የቃ/መ/ብ/ቅ/ገብርኤል ቤ/ክ ሐመረ ሕይወት ሰ/ት/ቤት
Open in Telegram
456
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፡-
ፍጥረታትን በማደስ ሕይወትን የማስቀጠል ሥልጣን በዋናነት የእግዚአብሔር ብቻ መሆኑ ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም፤ ይሁን እንጂ ሰውም ሥነ ፍጥረትን በማደስና በማጐስቈል ረገድ ያለው ሚና ቀላል አይደለም፤ ይህም ሰው በምድር ላይ እንዲሠለጥን ወይም ፍጥረትን እንዲገዛና እንዲመራ በፈጣሪ ከተሰጠው ሥልጣን የሚመነጭ ነው፤ ዛሬም ዓለማችን በመታደስ ያይደለ በማርጀት ላይ የምትገኘው ከሰዎች ድርጊት የተነሣ እንደሆነ እንገነዘባለን፤ የአየሩ መለወጥ፣ የበረዶው መቅለጥ፣ የሙቀቱ ማሻቀብ፣ የዝናሙ ማጥለቅለቅ፣ የባሕሩ መናወጥ ወዘተ. እየተፈጠረ ያለው ኃላፊነት ከጐደለው የሰው አጠቃቀም የተነሣ እንደሆነም ተደጋግሞ እየተነገረን ነው፤ እኛም በዓይናችን እያየን ነው፤
ከዚህ በተለየ ደግሞ በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ሰው ምድረ በዳውን ወደ ሐመልማለ ገነት ሲቀይር የሚስተዋልበት ሌላ ገጽታ አለ፤ ይህ የሚያሳየው ሰው በሥነ ፍጥረት ላይ የማደስና የማጐስቈል ብሎም የማጥፋት ሚና ያለው መሆኑን ነው፤ ሰውም እንደሌላው ሥነ ፍጥረት የሚያረጅም የሚታደስም ነው፤ ይህም በብዙ አቅጣጫ ሊከሠት ይችላል፤ ሰዎች በተናጠልም ሆነ በጋራ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ሁለቱንም ማለትም ማርጀትና መታደስን ሊያስተናግዱ ይችላሉ፤ ሰዎች በመንፈሳዊ፣ በኢኮኖሚያዊ በማኅበራዊና በመልካም አስተዳደር ወዘተ. የላቀ ዕድገትን ሲያስመዘግቡ በመታደስ ላይ እንደሆኑ ይታወቃል፤ የዚህ ተቃራኒ የሆነውን ይዘው እየተጓዙ ከሆነ ደግሞ ተቃራኒውን ወይም ማርጀትን እያስተናገዱ እንደሆነ ይታወቃል፤ ነገር ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ ሰዎች በመንፈሳቸውም ሆነ በአእምሮአቸው፣ በነፍሳቸውም ሆነ በአካላቸው በመታደስ እንዲኖሩ እንጂ እርጅና እንዲጫጫናቸው አይፈልግምና “የልባችሁን መንፈስ አድሱ” በማለት ያስተምረናል፤
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት!
