"ልጆቼ የቤተክርስቲያንን ነገር አደራ"
Open in Telegram
1 134
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-2330 days
Posts Archive
#ሰው_እንደ_ዘር_ነው
አባቶቻችን ሊቃውንት ሰው እንደ ዘር ነው ይላሉ። ሰው እንደ ዘር ነው ማለት ዘር ተዘርቶ የሚያድገው በሁለት መሠረታዊ ነገር ነው። በብርድ እና በጸሐይ። ዘር ዝናምና ጸሐይ ያስፈልገዋል። ዝናም ብቻ ከሆነ ሽባ ይሆናል ጸሐይ ብቻም ከሆነ ይደርቃል።
ሰውም እንደ ዝናሙ የእግዚአብሔር ቸርነት ያስፈልገዋል፤ እንደ ጸሐዩም መከራ ያስፈልገዋል። ዘር በዝናሙ እየለዘበ፣ በጸሐዩ እየበሰለ እንደሚያድገው ሁሉ ሰውም በመከራ እየጠነከረ በተስፋና በእግዚአብሔር ቸርነት እየተጽናና ያድጋል።
ሁልጊዜ የእግዚአብሔርን ቸርነት ብቻ ከሆነ የሚያስበው ሽባ ይሆናል። መከራ ባገኘው ጊዜ ወዲያው ተስፋ ይቆርጣል። ሃይማኖትን ሊክድ ይችላል። መከራ ብቻ ከሆነበት ደግሞ ወዲያው ደግሞ እንደዚሁ ተስፋ ቆርጦ ሊሠበር ይችላል።
ስለዚህ ዘር ዝናምና ጸሐይ እንደሚያስፈልገው ሁሉ ሰውም መከራና የእግዚአብሔር ቸርነት ያስፈልገዋል።
(#ርዕሰ_ሊቃውንት_አባ_ገብረ_ኪዳን)
#ከኃጢአት_መሸሽና_ከኃጢአት_ነጻ_መሆን
ከኃጢአት በመሸሽና ከኃጢአት ነጻ በመሆን መካከል ያለው ልዩነት ምንድር ነው?
አንድ ሰው ከኃጢአት ለመሸሽ ይሞክር ይሆናል፡፡ ይህ ማለት ግን ከዚህ ኃጢአት ነጻ ወጥቷል ማለት አይደለም ኃጢአቱን በእርግጥ ባይፈጽመውም እንኳ፡፡
ከኃጢአት መሸሽ ውጪያዊ የሆነ ድርጊት ነው። ከኃጢአት ነጻ መውጣት ግን ውስጣዊ የልብ ሁኔታ ነው፡፡
ይህ ይሁን እንጂ ከኃጢአት መሸሽ የመጀመሪያው ደረጃ ነው፤ በተለይም ለጀማሪዎች፡፡ ከኃጢአት ነጻ ለመውጣት መፈለግ ግን ወደ ጉልምስና ደረጃ በመሸጋገር ላይ ላሉት ሰዎች ነው፡፡
አንዳንድ ጊዜ ከኃጢአት መሸሽ ስሕተት ላይ ላለመውደቅ ከሚደረግ ፍርሃት የሚመጣ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ ሰውየው ገና ከውስጡ ነጻ አልወጣም ማለት ነው፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ከኃጢአት መሸሽ አንድ ሰው ኃጢአትን መቃወሙን ያመለክታል፡፡ ጻድቁ ዮሴፍ ከጌታው ሚስት ጋር ኃጢአት አልሠራም ብሎ ከኃጢአት መሸሹ ለዚህ ምሳሌ ሊሆነን ይችላል፡፡
አንዳንድ ቅዱሳን የሐሰት ክብር ባለቤት በሆነው ዲያብሎስ ተጠልፈው እንዳይወድቁ ሲሉ በትሕትና ከኃጢአት ይሸሻሉ፡፡
አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ቅዱሳን ከኃጢአት የሚሸሹት ራሳቸውን ለገንቢ መንፈሳዊ ሥራ አሳልፈው ለመስጠት ሲሹ ነው፡፡ ይህን ያድርጉ እንጂ እነርሱ በውስጣቸው እንደዚህ ካሉ ስሕተቶች ነጻ የወጡ ናቸው፡፡
(አቡነ ሽኖዳ ሣልሳዊ - የሕይወት ልምድ ገጽ 55 - በአያሌው ዘኢየሱስ የተተረጎመ)
#ሰኔ_21
#እመቤታችን_ቅድስት_ድንግል_ማርያም (ህንጸተ ቤተክርስቲያን)
ሰኔ ሃያ አንድ በዚች ዕለት የአዳምና የዘሩ ድኅነት የተደረገባት አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የታላቁ በዓል መታሰቢያና በዓለም ሁሉ የቤተ ክርስቲያን መታነፅ መታሰቢያ ነው።
