንቀበላት ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ ታላቅ ሐሴት እናደርጋለን፤ ርሷም ቁስለ ነፍሳችንን ትፈውስልናለች፡፡
❤ በሌላ አገላለጽ ብነግራችኹ ሐኪሞች በአንድ ታማሚ ሰውነት ውስጥ ያለውን ቆሻሻ፣ መርዘኛ ፈሳሽን ማስገድ ሲፈልጉ መጀመሪያ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር ታማሚው ምግብ ከመውሰድ እንዲቈጠብ ነው፡፡ ታማሚው ለጊዜው ምግብን ከመብላት ካልተከለከለ ሐኪሞቹ የሚሰጡት መድኃኒት እንደተፈለገው ውጤት አይሰጥም፡፡ እኛም ቁስለ ነፍስ ቁስለ ሥጋ የምትፈውሰውን ጾም ስንቀበላት ከዚኽ በላይ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስን የምንሻ ከኾነ ልቡናችንን ንጹሕና ንቁ በማድረግ ልንወስዳት ይገባናል፡፡ እንዲኽ ካልኾነ ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ያመዝናል፡፡ #ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ጾመ_ነነዌ_ወቅዱስ_ዮናስ_ነቢይ፦ ዮናስ ማለት 'ርግብ'፣ የዋህ' ማለት ሲሆን ከ12ቱ ደቂቀ ነቢያት አንዱ ነው:: በሰራፕታ ተወልዶ ያደገው ነቢዩ በልጅነቱ ታሞ ሙቶ ነበር:: ታላቁ ነቢይ ኤልያስ ግን 7 ጊዜ ጸሎት አድርጐ ከሞት አስነስቶታል። (1ኛ ነገ 17፥17) እናቱ የሰራፕታዋ መበለትም ደግ ሴት ነበረች።
❤ ቅዱስ ዮናስ በእድሜው ከፍ ሲል የቅዱስ ኤልያስ ደቀ መዝሙር ሆነ። የነ ኤልሳዕና አብድዩም ባልንጀራ ነበረ። ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስ ካረገ በኋላ ቅ.ል.ክርስቶስ በ800 ዓመት አካባቢ የነነዌ ሰዎች ኃጢአት ከመሥፈርቱ በማለፉ የእግዚአብሔር ቃል ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ መጣ።
❤ "ሒድና ለነነዌ ሰዎች ንስሐን ስበክላቸው" አለው። ከነቢያት ወገን ከሙሴና ከዳዊት ቀጥሎ የዮናስን ያህል የዋህ (ገራገር) የለምና እንቢ አለ (ሰምቶ ዝም አለ)። እግዚአብሔር እየደጋገመ ሲናገረው ግን "እንዲህ የሚዘበዝበኝ ከፊቱ ብቀመጥ አይደል!" ብሎ ወደ ተርሴስ ኮበለለ።
❤ ወገኖቼ አንድ ነገርን ልብ እንበል። እንኳን ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዮናስ እኛ ክፉዎችም ከጌታ ፊት መሸሸት እንደማይቻል ጠንቅቀን እናውቃለን። ታዲያ ለምን ሸሸ ቢሉ:- ጥበበ እግዚአብሔር በውስጡ ስለ ነበረበት ነው።
❤ ምክንያቱም ዮናስ በአሣ አንበሪ ሆድ 3 ቀን ሌሊት ኖሮ ሙስና (ጥፋት) ሳያገኘው መውጣቱ ለጌታ ትንሣኤ ጥላ (ምሳሌ) ነው። ለዚህም ምስክሩ ራሱ ጌታችን ነው።
"ወበከመ ነበረ ዮናስ ውስተ ከርሠ አንበሪ ሠሉሰ ዕለተ ወሠሉሰ ለያልየ፤ ከማሁ ይነብር ወልደ እጉዋለ እመ ሕያው ውስተ ልበ ምድር ሠሉሰ ዕለተ፤ ወሠሉሰ ለያልየ" እንዲል። (ማቴ. 12:39)
❤ ቅዱስ ዮናስ በገንዘቡ ዋጅቶ ወደ መርከብ በገባ ጊዜ ታላቅ ማዕበል ሆነ። የእምነት ሰው ነውና እንዲያ እየተናወጡ እርሱ በእርጋታ ተኝቷል። እነርሱ ግን ቀስቅሰው ቢጠይቁት (እጣ ወድቆበታልና) "የእኔ ጥፋት ስለ ሆነ ወደ ማዕበሉ ጣሉኝ" አላቸው።
❤ እያዘኑ ቢጥሉት ታላቅ ጸጥታ ሆነ። እነዚያ አሕዛብም እግዚአብሔርን በመስዋዕትና በስዕለት አከበሩ። ዮናስ ግን በማዕበልና በአሣ አንበሪ ሆድ ውስጥ ለ3 ቀናት ጸለየ። አሣ አንበሪው በ3ኛው ቀን ወደ ነነዌ ተፋው።
❤ ቅዱሱም "እስከ ሠሉስ ዕለት ትትገፈታእ ነነዌ ዐባይ ሃገር" እያለ ንስሃን ሰበከ። የነነዌ ሰዎች ኃጢአታቸውን አምነው ቢጸጸቱ ከሰማይ ወርዶ ከደመና ደርሶ የነበረው የእሳት ማዕበል ተመልሶላቸዋል::
❤ የነቢዩ ትንቢት ግን አልቀረምና ታላቁዋ ነነዌ ከ300 ዓመታት በኋላ ጠፍታለች። ቅዱስ ዮናስ ግን በቀሪ ዘመኑ ፈጣሪውን እያገለገለ ኑሯል። ጠቅላላ እድሜውም 170 ዓመት ነው::
❤ ዛሬ ያለን ሁላችን ሀገራችን ነነዌን ሕዝቦቿም ሕዝቦቻቸውን ከመሰልን ሰንብተናል። በእርግጥ እንደ ነነዌ እሳት አይዘንብብን ይሆናል። ግን የዘለዓለም እሳት ይጠብቀናል። ንስሐ ካልገባን የሚመጣብን ቅጣት የሚከፋ ይሆናል።
❤ አምላከ ቅዱስ ዮናስ እድሜ ለንስሃ፤ ዘመን ለፍስሃ አይንሳን። ጾሙንም የበረከት ያድርግልን::
❤ ክፉና አመንዝራ ትውልድ ምልክት ይሻል። ከነቢዩም ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት አይሰጠውም። ዮናስ በአሣ አንበሪ ሆድ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት እንደ ነበረ፤ እንዲሁ የሰው ልጅ በምድር ልብ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ይኖራል። የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነስተው ይፈርዱበታል። በዮናስ ስብከት ንስሐ ገብተዋልና:: እነሆም ከዮናስ የሚበልጥ ከዚህ አለ። (ማቴ 12፥39) ምንጭ፦ ከዲያቆን ዮርዳኖስ አበበ ቻናል የተወሰደ።
❤ ሁላችንም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ልጆች በጾም በጸሎትና በምሕላ እንድናሳልፍ አምላከ ቅዱሳን ልዑል እግዚአብሔር ለሁላችንን ኃይልና ብርታትን ያድለን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወኢትትኀጐሉ እምፍኖተ ጽድቅ። ሶበ ነደት ፍጡነ መዓቱ። ብፁዓን ኵሎሙ እለ ተወከሉ ቦቱ። መዝ 2፥12_13። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 2፥1_17፣ ያዕ 5፥1_10 እና የሐዋ ሥራ 2፥37_ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 12፥38_43። የሚቀደሰው ቅዳሴ ቅዳሴ እግዚእነ። ጾሙ ለአገራችና ኢትዮጵያና ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነቻችን ሰላም፣ ፍቅርና አንድነት መታሳሰብ የሚያመጣ ያድርግል። መልካም ጾምና የምህላ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤
❤ #ጥር ፳፭ (25) ቀን።
❤ እንኳን #ለታላቁ_ሰማዕት_ለሮም_ንጉሥ_ልጅ ለከበረ #ለሰማዕቱ_ለቅዱስ_ስብስትያኖስ ምስክርነቱ ለፈጸመበት ለዕረፍቱ በዓልና አስቀድሞ ቀራጭ ለነበረ ራሱን ለሸጠው በገድል ለተጸመደ ለኖረ ለከበረ #ቅዱስ_ጴጥሮስ_ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ከሰማዕት #ቅዱስ_አስኪላ ከመታሰቢያው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_ስብስትያኖስ፦ ይህም የቅዱስ የሮሜ ንጉሥ ልጅ ነው። እርሱንም ወላጆቹ በተግሣጽና እግዚአብሔርን በመፍራት የአሳደጉት ነው። አባቱም ከሞቱ በኋላ ዲዮቅልጥያኖስና መክስምያኖስ ነገሡ ይህንንም ቅዱስ አገረ ገዥነት ሾሙት እንደ አባቱም እጅግ አከበሩት። እርሱሜ በጥበብና በማስተዋል ይጓዝ ነበር በሽተኞችን ሁሉ የዕውራንንም ዐይኖች በጸሎቱ ከፈተ።
❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ክርስቶስን ዲዮቅልጥያኖስ በካደው ጊዜ ለጣዖት ይሰግድ ዘንድ ስብስትያኖስን ግድ አለው ባልሰማውም ጊዜ ከደረቀ ግንድ ጋር አሠረው ቊጥር በሌላቸው ፍላጻዎች ይነድፉት ዘንድ አዘዘ እንደሞተም ጠርጥረው ትተውት ሔዱ ምእመናንም በሌሊት ሲመጡ በሕይወት አገኙት ፈትተውም ወደ ደሴት መካከል ወስደው በዚያ አኖሩት።
❤ ዲዮቅልጥያኖስም ሰምቶ ወደርሱ አስቀረበውና በብረት ዘንጎች ይደበድቡት ዘንድ አዘዘ እየደበደቡትም ብዙ ቀኖች ኖሩ ከዚህም በኋላ ነፍሱን አሳለፈ። ለቅድስት ውሉድስና በሕልም ተገልጦ ሥጋው ያለበትን ነገራት እርሷም ሒዳ ወደ ቅዱስ ጴጥሮስና ጳውሎስ መቃብር ወስዳ ቀበረችው። ጌታችንም መታሰቢያውን ለሚያደርግና ስሙን ለሚጠራ የቸነፈር ሕመም እንዳይቀርበው ቃል ኪዳንን ሰጠው።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ጴጥሮስ፦ ይህም ቅዱስ አስቀድሞ ቀራጭ ነበረ እርሱም ልቡ የደነደነ ርኅራኄ የሌለው ነው በዚህም ክፉ ስም ጨካኝ ርኅራኄ የሌለው ብለው ይጠሩታል። ከዚህም በኋላ የኃጢአተኞች ሞት የማይሻ ጌታችን ከእርሱ ምጽዋት የሚለምነውን ድኃ ላከለትና ለመነው በዚያንም ጊዜ አገልጋዩ እንጀራ ተሸክሞ ደረሰ አገልጋዩ ከተሸከመው ከራሱ ላይ አንድ እንጀራ ለዚያ ድኃ ጣለለት ይህንንም ያደረገ ስለ ርኅራኄ አይደለም ከአጠገቡ እንዲሔድለትና ከቶ ወደርሱ እንዳይመለስ ነው ምስኪኑም ተቀብሎ ወደ ማደሪያው ሔደ።
❤ በዚያችም ሌሊት ተኝቶ ሳለ በሕልሙ እንዲህ አየ ብዙዎች ሊተሳሰቡት ይሻሉ በእጆቻቸውም ሚዛኖች ተይዘዋል ብዙዎችም መልካቸው እጅግ የከፉ ጥቋቊሮች ኃጢአቱ ሁሉ ከእርሳቸው ጋር አለ በግራ በኩል ባለው ሚዛን ውስጥ አኖሩት ደግሞ ልብሳቸቻው ነጫጭ የሆኑ ከብርሃናውያን መላእክት መልካቸው ያማረ ብዙዎች ነበሩ እነርሱም ቁመው በማዘን "ምንም ያገኘነው ነገር የለም በቀኝ ባለው ሚዛን ውስጥ ምን አናኖራለሁ" ይሉ ነበር በዚያንም ጊዜ ከእርሳቸው አንዱ መልአክ ጴጥሮስ ለድኃው የጣላትን ያችን እንጀራ አምጥቶ "ከዚች እንጀራ በቀር ሌላ ከበጎ ሥራ ምንም አላገኘሁለትም" አለ ባልንጀሮቹ መላእክትም "በእነዚህ ሁሉ ኃጢአቶቹ አንጻር ይቺ ምን ትጠቅማለች" ብለው መለሱ በዚያንም ጊዜ እየፈራና እየደነገጠ ከእቅልፋ ነቅቶ ከተኛበት ተነሣ።
❤ ከዚያችም ዕለት ወዲህ ስለቀደመች ክፉ ሥራው ተጸጸተ እጅግም የሚራራ ሆነ ቤቱንና ጥሪቱን ሁሉ ሽጦ ለድኆችና ለምስኪኖች ሰጠ ራሱንም ሸጠ። ብዙዎችም ከበጎ ሥራዎች ይህን ስለ ሠራ እንደሚአመሰግኑትና እንደሚያደንቁት በአወቀ ጊዜ ከዚያ በመሸሽ ወደ አስቄጥስ ገዳም ገብቶ ከአባ መቃርስ ገዳም በዚያ መነኰሰ ፍጹም በሆነ ተጋድሎም ተጠምዶ እግዚአብሔርን አገልግሎ የዕረፍቱን ጊዜ አውቆ የከበሩ አረጋውያንን ጠርቶ ተሳለማቸውና በዚያን ጊዜ ጥር24 ቀን ዐረፈ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቱ በቅዱስ ሰብስትያኖስና በአባ ጴጥሮስ በጸሎታቸ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር25 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለከ_ስብስትያኖስ_ሰማዕተ ዋሕድ ወልድ። ዘንዱፍ በአሕፃ ወእሡር በጒንድ። ተውላጠ ዝንቱ ፃማከ ወሕማምከ ፍድፉድ። መጽሐፈ ገድልከ በኀበ ሀሎ ዐፀድ። እግዚአብሔር አሕረመ ኢይባዕ ብድብድ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥር_25።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ተፈሣሕ በእግዚአብሔር ወይሁበከ ስእለተ ልብከ። ክሥት ለእግዚአብሔር ፍኖተከ። ተወከል ቦቱ ወውእቱ ይገብር ለከ"። መዝ 36፥4-5። የሚነበበው ወንጌል ማር 9፥16-30።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤
❤ #ጥር ፳፭ (25) ቀን።
