መፅሐፈ ሔኖክ (Metshafe Henok)
Open in Telegram
አባቶቻችን ለኛ ብዙ ነገርን ትተውልን አልፈዋል እኛም ቢያንስ የተውልንን እያወቅን (እያነበብን) እንዘክራቸዋለን መዳሕኒአለም ባከበራቸው መጠን እናከብራቸዋለን።
Show more943
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
#የተሠጠህን_ቁጠር
ሔዋን ከዕባብ ጋር እየተነጋገረች ነው። የመጀመሪያ ጥፋትዋ ካለደረጃዋ ወርዳ ከዕባብ ጋር ወዳጅነት መጀመርዋ ሳይሆን አይቀርም። ዕባብ ደግሞ የሰይጣን አንደበት ነበረ።
ሰይጣን እንዲህ አላት፦ በውኑ እግዚአብሔር ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ አዝዞአልን? አላት።
ልብ አድርጉ እግዚአብሔር "ከገነት ዛፍ ሁሉ እንዳትበሉ" አላለም። የከለከለው አንዲት ዛፍ ነው። ሰይጣን ግን ሁሉን ተከልክላችሁዋል? ብሎ እንዳላዋቂ ጠየቀ። ሰይጣን በመጽሐፍ ቅዱስ ንግግሩን የከፈተው በውሸት ነበረ።
ዓላማው ከሔዋን መረጃ ለማግኘት አልነበረም። ሔዋን እስከዛሬ ያላሰበችውን ማሳሰብ ነበር። ብሉ ተብሎ ከተሠጣቸው ብዙ ሺህ ዛፍ ይልቅ የተከለከሉትን አንዲት ዛፍ አሳይቶአት ሔደ። ከዚያች ደቂቃ ጀምሮ ስላልተሠጣት ማሰብ ጀምራ ደስታዋን አጣች። የተከለከለችውን በልታ የተሠጣትን ብዙ ሥጦታ ከነሠጪው አጣች።
#ወዳጄ_የቀደመው_እባብ_ዛሬም_መርዙን_ይረጫል በሕይወታችን ከተሠጠን ብዙ ነገር ይልቅ ያልተሠጠንን ጥቂት ነገር እናስባለን። ገንዘብ እንደሌለህ እያሰብክ ጤና እንዳለህ ትረሳለህ። ጫማ እንደሌለህ እያሰብክ እግር እንዳለህ ትረሳለህ። አልጋ እንደሌለህ እያሰብክ እንቅልፍ እንዳለህ ትረሳለህ።
ስለዚህ ውስጥህ ያለውን የዕባቡን ድምፅ አትስማ ከሌለህ ይልቅ ያለህ ይበልጣልና የተሠጠህን ቁጠር።
(Deacon Henok Haile)
Repost from Tariku Abera
† ይድረስ በሃገር ውስጥና በውጭ ላላችሁ የነገረ መለኮት ምሩቃን አገልጋዮች†
† በቅዱስ ሲኖዶስ ላይ እየደረሰ ያለውን የመንግሥትና የማኅበር ጫና በጋራ በማቅለል ቤተክርስቲያንን ከፈተና እንታደግ።†
ቅድስት ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ደም የተመሰረተች የእግዚአብሔር መንግሥት በመሆኗ የቱንም ያህል ወጀብና ማዕበል በዙሪያ ቢያጓራም ጠባቂዋ መንፈስ ቅዱስ ሁሉን በኃይልና በጥበብ ያሻግራታል።ደግሞም ጌታ በቅዱስ ቃሉ የገሃነም ደጆች አይችሏትም ብሎ ስለመሰከረላት የገሃነም ደጆች ማለት ወደ ገሃነም የሚያስገቡ አጋንንት ቤተክርስቲያንን መቼም ይሁን መች አያሸንፏትም። ግራኝ መሐመድ ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያንን ሊያጠፋት ሞክሮ ነበር ፈጽሞ አልቻላትም እርሱ ጠፍቶ ቀረ ቤተክርስቲያን ግን እስካሁን በክብር አለች።ዮዲት ጉዲት ቤተክርስቲያንን ልታጠፋ ብዙ ታገለች እሷ እስከ ዘርማንዘሯ ጠፋች ቤተክርስቲያን ግን ዛሬም በክብር አለች።ጣሊያን ቤተክርስቲያንን ሊያጠፋ በከባድ መሣሪያ ታጅቦ መጣ እግዚአብሔር ግን ዶግ አመድ አድርጎ አሳፍሮ ጣለው ቤተክርስቲያን ግን እስካሁን በታላቅ ክብር አለች።ፓርችጋሉች፣ደርቡሾችና አረቦች በተለያየ ጊዜ ቤተክርስቲያንን ሊያጠፉ በተለያየ ዘዴ መጡ እግዚአብሔር እነርሱን ጠርጎ አጠፋቸው ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ግን እስካሁን በክብር አለች።ደርግ ሃይማኖት አያስፈልግም ብሎ ኦርቶዶክስን ሊያጠፋ በጉልበት ተነሳ እግዚአብሔር ጉልበቱን ሽባ አድርጎ ሥልጣኑን ከጫካ ለመጡ ጥቂት ኃይሎች ሰጥቶ እርሱን አዋርዶ ከኢትዮጵያ ነቀለው።ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ግን በይበልጥ አምራና ደምቃ ቀጠለች።ከደርግ ያልተማረው ሕወኃት እግዚአብሔር ኢትዮጵያን አሳልፎ እንዲመራ ቢሰጠው የኦርቶዶክስን አከርከሪ እሰብራለሁ ብሎ ጥጋቡ እናቱ ላይ ወጥቶ ከአመድ ያነሳውን እግዚአብሔር ረስቶ ቤተክርስቲያንን እጅጉን ተዳፈረ እግዚአብሔር የሕወኃትን አከርካሪ ሰብሮ በየጢሻውና በየፍርክታው ሰባብሮ ጥሎ አጠፋው። ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን ግን በታላቅ ክብር አሁንም ቀጥላለች ወደፊትም ትኖራለች።
ከታሪክ መማር ያልቻለው ርካሹና ምናምንቴው የዓቢይ አህመድ መንግሥት ደግሞ እርሱም በተራው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን በዘር ከፋፍዬ ኃይልና ጥንካሬዋን አዳክሜ የክልል ሲኖዶስ ብዬ ሰነጣጥቄ እጥላታለሁ ብሎ ትግል ጀምሯል እርሱንም እግዚአብሔር እንደ ሰናክሬም ሰነጣጥቆ እንደ ፈርዖን ላቀባበር እንዳይመች አድርጎ በመለኮታዊ ክንዱ አይቀጡ ቅጣት እንደሚቀጣው ምንም ጥርጥር የሌለው ሐቅ ነው ቅድስት ቤተክርስቲያን ግን ገና በክብርና በከፍታ ዘመኑን እየዋጀች ትቀጥላለች።የተመሠረተችው በእግዚአብሔር ልጅ በኢየሱስ ደም ነው።
ሁላችሁ እንደምታውቁት ቅዱስ ሲኖዶስ በዘንድሮው ስብሰባው ከፍተኛ የመንግሥትና የማኅበር ጫና በግራና በቀኝ እየተፈራረቀበት እንደሆነ በግልጽ እያየን ነው።ሁለቱም ወገኖች ከግራና ከቀኝ ሲኖዶሱን የሚጎትቱት ለቤተክርስቲያን ክብርና ሉዓላዊነት ተጨንቀው ሳይሆን የራሳቸውን ጥቅምና ህልውና ለማስቀጠል ነው።ይህንን ጉዳይ ሁላችን የነገረ መለኮት ምሩቃን በጥልቀት ልናስብበትና በንሥር ዓይን ልናየው ይገባል።
በመንግሥት በኩል የኦሮሙማን የፓለቲካ ፕሮጀክትን ለማሳካትና የኦሮሞ ኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮችን ከክልሉ ጋር ለብቻ ገንጥሎ የዘር ፓለቲካውን ማስቀጠል ስለሚፈልግ የኦሮሞ ክልላዊ ሲኖዶስ ለማቋቋም የኦሮሞ ጳጳሳትን ይዞ ቤተክርስቲያንን ለመገነጣጠል በጥርሱም በጥፍሩም እየተንፈራገጠ ነው።በሌላ ወገን ደግሞ ማኅበሩ በተለያየ ጊዜ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አባቶችን ይዞ የማኅበሩን ጥቅምና ህልውና የሚያስጠብቁለትን የተለያዩ አጀንዳዎች እየቀረጸ ለቅዱስ ሲኖዶስ በማቅረብ ፍላጎቱን ሲያሳካ ቢኖርም አሁን ግን ማኅበሩ እንደልቡ የሚጭናቸው ጳጳሳት እያጣ በመሆኑ ጩኽቱን አጠናክሯል።ምክንያቱም ከጊዜ ወዲህ በማኅበሩ ጫና ደስተኛ ያልሆኑ ጳጳሳት ቤተክርስቲያን ከማኅበሩ ተጽኅኖ ነጻ እንድትወጣ ብዙ ድምጻቸውን አሰምተው ነበር ሰሚ ግን ሳያገኙ ቀሩ። ቅዱስ ፓትርያርኩ ሳይቀር አምርረው በይፋ ቤተክርስቲያን "በማኅበሩ ቅኝ ግዛት ተይዛለች" ብለው ተናግረው ነበር እሳቸውንም የሚሰማቸው ጠፋ። ቤተክርስቲያኒቱ በመንፈሳዊ አገልግሎቷ፣በአስተዳደር ሥራዋና ምጣኔ ሃብቷን እስከ መቃረመት ደርሶ ማኅበሩ በቤተክርስቲያን አስተዳደር ውስጥ ጣልቃ እየገባ ብዙ አተካሮዎች ሲፈጠሩ መኖራቸውን ብዙዎቻችን የምናውቀው የአደባባይ ሐቅ ነው።በቅርቡም ቅዱስ ሲኖዶስ የማኅበሩ አባል ላይ የእርምት መስጫ መግለጫ በማውጣቱ ማኅበሩ ቅዱስ ሲኖዶሱን ሲያብጠለጥልና አባቶችን እየዘረጠጡ ከፍ ዝቅ ሲያደርጉ በይፋ ስንመለከተው የሰነበተ ጉዳይ ነው።
ማኅበሩ እኔ ያልኩት ካልሆነ ሞቼ እገኛለሁ በማለት የተለያዩ አባቶችን በተለያዩ ጊዜ በማሸማቀቅና የግል ጉዳያቸውን እንደማስፈራሪያ በመያዝ መጠቀሚያ ቢያደርጋቸውም ይህንን ችግር ሲኖዶሱ በጋራ እንዲፈታ አጀንዳዎች ብዙ ጊዜ ቢቀርቡም ውሳኔዎች ግን መተግበር አልቻሉም፤ ስለዚህም የትግራይ ጳጳሳት የራሳቸውን ሲኖዶስ ገንጥለው ማህበሩን ከአካባቢያቸው አጽድተው አስተዳደራዊና መንፈሳዊ አግልግሎታቸውን ቀጥለዋል፣የኦሮሚያ ጳጳሳትም የኦሮሞ ቤተክህነት የሚባለውን አቋቁመው ማኅበሩን ከክልላቸው እያዳከሙና እያከሰሙ አሁን የራሳቸውን ክልላዊ ሲኖዶስ ለማቋቋም እየታገሉ ነው።ሁለቱም የትግራይና የኦሮሚያ ክልል ጳጳሳት ራሳቸውን እስከመገንጠልና ከቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባዔ እስከ መለየት ያደረሳቸው ምንም እንኳ የፓለቲካ ኃይሎች ድጋፍ ከጀርባቸው ቢኖሩም የተማረሩበትና በዚህ ደረጃ የተንገፈገፉበት ጉዳይ ግን የማኅበሩ ጫና ነው።ወደፊት የሌሎች ክልሎች ሲኖዶስ ወደፊት ላለመፈጠሩ እርገጠኞች መሆን አንችልም።
