ፍኖተ ጽድቅ መንፈሳዊ የጉዞ ማህበር ወደ ግሸን ላሊበላ ቁልቢ ገብርኤል እና ሌሎች ገዳማት ጉዞ እናዘጋጃለን
Open in Telegram
ይህ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክ ስርዓት እና ደንብ የተከተለ ሃይማኖታዊ መልእክት እሚተላለፍበት ነው ሃይማኖት እንደ አባቶቻችን ቴክኖሎጂ እንደዘመናችን! ተጠቅመን የገዳማት ታሪክ ወቅታዊ የቤ/ክ መልዕክት እና መረጃ የምንለዋወጥበት ቃለ እግዚአብሔር የምንማርበት ነ የአባቶቻችን ትምህርት እናስተምራለን ፤ ተስፋቸውንም ተስፋ እናደርጋለን ፤ የተማርናት ፤ ሃይማኖት ይህች ናት:: እንኖርባታለን
Show more579
Subscribers
No data24 hours
No data7 days
No data30 days
Posts Archive
እመቤታችን ድንግል ማርያምም ከዚህ በኋላ ከቤተ መቅደስ ወጥታ ከጻድቁ ዮሴፍ ጋር ኖረች፡፡ እርሱም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ፀንሳ ስትወልድ፣ በስዳቷ ወቅትም ወደ ግብጽና ኢትዮጵያ ስትጓዝ እንዲሁም መከራ ስትቀበል ሁሉ ከጎና ሳይለይ የጠበቃት ነው፡፡ ይህን ሁሉ ግን አምላካችን እግዚአብሔር በቸርነቱ ለእኛ ድኅነት ሲል ያደረገው በመሆኑ በእመቤታችን በኩል የተፈጸመውን የክርስቶስ የማዳን ሥራ በእምነት በመቀበል አማላጀነቷንና ተራዳኢነቷን ተስፋ በማድረግ ልንኖር ይገባል፡፡
በዓሉን የምሕረት፣ የበረከትና የረድኤት ያድርግልን፤ አሜን!
ምንጭ፡- “ነገረ ማርያም በሐዲስ ኪዳን” በመጋቤ ሐዲስ መምህር ሮዳስ ታደሰ
ቅዱስ ኢያቄምና ቅድስት ሐናም የእግዚአብሔርን ስእለት ለመፈጸም ዘመዶቻቸውንና ባልንጀሮቻቸውን በመጥራት ልጃቸውን ልዩና ንጹሕ ልብስን አልብሰው በመንፈሳዊ ዝማሬ እግዚአብሔርን እያመሰገኑ፣ መብራትን በእጆቻቸው ይዘው እያበሩ ኢየሩሳሌም ወዳለው ቤተ መቅደስ ወሰዷት፤ በዚያን ጊዜም ሊቀ ካህናቱ ዘካርያስ ከካህናቱ ጋር በመሆን እነርሱን ለመገናኘት ከመቅደስ ወጣ፡፡
በቤተ መቅደሱ ባሉት የሊቀ ካህናቱ መግቢያ ወደ ቅድስተ ቅዱሳኑ የሚያስወጡ ፲፭ ደረጃዎች ነበሩ፤ በእነዚያም በእያንዳንዱ ደረጃዎች መዝሙረ ዳዊት ተደጋግሞ የሚደረስባቸው ናቸው፤ ቅዱስ ኢያቄምና ቅድስት ሐናም ልጃቸው እመቤታችን ማርያምን ከአንደኛው ደረጃ ላይ ቢያኖሯት መንፈሳዊ ኀይልን ተመልታ ያለምንም ረዳት ብቻዋን ደረጃዎቹን በመውጣት ወደ ሊቀ ካህናቱ ወዳለበት ስፍራ ሄደች፤ እርሱም በእጅጉ ተደንቆ ባረካት፤ በዚያን ጊዜም ለሊቀ ካህናቱ ዘካርያስ መንፈስ ቅዱስ ምሥጢርን ገለጠለት፤ ነቢያት ትንቢት የተናገሩላት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አምላክን በድንግልና ፀንሳ በድንግልና እንደምትወልድ አስገነዘበው፤ መኖሪያዋም በዚሁ ቤተ መቅደስ እንዲሆን የአምላክ ፈቃድ መሆኑን አወቀ፡፡
እርሱም ይህንን የእግዚአብሔር ድንቅ ሥራን በማድነቅ ‹‹ይህቺን የመሰለች ልጅ ምን እናደርጋታለን? ምን እናበላታለን? ምንስ እናጠጣታለን? ምን እናነጥፍላታለን?›› ብሎ ሲጨነቅ ቸርነቱ የማያልቅ ልዑል እግዚአብሔር መልአኩ ፋኑኤልን ላከላት፡፡ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ፋኑኤልም ኅብስት ሰማያዊን በብርሃን ጽዋዕ ስቴ ሕይወትን ይዞ ረብቦ ታየ፤ ካህኑ ዘካርያስም ለእርሱ የመጣ ኅብስተ መና እንደሆነ አስቦ ታጥቆና እጅ ነሥቶ ቢቆም ወደ ላይ ራቀበት፡፡ የተሰበሰበው ሕዝብ በተራ በተራ ቢሞክሩም በተመሳሳይ ሁኔታ ወደ ላይ ራቀባቸው፡፡ ሐና እና ኢያቄምም ለእነርሱ የመጣ እንደሆነ ለማወቅ ቢቀርቡም ወደ ላይ ከፍ አለባቸው፤ ከዚህ በኋላ ካህኑ ዘካርያስ ሐናን ‹‹እግዚአብሔር የሚያደርገውን የሚያውቅ የለምና ልጅቷን ትተሸ ወደዚህ ነይ›› አላት፡፡ በዚህ ጊዜም መልአኩ በመውረድ አንድ ክንፉን አንጽፎ፣ አንዱን ክንፉን አጐናጽፎ ከመሬት የሰው ቁመት ያህል ከፍ አድርጓት ኅብስቱን መገባት፤ ጽዋውን አጠጣት፤ በኋላም ወደ ሰማይ ዐርጓል፡፡ ሊቀ ካህናቱም ‹‹የምግቧ ነገር ከተያዘልን ቦታዋ ከቤተ መቅደስ ይሁን›› ብለው ምንጣፉን አንጥፈው፣ መክዳውን ግራና ቀኝ፣ መጋረጃውን አድርገው ወደ ቤተ መቅደስ አስገቧት፤ ይህም ታኅሣሥ ፫ ቀን ነበር፡፡
እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ሰማያዊ ኅብስት እየተመገበች፣ ስቴ ሕይወት እየጠጣችና ከመላእክት ጋር እየተጫወተች ፲፪ ዓመት በቤተ መቅደስ ኖረች፡፡ ሆኖም ግን በቤተ መቅደስ ሳለች አይሁድ ተሰብስበው ክፉ ምክርን መከሩባት፤ “ሰማይንና ምድርን የፈጠረ አምላክን ትወልዳለችና እርሷም እንደ ባሪያ ልትገዛን ነው” በሚል ለማስገደል ሰዎችን ላኩ፡፡ እነዚያም አይሁድ የላኳቸው ሰዎች ሊገድሏት ሲሄዱ ቤተ መቅደሱ አራት ማዕዘን እሳት ሆኖ፣ መላእክትም ሰይፋቸውን መዘው፣ ረበው ታዩአቸው፡፡ ይህን ሲመለከቱ እመቤታችን በእሳት እንደ ተቃጠለች አስበው በመደሰት ወደ መጡበት ተመልሱ፤ በማግስቱ ግን በቤተ መቅዱስ በደኅና አገኟት፡፡
አይሁድ በዚህን ጊዜ እንዲገድሏት ወዳዘዙአቸው ሰዎች በመሄድ ለምን እንዳልገደሉአት ጠየቁአቸው፤ እነርሱም የሆነውን ባለ መረዳት በድጋሜ ሊገድሉአት ሄዱ፤ ዳግመኛም መንገዳቸው ዱር፣ ገደልና ባሕር ሆነባቸው፡፡ ይህን ጊዜ በአስማት እንዲህ የምታደርጋቸው እንደሆነ በማሰብ የእርሷን አስማት የሚበልጥ ለመፈለግ ተስማምተው መጥቁል የሚባል መተተኛ ጋር ሄዱ፡፡ እርሱም ‹‹ዋጋዬን ከሰጣችሁኝ እሺ፤ እርሷንስ አጠፋላችኋለሁ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ብዙ ወርቅ፣ ፈረስ፣ በግ፣ ፍየል፣ ጊደርና አልባሳት ሰጡት፡፡ ነገር ግን ይህን ሁሉ ሀብት ለማግኘት መለስ ቢል ብሩ፣ ወርቁና ሁሉ ነገር ዝጎና አፈር በልቶት አገኘው፡፡ ይህን ጊዜ ‹‹የኢያቄምና የሐና ልጅ ሳልቀድማት ቀደመችኝ›› ብሎ እጅን ጸፋ፡፡ ከዚያም ለእነርሱ ሲያሳያቸው ‹‹እኛማ ቀድመን አላልንህምን? አንተ ነህ እንጂ ሁሉን ማድረግ ይቻለኛል ያልከው›› አሉት፡፡ ገንዘባቸውንም እንዲመልስላቸው አስጨንቀው ያዙት፤ መጥቁልም ‹‹ቆዩኝ፥ የእርሷንስ ነገር አሁን በመንፈቀ ሌሊት አሳያችኋለሁ›› ብሎ ከእነርሱ መካከል ጎበዝ ጎበዙን መርጠው ፫፻፸ ሰው እንዲሰዱለት በጠየቃቸው መሠረት ሰጡት፤ ከእነርሱም መካከል ወንዝ ወርዶ አንዱን አርዶ ፫፻፸ አጋንንት ስቦ ካወጣ በኋላ እንዲረዱት ጠየቃቸው፤ በጠየቃቸው ነገር ደስ በመሰኘትም አጋንንቱ ከፊት፣ መጥቁል በመካከል አይሁድ በኋላ ሆነው ነጋሪት እየተመታ፣ እምቢልታ እየተነፋ፣ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ለመግደል ቤተ መቅደስ ሊደርሱ ሁለት ምንዳፈ ሐጽ ሲቀራቸው ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እስከዚያ ድረስ ያልተደረገ መብረቅና ነጎድጓድ ወርዶ አጋንንትን፣ መጥቁልንና አይሁድን ቀጥቅጦ አጠፋቸው፡፡