❤ እንኳን ለኢትዮጽያዊ ጻድቅ #ለአቡነ_ተክለ_ሃይማኖት_ለአጎት_ልጅ ለታላቁ አባት ከበሬ ጋር ተጠምደው በማረስ ሰማዕትነት ለተቀበሉት #ለአቡነ_ሕፃን_ሞዐ_ለልደታቸው በዓልና ለታላቁ ሰማዕት #ለቅዱስ_መርቆሬዎስ በሥዕሉ ላይ አድሮ ቅዱሳን ለሆኑ #ባስልዮስንና_ጎርጎርዮስን በመርዳት ከሃዲውን ንጉሥ ዑልያኖስን ለገደለባት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰማዕቱ_ቅዱስ_መርቆሬዎስ_ያደረገው ተአምር፦ በቀጰዶቅያና በቂሳሪያ በተሾመ በኢጲስቆጶስ ቅዱስ ባስልዮስ ዘመን ዑልያኖስ በነገሠ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ካደ። ከቅዱስ ባስልዮስ ተአምራት በአንዷ ውስጥ እንደተጻፈው ከሓዲ ዑልያኖስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የሚያምኑትን ከባድ ሥቃይ አደረሰባቸው። በቅዱስ ባስልዮስ ላይም ተቈጣ፤ አሰረውም። በክርስቲያኖች ላይ ከባድ ሥራ ባበዛባቸው ጊዜ ቅዱስ ባስልዮስ ስለ ከሐዲ ዑልያኖስ ወደ እግዚአብሔር ይጸልይ ይለምን ጀመረ። ወደ ቅዱስ መርቆሬዎስ ለመነ።
❤ እግዚአብሔር ጸሎቱን ሰማና ታላቁን ሰማዕት ቅዱስ መርቆሬዎስን ላከለት። በፈረስ ተጭኖ መጣና ከሓዲ ዑልያኖስን አንገቱን በጦር ወጋው። በፋርስ ምድር በውጊያ በክፉ አሟሟት ሞተ። ቅዱስ ባስልዮስ ይህን ራእይ በቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕል ላይ ባየ ጊዜ ፈጽሞ ደስ አለው። የታላቁ ሰማዕት የቅዱስ መርቆሬዎስ አካለ ሥጋ ያለበት ቦታ ተገልጦለት እየጸለየና እያደነቀ ገባ። ያን ጊዜ የቅዱስ መርቆሬዎስ ሰይፍና ጦር ከቅዱስ መርቆሬዎስ ሥዕል ሥር ያለበት ቦታ እስኪሞላ ድረስ ከእነርሱ ብዙ ደም እየፈሰሰ ወደ ቦታቸው ተመለሱ።
❤ ያን ጊዜ ቅዱስ ባስልዮስ ጮኸ። "የክርስቶስ ሰማዕት ሆይ፤ የእውነት ጠላት የሆነውን ዑልያኖስን ገደልከውን?" አለ። ቅዱስ መርቆሬዎስ በቅዱስ ባስልዮስ ፊት "አወን ገደልኩት" እያለ በሥዕሉ ላይ ራሱን ዘንበል አደረገ። ቅዱስ ባስልዮስ የእግዚአብሔርን ክብርና ምስጋና የኢየሱስ ክርስቶስ ሰማዕት የሆነውን የቅዱስ መርቆሬዎስን ብዙ ተአምርና ድንቅ ድንቅ ሥራ አደነቀ። የሰማዕቱ የቅዱስ መርቆሬዎስ ጸሎቱና በረቱ ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን። ምንጭ፦ ከቅዱስ መርቆሬዎስ ገድል ተአምር።
✝ ✝ ✝
❤ #የአቡነ_ሕፃን_ሞዐ_ልደት_በተመለከተ፦ በተጉለት አውራጃ ደርደሬ በምትባል ቦታ የሚኖር አንድ ሰው ነበር፡፡ ስሙም አርከለዲስ ይባላል፣ የሚስቱም ስም ትቤጽዮን ይባላል፣ ሁለቱም ለእግዚአብሔር እውነተኞችና ታማኞች ነበሩ፡፡ እንደ ሕልቃናና እንደ ሐና፣ እንደ ዘካርያስ፣ እንደ ኤልሳቤጥ፣ እንደ ኢያቄምና በድንግልና አምላክን እንደወለደች እንደ ማርያም እናት እንደ ሐናም ልጆችን ወለዱ፡፡
❤ ከዚህ በኋላ በግብረ ሥጋ እንዳይገናኙ ለእግዚአብሔር ብፅዓት ገቡ፡፡ አርከለዲስም እንደ ካህኑ ዘካርያስ በቤተ መቅደስ እግዚአብሔርን ያገለግል ነበር፡፡ ትቤ ጽዮንም መካን እንደነበረች እንደ አልሳቤጥ እነርሱን ለማገልገል ትተጋ ነበር፡፡ በግብር ሳይገናኙ ለዘጠኝ ዓመት ጸንተው ኖሩ፤ አርከለዲስም በዐፀደ ቤተ መቅደስ ሳለ የእግዚአብሔርመልአክ ወደ እርሱ መጣ፡፡ ለዘካርያስ እንዳለው ለእርሱም ተናገረው፤ "ከልጆችህ ሁሉ የተመረጠ ደግ ልጅ ትወልዳለህና ሒድ ከሚስትህ ጋር ተገናኝ" አለው። "ይኸውም በምድርም በሰማይም የሚጠቅም ይሆናል"፡፡ ሊነግራት ይህንንም ሊያማክራት ወደ ሚስቱ ላከ፡፡ እርሷም ለሌላ ሥራ የጠራት መስሏት ወደ እርሱ መጣች። ይህንንም በሰማች ጊዜ ፈጽማ ተቆጣችው፤ "ወደ ትፋቱ እንደሚመለስ ውሻ ነን? ወይንስ ከታጠበች በኋላ ከጭቃ ላይ እንደምትንከባለል እሪያ ነን? አንተ ሽማግሌ ነህ፣ እኔም አሮጊት ነኝ ሥጋችንን ለእግዚአብሔር ብፅዓት አድርገን እንደሰጠን እንደዚሁ እንኑር እንጂ" ብላ ቸል ብላው ሔደች፡፡
❤ ያም መልአክ ዳግመኛ ወደ እርሱ መጣ፤ "የእግዚአብሔርን ቃል ለምን ታቃልላለለህ?" አለው። ዳግመኛም ትመጣ ዘንድ ወደ እርሷ ላከ፡፡ እርሷም "በነገርከኝ ነገር ከሆነ አልመጣም" አለችው፡፡ ያም መልአክ ሦስተኛ ጊዜ ወደ እርሱ መጥቶ ተቆጣ፤ አርከለዲስም "እኔ ብነግራት እምቢ ብላኛለችና አንተ ንገራት" አለው። ያም መልእክ ወደ እርሷ ሔደ፣ ተቆጥቶ ሦስት ጊዜ ገረፋት፤ የግርፋቷንም ምልክት ለቤተሰቦቿ አሳየች፡፡ "ጠርታችሁ አምጡልኝ" አለች፡፡ "ለምን እንደዚህ አደረግኸኝ? አለችው፤ በተናገርኸው ነገር በአንተ ምክንያት በመልአኩ እጅ ተገረፍሁ"፡፡
❤ ከዚህ በኋላም እጃቸውን ዘርግተው ወደ እግዚአብሔር ለመኑ፡፡ "ፈቃድህን የሚፈጽምና አንተን ደስ የሚያሰኝ መልካም ልጅ ስጠን" አሉ፡፡ ከዚህ በኋላ ፀነሰች፣ እግዚአብሔር ነቀፌታየን ከሰው ያስወግድልኝ ዘንድ እንዲህ አደረገልኝ ስትል ራሷን እንደ ኤልሳቤጥ አምስት ወራት ሸሸገች፡፡
❤ ከዚህም በኋላ እንደ ኖኅ ልደት ሁሉ ሁለንተናው የሚያስደስትና ያማረ ፊቱም የበራ ልጅ ወለደች፡፡ ኖኅ በተወለደበት ዕለት ቤቱ ብርሃን እንደሆነ እንዲሁ እግዚአብሔርን በመፍራትና ሕጉን በመጠበቅ አደገ በእግዚአብሔር ዘንድ እንደ ሳሙኤል ካህን የታመነ ሆነ። የሳሙኤል ዜና ነገሩ ከዳን እስከ ቤርሳቤህ እንደ ተሰማ የሕፃን ሞአም ገድለ ትሩፋቱ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ ተሰማ።
❤ ከዚህ በኋላ ከብት ጠባቂ አደረጉት፡፡ እርሱም ከብቶቹን ትቶ ከባሕር ገብቶ ቆሞ ይጸልይ ነበር። ምሳውንም ከብቶቹን ለሚጠብቁለት ጓደኞቹ ይሰጣቸው ነበር፡፡ ዮሐንስ በደሴተ ፍጥሞ ቆሞ ይውል እንደነበር እርሱም በባሕር ውስጥ ለጸሎት ቆሞ ይውል ነበር፡፡ እርሱን የሚጠብቀው መልአክም ከብቶቹን ይመልስለት ያገለግለው ነበር።