ከሁሉ አስቀድሞ ያቺ ቤተ ክርስቲያን በሐዋርያት ዘመን ብቻዋን ታነፀች።
ይኸውም ጳውሎስና በርናባስ በአሕዛብ ውስጥ በሰበኩ ጊዜ ክብር ይግባውና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ ከሰዎች ቤቶች በቀር ቅዱስ ቊርባንን የሚቀበሉበት ቤተ ክርስቲያንም አልነበራቸውም ነበር። ስለዚህም ወደ ጴጥሮስና ወደ ሐዋርያት ሁሉ ስለ ቤተ ክርስቲያን መታነፅ ጉዳይ እየለመኑ መልእክትን ላኩ።
ሐዋርያትም እንዲህ ብለው መለሱላቸው ክብር ይግባውና ያለ ጌታችን ፈቃድ እኛ ምንም ምን አንሠራም። ነገር ግን የምንሠራውን እስኪያስረዳን ድረስ ወደ እግዚአብሔር እየጸለዩና እየማለዱ አንድ ሱባኤ ይጾሙ ዘንድ ወደ ሃይማኖት የተመለሱ አሕዛብን እዘዙአቸው እንዲህም አዘዙአቸው።
በሱባዔውም ፍጻሜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገለጸላቸው ሐዋርያትንም ሁሉ ከየአገሮች ሁሉ እስከ ፊልጵስዮስ በደመና ሰበሰባቸው ከእርሳቸውም ጋር ጳውሎስና በርናባስ ነበሩ ጌታችንም ባረካቸው እንዲህም ብሎ ነገራቸው "ይቺ ዕለት በእናቴ በማርያም ስም በአራቱ ማእዘነ ዓለም አብያተ ክርስቲያናት እንድታንፁ የፈቀድኩባት ናት።"
ይህንንም ብሎ ከከተማዋ በስተ ምሥራቅ በኲል አወጣቸው የቤተ ክርስቲያኒቱንም ቦታና መሠረቷን ወሰነላቸው ከእርሳቸውም ጋራ የእግዚአብሔር ኃይል ነበረ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሕንፃዋ እስከ ተፈፀመ ድረስ ደንጊያዎች በሐዋርያት እጆች ውስጥ ይለመልሙ ነበረ ጌታችንም ነዋየ ቅድሳቷን አልባሳትዋንና መሠዊያዋን አዘጋጀ።
ከዚህ በኋላ ጌታችን እጁን በጴጥሮስ ራስ ላይ ጭኖ በአራቱ ማእዘነ ዓለም ውስጥ "አርሳይሮስ" ብሎ ሾመው ይህም "ሊቀ ጳጳሳት" ማለት ነው። ለሐዋርያት አለቃ ጴጥሮስ ከጽንፍ እስከ ጽንፍ የጳጳሳት አለቃ ይሆን ዘንድ ይገባዋል ይገባዋል ይገባዋል እያሉ ሰማያውያን መላእክትና ምድራውያን ሰዎች ሦስት ጊዜ አሰምተው ተናገሩ።
ከዚህም በኋላ ጌታችን ሐዋርያትን የቊርባኑን ቅዳሴ ሥርዓት ያከናውኑ ዘንድ ለሕዝቡም ሥጋውን ደሙን ያቀብሏቸው ዘንድ አዘዛቸው እንዲህም የሚል አለ ራሱ መድኃኒታችን ቀድሶ ሥጋውንና ደሙን ለሐዋርያት አቀበላቸው። እንዲህም አላቸው በዚች ቀን የእጃቸውን ሥራ እንዳይሠሩ ሕዝቡን ሁሉ እዘዙአቸው ይኸውም በሰኔ ወር ሃያ አንድ ቀን ነው።
ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን ከእርሳቸው ዘንድ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ። ከዚያችም ቀን ጀመሮ አባቶቻችን ሐዋርያት በዓለሙ ሁሉ ውስጥ አምላክን በወለደች በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ቤተ ክርስቲያን የሚያሳንፁ ሆኑ።
በቂሣርያው ሊቀ ጳጳሳት በባስልዮስ ዘመን እንዲህ ሆነ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም ቤተ ክርስቲያን በሠራ ጊዜ በውስጡ የእመቤታችን የማርያምን ሥዕል ይሥልበት ዘንድ ሠሌዳ ፈለገ ሰዎችም በአንድ ባለጸጋ ዘንድ ስለ አለ አንድ መልካም ሠሌዳ ነገሩት።