እመቤታችን ድንግል ማርያምም በማግስቱ ይህን አይታ ‹‹መጥቁል ሆይ፥ እኔን አጠፋ ብለህ መጥተህ አንተ እንዲህ ሆንክ? ከአንተ መከራና መዓት ያወጣኝ አምላክ ይክበር ይመስገን›› ብላ አመሰገነች፡፡ ‹‹ዮሰሜር፣ አድሜሽ፣ ድቸር፣ አዶናዊስ፣ ሰራሰቅሰሬል›› ብላ የጌታን ኅቡእ ስሙን ብትጸልይበትም መሬት ተከፍቶ ከእነ ሥጋቸው ዋጣቸው፡፡
እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ከዚህ በኋላ ተፈራች፤ ለመልካም ሰው ወዳጅ ለክፉ ሰዎችም ጭምር አማላጅ የሆነችው እናታችን ለጠንቋይና ለአስጠንቋይ ግን በሕይወተ ሥጋ እስካሉ ድረስ ንስሓ ካልገቡ በስተቀር እንደማታማልዳቸው ከዚህ ታሪክ እንረዳለን፡፡
እናታችን፣ አማላጃችንና ተራዳኢያችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጠላት የተነሡባት በዚህ ጊዜ ብቻ አይደለም፡፡ ፲፭ ዓመት ሲሞላትም ‹‹ለአቅመ ሔዋን በመድረሷ ከቤተ መቅደስ መውጣት አለባት›› በሚልም አይሁድ በጠላትነት ተነሥተውባት ነበር፡፡ ካህኑ ዘካርያስም ይህን ሰምቶ እመቤታችንን እንዲህ ብሎ ጠየቃት፤ «ኦ ወለተ እስራኤል እፎ ትፈቅዲ ትንበሪ፤ ልጄ እንደምን ሆነሽ ልትኖሪ ትወጂያለሽ?» አላት፡፡ እርሷም «ከእግዚአብሔር በታች ያለኸኝ አባት አንተ ነህ፤ በዚያውም ላይ እናትና አባቴ አደራ ያሉህ አንተን ነው፤ ወደ እግዚአብሔር አመልክትልኝ» አለችው፡፡ ዘካርያስም ጸለየ፤ አምላካችን እግዚአብሔርም ለካህኑ ዘካርያስ ከነገደ ይሁዳ መካከል ሚስቶቻቸው የሞቱባቸውን ሰዎች በመምረጥ በትራቸውን ሰብስቦ በቀዳማይ ሰዓተ ሌሊት ከቤተ መቅደስ አግብቶ ሲጸልይ እንዲያድር እንዲሁም በቀዳማይ ሰዓተ መዓልት አውጥቶ ምልክቱን እንዲመለከት ነገረው፡፡ እርሱም እንደታዘዘው አድርጎ በማግስቱ ካህናቱን ሰብስበው በትሮቹን አውጥተው ቢያዩ የዮሴፍ በትር አብባና አፍርታ ተገኘች፡፡ ከበትሩ ጫፍ ላይም «ኦ ዮሴፍ ወልደ ዳዊት ዕቀባ ለማርያም ፍኅርትከ፤ ዮሴፍ ሆይ እጮኛህ ማርያምን ጠብቃት» የሚል ጽሑፍ በመገኘቱ ርግብም መጥታ በራሱ ላይ አርፋ ነበርና ለእርሱ ተጠሰች፡፡
‹‹ትነብር ውስተ ቤተ መቅደስ፤ በቤተ መቅደስ ውስጥ ትኖር ነበር›› ቅዱስ ያሬድ
ዓለም ሁሉ ተሰብስቦ ቢመዘን አንድ የራሷን ፀጉር የማያህል ደግ ፍጥረት፣ ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች፣ ንጽሕናዋንም ይሁን ቅድስናዋን ፍጥረት በአንደበቱ ተናግሮም ሆነ ጽፎ የማይጨርሰው፣ የአምላክ ማደሪያ፣ እመ አምላክ፣ እመ ብዙኃን፣ ሰዓሊተ ምሕረት፣ አቁራሪተ መዓት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ ቤተ መቅደስ የገባችበት ዕለት የከበረ በዓል ነው፡፡
ሊቁ ቅዱስ ያሬድም ‹‹ትነብር ውስተ ቤተ መቅደስ፤ በቤተ መቅደስ ውስጥ ትኖር ነበር›› በማለት ስለ እርሷ የቅድስናና የንጽሕና ሕይወት ገልጿል። እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በፈቃደ እግዚአብሔር ከአባቷ ቅዱስ ኢያቄምና ከእናቷ ቅድስት ሐና በስእለት የተገኘች መሆኗ ታሪኳ የተመዘገበበት የነገረ ማርያም መጽሐፍ ይገልጻል፡፡
ቅድስት እናታችን ድንግል ማርያም በተለወደች በስድስት ወሯ ከእናቷ እቅፍ ወርዳ በመቆምና ሰባት እርምጃን ተራምዳ ዳግም ወደ እናቷ እቅፍ ውስጥ በመግባት ሐናን አስደንቃታለች፡፡ አንድ ዓመት ሲሆናትም አባቷ ኢያቄም ታላቅ ድግስ አዘጋጅቶ ካህናቱንና ሕዝብን ጠርቶ ጋበዘ፡፡
ከዚህም በኋላ እመቤታችን ሦስት ዓመት በሆናት ጊዜ እናቷ ሐና የልጇን ስእለት አስታውሳ ለቤተ መቅደስ አገልጋይ እንድትሆን መስጠት እንዳለባቸው ለባሏ ለኢያቄም እንዲህ ብላ አወሳችው፤ ‹‹ይህቺ ብላቴና የስእለት ገንዘብ እንደሆነች ታውቃለህ፤ ወስደን ለቤተ እግዚአብሔር እንስጣት፤›› እርሱም ‹‹ፍቅርሽ ይለቅልሽ ብዬ ነው እንጂ እኔማ ፈቃዴ ነው›› አለ፤ ኢያቄም ይህን ማለቱ ሐና እመቤታችንን በመካንነት ኖራ ያገኘቻት አንዲት ልጇ ናትና ከፍቅሯ ጽናት የተነሣ ተለይታት አታውቅም ነበርና ነው፡፡
ነቢያት ጌታ "ይወርዳል ይወለዳል" ብለው የተናገሩት ትንቢት እንዲፈጸም ተመኝተው ጾሙ ጸለዩ:: እኛ ስለምን እንጾማለን? ክርስቶስ ተወልዶ ፣ ተጠምቆ ፣ አስተምሮ ፣ ተሰቅሎ ፣ ሞቶ ፣ ተነሥቶ ፣ ዐርጎ ፣ በአባቱ ቀኝ አይደለምን? አሁን ለምን እንጾማለን? ብለን እናስባለን::
ጌታ በእኔና አንተ ልብ ውስጥ እውነት ተወልዶአልን? እውነት የእኛ ልብ እንደ ቤተልሔም ግርግም ለክርስቶስ ማደሪያ ሆኖአል? ማደሪያ አሳጥተን ከእናቱ ጋር አልመለስነውም?
የጥምቀቱ ትሕትና በእኛ ልብ መቼ ደረሰ? የስቅለቱ ሕማም መች በእኛ ሕሊና ተጻፈ? የትንሣኤው ተስፋ የዕርገቱ ልዕልና በእኛ ልቡና መቼ ዐረፈ?
ስለዚህ ነቢያት "ውረድ ተወለድ" ብለው የጾሙትን ጾም እንጾማለን:: ጌታ ሆይ በእኔ ሕይወትም ውስጥ ውረድ ተወለድ የእኔን ሰውነት ማደሪያህ አድርገው:: ሕዋሳቶቼ ከኃጢአት አርፈው እንደ ቤተልሔም ግርግም ማደሪያህ ይሁኑ::
የቤተልሔም እንስሳት ትንፋሽ ገበሩልህ ፣ የቢታንያ ድንጋዮች ዘማሪ ቢጠፋ ሊዘምሩ ዝግጁ ነበሩ ፣ የቤተ መቅደስ መጋረጃ ለክብርህ ተቀደደ ፣ ጨረቃ ላንተ ደም ለበሰች ፣ ፀሐይ ስላንተ ጨለመች ፣ ከዋክብት ለስምህ ረገፉ ፣ ዓለቶች ለፍቅርህ ተሰነጠቁ::
ከቤተልሔም እንስሳት ፣ ከቢታንያ ድንጋዮች ፣ ከቤተ መቅደስ መጋረጃ እኔ እንዴት አንሼ ልገኝ? የቢታንያ ድንጋይ ያወቀህን ያህል ሳላውቅህ ፣ የቤተ መቅደስ መጋረጃ የተረዳህን ያህል ሳልረዳህ እንዴት ልኑር?