ማኅበሩ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ላለፉት ሦስት አስርት ዓመታት ብዙ የቤተክርስቲያን አገልጋዮች የማኅበሩን ሥህተቶች በመቃወማቸው ብዙዎች ተሰደዋል፣ብዙዎች ተገፍተዋል፣ብዙዎች የስም ታፔላ ተለጥፎባቸዋል፣ብዙዎች በአድማና በሴራ ከቤተክርስቲያን ወጥተው ወደ ሌላ ቤተ እምነት እንዲገቡ ተገደዋል።በዚህም ቤተክርስቲያን ብዙ ተጎድታለች፣ብዙ ልጆቿን አጥታለች፣ባለፋት ሦስት አስርት ዓመታት ውስጥ ከ20 ሚሊየን በላይ ኦርቶዶክሳውያን ወደ ሌሎች ቤተ እምነቶች እንዲፈልሱ ሆነዋል።ይህ ለቤተክርስቲያን ታላቅ ኪሳራ ነው።ደቡብ ኦሞ እየሄድክ ወንጌል ሳትሰብከው ነጭ አቡጀዴ እያከፋፈልህ እያለበስክ አጥመኩት እያልክ ጥፋትህን ለመሸፋፈን ፕሮፓጋንዳ ብትሰራም ምናልባት አንዳንድ የዋሕ ክርስቲያኖችን ታታልል ይሆናል የቤተክርስቲያን አምላክ ግን ስለሰራኸው ግፍ ቀን ጠብቆ የዘራኽውን ያሳጭድሃል እንጂ በእዚህ አይታለልም።
ስለዚህ የቅድስት ቤተክርስቲያን ልጆች የሆናችሁ የነገረ መለኮት ምሩቃን በሃገር ውስጥና በውጭ ያላችሁ በሙሉ ከየትኛውም ወገን ሳትሆኑ ለማኅበሩም ሆነ ለፓለቲካ ጥገኞቹ ሳታደሉ ለቤተክርስቲያን ክብርና ህልውና ስትሉ ለቅዱስ ሲኖዶስ አስፈላጊውን የመፍትሔ ሐሳብ እንድታቀርቡና ቤተክርስቲያን ከገባችበት የፈተና አጣብቂኝ በጋራ እንድንታደጋት ስል በክርስቶስ ፍቅር እጠይቃለሁ።ማኅበሩ ሳይኖር ቅድስት ቤተክርስቲያን ነበረች ያለ ማኅበሩም ቤተክርስቲያን ጸንታ ትኖራለች ትኩረታችን ታላቋ ቤተክርስቲያን ላይ ይሁን።
ታናሽ ወንድማችሁ መ/ር ታሪኩ አበራ
ሼር በማድረግ አድርሷቸው
ሚካኤል (በዕብራይስጥ: מִיכָאֵל, ሲነበብ፡ ሚካኤል, ሲተረጎም፡ 'ማንነው እንደ እግዚአብሔር?'; በግሪክ: Μιχαήλ, ሲነበብ፡ Mikhaḗl; በላቲን: Michahel-ሲነበብ፡ ሚካኤል; በአረቢኛ: ميخائيل, ሲነበብ፡ ሚካኤል) በክርስትና በአይሁድ በእስልምና እንዲሁም በመላዕክት አማላጅነት በሚያምኑ ሃይማኖቶች የመላዕክት ሁሉ አለቃ ሊቀ መላዕክት ተብሎ ይጠራል።
መላእክት ቊጥራቸው እጅግ ብዙ ቢሆንም በ 99ኙ ነገደ መላእክት የተከፈሉና አለቆችም ያሏቸው ናቸው፡፡ የእነዚህ ሁሉ መላእክት አለቃ የሆነው ቅዱስ ሚካኤል ነው፡፡ በትህትናው ልዕልናን ያገኘው ቅዱስ ሚካኤል በእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠው ክብር ከማንኛውም መልአክ የበለጠ መሆኑን መጽሐፍ ቅዱስ በግልጽ አስቀምጦታል፡፡
በተጨማሪም ስለ መላእክት ከመጽሐፍ ቅዱስ ለመረዳት እነዚህን ጥቅሶች ይመለከቱ:-
• ሰውን ይረዳሉ [ዘፍ.16፡7፤ ዘፍ.18፡15፤ ዘጸ.23፡20፤ መሳ6፡11፤ 1ኛነገ.19፡5፤ 2ኛነገ 6፡15፤ ዳን.8፡15-19፤ ዳን.3፡17፤ ት.ዘካ.1፡12፤ ማቴ.18፡10፤ሉቃ. 1፡26፤ ሉቃ.13፡6፤ ዩሐ.20፡11፤ ሐዋ.12፡6፤ ራዕይ 12፡7፤]
• ስግደት ይገባቸዋል [ዘፍ.19፡1-2፤ ዘኁ.22፡31፤ ኢያሱ 5፡12፤ መሳ.13፡2፤ 1ኛ ዜና 21፡1-7፤ ዳን.8፡15]
የቅዱስ ሚካኤል ስሞች
ሚካኤል ማለት << መኑ ከመ አምላክ (እግዚአብሔር) እንደ እግዚአብሔር ያለ ማነው>> ማለት ነው፡፡ ይህም የእግዚአብሔርን ገናንነትና እሱን የሚመስል አምላክ እንደሌለ የሚያመለክት ነው እንደ እግዚአብሔር ያለ ቅዱስ ንጹሕ ርህሩህ ኃይል ረቂቅ ማነው መልሱ የለም ነው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል የስሙ ዘርፍ ሆነው የሚጨመሩ መጠሪያዎች አሉት እነዚህም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠውን የባለሟልነት ክብር የሚገልጹ ናቸው፡፡ ይኸውም መልአከ ኃይል፣ መጋቤ ብሉይ፣ መልአከ ምክሩ፣…ናቸው፡፡
• መልአከ ኃይል የተባለው እግዚአብሔር በሱ አማካይነት ታላላቅ ሥራዎችን በመሥራት ኃይሉን ስለገለጸ - ዲያብሎስን ከነሠራዊቱ ስላሸነፈ ነው፡፡
• መጋቤ ብሉይ የተባለበት ምክንያት በብሉይ ኪዳን ውስጥ ከእግዚአብሔር እየተላከ ብዙ ታላላቅ ሥራዎችን የሠራ በመሆኑ ነው፡፡
• መልአከ ምክር ወይም የእግዚአብሔር የምክሩ አበጋዝ የተባለበት ምክንያት እግዚአብሔርን በምክሩ ይረዳዋል ለማለት ሳይሆን እግዚአብሔር የሚሠራውን ሥራ ለወዳጁ ለቅዱስ ሚካኤል ይገልጽለታል በሱም አማካኝነት ይሠራል
በዚህም እለት በታላቅ ድምቀት ከምናከብራቸው በዓላት ውስጥ አንዱ አባታችን አቡነ ተክለሃይማኖት ፍልሰተ አጽሙ ነው። በ1267 ዓ.ም ደብረ ሊባኖስን በአት አድርገው ኖሩ፡፡ ለ22 ዓመት ቆመው በመጸለይ የአንድ እግራቸው አገዳ ተሠበረ ደቀ መዝሙሮቻቸው በጨርቅ ጠቅልለው ቀበሩት፡፡ በአንድ እግራቸው ለ7 ዓመት በጸሎት ቆሙ በጠቅላላው ለ29 ዓመት በጸሎት ከቆሙ በኋላ በ99 ዓመት ከ10 ወር ከ10 ቀን ነሐሴ 24 ቀን 1290 ዓ.ም አረፉ። አባታችን ባረፉ 54 ዓመታቸው በ1354 ዓ.ም ለአባታችን ለአቡነ እዝቅያስ ተገልጸው አጽማቸው ከደብረ አስቦ ወደ ደብረ ሊባኖስ ግንቦት 12 ቀን እንዲፈልስ አድርገዋል፡፡
ኅዳር 24 ቀን 25ተኛ ካህናተ ሰማይ ሆነው በሰማይ የሥላሴን መንበር ያጠኑበት
ታኅሣሥ 24 ቀን የአባታችን ልደት፤ ጥር 24 ቀን የአባታችን ስባረ አጽም፤ መጋቢት 24 ቀን የአባታችን ጽንሠት፤ ግንቦት 12 ቀን የአባታችን ፍልሰተ አጽም፤ ነሐሴ 24 ቀን የአባታችን እረፍት የአባታችን ቡራኬ ይድረሰን አሜን!
“ልጆቼ ሆይ ሁሉም መነኩሴ መንግሥተ ሰማይ ይገባል ማለት አይደለም ዓለምን በሚገባ የናቀ ብቻ ይገባል እንጂ መጀመሪያ የእግዚአብሔርን ጽድቁን ብቻ ፈልጉ ጾምና ጸሎትን አዘውትሩ እርስ በእርሳችሁም ተዋደዱ ትዕዛዛቱንም ጠብቁ” የሐዲስ ኪዳኑ ሙሴ የአባታችን የተክለሃይማኖት ምክር።
አቡነ ተክለሃይማኖት, የመጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ጳጳስ ...
በወላጅ አባታቸው በካህኑ ቅዱስ ጸጋ ዘአብ ግብረ ዲቁናን ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን ሲያጠኑ ቆይተው በአሥራ አምስት ዓመታቸው ከእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቄርሎስ /ቄርሎስ/ ዲቁናን ተቀብለዋል፡፡ በዚህም ቅድስት ቤተክርስቲያንን በወጣትነት ዕድሜያቸው ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡
አባታችንም ሐዋርያዊ ጉዟቸውን ሲጀምሩ
«አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ . . . ደካማ ለሆንኩ ለእኔ ያለ አንተ የሚያፀናኝ የለም። ለምፍገመገም ለእኔ ያለ አንተ ደጋፊ የለኝም። ለወደቅሁ ለእኔ ያለአንተ የሚያነሳኝ የለም። ለአዘንኩ ለእኔ ያለአንተ የሚያረጋጋኝ የለም። ለድሀው ለእኔ ያለ አንተ መጠጊያ የለኝም፡፡» [ገድለ ተክለ ሃይማኖት ምዕ 28 ቁ 2 - 3]
ይህን ብለው ትሕትና በተሞላበትና በተሰበረ ልብ ወደ ፈጣሪያቸው ከለመኑ በኋላ በልዩ ልዩ የኢትዮጵያ ክፍለ ሀገራት ከኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከክህደት ወደ ሃይማኖት መልሰዋል፡፡ በዚህም የተነሣ ለኢትዮጵያውያን ብርሃን ፀሐይ ተብለዋል፡፡
የቅዱስ ሚካኤል እና የአባታችን የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ምልጃና ጸሎት ከእኛ ጋር ይሁን
Repost from Aesop Ethiopia
ውድ የኤሶፕ ኢትዮጵያ ቤተሰቦች ሰላም ለእናንተ ይሁን። እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እሁድ 30/4/23 እኤአ፥ በዚህ መርሃ ግብር በቀጥታ ስርጭት እንቀርባለን። እስከዛው ለሌሎች ሼር ማድረግን እንዲሁም ሰብስክራይብ ማድረግን አትርሱ። ዘመኑን አብረን እንዋጅ። እውነትን ማወቅ አርነት ያወጣናል።
የብልጽግና ወንጌል ምንድን ነው?
