ማዕደ ፡ ጥበብ | Banquet of Wisdom
Open in Telegram
“ለንባብ ክብርን ስጥ። ራስኽን ለንባብ አስገድድ። ከቻልኽ ፥ ከምትጸልየው አስበልጠኽ አንብብ። የጥሩ ጸሎት ምንጩ ንባብ ነውና" (አቡነ ቄርሎስ ፮ኛ)
Show more1 394
Subscribers
-124 hours
+27 days
+2030 days
Posts Archive
+• ውሃ የሚያናውጥ መልአክ •+
በጥንት ዘመን በኢየሩሳሌም ውስጥ በሽታ የጸናበት ሰው ሁሉ የሚናፍቃት አንዲት መጠመቂያ ነበረች። ይህቺ መጠመቂያ ጤናማ ሰው ቢመለከታት የተለየ ነገር ላያይባት ይችላል። ታሞ ያያት ሁሉ ግን በውስጧ የመዳን ተስፋን ያይባታል። ስሟ ቤተ-ሳይዳ ይባል ነበር። በዚህች መጠመቂያ ቦታ ደዌ የበረታባቸው ሁሉ በዙሪያዋ ቁጭ ብለው አንዳች ነገር ይጠባበቃሉ።
ይህ የሚጠባበቁት አንዳች ነገር የውሃውን መናወጥ ነበር። ሰላምና የተረጋጋ የነበረው ውሃ ድንገት ከተናወጥ፥ አካባቢው በአንዴ ይረበሻል። ሁሉም ይሯሯጣል። እድል ቀንቶት መጀመሪያ የገባ ካለበት በሽታ ሁሉ በአንዴ ይፈወሳል። የመዳን ሎተሪ እንደማለት ነው። ለአንድ ሰው ብቻ ይወጣል። ሐኪም ቤት ለመታከም ሄደን ቀድሞ የደረሰው ሰው ብቻ ታክሞ ቢድን፥ ሌላው ሁሉ ወደ ቤቱ ቢሸኝ ማለት ነው። ለአንዱ ፈንጠዚያ፥ ለሌላው ግን እንደገና ሌላ የመዳን ጥበቃ።
ውሃው ግን የሚናወጠው በተፈጥሮ ምክንያት አልነበረም። የዮሐንስ ወንጌል "አንዳንድ ጊዜ የጌታ መልአክ ወደ መጠመቂያይቱ ወርዶ ውኃውን ያናውጥ ነበርና" (ዮሐ 5፡4) ይለናል። ለመሆኑ ይህ ውሃውን የሚያናውጥ መልአክ ማነው? በዚህ ዙሪያ ሁለት ምልከታዎች አሉ። አንዱ ወገን መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ነው ሲል ሌላው ደግሞ ቅዱስ ሩፋኤል መሆኑን ይገልጻል።
ከሁለቱ ትውፊቶች ምናልባትም "ቅዱስ ሩፋኤል ነው" የሚለው ቢያመዝን ስንኳ የሚገርም አይሆንም። ቅዱስ ሩፋኤል ብዙ ነገሩ ከፈውስ ጋር የተጣመረ ነው። ሊቃውንት ስሙን ሲተረጉሙት "ደስ የሚያሰኝ፣ ቸር፣ መሐሪ፣ ቅን የዋህ" ብለው ቢሆንም፥ የዕብራይስጡ የስሙ ፍቺ ግን የመልአኩን እውነተኛ ማንነት ይበልጥ አጉልቶ ያሳያል። በዕብራይስጥ ስሙ ራፋኤል (רָפָאֵל) ሲሆን፥ የስሙ ዋና ሥር የሆነው ረፈአ (רפא) እንደ ግሥ ስንጠቀመው "ፈውስ" ማለት ነው። በመሆኑም ራፋኤል የሚለው ስም ፍቺ "እግዚአብሔር ፈወሰ" ወይም "እግዚአብሔር ፈውሷል" ማለት ይሆናል።
በአንድ የጥንት የአይሁድ ትውፊት ላይ አብርሃም ከተገረዘ በኋላ እግዚአብሔር ቁስሉን ይፈውስለት ዘንድ ቅዱስ ሩፋኤልን እንደላከለት ያትታል። መጽሐፈ ሄኖክም ስለዚህ መልአክ "በበሽታ ሁሉ ላይ በሰው ልጆችም ቁስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው"(ሄኖ 10፡13) በማለት ይገልጻል። ሊቃውንትም ሕሙማንን የሚፈውስ (ፈዋሴ ዱያን) ይሉታል። እንግዲህ "ውሃውን እያናወጸ ሰዎች እንዲፈወሱ ያደርግ የነበረው ቅዱስ ሩፋኤል ነው" ቢባል የማይገርመው ለዚያ ነው፤ እንዲያውም ከስሙም ሆነ ከግብሩ የሚስማማ ይሆናል።
ቅዱስ ሩፋኤል ሆይ፥ የእኛ ደዌ ለሠላሳ ስምንት ዓመት ከተኛው ከመጻጉዕ ይጸናል። በቤተሳይዳ ከተሰበሰቡት ድውዮች ሕመምም ሁሉ ይከፋል። የእነርሱ ደዌስ ለራስና ለአስታማሚ ብቻ ተረፈ። የእኛ ውስጣዊ ደዌ ግን መዘዙ ለሀገር ሁሉ ሆነ። ታላቁ መልአክ ሆይ፥ በተሾምህባት በዚህች ዕለት፥ የተጨነቁትን ነፍሳት ሁሉ አስብ። ደመናቱን አናውጸህ፥ ዝናቡንም ባርከህ በጠበልነቱ ክፉ በሽታችንን ፈውስልን።
🖋 Fresenbet G.Y Adhanom
« ያልታጠበቀው የምርመራ ውጤት »
አንድ እኅቴ ያጋራችኝን ይህን እውነተኛ ታሪክ ለመፖሰት ለስድስት ወራት አቅማማሁ በእውነት። ነገር ግን "ፖስተው! ለብዙዎች መማሪያ ይኾናል!" የሚለውን ድምጽ ማሸነፍ አልቻልሁም። ምንም ስጽፈው እየከበደኝ ቢኾንም እንዲህ ልፖስተው ወደድሁ። አንባቢ ሆይ! ይቅርታ አድርግልኝ!
ልጅቱ የሰባተኛ ክፍል ተማሪ እያለች ነበር ያለ ልማዷ አልፎ አልፎ ጠዋት ጠዋት ማቅለሽለሽና ትውኪያ የጀማመራት። ለጥቂት ቀናት እንዲሁ
ቸላ ብላው ትታው ነበር። ሲደጋገም ግን ለመመርመር ወሰነች። የምርመራው ውጤት ግን ጆሮን ጭው የሚያደርግ ዜና ነበር፦
“ነፍሰ-ጡርነሽ!” የሚል ዜና!
ከማንም ወንድ ጋር ደርሳ አታውቅም ነበርና እጅግ ተጨነቀች። ‘ምን ጉድ ነው? ምን አግኝቶኝ ነው’ እያለች ዕለት ዕለት እጅግ ትጨነቅ ጀመር።ለወላጆቿስ ምን ብላ ትናገር? ያው ልሸሽገው ብትል ሆድ ሲገፋ መታወቁ አይቀርምና ልትናገር ወሰነች። ነገር ግድ ድፍረቱ አልነበረምና በጓደኛዋ በኩል ለማሳወቅ ወሰነች።
ጓደኛዋን ጠርታ ጉዳዩን አስረድታ ለአባቷ ትነግራለት ዘንድ መማለድ ጀመረች። እርሷም ተስማማች። አባቷንም ጠርታ እየተንተባተበች ነገሯን ጀመረች፦
“አባ! ልጅህ…”
“ልጄ ምን?
“ነ ፍ ሰ ጡ ር ናት”
የሰማውን ማመን አልቻለም። አንገቱን ደፍቶ እጁን በራሱ ላይ ጭኖ “ያገር ያለህ!” ነበር ያለው። ቀጥታ ልጁ ወደ ተኛችበት ክፍል ያመራል። “ከማንም ጋር ተጋድመሽ … ተሸክመሽልኝ መጣሽ አይደል?” እያለ ከተኛችበት አንቆ እያንጠለጠለ በተደጋጋሚ አልጋው ያፈርጣት ጀመር።
“ኧረ አባ! ኧረ አባ! ከማንም ጋር አልተኛሁም! እኔም ምን እንደተፈጠረ
አላውቅም” እያለች ከዕንባ ጋር ትማጸናው ጀመር
“ቀልድሽ ይቆየኝ!”
“ኧረ ቀልድ አይደለም! የምሬን ነው!”
ጥቂት ቀናት ነጎዱ። አባትዬው በንዴት እንደጦፈ ነው። ከጊዜ በኋላ ግን ከመረጋጋት ውጭ አማራጭ አልነበረውምና ሰከን እያለ መጣ። ልጅቷ ሆዷ እየገፋ እየገፋ እየመጣ ነው። የመውለጃዋ ቀንም ቀረበ።
የምጧ ቀንም በደረሰ ጊዜ ልትወልድ ሆስፒታል ገባች። ነገር ግን
ሐኪሞች አንድ ነገር አስተዋሉ፦
ድንግልናዋ እንዳለ ነበር።
ግራ ተጋቡ። ለአባቷም ነገሩን አሳወቁት። ግራ ተጋባ። ነገሩን ለማጣራት ከወሊድ በኋላ ቀጠሮ ያዘ። ብቻ ለጊዜው ድንግልናዋ በሕክምና መሳሪያእንዲወገድ ተደረገና ልጇን በሠላም ተገላገለች።
ከቀናት በኋላ አባቷ ሕሊናውን ሲከነክነው የነበረውን አንድ ጥያቄ ልጁን ጠርቶ ጠያቃት፦
“እኔ የምልሽ ፥ ከወንድምሽ ጋር ፓንት ትጋራላችሁ እንዴ?”
“አዎ!”መልሷ ነበር።
ጥርጣሬ ገባው። ወንድ ልጁን ጠርቶ፦
“ሕልመ ሌሊት አግኝቶህ ፓንትህን ወዲያው ነው የምታጥበው ወይስ ይቆያል?”