❤ ከዕለታት አንድ ቀን በባሕር ውስጥ ለጸሎት ውሎ ሳለ ወንድሙ "ከብቶችህን ትተህ ወዴት ዋልህ?" አለው፡፡ ሕፃን ሞአም "በባሕር ውስጥ ስጸልይ ዋልኩ" ብሎ መለሰለት እርሱም እየተቆጣ "እናትህ በባሕር ትጥፋ" አለው፡፡ ከበሬ ጋር ጠምዶት ሦስት ትልም (ፈር) አረሰበት፡፡ እያለቀሰ ሲሔድ እግዚአብሔር በመንገድ ተገናኘው፡፡ "በልብህ የተመኘኸውን ምኞትህን እፈጽምልሃለሁና አትፍራ" አለው...። ከአባታችን ከአቡነ ሕፃን ሞዐ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ አቡነ ሕፃን ሞዐ አንደበት።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ እንኳን #ለዘመነ_አስተርዮ_አራተኛ_ሳምንት ዕለተ ሰንበት (እሑድ) እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ የዚህ ሳምንት መዝሙር፦ ሃሌ ሉያ በ፮ "እሙነ_ኮነ_ልደቱ_ለመድኅኒነ_ክርስቶስ እምሰማያት ወረደ #ወእመላእክት_ተአኵተ_ወእማርያም_ተወልደ (እ)፣ በቤተ ልሔም ተወልደ ወበናዝሬት ተሐፅነ ወአስተርአየ ገሃደ (እ)፣ #ውእቱ_እክሊለ_ሰማዕት ውእቱ መድኀኔ ነገሥታት ኖላዊሆሙ ለአሕዛብ እሙነ ኮነ #ልደቱ_ብርሃነ_ኮነ_ምጽአቱ_ለመድኀኒነ_ክርስቶስ። ትርጉም፦ #የጌታችን _የመድኃኒታችን_የክርስቶስ_ልደት_እውነት_ነው፤ ከሰማያት ወረደ #በመላክት_ዘንድ_ተመሰገነ_ከማርያም_ተወለደ፣ እርሱም #የሰማዕታት_እክሊል_ነው፣ የነገሥታት መድኃኒት ነው የአሕዛብ እረኛቸው ነው፣ #የመድኃኒታችን_የክርስቶስ_ምጽአቱ_ብርሃነ_ልደቱ እውነት ነው"። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እግዚአብሔር እግዚእ አስተርአየ ለነ። ግበሩ በዓለ በትፍሥሕት በኀበ እለ ያስተሐምምዎ። እስከ አቅርንቲሁ ለምሥዋዕ"። መዝ 117፥27-28። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ቆሮ 1፥13-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 2፥22-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 13፥20-28። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 2፥42-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ቅዳሴ ነው። መልካም ዕለተ ሰንበት ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤
❤ #ጥር ፳፬ (24) ቀን።
❤ እንኳን #ከእስክድርያ_አገር_ከታላላቆቿ_ወገን ለሆነች በዓቷን በማጽናት #ለ22_ዓመታት ዘግታ ለኖረችውና የላመ የጣፈጠ ቀምሳ ለማታውቀው፤ ለከበረች ተጋዳ #ቅድስት_ማርያ_ለዕረፍቷ በዐሏ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ከሚታሰቡ፦ ከተመሰገነ #ቀሲስ_አብሳዲ ከመታሰቢያው፣ ከግብጽ አገር ከጥሐ አውራጃ ስፍጥ ከምትባል መንደር ከሆነ ከከበረ #ከታላቅ_አባት_ከቢፋ በሰማዕትነት ከዐረፈና #ከሐውዚን_ጻድቃን ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለጻድቃን እለ #በሐውዜን"። ትርጉም #በሐውዜን ያሉ ለኾኑ #ጻድቃ_ ሰላምታ_ይገባል። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ በተአምኆ ቅዱሳን ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅድስት_ማርያ፦ ይቺም ቅድስት ከእስክንድርያ አገር ከታላላቆቿ ወገን የሆነች ነች። የዚችም ቅድስት ወላጆቿ ክርስቲያኖች ናቸው በአደገችም ጊዜ ሊአጋቧት አሰቡ እርሷ ግን ይህን ጋብቻ አልወደደችም እናትና አባቷም በሞቱ ጊዜ የተዉላትን ገንዘብ ሁሉንም ለድኆች ሰጥታ ከእስክንድርያ አገር ውጭ ከአሉ ገዳማት ወደ አንዱ ገዳም ገባች የምንኵስና ልብስንም ለብሳ ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለች ድል እስካደረገችውም ድረስ እንቅልፍን ዐሥራ ሁለት ዓመት ስትታገለው ኖረች ከቶ አትተኛም ነበር እንደዚያ ገዳም ሕግ በእሊህ በዐሥራ ሁለት ዓመታት ሁልጊዜ እስከማታ ትጾም ነበር።
❤ ከዚህም በኋላ የከበረ አስኬማን ለበሰች ያን ጊዜ ከጥጥ ባዝቶ የተሠራውን ልብስ ከላይዋ አውልቃ ማቅ ለበሰች ትችል እንደሆነ ወይም አትችል እንደሆነ ራሷን ትፈትን ዘንድ ለመዝጋት ትፈቅድላት ዘንድ እመምኔቷን ለመነቻት እርሷም ፈቀደችላት በዚያንም ጊዜ በዓቷን ዘጋች ምግቧን የምትቀበልበት ትንሽ መስኮት ቀደደች ሥጋውንና ደሙን በዚያው ትቀበላለች በዚያችም በዓት ውስጥ ሃያ ሁለት ዓመት ዘግታ ኖረች።
❤ በዚህ ሁሉ ዘመን ቁማ ትጸልያለች በመኝታ ጊዜም ጥቂት ትተኛለች የቀረውንም ሌሊት እስቲነጋ ቁማ ስትጸልይ ታድራለች። በየሁለት ቀን የምትጾም ሆነች የምትመገበውም በውኃ የራሰ ለምለም እንጀራ ነበር በከበረችም በአርባ ጾም እንጀራ አትበላም በየሦስት ቀን እየጾመች በውኃ የራሰ ሽምብራ ትመገባለች እንጂ።
❤ ጥር ዐሥራ አንድ ቀን የከበረ የጥምቀት በዓልም በሆነ ጊዜ ከተባረከው ውኃ ያመጡላት ዘንድ ለምና አመጡላት ፊቷንና እጆቿን ታጥባ ሥጋውንና ደሙን ተቀበለች ከተባረከውም ውኃ ጠጣች ከዚህም በኋላ ታመመች እስከ ሃያ አንድ ቀንም በመኝታዋ ላይ ተኛች ዳግመኛ በዚች ቀን በጥር በሃያ አንድ ሥጋውንና ደሙን ተቀበለች።