የክርስትና ሃይማኖት የመጨረሻው ግብ የፍጥረት መታደስ ነው፤
ይህም ማለት የሃይማኖቱ አስተምህሮ መዳረሻ ከሞት በኋላ ትንሣኤ ከዚያም ፍጻሜና እንከን የሌለው ጣዕመ ሕይወት አለ ብሎ ሰውን ለዘላለማዊ ሕዳሴ ማብቃት ነው ማለት ነው፤
ከዚህ አንጻር የሰው የመጨረሻ ዕድሉ ማርጀት ሳይሆን መታደስ እንደሆነ እንገነዘባለን፤ እግዚአብሔር የሰውንና የፍጥረታትን መታደስ የሚሻው በሰማያዊው ዓለም ብቻ ሳይሆን በምድራዊው ዓለምም ጭምር ነው፤ ለዚህም ነው በየወቅቱ የሥነ ፍጥረትን ውበት እያደሰ የሚመግበን፤ አሁን ትልቁ ጥያቄ የሚሆነው እኛስ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመታደስ ተዘጋጅተናል ወይ? የሚለው ነው፤ ዛሬ እያንዳንዳችን ይህንን ጥያቄ አንሥተን ኅሊናችንን በጥልቀት መጠየቅ አለብን፤ በዚህም ሳናበቃ መልሱን በትክክል ማግኘት አለብን፤ በሁለንተናችን ለመታደስም ቈራጥ ውሳኔ በራሳችን ላይ ማሳለፍ አለብን፤ አዲሱ ዘመን አዲስና ብሩህ የሆነ የደስታ ሕይወት ሊያጐናጽፈን የሚችለው በዚህ መንፈስ ተቀብለን ስንጠቀምበት ነው፤
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት!
እኛ ኢትዮጵያውያን ለብዙ ዘመናት የታደሱ ያይደሉ በርካታ ዓመታት ተጭነውን አልፈዋል፤ ቀድሞ እንበልጣቸው ከነበሩ አህጉር በታች ሆነንም በርካታ ዓመታትን አስቈጥረናል፤ የእርስ በርስ ግጭት፣ ረኃብ፣ ጦርነት፣ ድህነት፣ ኋላ ቀርነት የመልካም አስተዳደር እጦት በዓለም ፊት ልዩ መለያችን ሆኖአል፤ ዛሬም ከዚህ አልተላቀቅንም ብቻ ሳይሆን እንዲያውም አጠናክረን ለማስቀጠል ውል የገባን እስክንመስል ድረስ እየቀጠልንበት እንገኛለን፤ በእውነቱ እንዲህ የመሰለ ልምድ ልናፍርበትና ንስሐ ልንገባበት እንጂ ልናስቀጥለው አይገባም፤
በተፈጥሮ የታደለች ሁሉንም አሟልታ የምትገኝ ኢትዮጵያን የመሰለች ሀገር ይዘን ከሰው በታች ሆነን ስንገኝ በስንፍናችሁ ከምንባል በቀር የሀብተ ጸጋ እጥረት አለባችሁ የሚለን አናገኝም፤
ስለዚህ አሁንም ለኢትዮጵያውያን ልጆቻችን በአጽንዖት የምናስተላልፈው መልእክት ኢትዮጵያ ለኢትዮጵያውን አይደለም ለዓለም የሚተርፍ ሀብተ ጸጋ አላትና ለኔ ለኔ በመባባል የሕዝባችንን ሰቆቃው አናስረዝም፤
ኢትዮጵያ የሁሉም ኢትዮጵያውያን ናት የሚለውን ጥሬ ሓቅ በደምብ አላምጠን መዋጥ አለብን፣ ከዚያም በእኩልነትና በአንድነት ሀገራችንን እናድስ፤ ከሌሎች በደባል የሚመጡ ነገሮችን ሳይሆን የሀገሪቱ በሆኑ ዕሤቶች እንመራ፤ ለበርካታ ዓመታት የተሸከምነው ደባል የአስተዳደር ስልት ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር የሚጣጣም ሆኖ አልተገኘም፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምንም ከማንም በላይ በፈጣሪው እንደሚመካ እሱንም አጥብቆ እንደሚያምን ልኂቃኖቻችን ተገንዘቡልን፤
እኛ ኢትዮጵያውያን ከሦስት ሺሕ ዓመታት በላይ ባስቆጠረ ታሪካችን ከእግዚአብሔር ተለይተን አናውቅም፤ በዚህም ተጠቃሚዎች እንጂ ተጐጂዎች የሆንበት ጊዜ የለም፤ በለመደው እምነት ባህልና ዕሤት ሕዝቡን ብንመራው ሁሉም ነገር ቀላል ይሆንልናል፤ ከዚህ ውጭ እንምራህ ብንለው ግን ያጋጠመንን ችግር ማስቀጠል ነው የሚሆነው፤ ስለዚህ የሁሉም መነሻ ማለትም የክፋትም ሆነ የደግነት መነሻ ውሳጣዊ አእምሮአችን ነውና እሱን በማደስ በአዲሱ ዓመት አገራችንን እንድናድስ በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡
በመጨረሻም
አዲሱ ዘመን በሃይማኖት መንፈስ ግጭትን በውይይት፤ መለያየትን በአንድነት፤ አለመግባባትን በዕርቅ ፈትተን በመታደስ ማማ ላይ የቆመ ማኅበረ ሰብን ለመገንባት ሁላችንም ጥረት እንድናደርግ በእግዚአብሔር ስም መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡
አዲሱ ዓመት የሰላም የዕርቅ የእኩልነትና የአንድነት ያድርግልን፡፡
እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!