ዓለት ላንተ ሲሰነጠቅ የኔ ልብ ለምን ከዓለት ደነደነ? ጨረቃ ደም ስታለቅስ እኔ መከራህ ለምን አልተሰማኝም?
ሙታን በሞትህ ሲነሡ እኔ ምነው ከኃጢአት ሞት መነሣት ተሳነኝ?
ለዚህ ነው በእኔ ሕይወት ገና አልተወለድክም የምለው::
ስለዚህ ጌታ ሆይ የነቢያትህን ጾም ጸሎት ሰምተህ የወረድህ የተወለድህ ጌታ ሆይ በእኔም ሕይወት ውረድ ተወለድና እኔም ከመላእክት ጋር አብሬ ልዘምር ፣ ከሰብአ ሰገል ጋር ሥጦታህን ልቁጠር ፣ ከእረኞች ጋራ ልደነቅ:: ልደትህ ሳይገባኝ ምጽዓትህ እንዳይደርስብኝ እርዳኝ::
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ጾመ ነቢያት 2015 ዓ.ም. የተጻፈ
ከመፅሐፍ ቅዱስ የልጇት ስም ማውጣት ይፈልጋሉ እስከ ትርጉሙ
1 ሩሐማ፦ምሕረት ማለት ነው።
2 ዮዳሔ፦እግዚአብሔር ያውቃል ማለት ነው።
3 ቴዎፍሎስ፦የእግዚአብሔር ወዳጅ ማለት ነው።
4 ኑኃሚን፦ደስታየ ማለት ነው።
5 ናትናኤል፦የእግዚአብሔር ስጦታ ማለት ነው።
6 አዛሄል፦እግዚአብሔር ያያል ማለት ነው።
7 ኢዮስያስ፦እግዚአብሔር ይደግፋል ማለይ ነው
8 ኢዩኤል፦እግዚአብሔር አምላክ ነው ማለት ነው።
9 በርናባስ፦የመጽናናት ልጅ ማለት ነው።
10 ሶፎንያስ፦እግዚአብሔር ሰውሯል/ጠብቋል ማለት ነው።
11 ሕዝቅኤል፦እግዚአብሔር ብርታትን ይሰጣል ማለት ነው።
12 ኬልቅያስ፦እድል ፈንታየ እግዚአብሔር ማለት ነው
13 ሳሙኤል፦እግዚአብሔር ሰማኝ ማለት ነው።
14 ሚኪያስ፦ እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው! ማለት ነው።
15 ሆሴዕ፦እግዚአብሔር ያድናል ማለት ነው።
16 ሔዋን፦የሕያዋን ሁሉ እናት ማለት ነው።
17 ሕዝቅያስ፦እግዚአብሔር ኃይሌ ነው ማለት ነው።
18 መልከጼዴቅ፦የሰላም ንጉሥ ማለት ነው።
19 ሚልኪያስ፦መልእክተኛየ ማለት ነው።
20 ሣራ፦ልዕልት ማለት ነው።
21 ስምዖን፦ሰማ ማለት ነው።
22 ብንያም፦የቀኝ እጄ ልጅ ማለት ነው።
23 ናሆም፦መጽናናት ማለት ነው።
24 ናታን፦ እግዚአብሔር ሰጥቷል ማለት ነው።
25 አልዓዛር፦እግዚአብሔር ረድቷል ማለት ነው።
26 አስቴር፦ኮከብ ማለት ነው፣
27 አቤሜሌክ፦የንጉሥ አገልጋይ ማለት ነው።
28 አቤሴሎም፦አባቴ ሰላም ነው ማለት ነው።
29 አብድዩ፦የእግዚአብሔር አገልጋይ ማለት ነው።
30 አብራም፦ታላቅ አባት ማለት ነው።
31 አብርሃም፦የብዙዎች አባት ማለት ነው
32 አኪያ፦እግዚአብሔር ወንድሜ ነው ማለት ነው።
33 አክዐብ፦የአባት ወንድም ማለት ነው።
34 ባሮክ፦ቡሩክ ማለት ነው።
35 አዳም፦መልካሙ ማለት ነው።
36 ኢሳይያስ፦ እግዚአብሔር ደኅንነት ነው ማለት ነው።
37 ባርቅ፦መብረቅ ማለት ነው።
38 ኢያሱ፦እግዚአብሔር አዳኝ ነው ማለት ነው።
39 ኢዮሳፍጥ፦እግዚአብሔር ፈርዷል ማለት ነው።
40 ኢዮራም፦እግዚአብሔር ከፍ ከፍ አለ ማለት ነው።
41 ኢዮርብዓም፦ሕዝቡ እየበዛ ይሄዳል ማለት ነው።
42 ቤተልሔም፦የእንጀራ ቤት ማለት ነው።
43 ኢዮአስ፦እግዚአብሔር ሰጥቷል ማለት ነው።
44 ኢዮአቄም፦እግዚአብሔር አቆመ ማለት ነው።
45 ኢዮአብ፦እግዚአብሔር አባት ነው ማለት ነው።
46 ኢዮአታም፦እግዚአብሔር ፍጹም ነው ማለት ነው።
47 ኢዮአካዝ፦እግዚአብሔር ይዟል ማለት ነው።
48 ኤልሳዕ፦እግዚአብሔር ደኅንነት ነው ማለት ነው።
49 ኤልያስ፦እግዚአብሔር አምላክ ነው ማለት ነው።
50 ኤልያቄም፦እግዚአብሔር ያስነሳል ማለት ነው።
51 ኤዶም፦ቀይ ማለት ነው
52 እስራኤል፦ከእግዚአብሔር ጋር ይታገላል ያሸንፍማል ማለት ነው።
53 ኤልሳቤጥ፦እግዚአብሔር መሐላየ ነው ማለት ነው።
54 ኤልሻዳይ፦ሁሉን ቻይ አምላክ ማለት ነው።
55 ሀሌሉያ፦እግዚአብሔርን አመስግኑ ማለት ነው።
56 ሰሎሞን፦ሰላማዊ ማለት ነው።
57 ኬብሮን፦ኅብረት ማለት ነው
58 አዛርያስ፦እግዚአብሔር ረድቷል ማለት ነው።
59 ኤደን፦ደስታ ማለት ነው።
60 ዖዝያን፦እግዚአብሔር ኃይሌ ነው ማለት ነው።
61 ዘካርያስ፦እግዚአብሔር ያስታውሳል ማለት ነው።
62 ይሳኮር፦ ዋጋዬ ማለት ነው
63 ይዲድያ፦በእግዚአብሔር የተወደደ ማለት ነው።
64 ዮሐናን፦እግዚአብሔር ጸጋ ሰጪ ነው ማለት ነው።
65 ዮሐንስ፦እግዚአብሔር ጸጋ ነው ማለት ነው።
66 ዮሴፍ፦ይጨምር ማለት ነው።
67 ዮናስ፦ርግብ ማለት ነው።
68 ዮናታን፦እግዚአብሔር ሰጥቷል ማለት ነው።
69 ዮአኪን፦እግዚአብሔር ያቆማል ማለት ነው።
70 ዮካብድ፦እግዚአብሔር ክብር ነው ማለት ነው።
71 ምናሴ፦ማስረሻ ማለት ነው።
72 ዮፍታሔ፦እግዚአብሔር ይከፍታል ማለት ነው።
73 ዲቦራ፦ንብ ማለት ነው።
74 ዳንኤል፦እግዚአብሔር ፈራጅ ነው ማለት ነው።
75 ጎዶልያስ፦እግዚአብሔር ታላቅ ነው ማለት ነው።
76 ጽዮን፦አምባ ማለት ነው።
77 ጳውሎስ፦ብርሃን ማለት ነው።
78 ሴት፦ምትክ ማለት ነው።
79 ጴጥሮስ፦አለት ማለት ነው።
80 ሄኖክ፦ታደሰ ማለት ነው።
81 ኄራኒ፦ሰላም እና ፍቅር ማለት ነው።
።
ፍቅር : ሰላም : ለምድራችን !