❤ ከዚህም በኋላ እመ ምኔቷን አስጠራቻት እግሮቿንም እንታቀርብላት ብዙ ልመናን ለመነቻትና ስታቀርብላት ሳመቻቸው ፊቷንም አሸችባቸው "ወደ ክብር ባለቤት ጌታዬ ክርስቶስ ላቀረቡኝ እግሮችሽ እገዛለሁ" አለች ዳግመኛም ደናግሉን ሁሉ አስጠርታ ተሳለመቻቸውና ከሦስት ቀን በኋላ እንዲጐበኟት ለመነቻቸው ይኸውም ጥር ሃያ አራት ቀን ነው በመጡም ጊዜ ሙታ አገኟት ገንዘውም ከደናግል አስከሬን ጋር አኖሩዋት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅድስት ማርያ ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ ጥር 24 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለማርያም ዘአጥብዓት ትፍዲ። ለነዳያን ምጽዋተ ንዋየ አቡሃ ወላዲ። ወወጠነት ገድለ በአጽርዖ ንዋም ዓዲ። እምአምኆ ዛቲ ዕለት እንበለ ሕቀ እጐንዲ። ሰላም እብል ለቀሲስ አብሳዲ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥር_24።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኃይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 1-17።
❤ መልካም የአቡነ ተክለ ሃይማኖት የስብረተ አፅማቸው በዓልና የአባ ኖብ የልደት በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ጥር ፳፬ (24) ቀን።
❤ እንኳን #ከደቡባዊ_ግብጽ ከታችኛው ምድር አውራጃ ከንሒሳ ከተማ ለሆነ #ለቅዱስ_ለአባ_ኖብ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለልደት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በፍቅር አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_አባ_ኖብ፦ይህም ቅዱስ ከደቡባዊ ግብጽ ከታችኛው ምድር አውራጃ ከንሒሳ ከተማ ነው።
ወላጆቹ ቅዱሳን ንጹሐንና የሚራሩ ነበሩ። ይህንንም ቅዱስ ኖብን በወለዱት ጊዜ ዐሥራ ሁለት ዓመት እስኪሆነው ፈሪሀ እግዚአብሔርን እያስተማሩ አሳደጉት። ቤተ ክርስቲያንን የመጻሕፍትን ቃል መስማትንና መማርን የሚወድ ሆነ።
❤ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም የክርስቲያን ወገኖችን ዲዮቅልጥያኖስ በአሠቃያቸው ጊዜ ይህ ቅዱስ ደሙን ስለ ጌታችን ሊአፈስ አሰበ ያን ጊዜም ወደ ቤተ ክርስቲያን ገባ ቄሱንም ምእመናንን እንዲህ እያለ ሲያስተምራቸውና ሲያበረታቸው "ጣዖታትን ከምታመልኩ ክብር ይግባውና ስለ መድኃኒታችን ስለ ክርስቶስ ነፍሳችሁን ለሞት አሳልፋችሁ ብትሰጡ ለእናንተ መልካም ነው" ሲላቸው ሰማው። ይህም ቅዱስ እያዘነና እየተከዘ ወደ ቤቱ ተመለሰ አባቱም የተወለትን ወርቁንና ብሩን ልብሶችን ሁሉ ተመልክቶ እንዲህ አለ ሁሉ ነገር የዚህ ዓለም ፍላጎቱም ሁሉ እንደ ሚያልፍ እነሆ ተጽፏል። ከዚህም በኋላ ገንዘቡን ሁሉ ወስዶ ለድኆችና ለችግረኞች ሰጠ።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ ሀገረ ገምኑዲ ሔደ በእግሩም ሲጓዝ በባሕሩ ዳርቻ ሉስዮስ የሚባለውን መኰንን አገኘው በፊቱም ቁሞ ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመነ። መኰንኑም ታላቅ ሥቃይን አሠቃየው። ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለት በእርሱ ላይም የሚደርሰውን ሁሉ ነግሮት አጽናናው።
❤ ከዚህም በኋላ መኰንኑ ወደ ሰሜን አገር ሲጓዝ የከበረ ኖብን ከእርሱ ጋራ በመርከብ ወሰደው በመርከቡም ምሰሶ ላይ ዘቅዝቆ ሰቀለው መኰንኑም ሊበላና ሊጠጣ ተቀመጠ በመኰንኑም እጅ የነበረው ጽዋ ወዲያውኑ እንደ ደንጊያ ሆነ የወታደሮቹም ዐይኖቻቸው ታወሩ የእግዚአብሔር መልአክም ከሰማይ ወርዶ አባ ኖብን ፈትቶ ከተሰቀለበት አወረደው በአፍንጫውና በአፉ የወረደውንም ደሙን አሻሸለት።
❤ ከዚህ በኋላም መልካም ነፋስ ነፍሶ መርከቢቱ ተጓዘች። ወደ አትሪብ ከተማም ደረሱ ወታደሮችም ይህን ድንቅ ተአምር አይተው ትጥቃቸውን ፈተው በመኰንኑ ፊት ጣሉ። ክብር ይግባውና በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ታመኑ ሰማዕታትም ሆነው ራሳቸውን ቆረጡአቸው የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበሉ። መኰንኑም በአትሪብ ከተማ ቅዱስ አባ ኖብን ታላቅ ሥቃይን አሠቃየው በብረት ዐልጋ ላይም አስተኝተው ከበታቹ እሳትን አነደዱ በጸለየ ጊዜም እግዚአብሔር ከእሳት አዳነው።
❤ ከዚህም በኋላ በመጋዝ መገዙት ሕዋሳቱንም ቆራረጡ የእግዚአብሔር መልአክም ወርዶ አዳነው ያለ ጉዳትም በጤና አስነሣው። ከዚህም በኋላ ወደ እስክንድርያ ከተማ ወሰዱት በዚያም ብዙ አሠቃዩት በላዩም እባቦችን ሰደዱ ግን አልቀረቡትም ከእባቦችም አንዱ ሒዶ በመኰንኑ አንገት ተጠመጠመ ያስጥሉትም ዘንድ ሟርተኞቹን አዘዛቸው ግን አልተቻላቸውም ከዚህም በኋላ ያድነው ዘንድ ቅዱስ አባ ኖብን ለመነው ቅዱሱም ከይሲውን ትቶት ከአንገቱ እንዲወርድ አዘዘው።
❤ መኰንኑም ሁለተኛ በእሳት እንዲአቃጥሉት ሟርተኞችንና ሥራየኞችን አዘዛቸው እሳቱም ምንም አልነካውም። አቅፋሐስ ከሚባል አገርም ዮልዮስ መጣ ከእርሱም እንደ ተረዳ ገድሉን ጻፈ። መኰንኑም ማሠቃየቱን በሰለቸ ጊዜ አንገቱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ።
❤ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ተገልጾለት አጽናናው እንዲህ ብሎም ቃል ኪዳን ሰጠው "ሥጋህ በሚኖርበት ቦታ ከእርሱ ታላቅ ፈውስ ይሆናል እንዲሁም በመከራው ጊዜ ስምህን በመጥራት ከእግዚአብሔር ርዳታ ለሚሻ ሁሉ ድኅነት ይደረግለታል። መታሰቢያህንም ለሚያደርግ ሁሉ የተራበ ለሚያጠግብ፣ የተጠማም ለሚያጠጣ፣ ለቤተ ክርስቲያንም በስምህ መባ ለሚሰጠው፣ የገድልህንም መጽሐፍ ለሚጽፍ ኃጢአቱን ይቅር እለዋለሁ መንግሥተ ሰማያትንም አወርሰዋለሁ"።