“ለቀናት ይቆያል” ምላሹ ነበር።
“ከማንም ጋር አልተኛሁም!” ከሚለው የሴት ልጁ ቃል ጋር ተደምሮ ጥርጣሬው እየገዘፈ መጣ። እናም የልጇንና የወንድ ልጁን ዘረ-መል (DNA) ለማስመርመር ወሰነ። አደረገውም። የምርመራውን ውጤት ሲያይ ግን ዐይኑን ማመን አልቻለም፦
የልጁ አባት ወንድሟ ነበር። አባቱም አጎቱም ወንድሟ!
ድጋሜ ሌላ የልብ ሥብራት። ከጠላት ሰይጣን ውጭ በማን ይፈረዳል? እርሷ አጠፋች ወይስ ወንድሟ? ልጆቹ ጋርም የሚደርሰውን የልብ ስብራት አስቡት! በተለይ ሴት ልጁ ላይ!ልጁ ጤናማ መኾኑ ግን ተመስገን ነው።ይኼም የእግዚአብሔር ምሕረት ነው! ብዙ ጊዜ እንዲህ ያለ ፅንስ የአእምሮ ጤና እክል ይገጥመዋልና።
ዘወር ብላ ስታስታውስ በአንድ ወቅት ረጠብ ያለ የወንድሟን ፓንት አግኝታ ያለ ማስተዋል ለብሳው ነበር። ሕልመ ሌሊት አግኝቶት ያስቀመጠውን ፓንት መኾኑ ነው። ይህ ከኾነ ከአንድ ከኹለት ወራት በኋላ ነበር ማቅለሽለሹ የጀመረው።
እኅቴ ታሪኩን ነግራኝ እንደጨረሰች ውስጤ አንድ ጥያቄ ይመላለስ ጀመረ፦
“እግዚአብሔር እንዴት እንዲህ ያለውን መከራ ቤተሰቡ ላይ ፈቀደ?” የሚል። ወዲያውም አንድ ጥቅስ ውስጤ ብልጭ አለልኝ፦
«በመጠን ኑሩ ንቁም ፥ ባላጋራችሁ ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ እንደሚያገሣ አንበሳ ይዞራልና» (፩ኛ ጴጥ. ፭ ፥ ፰) የሚለው።
ከዚያም ወዲያው እኅቴን ስለቤተሰቡ መንፈሳዊ ሕይወት ጠየቅኋት። እርሷም መልሳ፦
“ጾም ጸሎት አይደለም። ቤተ- ክርስቲያን አያውቁም” አለችኝ።
እግዚአብሔር ፈረድህ አይበለኝና እኔም በልቤ “ምናልባት ለዚያ ይኾናል” አልሁ። አያይዛም፦ “ልጁ ከተወለደ በኋላ ግን ልጁን ይዞ ቤተ - ክርስቲያን መኼድን ያዘወትር ጀመረ” አለችኝ።
ወዳጄ! አንድ ነገር አፌን ሞልቼ ልንገርህ፦ቤተ-ክርስቲያን መመላለስህ ብቻ ከብዙ መከራ ይጠብቅኻል! ከእንዲህና መሰል ጆሮን ጭው ከሚያደርጉ ፈተናዎች ይታደግኻል! ጾም ጸሎቱ ስግደት ምጽዋቱ ሲጨመርማ እንዴት ይታደግ ይኾን?!
አምላካችን ሆይ! እንደ ቸርነትህ ነው እንጂ እንደ በደላችን አይኹን!
✍️ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
ያነበብሁት ዕለት ውስጤን ዘልቆ የነካው ታሪክ ነበር። በድጋሜ ድንገት አእምሮዬ ላይ ብልጭ አለብኝና እንዲህ ላስታውሳችሁ ወደድሁ፦
❝ ባለጸጋው ሮክፌለር ❞
በዓለም ታሪክ ውስጥ ከሚጠቀሱ ታላላቅ ከበርቴዎች መኻከል አንዱ ነው። በሠላሳ ዓመቱ በአሜሪካ የመጀመሪያው ሚሊየነር ነበር። የዘይት ማቀነባበሪያ ፋብሪካ ባለቤት ነው። በዚኹ ቢዝነስ ተሳክቶለት በኀምሳ ዓመቱ በአሜሪካ ታላቁ ከበርቴ እርሱ ነበር።
በወጣትነት ዘመኑ ፥ ውሳኔዎቹ ፣ አመለካከቶቹ ፣ ግንኙነቶቹ ኹሉ ግላዊ ሀብትን ማከማቸት ላይ ነበር የተመሠረቱት። ይኽ ግን የቀጠለው ኀምሳ ሦስት ዓመት እስኪሞላው ድረስ ብቻ ነበር።
ኀምሳ ሦስተኛው ዓመቱ ላይ ግን ታሪክ ተቀየረ። በአሜሪካ የመጀመሪያው ቢሊየነር በኾነበት በዚኽ ዓመት ሕይወት ፊቷን አዞረችበት። በከባድ ሕመም ተያዘ። መላ ሰውነቱ በሕመም ተመታ። የራስ ጸጉሩ ኹሉ ከዳው። ያሻውን አማርጦ ይበላ ይጠጣ የነበረው ይኽ ባለጸጋ ከሾርባና ከቁራሽ ዳቦ ውጭ አልቀመስልኽ አለው። እንቅልፍ ኹሉ እምቢ አለው። እንዲያውም አንድ የቅርቡ ሰው እንደጻፈው ከሕመሙ ጽናት የተነሣ ፥ ፈገግ ማለት እንኳን ተስኖት ነበር።
እነዚያ ጊዜያት ማለት ለእርሱ ሕይወት ትርጒም ያጣችበት ጊዜያት ነበሩ። ምንም ምን አልጥምኽ አለው። የበቁ የነቁ የግል ዶክተሮቹም በዓመት ውስጥ የሕይወቱ ፍጻሜ እንደሚኾን ተንብየው ነበር።
በአንድ ሌሊት ግን ታሪክ ተቀየረ። እንዲኽ ኾነ፦ እንቅልፍ እምቢ ብሎት ከሕመሙ ስቃይ የተነሣ እያጣጣረ ሳለ ብቸኛ ተስፋው ወደኾነው ወደ አምላኩ በጸሎት ተመለሰ። ለጸሎቱም መልስ በሕልም ምላሽን አገኘ። እንዲኽ የሚል ድምጽንም ሰማ፦
“በምድር ያኸማቸኸው ሀብት ኹሉ
በገነትም ኾነ በሲኦል ምን ምን
አይረባህም። ሥራኽና ሓላፊነትኽ
ለሌሎች ጥቅም ይኾን ዘንድ
በዚኽ ምድር በትነኸው ትኼድ
ዘንድ ነው”
በሕልሙ ተግሣጽ ልቡ የተነካው ሮክፌለር ከሀብቱ ኹሉ ቅንጣቷን እንኳን ወደ ቀጣዩ ዓለም ይዞ መኼድ እንደማይችል ልብ አደረገ። በማግስቱም የሥራ ባልደረቦቹን ሰብስቦ ተግሣጹን እውን ያደርገው ዘንድ ተነሣ። አብዛኛውን የሀብቱ ክፍል ለበጎ አድራጎት ድርጅቶች መስጠት እንደሚፈልግ ነገራቸው። እነርሱም ሓሳቡን ተቀብለው ወደ ትግበራው ገቡ። በስሙ ፋውንዴሽን አቋቋሙ።
በሀብቱ እጅግ ብዙ ሆስፒታሎች ፣ የጥናት ማዕከላት (Research centers)ና የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ተደገፉበት። ይኽ ተግባሩ ከእርሱ አልፎ ለዓለም ታላላቅ የመድኃኒት ግኝቶችን አበረከተ፦ ፔንስሊን ፣ የወባ መድኃኒቶች ፣ የ ‘ቲቢ’ መድኃኒቶችና ሌሎች በርካታ የመድኃኒት ግኝቶች የተገኙት በእርሱ ድጋፍ በበረቱ የጥናት ተቋማት ጥረት ነበር። ሮክፌለር በአጠቃላይ ከ $500 ሚሊዮን ዶላር በላይ ለእነዚኽና መሰል ተቋማት ለመለገስ በቅቷል። ይኽን ያኽል እንኳን ሰጥቶ ሀብቱ አልጎደለበትም ነበር፦ ሮክፌለር ሀብቱን በሰጠው ቍጥር የበለጠ ይበዛለት ነበር እንጂ!
የጤናውስ ጉዳይ እንዴት ኾነ? ታሪኩ እዚኽ ላይ አላበቃም። ምናልባት ከታሪኩ ኹሉ የሚደንቀው ይኽ ነበር፦ መስጠት ሲጀምር የሰውነቱ ኬምስትሪ በሚገርም ፍጥነት እየተሻሻለ ነበር። ጤናው በአስገራሚ ኹኔታ ይመለስ ጀመረ። በመስጠት ውስጥ ያገኘው ‘አእምሮንም ኹሉ የሚያልፍ የእግዚአብሔር ሠላም’ና የውስጥ እርካታ ሰውነቱን እያከመው ነበር። የፈወሰው እርሱ ነበር።
የውስጡ መፈወስ ነበር ለሚታየው ሰውነቱ ፈውስ ምክንያት የኾነው። መ‘ፈወስም ብቻ አልነበረም። ፍጹም ጤነኛም ኾነ እንጂ። በዓመት ውስጥ በሞቱ አልጋ ላይ ሲጠባበቁት የነበሩት ዶክተሮቹ ምናልባት በመሞት ሳይቀድሙት አልቀረም - ሮክፌለር ከዚያ በኋላ አርባ አምስት ዓመታትን ኖረ! በመጨረሻዎቹ ዓመታቶቹም በውሎ ማስታውሻው እንዲኽ ብሎ ነበር፦
❝እግዚአብሔር ይኽንን አስተማረኝ -
ኹሉም ነገር የእርሱ እንደኾነ! እኔም
እንዲኹ የእርሱን ሓሳብና ዓላማ
ለማስፈጸም የተሰየምኹ አንድ
ግለሰብ እንደኾንኩ!