ብዙ ጊዜ የብልጽግና ወንጌል ሲባል ሰዎች ስለ ብልጽግና ፓርቲ የምናወራ ይመስላቸዋል። ነገር ግን ሁለቱ የተለያዩ ጽንፎች ናቸው። የብልጽግና ወንጌል ሃይማኖት ሲሆን ብልጽግና ፓርቲ ደግሞ የፖለቲካ ድርጅት ነው።
የምዕራባውያን ርዕዮተ ዓለም ይህችን ዓለም ለመሰልቀጥ ካሰፈሰፈ ዘመናት ተቆጥረዋል። በብዙ ክፍላተ ዓለማት ተሳክቶለታል። በከፊል አፍሪካ፣ በቻይናና በሩሲያ ግን ምናብ ከሆነበት ሰነባብቷል። አፍሪካን ሙሉ ለሙሉ ለመቀራመት እንቅፋት የሆነችበት ኢትዮጵያ ናት። ከኢትዮጵያ ደግሞ ኦርቶዶክስ ሃይማኖት እና አማራ ብሔር ዋነኛ እንቅፋቶቻቸው እንደሆኑ ከጥንት እስከ ዛሬ በድርሳኖቻቸው ሲከትቡ ኖረዋል። ሀገር በቀሉ እስልምናም በሦስተኛ ጠላትነት ይፈረጃል።
ምዕራባውያን ርዕዮታቸውን በገቢር ለማየት ሁሉንም ሃይማኖት ሲመረምሩ በግማሽ አመቺ ሆኖ ያገኙት የማርቲን ሉተር ፕሮቴስታንቲዝም ነው። ፕሮቴዝታንቲዝምን በሚመቻቸው መንገድ ጠፍጠፈውም የብልጽግና ወንጌል የሚባል አዲስ እምነት መሠረቱ። ይህ የብልጽግና ወንጌል እምነት ለምዕራባውያን ርዕዮት መተግበሪያ እጅግ ምቹ ነው። ሰዎቹም በእምነት ስም ማደንዘዝ እንጂ እምነት አልባ ግዑዞች ናቸው። ዶር ዐቢይ አሕመድ በምዕራባውያን ርዳታ ወደሥልጣን ሲመጣ የቃልኪዳን ሰነዱ የብልጽግናን ወንጌል ማስፋፋት፣ ለዚህ እንቅፋት የሚሆኑትን በየትኛውም ቦታ የሚገኙ ኦርቶዶክሳውያንን እና አማራን ሽባ አድርጎ፣ በነቢብ ብቻ እንዲታወቁ በገቢር ግን ልፍስፍስ እንዲሆኑ መሥራት ነው።
ይህንን ለመተግበር ወጣቱን በጦርነት መቀነስ፣ ጠንካራ ተቋማትን መከፋፈል፣ ማክሰም፣ ሰርጎ ገቦችን አስርጎ ከነባቢነት ያለፈ ግብር እንዳይታይባቸው ማድረግ እና በስተመጨረሻም የብልጽግናን ወንጌል በሀገሪቱ ማዳረስ ግባቸው ነው።
የሰሜኑ ጦርነት ያልገባቸው ሰዎች ፖለቲካዊ አንድምታ ይስጡት እንጂ ዋና ግቡ ኦርቶዶክሳውያንን መቀነስ ነበር። በዚህም ዋነኛ ተጠቂዎቹ ተጋሩና አማራ በመሆናቸው በሁለቱም ክልል በመቶ ሺህዎች ሞተዋል። አካል ጉዳተኛ ሆነዋል። የትግራይ ገዳማት እና አድባራት ተዘርፈዋል፤ ፈራርሰዋል።
አሁን በአማራ ክልል የሚጎሰመው ጦርነትም የብልጽግና ወንጌል አማኞች ኦርቶዶክስን ለመምታት ያሰፈሰፉበት ድርጊት ነው። የጦርነቱን አጨራረስ የሚያውቀው እግዚአብሔር ቢሆንም፣ የሚፈለገው ግን ኦርቶዶክሳውያንን መጨፍጨፍ፣ ገዳማትና አድባራትን ማፍረስ፣ ቅርሶችን መዝረፍና ብዙዎችን አካል ጉዳተኛ አድርጎ ጎዳና ላይ መጣል ነው። በስተመጨረሻም በሌላ አካባቢ ያሉ ኦርቶዶክሳውያንን ድምፅ አልባ አድርጎ አንድ በአንድ መጨረስ ነው።
ይህ ነገሮችን አቅልለው ለሚያዩ የዋሃን ተራ ወሬ ይመስላቸዋል። ነገሮችን በጥልቀት ለሚመረምሩ ልበ ብርሃኖች ግን ግልጽ ነው። የብልጽግና ርዕዮተ ዓለም ታላቅ ግቡ ኦርቶዶክስን ማጥፋት ነው። ላለመጥፋት ትልቁ መፍትሔ ርዕዮቱን መታገል ብቻ ነው።
እነሆ አውሮፓውያን የብልጽግና ወንጌልን ወለዱ፤ የብልጽግና ወንጌል ብልጽግና ፓርቲን ወለደ። የሆነው ይህ ነው። ቀጣይ ጉዳዮችን ይዘን እንመለሳለን።
ድምፀ ተዋሕዶ - VoT
ቴሌግራም ቻናላችንን ይቀላቀሉ።
https://t.me/onesinod
Repost from Tariku Abera
† በእርሱ ቁስል እኛ ተፈወስን †
ኢሳይያስ 53 ፥ 5. "እርሱ ግን ስለ መተላለፋችን ቈሰለ፥ ስለ በደላችንም ደቀቀ፤ የደኅንነታችንም ተግሣጽ በእርሱ ላይ ነበረ፥ በእርሱም ቍስል እኛ ተፈወስን።"
የክርስቶስ ውበቱ በደም ላብ መታየቱ ነው።የዓለምን ውበት ከንቱ ያደረገው፣ ሕዝብና አሕዛብን፣ጠቢባንና ኃያላንን በፍቅር ያንበረከከው በክርስቶስ ገጽ ላይ የፈሰሰው የደም ጅረት ነው። ይህ ደም በፍቅር መግነጢሳዊ ኃይል ስቦ ወደ ጸጋው ዙፋን የማቅረብ ረቂቅ ኃይል አለው።ይህ ደም እንደ ሳሮን ጽጌረዳ ፣ እንደ አልባስጥሮስ ሽቱ ፣ከሩቅ እንደ ሚሸት እንደ ናርዶስ መዓዛ ነፍስን በደስታ የሚያውድ በልብም ሰላምን የሚያፈስ የፍቅር መዓዛ አለው። ይህ ደም በገለሃድ ተራሮች ላይ እንደ ሚወርድ እንደ አርሞንኤም ጠል ልዩ ውበት አለው። ከዚህ ደም ጋር ሕያው ፍቅር አብሮ ሲፈስ ታይቷል ፣የምህረትና የርኅራኄ ድምጽ ከደሙ ውስጥ ሲጮኽ ተሰምቷል፤ላመኑበትና ለተቀበሉት ሁሉ በዚህ የዘለዓለም የኪዳን ደም የኃጢአት ሥርየት፣ ይቅርታና ሰላም ታውጇል።
ዓለም ከተፈጠረ ዘመን ከተቆጠረ ጊዜ ጀምሮ ሕዝብን ሁሉ በፍቅር ያንበረከከ፣የፍጥረትን ዓይን ሁሉ በውበቱ የማረከ፣ ያለ አዋጅ ጠርቶ፣ጽድቅን ያለ ዋጋ እንዲያው በጸጋ ያጎናጸፈ የክርስቶስ ደም ብቻ ነው። ይህ ቅዱስ ደም ዋነኛውና ብቸኛው እስከ ዛሬም አቻ ያልተገኘለት የነፍሳችን ቤዛ፣የድኅነታችን ዋስትና የጽድቃችን ማረጋገጫ፣እግዚአብሔርን ያየንበት፣ዕለት ዕለት በእግዚአብሔር ዓይን የምንታይበት የዕርቅ ማህተባችን እንደ በግና እንደ ጊደር ደም ዕለት ዕለት መፍሰስ ሳያስፈልገው አንድ ጊዜ ፈሶ ለዘለዓለም ሲያድን የሚኖር ብቸኛው የጽድቅ መስዋዕት የሕያው እግዚአብሔር ልጅ የኢየሱስ ደም ብቻ ነው።
የሁላችንን የልብ ትጥቅ አስፈትቶ ከመስቀሉ ሥር ያንበረከከን የትኛውም የጦር ኃይል ሳይሆን፤ ደም የተረጨ ፊቱ ፣በጅራፍ የተነቀሰ እትራቱ ፣በመከራ የደቀቀ ሰውነቱ፣በችንካር የቆሰለ መዳፋ፣በሌንጊኖስ ጦር የተዋጋ አካሉ ነው።ጦር ከማረከው ይልቅ ፍቅር የማረከው ይበልጣልና የዓለም ጠቢባንና ነገሥታትን ሳይቀር በፍቅር ማርኮ፣በእምነት ያንበረከከው በእግዚአብሔር አንድያ ልጅ በኢየሱስ ክርስቶስ ልብ ውስጥ የታየው እውነተኛ ፍቅር ነው።እርሱ ስለ መተላለፋችን ቆሰለ፣ስለ በደላችን ደቀቀ፣የሁላችንን ነውር እርሱ ተሸከመ ፣ተሰቃየ፣ደከመ፣ከአመፀኞችም ጋር ተቆጠረ፣ለመታረድ እንደሚነዳ ጠቦት፣በሸላቾቹም ፊት ዝም እንደሚል በግ በገመድ ተጎተተ፣በኃይል አሰሩት በፍቅር ተከተላቸው፣በግፍ ሰቀሉት በምሕረት ተመለከታቸው፣ ከብዙ ዕንባ ጋር ጸሎትና ምልጃንም አቀረበ ልጅ ስለ መሆኑም ተሰማለት።በእርሱ ቁስል እኛ ተፈወስን።ያ ትኩስ ደም ዛሬም ስለ እኛ በአብ ፊት ይጮኻል።ከደሙም የተነሰ ምህረትና ይቅርታ ከልዑል ዙፋን ላመኑትና ለተቀበሉት ሁሉ ይፈሳል።
" የአዲስም ኪዳን መካከለኛ ወደሚሆን ወደ ኢየሱስ፥ ከአቤልም ደም ይልቅ የሚሻለውን ወደሚናገር ወደ መርጨት ደም ደርሳችኋል።"
(ወደ ዕብራውያን 12:24)
የአቤል ደም ከምድር ወደ አርያም ፍረድልኝ እያለ ሲጮኽ የኖረ ከሳሽ ደም ነው።የክርስቶስ ደም ግን ከአቤል ይልቅ የሚሻል ደም ነው ማርልኝ፣ይቅር በልልኝ እያለ የሚሻለውን የሚገር የሚያስታርቅ ደም ነው።
የክርስቶስ ደም እንደ ተራ ሰው ደም እንዲሁ በከንቱ ፈሶ የቀረ ደም አይደለም፤ መለኮት የተዋሐደው ሕያው ደም ስለሆነ ያመነበትን ሁሉ ሲያነጻና ሲቀድስ ለዘለዓለም የሚኖር ሕያው መታረቂያ ነው። የክርስቶስ ደም የፈሰሰው በእግዚአብሔር ዘለዓለማዊ መለኮታዊ ዕቅድ ለዘለዓለም ሲያድን እንዲኖር በዓላማ የፈሰሰ ደም ነው።የበጎችና የጊደሮች ደም በየዕለቱ ስለ ሰው ልጆች ኃጢአት ማስተሰርያ ቢፈሱም ፍጹም ድኅነትንና ዘለዓለማዊ ሕይወትን ማስገኘት አልቻሉም።ደግሞም ማንኛውም የኦሪት አማኝ ኃጢአት በሰራ ቁጥር የበግ ጠቦት ተሸክሞ የኦሪቱን ካህን ፍለጋ ወደ መገናኛው ድንኳን በመሄድ እጁን በበጉ ላይ ጭኖ በመናዘዝ ስለ እርሱ ኃጢአት በጉ እንዲሰዋ አድርጎ በበጉ ደም ስርየት ይደረግለት ነበር።
ዘሌ 4:1
አሁን በሐዲስ ኪዳን ግን ዕለት ዕለት የሚሰዋልን መስዋዕት የለም አንድ ጊዜ ቀራንዮ ላይ የተሰዋልን ደም ነው ሕያው መታረቂያ ሆኖ የተሰጠን። በእምነትና በንስሐ ወደ ክርስቶስ የሚቀርቡትን ሁሉ ያ ደም ዛሬም ሲያነጻቸው፣ሲቀድሳቸው፣ሲያስተርቃቸው ይኖራል።
ዛሬ በአዲስ ኪዳን መቅደስ ዕለት ዕለት አዲስ መስዋዕት እየሰዋን ሳይሆን አንድ ጊዜ ሊቀ ካህናችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ መስዋዕት አቅራቢ፣ራሱ መስዋዕት ተቀባይ፣እርሱ ራሱ መስዋዕት ሆኖ የሰዋልንን ደም ነው ዕለት ዕለት በእምነት ይምንቀበለው።
ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ እንዲህ ይላል"አኮ ዘንሰውዕ መስዋዕተ ካልዐ ከመ ሊቀ ካህናት አላ ኪያሁ ንሰውዕ በጽድቅ።"
"አሁን የምንሰዋው መስዋዕት እንደ ኦሪቱ ሊቀ ካህናት ዓይነት ያለ መስዋዕት ሳይሆን ራሱን የዕለተ አርቡን እንሰዋለን እንጂ።"/ድርሳን ዘዮሐንስ አፈወርቅ/
እኛ ኢትዮጵያውያን ከማንም በላይ የቤዛነት ደም ትርጉም በደንብ ይገባናል። ጀግኖች አባቶቻችን አንድ ጊዜ ባፈሰሱት ደም ለዘለዓለም ከቀኝ ግዛት ነጻ የወጣን የነጻነት ምድር ልጆችነን። አንድ ጊዜ የፈሰሰው የጀግኖቹ ደም በባርነት እንዳንያዝ በቅኝ ግዛት እንዳንዋረድ ዘለዓለማዊ ነጻነትና ክብርን አቀዳጅቶናል።የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ደግሞ ከዚህ ይልቃል አንድ ጊዜ በመስቀል ላይ ፈስሶ ለዘለዓለም ከየትኛውም ዓይነት ኃጢአት ሁሉ ነጻ ሲያደርገን ይኖራል።ከእኛ የሚጠበቀው ማመንና በንስሐ በጌታ ፊት መውደቅ ነው። "የኢየሱስ ክርስቶስ ደም ከኃጢአት ሁሉ ያነጻል" ተብሎ ተጽፏል።ሁሉ የሚለው ቃል ገደብ የለሽና ከክርስቶስ ደም በላይ የሆነ ምንም ዓይነት ኃጢአት አለመኖሩን የሚያበሥር ቃል ነው ።1ዮሐ 1:7
ንስሐ ከገባን ሁላችን ጽድቅን ወራሾች ነን።
ወገኖቼ አትጨነቁ ጠላት ዲያብሎስም በተለያየ ጊዜ የሰራነውን ኃጢአት እያስታወሰ ተስፋ ሊያስቆርጠን ቢሞክርም ለአንድ አፍታ ያህል እንኳ ዕድል ልንሰጠው አይገባም። በእግዚአብሔር ፊት ከእኛ ኃጢአት ይልቅ የክርስቶስ ደም ሚዛን ይደፋል።የደሙን ኃይል አልፎ የሚያገኘን ምንም ዓይነት ፍርድና ኩነኔ የለም።በክርስቶስ አምነን በደሙ ጽድቅን እንደምናገኝ በልብ ተቀብለን በንስሐ የምንበረከክ ሁሉ እግዚአብሔር እኛን የሚመለከተን በልጁ በክርስቶስ ደም በኩል ስለሆነ ከኃጢአታችን ይልቅ የጌታ ደም ሚዛን ደፍቶ ምሕረትና ይቅርታን እናገኛለን።ስለዚህም በንስሐና በእምነት ወደ ክርስቶስ እንቅረብ።እርሱ ሸክማችንን ሊያቀል ቀንበራችንን ሊሰብር የታመነ አምላክ ነው ክብር ሁሉ ለስሙ ይሁን።"በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉ አሁን ኩነኔ የለባቸውም።" ሮሜ 8፥1
ኢየሱስ ሆይ በአንተ ደም በኩል በአብ ፊት በልጅነት ክብር መታየት ሆኖልናልና ስምህ ለዘለዓለም ከፍ ከፍ ይበል።አማኑኤል ሆይ የመለኮት ባሕርይ ተካፋይ አድርገኽናልና አምልኮና ውዳሴ ላንተ ይሁን።ኢየሱስ ሆይ ማንም የማይነጥቀን ሰላማችን ነህና ውዳሴና ጌትነት ለክብርህ ይሁን።
እባካችሁ ምሥጋናውን ለሌሎችም አካፍሉት።
መ/ር ታሪኩ አበራ
+ ወደ ኖኅ መርከብ ለመጨረሻ ጊዜ የገባችው እንስሳ +
የኖኅ መርከብ ጉዳይ በጣም አስገራሚ ከሚሆኑብኝ የመጽሐፍ ቅዱስ ታሪኮች አንዱ ነው:: በዓለማችን አሁን ያሉ እንስሳት ሁሉ "ከነ ባለቤትዎ" እንዲገኙልን እንደሚባልበት ሰርግ ጥንድ ጥንድ ሆነው የገቡባት ትልቅ መርከብ ታሪክ : ዳግም ለሰው ልጆች ወላጆች ለመሆን የተመረጡ አራት ወንዶችና አራት ሴቶች ብቻ የተሳፈሩባት ትልቅ መርከብ ሁኔታ ትኩር ብሎ ላየው አስገራሚ እውነቶችን ያዘለ ነው::
ከሁሉም በላይ ግን መርከቢቱ የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ መሆንዋ ብዙ ነገር እንድናስብ ያግዘናል:: ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ "ወደ ኖኅ መርከብ ተኩላ ገብቶ ሲወጣም ተኩላ ሆኖ ይወጣል:: ወደ ቤተክርስቲያን ግን ተኩላ ሆነው ገብተው በግ ሆነው የወጡ ብዙዎች ናቸው" ብሎአል::
እውነትም ቤተ ክርስቲያን ወደ እርስዋ የገቡትን መለወጥ የምትችል መርከብ ናት:: ወደ ቤተ ክርስቲያን እንደ ጅብ ሆዳም ሆነው ገብተው ጾመኞች ሆነው የወጡ አሉ:: እንደ የሌሊት ወፍ በቀን መኖር አቅቶአቸው ሌሊቱን የልባቸው ዓይን ታውሮ በኃጢአት ጨለማ ሲደናበሩ የኖሩ ሰዎች ወደ መርከቢቱ ገብተው እንደ ንስር አርቀው አጥርተው ቀኑን የሚያዩ ሆነዋል:: ቤተ ክርስቲያን ወደ እርስዋ የገቡትን የምትለውጥ መርከብ ናት:: ውኃ ወደ እርስዋ ሲገባ ጠበል ይሆናል:: አፈር ወደ እርስዋ ሲገባ እምነት (እመት) ይሆናል:: ዘይት ወደ እርስዋ ሲገባ ቅዱስ ቅባት ይሆናል:: ኅብስትና ወይን ወደ እርስዋ ሲገባ ወደ ቅዱስ ቁርባን ይለወጣል::
ወደ ቤተ ክርስቲያን ገብቶ ያልተለወጠ ሰው ግን ሲገባም ጅብ ሲወጣም ጅብ ሆኖአል:: ኖኅ ከመርከብ መልእክት ልኮት የቀረው የቁራ ነገርስ? ከቤተ ክርስቲያን ወጥተው ስንቶች በዚያው ቀርተዋል? ለዓለም ጨው እንዲሆኑ ተልከው በዚያው ሟሙተው የቀሩ ስንት አሉ:: ርግብ ግን ማረፊያ ስታጣ ተመልሳ ነበር:: ከመርከቢቱ የራቅን ሁላችን "ልባችን በእግዚአብሔር እስካላረፈ ድረስ ዕረፍት የለውም" እንዳለ ሊቁ ወደ መርከቢቱ ፈጥነን መመለስ አለብን::
ሰሞኑን ደግሞ አንድ ጥያቄ በአእምሮዬ ተመላለሰብኝ:: "ወደ ኖኅ መርከብ ለመጨረሻ ጊዜ የገባው እንስሳ ማን ሊሆን ይችላል?" የሚል:: ይህን ጥያቄ በግልም በጉባኤ ላይም ሰዎችን ጠይቄ ነበር:: መቼም ለዚህ ጥቅስ አያስፈልገውም:: ኖኅ ቆሞ እንስሳቱ እስኪገቡ ድረስ እንደጠበቀና ማንንም እንስሳ ጥሎ እንዳልገባ የታወቀ ነው::
በዚህ ምክንያት እንስሳቱ ወደ መርከቢቱ የሚገቡት እንደደረሱበት ቅደም ተከተል ነው:: ክንፍ ያላቸው በርረው ቀድመው ይገባሉ:: እንደ ጥንቸል እንደ ካንጋሮ እንደ ሚዳቁዋ ያሉትም እየዘለሉ ፈጥነው ይገባሉ::
ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነፍሳቸውን ለማዳን ፈጥነው በርረው የገቡ እንደ ሚዳቋ ዘልለው የደረሱ ብርቱዎች አሉ:: እንደ ፒኮክ ያሉ ባለ ውብ ክንፎች : እንደ ቀጭኔ ያሉ ባለ ረዥም አንገቶች እንደ ጃርት ያሉ ሌላው ላይ የሚሰኩት እሾኽ የለበሱ እንስሳት ወደ መርከብዋ ገብተዋል:: በቤተክርስቲያን እንደ ፒኮክ አምሮ መታየት መዘባነን የሚወዱ ለታይታ የሚገዙ ብዙዎች ገብተዋል:: እንደ ቀጭኔ አንገታቸውን ከፍ አድርገው ሰውን ቁልቁል የሚመለከቱና "አንገታቸውን እንደሚያገዝፉ የዕብራውያን ሴቶች" ዓይነት ሕይወት ያላቸውም ገብተዋል:: እንደ ጃርት በክፉ ንግግር የሰው ልብ ላይ የሚሰኩት ጥላቻ የተላበሱ ሰዎችም ገብተዋል:: የኖኅ መርከብ ያልያዘችው እንስሳ እንደሌለ ቤተ ክርስቲያንም ያልተሸከመችው ዓይነት ሰው የለም::
ወደ ጥያቄው ስመለስ በእኔ ግምት ወደ መርከቡ በጣም ዘግይታ የገባችው ኤሊ ነበረች:: በላይዋ ድንጋይ የተጫናት እጅግ ቀርፋፋዋ ኤሊን የማይቀድም እንስሳ መቼም አይኖርም:: ምንም ብትዘገይም ኖኅ እስከመጨረሻው ጠብቆ አስገብቶ ለዘር አትርፎአታል:: የኤሊ ዘሮችም "ኖኅ ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ዳይኖሰር በጠፋን ነበር" ብለው ኖኅን ማመስገናቸው አይቀርም:: እግዚአብሔር ምንም ብትዘገይ ኤሊ ሳትገባ መርከቡን አልዘጋውም::
የኤሊ በመርከቡ መትረፍ በቤተ ክርስቲያን ልንተርፍ ተስፋ ለምናደርግ ለእኛ ትልቅ መጽናኛችን ነው::
ወዳጄ ወደ ቤተ ክርስቲያን ለመምጣት እንደ ወፍ ትበርራለህ? እንደ ሚዳቋ ትዘልላለህ? ወይንስ እንደ ኤሊ ትጎተታለህ? እግሮችህ ለመንፈሳዊ ነገር ሲሆን አቅም እያጡ አልተቸገርህም?
ልብህ ቢፈልግም እንደ ኤሊዋ የተጫነህ የኃጢአት ድንጋይ አላንቀሳቅስ ብሎህ አልዘገየህም?
እንዲህ ከሆነ አትጨነቅ መርከብዋ ቤተ ክርስቲያን አንተን ሳትይዝ ጥላህ ወዴትም አትሔድም:: ጉዞህን እስካላቆምህ ድረስ ትጠብቅሃለች:: እየተጎተትህም እየተሳብህም ቢሆን አንተ ብቻ ወደ ደጁ ገስግስ::
አንተ ብቻ መንገድ ጀምር እንጂ ፈጣሪ በሩን የሚዘጋው አንተ እስክትገባ ጠብቆ ነው::
ከቅዱስ ኤፍሬም ጋር እንዲህ ብለህ ለምነው :-
"ብበድልህም እንኳን አሁንም በርህን እያንኳኳሁ ነው:: እየተጎተትሁም ቢሆን አሁንም የምጉዋዘው ወደ አንተ ለመምጣት ነው"
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ሚያዝያ 5 2013 ዓ ም
ለተጨነቀች ነፍስ ዕረፍት የሆነው የእግዚአብሔር ቃል ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ :: እኔም ለእናንተ ከሰበክሁ በኁዋላ የተጣልሁ እንዳልሆን ስለ እኔ ጸልዩ!