❤ ከዚህም በኋላ ራሱን በሰይፍ ቆረጡ ተጋድሎውንም ፈጸመ ሥጋውንም ቅዱስ ዮልዮሰ አንሥቶ ከሁለት አገልጋዮቹ ጋራ ንሒሳ ወደ ሚባል አገሩ ላከው። የመከራውም ወራት በተፈጸመ ጊዜ አብያተ ክርስቲያናትን ሠሩለት በውስጣቸውም ብዙዎች ድንቆችና ተአምራቶች ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕቱ አባ ኖብ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
ምንጭ፦ የሐምሌ 24 ስንክሳር።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤
❤ #ጥር ፳፬ (24) ቀን።
❤ እንኳን #ለታላቁ_አባት_ለሐዲስ_ሐዋርያ ለፀሐይ ዘኢትዮጵያ #ለአቡነ_ተክለሃይማኖት በቁመትና በጸሎት ብዛት አንዲቱ የእግሩ አገዳ ለተሰበረበት (#ለስብረተ_አፅማቸው) ዓመታዊ መታሰቢያ በዓልና ለኢትዮጵያዊው ጻድቅ እንደ ነዳይ ሆነው ለምነው ያገኙትን ለጦም አዳሪዎች በመመጽወት ለሚታወቁት #ለአቡነ_እጨጌ_መርሐ_ክርስቶስ (ዘሸዋ) ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የአቡነ_ተክለ_ሃይማኖት_ስብረተ_አፅም፦ "...ከበዐቱ ሳይወጣ ሌሊትና ቀን ቆመ። አልተቀመጠም ወደ ግራና ወደ ቀኝም አልተንቀሳቀሰም። ውኃም ቅጠልም ቢሆን ከቅዳሜና ከእሑድ በቀር በዚያ ወራት ምንም ምን አልቀመሰም። እህል ግን ከመነኰሰ ጀምሮ እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስ አልቀመሰም። ፀሓይንም ጨረቃንም ከዋክብትን በጋና ክረምትንም ቡቃያና አበባንም ፍሬውንም አላየም። ዓይኖች ሳሉት እንደ ዕውር ጆሮዎች ሳሉት እንደ ደንቆሮ የሚናገር የተከናወነ አንደበት እያለው እንደ ዲዳ ሆነ። ከምስጋና በቀር ምንም ምን አይናገርም። ሌሊትና ቀንም እግዚአብሔርን አመሰገነ። ዓለምንም እንደ ትቢያና እንደ ጉድፍ ቆጠረው ከክርስቶስ ጋር እንደተሰቀለ ሆነ ልቡናውም ዘወትር ወደ ዓየር የተመሰጠ ነበር። እንዲህ ባለም ገድል ብዙ ዘመን (22ዓመታት) ኖረ። ቁመትንም ካበዛ ወዲህ አንዲቱ የእግሩ አገዳ ተሰበረች ደቀ መዛሙርቱ አንሥተው አክብረው በሰበን ጠቅልለው ከመንበሩ እግር በታች ቀበሯት። ከዚህም ባንዲት እግሩ ሰባት ዓመት ቆመ። ከነዚህም አራቱን ዓመት ውሃው አልጠጣም"። ምንጭ፦ ገድለ ተክለ ሃይማኖት።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #እጨጌ_መርሐ_ክርስቶስ (ዘሸዋ)፡- ትውልዳቸው አገራቸው ሸዋ ሚዳ ሲሆን ለገዳማት ብዙ የደከሙ ታላቅ አባት ናቸው፡፡ በተለይም በእጅጉ የሚታወቁበት አንድ ገድል አላቸው፡፡ ይኸውም እንደ ነዳይ ሆነው ለምነው ያገኙትን ለጦም አዳሪዎች በመመጽወት ይታወቃሉ፡፡ ከባለ ሀብቶች ለምነው ያገኙትን ለድሆች ይመጸውቱትና በቀረው ቤተ ክርስቲያን ይሠሩበታል፡፡ አስደናቂ ገድላቸውና ዐፅማቸው በደብረ ሊባኖስ ይገኛል፡፡ በትግራይም ትልቅ ገዳም አላቸው። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤
❤ #ጥር ፳፫ (23) ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት_ለአንዱ ለሐዋርያው #ቅዱስ_ጳውሎስ_ደቀ_መዝሙሩ (በመንፈስ ልጁ) ለሆነው #ለቅዱስ_ጢሞቴዎስ ለዕረፍት በዓልና ለጻድቁ ንጉሥ #ለቅዱስ_ቴዎዶስዮስ ለመታሰቢያ በዓሉ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከከበሩ ሰማዕታት ከቅዱሳን ጌርሎስና አትናቴዎስ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ጢሞቴዎስ፦ የዚህም ቅዱስ ልደቱና እድገቱ ልስጥራን ከሚባል አገር ነው አባቱም ከዋክብትን የሚያመልክ ዮናናዊ ነው እናቱ ግን በኦሪት ሕግ ጥላ ሥር ያለች ናት። የከበረ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም በልስጥራን አገር በሰበከ ጊዜ ይህ ጢሞቴዎስ ስብቱንና ትምህርቱን ሰማ እግዚአብሔርም በቅዱስ ጳውሎስ እጅ የሚደያደርጋቸውን ድንቆች ተአምራቶችን አይቶ እሊህም ተአምራቶች አስተዋዮችን አይቶ እሊህም ተአምራቶች አስተዋዮችና ጥበበኞች የሚደነግጡባቸው ናቸው ስለዚህም ወደ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ሒዶ በእርሱ ትምህርት በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቆ የሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ደቀ መዝሙሩ ሆነ ወደ ብዙ አገሮችም ተከትሎት በመሔድ ከእርሱ ጋር ደከመ ታላቅ መከራና ብዙ ኀዘንም ደርሶበታል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም በኤፊሶን ውስጥ በአንዲት አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት ሾመው።
❤ በዚያንም ጊዜ ወደርሷ ገብቶ ለሰዎቿ በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ሰበከ ብዙዎችንም ወደ ቀናች ሃይማኖት መልሶ የክርስትና ጥምቀትን አጠመቃቸው ከዚህም በኋላ በዙሪያዋ ወዳሉ ብዙዎች አገሮች በርቀትም ለሚገኙ አገሮችም የከበረ ወንጌልን ሰበከላቸው። የከበረ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ሁለት መጻሕፍቶችን ጽፎ ወደርሱ ልኳል እርሳቸውም ሕዝቡን የሚያስተምርባቸው ራሱም ከቢጽ ሐሳውያን የሚጠብቅባቸው ቅስና ወይም ዲቁና ሊሾም የሚገባውንና የማይገባውን የሚለይበት ክህነት በማይገባው እጁን እንዳይጭን የሚያስጠነቅቁ ናቸው ጢሞቴዎስን ደግሞ ለርሱ ተወዳጅ ልጁ አድርጎ ይጠራዋል መልእክቶቹንም በእርሱ እጅ ወደ አገሮች ልኳል።