የሕይወቴ ጉዞ ረጅም ፥ ዳሩ ግን
ፍሥሐን ሐሴትን የተመላ ነበር።
ጭንቅ ፣ ፍርሃት ጠፍቶልኝ ነበር።
እግዚአብሔርም ዕለት ተዕለት ለእኔ
መልካም ነበር! ❞
አኹን ከስሙ ቅጥያ 'philanthropist' የሚል ቃል ይገኝበታል። በግእዙ 'ፍቅረ ኲሉ ደቂቀ እጓለመሕያው' ማለት ነው። በበጎ አድራጎት ድርጅት ላቅ ብለው የኼዱ ሰዎች የሚጠሩበት ስያሜ ነው። እርሱም ከእነዚኽ አንዱ ኾኖ አልፏል!
ጆን ዲ ሮክፌለር! (1839 - 1937 እ.ኤ.አ)
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
❝ እግዚአብሔርን የምትፈታተኑት እናንተ ምንድን ናችኹ? ❞
በወርኃ ጳጉሜን የምናስበው ጾመ ዮዲት በመጣ ቍጥር ፥ ይኽቺ ዮዲት በመጽሐፈ ዮዲት የተናገረችውን አንድ ድንቅ ኀይለ ቃል አስታውሳለኹ። ዝርዝሩን መጽሐፈ ዮዲት ላይ ታነቡት ዘንድ ጋበዝኋችሁ። ወደ ጉዳይዬ ልግባ፦
በዮዲት ጊዜ እስራኤላውያን ጠላቶቻቸው በተነሡባቸው ጊዜ ከፍርሃታቸው የተነሣ 'ዐምስት ቀን ለእግዚብሔር ዕድል እንስጠው። በእነዚኽ ቀናት ከጠላቶቻቸን ባያድነን እንገዛላቸዋለን' ሲሉ ጊዜን ለፈጠረ ፈጠሪ ጊዜ ሰጡት።
በዚኽ ጊዜ ዮዲት ተነሥታ ለእኛም ትልቅ ትምህርት የሚኾነንን በአንድ ታላቅ ተግሣፅ ገሠጸቻቸው። ቃሉን ባነበብኹት ጊዜ አኹንም ድረስ ሙቀት ልምላሜ ይሰማኛል። ተግሣጿ ይኽ ነበር፦
«እግዚአብሔር በእነዚኽ በዐምስቱ ቀን ባይረዳችኹ ሀገራችሁን ለጠላቶቻችኹ አሳልፋችኹ ትሰጡ ዘንድ በእግዚአብሔርና በእናንተ መካከል የተማማላችኹትን መሐላ በዚኽ አጸናችኹ። አኹን በዚኽች ቀን እግዚአብሔርን የምትፈታተኑት በሰውና በእግዚአብሔር መካከል የተነሣችኹ እናንተ ምንድን ናችኹ?...
አኹንም እርሱ እግዚአብሔር ይመረምራል። እናንተ ግን እግዚአብሔር ኹልጊዜ የሚያደርገውን አታውቁም። በሰው ልቡና ያለ ረቂቅ ምሥጢርን የማታውቁ የልቡናውንም ሓሳብ የማታስታውሉ ይኽን ኹሉ ያደረገ እግዚአብሔርን እንዴት ትመረምራላችኹ?
ልቡናውንስ መርምራችኹ ታውቁ ዘንድ እንዴት ትወዳላችኹ? ምክሩንስ መርምራችኹ ታገኙ ዘንድ እንዴት ትመረምራላችኹ?
ወንድሞቼ! ይኽ ለእናንተ አግባባችኹ አይደለም። ፈጣሪያችን እግዘብሔርን አታሳዝኑት! በእነዚኽ በዐምስቱ ቀናት ይረዳን ዘንድ ቢወድም በወደደ ገንዘብ የሠለጠነ ነው።
በዘመኑም ኹሉ ቢኾን በጠላቶቻችንም ፊት ያጠፋን ዘንድ ቢወድድ የሠለጠነ ነው። እግዚአብሔር እንደሰው የሚጨክን አይደለምና! እንደ ሰውም የሚቀየም አይደለምና! እናንተ ግን ፈጣሪያችኹ እግዚአብሔርን አትፈታተኑት! ነገር ግን ከእርሱ የምትገኝ ረድኤትን ደጅ ጥኑ። ቃላችንን ሰምቶ ይረዳን ዘንድ ይወድድ እንደኾነ ለምኑት» ( ዮዲ. ፰ ፥ ፲፩ - ፲፯)
እግዚአብሔርን ልመናችንን በራሳችን የጊዜ ገደብ (Time frame) እንዲፈጽምልን ችክ ለምንል ለእኛ ተግሣጽ ትኾነን ዘንድ ተጻፈች።
እንኳን ለጾመ ዮዲት በሠላም አደረሰን!
✍️ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
« ሺሕ ሙታንን ያስነሱ አባት »
"... ንጉሥ ሞተሎሚ በብዙ ተአምራት ወደ ክርስትና ከተመለሰ በኋላ ትንሣኤ ሙታንን ሊያምን አልቻለምና አባታችን ቅዱስ ተክለ ሃይማኖትን ሙታንን አስነሥቶ ካላሳየው ትንሣኤ ሙታንን ማመን እንደማይቻለው ይናገራል።
አባታችንም በዚያን ጊዜ በሲኦል የነበሩ አንድ ሺሕ ሙታንን አስነሥቶ በፊቱ አቆማቸው። ንጉሡም ዐይቶ ደነገጠ። መናገርም ተሣነው። የተሰበሰቡትም ፈጽመው ፈሩ። 'ይህ ሰው ነውን ወይስ አምላክ ነው?' አሉ ፡፡ ንጉሡም የተነሡትን ጠየቃቸው፦ 'ከሞት በኋ ላ ኵነኔ አለን?' አላቸው።
እነርሱም እንዲህ አሉት፦ "ንጉሥ ሆይ የዚህንማ የጨለማውን ሀገርና የመከራውን ነገር ምን እንነግርሃለን! እንደዚህ ዓለም ፀሐይ ያሉ መቶ ሺህ ፀሐዮች ከዚያ ከጨለማው ሥፍራ ቢገቡ ለአንድ ሰው እንኳን ሊያበሩ ባልቻሉ ነበር። እኛም ከዚያ ነበርን'
ንጉሡም ይህን ሰምቶ ሰውነቱ ተነዋወጠ። ኹለንተናው ስቅጥጥ ስቅጥጥ ይል ጀመር። እጅግም ፈራ፡፡ ብፁዕ አባታችንም ዳስሶ እስኪያጸናው ድረስ እንደ በድን ኾነ፡፡ ብፁዕ አባታችን ተክለ ሃይማኖትም ይህን ዐይቶ "ወይ ሰው! ይህ ኹሉ መከራ እኮ ይቆየዋል!" አለ።
ምንጭ፦ገድለ ተክለ ሃይማኖት ዘኀሙስ።፴፰ ፥ ፰ -፲
እንኳን አደረሳችሁ!
< እንዴት ሞተች እንጂ እንዴት ተነሣች ብለኽ አትገረም! >
ከሰው ኹሉ መርጦ እናቱ ያደረጋት ጌታ፥ ከሰው ኹሉ መርጦ ከሞት አሥነሳት፤ አሳረጋት፡፡ ከሰው ኹሉ ተመርጣ ሰማይና ምድር የማይችሉትን ጌታ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ጸንሳ ወልዳው የለምን? ከተገረምክ በዚኽ ተገረም፡፡
እናት ኾና ድንግል፥ ድንግል ኾና እናት መኾን የምትችል ሴት በምድር ላይ አልነበረችም፤ ወደፊትም አትኖርም፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም ግን በዐለም ያሉ ሴቶች ኹሉ የማይኾኑትን ኾነች፡፡ ድንግልም እናትም፡፡ ከትንሣኤዋ ይልቅ ይኽ አይደንቅምን?
የክብር ትንሣኤና ዕርገትማ በሃይማኖትና በምግባር ለጸኑ ሰዎች ኹሉ ጊዜው ሲደርስ ይፈጸምላቸዋል፡፡ይነሣሉ ያርጋሉ፡፡ ከአንስተ ዐለም ተለይታ አምላኳን ልጄ ብላ መጥራት የቻለች የሕይወት እናት፥ መሞቷ እንጂ መነሣቷ ምን ይገርማል??
ሙሴ በሲና ያያት ዕፅ፥ ቀርበው ካላይዋት በስተቀር እሳት ያቃጠላት ትመስላለች፡፡ እንደሙሴ ቀርቦ ለተመለከታት ግን እሳት ቢነድባትም ዕፀ ጳጦሷ አትቃጠልም፡፡ ይኽ እሳት የመለኮት ምሳሌ ኾኖ በሊቃውንቱ ተተርጉሞ ነበር፡፡ ዛሬ ግን እሳቱ የሞት ምሳሌ ኾኖ ይገለጣል፡፡ እሳት ያላቃጠላት ቅጠል ደግሞ እመቤታችን ናት፡፡
ዳሩ ይኽን ለመረዳት ወደደብረ ሲና መውጣት ብቻም አይጠቅምም፡፡ እንደ ሙሴ ጫማንም ማውለቅ ይበጃል፡፡ ሊቃውንቱ፥ "ሙሴ የለበሰው ጫማ ከሞቱ እንስሳት ቆዳ የተሠራ በመኾኑ ያን ተጫምቶ እንዳይቀርብ ተከለከለ" ብለው ተርጉመዋል፡፡
የሞቱ እንስሳት ቆዳ ውጤት የኾነው ጫማ፥ ሙታነ ሕሊናን ይወክላል፡፡ ጌታችን ክርስቶስ በእናቱም ለእናቱም ያደረገውን ድንቅ ነገር የማያምን ልብ፥ የሙሴ ጫማ ነው፡፡ መውለቅ አለበት፡፡ እግርን ሳይኾን ዐይንን የሚጋርድ ግርዶሽ ነውና፡፡
ዕፀ ጳጦስ የተባልሽ ድንግል ኾይ፥ጫማችንን የፈታን ሙሴዎች ኾነን ክብሩን እናይ ዘንድ ለምኝልን!