ሌሎች እንዲያነቡትም የሚከተሉት አድራሻዎች Like, Subscribe እና Share ያድርጉ :-
የፌስቡክ ገጽ :- https://www.facebook.com/officialHenokhaile/
ጴጥሮስ ሆይ ከሰው ሁሉ ለገጽህ ግርማ ሰጥቶህ ነበር፤ ብርሃናቸው የማይጠፋ ዓይኖችን የሰጠህ ሲሆን ስለጌታህ አንዲት ጥፊ ትቀበል ዘንድ ዛሬ አልታገሥክም።
ጴጥሮስ ሆይ የመንግሥት ሰማያትን መክፈቻ የሰጠህን ልጄን በካድከው ጊዜ አልፈራህም፤ በሊቀ ካህናቱም ግቢ አልታገሥክም፤ በእርሱ ፈንታም ለዓለሙ ሁሉ የታመነ ጠባቂ አድርጎ ሾመህ።
ጴጥሮስ ሆይ ስለ ጌታህ አንድ ጊዜ እንኳ ጥቂት መከራ አልተቀበልክም።
ጴጥሮስ ሆይ ለዓለሙ ሁሉ አባት ትሆን ዘንድ ሾመህ፤ አንተ ግን ለልጄ የወንድማማችነት ፍቅርን አላደረግህም።
ጴጥሮስ ሆይ አምላካዊ እጁን በራስህ ላይ ጫነ፤ አንተ ግን ከመካድህ በፊት ዛሬ በራስህ ላይ የእሾህ አክሊል ይጭኑብህ ዘንድ አልፈቀድክም።
ጴጥሮስ ሆይ ልጄ ለአንተ ወዳጅህ እንጅ እንደ ጌታህ እንዳልሆነ አስብ። ልጄን እንደዚህ ትክደው ዘንድ ለአንተ አግባብ ኣይደለም።
ጴጥሮስ ሆይ ከእኛ ጋራ ይህ ሁሉ ድካም እንዳገኘው እንደ አባቴ ዮሴፍ ብትሆን ኖሮ። ጴጥሮስ ሆይ እንደ እርሱ ወደ ኄሮድስ ቢጎትቱህ በግብጽ ምድርም ከእኛ ጋራ መከራ ተቀባይ ብትሆን እንደ እርሱ መታገሥ ባልቻልክም ነበር እንጃ።
አባቴ ጸድቁ ዮሴፍ ሆይ በአጥንቶችህ ላይ የሰማይ ጠል ይውረድ። ነፍስህም ዕፀ ሕይወትን ትመገብ፤ ከእኛ ጋራ ታግሠህ መከራ፡ ስትቀበል እንደ ጴጥሮስ ልጄን አልካድከውምና።
ጴጥሮስ ሆይ ወደ ፍርድ አደባባይ አልወሰዱህ በባለ ሥልጣኖችም ፊት አላቆሙህ ፈጥነህ ጌታህን ካድከው።
ድንግል በዮሐንስ ቤት እንደዚህ ስታለቅስ ሳለ ዮሐንስ እያለቀሰ መጣ እርሷንም እያለቀሰች አገኛት። ድንግል እመቤታችንና ዮሐንስም ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እርስ በርሳቸው እየተላቀሱ ሁለቱም አብረው ነበሩ።
ዮሐንስም ድንግልን እናቴ ሆይ ጌታችንን ጴጥሮስ ስለካደው አታልቅሺ አላት፣ አሳልፎ እንደ ሰጠው እንደ ይሁዳ ነውር የለበትምና። በእራት ጊዜ ጴጥሮስ ሆይ ሦስት ጊዜ ትክደኛለህ ሲለው መምህሬን ሰምቻለሁና።
ጴጥሮስም እንደዚህ በአንተ ላይ ይደረግ ዘንድ አይገባም፤ ጌታዬ ፈጣሪዬም እስከ ዘላለሙ ድረስ እልክድህም መሞት ይሻለኛል፤ እንደዚህም በእኔ ላይ አይሆንም፤ ስለ አንተ ነፍሴን አሳልፌ እሰጣለሁ እንጂ። ከዚህ ቀደምም መምህራችን ጌታ መምህሬ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ሲገሥፀው ሰምቻለሁ። ሰይጣን ባለጋራዬ ወግድ ከኋላዬ ዕንቅፋት ሁነህብኛልና ሰው ሰውኛውን እንጂ የእግዚአብሔርን አታስብምና አለው።
አሁንም እመቤቴ እናቴ ሆይ ስለ አባቴ ጴጥሮስ መካድ አታልቅሽ ለኃጢአተኞች ሁሉ ለንስሐ ምሳሌ ነውና። በቃሉ ያመነውን የጌታችንን ቃል አስተባብሎ ነበርና።
በሐዘኗ የሚገኝ በረከት ከዐይንዋ የፈሰሰ የዕንባ ውኃ ጸጋ ለዘላለሙ ከእኛ ጋራ ይኑር አሜን።
(#ግብረ_ሕማማት_ዘዓርብ_ሦስት_ሰዓት)
#የማርያም_ሐዘን
(#ዓርብ_በሦስት_ስዓት_የሚነበብ አባ፡ ሕርያቆስ፡ የደረሰው፡ ድርሳን፡ ይህ፡ ነው።)
ወዳጆቼ ሆይ የአባቶች አለቃ የያዕቆብ ልቅሶ፤ ዛሬ ታደሰ አለ። በድንግልና ፀንሳ በድንግልና ለወለደችው ለተወዳጅ ልጅዋ ድንግል ማርያም ለምን አታለቅስም።
መከራ ስለተቀበለችበት ድንግል ማርያም ለምን አታለቅስም። የድንግልና ጡቷን ለእጠባችው ድንግል ማርያም ለምን አታለቅስ። በቤተልሔም በበረት ስለወለደችው ልጅዋ ድንግል ማርያም ለምን አታለቅስ።
በማኅፀንዋ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ለተሸከመችው ተወዳጅ ልጅዋ ድንግል ማርያም ለምን አታለቅስ። ከቶ ወልዳ ላልሳመቻቸው ልጆች ራሔል የምታለቅስ ከሆነ፤ እንደ ሰው ሁሉ በብብቷ ለተሸከመችው ልጇ ድንግል ማርያም ለምን አታለቅስ።
ከቦታ ወደቦታ ይዛ ላልተሰደደችባቸው ልጆች ራሔል የምታለቅስ ከሆነ። ከሀገር ወደ ሀገር አዝላ ለተሰደደችበት ልጅዋ ድንግል ማርያም ለምን አታለቅስ።
ከቶ መቃብራቸውን ላላአየች ልጆች ራሔል የምታለቅስ ከሆነ። በአንድ ልጅዋ መቃብር ደጃፍ ላይ ድንግል ማርያም ለምን አታለቅስ።
የባለ መልካም ጽሕም ሽማግሌ የያዕቆብ ልቅሶ በብላቴናይቱ ድንግል ዘንድ ዛሬ ታደሰ። ወንድሞቹ ባሰሩት ጊዜ ያዕቆብ ወደ ዮሴፍ አልተመለከተም። ድንግል ግን ልጅዋን በዕንጨት መስቀል ላይ ተቸንክሮ አየችው።
ዮሴፍ በሰፊ ጉድጓድ ውስጥ ሳለ ያዕቆብ በላዩ፡ ያለቅስ ዘንድ ወደ ዮሴፍ አላየም። ድንግል ግን በአይሁድ ጉባዔ መካከል ተሰቅሎ ልጅዋን አየችው።
ዮሴፍን ወንድሞቹ ልብሱን ገፈው ሲያራቁቱት ያዕቆብ አላየም። ድንግል ግን በጎ ምክር በሌላት በአይሁድ መካከል ልብሱን ተገፎ ራቁቱን ሁኖ አየችው።
ወንድሞቹ ዮሴፍን በሃያ ብር ሲሸጡት ያዕቆብ አላየም። ድንግል ግን ይሁዳ ልጅዋን በሠላሳ ብር ሲሸጠው አየች።
አራዊት ባልቀደዱት ልብስና በሌላ ደም ላይ ያዕቆብ አለቀሰ። አምላካዊ ደም ግን ድንግል ማርያም ስለእርሱ በላዩ የምታለቅስበት በቀራንዮ አለት ላይ የፈሰሰው ነው። ድንግል ግን ዛሬ ያየችው ልጅዋን ያለበሱትን ሌላ ልብስ ነበረ፤ የራሱን ልብስ ግን እርስ በርሳቸው ተካፈሉት።
የዮሴፍ ወንድሞች ወንድማቸው ዮሴፍን በሸጡት ጊዜ አለቀሱ ተጸጸቱ። የእስራኤል ልጆች ግን ጌታቸውን በሸጡት ጊዜ አላለቀሱም፤ አልተጸጸቱም።
የያዕቆብ ልጆች ወንድማቸው በነገሠ ጊዜ ተደሰቱ። አይሁድ ግን ጌታቸው ከሙታን ተለይቶ በተነሣ ጊዜ ደስ አላላቸውም።
ድንግል ሆይ፤ በእውነት በልጅሽ መቃብር ላይ ልቅሶሽ ጣዕም ያለው አሳዛኝ ነበረ ማርያም ሆይ ለምን ተቀምጠሻል? ምን ታደርጊያለሽ? ብለው የልጅሽን መሰቀሉን በነገሩሽ ጊዜ በመላእክት መካከልም ቃልሽ ያማረ ነበር።
እነሆ ልጅሽን በመኰንኑ ፊት አቁመውታል፤ የአይሁድ ሊቃነ ካህናትም ያሰቃዩታል፣ ያቃልሉታል፣ ማርያም ሆይ ምን ታደርጊያለሽ? እነሆ ልጅሽን በፍርድ አደባባይ መካከል ልብሱን ገፈው እያራቆቱት ነው።
የኢያቄም ልጅ ማርያም ሆይ ለምን ተቀምጠሻል? ምንስ ታደርጊያለሽ? እነሆ በኢየሩሳሌም ሜዳ የሚሰቀልበትን ግንድ ብቻውን ተሸክሞአል፤ አንድ እንኳ ወደ እርሱ የሚቀርብ የለም።
የሐና ርግብ ሆይ ለምን ተቀመጥሽ? የምትሰሪውስ ምንድን ነው? እነሆ ልጅሽን ሰቅለውት በቀራንዮ ቦታ ቁሞአል።
የዳዊት ዘር ሆይ ልጅሽን በመስቀል ላይ ለምን ከፍ ከፍ አደረጉት? እመቤት ድንግል ሆይ በዮሐንስ ቤት ዛሬ ልቅሶሽ በእውነት ጣዕም ያለው ነበረ እንዲህ ስትዪ።
ወዮ ለዚህ መራራ ወሬ ነጋሪ ለኢዮብና እስራኤል ለተባለ ያዕቆብ ከአረዷቸው መርዶ የመረረ ነው።
ዛሬ ወደእኔ ለሚመጣ ለዚህ ለክፉ ወሬ ወዮ። ልጄ ሆይ አገሩን በኢቃጠሉ ጊዜ ለሎጥ ከአረዱት መርዶ ያስጨንቃል።
በእኔ ላይ ለደረሰው ለዚህ አስጨናቂ ስብከት ወዮ። ልጄ ሆይ ስለ ኃያላነ እስራኤል ሞት ከአረዱአቸው መርዶ ይበልጣል።
በዚህ በክፉ ወሬ ወደእኔ ለመጣው ለዚህ ወሬ ነጋሪ ወዮ። ልጄ ሆይ እነሆ ስታረጋጋኝ ሠላሳ ዓመት ይሆናል፤ ልገሥጽህም አልተቻለኝም። ዛሬ ወደ እኔ ወሬህ እስከመጣ ድረስ ወጥተህ እስከምትገባ አንዲት ሰዓት እንኳ አላመንኩህም።
ልጄ ሆይ ለሐዘኔ ሁሉ ጥንቱ ሰሎሜ ናት፤ እኔ ዳኛውን አየው ዘንድ ከቤቴ አልወጣም፤ በፈራጁም ፊት አልቆምም። ሌባውን ራሱን ሲቆርጡት ሽፍታውንም ይገድሉት ዘንድ ሲፈርዱበት አላየሁም። ከቶ ቀራንዮን አላየሁትም፤ የጎልጎታንም ቦታ አላውቅም፤ ሁል ጊዜም በሚጣሉበት ቦታ አልቆምኩም።
ልጄ ሆይ ክፉ የሆነ ፍርድ አላየሁም፤ በፍርድ አደባባይም ከቶ ለዘላለሙ አልቆምኩም።
ልጄ ሆይ ያደረኩብህን ግፍ አላውቅም እኔም በዮሐንስ ቤት ነበርኩ።
ልጄ ወዳጄ ሆይ በሊቀ ካህናቱ በሐና ግቢ የተቀበልከው ግፍ ወሬው መራራ ነው።
ልጄ ወዳጄ ሆይ ዛሬ ከእኔ ላይ ነጻነቴን አስወገድክ፤ ስለልደትህ በናዝሬት መልካም የምስራች ነገሩኝ። ዛሬ ግን በኢየሩሳሌም ይህችን ክፉ መርዶ አረዱኝ። በዮሴፍ ቤት መልካም ዜና በዮሐንስ ቤት ግን የሞት ዜና መጣልኝ ።
ልጄ ወዳጄ ሆይ እኔ በልቤ ደስ እያለኝ ተቀምጨ ነበር። በየዕለቱ ፋሲካ ደርሶአል በዓሉን እናከብር ዘንድ ወደሀገራችንም እንመለሳለን እያልኩ ነበር፤ የዚህ ዓይነት ፋሲካም ደረሰኝ።
ልጄ ወዳጄ ሆይ በእንባና በሐዘን በዓሌ ወደ ልቅሶ ተመለሰ፤ ፋሲካየም ወደልብ ሐዘን።
በዮሐንስ ቤት ሳለች ስለ ልጅዋ የመከራ ወሬ በመጣበት ጊዜ ድንግል እመቤታችን ይኸንን ልቅሶ ታለቅስ ነበር።
ከእርስዋ ጋራ ይሔድ ዘንድ ከንጹሐን ሐዋርያት አንድ ፈለገች አላገኘችም፤ አይሁድን ከመፍራት የተነሳ ሁሉም ትተውት ሸሽተዋልና።
ከእርስዋ ጋራ ይሔድ ዘንድ ስለ ጴጥሮስ መረመረች፤ እርሱማ የካህናት አለቆችን ከመፍራቱ የተነሳ ልጅሽን ከቶ አላውቀውም አለ፤ ሒዶም ተሸሽጓል አልዋት።
ዳግመኛም ስለ ጌታችን ወንድም ስለ ያዕቆብ መረመረች፤ ለያዙት ሰዎች በተራራ ላይ ልብሱን ትቶ እንደ ሸሸ ነገርዋት።
እንድርያስንም ፈለገችው፤ እርሱስ ወደ ከተማ አብሮት አልመጣም አልዋት፤ እንደዚሁ ቶማስም ሽሽቶ ሔደ።
ስለ በርተሎሜዎስም ጠየቀች፤ እርሱም ከወንድሞቹ አስቀድሞ እንደሸሸ ነገርዋት።
ስለ ፊልጶስም ጠየቀች፤ እርሱም የፋናዎችን ውጋገንና መብራቶችን ባየ ጊዜ ፈርቶ እንደሸሸ ነገርዋት።
ስለ ዮሐንስ ወንድም ስለ ያዕቆብ መረመረች፤ አንድ ጊዜ ስንኳ እንዳልቆመ ነገርዋት።
ስለ ማቴዎስም መረመረች፤ እርሱም ግብር ስለሚቀበላቸው አይሁድንና የካህናት አለቆችን እጅግ ስለፈራ እነርሱም ስለሚጠሉት በሌሊት ጨለማ እንደሸሸ ነገርዋት።
ስለ ሁሉም መረመረች፤ አብሮ ወደ ቀራንዮና ወደጎልጎታ ከሔደው ዮሐንስ በቀር አንድም አላገኘችም።
ድንግልም ከልጅዋ ደቀ መዛሙርቶች ከዮሐንስ በቀር አንድ እንኳ ባለማግኘቷ እንደገና ዳግም ወደ ጽኑ ልቅሶና ሐዘን ተመለሰች።
እንዲህ እያለችም አለቀሰች፦
ልጄ ወዳጄ ሆይ ወዮልኝ ወንድሞችህ ሸሹ ትተውህም ተሸሸጉ።
አባቴ ጴጥሮስ ሆይ ጌታህን እንዳትክድ ሁልቀን እጠራጠርህ ነበር፤ ስለ እርሱ ወርቅ ብር አልሰጠህ ለምን ጌታህን ፈጥነህ ካድከው? ስለርሱ መርከብ ወይም ቀዛፊ አልሰጠህም፤ መምህርህንና ጌታህን ዛሬ ለምን ካድከው? ስለርሱ ምንም አልሰጠህም ወንድ ልጅም ቢሆን ወይም ሴት ልጅ። ጴጥሮስ ሆይ ስለ እርሱ ወንድምን ወይም ወዳጅን አልሰጠህም። ልጄን ለምን ካድከው? በዚህ ሁሉ ልብህ ለምን ቀላል ሆነ?