❤ በላያቸው የተሾመባቸውን የክርስቶስን መንጋዎች ፈጽሞ በጠበቀ ጊዜ በትምህርቶቹ በተግሣጾቹና በድርሰቶቹ ልቡናቸውን ብሩህ አደረገ አይሁድንና ዮናናውያንን ይገሥጻቸውና ይዘልፋቸው ነበር እነርሱም ቀንተውበት ሁሉም በጠላትነት ተነሡበት ተሰብስበውም ጥር 23 ቀን ገደሉት ምእመናንም ሥጋውን አንሥተው ቀበሩት ጻድቅ ቈስጠንጢኖስም እስከ ነገሠ በዚያው ኖረ እርሱም ስለ ሥጋው አስቦ ወደ ቊስጥንጥንያ ከተማ በጥር ወር በሃያ ሰባት ቀን አፈለሰው በዚያችም ቀን በዓል አደረገለት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያ ቅዱስ ጢሞቴዎስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጥር 23 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለጢሞቴዎስ_ዘተሠይመ_ቀዋሜ። በመልእክተ ጳውሎስ መምህረ ሮሜ። ለዮናናውያን ኮኖሙ ዘላፌ ወለአይሁድ ረጋሜ። እስከ አድምዐ እዴሆሙ ዘስምዐ ሞቱ ፍጻሜ። እንተ ተወሰነ ሎቱ ሶበ በጽሐ ዕድሜ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጥር_23።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወበመንፈስ አዚዝ አፅንዐኒ። ከመ እምሐሮሙ ለኃጥአን ፍኖተከ። ወረሲዓን ይትመየጡ ኀቤከ። መዝ 50፥12-13። የሚነበቡት መልዕክታት 2ኛ ጢሞ 1፥1-10፣ 1ኛ ጴጥ 3፥13-18 እና የሐዋ ሥራ 16፥1-13። የሚነበበው ወንጌል 12፥17-35። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው የቅዱስ ጢሞቴዎስ የዕረፍት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እምክቡዳን አቅርንት ዘእምኔሆሙ። አውልደ ንግሥት ለክብር። ወትቀውም ንግሥት በየማንከ"። መዝ 44፥8-9። የሚነበበው ማቴ 11፥28-ፍ.ም።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ጻድቅሰ ከመ በቀልት ይፈሪ። ወይበዝኅ ከመ ዘግባ ዘሊባኖስ። ትኩላን እሙንቱ ውስተ ቤተ እግዚአብሔር"። መዝ 91፥12-13 የሚነበቡት መልዕክታት ኤፌ 7፥10-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 4፥4-12፣ እና የሐዋ ሥራ 15፥1-4 ወይም 28፥1-11። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 6፥5-19። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ወይም የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ዑራኤልና የሲመት በዓልና የአባ እንጦንስ የዕረፍት ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አሜን"። ❤
❤ #ጥር ፳፪ (22) ቀን።
❤ እንኳን #ለሊቀ_መላእክት_ለቅዱስ_ዑራኤል ለሢመቱ (ለተሾመበት) ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሊቀ_መላእክት_ቅዱስ_ዑራኤል፡- ኢዮር፣ ራማ እና ኤረር የተባሉ ሦስት የመላእክት ከተሞች አሉ፡፡ እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክት ከፈጠራቸው በኋላ በነገድ 100 በአለቃ 10 አድርጎ በሦስቱ ሰማያት አስፍሯቸዋል፡፡ ኢዮርን በ4፣ ራማን በ3፣ ኤረርንም በ3 ከፍሎ ነው በዓሥሩ ከተማ ያሰፈራቸው፡፡
❤ በዚህም መሠረት ኢዮርን ላይና ታች አድርጎ በ4 ከተማ ከፍሏታል፡፡ በእርሷ ያሉትን መላእክትን በ40 ነገድ 4 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያው ነገድ "አጋእዝት" ይባላሉ፡፡ አለቃቸው ሣጥናኤል ነበር፤ እርሱም የመላእክትን ሁሉ ጸሎት ወደ እግዚአብሔር ያሳርግ ነበር፡፡ ከክብሩ ሲዋረድ ቅዱስ ሚካኤል በምትኩ ተሹሞበታል፡፡ ሁለተኛው ነገድ "ኪሩቤል" ይባላሉ፡፡ እነርሱም መንበረ ሥላሴን ይሸከማሉ፡፡ የቀሳውስት አምሳል ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ሰብና ገጸ አንበስ ናቸው፡፡ በሦስተኛው ከተማ በኢዮር ያሉት "ሱራፌል" ይባላሉ፡፡ የዲያቆናት አምሳል ናቸው፡፡
❤ በትንቢተ ኢሳያስ በምዕራፍ 6 ላይ የተገለጹትና ኢሳያስን ከለምጹ እንዲፈወስ ያደረጉት ናቸው፡፡ አለቆቻቸው ገጸ ላህምና ገጸ ንስር ናቸው፡፡ (በነገራችን ላይ "ከሩቤል" ወይም "ሱራፌል" የሚባሉ የግለሰብ መጠሪያ ስሞች ስህተት ናቸው፡፡ አንደኛ እነዚህ ስሞች የብዙ መላእክት መጠሪያን የሚወክሉ ናቸው፡፡ ለአንዱ ሲሆን "ኪሩብ፣ ሱራፊ" ይባላል፡፡ "ኪሩቤል" ወይም "ሱራፌል" ማለት ግን የብዙ ቁጥራቸው መጠሪያ ነው፡፡ ሁለተኛው ምክንያት ደግሞ የቅዱሳን መላእክትን ስም እንዳለ በቁሙ ወስዶ ለግል መጠሪያ ስም ማዋል ተገቢ አይደለም፡፡ "ወለተ ሚካኤል፣ ክብፈ ገብርኤል…." እየተባሉ ይሰየማሉ እንጂ ቀጥታ "ሚካኤል"፣ "ገብርኤል" እያሉ ሰዎችን መሰየም ስህተት ነው፡፡ 4ኛው ከተማ በኢዮር ያሉት ኃይላት ይባላሉ፡፡ የእሳት ሰይፍ ይዘው በሥሉስ ቅዱስ ፊት የሚቆሙ ናቸው፡፡ በመንፈሳዊ ሕይወት የዛሉና የደከሙ ክርስቲያኖችን የሚያበረታቱ ናቸው፡፡ አለቃቸውም ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡
❤ ዳግመኛም እግዚአብሔር በራማ ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ "አርባብ" ይባላሉ፡፡ የሥላሴ እልፍኝ አስከልካዮች ናቸው፡፡ የእግዚአብሔርን መንበር በክንፎቻቸው ይሸፍናሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ገብርኤል ነው፡፡ ሁለተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት "መናብርት" ይባላሉ፡፡ ለእግዚአብሔርን እጅግ ቅርብ የሆኑ ናቸው፡፡ የመብረቅ ጋሻቸውን የእሳት ጦራቸውን ይዘው የሥላሴ ጋሻ ጃግሬዎች ሆነው በተጠንቀቅ ይቆማሉ፡፡ የሰውን ችግር ለእግዚአብሔር ያቀርባሉ፡፡ መዝ 88፡6፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሦስተኞቹ በራማ ከተማ ያሉት "ሥልጣናት" ይባላሉ፡፡ መላውን ፍጥረት ለመጠበቅ ሥልጣን የተሰጣቸውና የምጽአት ዕለት አዋጅ ነጋሪዎች ናቸው፡፡ ዳን 12፡1፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሱርያል ነው፡፡