አሜን::
አባ ማትያስ ቀዳማዊ
ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም
ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
መስከረም 1 ቀን 2017 ዓ.ም.
አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
Repost from የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት -EOTC GSSU
በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ ወደ ትግበራ ስለገባው ወጥ የሰንበት ት/ቤቶች ሥርዓተ ትምህርትና መዋቅር የመመሪያ አቅጣጫ እንዲሁም የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር ተካሔደ ።
(የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት) ነሐሴ 20 /12/2016 ዓ.ም
በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ ወደ ትግበራ ስለገባው ወጥ የሰንበት ት/ቤቶች ሥርዓተ ትምህርትና መዋቅር የመመሪያ አቅጣጫ እንዲሁም የግንዛቤ ማስጨበጫ መርሐ ግብር የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ማእምራን የማነ ዘመንፈስ ቅዱስ፤ ሀገር አቀፍየሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ተ/ም/ሰብሳቢ ዲ/ን ስንታየሁ ምስጋናው፤ የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ተ/ም/ሰብሳቢ ላዕከ ኄራን መንክር ግርማ ና የሚመለከታቸው አካላት በተገኙበት ዛሬ ነሐሴ 20 በዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት መሰብሰቢያ አዳራሽ ተካሒዷል።
የግንዛቤ ማስጨበጫው የተሠጠው በአ.አ ውስጥ ለሚገኙ አቢያተ ክርስቲያናትና ገዳማት አስተዳዳሪ ፣ ጸሐፊ ፣ የሰበካ ጉባኤ ም/ሊቀ መናብርት ፣ የስብከተ ወንጌል ሓላፊዎችና ለሰንበት ት/ቤት ሰብሳቢዎች ነው። በመርሐ ግብሩም የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ተ/ም/ሰብሳቢ ላዕከ ኄራን መንክር ግርማ ከመንበረ ፖትርያሪክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የሰንበት ቤቶች አንድነት እስከ አጥቢያ ሰንበት ት/ቤት ድረስ ያለውን መዋቅር ፤ የሰንበት ት/ቤቶች ጠቅላላ ጉባኤ በበዓለ ጰራቅሊጦስ እንደሚካሔድ በዚያ የሚተላለፉ መመሪያዎች ተግባራዊ እንደሚሆኑ፤ የሰንበት ት/ቤቶች የውስጥ ደንብ በሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጸድቆ ወደታች እንደሚወርድ እንዲሁም የሰንበት ት/ቤቶች የምርጫ ጊዜ በተመሣሣይ ወቅት እንደሚሆን ለተሣታፊዎች ገለፃ አድርገዋል። በመቀጠልም የሀገር አቀፍ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ተ/ም/ሰብሳቢ ዲ/ን ስንታየሁ ምስጋናው ስለ ሥርዓተ ት/ት ገለፃ ሲያደርጉ ሥርዓተ ትምህርቱ የዕድሜ ደረጃቸውን ያማከለ እንደሆነና ከ1ኛ-12ኛ ክፍል በ6 ክፍላተ ትምህርትና 1 አጋዥ ክፍለ ትምህርት የተከፋፈለና እንደሆነ አስረድተዋል። ከ1ኛ-4ኛ ክፍል ያሉት 23 መጽሐፍት በ4 ጥራዝ በ13ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ላይ ማስመረቁ ይታወሳል። በቀጣይም የቀሩትን መጻሕፍት ለማሳተም ዕቅድ መያዙን እንዲሁም ከሊቃውንት ጉባኤ ጋር የአርትዖ ሥራ እየተደረገባቸው እንደሆነ አስረድተዋል። አያይዘውም የመማሪያ ቦታ ፣ መምህራን ና መጽሐፍቱ ለሥርዓተ ትምህርቱ ትግበራ ጉልህ ድርሻ እንዳላቸውና ይሄንን ማሟላት የሁሉም ባለ ድርሻ አካላት ተግባር ሊሆን እንደሚገባ ገልጸዎል።
በመጨረሻም የዐዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ማእምራን የማነ ዘመንፈስቅዱስ" ሰንበት ት/ቤት የቤተ ክርስቲያን ናትና የሰንበት ት/ቤት ዓባላትም ቤተክርስቲያኒቱን በሓላፊነት መምራትና መቆጣጠር ይገባቸዋል ፤ የሰበካ ጉባኤ ዓባላትም ከሰ/ት/ቤቶች ጋር በመመካከር መሥራት ይኖርባቸዋል።" ብለዋል አያይዘውም " የአጥቢያው ሰበካ ጉባኤ ከ1-4 ኛ ክፍል ያሉትን መጽሐፍት ከየአንዳንዱ ስድስት ስድስት መጽሐፍት ለሰንበት ት/ቤቶቹ እንዲገዙ" መመሪያ አስተላልፈዋል። ከተሣታፊዎች ለተነሱ ጥያቄዎችም መልስ ተሰጥቶባቸው ጉባኤው ተጠናቋል።
(የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት)
የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት የማኅበራዊ የትስስር ገጾችን ቤተሰብ ይሁኑ!
👉 Youtube
👉 Facebook
👉 Telegram
👉 Tiktok
#ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን እረፍት ሲያስቡት ሊቃውንት አባቶቻችን “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ፣ ሞታ ለማርያም የአጽብ ለኩሉ” “መዋቲ ለሆነ ሰው ሞት ይገባዋል የማርያም ሞት ግን ለሁሉም ይገርማል” ይላሉ፡፡ ይህስ እንደምን ነው ቢሉ፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በ64 ዓመቷ በጥር በ21 ቀን በ49 ዓ.ም አርፋለች፡፡ ጥር ልደታ ሰኞ ነበር፣ ስምንት፣ አስራ አምስት፣ ሃያ ሁለት እያለ ሰኞ ላይ ይውላል፡፡ እመቤታችን እሁድ በ21 አርፋለች፡፡
ቅዱሳን ሐዋርያት በአጎበር አድርገው ሊቀብሯት ሲሔዱ፣ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉምና ከዚህ ቀደም ልጇን ተነሳ አረገ እያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ፡፡ አሁን ደግሞ እሷን ተነሳች አረገች እያሉ ሊያወርኩን አይደለምን? ለምን ስጋዋን በእሳት አናቃጥለውም ብለው ተነሱ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም ተራምዶ አጎበሯን ቢይዘው መልአክ ሁለት እጁን በሰይፍ ቀጣውና ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡ ኋላም ማረው ብላ እመቤታችን አማልዳው መልሶለታል፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱሳን ሐዋርያት ደንግጠው ተበታተኑ፡፡