ጴጥሮስ ሆይ እስከ ፈራህና ፈጥነህ እስከ ካድክ ድረስ ለእኔ ነው ትል ዘንድ በድጋሚ ሌላ መስቀል አላየህ፣ እንደ ብረትም የተሳለ አንደበት ሰጥቶህ ነበር። ጴጥሮስ ሆይ አንተስ ያለ እሳትና ያለእንጥረኛም ፈጽመህ አቀለጥከው።
#የሰሙነ_ሕማማት_ማክሰኞ
#የጥያቄ_ቀን_ይባላል፦
ሰኞ ባደረገው አንጽሖተ ቤተመቅደስ ምክንያት፣ ሹመትን ወይም ሥልጣንን ለሰው ልጅ የሰጠ ጌታችን፣ ስለ ሥልጣኑ በጸሐፍት ፈሪሳውያን ተጠይቋልና፤ የጥያቄ ቀን ይባላል፡፡
ጥያቄውም ከምድራውያን ነገሥታት፣ ከሌዋውያን ካህናት ያይደለህ ትምህርት ማስተማር፣ ተዓምራት ማድረግ፣ ገበያ መፍታትን፣ በማን ሥልጣን ታደርጋለህ? ይህንንስ ሥልጣን ማን ሰጠህ? የሚል ነበር፡፡ /ማቴ. 21፥23-27፣ ማር. 11፥ 7-35፣ ሉቃ.21፥23-27፣ ማር.11፥27-33፣ ሉቃ. 20፥1-8/፤ እርሱም ሲመልስ፤ «እኔም አንድ ነገር እጠይቃችኋለሁ፣ እናንተም ብትነግሩኝ በማን ሥልጣን እነዚህን እዳደርግ እነግራችኋለሁ፡፡ የዮሐንስ ጥምቀት ከወዴት ነበረ፣ ከሰማይ ነውን? ወይስ ከሰዉ? በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ ወይስ በሰው ፈቃድ?» አላቸው፡፡ እነርሱም ከሰማይ ብንል ለምን አልተቀበላችሁትም ይለናል፤ ከሰው ብንል ሕዝቡ ሁሉ ዮሐንስን እንደ አባት ያከብሩታል፣ እንደ መምህርነቱ ይፈሩታልና ሕዝቡን እንፈራለን፤ ተባብለው ከወዴት እንደሆነ አናውቅም ብለው መለሱለት፡፡ እርሱም እኔም በማን ሥልጣን እነዚህን እንደማደርግ አልነግራችሁም አላቸው» ይህንንም መጠየቃቸው እርሱ የሚያደርጋቸውን ሁሉ በራሱ ሥልጣን እንዲያደርግ አጥተዉት አልነበረም፣ ልቡናቸው በክፋትና በጥርጥር ስለተሞላ እንጂ፡፡
#የትምህርት_ቀንም_ይባላል፡-
በማቴ. 21፥28፣ ማቴ. 25፥46፣ ማር.12፥2፣ ማር.13፥37፣ ሉቃ. 20፥9፣ ሉቃ. 21፥38 የሚገኙት ትምህርቶች ሁሉም የማክሰኞ ትምህርት ይባላሉ፡፡ በዚህ ዕለት በቤተ መቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረ፣ የትምህርት ቀን ይባላል፡፡ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ከሥጋዊ ነገር ርቆ በዚህ ሰሞን የሃይማኖት ትምህርት ሲማር ሲጠይቅ መሰንበቱም መጽሐፋዊ ሥርዓት ነው፡፡
"እንበለ ደዌ ወሕማም እንበለ ጻማ ወድካም
አመ ከመ ዮም ያብጽሐነ ያብጽሕክሙ
እግዚአብሔር ለብርሃነ ትንሣኤሁ በፍስሓ ወበሰላም!"
#የሰሙነ_ሕማማት_ሰኞ
#መርገመ_በለስ የተፈጸመበት ዕለት ነው
ጌታችንና አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሆሣዕና ዕለት ቢታንያ አድሮ በማግሥቱም ከቢታኒያ ሲመጡ ተራበ፡፡ (ማር.11፤11-12) ቅጠል ያላት በለስ ከሩቅ አይቶ ወደ በለሲቱ ቀረበ፤ ነገር ግን ከቅጠል በቀር አንዳች ፍሬ አላገኘባትም፡፡ ከአሁን ጀምሮ ማንም ከአንቺ ፍሬ አይብላ ብሎ ረገማት። በለስ የተባለች ቤተ እስራኤል ናት፤ ፍሬ የተባለች ሃይማኖትና ምግባር ናት፤ ከእስራኤል ፍቅርን፤ ሃይማኖትን፤ ምግባርን ፈለገ አላገኘም፤ እስራኤል (ሕዝበ እግዚአብሔር) መባልን እንጂ፤ ደግ ሰው አይገኝብሽ ብሎ ረገማት፤ በመርገሙ ምክንያት እርሱ ከለያቸው በስተቀር ደግ ሰው ጠፋባት፡፡
በለስ ኦሪት ናት፤ ኦሪትን በዚህ ዓለም ሰፍና ቢያገኛት ኦሪትና ነቢያትን ልሽር አልመጣሁም ልፈጽም እንጂ በማለት ፈጸማት፤ ሕገ ኦሪትን ከመፈጸም በቀር በእርሷ ድኅነት አላደረገባትምና፤ ፍሬ በአንቺ አይሁን አላት፤ ደኅነት በአንቺ አይደረግብሽ ብሏታልና እንደመድረቅ ፈጥና አለፈች፡፡
በለስ ኃጢአት ናት፤ የበለስ ቅጠል ሰፊ እንደሆነች ሁሉ ኃጢአት በዚህ ዓለም ሰፍታ ሰፍና አገኛት፡፡ በለስ ሲበሉት ይጣፍጣል፤ ቆይቶ ግን ይመራል፤ ኃጢአትም ሲሰሩት ደስ ደስ ያሰኛል፤ ኋላ ግን ያሳዝናል፤ ወደ እርሷም ሄዶ ማለትም ከኃጥአን ጋር ዋለ፤ ኃጥእ ከመባል በቀር በአንደበቱ ሐሰት፤ በሰውነቱ ክፋት እንዳልተገኘበት ለማመልከት ፍሬ አላገኘባትም አለ፤ በአንቺ ፍሬ አይገኝ የሚለውም፤ በኃጢአት ፍዳ ተይዞ የሚቀር አይኑር ለማለት ነው፤ ስትረገም ፈጥና መድረቋም፣ በአዳም ምክንያት ያገኘችን ዕዳ በደል በእርሱ ካሣነት እንደጠፋችልን ለመግለጽ ነው፡፡
#አንጽሆተ_ቤተ_መቅደስ የተፈጸመበት ዕለት ነው፦
ጌታችን በለስን ከረገማት በኋላ ወደ ቤተ መቅደስ ሄደ፤ ቤተ መቅደስ፣ ቤተ ጸሎት፣ ቤተ መሥዋዕት መሆኑ ቀርቶ ቤተ ምስያጥ (የንግድ ቤት) ሆኖ ቢያገኘው ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች፤ እናንተ ግን የወንበዶች ዋሻ አደረጋችኋት ብሎ የሚሸጡበትን ሁሉ ገለበጠባቸው፤ ገርፎም አስወጣቸው፤ ይህም የሚያሳየው ማደሪያው ቤቱ የነበርን የአዳም ልጆች ኃጢአት ሰፍኖብን ስንኖር ቢያገኘን ኃጢአታችንን ሁሉ እንዳራቀልን የሚገልጽ ነው፡፡
በዚህ በሰሙነ ሕማማት ካህናትና ምእመናን በቤተክርስቲያን ተገኝተው ወዛቸው ጠብ እስኪል ድረስ በነግህ፤ በሠለስተ፣ በስድስቱ ሰዓት፤ በተሰዓቱ ሰዓትና በሠርክ መላልሰው ሲሰግዱና ሲጸልዩ ይሰነብታሉ፤ በተለይም ካህናት በማንኛውም አገልግሎት ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ፤ ምክንያቱም የደረሰብን መከራ ኀዘኑን እና 5ሺ ከ5መቶ ዘመን የሰው ልጅ በጨለማ ይኖር እንደነበረ ለማዘከር ነው፡፡
Repost from Tariku Abera
† ኢየሱስ በመጽሐፈ ሕማማት /ዘምሮ ዘእግዚእነ/ †
• ጌታ ኢየሱስ ሆይ ስምህ ዋጋው እጅግ የከበርና ነጋዴ ያለውን ሁሉ ሽጦ የገዛው ዕንቁን ይመስላል ይህ የከበረ ዕንቁ ስምህ በልባችን ውስጥ ያበራ ዘንድ ተወው።
• ጌታ ኢየሱስ ሆይ ስምህ የነፍሳችን ጌጥ የልባችንም ሐሴት ነው።
• በምሕረትህ ባለ ጸጋ የሆንህ ቸሩ ጌታ ኢየሱስ ሆይ ኪሩቤልና ሱራፌል ክንፎቻቸውን እያማቱ ያመሰግኑሃል።
• ጌታ ኢየሱስ ሆይ በፊትህ የሚቆሙ ሱራፌልና ኪሩቤል ያዪህ ዘንድ አይችሉም እኛ ግን ዘወትር በመሰዊያው ላይ ሆነህ እናይሃለን፤ቅዱስ ሥጋህንና ክቡር ደምህንም እንቀበላለን።
• የእግዚአብሔር እውነተኛ በግ ጌታ ኢየሱስ ሆይ በመንግስትህ ምሕረትህን አድርግልን።
• በ ዕፀ መስቀል ላይ የተሰቀልክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ጠላታችን ሰይጣንን ከእግራችን በታች ጣልልን።
• በከርሰ መቃብር 3 ቀንና 3 ሌሊት ያደርክ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ የሞትን መውጊያ እሾህ ስበርልን።
• ከሙታን የተነሳህ ወደ ሰማያትም ያረግህ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በኃይልህ አንሳን።
• በታላቅ ክብር ዳግም የምትመጣው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በአስፈሪዋ የፍርድህ ቀን ምሕረትህንና ይቅርታህን አድርግልን በራስህ ፈቃድ በአባትህ ፈቃድ መጥተህ አድነኽናልና።
• በሚጣፍጥ ቃል ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ብለን ስንጠራህ ለነፍሳችን ምሕረትን አድርግልን።
• ስብሐት ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ይሁን፤ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን።
“ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! መንፈሳዊ ምስጋና ሁሉ ለአንተ ይገባል፡፡ ዋጋው የማይታወቅ ነጋዴ ገንዘቡን ሁሉ ሰጥቶ የተወዳጀው እውነተኛ ዕንቁ ደንጊያ አንተ ነህ፡፡ ይህንን የዕንቁ ደንጊያ በሰውነታችን ውስጥ ያበራ ዘንድ ደግሞ ዛሬ ለእኛ አድርግልን፡፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የተቀደሰው ስምህ የልባችን ደስታ የሰውነታችን ሽልማት ጌጥ ነው፡፡