❤ ዳግመኛም እግዚአብሔር በኤረር ያሉትን መላእክት በ30 ነገድ በ3 አለቃ አድርጎ ከፈላቸው፡፡ የመጀመሪያዎቹ "መኳንንት" ይባላሉ፡፡ የሥላሴ የእሳት ባለ ቀስት ናቸው፡፡ የሰው ልጅ ልዩ ጠባቂዎች ናቸው፤ በተለይ በአደጋ ጊዜ ሎጥን እንዳዳኑት ፈጥነው ይደርሳሉ፡፡ በዕለተ ምጽዓት የሰውን ሁሉ ዐፅም ሰብስበው ለትንሣኤ ዘጉባኤ ያበቃሉ፡፡ አለቃቸው ቅዱስ ሰዳካኤል ነው፡፡ ሁለተኛዎቹ "ሊቃናት" ይላሉ፡፡ የሥላሴ የእሳት ፈረሶች ናቸው፡፡ በእሳት ፈረስ ይመላለሳሉ፡፡ እነዚህም 24ቱ ካህናተ ሰማይ ሲሆኑ አለቃቸው ቅዱስ ሰላታኤል ነው፡፡ በኤረር ከተማ የሰፈሩት ሦስተኛዎቹ "መላእክት" ይባላሉ፡፡ ፍጥረትን ሁሉ የሚጠብቁ ናቸው፡፡ አለቃቸው ቅዱስ አናንኤል ነው፡፡ በእነዚህ የማይጠበቅ ፍጥረት የለም፡፡ ከአዝርእት ጀምሮ ሁሉን ይጠብቃሉ፡፡
❤ ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ "በእግዚአብሔር ፊት የሚቆሙ 7 መላእክትን አየሁ" (ራዕ 8፥2) እንዳለ ሊቃነ መላእክት በቁጥር 7 ናቸው፡፡ እነርሱም፡- ቅዱስ ሚካኤል፣ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቅዱስ ሩፋኤል፣ ቅዱስ ራጉኤል፣ ቅዱስ ዑራኤል፣ ቅዱስ ፋኑኤል እና ቅዱስ አፍኒን ናቸው፡፡ "ዑራኤል" የሚለው ስም "ዑር" እና "ኤል" ከሚሉ ሁለት ቃላት የተመሠረተ ስም ነው፡፡ "ዑራኤል" ማለት ትርጉሙ "የብርሃን ጌታ፣ የአምላክ ብርሃን" ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዑራኤል ከ7ቱ ሊቃነ መላእክት አንዱ ሲሆን ከፍጥረተ ዓለም ጀምሮ በመብረቅና በነጎድጓድ ላይ የተሾመ መልአክ ነው፡፡
❤ በመሆኑም መጽሐፈ ሄኖክ እንደሚገልጸው መባርቅት ለጥጋብና ለበረከት እንዲበርቁ ነጎድጓድም ለሰላም እንዲሆን ያሰማራል፡፡ ምሥጢረ ሰማይንና ሰማያዊውን ዕውቀት ሁሉ ለሄኖክ የገለጸለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ የፀሐይን፣ የጨረቃን፣ የከዋክብትንና የሰማይ ሠራዊትን ብርሃንን የሚመራው ይኸው ገናና መልአክ ነው፡፡ መጽሐፈ ሄኖክ 28፡13፡፡ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለዓለም ቤዛ ሆኖ በተሰቀለ ጊዜ ክቡር ደሙን በብርሃን ጽዋ ተቀብሎ በብርሃነ መነሳንስ በዓለም ላይ የረጨው ይኸው ገናና መልአክ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
❤ ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ ዕውቀት ተሠውሮበት ለነበረው ለኢትዮጵያዊው ሊቅ ለአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫም በእመቤታችን ትእዛዝ ጽዋ ጥበብን አጠጥቶ ሰማያዊውን ምሥጢር የገለጠለት ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ "ዑራኤል የተባለ መልአክ ሊረዳኝ መጣ"፡፡ መጽሐፈ ዕዝራ 2፡1፡፡ አምላካችን እግዚአብሔር የሕይወትና የይቅርታ ዝናም በምድራችን ላይ ያዘንብ ዘንድ እንዲሁም የእርሻችንን አዝመራ በዝናም አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ለምግብነት እንዲበቃ ከፈጣሪ ዘንድ ምሕረትን የሚለምን መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
❤ ሊቁ አባ ጊዮርጊስም በመልአኩ አማላጂነት እጅግ ብዙ ድርሰቶችን የደረሱት መልአኩ ጽዋ ሕይወትን ካጠጣቸው በኋላ ነው፡፡ በመጀመሪያም አባ ጊዮርጊስ የተወለዱት በቅዱስ ዑራኤል አብሳሪነት ነው፡፡ በቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ የተመሠረቱ አብዛኞቹ ቅዱሳት ገዳማት በቅዱስ ዑራኤል መሪነት ነው፡፡ ድርሳኑ ላይ የማይጠቅሳቸው የሀገራችን የከበሩ ቅዱሳት ገዳማትና ቅዱሳን ነገሥታት የሉም፡፡
የብርሃን እናቱ ድንግል ወላዲተ አምላክን ከልጇ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ስትሰደድ መንገድ እየመራ ወደ ግብጽ እና ወደ አገራችንን ኢትዮጵያ ያመጣቸው ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡ እመቤታችንን ከተወደደ ልጇ ጋር በደመና ጭኖ መላ ኢትዮጵያን ካስጎበኛት በኋላ ቅድስት አገራችንን ለእመቤታችን የዓሥራት አገር እንድትሆን ያደረገው መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነው፡፡
❤ መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል በዓመት 3 ዓበይት በዓላት አሉት፡፡ ጥር 22 በዓለ ሲመቱ ነው፡፡ መጋቢት 27 የጌታችንን ክቡር የሆነ ወርቀ ደሙን ለዓለም የረጨበት ነው፡፡ ሐምሌ 22 ቀን ቅዳሴ ቤቱ የሚከበርበትና ለነቢዩ ዕዝራ ሱቱኤል የዕውቀትን ጽዋ ያጠጣበት ዕለት ነው፡፡ ከሊቀ መላእክት ከቅዱስ ዑራኤል እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። አማላጅነቱ አይለየን! በጸሎቱ ይማረን!። ምንጭ፦ ከገድላት አንደበት።