© ሊቀ ሊቃውንት ሥሙር አላምረው
በድጋሜ እንኳን አደረሳችኹ!
https://l1nk.dev/my3noxr
በዓሉን ይህቺን ጣፋጭ መዝሙር እስኪ ተጋበዙልኝ!
ከጠዓሙ ብዛት የተነሣ አጥንትን የሚያለመልም!
ጠያቂ፦ ማርያም የምትሏት 'ዐርጋለች' የምትሉን ማረጓ መቼ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተጽፏል?
መላሽ፦ ማረጓን ተወውና መሞቷ መቼ መጽሐፍ ቅዱስ ላይ ተጽፏል? እና ስላልተጻፈ አልሞተችም እንበል?! ስለዚኽ...
እንኳን ለእመቤታችን የዕርገት በዓል በሠላም አደረሳችሁ!
ተአምር ፲፩
« እግዚአብሔር ቅርብ ነው!» (ፊል.፬ ፥ ፮)
ወሀሎ አሐዱ ብእሲ ዘስሙ 'ቲኮን' በሀገረ ራሽያ፡፡ በራሽያ ሀገር ቲኮን የሚባል አንድ አባት እንደ ነበረ ተነገረ፡፡ ይኽ ሰው ለ 60 ዓመታት በአቶስ ተራራ በተጋድሎ የኖረ አባት ነው፡፡ ዕለት ዕለትም ዕንባ በተቀላቀለበት ታላቅና የማይነጥፍ በኾነ ምስጋና በእመቤታችንን ስዕል ፊት በፍጹም ክብር መማለልን ፣ ማመስገንንና መጸለይን አያስታጒልም ነበር፡፡ ወደዚኽ ሕይወት ግን እንዲገባ ምክንያት የኾነው አንድ ተአምር ነበር፡፡ ይኼውም እንዲኽ ነው፦
በሳይቤሪያ ሀገር ስንዴ በብዛት ይመረት ነበረና ከዚህች ሀገር የኾነ ይኽ አባት እንደ ሀገሪቱ ነዋሪዎች እርሱም የፊኖ ዳቦ ("white bread”) የመመገብ ባህል ነበረው፡፡
በወጣትነት ዘመኑ የራሽያ ገዳማትን እየጎበኘ ባለበት ወቅት ሞስኮው ከምትባል ከተማ ይደርሳል፡፡ የዚህች ከተማ ነዋሪዎች የዳጉሳ ዳቦ (እንግዲኽ እንግሊዘኛው "black bread" ይለዋል። የትርጒም ስሕተት ካለ ይቅርታ ይደረግልኝ።) የመመገብ ባህል ነበራቸው እንጂ የፊኖ ዳቦ አይደለም፡፡ እርሱም እንደዚህ ያለውን ዳቦ የመመገብ ባህል አልነበረውምና ለብዙ ቀናት በረኃብ ለመቆየት ተገደደ፡፡
ታዲያ አንድ ቀን በአንድ የዳቦ መጋገሪያ ቤት እያለፈ ባለበት ወቅት አንዲት ሴት ይመለከትና ዳቦ ትሰጠውም እንደኾነ አትሰጠውም እንደኾነ ከፍ ዝቅ እያደረገ ዐይን ዐይኗን ይመለከት ጀመር፡፡ እርሷም ትኩስ የፊኖ ዳቦ አምጥታ ሰጥታው ትመለሳለች፡፡
እርሱም ዳቦውን የተወሰነ ተመግቦ ይህችን ሴት ሊያመሰግናት ወድዶ ወደ ዳቦ መጋገሪያው ቤት ያቀናል፡፡ በደረሰም ጊዜ ሠላምታ ሰጥቶ የፊኖውን ዳቦ የሰጠችው ሴት የት እንዳለች ይጠይቃል፡፡ እለርሱም "እዚህ ቦታ ሴት የለችም፡፡ የፊኖም ዳቦ የለም፡፡" ሲሉ ይመልሱለታል፡፡ በዚህም ጊዜ ዕንባ ከዐይኖቹ ይፈሱ ጀመሩ።አንዳች ተአምር እንደተደረገለት ተረድቷልና!) ዳቦውን የሰጠችው እመቤታችን ቅድሰት ድንግል ማርያም እንደኾነችም ዐወቀ፡፡ የተቀበለውም ዳቦ ለጉዞው ኹሉ የሚበቃም ነበር!!
ይኽን ተአምር ከተረዳ በኋላ በቀረ ዘመኑ ፈጣሪን በምንኩስና ሊያገለግል ወድዶ ፈቅዶ ወደ ገዳም ገብቶ ምንኩስናን ተቀብሎ ፈጣሪን ሲያገለግል ኖረ፡፡ (በመግቢያው ላይ እንደገለጽኹት ይኽ አባት ከዚኽ ተአምር የተነሳ በገዳም ከ ፷ (60) ዓመታት በላይ በተጋድሎ ኑሯል)
source: Orthodox parables and short stories
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን
ተአምር ፲
❝ ማንም እኮን አልተወሽም ❞
ልድያ ትባላለች። ባለታሪኳ ናት። በሥራ ቦታዋ ውስጥ ጒድጓድ እየቆፈሩ ፣ ሕንፃ ነገር እየገነቡ ባለቡት ወቅት በሥራው ትሳተፍ ነበርና ድንገት ወድቃ ትጎዳለች። ጉዳቱንም ዕብጠት ይከተለዋል። 'ዕብጠቱ በጊዜ ኺደት ይቀንሳል ይሻለኛል' ብላ ብታስብም እንዳሰበችው ግን አልኾነም።
ከረጅም ጊዜ በኋላ ነገሩም ስላሳሰባት ዶክተሮች ጋር ኼዳ ልትታይ ወሰነች። በታየችውም ጊዜ ወደ ተለያያ የሰውነት ክፍሎቿ የተሰራጨ ካንሰር እንደኾነም ይነገራታል።
ልቧም በድንጋጤ ተሰበረ! በሆስፒታሉ ውስጥ ብቻዋን ተቀምጣ ፊቷን በእንባ ታጥብ ጀመር። "አምላኬ ሆይ! ለምን??? ለምን ተውኸኝ???" እያለች አኹንም አኹንም መራር እንባን ታነባ ጀመር።
በዚኽ ኹናቴ ሳለች ከዚኽ ምድር የኾነች የማትመስል እጅግ ውብ የኾነች አንዲት ሴት ድንገት ባጠገቧ ትመለከታለች። እንዲኽም አለቻት፦ «ልድያ ሆይ! ስለምን ታለቅሳለሽ? ማንም እኮን አልተወሽም!» ስትል ታጽናናታለች። ይኽን ነግራትም ከአጠገቧ ትሰወራለች።
ዶክተሮች ሊረዷት አልቻሉም። ተስፋ እንደሌለው ነግረው አሰናብተዋታል። እናቷ ግን እምነት ነበራት። የልጇንም ጉዳይ በሰማች ጊዜ ትኩረቷን ወደ ላቭራ መነኮሳት መለሰች። ሥጋ ወደሙን ያቀብሏት ዘንድ ለመነቻቸው።
ልጇም ትቀበል ዘንድ አስፈላጊውን ዝግጅት ጨረሰች ልጇንም ወደ ገዳሙ አመጣቻት።... ለሦስት ጊዜም ሥጋ ወደሙን ተቀብላ በጤና ወደ ሥራ ተመለሰች። 'እንዴት ልትፈወሺ ቻልሽ ?' ሲሉ የስራ ባልደረቦቿ ይጠይቋት ነበር። እርሷም 'ክርስቶስ በሥጋው በደሙ ፈወሰኝ ' ስትል ትመልስ ነበር።..."
አንባቢ ሆይ! ታሪኩ ልብ ወለድ አይደለም እሺ! በእውነት የኾነ እንጂ! በመከራ ውስጥ ያለን ስንቶቻችን ነን እግዚአብሔር አምላክ እንደተወን የምናስብ? እንደዚኽ ያለነው ሰዎች ይኽቺን ታሪክ ጠዋት ጠዋት ብንደግማት መልካም ነው ብዬ ዐስባለኹ። ይቆየን!
Source: Orthodox parables and short stories, miraculous healing,
ትረጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
ተአምር ፱
«አፍጣኒተ ረድኤት»
ልጃገረዶችን እየጠለፈች ለወጣት ወንዶች ትሸጥ የነበረች አንዲት እኩይ ሴት እንደነበረች ተነገረ። ይኽንን ተግባሯም ማንም አይውቅም ነበር።
ታዲያ በአንድ ወቅት እንዲኽ ኾነ ፦ ቀድሞ ታውቃት የነበረችን አንዲት ደግ ወጣት ሴት አግኝታ ወደ መኖሪያ አፓርትመንቷ መጠጦችን ትወስድ ዘንድ ርዳታ እንደምትሻ ነገረቻት። በዚኽም እያታለለቻት ነበር እንጂ የእውነቷን አልነበረም። ነገር ግን ሴቲቱ የእውነት እንደኾነ ዐስባ በሓሳቧ ተስማማች። አብራትም ኼደች።
ነገር ግን ቤት ደርሳ ወደ ውስጥ በገባች ጊዜ በተመለከተቺው ነገር እጅግ ደነገጠች። የብዙ ሴቶች ስብስብ ክፍሉን ሞልቶት ነበር። በዚኽም እጅጉን ደንግጣ እንባ በተቀላቀለበት ጩኸት እየጮኸች ወደ እመቤታችንም “ድንግል ሆይ! አድኚኝ! ርጂኝ!” እያለች መለመን ጀመረች። ያቺ እኩይ ሴት ግን “ ‘ድንግል ሆይ!’ ምናምን የምትዪውን ነገር ርሺው! አንቺን ይረዳ ዘንድ ማንም ወደዚኽ አይመጣም!” ስትል በስላቅ ቃል ተናገረቻት።
ነገር ግን እመቤታችንና ‘አባ ኤንጀሎስ’ የሚባሉ አንድ አባት ወጣቷን ሴት ከነጣቂ ተኲላዎች ይሠውሯት ዘንድ ድንገት በክፍሉ ተገለጡ። እርሷንም ይዘው ሊሠወሩ በነበረበት ወቅት አባ ኤንጀሎስ እመቤታችንን ፥ “እመቤቴ ሆይ! ይኽቺ እኩይ ሴት በእኽቶቻችን ላይ ዳግም እንደዚኽ እንዳታደርግ አንድ ጥፊ አቀምሳት ዘንድ ፍቀጂልኝ” ሲል ተማጸናት። መልሷንም ሳይጠብቅ ደኅና አድርጎ በጥፊ አጮላት።
ከጊዜ በኋላ ከአባ ኤንጀሎስ እንደሰማነው ከኾነ ሴቲቱ በጮኸችበት ቅጽበት እመቤታችን ተገልጻለት ‘ተነሥ እንኺድ! ፈጥነን እንፈጽመው ዘንድ አንዳች አስቸኳይ ተልዕኮ አለብን!” እንዳለችውና ከዚያም ለሴቲቱ እንደደረሱላት አጫውቶን ነበር። ከዚያም እመቤታችን የሴቲቱን አንድ እጇን አባ ኤንጀሎስ ደግሞ ሌላኛው እጇን ይዘው ወደ መኖሪያዋ በሠላም መለሷት።
Source: orthodox saint stories, “permit me to slap her”
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
« የሚናገረውንም አያውቅም ነበር! »
ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ‹‹በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው›› በማለት ቅዱስ ጴጥሮስ የተናገረውን ተከትሎ ‹‹የሚናገረውንም አያውቅም ነበር!›› (ሉቃ. 9፡33) ብሎ ጽፏል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው›› ማለቱ ምን ስሕተት ተገኝቶበት ይሆን ወንጌላዊውን እንዲህ ያሰኘው? ፤ ከጌታ ጋር ከመሆን በላይ ምን መልካም ነገርስ አለ? ቅዱስ ጴጥሮስ ይህን በመናገሩ ምን አጠፋ?