ቅዱስ ባስልዮስም ሠሌዳውን እንዲሰጠው ወደ ባለጸጋው ላከ ባለጸጋውም ይህ ሠሌዳ ለልጆቼ ነው አለ እንጂ ፈቃደኛ አልሆነም። ከዚያም አልፎ በመድፈር በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ላይ የስድብ ቃል ተናገረ ወዲያውኑም በድንገት ወድቆ ሞተ ልጆቹም ፈሩ ያንንም ሠሌዳ ከብዙ ወርቅና እንቊ ጋራ ወደ ቅዱስ ባስልዮስ አምጥተው የአባታቸውን በደል ያቃልልለት ዘንድ ለመኑት።
ቅዱስ ባስልዮስም ያንን ሠሌዳ ወስዶ የእመቤታችንን ሥዕል ይሥልበት ዘንድ ለሠዓሊ ሰጠው። እመቤታችንም ቅድስት ድንግል ማርያም በሌሊት ራእይ ለቅዱስ ባስልዮስ ተገለጸችለት ሥዕሏንም በዚያ ሠሌዳ ላይ እንዳይሥል ከለከለችው። ከዐመፀኛ ሰው እጅ ወስዶታልና። እጅግም ያማረ የእመቤታችን ሥዕሏ የተሣለበት የሁለት ደናግልም ሥዕል ያንዲቱ በቀኝ ያንዲቱ በግራ ሆኖ የተሣለበት ቀይ ሠሌዳ ያለበትን ቦታ ነገረችው።
ቅዱስ ባስልዮስም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ወደ አመለከተችው ወደዚያ ቦታ ሔደ ያንንም ሠሌዳ አገኘው ወደዚያች ቤተ ክርስቲያንም በታላቅ ደስታ አመጣው።
ከዚህም በኋላ ዳግመኛ በአንድ ጣዖት ቤት ሁለት ምሰሶዎች እንዳሉ አስረዳቸው እነርሱንም አምጥቶ በመቅደሱ ፊት ለፊት እንዲአቆማቸው በላያቸውም ሥዕሏን እንዲያኖር አዘዘችው።
ቅዱስ ባስልዮስም እነዚያን ምሰሶዎች ያመጣቸው ዘንድ ሔደ መሠርያኑም ሊከለክሉት ፈለጉ ጌታችንም ኃይላቸውን ደመሰሰ እነዚያንም ምሰሶዎች አምጥቶ በቤተ መቅደሱ ፊት ለፊት አቆማቸው በላያቸውም የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሥዕሏን አስቀመጠ እግዚአብሔርም ከእነዚያ ምሰሶዎች በታች የውኃ ምንጭ አፈለቀ በውስጥዋም የሚታጠብ ሁሉ ከአለበት ደዌ ሁሉ የሚድን ሆነ።
እንዲሁም ከእመቤታችን ማርያም ሥዕል በሽተኞችን ሁሉ የሚፈውስ የዘይት ቅባት ፈሰሰ ይህ ሁሉ የሆነ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን በከበረችበት በሰኔ ወር በሃያ አንድ ቀን ነው።
በዚያችም ቀን እንዲህ ሆነ አንዲት ሴት መጥታ ታጠበች ወዲያውኑም ሁለመናዋ በለምጽ ተሸፈነ ቅዱስ ባስልዮስም ወደርሱ አስቀርቦ በእርሷ ላይ የሆነውን ጠየቃት እርሷም የእኅቷን ባል እንደወደደችና እኅቷን በመርዝ ገድላ እንዳገባችው ነገረችው። ቅዱስ ባስልዮስም ታላላቅ ሦስት ኃጢአቶችን ሠራሽ ግን ወደ እግዚአብሔር ንስሐ ግቢ ምንአልባት በደልሽን ይቅር ይልሽ እንደ ሆነ አላት በዚያን ጊዜም ምድር ተሠንጥቃ እንደ ዳታን ዋጠቻት እርሷ የረከሰች ስትሆን ወደ ቤተ ክርስቲያን መግባትን ደፍራለችና።
እኛ ሁላችን የክርስቲያን ወገኖች አምላክን ለወለደች ለእመቤታችን ለከበረች ድንግል ማርያም ለመታሰቢያዋ መንፈሳዊ በዓልን ልናደርግ ይገባናል ሰለ እርሷ ለአዳምና ለሁላችን ለልጆቹ ድኅነት ሆኖአልና ይህንንም በዓል ለማድረግ የሚተጋ የተመሰገነ ነው።
እርሷን ለመረጣትና ለወደዳት በሥጋም እንድትወልደው ላደረግ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በእርሷ በእመቤታችን ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን ።
(#ስንክሳር_ዘወርኀ_ሰኔ ➛
እችላለሁ ካልህ ትችላለህ!?