በድርሳነ ዑራኤል ተጽፎ እንደምናገኘው እመቤታችን ወደ ኢትዮጵያ የመጣችው በሀገረ ናግራን በኩል አልፋ በደብረ ዳሞ፥ በአክሱም፣ በደብረ ዓባይ ከዚያም በታላቁ ገዳም ዋልድባ አድርጋ መላው ኢትዮጵያን በደመና ተጭና በመልአኩ ዑራኤል መሪነት ሲሆን በብዙ ቦታዎች በኪደተ እግሯ ተመላልሳ ጎብኝታታለች፤ ባርካታለች፡፡ ‹‹ሰላም ለምጽአትክሙ ጥንተ ዜና ነገር አእመነ፤ በዓለ ደመና ዑራኤል ወድንግለ ሲና እምነ፡፡ ሰሎሜ ወዮሴፍ በኢትዮጵያ ምድርነ፡፡..፤ ከጥንት ጀምሮ የተነገረውን ዜና ለማሳመን የደመናው ባለቤት ዑራኤል ዮሴፍና ሰሎሜ፤ የሲናዋ ድንግል እናታችን ሰላምታ ይገባችኋል፤ ለአደረጋችሁት አመጣጥ በኢትዮጵያ ምድራችን›› እንዲል፡፡
እመቤታችን ለተወዳጁ ሐዋርያ ቅዱስ ዮሐንስ እንደ ነገረችው ጌታችን በተወዳጅ እናቱ ጀርባ ላይ ሆኖ አብዝቶ ወደ ምዕራብ ይባርክ ስለ ነበረ እንዲህ ስትል ጠይቃው ነበር፡፡ ‹‹ለምንት ኩለሄ ትባርክ ነቢረከ ኅዙለከ ዲበ ዘባን ምድረ አዜብ…፤በጀርባዬ ላይ ሆነህ ሁል ጊዜ ወደ ምዕራብ የምትባርከው ስለምን ነው ብዬ ጠየቅሁት፡፡›› (የኅዳር ድርሳን) ልጇም እንዲህ ሲል መለሰላት፤ ‹‹ኦ እምየ ይእተ ሀገረ ዘእባርክ ወሀብኩኪ ዐሥራተ ወይኩኑ ለኪ ሰብአ ኢትዮጵያ ክፍለ ለርስትኪ እስከ ኅልቀተ ዓለም….፤ እናቴ ሆይ በዚች በምባርካት አገር በኢትዮጵያ የሚኖሩ ሰዎችን እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ዐሥራት አድርጌ ሰጥቸሻለሁ፤ እናቴ ሆይ አሁንም ወደዚያች ሀገር እንሄድ ዘንደ ተነሽ..›› ይላታል፡፡ እናቱን እንዲህ ባለ ቃል ከነገራት በኋላ ብሩህ ደመና ጭናቸው ወደ ኢትዮጵያ ገብተዋል፡፡
በዚህም በሃማሴን በኩል አድርገው በደብረ ዳሞ፣ በአክሱም ጽዮን፣ በደብረ ዓባይ በተለይም በዋልድባ ወደ ጣና ደሴት ከመግባታቸው በፊት ቆይታ አድርገዋል፤ በአክሱም ጽዮን ገብታ ሕዝቡንም ካህናቱንም ንጉሡንም ባረካቸዋለች፡፡ ደራሲው ይህንንም በውብ ቃል እንዲህ ሲል ይገጸዋል፤ ‹‹…ተፈስሐት ዓውደ ጽዮን ወተሰርገወት ብርሃነ፡፡ እስመ ጽዮን እንዘ ጽዮን አብዓለት ጽዮነ፤ እርሷ ጽዮን ስትሆን የጽዮንን በዓል አከበረች ጽዮን፡፡ የጽዮንንም አደባባይ ደስ እያላት አከበረች በብርሃን›› ይላል፡፡ እመቤታችን በገዳመ ዋሊ (ዋልድባ) በዋሻዎቿ ሁሉ ተቀምጣ፣ የሚበላ ሳይኖር ልጇ መራራ የዕፀዋት ሥሮችን ቆፍሮ ሰጥቷት ቀምሳ ስለ እርሷ ፍቅር መራራውን ቀምሰው፣ መከራውን ታግሠው፣ በስሟ ተማጽነው፣ በውዳሴዋና በቅዳሴዋ ተጽናንተው፣ ሥጋን እስከ ክፉ መሻቱ አሸንፈው ሰማያዊ ሰው ምድራዊ መልአክ ሆነው የሚኖሩ መነኮሳት መናንያን የሚኖሩበት ታላቅ የቅድስና ስፍራ እንዲሆን ያደረገችው በዚሁ በስደቷ ወቅት ነው፡፡
ኢትዮጵያውያን ደጎች እንደ ነበሩ፤ እንግዳ ተቀባይነታቸውም በቃላት የማይገለጽ እንደ ሆነ እመቤታችን ምስክርነት ሰጥታለች፡፡ ከዋልድባ ተነሥታ ጣናንና አካባቢውን በጎበኘችበት ጊዜ በደስታ እንደ ተቀበሏት እንዲህ ትላለች፤ ‹‹በብርሃን ሠረገላ ተጭነን ተነሣንና ከጣና ባሕር ወደብ ደረስን በዚያች የባሕር ደሴት ውስጥ የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ እነዚህ የነገሥታት ልጆች የሚመስሉ እንግዶች ከወዴት መጡ እያሉ በመደነቅ በደስታ ተቀበሉን፤….እነዚያ ደጋግ ሰዎች መምጣታችንን ለጌታቸው ነገሩት፡፡ እርሱም ፈጥኖ ተነሣና ወደ እኛ መጥቶ በሰላም፣ በደስታ ተቀበለን፤ ማረፊያ ቦታም ሰጠን›› በማለት ለቅዱስ ዮሐንስ ስትተርክለት ጽፎታል፡፡
እመቤታችን በጣና ውስጥ ሦስት ወር ከዐሥር ቀን ተቀምጣለች፡፡ በዚህም ምክንያት የጣናን ባሕር የብርሃን መላእክት መጥተው በእሳት ሰይፍ ስለ ከበቧት አጋንንት እንደ ሸሹ፣ መባርቅትም ሊያጠፏቸው እንደ ተከታተሏቸው፣ በዚያም በባሕር እንዳሰጠሟቸውና ወደ ሲኦልም እንደ ጣሏቸው በድርሳነ ዑራኤል ላይ ተጽፏል፡፡ (ደርሳን ዘታኅሣሥ)
እመቤታችን እና ተወዳጅ ልጇ በስደት የቆዩበት ዘመን የተፈጸመውም በኢትዮጵያ ነው፡፡ ‹‹ወመዊቶ ሄሮድስ፤ ናሁ መላከ እግዚአብሔር አስተርዮ በሕልም ለዮሴፍ በምድረ ግብጽ እንዘ ይብል ተንሥእ ወንሣእ ሕፃነ ወእሞ ወሑር ውስተ ምድረ እስራኤል፤ ሄሮድስ ከሞተ በኋላ በግብጽና በኢትዮጵያ ሳለ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ለዮሴፍ በሕልም ነገረው፤ ብላቴናውንና እናቱን ይዘህ ወደ ምድረ እስራኤል ተመለስ፤ ሕፃኑን የሚፈልጉት ሞተዋልና›› እንዲል፡፡ (ማቴ.፪፥፲፱) የሄሮድስ መሞት የምሥራቹን የሰሙት በጣና ደሴት ለሦስት ወር ከዐሥር ቀን ያክል ከተቀመጡ በኋላ ነው፡፡ በዚህ ጊዜ መልአኩ እንዲህ አላት፤ ‹‹ተንሥኢ እግዝእትየ ከመ ንሁር ሀገረኪ ናዝሬተ ወተጸዓኒ ዲበ ሠረገላ ብርሃን መልዕልተ ደመና ዘሀሎ፤ ተነሽ ወደ ሀገርሽ ናዝሬት እንሂድ አላትና ሊሄዱ ተነሡ፡፡ ያ ደግ እንግዳ ተቀባይ ሀገረ ገዥ ምነው ምን በደልኩ ለምን ትሔዳላችሁ›› እያለ እያለቀሰ ለመናቸው፡፡
በዚህ ጊዜ መልአኩ ‹‹ምንም አልበደልክም፤ አንዳችም ክፉ ሥራ አልሠራህባቸውም፤ ሄሮድስ ስለ ሞተ ወደ ገሊላ ስለሚመለሱ ነው›› አለው፡፡ ያ መኮንንም ይህን በሰማ ጊዜ ጮሆ አለቀሰ፤ የደሴቱና አካባቢው ሰዎችም እስኪሰበሰቡ ድረስ ጮኸ፡፡ ከዚህ በኋላ ከደመናው በላይ ባለው የብርሃን ሠረገላ ላይ ወጥታ ቆመችና በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ተራሮችን ሁሉ እያሳየ ‹‹ለስምሽ መታሰቢያ ይሁኑሽ›› አላት፤ ባረከቻቸውም፡፡
በዚህ የተደሰቱ የመላእክት ማኅበር በሙሉ ተሰብስበው ‹‹በእንቲአኪ ተራከባ ሣህል ወርትዕ ጽድቅ ወሰላም ተሰዓማ ለዛቲ ሀገረ ኢትዮጵያ ምሕረትኒ ወጽድቅ ይነብር ላይሌሃ..፤ በአንቺም ይቅርታና ቅንነት እውነትና ሰላም ተገናኙ፤ በዚችም በኢትየጵያ ምድር ላይ ምሕረትና እውነት ይኖራሉ›› ሲሉ አመስግነዋታል፡፡ ይህን ሁሉ ከስደቷ መልስ ለዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ የተረከችለት ነው፡፡
ተወዳጆች ሆይ! እመቤታችንና ኢትዮጵያውያንን ያቆራኛቸው ቃል ኪዳን እስከ ዓለም መጨረሻ መሆኑን እንደተገነዘባችሁ ተስፋ እናደርጋለን፡፡ የማንዘልቀውን ጀምረናልና በዚሁ ይበቃናል፤ ብቻ ዝም ብለን በጠቢቡ ቃል እኛም ‹‹ተመየጢ፥ ተመየጢ፥ ሰላመ ሰጣዊት ወንርአይ ብኪ ሰላመ›› አንቺ የሰላም መፍሰሻ፣ አንቺ የደስታ መገኛ ሆይ፥ ተመለሽ!›› እንበላት፡፡ (መቅድመ ኪዳን)
አሁን ኢትዮጵያውያ ስደተኛ መቀበል አትችልም ስደተኛ ሆናለችና፤ ሱላማጢስ ሆይ አሁን እነዚያ ደጋግ ሰዎች ለእንግዳ ማረፊያ አይሰጡም፤ እነርሱም ማረፊያ መጠለያ አጥተዋልና፤ አሁን የተራበን ለማብላት አቅም የላቸውም፤ እነርሱም ረኃብተኞች ናቸውና፡፡ እናታችን ሆይ ተመለሽ! ሰላማችን ሆይ ነይ! ወደ ዐሥራት ሀገርሽ ተመለሽ! ቃል ኪዳንሽንም አድሽ! የአዲስ ኪዳን ስደተኞች በኩር ሆይ ተመለሽ! መከራችን ያበቃ ዘንድ፣ እንባችን ይታበስ ዘንድ ተመለሽ!