አቤቱ ምድርንና ዓለሙን ሁሉ ዞርሁ ያለ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በቀር ጣፋጭ ስምን አላገኘሁም፡፡ በምድር ላይ የሚደረግ ረድኤትና ኃይል ሁሉ ያለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በቀር አይሆንም፡፡ እግዚአብሔርን ያገለገሉ የሰው ወገኖች ሁሉ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኵል ነው፡፡ የከበረና የተመረጠውን እጅ መንሻ ሁሉ ያለ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም አልተቀበልንም፡፡ ሰማይና ምድር ያለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከሁከት አልጸኑም፡፡
የጌታዬ የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከማር ከወለላና ከሦከር ይጥማል፡፡ ማርና ሦከር በሚበሉበት ጊዜ ይጠገባሉ፤ የጌታዬ የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ግን አይጠገብም፡፡ የጌታዬ የኢየሱስ ክርስቶስ ስም በምጠራ ጊዜ ከንፈሮቼ ማርን ያንጠባጥባሉ፡፡ ማር፣ ስኳርና እንጀራ ቢሆኑም እንደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በእኔ ዘንድ ጣዕም የላቸውም፡፡ የጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ይሻለኛልና ከሰማይ በታች ካለ ፍጥረት ሁሉም ይበልጣልና፡፡
ቸርነትህ ብዙ ነው፤ አይነገርምም፡፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! በሚያምንብህና በሚወድህ አፍ ሁሉ ስምህ የታወቀ ነው፡፡ በሕግ ከታወቁ ምስጋናዎች ሁሉ ከውስጣቸው የሚመስልህ የለም፡፡ የዓይኖቼ ብርሃንና የሥጋዬ ብርታት ከከበረው ስምህ ወገን ነው፡፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! እስከ ሕይወቴ መጨረሻ የከበረ ስምህን በአንደበቴ ዘወትር የተሾመ አድርገው፡፡ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስቲያን ሰውነት ሁሉ የጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም በአንድነት ያከብራሉ፤ ያመሰግናሉ፡፡
ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ከኃጢአት ወገን የሚሆን የክፋት መንፈስን ሁሉ ከእኔ አስወግድ፡፡ መዳኛችን በሚሆን በዚህ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ክርስቲያኖች ሁላችሁም ፈጽሞ ደስ ይበላችሁ፡፡
የጌታዬ የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ጣፋጭ ነው፤ በገነት ካለ ፍሬም ይልቅ ይጣፍጣል፡፡ አባታችን ዳዊት በአመሰገነበት በከበረ መዝሙር የጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን ስም ፈጽሞ እናመሰግናለን፤ እናከብራለን፡፡
ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! ብዙ የሆነ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ በእኔ ላይ አሳድር፡፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! አንተን ደስ የማያሰኝህን ሓሳብ ሁሉ ከእኔ ታርቅ ዘንድ ወዳንተ እለምናለሁ፤ ከአንተም እሻለሁ፡፡ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! በጌትነትህ ከእኔ ጋር ቸርነትህን አድርግ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ እንሰግድልሃለን! ፈጣሪያችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ እንሰግድልሃለን! መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ ሰማያዊ ከሚሆን ከቸር አባትህ ጋራ ማኅየዊ ከሚሆን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እንሰግድልሃለን፡፡ አሜን!”
(ምንጭ፡ ግብረ ሕማማት)
እባካችሁ ሼርና ታግ በማድረግ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ለክርስቶስ ያላትን ፍቅርና እውነት ለሌሎች እናስተምር።
ለበረከት ሁኑ።
መ/ር ታሪኩ አበራ
አደገኛው መጽሐፍ
==+++==
በሙስሊሙ ማኅበረሰብ እንደ ቁርዓን የሚነበብ፣ ለእኛ መሪዎች መረጃውን ብናደርሳቸውም ከቁብ ያልቆጠሩት አንድ መጽሐፍ አለ። የመጽሐፉም ስም "አያት ዳይሬክቶሬት" ይባላል።
ይህ መጽሐፍ በገበያ የማይሸጥ ነገር ግን ለሙስሊሙ ማኅበረሰብ በውስጥ የሚታደል መጽሐፍ ነው። መጽሐፉ ከታተመ ጥቂት ዓመታት ተቆጥረዋል። ይዘቱ የሙስሉሙን ኢኮኖሚ ለማነቃቃት (የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በሙስሊሙ እጅ ለማድረግ) ታስቦ የተጻፈ ነው። በውስጡም የኢኮኖሚውን ዓለም ከክርስትናው ነጥቆ እንዴት ወደ ሙስሊሙ ማኅበረሰብ መውሰድ እንደሚቻል ያትታል።
ከመጽሐፉ ይዘቶች አንዱ ስለ ምርት ግዥ የሚያትት ሲሆን "ከሙስሊም ግዛ ለሁሉም ሽጥ" የሚል መርህ አለው። በዚህ መርህ ሥር በየትኛውም የሀገሪቱ ክፍሎት የሚገኙ ሙስሊሞች የሚፈልጉትን እቃ ከሙስሊሞች ብቻ እንዲገዙ፣ ነገዴዎች ግን ለሁሉም እንዲሸጡ የሚተነትን ነው። ይህም ሙስሊሙን ነጋዴ የሚያበረታታ፣ ክርስቲያኑን ነጋዴ የሚያከስር፣ ክርስቲያኑ ማኅበረሰብ ገዥ ብቻ እንዲሆን ያለመ ስልታዊ የገበያ ሴራ ነው። (ክፍለ ሀገር ያለ አንድ ሙስሊም ነጋዴ እቃ ለማምጣት አዲስ አበባ ሲሄድ ከማን መግዛት እንዳለበት የተሠራለት የገበያ መዋቅር እንዳለም አንድ ሙስሊም ወዳጄ እንዳጫወተኝ አስታውሳለሁ።)
የዛሬ ሁለት ዓመት ይህንን ጉዳይ ለሚመለከተው የቤተ ክርስቲያን አካል ብናቀርብም የጠበቀን ስለላ እና እንዳንወጣ እንዳንገባ እንግልት ነበር። ጥቆማችን ለምን ሙስሊሞቹ እንዲህ ያደርጋሉ የሚል ሳይሆን በሴራ ኢኮኖሚ ለሚሰቃየው ሕዝበ ክርስቲያን ክርስቲያናዊ መፍትሔ እንዲበጅለት የሚያሳስብ ነበር።
የሆነው ሆኖ አሁን ላይ ያለው የቤተ ክርስቲያን ጥቃት ዛሬ የጀመረ ሳይሆን ከምጽአተ ብልጽግና በፊት ታስቦበት የቆየ፣ ምኞት ተሳክቶ ዘመነ ብልጽግና እውን ሲሆን ወደ ተግባር የተገባበት ነው። የተፈጠረብን ጦርነት በሴራ ፖለቲከኞች፣ በቤተ እምነቶችና በአክራሪ ሃይማኖተኞች ጥምር እንቅስቃሴ ነው። በአርምሞ እና በፍርሃት ተሸብበን ትኩረት ያልሰጠነውን ይህንን ዘርፈ ብዙ ጥቃት በየአጥቢያችን ተደራጅተን መመከት ካልቻልን ነገ ታሪክ እንሆናለን።
ራሳችሁን ለመጠበቅ ከማንም አትጠብቁ። በዚህ ሰአት እውነተኛውን መሪ ከሐሰተኛው መሪ መለየት የተሳነበት አስቸጋሪ ዘመን ነው። (ትናንት ባርከኒ ያልነው ጳጳስ ዛሬ ፀረ ቤተ ክርስቲያን ሆኖ እየወጋን ነውና)። ነገ ከዚህ የባሰ ልብ ሰባሪ ክስተት በቤታችን ልናይ እንችላለን። መፍትሔው ግን መደንገጥና ተስፋ መቁረጥ ሳይሆን በየአካባቢያችን ተደራጅተን መታገል ነው።
ሌሎች ጥቆማዎች ይኖሩናል። ወደ ቻናላችን ተቀላቀሉ ጓደኞቻችሁን አስገቡ።
https://t.me/onesinod
+ የመጽሐፍ ዮሴፍ +
ዮሴፍ ግብፅ ወርዶ ፣ የግብፅን ንጉሥ የፈርኦንን ሕልም ፈትቶ ፣ ሀገረ ገዢ ሆኖ ነበር፡፡ ግብፅን ከረሃብ ከማዳንም አልፎ የዓለም የእህል ጎተራ እንድትሆን አድርጓት ነበረ፡፡ ይህንን የዮሴፍን ውለታ ያልዘነጋው የግብፅ ንጉሥ ፈርኦን ለዮሴፍና በቁጥር ሰባ ለነበሩት የዮሴፍ ዘመዶች የክብር ማረፊያ ሠጥቶ እንደ ሀገራቸው ተስፋፍተው እየተዋለዱ በግብፅ እንዲኖሩ አደረጋቸው፡፡ በፈርኦን ላይ ፈርኦን ፣ በትውልድ ላይ ትውልድ ሲተካ ግን ድንገት ‘ዮሴፍን የማያውቅ ፈርኦን ተነሣ’ (ዘጸ. 1፡8)
ከዚያ በኋላ የሆነውን ምኑን ልንገራችሁ? ፳ኤል ልጆቻቸውን ከሲሚንቶ ጋር ለውሰው ፒራሚድ እስኪሠሩ ድረስ የወረደባቸው መከራ ምኑ ይነገራል? ለዚህ ሁሉ መከራ መነሻው ግን ‘ዮሴፍ ደግሞ ማን ነው?’ የሚል ትውልድ መምጣቱ ነው፡፡
‘ዮሴፍን የማያውቅ ፈርኦን ተነሣ’ የሚለውን የመጽሐፍ ቃል ያስጠቀሰኝ የመጽሐፍም ዮሴፍ አለ ለካ የሚያሰኝ የሰሞኑ አንድ ገጠመኝ ነው፡፡ ከዐሠርት ዓመታት በላይ ከገበያ ጠፍቶ የቆየውን ውድ መጽሐፍ ‘ወላዲተ አምላክ በነገረ ድኅነት’ እኮ ታተመ!’ የሚል ዜና የነገርናቸው ሰዎች ሁሉ ብዙም አለመደነቃቸውን ሳይ ለካ የመጽሐፍም ዮሴፍ አለ? ብዬ እንድተክዝና ይህንን የመጽሐፍ ዮሴፍ ለማስተዋወቅ ብእሬን እንዳነሣ ግድ ሆነብኝ፡፡