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የጴጥሮስን ጥፋት እንዲህ ይግረናል ፤ ጌታ ደቀ መዛሙርቱን ወደ ታቦር ይዞ ከመውጣቱ በፊት ፤ ወደ ኢየሩሳሌም ሄዶ በአይሁድ ተይዞ እንደሚገደል ፤ በሦስተኛውም ቀን እንደሚነሣ በነገራቸው ጊዜ ፤ ጴጥሮስ ‹‹አይሁንብህ ጌታ ሆይ!›› ብሎ ነበር፡፡ ጌታችንም ገሥጾት ነበር ፤ ጴጥሮስ ግን ለክርስቶስ ከነበረው ፍቅር የተነሣ ከተግሣጹም በኋላ ጌታችን እንዳይሞት በልቡ ውስጥ ይፈልግ ነበር፡፡
ወደ ደብረ ታቦር ጌታ ካወጣቸው በኋላ ፤ የደብረ ታቦርን ከፍታውን መልክዓ ምድሩን ማንም የማይኖርበት ጸጥ ያለ ቦታ መሆኑን በተመለከተ ጊዜ ፤ ወደ ኢየሩሳሌም በመሄድ ጌታ እንዳይያዝ እና እንዳይሰቃይ ‹‹በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነው›› አለ፡፡
አይሁድ እንኳን ወደ ደብረ ታቦር ቢመጡ ፤ እሳት ከሰማይ የሚያወርደው ኤልያስ (2ነገ. 1፡9) ፤ በደመና ውስጥ መግባት መሰወር የሚቻለው ሙሴ (ዘጸ. 24፡18) ከእነርሱ ጋር መኖራቸው ልቡን አበረታው፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ጌታን ከመውደድና በአይሁድ የሚደርስበትን መከራ በመፍራት ውስጥ ቅዱስ ጴጥሮስ የተናገረውን ተመልክቶ ‹‹የሚናገረውንም አያውቅም ነበር!›› አለ፡፡
አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በዚህ በጴጥሮስ ንግግር በመገረም ‹‹አንተስ የቀደመውን የአዳምን ደም ግባት አይተህ ፤ ከአዳም ሴት ልጅ በተወለደው በኢየሱስ ክርስቶስ በፊቱ ብርሃን እየተደሰትኽ በዚያ ትኖር ዘንድ በተሻለህ ነበር፡፡›› ካለው በኋላ ለጴጥሮስ ይህን በመጠየቅ ይዋቀሰዋል፡
+ እናንተ በዚያ ኖራችሁ ቢሆን የፊቱ መልክ በታቦር ተራራ ብርሃን በሆነው በእርሱ በጉንጮቹ በጥፊ መመታት ካልሆነ በቀር ፣ ቤተ ክርስቲያን በማን ፊት ትድን ነበር?
+ እናንተ በዚያ ከኖራችሁ በቀራንዮ ተራራ በመስቀል ላይ ለዓለም መዳን ማን እጁን ይቸነከር ነበር? ከማንስ ጎን የሕይወት ውኃ ወደ አዳም መቃብር ይፈስስ ነበር?
+ እናንተ በዚያ ከኖራችሁ ለሙታን ሕይወት ይሆን ዘንድ ማን በሥጋ ሞትን ይቀምስ ነበር? ማንስ የጻድቃንን ነፍሳት ከአንጦርጦስ ሊያወጣቸው ይችል ነበር?
+ እናንተ በዚያ ኖራችሁ ቢሆን ጦርነትን ያደርግ ዘንድ ማን ከጨለማ ሠራዊት ጋር ለመዋጋት ይዘጋጅ ነበር? አሕዛብን ከጣዖት አምልኮ ይታደጋቸው ዘንድ በቤልሆር ሠራዊት ላይ ማን ጦረኛ ያስነሣ ነበር?
+ እናንተ በዚያ ኖራችሁ ቢሆን ማን ቤተ ክርስቲያንን በአንተ ላይ ይሠራት ነበር? ምሰሶዎቿ ሐዋርያትን ፣ በሮቿ ነቢያትን ፣ ግድግዳዎቿ ሰማእታትንስ ማን ያቆም ነበር?
+ እናንተ በዚያ ኖራችሁ ቢሆን ማን ሂዱና በዓለም ዳርቻዎች ሁሉ የመንግሥትን ወንጌል አስተምሩ ፤ ስታጠምቁአቸውም "በአብና በወልድ በመንፈስ ቅዱስም ስም በሉ' ብሎ ይልካችሁ ነበር፡፡ (አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ፤ መጽሐፈ ምሥጢር ምዕ. 30 ፤ ቁ. 36 - 38)
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ መልሶ ‹‹ጴጥሮስ ሆይ ፤ ክርስቶስ ለአብ ‹ልጁ› ብቻ ሳይሆን ‹የሚወደው ልጁ ነው› ፤ ማንም የሚወደውን ለከንቱ አሳልፎ አይሰጥምና አትፍራ ፤ አንተ ከልክ በላይ እንደምትወደው አውቃለሁ ፤ ምንም ያህል ብትወደውም ፍቅርህ ከአባቱ ፍቅር አይበልጥምና ፤ ስለ ክርስቶስ መከራና ሞት አትፍራ አትጨነቅ›› ይለዋል፡፡
ለእግዚአብሔር ቀናዒ የሆኑት ሙሴና ኤልያስ እንኳን በታቦር በተገለጡ ጊዜ ስለ ክርስቶስ መከራና ሞት ‹በኢየሩሳሌም ይደረግ ዘንድ ያለውን ክብሩንና መውጣቱን› (ሉቃ. 9፡31) በደቀ መዛሙርቱ ፊት ይነጋገሩ ነበር፡፡
ስለዚህ ጴጥሮስ ሆይ ምንም ብትወደውም ፤ አንተ መሠረት ሆነህ በክርስቶስ ደምና በሞቱ የምትሠራውን ታላቂቷን ቤተ ክርስቲያን ልትሠራ የተመረጥኽ ነህና ፤ ዳስ መሥራቱ የአንተ ሥራ አይደለም ፤ አብ ከደመና ውስጥ ‹‹ልጄን ስማው›› ያለህን ቃል አስተውል!
ስብሐት ለእግዚአብሔር
ዲያቆን ደረጀ ድንቁ
ነሐሴ 12 2017 ዓ.ም
እንኳን ለደብረ ታቦር በዓል በሠላም አደረሳችሁ!
ተአምር ፰
« የቱን ትመርጫለሽ? »
ልመናዋ ክብሯ የልጇ የወዳጇም ቸርነት በእኛ በኹላችንም ላይ ይደርና በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ይኽ ነው፦
በካንሰር ሕመም ትሰቃይ የነበረች አንዲት ሴት እንደነበረች ተነገረ። ካንሰሩም ወደ ተለያዩ የሰውነት ክፍሎቿ ተሰራጭቶ ነበር። ልጆቿንም እጅግ ትወዳቸው ነበርና ለልጆቿ ትኖርላቸው ትንከባከባቸውም ዘንድ ከሕመሙ ተፈውሳ በሕይወት መቆየትን እጅግ ትናፍቅ ነበር። ይኽ መሻቷ ይፈጸምላትም ዘንድ የተለያዩ ገዳማትን ትሳለም ጸሎትንም ታበዛ ነበር።
በመጨረሻም እመቤታችን በአንድ እጇ የወርቅ አክሊል ፣ በሌላኛው እጇ ነጫጭ አልባሳት ይዛ ተገልጻ እንዲኽ አለቻት ፦ “ብፈውስሽና ለልጆችሽ ብትኖሪላቸው ይሻልሻል ወይስ ይኽን የወርቅ አክሊልና ነጫጭ አልባሳት ተሸልመሽ ልጆችሽን እኔ ብንከባከባቸው? የቱን ትመርጫለሽ?” ሴቲቱም የወርቅ አክሊሉን ከነጫጭ አልባሳት ጋር ምርጫዋ አደረገች።
ከኹለት ቀን በኋላ እንዲኹ እመቤታችን ተገልጻ እጅግ የተዋበ ቦታ አሳየቻትና “ወደዚኽ” ቦታ ብወስድሽ ትመርጫለሽ ወይስ ከልጆችሽ እና ከቤተሰቦችሽ ጋር መቆየትን?” ስትል ሌላ ምርጫ አቀረበችላት። ሴቲቱም ቦታውን እጅግ ወድዳው ነበርና ምርጫዋ እርሱ ኾነ።ያየችውን ኹሉ ለቤተሰቦቿ ትነግራቸው ነበር። ከጥቂት ቀናት በኋላም በሠላም አረፈች። ልጇቿና ቤተሰቦቿም የነገረቻቸውን አስታውሰዋልና ስለ ዕረፍቷ መጽናናት ኾነላቸው።
ይቆየን!