ጨለማው ይገፈፍ ዘንድ፥ ብርሃናችን ሆይ ተገጭ! መላእክት እንደ ተናገሩት ለኢትዮጵያ ምድር ምሕረትና እውነት ይኖሩ ዘንድ ተመለሽ! ሱላማጢስ ሆይ፥ ተመለሽ! ተመለሽ! እናይሽ ዘንድ ተመለሽ! እንበላት፤ ሰላማችን ሆይ ተመለሽ!
ወስብሐት ለእግዚአብሔር!
"ሱላማጢስ ሆይ ተመለሽሽ ተመለሽ" (መሓ.፯፥፩)
ክፍል አምስት (የመጨረሻ ክፍል)
‹‹ወጎየ እግዚእ ኢየሱስ ውስተ ደብረ ሊባኖስ ወውስተ ምድረ ግብጽ ወብሔረ አግዓዚ ምስለ ማርያም እሙ፤ ጌታችን ከእናቱ ማርያም ጋር ወደ ሊባኖስ ተራራ ወደ ግብጽና ወደ ኢትዮጵያ መልአኩ እንደነገረው ሳያመነታ ተሰደደ፡፡›› (ትርጓሜ ማቴ. ፪፥፲፫)
እመቤታችን ወደ ኢትዮጵያም ጭምር እንደ ተሰደደች፣ በኢትዮጵያ ውስጥም በተለያዩ ስፍራዎች እንደ ተመላለሰች፣ ሀገራችንንም፣ ሕዝባችንንም እንደ ባረከች፣ ተወዳጅ ልጇ ስለ ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን ብዙ እንደ ነገራት፣ በቃል ኪዳኗ እንድትጠብቃቸው፣ በምልጃዋ እንድታስምራቸው፣ ዐሥራት አድርጎ እንደ ሰጣት፣ በዚህም የእመቤታችንና የኢትዮጵያውያን ጥልቅ ፍቅር የጸና መሆኑን ሊቃውንትም መዛግብትም ያስረዳሉ፡፡ (ድርሳነ ዑራኤል መቅድም)
ይህን የሚያረጋግጥልን ‹‹ወጎየ እግዚእ ኢየሱስ ውስተ ደብረ ሊባኖስ ወውስተ ምድረ ግብጽ ወብሔረ አግዓዚ ምስለ ማርያም እሙ፤ ጌታ ከእናቱ ከማርያም ጋር ወደ ሊባኖስ ተራራ ወደ ግብጽና ወደ ኢትዮጵያ መልአኩ እንደ ነገረው ሳያመነታ ተሰደደ›› የሚለው ነው፡፡ (ትርጓሜ ማቴ. ፪፥፲፫)
መምህራነ ቤተ ክርስቲያንም ዕንባቆም ‹‹የኢትዮጵያ ድንኳኖች ሲጨነቁ አየሁ የምድያም አገር መጋረጃዎች ተንቀጠቀጡ›› ሲል የተናገረውን ጌታችን እና ከእናቱ ወደ ኢትዮጵያ መሰደድ ጋር አገናኝተው ይተረጉሙታል፡፡ (ዕንባ. ፫፥፮)
የዳክርስ ክፋቱ እስከ መስቀልም አብሮት ዘልቆ በግራው በተሰቀለ ጊዜ ፀሐይ ስትጨልም፣ ጨረቃ ደም ስትለብስ፣ ከዋክብት ሲረግፉ፣ መቃብራት ሲከፈቱ፣ ሙታን ሲነሡ፣ ተአምራቱን አይቶ እንኳን አላመነም፡፡ ይልቁንም ‹‹አንተስ ክርስቶስ አይደለህምን ራስህንም አድን፤ እኛንም አድን›› እያለ ይሰድበው ነበር፡፡ (ሉቃ.፳፫፥፴፱) የጥጦስ ግን ወሮታው እንዳይቀርበት ጌታን የታቀፈበትን ልብሱን ቢያጥበው ከወዙ ፫፻ ወቄት የሚያወጣ ሽቱ አግኝቷል፡፡ ጌታን ማርያም እንተ ዕፍረት በ፫፻ ወቄት ገዝታ የቀባችውና ይሁዳ ‹‹ይህስ ተሸጦ ለድሆች ይሆን ነበር›› ብሎ ያንገራጎረበት ሽቱ ይህ ነው፡፡ (ዮሐ.፲፪፥፫ እና ማቴ.፳፮፥፮)
ምክንያተ ስደት፡- በቤተ ልሔም ሲወለድ አጋንንትን በእሳት ፍላጻ የነደፋቸውን፣ አሳዳጆቹን እንደ ፈርዖንና ሠራዊቱ የውኃ ሽታ ሊያድረጋቸው የሚቻለውን፥ ሁሉ በእጁ የሆነ ልጇን ይዛ ስለምን እመቤታችን በረሃ ለበረሃ ተንከራተተች? ግብጽስ ለምን ለስደቷ ተመረጠች?
‹‹እንዘ ኪሩቤል አፍራሲሁ ወሱራፌል ላእካኒሁ ወክነፈ ነፋስ ሠረገላሁ፤ ኪሩቤል ፈረሶቹ ሱራፌልም መልእክተኞቹ የነፋሳት ክንፎቹም ሰረገላዎቹ›› የተባለለት ጌታስ ስለምን ከናዝሬት እስከ ቁስቋም ተራራ በእግሮቹ ሄደ? (መጽሐፈ ሰዓታት)
ሀ. አንዱና ዋናው ስለምን ተሰደደ ቢሉ የቤዛነት ሥራውን የሚፈጽመው ገና በቀራንዮ ነውና ጊዜው ሳይደርስ እንዳይሞት ወደ ግብጽ ነው፡፡
ለ. ትንቢቱና ምሳሌው ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡
ትንቢቱ፡- በነቢዩ ኢሳይያስ ‹‹ወይወርድ እግዚእነ ውስተ ምድረ ግብጽ ተጽዒኖ ዲበ ደመና ቀሊል፤ እግዚአብሔር በፈጣን ደመና እየበረረ ወደ ግብጽ ይመጣል›› ተብሎ የተነገረው ትንቢት ሊፈጸም ነው፡፡ (ኢሳ.፲፱፥፩) ‹‹እምግብጽ ጸዋእክዎ ለወልድየ፤ ልጄን ከግብጽ ጠራሁት›› የሚልም አለና ‹‹ትንቢት ይቀድሞ ለነገር›› እንዲሉ አስቀድሞ ይህ ትንቢት ተነግሮ ስለነበር፣ ትንቢትን የሚያናግር ደግሞ መንፈስ ቅዱስ በመሆኑ በመንፈስ ቅዱስ አናጋሪነት የተነገረ ትንቢት ሳይፈጸም አይቀርም፤ ጌታ ደመና ቀሊል በተባለች ድንግል ማርያም ጀርባ ታዝሎ ወደ ምድረ ግብጽ ወረደ፡፡ ደመና ያላት እመቤታችንን ነው፡፡ ዝናመ ሕይወት ክርስቶስን ያዘለች እውነተኛ ደመና እርሷ ናትና፡፡ ‹‹አንቲ ዘበአማን ደመና እንተ ለነ ማየ ዝናም፤ የዝናም ውኃ የታየብሽ እውነተኛ ደመና አንቺ ነሽ›› እንዳለ ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም፡፡
ምሳሌው፡- ዮሴፍን ወንድሞቹ ‹‹ሊሾምብን ሊገዛን ነው›› ብለው በክፋት ተነሥተውበት ሸጠውት ወደ ግብጽ ወርዶ ነበር፡፡ (ዘፍ.፴፯፥፩-፳፰) ጌታም ‹‹ሊሾምብን ሊነግሥብን ነው›› የሚሉ አጋንንትና ሄሮድስ በክፋት ተነሥተው አሳድደውት ወደ ግብጽ ወርዷልና ነው፡፡
ሐ. ክህደት በግብጽ ጸንቶ ነበርና ወደ ግብጽ ተሰደደ፡፡
ክህደት ወደ ጸናበት መሄድ ልማድ ነውና፡፡ በግብጽ አምልኮ ጣዖት የተስፋፋበት ነበር፡፡ ክህደትም በሰው ልቡና የጸናበት እንደነበረ አጋንንንትም በሰው ልቡና ሠልጥነው እንደነበር እና ቁራሽ ኀብስት፣ ጽዋዕ መጠጥ ከልክለዋት እመቤታችን እንዴት እንዳዘነች ቀድመን አይተናል፡፡
መለኮት ዕጓላ ሶበ ጸምዐ ከመ ደቂቅ-------ዘይሰፍሮ በኅፍኑ ለማየ ባሕር ዕሙቅ
በከየት ወትቤ ማርያም ማዕነቅ------------አልቦ እምሰብአ ሀገር ዘየአምራ ለጽድቅ
ሶበ ሰአልክዎሙ ማየ ኢወሀቡኒ በሕቅ---------ወአህጎልኩ ለወልድየ አሳዕኖ ዘወርቅ፡፡
‹‹ጥልቅ የሆነ ባሕርን በእጁ የሚሰፍረውንና የማይመረመር መለኮት የተባለ የባሕርይ አምላክ ልጇ በተጠማ ጊዜ ከዚህች ሀገር ሰዎች ቸርነትን የሚያውቃት የለም፤ ውኃን በእጅጉ ለመንኋቸው፤ አልሰጡኝም፤ የልጄን የወርቅ ጫማውን አስጠፋሁ እያለች ዋኖስ ማርያም አለቀሰች፤›› (ሰቆቃወ ድንግል) በዚህም ወደ ግብጽ በመሰደዳቸው ጣዖታትን አፈራርሷል፤ አጋንንትን ከግብጽ ከሰው ልቡና አሰድዷል፡፡ ‹‹…በዚያች ሀገር ያሉ ጣዖታትም ወድቀው ተሰባበሩ፤ አማልክቱን የሚያመልኩትም ሁሉ ፈሩ፡፡ ወደ ቤታቸውም ገብተው ተደበቁ፤ ….ብዙ ሰዎችም አመኑ፤ የሀገር ሽማግሌዎቹም ጣዖት የሚያመልኩትን ለምን ተሰወራችሁ? አማልክቶቻችሁንስ ለምን ተዋችሁ? አሏቸው፡፡ ይህች ሴት ከልጇ ጋር በገባች ጊዜ ጣዖታቱ ተሰበሩ፤ የአማልክቶቻችን ቤቶችም ወደቁ፤ ሌሊት ሠርተናቸው ሲነጋ ተሰባብረው እናገኛቸዋለን አሉ›› ትላለች እመቤታችን፡፡ (ድርሳነ ማርያም ገጽ ፪፻፰)