ክርስቲያን "ሁሉን እችላለሁ" ይላል ወይ? አዎ ይላል:: ግን ከፊቱ የሚቀር ሐረግ አለ::
"ኃይልን በሚሠጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ" (ፊል. 4:13)
በራስ መተማመንም እግዚአብሔርን ከለላ በማድረግ ብቻ ነው:: "በፍጹም ልብህ በእግዚአብሔር ታመን በራስህም ማስተዋል አትደገፍ" ምሳ. 3:5
ስለዚህ በእግዚአብሔር መታመን በራስ ከመታመን በላይ ነው:: Confidence ከሚለው ይልቅ Godfidence የሚል አዲስ ቃል ሳይገልጸው አይቀርም::
የተፈጥሮ ጸጋህን እወቅ በሚል በጎ መነሻ የተጀመረው "ነኝ ካልኩ ነኝ" የሚለው መፈክር አሁን ላይ ምድርን እየበጠበጠ ይገኛል:: ሰዎች "ውብ ነኝ ጎበዝ ነኝ ፤ ደፋር ነኝ" ብለው ራሳቸውን በኃይል እንዲሞሉና አቅማቸውን እንዲረዱ ማድረጉ ባልከፋ ነበር:: መጽሐፍ ቅዱስ ላይም "ጥቁር ነኝ ግን ውብ ነኝ" "ድሆች ስንሆን ሌሎችን ባለጸጎች እናደርጋለን" "እንገፋለን እንጂ አንወድቅም" "እንጨነቃለን እንጂ ተስፋ አንቆርጥም" የሚሉ ሰው ከድካሙ ውስጥ ኃይሉን እንዲያይ የሚያደርጉ በጎ ቃላት አሉ::
"ውብ ነኝ ፤ ደፋር ነኝ ፤ጀግና ነኝ" የሚለው ግን ገደብ አልፎ ወንዱ "ሴት ነኝ" ሴትዋ "ወንድ ነኝ" እስከማለት ደረሰ:: I identify as a woman የሚሉ ጎረምሶች I identify as a man የሚሉ ልጃገረዶች ተነሡ:: አልፎ ተርፎ ትዳር ለምኔ ብለው የሰው ልጅ ሕልውናን የሚያስቀጥለውን የቤተሰብ ተቋም ገደል ሊከቱ መሮጥ ጀመሩ:: ሕፃናትን ስለዝሙት ጥበብ የሚያስተምሩ ጾታቸውን እያጠራጠሩ የሚያወዛግቡ ግፈኞችም በዙ:: ውስጥህን አታምቀው ነኝ ካልክ ነህ ተብለው ብዙዎች ነኝ ያሉትን ለመሆን በቀዶ ህክምና ፍዳቸውን እያዩ ነው:: Youtube ዕድሜ አይሠጠውም እንጂ በጉዳዩ ላይ የተሠሩ ዘጋቢ ፊልሞች እጅግ ልብ ይሠብራሉ::
አልበርት አንስታይን "ሰው የሚችለውን ነገር ከማወቅ በላይ የማይችለውን ማወቁ ይጠቅመዋል" ብሎ ነበር
ፍጡር እንደመሆናችን አደርጋለሁ ያልነውን ሁሉ ላናደርግ እንችላለን::
"ዛሬ ወይም ነገ ወደዚህ ከተማ እንሄዳለን በዚያም ዓመት እንኖራለን እንነግድማለን እናተርፍማለን፡ የምትሉ እናንተ፥ ተመልከቱ፥ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና።
ሕይወታችሁ ምንድር ነው? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፋሎት ናችሁና። በዚህ ፈንታ፦ ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን፡ ማለት ይገባችኋል" ያዕ. 4:13
ሰውዬው ወደ ሥራ ሲሔድ ከአንድ ወዳጁ ጋር ተገናኘ:: "ወዴት እየሔድክ ነው?" አለው:: "እግዚአብሔር ቢፈቅድ ገበያ ውዬ ልመጣ ነው" አለው:: ባለ ሥራው "ምን እግዚአብሔር ቢፈቅድ ትላለህ? ገበያ ልሔድ ነው አይበቃም?" ብሎ አሾፈበትና ተለያዩ::
ባለ ሥራው ወደ ሥራው ሲሔድ ሌቦች ጠብቀው ደብድበውት እጁ ተሠብሮ ሥራ በመግባት ፈንታ ሐኪም ቤት ዋለ:: ከሐኪም ቤት እጁን በፋሻ አንጠልጥሎ ወደ ቤቱ ሲመለስ "እግዚአብሔር ቢፈቅድ ገበያ ውዬ ልመጣ ነው" ያለው ሰውዬ ጋር ተገናኙ:: "ውይ ወንድሜን ምነው ምን ነካህ" ብሎ የጉዳቱን ሁኔታ በዝርዝር ጠይቆ ከተረዳ በሁዋላ ታማሚውን "ታዲያ አሁን ወዴት እየሔድህ ነው?" ሲለው የጠዋቱ ትዕቢቱ ተንፍሶ እንዲህ አለ :-
"እግዚአብሔር ከፈቀደ ወደ ቤቴ እየሔድሁ ነው"
ሐዋርያው " ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን፡ ማለት ይገባችኋል። አሁን ግን በትዕቢታችሁ ትመካላችሁ፤ እንደዚህ ያለ ትምክህት ሁሉ ክፉ ነው" ያለው ለዚህ ነው:: ያዕ.4::15-16
እግዚአብሔርን ማክበር ማለት በአሚንም በገቢርም ነው፡፡
እግዚአብሔርን በአሚን ብቻ ልናከብረው አይቻለንም፡፡ በአሚን ብቻ እግዚአብሔርን አከብራለሁ የሚል ሰው ካለ እርሱ ከከሐድያን ይልቅ እግዚአብሔርን የሚያስነቅፍ ሰው ነው፡፡ እግዚአብሔር ስሙ የሚሰደበው በከሐድያን ብቻ አይደለም፤ በምግባራቸው በካዱት ክርስቲያኖችም ጭምር እንጂ፡፡
ልጆቼ እማልዳችኋለሁ! እግዚአብሔርን በሁለንተናችን እናክብረው፡፡ በእርሱ ምክንያት የእግዚአብሔር ስም የተሰደበበት ሰው ወዮታ አለበት፤ በእርሱ ምክንያት የእግዚአብሔር ስም የከበረበት ሰውም ንዑድ ክቡር ነው፡፡ እንኪያስ ልጆቼ! በጨለማ ሥራ ውስጥ እየተመላለስን የአባታችንን ስም አናሰድብ፡፡ ኃጢአቶቻችንን እናርቃቸው፡፡ በተለይ ደግሞ ሰውን ከመጉዳት እንከልከል፤ የእግዚአብሔር ስም አብዝቶ ከሚሰደብባቸው ርእሰ ኃጣውእ ይኸው ነውና፡፡ ድሆችን መርዳት እንዲገባን ከአባታችን ተምረን ሳለ የድሆችን ገንዘብ ለራሳችን ነጥቀን የምንወስድ ከሆነ ሊደረግልን የሚችል ምሕረት እንደምን ያለ ነው? ሊደረግልን የሚችል ይቅርታ እንደምን ያለ ነው? የታረዙትን እንድናለብስ ታዘን ሳለ ይባስ ብለን የለበሱትን የምናራቁት ከሆነ ሊደረግልን የሚችል ይቅርታ እንደምን ያለ ነው?