Source: Fourty miracles of the Virgin St Mary - book 3, p. 33
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን
ተአምር ፯
❝ ጾምን ስለሻርኽ ነው! ❞
ልመናዋ ክብሯ በኹላችን ላይ ይደርብንና አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ይኽ ነው፦
የአንድ ገዳም አበምኔት ከወዳጅ ዘመዶቹ ቤት ጥሪ ተደርጎለት በኼደ ጊዜ "እኔ ማነኝና ለኔ የተለየ ምግብ ያዘጋጃሉ?" በሚል ስሜት ዕረቡም ይኹን ዐርብ ያቀረቡለትን የጥሉላት ምግብ ይመገብ ነበር (እሊኽ ዘመዶቹ የረቡዕንም የዐርብንም ጾም አይጾሙም ነበርና)።
ታዲያ አንድ ቀን ያለመውን ህልም እንዲኽ ሲል ይተርካዋል፦ "ለየት ያለ ሰማያዊ ውበት የተጎናጸፈ እጅግ ሰፊ የኾነ ቤተ - መቅድስ ውስጥ ራሴን አገኘዋለኹ።... በዚኽም መቅደስ ውስጥ የእመቤታችን ምስለ ፍቁር ስዕል እመለከታለኹ። ወድቄ ከሰገድኹላት በኋላ ፣ ትምረኝ ታማልደኝ ዘንድ ጸሎቴን ማቅረብ ስጀምር ፣ እስክፈራ ድረስ ደርሼ እመቤታችን ፊቷን ከኔ ስትመልስ እመለከታለኹ ። እኔም በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ ኾኜ "እመ - አምላክ ሆይ! እመ - አምላክ ሆይ! ምን ባስቀይምሽ ነው ፊትሽን ከኔ ከኃጢአተኛው የምትመልሺ" ስል እጮኻለኹ።
እንዲኽ ያለ መልስም ከስዕሏ ይወጣል ፦
❝ ጾምን ስለሻርኽ ነው! በረቡዕና በዐርብ የጾም ያልተፈቀደ ምግብ ተመግብኻልና። ስለዚኽም ነገር የልጄን ስቃይ አቃለልኽ። በዚኽም ፣ ልጄንም እኔንም ተሳደብኽ' በሚል ቃል ከተናገረቺኝ በኋላ የህልሙ ፍጻሜ ኾነ። ለቀሪው የሕይወት ዘመኔም ትምህርት ኾነኝ ❞ ይለናል።
የልጇ የወዳጇም ቸርነት በኹላችን ላይ ይደርብን! ለዘላለሙ አሜን!
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
ተአምር ፮
« ያለማቋረጥ ወደእኔ ጩኹ ለምኑም »
ልመናዋ ክብሯ የልጇ የወዳጇም ቸርነት በኹላችን ላይ ይደርብንና አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ይኽ ነው፦
በአንድ ወቅት በጭንቅላት ውስጥ ደም የመፍሰስ (የመቋረጥ) በሽታ (Stroke) ተጠቅታ የነበረች “ማሪያ” የምትባል ሴት እንደነበረች ተነገረ። ይኽቺ ሴት ከበሽታው የተነሣ ከወገቧ በታች (በአጠቃላይ) እና ከወገቧ በላይ ደግሞ በቀኝ በኩል ደግሞ በከፊል መንቀሳቀስ የተሳናት (paralyzed) ነበረች።
ደግነቱ ፥ “ቅድስት ማክሪና” የተሰኘች አንዲት ቅድስት ከዐምስት ዓመታት በፊት (በዚኽ ሕመም ከመጠቃቷ በፊት) “እግዚኦ መሓረነ ክርስቶስ” የሚለውን ጸሎትና “ቅድስተ ቅዱሳን የአምላክ እናት ሆይ! አድኝን!” የሚለውን ጸሎት በቀን ውስጥ በተቻለት መጠን በድግግሞሽ እንድትጸልይና አንዳች ችግርም በተፈጠረ ጊዜ እንዲኹ በተቻለት መጠን በድግግሞሽ እንድትጸልይ አስተምራት ነበር።
ታዲያ ማሪያ የአልጋ ቁራኛ በኾነችበት በዚኽ ጊዜ በሕመም ውስጥ ኾና በእምነት ያለማቋረጥ ጸሎቱን ደጋግማ መጸለይ ትጀምራለች። “ቅድስተ ቅዱሳን የአምላክ እናት ሆይ! ረዳት ኹኚኝ! ቅድስተ ቅዱሳን የአምላክ እናት ሆይ! እኔን ኃጢአተኛዋን አድኚኝ!” አኹንም አኹንም ከልብ በመነጨ መማለል መለመኗን ቀጠለች።
ከቀናት በኋላ ፥ በተለመደው ጸሎቷ ላይ እያለች ድንግል ማርያም እልፍ አእላፍ ሊቃነ መላእክትን አስከትላ ከፀሓይ ሰባት እጅ በሚያበራ በታላቅ ግርማ ተገለጠችላት። መላው ክፍልም በታላቅ ብርሃን ተመላ። በሰማያዊ መዓዛም ታወደ።
ወላዲተ አምላክም አጥንትን በሚያለመልም በድንቅ አጠራሯ “ልጄ! ማርያ ሆይ! ምን አደርግልሽ ዘንድ ትወጃለሽ?” ስትል ጠየቀቻት። ይኽቺም ቡርክት ሴት ጥቂት መገላበጥ እንኳን አትችልም ነበርና ይኽም ታላቅ ሕመም ኾኖባት ነበርና ከጎን ወደ ጎን መገላበጥ ትችል ዘንድ እመቤታችንን ለመነቻት። ቀጠል አድርጋ ግን “ነገር ግን ፥ ከኹሉም በላይ ነፍሴ ትድን ዘንድ እወዳለኹ። የነፍሴን ድኅነት እናፍቃለኹ” ስትል ለመነች።
ከሩኅሩኃን በላይ ርኅርኅት የምትኾን እመቤታችንም መለሰች ፦“የለመንሽኝን ኹሉ እሰጥሻለኹ። ስለዚኽ መጥቻለኹና። በቀንም በሌትም ስሜን ትጠሪ ነበርና። ኹላችኹም ስሜን ትጠሩ ዘንድ እሻለኹ። ያለማቋረጥ ወደ እኔ ጩኹ ለምኑ! ልመናችኹን እሰማለኹ ወደ እናንተም እመጣለኹ” አለቻት።
ስለዚኽ ተአምር በክፍሉ የነበሩ ቤተሰቦቿ ኹሉ ምስክር ነበሩ። እመቤታችን ከማርያ ከተሰወረች በኋላም እንኳን ክፍሉ በሰማያዊ መዓዛ ለቀናት እንደታወደ ነበር።
‘ማርያ’ ም ከእመቤታችን ዘንድ ስለተቀበለችው ጸጋ መንፈስ ቅዱስ እንዲኹ ለቀናት ፊቷ ብርሃንን የተመላ ነበር። ማርያ ፥ ከጎን ወደ ጎን መገላበጥ ብቻ የቻለች አይደለችም። ዳሩ ግን ፥ ከቀናት በኋላ ፥ ሙሉ በሙሉ ከሕመሟ ተፈውሳ ከአልጋ ቁራኝነቷ ተላቀቀች እንደ ልቧም መንቀሳቀስ ቻለች እንጂ!
❝ ድንግል ማርያም ማንኛውም ሰው ወደርሷ ይጣራ ይለምን ዘንድ ትሻለች። እርሷ ራሱ ምን አለች? ‘ቅድስተ ቅዱሳን ወላዲተ አምላክ ሆይ! ረዳት ኹኚኝ! ወላዲት አምላክ ሆይ! አድኚኝ!’ እያላችኹ ትጠሩኝ ዘንድ እወዳለኹ። ከልባችኹ የምትሽቱን ኹሉ ንገሩኝ። ልመናችኹን እሰማለኹ። ወደእናንትም ፈጥኜ እመጣለኹ' አለች።❞
ይቆየን!
Source: The Art of orthodoxy, The power of the prayer ‘Most holy theotokos save us!’
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
❝ ሰው ብቻውን ይኾን ዘንድ መልካም አይደለም!. . . ❞
ሥላሴ ፍጥረታትን ፈጥረው ከጨረሱ በኋለ የአዳምን ብቸኝነት ባዩ ጊዜ “ሰው ብቻውን ዘንድ መልካም አይደለም። የምትመቸውን ረዳት እንፍጠርለት” ብለው ነበር። “እንደ እውነቱ ከኾነ ሔዋን በሥጋ ከመርዳት በቀር ለነፍሱማ ሞትን አመጣችለት እንጂ ምን ረዳቺው?