መ. ገዳማተ ግብጽን ለመባረክ ወደ ግብጽ ተሰደድዋል፡፡
በግብጽ ታላላቅና ደጋግ ገዳማት እነ ገዳመ ሲሐት፣ እነ ገዳመ አስቄጥስ አሉና ገዳማትን ለመባረክ ወደ ግብጽ ተሰድደዋል፡፡
ሠ. መልኩን አይተው የሚያምኑ አሉና ወደ ግብጽ ተሰደደ፡፡
‹‹ወተበሀላ አዋልደ ሲሐት፤ ንዑ ንርአዮ ለወልደ መንክራት፤ የሲሐት ልጅ ተባለ፤ የወልድን ተአምር ኑ እዮ›› እንዲል፤ (ትርጓሜ ማቴ.፪፥፲፭)
ረ. ሃይማኖት ከሁሉ ቢጠፋ ከግብጽ አይጠፋም ሲል ወደ ግብጽ ተሰደዋል፡፡ እስከ ዕለተ ምጽአት ወልድ ዋሕድ ስትል ትኖራለችና፡፡
ሰ. የበደለ አዳም ከገነት ተሰዶ ነበርና ያልበደለ ክርስቶስ ስለ አዳም ካሣ ሊሆን ወደ ግብጽ ተሰደደ፡፡
ሸ. ለሰማዕታት ስደትን ለመባረክ ተሰደደ/ተሰደደች፡፡ እመቤታችን ‹‹ሰማዕት ዘእንበለ ደም ናት፤ ሰማዕት ያለ ደም መፍሰስ›› ሰማዕትነት በእሳቱ መበላት፣ በስለቱ መወጋት ብቻ አይደለም፡፡ ስደቱ፣ ረኃቡ፣ ጥሙ፣ እርዛቱ፣ እንግልቱ ሁሉ ሰማዕትነት ነውና ለሰማዕታት ስደትን ልትባርክላቸው/ሊባርክላቸው ተሰደደች/ተሰደደ፡፡ ‹‹ወሶበ ይሰድዱክሙ እምዛቲ ሀገር ጒዩ ኀበ ካልእታ፤ …በአንዲቱ ከተማም መከራ ቢያሳዩአችሁ ወደ ሌላይቱ ሽሹ ..›› እንዳለ ጌታ በወንጌል፡፡ (ማቴ.፲፥፳፫) በዚህም ብዙ ሰማዕታት ክብር አግኝተዋል፤ እመቤታችንና አብረዋት የነበሩት ዮሴፍና ሰሎሜ ሰማዕት ዘእንበለ ደም መሆናቸው ብቻ አይደለም፡፡ ሰማዕት በደም የሆነው ጊጋር መስፍነ ሶርያንም እናገኛለን፡፡
መልአከ እግዚአብሔር ለዮሴፍ ‹‹እናቱንና ሕፃኑን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሽ፤ ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይሻዋልና›› ባለው ጊዜ በስደታቸው መጀመሪያ መሽቶባቸው ያደሩት ከጊጋር መስፍነ ሶርያ እንደ ነበር እንረዳለን፡፡ (ማቴ.፪፥፲፫) ገሥግሰው የደረሱ የሄሮድስ ሠራዊት ግን ጊጋርን በሰይፍ ቀልተው ገድለውታልና፡፡ የሐዲስ ኪዳን የመጀመሪያው ሰማዕት ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በኢትዮጵያ የቅኔ ጉባኤ ቤቶች በትልቁ ከሚተረኩ ታሪኮችና ብዙ የቅኔ ተማሪዎች ቅኔ ከሚቆጥሩበት አንዱ ጊጋር ሰማዕት ነው፡፡
የተወዳጆችሁ የእግዚአብሔር ቤተ ሰቦች! መቼም የስደቷን ታሪክ ተርከን አንዘልቀውምና ከዚህ በላይ ልንጓዝበት አንችልም፡፡ ይሁን እንጂ የእመቤታችንን ስደትና የኢትዮጵያን ግንኙነት ሳይዳስሱ ማለፍ አይቻልም፡፡ ቸር ብንሰነብት፣ የእመቤታችን ከስደት መመለስ ከኢትዮጵያ ጋር አገናኝተን ክፍል አምስትና የመጨረሻውን ክፍል ይዘንላችሁ እንቀርባለን፡፡
ይቆየን!
‹‹ሱላማጢስ ሆይ፥ ተመለሽ፥ ተመለሽ›› (መሓ.፯፥፩)
ክፍል አራት
ውድ አንባብያን! እንደምን ሰነበታችሁ? ከዚህ በፊት የእመቤታችንን የስደቷን ነገር አንሥተን ‹‹ሱላማጢስ ሆይ፥ ተመለሽ፥ ተመለሽ›› በሚል ርእስ ከክፍል አንድ እስከ ሦስት አድርሰናችሁ ነበር፡፡ ጥሩ ትምህርት እንዳገኛችሁበት ተስፋ እናደርጋለን፡፡
የዛሬው ትኩረታችን ያን ሁሉ መከራ የተቀበለችበት የስደቷን ምክንያትና ዓላማ መዳሰስ ነው፡፡ ከዚያ በፊት ግን ስለ ግብጻዊው ወንበዴ ማለትም በጌታ ቀኝና በግራ ስለተሰቀለው ፈያታዊ ዘየማን ትንሽ ታሪክ እንጨምርና ወደ ዋናው ሐሳባችን እንገባለን፡፡
ጥጦስና ዳክርስ የተባሉት ሁለት ወንበዴዎች እመቤታችንን በመንገድ አግኝተው እንደዘረፏት፣ በኋላ ጥጦስ አዝኖላት ንብረታቸውን እንደመለሰና ጌታን አቅፎ እንደሸኘ በክፍል ሦስት ቀንጨብ አድርገን አቅረበንላችሁ ነበር፡፡ ይህ ፈያታዊ ዘየማን ጥጦስ ጌታን አቅፎት ሲሸኛቸው ሳለ ሰይፉ ከእጁ ወድቃ ተሰበረችበትና በጣም አዘነ፡፡ ጌታም ‹‹ኦ ጥጦስ አስተጋብእ ስባራተ ሰይፍከ፤ ጥጦስ ሆይ፥ የሰይፍህን ስባሪ ወደ ሰገባው ክተተው›› አለው፡፡ ሰብስቦ ቢያቀርብለት እንደ ነበረ አድርጎ ሰጠው፡፡ ጥጦስም ደስ ብሎት ‹‹ዝንቱ ሕፃን እምደቂቀ ነቢያት፤ ይህ ሕፃን ከነቢያት ልጆች አንዱ ነው›› አለ፤ ዳክርስ ግን ‹‹እውነትም ከነቢያት ወገን ቢሆን አይደል አንተን ቀማኛውን ገነት ትገባለህ ማለቱ!›› ብሎ ዘበተበት፡፡
ጥንተ ስቅለቱ ለመድኃኔዓለምን ምክንያት በማድረግ የሚከበረው የመድኃኒዓለም በዓል
እንኳን አደረሳችሁ አደረሰን መልካም መልካም በዓል ይሁንልን ።
ጥንተ ስቅለቱ ለመድኃኔዓለም
እንኳን አደረሳችሁ አደረሰን መልካም ዓውደ ዓመት ይሁንልን ።
✞አባ ጽጌ ድንግል✞
አባ ጽጌ ድንግል ፍቅርሽ አገብሮት
ምስጋናን አበዛ በስደትሽ ሰዓት
በተመስጦ ሆኖ ለአንቺ እየዘመረ
ምድርን ለቆ ሄደ ከፍ ከፍ እያለ
ይወድሻል ከልቡናው
አቤት ሲያዜም ስንሰማው
ማህሌትሽ ሲወረብ
ትመጫለሽ ከመ ርግብ
አዝ= = =
ስዕልሽን ታቅፈውት
በማዕጠንት ውስጥ ሲያዩት
ትታያለሽ እመ ብርሀን
ስትባርኪን በብርሃን
አዝ= = =
ካህናቱ ነጭ ለብሰው
ፅጌረዳ ሁሉም ይዘው
ሲወረቡ በሽብሸባ
አቤት ሲያምር ልቤ ገባ
አዝ= = =
የብርሃንሽ ፀዳል በዝቶ
በምስጋናሽ ሁሉ ፈክቶ
ሌሊቱ አጥሮ ነጋብን
ማርያም እያልን ስላደርን
መልአከ ሰላም
ቀሲስ እንግዳወርቅ በቀለ
"ደስ ይበልሽ÷ ጸጋን የተመላሽ ሆይ÷ እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ነው፤ ከሴቶች መካከል አንቺ የተባረክሽ ነሽ"
ሉቃ ፩፥፳፰-፳፱
ቀጸላ መንግሥቱ ለጊዮርጊስ
(ዲ/ን ሕሊና በለጠ)
በማኅሌተ ጽጌ
"አክሊለ ጽጌ ማርያም
ቀጸላ መንግሥቱ ለጊዮርጊስ
ክበበ ጌራ ወርቅ" እያልን እንዘምራለን። ግን ለምን እንዲህ እንላለን?