ልጆቼ! እነዚህን ነገሮች ደግሜ ደጋግሜ መናገሬን ፈጽሜ
አላቆምም፡፡ ዛሬ ያልሰማኝ ሰው ምናልባት ነገ ይሰማኝ ይሆናልና፡፡ ነገ ያልሰማኝ ሰው ምናልባት ቀጣዩ ቀን ላይ ይሰማኝ ይሆናልና፡፡ ምናልባት ከነገ ወዲያ ባይሰማኝ እንኳ ፍርዱን ከራሴ አወርዳለሁ፡፡ የእኔ ኃላፊነት ቃሉን መናገር ነው፡፡ እንኪያስ ይህን ደጋግማችሁ የምትሰሙ ልጆቼ! ቃሌን ላለመስማት ፊታችሁን አትሸፍኑ፡፡ በክርስቶስ የፍርድ ወንበር ፊት በሞገስ ለመቆም ሊመጣ ያለውንም ተድላ መንግሥተ ሰማያትን እናገኝ ዘንድ እግዚአብሔርን በአሚንም በገቢርም እናክብረው፡፡ ይህን እንድናደርግ ሰውን በመውደዱ ሰው የሆነው አምላክ ይርዳን አሜን፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዮሐንስ ወንጌልን ሲተረጕም በ67ኛ ድርሳኑ የተናገረው
“በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል፤”
ት.ዳንኤል 12፥1
በመንፈሳዊ ህይወት የዛሉ በስጋ የደከሙ ምዕመናን ሊያበረቱ የሚላኩ ኃይላት የሚባሉ ቅዱሳን መላዕክት አለቃ ለሆነው
ህዝበ እስራኤልን በበረሃ ለጠበቀው
ሶስናን ከሀሰተኛ መምህራን ክስ ላዳናት
ዳንኤልን ለረዳው
ጴጥሮስን ከወህኒ ቤት ነፃ ላወጣው
ዲያብሎስን ለተዋጋው
በልዑል እግዚአብሔር ፊት ከሚቆሙ ከሰባቱ ሊቃነ መላዕክት አንዱ ለሆነው
የባህራንን የሞት ደብዳቤ ወደ ህይወት ለቀየረው
አፎሚያን ለታደገው
እኛንም በህወታችን በመንገዳችን ሁሉ ለሚጠብቀን
ለኃያሉ መልዐክ መልዓከ ምህረት ቅዱስ ሚካኤል የንግስ በዓል እንኳን አደረሳችሁ አደረሰን
የሊቀመልአክት ቅዱስ ሚካኤል ጥበቃ እና አማላጅነት አይለየን
ሰኔ 12 ቅዱስ ሚካኤል ቅድስት አፎምያ ያዳነበት ዕለት
ሰኔ 12 ቀን ቅድስት አፎምያ የቅዱስ ሚካኤልን መታሰቢያ እያዘጋጀች ሳለች ሰይጣን ብርሃናዊ
መልአክ መስሎ መጣ፡፡ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል እንደሆነ ገልጾ ሰይጣናዊ ምክሩን
አሰማምሮ አቀረበላት፡፡ አሳቡንም የእግዚአብሔር ፈቃድና አሳብ እንደሆነ አድርጎ ለማሳመን ሞከረ፡፡
ሰይጣን አስቀድሞ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በገዳመ ቆሮንቶስ መጻሕፍትን
እየጠቀሰ እንደተፈታተነው ሁሉ ቅድስት አፎምያንም ለማሳመንም አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣
ያዕቆብን፣ ዳዊትን የመሳሳሰሉትን እየጠቀሰ ለማሳመን ቢሞክርም ቅድስት አፎምያ ቅዱስ
ሚካኤል ከሆንክ በትረ መስቀልህ የታለ ብላ የቅዱስ ሚካኤል ስእል ቤቷ ነበረና ቅዱስሚካኤል
ከሆንክ ይህ ያንተ ስእል ነውና ተሳለመው አለችው እሱም ተናዶ ዘሎ አነቃት ያንጊዜ ቅዱስ
ሚካኤል ከሰማያት ወርዶ በበትረ መስቀሉ ቀጥቅጦ በጦሩ ወግቶ ሠይጣንን ድል ነስቶ አፎምያን
ከእደ ሰይጣን አድኗታል እኛንም መላኩ ቅዱስ ሚካኤል ከሰይጣን አሽከላ ይጠብቀን፡፡
እስራኤላውያን በግብፃውያን ለ430 ዓመታት ከተገዙ በኋላ እግዚአብሔር ይቅር አላቸው።ሙሴን
መሪ አድርጎ ነፃ እንዲወጡ አደረገ ታዲያ በጉዞ ላይ ሳሉ ፈርኦን በቁጣ ተከተላቸው ።እግዚአብሔር