ነገር ግን ፥ በርግጥም ሰው ድንግል ማርያም ከመፈጠሯ በቀር ድኅነት ያገኝ ዘንድ አልቻለምና ፥ ‘ረዳት እርሷን በንጽሕና እንጠብቅለትና ከእኛ አንዱ በእርሷ ተወልዶ ያድነው’ ማለት ነበር። በእውነት ሰው ያለ ድንግል ማርያም ብቻውን ይኾን ዘንድ መልካም አይደለምና አይኾንለትምና እርሷ ተፈጠረች። ሔዋንም ፥ ሕይወት እመቤታችን በእርሷ ማሕፀን አለችና ‘ሕይወቴ’ ተባለች።¹ በጊዜው በምታመጣው መከራማ እኮን ሔዋን ‘ሞቴ ነሽ’ መባል በተገባት ነበር። ነገር ግን ፥ ውድቀት በእርሷ እንደመጣ በኋላ በልጇ በድንግል ማርያም ትንሣኤ ይመጣልና ‘ሕይወቴ ነሽ’ መባል ተገባት።”²
እግዚአብሔር ለአዳም ሔዋንን ለረዳትነት በሚፈጥርበት ጊዜ ከአንዲት አጥንት ነበር። ‘ለምን?’ ቢሉ ፥ አጥንት ጽኑዕ ነው። ኃጢአት የማያደክማት ድካመ ነፍስ ድካመ ሥጋ የሌለባት ጽንዕት በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ ለዘላለሙ የጸናች እመቤት ከእርሱ እንድትገኝ ሲነገግረው ነበር። አጥንት ከሥጋ ሲገኝ ነገር ግን ንጹሕና ነጭ ነው። እመቤታችንም ምንም በኃጢአት በመርገም ምውት ከኾነ ከአዳም ባሕርይ ብትገኝ ርስሐተ ሥጋ ወነፍስ የሌለባት ፅድልት ንጽሕት ናት።³
“ዳግመኛም እግዚአብሔር ለአዳም ‘ረዳት እንፍጠርለት’ አለ። ይኽቺውም ትረዳው ዘንድ የተፈጠረችው ሞትን በአዳም ላይ ሞት ያመጣች ሔዋን ናት። ረዳትስ አልኾነችውም ገዳይ ኾነቺው እንጂ! ሔዋንስ ‘ረዳት’ የተባለችው በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ምክንያት ነው።. . . መድኃኒት ኢየሱስን ወልዳ ሕይወት ኾናለችና” እንዳለ አባ ጊዮርጊስ⁴ ፥ ሥላሴ እንዲያ የተናገሩት ስለ እመቤታችን ውልደት ነበር።
ሥላሴ እንዲኽ መናገራቸው በዋናነት ስለ ሔዋን ቢኾን ኑሮ “ሰው ብቻውን ይኾን ዘንድ መልካም ነው” ቢሉ በተገባ ነበር! በእርሷ ምክንያት ሞት ወደ ዓለም ገብቷልና! ነገር ግን ሥላሴ ይኽን ያሉት በዋናነት ስለ ድንግል ነውና “ሰው ብቻውን ይኾን ዘንድ መልካም አይደለም” አሉ። ዳግመኛም “የምትመቸውን” የሚል ቅጽል ሥላሴ መጨመራቸው ፥ ኃይለ ቃሉ የተነገረው ስለ እመቤታችን መኾኑን ያጠይቃል። “‘ረዳት’ እንፍጠር” ብቻ ቢሉ ኖሮ ለውድቀትም የሚረዳ አ‘ለና “ስለ ሔዋን የተነገረ ነው” ሊያሰኝ ይችል ነበር። ዳሩ ግን ፥ ሥላሴ እንዲያ አልተናገሩም። "የምትመቸውን እመቤታችንን እንፍጠርላቸው" አሉ እንጂ።
ይትባረክ እግዚአብሔር ዘወሀበነ እሙ ለድኅነተ ዓለሙ! አሜን! ይቆየን!
--------
¹ “አዳም ፥ እመቤታችን ከአብራኩ በሔዋን ማሕፀን እንድትወለድ ዐውቆ ሚስቱን ሔዋንን ‘ሕይወቴ ነሽ’ ይላት ነበር” እንዲል መቅድመ ተአምረ ማርያም።
² መጋቤ ሐዲስ ወብሉይ አባ ገብረ ኪዳን ግርማ (2013)። ጸያሔ ፍኖት። ፪ኛ ዕትም። ገጽ 163
³ ዝኒ ከማሁ
⁴ ኆኅተ ብርሃን ዘቀዳሚት
---------
እንኳን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የፅንሰት በዓል በሠላም አደረሰን!
ተአምር ፭
❝ ስምስ ይሉኻል ይኼ ነው! ❞
ልመናዋ ክብሯ የልጇ የወዳጇም ቸርነት በኹላችን ላይ ይደርብንና አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ይኽ ነው፦
በአንድ ወቅት ፊደል ያልቈጠረ መነኲሴ እንደነበረ ተነገረ። ታዲያ ከአባቶች አንዱ ወደርሱ ጠጋ ብለው “ሌሎችን ጸሎታት መጸለይ ስለማትችል ፥ ይኼን ጸሎት ጸልይ” ብለው “በሠላመ ገብርኤልን” ያሰተምሯቸዋል። መነኲሴም ፥ “እርሱንም ቢኾን መጸለይ አልችልም” ሲል ይመልሳል። “እሺ! ችግር የለውም! ‘ቅድስት ማርያም ሆይ!’ እያልኽ ብቻ ጸልይ” ሲሉ አዛውንቱ ያሳስቧቸዋል። መነኲሴውም መልሶ ፦ “እርሱንስ ማድረግ እችላለኹ! እስኪ ልሞክር” ብሎ ጸሎቱን ይጀምራል።
መነኲሴው “ቅድስት ማርያም ሆይ!” የሚለውን ቃል ብቻ እየደጋገመ እየጸለየ ይመሻል ይነጋል። በዚኽ አኳዃን ቀናት ተቈጠሩ። ታዲያ አንድ ቀን ሰይጣን መጥቶ ምን ቢለው ጥሩ ነው? “ወደ አንተ መቅረብ አልቻልኹምና ይኽን ስም መጥራት አቁም!” ብሎት ዕ‘ርፍ! ታዲያ መነኲሴው ሊሰማ ነው? ይባስ ብሎ ጸሎቱን ብርትቶ ቀጠለበት እንጂ!
“ዙሮ ዙሮ ከቤት ኑሮ ኑሮ ከሞት ከመሬት” ነውና ቀኑ ደርሶ መነኲሴው ያርፋል። ከጊዜያት በኋላ መቃብሩ ላይ ታዲያ ምን ተአምር ቢፈጠር ጥሩ ነው? መቃብሩ ላይ አበባ አብቦ ቁጭ! መነኰሳቱ መቃብሩን ቢከፍቱት የአበባው ሥር ያልፈረሰው ያልበሰበሰው የመነኲሴው ልብ ላይ ተተክሎ ኑሯል ለካ! ምን ይኼ ብቻ! “ቅድስት ማርያም ሆይ!” የሚለው ስም በወርቅ ቀለም በመነኲሴው ልብ ላይ ተጽፎ ይታይ ነበር።
መነኲሴው በታሪክ መዝገብ ላይ “ቅድስት ማርያም ሆይ!” እየተባለ ሲታወስ ይኖራል።
❝ ድንግል ማርያምን የሚያመሰግናት እርሱ የከበረ ነው! እርሷን ባመሰገናት ቍጥርም ከፍ ከፍ ይላል!❞
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
ተአምር ፬
ልመናዋ ክብሯ በእኛ ለዘላለም በእውነት ይደርብንና አምላክን የወለደች በድንጋሌ - ሥጋ በድንጋሌ - ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን የሶርያ ዕፃ በምትኾን በጸደንያ ከተማ ያደረገችውን ተአምር የወንጌል ልጆች ሆይ ስሙ፡፡
ጊዜው በሶርያ ሀገር የእርስበርስ ጦርነት የነገሰበት ጊዜ ነበር፡፡ ይኽ የምነግራችሁም ተአምር የተከሰተው በከተማዋ በሚገኝ በአንድ ገዳም ላይ ከእርስበርስ ጦርነቱ ጋር በተያያዘ የሮኬት ጥቃት በደረሰበት ወቅት ነበር፡፡ በገደሙ ውስጥ የነበሩ መነኮሳት የሮኬቱ ፍንዳታ ያስከተለውን ከባድ ንውጽውጽታ በሰሙ ጊዜ ጥቃቱ ለእነርሱም ኾነ ለገዳሙ እንደሚተርፍ እርግጠኛ ነበሩ፡፡ ነገር ግን እንዳሰቡት ሳይከሰት በመቅረቱ ሮኬቱ የገጠመውን ቢያውቁ ወደዱ፡፡
ከጥቂት ቀናት በኋላ ከሀገሪቱ ሠራዊት ከጦር ጄኔራሎች አንዱ በሀገሪቱ ይከበር የነበረውን አዲሱን ዓመት አስመልክቶ ለገዳሙ መነኮሳት ሰላምታ ሊያቀርብ ወድዶ ወደዚህ ገዳም ጎራ አለ፡፡ ... በንግግራቸው መካከል ጄኔራሉ ሰሞኑን በአካባቢያቸው ያልተለመደ ክስተት ተከስቶ እንደኾነ ይጠይቃል፡፡ የገዳሙ መነኮሳትም የሮኬቱን ፍንዳታ እንደሰሙ በእነርሱ ላይ ግን አንዳች እንዳልደረሰባቸው ይነግሩታል፡፡ ጄኔራሉም ተመሳሳይ ነገር ከእነርሱ በመስማቱ እየተደነቀ ሮኬቱ ወደ ገዳሙ ሲወረወር እንደተመለከተ ነገር ግን በአካባቢው ከነበሩ ሰዎች ጋር አንድ ያልተለመደ ክስተት እንዳስተዋሉ ይነግራቸዋል፡፡ ይኸውም፦ ሮኬቱ ገዳሙ ላይ ጥቃት ሊያደርስ በነበረበት ወቅት በድንገት በሰማያዊ ቀሚስ የተዋበች አንዲት ሴት ከሰማይ ወርዳ ሮኬቱን በእጇ ይዛ ከገዳሙ አርቃ ትወረውረዋለች፡፡ ይኽንን ይመለከቱ የነበሩ ሰዎችም ፈጽመው አደነቁ፡፡ ጄኔራሉ ሰማያዊ ቀሚስ የለበሰች ፣ ድንቅ የኾነ ግርማ ሞገስን የተጎናጸፈች ይኽቺ ሴት ማን እንደኾነች ይጠይቃቸዋል፡፡ እነርሱም ከወላዲተ -አምላክ ከአምላክ እናት ከቅድስት ድንግል ማርያም በቀር ሌላ ልትኾን እንደማትችል አስተዋሉ፡፡
ልመናዋ ክብሯ የልጇ የወዳጇም ቸርነት ከኹላችን ጋር ይኹን! ለዘላለሙ አሜን!