‘ወላዲተ አምላክ በነገረ ድኅነት’ የሚለውን [በወቅቱ በሚጠራበት ስም] የዲያቆን አንዱዓለም ዳግማዊ መጽሐፍ ውለታ እንዴት ልንገራችሁ? ይህ መጽሐፍ የአዲሱ ትውልድ የነገረ ማርያም ሥነ ጽሑፍ የተወለደበት እጅግ አንገብጋቢ (critical) ሥራ መሆኑን ለመግለጽ ቃላት ሊያጥረኝ ይችላል፡፡ ስለተጻፈበት ዘመን ሁኔታ ብቻ ላስታውስ፡፡
ያ ጊዜ መንፈሳዊ ኮሌጆች በእንግዳ ትምህርቶች ተጽእኖ ሙሉ በሙሉ የወደቁ በሚያስመስል ሁኔታ ላይ ነበርን፡፡ ‘ወደ መንፈሳዊ ኮሌጅ የገባ ሰው ጤነኛ ሆኖ አይወጣም’ የሚል ድምዳሜ ላይ እስኪደረስ ድረስ ብዙዎች ከመንፈሳዊ ኮሌጅ ነን እያሉ ከኦርቶዶክሳዊ መንገድ የወጣ ትምህርት ያስተምሩ ነበረ፡፡ በቅርቡ ያረፉት ባለቅኔው መጋቤ ምሥጢር ወልደ ሩፋኤል ፈታሒን የመሳሰሉ ሊቃውንት ሳይቀር ‘የሀገር ውስጥ ቦንኬ ማምረቻ’ ብለው መንፈሳዊ ኮሌጁን እስኪያማርሩ ድረስ የተደረሰበትና ቤተ ክርስቲያን በራስዋ በጀት ጠላት እንዴት ታፈራለች የሚባልበት ዘመን ነበረ፡፡ (ቦንኬ ልጆች ሳለን የብዙ ውዝግብ ምክንያት የነበረ ፈረንጅ ፓስተር ስም ነው) ያ ጊዜ የአብነት ትምህርት ከመንፈሳዊ ኮሌጅ ትምህርት ጋር እንደ እሳትና ጭድ ተደርጎ የሚቆጠርበት ፣ ቀሚስ ለባሹ ነጠላ ለባሹን በንቀት ፣ ነጠላ ለባሹ ቀሚስ ለባሹን በጥርጣሬ የሚያይበት ወቅት ነበር፡፡
በዚያን ወቅት ራሳቸው ዩኒቨርሲቲ መግቢያ ነጥብ ስላልመጣላቸው መንፈሳዊ ኮሌጅ የገቡና መመረቂያ ጽሑፋቸውን ሳይቀር በሰው የሚያሠሩ አንዳንድ ድኩማን ተማሪዎች ‘traditional’ በሚል በጉባኤ ቤት ያለፉ ሊቃውንትን የማሸማቀቂያ ቃል ነባሩን የቤተ ክርስቲያኒቱን ጥልቅ ነገረ ሃይማኖት ሳይረዱ የሚያናንቁ ወጣቶች የተነሡበት ጊዜ ነበር፡፡ ‘Salvation, redemption, Christology’ የሚሉ ቃላትን ከማዘውተራቸው ውጪ የጠለቀ theological እውቀት ሳይኖራቸው በትዕቢት የተወጠሩ ሰዎች የመንፈሳዊ ኮሌጅን ገጽታና ምንነት የሸፈኑበት ዘመን ነበረ፡፡
በተለይ ነገረ ማርያምን ከመንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪ አቅጣጫ መስማት እንደ ሶምሶን እንቆቅልሽ ‘ከበላተኛ መብል ወጣ ፣ ከሚያፈራውም ጥፍጥ ወጣ’ (እምአፈ በላዒ ወጽአ መብልዕ ፤ ወእምአፈ ግሩም ወጽአ ጥዑም)ን የሚያስጠቅስ ክስተት ነበር፡፡ የጉባኤ ቤት ትምህርትና ቴዎሎጂን ማዋሐድም ዘይትና ውኃን የማዋሐድ ያህል ከባድ እንደሆነ ተደምድሞ በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ሆነው ሁለት ዓይነት ጎራዎች እንዲፈጠሩ ምክንያት እየሆነ በመምጣቱ በወቅቱ ገና ልጆች ለነበርነው ግራ የሚያጋባና የቱን መስመር ልከተል የሚያሰኝ መንታ መንገድ ነበረ፡፡
በዚህን ወቅት ነው የዲያቆን አንዱ ዓለም ዳግማዊ ዓይነት ዘይትና ውኃን ያዋሐዱ ፣ ቴዎሎጂን ከአብነት ትምህርት ፣ እንግሊዝኛን ከግእዝ ፣ ፋዘር ጆሲን ከመምህር ደጉ ዓለም ፣ ነገረ ክርስቶስን ከነገረ ማርያም ፣ የሰባኪ ቀሚስን ከልብሰ ተክህኖ ያስታረቁ ልጆች ከዚያው ከቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ አብራክ ተወልደው ብቅ ብቅ ሲሉ አይተን ልባችን ማረፍ ጀመረ፡፡ የዲያቆን አንዱዓለም ዳግማዊ ዓይነቶቹ ከመንገድ ሲያልፉ ውዳሴ ማርያም ዜማ ሲደርስ በፍርሃት ቆመው ሰአሊለነ ቅድስት እስኪባል የሚጨርሱ ፣ በወጣትነታቸው የአንደበታቸው ላህይ የቀደምት መምህራን የሆነ ፣ ትሕትናቸው የሊቃውንት የሆነላቸውን ‘በማር ላይ ቅቤ’ የሆኑ ጥንቅቅ ያሉ ሰባኪያንን ቆመው ሲያገለግሉ ማየት በዚያን ወቅት ለብዙዎቻችን ተስፋና መነሻ ነበረ፡፡
ይህ በሆነበት ሁኔታ በተሐድሶ (የጲጥፋራ ሚስት) የሐሰት ክስ ምክንያት በግፍ የታሰረውን ነገረ ማርያም (ዮሴፍን) ከእስር ቤት ያስፈታ የብዙዎቻችን እውነተኛ የሕልም ፍቺ ፣ የወላዲተ አምላክን ፍቅር ለተራብን ሁሉ ምግብ የሆነ ‘ወላዲተ አምላክ በነገረ ድኅነት’ የተሰኘ መጽሐፍ ታተመ፡፡
ይህ መጽሐፍ የነገረ ማርያም (Mariology) ድንቅ ምሁራዊ ጥናት ከመሆኑ ባሻገር ውዳሴ ማርያም ትርጓሜን ከቤተ ክርስቲያን ቀደምት አበው ሥነ ጽሑፍ (Patristic Litrature) ጋር ያጣመረ አባ ጊዮርጊስን ከቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ፣ ቅዱስ ያሬድን ከዮስጦስ ሰማዕት ፣ አባ ህርያቆስን ከቅዱስ ጄሮም ጋር ለምስክር የጠራ ቴዎሎጂ ከአብነት ትምህርት ጋር ሲጣመር እንዴት ያለ ውበት እንዳለውና ለክህደት የሚዳርጋቸው በአግባቡ ያልተማሩና ያላነበቡትን ሰዎች ብቻ እንደሆነ በተግባር ያስመሰከረ ፣ ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅን ያስከበረ እጅግ እጅግ ውብ ሥራ ነበረ፡፡
በዛሬው መጠሪያቸው የመጋቤ ሃይማኖት ቀሲስ ዶ/ር አንዱዓለም ዳግማዊ ‘ወላዲተ አምላክ በነገረ ድኅነት’ መጽሐፍ ያለ ምንም ማጋነን ይሄ ትውልድ ተሳልሞ ሊያነበው የሚገባ እጅግ ድንቅ መጽሐፍ ጸሐፊውን ለPHD ያበቃ እኛን ደግሞ ለጥልቅ ንባብ ያነቃ ታሪካዊ መጽሐፍ ነው፡፡ ምንም እንኳን በጸሐፊያን ዘንድ የተሻሉ ሥራዎችን አይቶ እንዳላየ የመሆን በሽታ (Silent conspiracy) የጸናበት ዘመን ቢሆንም በመጽሐፉ የተጠቀማችሁ ጸሐፍት ሁሉ ስለዚህ መጽሐፍ ውለታ ዝም ልትሉ አይገባም::
መጽሐፉ ከገበያ ጠፍቶ አሁን ሲታተም ‘ዮሴፍን የማያውቅ ፈርኦን ተነሣ’ እንዲል ብዙ ሰው የዚህን መጽሐፍ ምንነት አልተረዳም፡፡ ወዳጄ ይህ መጽሐፍ ትናንት ባይኖር የዛሬዎቹ እነ ‘የብርሃን እናት’ ጨርሶ ባልኖሩም ነበረ፡፡ በእያንዳንዱ ኦርቶዶክሳዊ ቤት ሊኖር የሚገባና በማንበብህ የምትኮራበት ውድ መጽሐፍ መሆኑን ስታነቡት ታምኑኛላችሁ፡፡ መጽሐፉን በይፋ ግንቦት ላይ እስክንመርቀው ድረስ ‘ይህን መጽሐፍ ብላ’ ብዬ ስናገር እንደ ሕዝቅኤል ‘በላሁት ጣፈጠኝ’ እንደምትሉ በመተማመን ነው፡፡ አሁን በገበያ ላይ ያለው ውስን ኮፒ ሳያልቅ እጃችሁ አስገቡ::
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
መጋቢት 13 2015 ዓ.ም.
Repost from Tariku Abera
★ አውሬው ዓቢይ አህመድ ኦርቶዶክሳውያንን እንዲህ እየቀጠፋቸው ነው።★
የዓቢይ አህመድ ቅልብ ወታደሮች ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን በአገልግሎት ላይ የነበሩ ሰንበት ተማሪዎችንና መንፈሳዊ በዓሉን ለማክበር በሄዱ ምዕመናን ላይ አስለቃሽ ጭስ በመተኮስ እንዲሁም በዱላ በመደብደብ ለከባድ የአካልና የሥነ ልቡና ጉዳት ዳርገዋቸዋል።
ሼር በማድረግ ለሕዝብ አድርሱ
ሠላም ሠላም፤ በሀገር ውስጥም ሆነ በተለያየ ዓለም (በእኛዋ ሰማይ ወሰን)ና በኛዋ ፀሐይ(ቶማስያ) የምትኖሩ ሁሉ ሠላም ለእናንተ ይሁን፡፡ እግዚአብሔር ይመስገን ሰላም ነን፡፡ ተጠፋፍተናል….፡፡
በቅርብ ቀን(Coming soon)
ዩቲዩብ ቻናል (youtube channel)
ማክዳ ሚዲያ (Makeda Media)
ቶማስያ ሚዲያ (Tomasia Media)
ፌስቡክ (facebook)
ቶማስያ ሚዲያ (Tomasia Media)
ቴሌግራም ቻናል (Tellgram channel)
ማክዳ ሚዲያ @ t.me/Makedamedia
ቶማስያ ሚዲያ @t.me/Tomasia Media
በቅርብ ቀን ስራ የሚጀምር መሆኑን በአክብሮት እየገለጽን፤ኢትዮጵያዊነትን አንድ እርምጃ/ደረጃ ከፍ የሚያደርጉ ስራዎችን ይዘን ለመምጣት ዝግጅታችን አጠናቀናል፡፡….በጥቂት ቀን ውስጥ ቪዶዎችን የምንለቅ /upload የምናደረግ ይሆናል፡፡ ሳብስክራብ(subscribe)፤ሸር(Share)፤ጆይን(join)፤ኮመንት(comment)፤ላይክ(like) እንድታደርጉን በትህትና እየጠየቅን…በተቻለ መጠን እውነተኛ፤የሚጨበጥና የሚዳሰሱ እንዲሁም ማህበረሰብ፤ በተለይ ትውልድ ላይ ለውጥ ያመጣሉ የተባሉ ፕሮግራሞችን እንደሚኖሩን ከወዲሁ እየገለጽን እስከዛው ሠላም ለዓለሙ ሁሉ ይሁን፡፡
ወደውና ፈቅደው ቤተሰብ ስለሆኑ ስላደረጉን እጅግ እናመሰግናለን፡፡
ሠላም ለዓለሙ ሁሉ ይሁን፤እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይጠቅብልን/ይባርክልን አሜን(3)፡፡
ቶማስያ ሚዲያ!!!
ማክዳ ሚዲያ!!!!!