በቅድሚያ ሙሉ የማኅሌተ ጽጌ ድርሰቱን ከነ ትርጉሙ ላስቀምጥ:-
"ክበበ-ጌራ-ወርቅ ጽሩይ እምዕንቈ ባሕርይ ዘየኀቱ፣
ዘተጽሕፈ ብኪ ትእምርተ ስሙ ወተዝካረ ሞቱ፣
አክሊለ ጽጌ ማርያም ለጊዮርጊስ ቀጸላ መንግሥቱ፣
አንቲ ኲሎ ታሰግዲ ሎቱ፣
ወለኪኒ ይሰግድ ውእቱ።"
#ትርጉም:-
"ባሕርይ ከሚባል ከሚያበራ ዕንቁ ይልቅ የጠራ የወርቅ ጌጥ የኾንሽለት፣
(የጊዮርጊስ) የስሙ ምልክትና የሞቱ መታሰቢያ የተጻፈብሽ፣
ለጊዮርጊስ የመንግሥቱ ዘውድ የሆንሽ የአበባ አክሊል ማርያም ሆይ፣
አንቺ ለእርሱ ኹሉን ታሰግጂለታለሽ፣
እርሱ ግን ላንቺ ይሰግዳል።"
ቅዱስ ጊዮርጊስ የ7 ዓመታት ተጋድሎውን የጀመረው በ20 ዓመቱ ነበር። ለሰባት ዓመታት ያክል እየሞተ እየተነሣ ተጋድሎውን ፈጽሞ በ27 ዓመቱ፣ በሚያዝያ 23፣ በ304 ዓ.ም. ዐረፈ። እስከዚያው ጌታችን ቃል እንደ ገባለት 3 ጊዜ ሞቶ 3 ጊዜ ተነሥቷል። በዐራተኛው ሞቱ ፈጽሞ ዐረፈ። ያረፈውም በዕለተ ዓርብ በ9 ሰዓት ነበር።
ቅዱስ ጊዮርጊስ 4 ጊዜ መሞቱን "ማርያም" ከሚለው ባለ 4 ፊደል ቃል ጋር ያመሣጠረው ደራሲው "ዘተጽሕፈ ብኪ ትእምርተ ስሙ ወተዝካረ ሞቱ - የስሙ ምልክትና የሞቱ መታሰቢያ የተጻፈብሽ" ሲል እመቤታችንን በማኅሌተ ጽጌ አመሰገናት።
ቅዱስ ጊዮርጊስን ያንገላታ የነበረው ንጉሥ ዱድያኖስ ንግሥት እለስክንድርያ የምትባል ሚስት ነበረችው። መሳፍንቱና መኳንንቱ ኹሉ ለእርሷ ይሰግዱ ነበር። በሰማዕቱ ትምህርት አምና ለቅዱስ ጊዮርጊስ የፀጋ ስግደትን ሰገደችለት። በዚህም ምክንያት በሚያዝያ 15 አንገቷን በሰይፍ እንድትቆረጥ ተደርጋለች።
ያቺ ሣር ቅጠሉ ኹሉ ይሰግድላት የነበረች ንግሥት ለቅዱስ ጊዮርጊስ መስገዷን ያስተዋለው ሊቁ ግን በማኅሌተ ጽጌው "አንቲ ኲሎ ታሰግዲ ሎቱ - አንቺ ለእርሱ ኹሉን ታሰግጂለታለሽ" ሲል በእመቤታችንና በሰማዕቱ ምስጋና ላይ ዘከራት። ቅዱስ ጊዮርጊስ ፍጥረት ኹሉ "ብፅዕት" ለሚላት ለድንግል እንደሚሰግድም "ወለኪኒ ይሰግድ ውእቱ - እርሱ ግን ላንቺ ይሰግዳል" ሲል ገልጾአል።
"የደናግል መመኪያ፣ የሰማዕታት አክሊል፣ ..." የምትባለው እመቤታችን: ቀደም ሲል ባነሣናቸው ምክንያቶች የተነሣ: ይልቁንስ ለሊቀ ሰማዕታት ለቅዱስ ጊዮርጊስ የከበረች አክሊሉና ዘውዱ መኾኗን ሲገልጽም "ክበበ-ጌራ-ወርቅ ጽሩይ እምዕንቈ ባሕርይ ዘየኀቱ... አክሊለ ጽጌ ማርያም ለጊዮርጊስ ቀጸላ መንግሥቱ - ባሕርይ ከሚባል ከሚያበራ ዕንቁ ይልቅ የጠራ የወርቅ ጌጥ የኾንሽለት... ለጊዮርጊስ የመንግሥቱ ዘውድ የሆንሽ የአበባ አክሊል ማርያም ሆይ" ብሏል።
እኛም እንደ አባ ጽጌ ድንግልና እንደ አባቶቻችን በማኅሌተ ጽጌ "ቀጸላ መንግሥቱ ለጊዮርጊስ" እያልን እመቤታችንንና ሰማዕቱን እንዘክራለን።
ዘመነ ጽጌ፣ 2013 ዓ.ም.
እንኳን ለ፳፻፲፮ ዘመነ ጽጌ አደረሳችሁ።
ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፮ በሚቆየው ወርኃ ጽጌ ከእመቤታችን ከቅድስት ከድንግል ማርያም ስደት ረድኤትና በረከት ልጅዋ ወዳጅዋ ይክፍለን።
ሰላሙን ይዘዝልን ሰደተኞችን ያረጋጋልን የሞቱትንም ይማርልን በሕይወትም በችግር ያሉትን ያሳርፍልን።
༒ ሥርዓተ ማኅሌት ዘወርኃ ጽጌ
በቅድስት ቤተክርስቲያናችን የ፳፻፲፮ ዓ.ም
የመስከረም ፳፯ የመጀመሪያው ሰንበት የጽጌ ማኅሌት
፩. ነግሥ
ሰላም ለኵልያቲክሙ እለ ዕሩያን በአካል፤
ዓለመክሙ ሥላሴ አመ ሐወፀ ለሣህል፤
እምኔክሙ አሐዱ እግዚአብሔር ቃል፤
ተፈጸመ ተስፋ አበው በማርያም ድንግል፤
ወበቀራንዮ ተተክለ መድኃኒት መስቀል ፡፡
ዚቅ፦
ሃሌ ሉያ ትወጽእ በትር እምሥርወ ዕሴይ ፨ ወየዓርግ ጽጌ ይእቲ በትር አምሳለ ማርያም ፨ ቅድስት ይእቲ ፨ ወጽጌ ዘወጽአ እምኔሃ ፨ አምሳሉ ለወልድ ኀደረ ላዕሌሃ ፨ ቃል ሥጋ ኮነ ወተወልድ እምኔሃ፡፡
፪. ጽጌ አስተርአየ / ማኅሌተ ጽጌ /
ጽጌ አስተርአየ ሠሪፆ እምዐፅሙ፤
ለዘአማኃኪ ጽጌ ለገብርኤል ምስለ ሰላሙ፤
ወበእንተዝ ማርያም ሶበ ሐወዘኒ መዓዛ ጣዕሙ፤
ለተአምርኪ አኀሊ እሙ ማኅሌተ ጽጌ ዘይሰመይ ስሙ።
ወረብ፦
መዓዛ ጣዕሙ ለተአምርኪ ሶበ ሶበ ሐወዘኒ /፪/
ወበእንተዝ ማርያም አሐሊ ለተአምርኪ /፪/
ዚቅ፦
ሃሌ ሉያ ሃሌ ሃሌ ሉያ ፨ ናሁ አስተርአየ ጽጌ ፨ መርዓቱኒ ትቤ ወልድ እኁየ ይምዕዝ ከርቤ ፨ ናሁ አስተርአየ ጽጌ ፨ዕንባቆም ነቢይ ግብረ ምግባሩ ለወልድ አንከርኩ ይቤ ፨ ናሁ አስተርአየ ጽጌ ፨ ንጉሠ ሰላም ክርስቶስ፨ ዓቢይ ልዕልናከ ወመንክር ፨ ስብሐቲከ ለዕረፍት ሰንበተ ሠራዕከ።
፫. ከመ ይትፌሣሕ መርዓዊ / ማኅሌተ ጽጌ /
ከመ ይትፌሳሕ መርዓዊ ውስተ ገነቱ ዘወረደ፤
ጽጌያተ ይርአይ በጊዜ ፈቀደ፤
በተአምርኪ ድንግል እትፌሣሕ ፈድፋደ፤
ዘያቀልል እምኃጥአን ፆረ ክቡደ፤
እስመ እምኔኪ ፍስሐ ተወልደ።
ወረብ፦
ዘያቀልል እምኃጥአን ፆረ ኃዘን፤
እስመ እምኔኪ ፍስሐ ተወልደ ፍስሐ ተወልደ ፍስሐ ተወልደ እምኔኪ ።
ዚቅ፦
ከመ ፍስሖ ቀይሕ ከናፍርኪ ፨ ቡርክት አንቲ እምአንስት ፨ መንፈስ ቅዱስ ኀደረ ላዕሌኪ ፨እሞሙ ይእቲ ለሰማዕት ፨ ወእኅቶሙ ለመላእክት ፨ መንፈስ ቅዱስ ኀደረ ላዕሌኪ ፨ ወተወልደ ፍስሐ እምኔኪ።