መልዓኩን ሚካኤልን ላከው።እርሱም ባሕር ከፍሎ መንገዱን እየመራ ወደ ከነዓን
አገባቸው።በሐዲስ ኪዳንም በአማላጅነቱ የሀጥያትን ባሕር ከፍሎ ያሻግረን። ህዳር12 ባህርን
ከፍሎ እስራኤልን ያሻገረበት ፈርኦንን ከነሰራዊቱ ያሰጠመበት ነው። ዛሬ እኛንም ከጠላት
ዲያቢሎስ አድኖ ዘረኝነትንና ጥላቻን አጥፍቶ ሀገራችንን ሰላም ያድርግልን።
#አሜን_አሜን_አሜን 🙏 🙏🙏
እግዚአብሔር ዓሣን ሲፈጥር "ሕይወት ያላቸውን አስገኝ" ብሎ ባሕርን ተናገረው
እግዚአብሔር ዛፎችን ሲፈጥር ደግሞ ዛፍ እንድታበቅል መሬትን ተናገራት
ሰውን ሲፈጥር ግን የተናገረው ለራሱ ነበር
እግዚአብሔርም አለ "ሰውን በመልካችን እንደ ምሳሌያችን እንፍጠር"
ልብ አድርጉ :-
ዓሣ ከባሕር ከወጣ ወዲያውኑ ይሞታል
ዛፍም ከምድር ላይ ከተነቀለም ይሞታል
ሰውም ከእግዚአብሔር ከተለየ ይሞታል:: ባሕር ለዓሣ መሬት ለዛፍ ተፈጥሮአዊ መጠለያቸው እንደሆነ የሰው ልጆች ተፈጥሮአዊ መጠጊያችንም እግዚአብሔር ነው:: የተፈጠርነው ከእርሱ ጋር ልንኖር ነው:: ሕይወት ያለን ከእርሱ ጋር ነውና መኖር የምንችለው በእርሱ ብቻ ነው::
ይህንንም እናስታውስ
ዓሣ ያለ ባሕር ምንም ነው:: ባሕር ግን ያለ ዓሣ ያው ባሕር ነው:: ዛፍ ያለ መሬት ምንም ነው መሬት ግን ያለ ዛፍ ያው መሬት ነው:: ሰው ያለ እግዚአብሔር ምንም ነው:: እግዚአብሔር ግን ያለ ሰው ያው እግዚአብሔር ነው::
ቅዱስ ባስልዮስ እንዲህ እንዳለ :-
"ጌታ ሆይ የአንተ አምላክነት ለእኔ ያስፈልገኛል እንጂ የእኔ ፍጡርነት ለአንተ አያስፈልግህም"
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ኅዳር 23 2013 ዓ ም
Translated from Mighty arrows publications
#መልካም_እለተ_ሰንበት 🙏❤️
የኃጢአተኞች ተስፋ የሆነው መድኃኒታችን በኢያሪኮ ገብቶ ሲያልፍ፣ የቀራጮች አለቃ ባለጠጋው ዘኬዎስ ሊያየው ወድዶ ነበር። ነገር ግን አልቻለም። ያለማየቱንም ምክንያት ጸሐፊው ቅዱስ ሉቃስ ሲነግረን "ቁመቱም አጭር ነበረና ስለ ሕዝቡ ብዛት አቃተው" ይለናል።(ሉቃ 19፥3) ዘኬዎስ ጌታን ማየት ያልቻለው በእርሱ የቁመት ማጠር ላይ የሕዝቡ ብዛት ተጨምሮበት ነው። ታዲያ ለዚህ ችግር ጥሩ መፍትሔ የሚሆነው "እስኪ ዘወር በሉ" እያለ ከእያንዳንዱ ሰው ጋር መጣላት ሳይሆን፣ የራሱን ቁመት ማጠር የሚፈታበት ሌላ መንገድ መፈለግ ነው። ስለዚህም ከፊቱ ወዳለው የሾላ ዛፍ ሮጦ ወጣ። "ባለጠጋ ነኝ፤ በዚያ ላይ ትልቅ ሰው። ራሴን እንደ ትንሽ ልጅ እዚህ ዛፍ ላይ ሳንጠለጥል የሚያየኝስ ምን ይለኛል?" አላለም። ዘኬዎስ ስለ ክብሩና ስለ ሰው አስተያየት ቢጨነቅ ኖሮ "ሰው የሆነውን አምላክ" ማየትና በቤቱ ማስተናገድ ይቀርበት ነበር። ብዙዎቻችን እኛ ክርስቶስን ክርስቶስም እኛን ከሚያይበት የሾላ ዛፋችን "ንስሐ" የምንርቀው "ሰው ምን ይለኛል?" በሚል አጉል ጭንቀት ነው።
አሁን ዘኬዎስ ከሾላው ዛፍ ላይ ነው። የቁመቱን ማጠር ችግር ለመፍታት ባደረገው ጥረት ከአንድ ሰው ጋር ሳይጣላ ያለ ማንም ከልካይ የፈለገውን ክርስቶስ ለማየት በቃ። ጌታም ከበለሷ ተክል ፈልጎ ያጣውን ፍሬ አሁን ከሾላው ዛፍ ላይ ተንጠልጥሎ አገኘው።(ማቴ 21፥19) ይህም በሾላው ዛፍ ላይ የተገኘው ፍሬ "የዘኬዎስ ተነሳሒ ልብ" ነው።