እመቤታችንንም ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር ነጥቆ በገነት አኖራቸው፡፡ ቆይቶ ዮሐንስን አግኝተው የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ አሉት። እርሱም በገነት ከእፀ ሕይወት ስር አለች አላቸው፡፡ እነርሱም ዮሐንስ ይህን ድንቅ ነገር አይቶ እኛ ሳናይ ቀረን ብለው በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፡፡ ነሐሴ እንደ ጥር ሁሉ ሰኞ ነው የሚብተው፡፡ ከሰኞ እስከ ሰኞ 8፣ ከሰኞ እስከ ሰኞ 15 ይሆናል፡፡ እሁድ በ14 ጌታችን ቅዱስ ስጋዋን ሰጥቷቸው ቀብረዋታል፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ አልነበረም፡፡ ከሦስት ቀን በኋላ በ16 እንደ ልጇ ከሙታን ተነስታ ስታርግ እርሱ ከሀገረ ስብከቱ በደመና ሲመለስ አገኛት፡፡ በጣም አዘነ፣ ተበጸበጻ “እንደኔ ያለ እድለ ቢስ ማን አለ ቀድሞ የልጅሽን የጌታዬን ትንሳኤ ሳላይ ቀረሁ አሁን ደግሞ ያንቺን” በማለት ከሚጓዝበት ደመና ሊወድቅ ቃጣው፡፡ እመቤታችንም “አይዞህ አትዘን ወንድሞችህ ትንሣኤዬን እርገቴን አላዩም አንተ ግን አይተሃል፤ እመቤታችን ተነሳች አረገች ብለህ ንገራቸው” ብላ የያዘችውን ሰበን (መግነዝ) ሰጥታ ሰደደችው፡፡
እርሱም ሐዋርያትን ሲያገኛቸው “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው፡፡ “አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ “ተው ይህ ነገር አይመስልም ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር?” ሲላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ ተቆጥቶ አንተ ወትሮውንም መጠራጠር ልማድህ ነው፣ ብቻህን ተጠራጥረህም አትቀርም ሌላውንም ታጠራጥራለህ ብሎ ወደ መቃብሯ እየሮጠ ሔዶ ቢከፍተው አጣት፤ ደንግጦ ቆመ፡፡ ቶማስም አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሳች አረገች አላቸው፡፡
እነርሱም በዓመቱ ቶማስ ትንሳኤሽን እርገትሽ አይቶ እኛ ሳናይ ቀረን ብለው በነሐሴ አንድ ቀን ጾም ጀምረው ሁለት ሱባኤ ጾመው በአስራ አምስት አጠናቀዋል፡፡ በትንሣኤዋ ቀን በ16 ጌታችን እርሷን መንበር አድርጎ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካሕን ቅዱስ እስጢፋኖስን ገባሬ ሰናይ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ አቁርቧቸዋል፡፡ እርሷንም እንዲህ አድርጎ አክብሯታል፡፡ ሊቃውንት አባቶች “ወተቄረበት በእደ ወልዳ” እንዲሉ እርሷም በልጇ እጅ ቆርባለች፡፡
ቅዱሳን ሐዋርያት ከአንዴም ሁለቴ የጾሙትን ጾም አብነት አድርገን በረከታቸው እንዲያድርብን የእመቤታችንን ጾመ ፍልሰታ እንጾማለን። በተለይ ገዳማውያን አባቶች የስጋቸውን ጉዳይ ትተው ዓለምን ንቀው መንነዋልና ሁሌም ቢሆን በጾም ይኖራሉ። እኛ በቅበላውም በጾም ፍቺውም ከመብሉም ከመጠጡም ከልክ በላይ እንደፈለግን ስንሆን እነርሱ ግን እጅግ በሚያስቸግር ሁኔታ ውስጥ ሆነው፣ የገዳሙ ህልውና አደጋ ላይ ወድቋል። ካለን ከፍለን ልንደግፋቸው ይገባል።
የንግስተ ሰማይ ወምድር ልመናዋ፣ ክብራ፣ የልጇ የወዳጇ ቸርነት በኛ ላይ አድሮ ይኑር አሜን!!!
የብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያክ ፲፪ኛ የዕረፍተ ሥጋ የመታሰቢያ ጸሎተ ፍትሐት በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል እየተከናወነ ይገኛል።
የ2016ዓ.ም የሰንበት ትምህርት ቤቶች የ12ኛ ክፍል የሞዴል ፈተና የፊታችን ቅዳሜና እሑድ እንደሚሰጥ ተገለጠ።
(የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት) 25/11/2016ዓ.ም
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፖትርያርክ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት በሀገር አቀፍ ደረጃ ለ2ኛ ጊዜ የሚሰጠው የ12ኛ ክፍል ማጠቃለያ ፈተና የሞዴል ፈተና ለመስጠት ዝግጅቱን ማጠናቀቁን ገለጠ።
በሥርዓተ ትምህርቱ መሠረት እየተማሩ 12ኛ ክፍል ለደረሱ በአዲስ አበባና ከአዲስ አበባ ውጪ ላሉ ሀገገረ ስብከቶች ሥር ለሚገኙ አጥቢያ ሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ሐምሌ 27 እና 28 2016 ዓ.ም ፤ የሚሰጥ እንደሆነ የሀገር አቀፍ የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ትምህርት ክፍል ሓላፊ መምህር መኩርያ ጌታቸው ገልጠዋል።
አያይዘውም የማጠቃለያ ፈተናው በተመረጡ የፈተና ጣቢያዎች ነሐሴ 18 እና 19/2016 ዓ.ም እነደሚሰጥ ተናግረዋል።
(የሰ/ት/ቤቶች አንድነት)
Repost from የቃ/መ/ብ/ቅ/ገብርኤል ቤ/ክ ሐመረ ሕይወት ሰ/ት/ቤት
መልእክቱን ያጋሩ ሌሎችን ይጋብዙ። ከላይ በተዘረዘሩት መንገዶች መመዝገብ ይችላሉ።
https://t.me/+54ijITEXeIdjNTNk
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የማጽናኛ መልእክት አስተላለፉ።
“ምንም እንኳ የመከራ ድሀ ባንሆንም ይህ መከራ ለነጋሪውም ለሰሚውም ከባድ መሆኑን እንገነዘባለን ። “
++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++
በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን !
“እግዚኦ ሚ በዝኁ እለ ይሣቅዩኒ፦አቤቱ፥ የሚያስጨንቁኝ ምንኛ በዙ ! ”
(መዝ. 3፡1)
አባታዊ የማጽናኛ መልእክት
በጎፋ ዞን፣ በገዜ ጎፋ ወረዳ፣ ኬንቾ ሻቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት ናዳ እጅግ ብዙ የሚሆኑ ወገኖቻችን በመሞታቸው ታላቅ ኀዘን ተሰምቶናል ። ምንም እንኳ የመከራ ድሀ ባንሆንም ይህ መከራ ለነጋሪውም ለሰሚውም ከባድ መሆኑን እንገነዘባለን ።
ይሁን እንጂ ጭንቀታችን ብዙ ቢሆንም እግዚአብሔር መልካም የምንሰማበትን ዘመን እንደሚያመጣ ተስፋ እናደርጋለን ።
በተለይም ደግሞ እኛ ክርስቲያኖች በወገኖቻችን መጎዳት ብናዝንም በትንሣኤ ሙታን ስለምናምን የምጽናና በመሆኑ የሞቱት ልጆቻችን ዕረፍተ ነፍስ እንዲያገኙ እየጸለይን፤ የመከራው ገፈት ቀማሽ ለሆኑት የአካባቢው ማኅበረሰብእ ሁለንተናዊ ድጋፍ በማድረግ ሁሉም አቅሙ በፈቀደው መጠን እንዲደርስላቸው ስንል አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን።
እግዚአብሔር አምላክ ለቤተሰቦቻቸውና ለሕዝቡ መጽናናትን ይስጥልን፤ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!!
አሜን።
አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ
ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም
ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ሐምሌ 17 ቀን 2016 ዓ.ም. ዋሽንግተን ዲሲ~ አሜሪካ