፬. እንዘ ተሐቅፊዮ / ማኅሌተ ጽጌ /
እንዘ ተሐቅፊዮ ለሕጻንኪ ጽጌ ፀዓዳ ወቀይሕ፤
አመ ቤተ መቅደስ ቦእኪ በዕለተ ተአምር ወንጽሕ፤
ንዒ ርግብየ ትናዝዝኒ እምላሕ፤
ወንዒ ሠናይትየ ምስለ ገብርኤል ፍሡሕ፤
ወሚካኤል ከማኪ ርኅሩሕ፡፡
ወረብ፦
እንዘ ተሐቅፊዮ ለሕጻንኪ ጽጌ ጸዓዳ ወቀይሕ፤
አመ ቤተ መቅደስ ቦእኪ ሠናይትየ በዕለተ ተአምር ወንጽሕ።
ዚቅ፦
በሰላም ንዒ ማርያም፨ ትናዝዝኒ ኃዘነ ልብየ፨ በሰላም ንዒ ማርያም ፨ ምስለ ሚካኤል ወገብርኤል ፨ በሰላም ንዒ ማርያም ፨ ምስለ ሱራፌል ወኪሩቤል ፨ በሰላም ንዒ ማርያም ፨ ምስለ ኲሎሙ ቅዱሳን ፨ በሰላም ንዒ ማርያም ፨ ምስለ ወልድኪ አማኑኤል ፨ በሰላም ንዒ ማርያም ፨ ለናዝዞ ኩሉ ዓለም ።
፭ ክበበ ጌራ ወርቅ / ማኅሌተ ጽጌ /
ክበበ ጌራ ወርቅ ጽሩይ እምዕንቈ ባሕርይ ዘየኃቱ፤
ዘተጽሕፈ ብኪ ትእምርተ ስሙ ወተዝካረ ሞቱ፤
አክሊለ ጽጌ ማርያም ለጊዮርጊስ ቀጸላ መንግሥቱ፤
አንቲ ኵሎ ታሰግዲ ሎቱ፤
ወለኪኒ ይሰግድ ውእቱ፡፡
ወረብ፦
ክበበ ጌራ ወርቅ ጽሩይ ክበበ ጌራ ወርቅ ጽሩይ እምዕንቈ ባሕርይ/፪/
አክሊለ ጽጌ ማርያም ቀጸላ መንግሥቱ/፪/
ዚቅ፦
አክሊል ዘእምጳዝዮን ተደለወ ፨ ጌራ ባሕርይ ወቀጸላ ወርቅ ጽሩይ ፨ በቤተልሔም ተወልደ እምድንግል ብሥራትክሙ መሃይምናን ፨ እምአፈ ዮሐንስ ሥርግው ተቀሰመ አፈው ፨ ሰባኬ ወንጌል ነዋ በማዕከለ አኃው ።
፮. አይቴ ሀሎ / ሰቆቃወ ድንግል /
አይቴ ሀሎ ንጉሰ እስራኤል ዘተወልደ፤
ከመ ነሀብ ሎቱ አምኃ ወሰጊደ፤
እንዘ ይብሉ ሰብአ ሰገል ሰሚዖ ገሃደ፤
ሄሮድስ አሜሃ በእሳተ ቅንአት ነደ፤
ከመ ይቅትሉ ሕፃናተ ወኢያትርፉ አሐደ፤
እስከ ቤተልሔም እምገሊላ ሐራሁ አዖደ።
ወረብ፦
አይቴ ሀሎ ንጉሰ እስራኤል ዘተወልደ ንጉሰ እስራኤል፤
እንዘ ይብሉ ሰብአ ሰገል ሰሚዖ ገሃደ አሜሃ ሄሮድስ በእሳተ ቅንአት ነደ ።
ዚቅ፦
እምብሔረ ጽባሕ አምጽኡ ወርቀ ወጋዳ ፨ ለንጉሥነ ለወልደ ማርያም ፨ኮከብ ኮነ ሐዋርያ ወዜነዎሙ ፍስሐ።
++++++++++ ༒ መዝሙር ༒ ++++++++++
ሃሌ ሉያ ሃሌ ሉያ ሃሌ ሃሌ ሉያ ትወጽእ በትር እምሥርወ እሴይ ወየዓርግ ጽጌ፥ ይእቲ በትር አምሳለ ማርያም ቅድስት ይእቲ ጽጌ ዘወጽአ እምኔሃ አምሳሉ ለወልድ፥ ኀደረ ላዕሌሃ ቃል ሥጋ ኮነ፥ ወተወልደ እምኔሃ።
+++++ ༒ ሰላም ༒ +++++
ናሁ አስተርአየ ጽጌ ፨ መርዓቱኒ ትቤ ወልድ እኁየ ይምዕዝ ከርቤ ፨ ናሁ አስተርአየ ጽጌ ፨ ዕንባቆም ነቢይ ግብረ ምግባሩ ለወልድ አንከርኩ ይቤ ፨ ናሁ አስተርአየ ጽጌ ፨ ንጉሠ ሰላም ክርስቶስ ፨ ዓቢይ ልዕልናከ ወመንክር ስብሐቲከ፨ ለዕረፍት ሰንበተ ሠራዕከ።
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም
ምልጃዋ የልጅዋም ቸርነት አይለየን!!!
ይቆየን !!!
ታላቁ አባት የጸሎት ሰው እና የፈውስ ሀብት የነበራቸው ብፁዕ አቡነ ሰላማ ከዚህ ዓለም ድካም አረፉ።
አረጋዊው አባት ብፁዕ አቡነ ሰላማ ባደረባቸው ህመም ምክንያት በአዲስ አበባ ሃሌሉያ ሆስፒታል በህክምና ሲረዱ ቆይተው ዛሬ መስከረም 18 ቀን 2016 ዓ.ም ከዚህ ዓለም ድካም አርፈዋል።
የብፁዕነታቸውን ሽኝት መርሐ ግብር በተመለከተ በቋሚ ሲኖዶስ እንደተወሰነ ዝርዝሩን የምናሳውቅ ይሆናል።
የብፁዕነታቸው ቡረከት ይደርብን
ለኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ልጆች👇
•➢ ሼር // SHARE
✞ እሰይ እልል በሉ ✞
እሰይ እልል በሉ
ተገኘ መስቀሉ ✞ (፪)
የጥል ግድግዳ - አበባ -የፈረሰበት -አበባ
ሰው ከእግዚአብሔር ጋር -አበባ -የታረቀበት -አበባ
የእግዚአብሔር ልጅ - አበባ -የነገሰበት -አበባ
የሞት አበጋዝ - አበባ -የወደቀበት- አበባ
አዝ = = = = = =
አይሁድ በቅናት -አበባ -መስቀሉን ቀብረው - አበባ
ቢከድኑት እንኳን - አበባ -በቆሻሻቸው - አበባ
ጌታን መቃወም - ስለማይችሉ - አበባ
ይኸው ተገኘ - አበባ -ወጣ መስቀሉ አበባ
አዝ = = = = = =
ደጉ ኪራኮስ - አበባ -ሽማግሌው -አበባ
እሌኒን መራ - አበባ - በደመራው - አበባ
ጌታ በሱ ላይ - አበባ - በመሰቀሉ - አበባ
ጢሱ ሰገደ - አበባ - ወደ መስቀሉ - አበባ
አዝ = = = = = =
የእምነት ምልክት - አበባ - መስቀል ነውና - አበባ
ተራራው ሜዳ - አበባ - ሆነ እንደገና - አበባ
እንደ ተነሳው - አበባ -ጌታ እንደቃሉ - አበባ
ከጉድጓድ ወጣ - አበባ - እፀ መስቀሉ - አበባ
አዝ = = = = = =
እኛም በመስቀል - አበባ -እንመካለን - አበባ
በእግዚአብሔር ጥበብ - አበባ -መች እናፍራለን - አበባ
ሞኝነት እንኳን - አበባ -ቢሆን ለዓለም - አበባ
ኃይል እፀ ወይን ነው - አበባ - ለዘላለም - አበባ
አዝ = = = = = =
ግድግዳው ፈርሷል -- አበባ - የልዩነቱ - አበባ
ምድርና ሰማይ - አበባ - ሆኑ እንደ ጥንቱ - አበባ
ነፍስና ስጋ - አበባ - በሱ ታርቀዋል - አበባ
ሕዝብና አሕዛብ -አበባ - ወንድም ሆነዋል - አበባ