Source: Orthodox christian.com, Miracle of Holy Theotokos In the Christian Town Of Saidnaya,
ትርጉም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን
ተአምር ፫
« እኔ እናት እኾንኻለሁ »
ውልደቱ በአውስትራሊያ ሀገር ነበር። የምንኲስና ኑሮው ደግሞ የቅዱስ እንጦንስ ገዳምን ጨምሮ በሌሎች ገደማት። “አባ አልዓዛር” ይባላል።
በ‘እግዚአብሔር የለም’ እምነት ውስጥ ለአርባ ዓመታት የኖረ አባት ነበር። የእናቱን ሞት ተከትሎ ለዓመት ያኽል ውስጡ ሠላምን አጥቶ አለመረጋጋትን ተመልቶ ከባድ ጊዜያትን አሳልፏል።
ወደ ምንኲስና ሕይወት ከመግባቱ በፊት በአንድ ወቅት ‘ቅዱስ ሳቫ’ ተብሎ በሚታወቅ አውስትራልያ ሀገር ውስጥ በሚገኝ አንድ የሰርቪያ ኦርቶዶክስ ገዳም ውስጥ የገጠመውን እንዲኽ ይተርክልናል፦
‘ወደ ቤተ - ክርስቲያኑ ስገባ እኔ የመጨረሻው ነበርኹ። ቀድመው የገቡ ኹሉ ፊት ለፊታችን በምትገኝ ለየት ባለ ትልቅ ፍሬም የተቀመጠች ግድግዳው ላይ ተስቅላ ፊት ለፊቷም ላይ መቅረዝ ይበራባት በነበረች በአንዲት የእመቤታችን ስዕለ አድኅኖ ፊት እየተሳለሙ ሦስቴ እየሰገዱ ሲያልፉ እመለከታለኹ።
የሚያደርጉትን ተግባር ምን እያሰቡ ይሰግዱም እንደነበር አልተረዳኹትም ነበርና ተግባራቸውን በአትኩሮት እመለከት ጀመር። ኹሉም ተሳልመው ከጨረሱ በኋላ ተራዬ ደረሰና ወደ ስዕሏ ተጠጋኹ። “እኔ በዚኽ ቦታ ጎብኚ ነኝና ሌሎች እንዳደረጉት ማድረግ ይገባኛል” ስል አሰብኹ።
ምንም ለኔ ዐዲስና እንግዳ ነገር ቢኾንብኝም በጉልበቴ ተንበረከክኹ። ወደ ቤተ - ክርስቲያኑ ስገባ ስዕሏ የ “ወላዲተ - አምላክ” ወይም “የእመ - አምላክ” ስዕል እንደኾነች ሰዎች ነግረውኝ ነበር።
በጉልበቴ እንደተንበረከክኹ “እመ - አምላክ - የአምላክ እናት” ስለሚለው ስም ማሰብ ጀመርኹ። “እኔ በዚኽ ሰዓት እናት የለኝም። እግዚአብሔር ደግሞ አ‘ለው። እግዚአብሔር ስለምን እናት ኖረው? እኔስ ስለምን አልኖረኝም?” የሚል ሓሳብ ውስጥ ገባኹ። ያለ እናቴ ምን ያኽል ብቸኝነት እንደወረሰኝ እያሰብኹ ዕንባዬ በጉንጮቼ ላይ ይፈስስ ጀመር።
በዝግታ ተነሥኹና ኹለተኛውን ስግደቴን ለመስገድ ተዘጋጀኹ። እንደ ቀድሞው ተንበረከክኹና ግንባሬን መሬት አስነክቼ ተመሳሳይ ቃላትን ደጋግሜ እናገር ጀመር። ከዚያም ፥ ለስለስ ያለ ፣ ጥርት ያለ እና እጅግ መሳጭ ድምጽ “እኔ እናት እኾንኻለኹ” ብሎ ሲናገኝ ተሰማኝ። ምናልባት ከሰርቪያውያን ሴቶች አንዷ ከኋላዬ ደርሳ ልታጽናናኝ የተናገረችው መስሎኝ ቀኝና ግራዬን ዘወር ዘወር ብዬ ቃኘኹ። ነገር ግን ማንም አልነበረም።
ሦስተኛውን ስግደቴን ለመስገድ ቀጥ ብዬ ቆምኹ። በዚኽ ጊዜ ደጋግሜ ስጠራቸው የነበሩትን ቃላት ሙቀት ልምላሜ በተዋሕደው ጸሎት እጠራቸው ጀመር። እኔ ግን አልታወቀኝም ነበር። ታዲያ በዚኽም ጊዜ ቀድሞ የሰማኹትን ድምጽ “እኔ እናት እኾንኻለኹ” ሲል ደግሜ ሰማኹት። ማን እንደሚናገረኝ ለማወቅ ጓጓቼ ጣሪያ ጣሪያውን አስስ ጀመር። ምንም የለም። ነገር ግን በድንገት ስዕሏ ወደ እኔ አዘነበለች። ስዕለ አድኅኖው በቦታው እንዳለ ቅድስት ድንግል ማርያምም ከስዕሏ ወጥታ በፊቴ ቆመች። ፍቅርን በተመሉ ዓይኖቿም ፈገግ ብላ ትመለከተኝ ጀመር። ከዚያም ቃሏን ደገመችው ፦ 'እኔ እናት እኾንኻለኹ!'
ውስጤ ታላቅ የኾነን መጽናናትን አገኘ። ሕመሜና ሐዘኔ ጓዘቸውን ጠቅልለው ውልቅ አሉ። ውስጤ ቀምሼው በማላውቅ አንዳች ደስታ ተጥለቀለቀ። ሌላ እናት እንዳገኹ አወቅኹ። እመቤቴ አኹንም ዘንበል ብላ እየተመለከተችኝ ነው።እኔም ልጇን እጅግ በጥንቃቄ እንደምትንከባከብ እናት ኾና በብሩህ ገጽ እያየኋት ነው። ጭንቀቴ ኹሉ ጥሎኝ ጠፋ። ከእርሷ የሚወጣው የብርሃኑን ነጸብራቅ መቋቋም ስላቃተኝ ፥ ራሴን ዘንበል አደረግኹ። እርሷም ወደ ስዕሉ ተመልሳ ገባች። ቆም ብዬ አካባቢውን ቃኘኹ። ቤተ - ክርስቲያኑ እንደ ቀድሞው ጸጥታ እንደሰፈነበት ነበር። ማንም ኾነ ማን ምንም ምን አላየም ነበር።
(አባ አልዓዛር ከዚኽ በኋላ እመቤታችን ባደረግችላቸው ነገር ልባቸው ተነክቶ በብሐትውና ኑሮ በሕይወት እየኖሩ የሚገኙ አባት ናቸው።)
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን።
ተአምር ፪
~ ምልጃ ይሉኻል እንደዚኽ ነው! ~
ልመናዋ ክብሯ የልጇ የወዳጇም ቸርነት በኹላችን ላይ ይደርብንና አምላክን የወለደች በድንጋሌ ሥጋ በድንጋሌ ነፍስ የጸናች ክብርት እመቤታችን ያደረገችው ተአምር ይኽ ነው፦
የሳሮቩ አባ ሴራፊም (St.Seraphim of sarov) አንድ ቀን በጠዋት "ቅዱስ አባት ሆይ እርዳኝ! ቅዱስ አባት ሆይ እርዳኝ!" እያለ ወደርሱ የሚጮኽ ሰው ድምጽ ይሰማል። ይኽም ቅዱስ አባት ከሚኖርባት አነስተኛ በኣት ወጥቶ ወደ ሚጮኸው ሰው ድምጽ ይመጣል። ሰውዬውም በዕንባ ታጅቦ መለመኑን ተያያዘው፦ "ቅዱስ አባት ሆይ! ልጄ እየሞተብኝ ነው። ዶ/ሩ ምንም ማድረግ አልቻለም። ቅዱሱ ሆይ! እባክኽ ስለልጄ ጸልይልኝ ገና ስምንት ዓመቱ ነውና።"
አባ ሴራፊም ውስጡ ይረበሻል። በእርሱ ባደረበት መንፈስቅዱስ እግዚአብሔር የልጁን ነፍስ ይወስድ ዘንድ ቁርጥ ውሳኔ ማድረጉን ዐሳቡንም እንደማይቀር አውቋልና። ከዛም መለሰ ፦ "ልጄ ሆይ! ምንም ማድረግ አልችልም! እግዚአብሔር አምላክ የልጁን ነፍስ ይወስድ ዘንድ ቁርጥ ውሳኔን አድርጓልና" አለው። ሰውዬው ግን አኹንም አኹንም በዕንባ ይለምን ነበር። ቅዱስ ሴራፊምም መለሰ ፦ "እሺ ትንሽ ጠብቀኝ መጣኹ" ብሎት ወደ በኣቱ ይመለሳል። ከአፍታ ቆይታ በኋላ ተመልሶ መጥቶ "ልጄ ሆይ! ለቅሶኽን ተወው። ልጅኽም በሕይወት ይኖራል እንጂ አይሞትም" ይለዋል።
ሰውዬውም ለቅሶውን ትቶ በአግራሞት ይጠይቃል፦ "ቅዱሱ ሆይ! እንዴት የእግዚአብሔር ቁርጥ ውሳኔ ልታስቀይር ቻልኽ?" ይለዋል። ቅዱስ ሴራፊምም መለሰ ፥ እንዲኽም አለ፦ "ልጄ ሆይ! እኔ ውሳኔውን አላስቀየርኹም። እመ - አምላክ ውሳኔውን አስቀየረችው እንጂ!" ሲል መለሰለት።
አባ ሕርያቆስ "ወሥሉጥ ስምኪ በኀበ እግዚአብሔር - ስምሽ በእግዚአብሔር ዘንድ የሠለጠነ ነው!" ያለው ይኽንንም አይደል?
ይቆየን!
(ለጊዜው ምንጩን ካረሳኹት ከአንድ የውጭ ምንጭ የተተረጎመ)
ትርጒም፦ ዲ/ን ዳዊት ሰሎሞን