አንዳንድ ጊዜ መንፈሳዊ ሕይወትህን፣ ዓላማህን እንዳታይ ከፊትህ ቆመው የሚጋርዱህ ውጫዊ ነገሮች ይኖራሉ። "ዘወር በሉልኝ!" እያልክ ከእነርሱ ጋር አትጋጭ። "ለምን ትከልሉኛላችሁ?!" በማለትም በብስጭት አታጉረምርም። እንደ ዘኬዎስ የራስህ ችግር ላይ አተኩር። የውጭውን ነገር ማማረር ትተህ እጥረትህን የሚቀርፍልህ የምትወጣበት ዛፍ ፈልግ። እዚያው ሆነህ ለመንጠራራት አትሞክር። ችግርህ ከመንጠራራት በላይ ነው። አትታክት፣ እስኪ መጋፋት ተውና መሬቱን ልቀቅ አድርግ። ያን ጊዜ ከማንም ሳትጣላ ከምትፈልገው እና ከናፈቅኸው ነገር ጋር ያለ ምንም ከልካይ በግልጽ ትተያያለህ። ብቻ የሕዝቡን ብዛት ትተህ የራስህ ማጠር ላይ አተኩር።
ዲያቆን አቤል ካሳሁን
አስታውስ
ደካማነትህን አስታውስ፦ ያን ጊዜ በጣም ጠንቃቃ ትሆናለህ፣ ሊጎዱህ በሚችሉ በትምክህትና በውዳሴ ከንቱም አትሸነፍም።
የተሰጠህን በፍቅር የተሞላ የእግዚአብሔርን ቸርነት አስታውስ፦ ይህም በምስጋና የተሞላ ሕይወት እንድትመራ ያደርግሃል። በእግዚአብሔር ፍቅርና ሥራ ላይ ስትታመን ፍጹም የሆነ እምነት በልብህ እያደገ ይመጣል። ከእግዚአብሔር ጋር ያሳለፍከው ጊዜ ደግሞ በእምነት እንድትኖር ያበረታታሃል።
የሰዎችን ፍቅርና ካንተ ጋር ያሳለፉትን መልካም ጊዜ አስታውስ፦ የሰዎችን ቀናነት ትጠራጠር ዘንድ ወይም ያደረጉብህን ክፉ ነገር ታስብ ዘንድ ይገባሃልን? የቀደመ ፍቅራቸው ስለ እነርሱ ይማልዳል ያንተንም ቁጣ ያበርዳል።
ሞት እንዳለ አስታውስ፦ እንዲሁ በዓለም ያለ ፈተናም እንደሚያልፍ። “ከፀሐይ በታች የተሠራውን ሥራ ሁሉ አየሁ፤ እነሆም፥ ሁሉ ከንቱ ነው፥ ነፋስንም እንደ መከተል ነው።” መክብብ 1፡14 ማለትን ትረዳለህ።
በእግዚአብሔር ፊት መቆምህንና እርሱም እንደሚመለከትህ አስታውስ፦ ያኔ ኃጢአት አትሰራም እግዚአብሔርን ታየዋለህና።
ስለ አንተ የፈሰሰውን የክርስቶስን ክቡር ደም አስታውስ፦ በዚህም ሕይወትህ ያለውን ዋጋ በእርግጥ ታውቃለህ፤ በዓይኖችህ ፊት የከበረ ይሆናል፣ ስለዚህም በከንቱ በመኖር አታጠፋውም “በዋጋ ተገዝታችኋልና” 1ኛ ቆሮ. 6፥20 እንዲል ቅዱስ ጳውሎስ።
በወላጆችህ እምነት በተጠመቅህባት ቦታ ለእግዚአብሔር የገባኸውን ቃል አስታውስ፦ ዲያብሎስን፣ ሥራዎቹን ሁሉ፣ ሐሳቦቹንና ጥበቡን፣ ኃይሉንም ትክድ ዘንድ ኃይል ታገኛለሕና።
በዚህ ዓለም እንግዳ መሆንህንና ወደ ሰማያዊው ቤትህ እንደምትመለስ ዘወትር አስታውስ፦ ያን ጊዜ በዚህ ዓለምና በደስታው ተስፋ ማድረግን ትተዋለህ።
በጠባቡ በር መጓዝ ወደ መንግስተ ሰማያት እንደሚያደርስህ አስታውስ፦ ሰፊው ደጅ ፊት ለፊትህ ተከፍቶ ብታየው፣ አልፈኸው ሂድ ከእሱም ራቅ፣ በእርሱ የሄዱ እንዳሉ አልቀዋልና።
ዘላለማዊውን ሕይወትህን አስታውስ፦ ሁልጊዜም ስለዚህ ትጋ።
የእግዚአብሔር ልጅ መሆንህንና እርሱን መምሰል እንዳለብህ አስታውስ፦ እውነተኞች ከሆኑት ከእግዚአብሔር ልጆች ጋር አካሄድህን አስተካክል።
የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ መሆንህን አስታውስ፦ በውስጥህ ያለውንም ቅዱሱን የእግዚአብሔር መንፈስ አታሳዝን። ዘወትርም ቅዱስ የእግዚአብሔር ማደሪያ ሁን።
#ብፁዕ_አቡነ_ሺኖዳ
መስጠት ወይም ልግስና ትእዛዙን ሟሟላት ብቻ አይደለም መጽሐፍ ቅዱስ "እግዚአብሔር በደስታ የሚሰጠውን ይወዳልና።" /2ቆሮ 9፥7/ እንዲል። እግዚአብሔር የምትሰጠውን ገንዘብ ሳይሆን የመጀመሪያውን ፍሬ እና ቃል ኪዳን የሆነውን ከማዕረጎች ሁሉ የሚልቀውንና ያለ ነቀፋ በነፃነት የሚሰጠውን ፍቅር ከአንተ ይጠብቃል።
ፍቅር የመንፈስ ቅዱስ የመጀመርያ ፍሬ ነው። ስለዚህ ጌታ የኤፌሶንን ቤተ ክርስቲያን በነቀፋ ንሥሓም እንዲገባ በጠራው ጊዜ ነቀፋውን የተወሰነ ኃጢአትን በመግለጽ ሳይሆን በአንድ ሐረግ አጠቃልሎ "ዳሩ ግን የምነቅፍብህ ነገር አለኝ የቀደመውን ፍቅርህን ትተሃልና።" /ራዕ 2፥4/ በማለት ነው።
እግዚአብሔር ይህንን ፍቅር ይፈልጋል ስለዚህ "ልጄ ሆይ ልብህን ስጠኝ ዓይኖችህም መንገዴን ይውደዱ።" /ምሳ 23፥26/ አለ። ትእዛዙን መፈጸም የፍቅር ተፈጥሮአዊ ፍሬ ነው።
ውጪያዊ የንሥሓ ሕይወት ብቻ የሚኖሩ ነገር ግን ውስጣዊ ፍቅር የሌላቸው ይወድቃሉ። ምክንያቱም ሥራዎቻቸውና ከእግዚአብሔር ጋር ያላቸው ግንኙነት ፍቅር የጎደለው ነውና።
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሕግ ማንኛይቱ ትእዛዝ ታላቅ ናት? ተብሎ ለተጠየቀው ጥያቄ የሰጠው መልስ "ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም አሳብህም ውደድ፣ ታላቂቱና ፊተኛይቱ ትእዛዝ ይህች ናት። ሁለተኛይቱም ይህችን ትመስላለች እርሷም ባልጀራህን እንደ ነፍስህ ውደድ የምትል ናት። ኦሪትና ነቢያት በነዚህ በሁለቱም ትእዛዛት ጸኑ።" /ማቴ 22፥36-40/ የሚል ነበር።
በዚያን ቀን ብዙዎቹ "ጌታ ሆይ በስምህ ትንቢት አልተናገርንም በስምህ አጋንንት አላወጣንም?" /ማቴ7፥22/ ይሉታል። ነገር ግን እርሱ ይህን ሁሉ ትቶ በውስጣቸው ስላለው ፍቅር ይጠይቃቸዋል።
ይህ የተአምራት እና የስጦታዎች ችግር አይደለም፣ ባሏቸው በተሰጡአቸው ስጦታዎች የተነሳ የሚጠፉ ብዙዎች ናቸውና። ለዚያ ነው ሐዋርያት ስለመንፈሳዊ ስጦታዎች ባወሩ ጊዜ ሁሉ ይህንን ከሁሉ ይልቅ በተሻለ መንገድ አብራርተውታል።
#አብነ_ሺኖዳ_ሣልሳዊ
ወዳጄ ሆይ! ኃጢአተኛ ከኾንህ በደልህን ትናዘዝ ዘንድ ወደ ቤተ ክርስቲያን ና፤ ጻድቅም ከኾንህ ከጽድቅ (ጎዳና) እንዳትወድቅ ወደ ቤተ ክርስቲያን ና፤ ቤተ ክርስቲያን የኃጥኡም የጻድቁም ወደብ ናትና፡፡
ኃጢአተኛ ነህን? ተስፋ አትቁረጥ፤ ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተህም ንስሐ ግባ፡፡ ኃጢአት ሠርተሃልን? እንግዲያውስ እግዚአብሔርን “በድያለሁ” በለው፡፡
እስኪ ንገረኝ! “በድያለሁ” ብለህ ለመናዘዝ ምን ውጣ ውረድ፣ ምን ዓይነት የሕይወት መርሕ፣ ምንስ መከራ አለው? “በድያለሁ” ብሎ አንዲት ቃል ለመናገር ክብደቱ ምኑ ላይ ነው? ምናልባት (ኃጢአት ሠርተህ ሳለ) በደለኛ አይደለሁም የምትል ከኾነ ዲያብሎስም አንተን አይወቅስህም፡፡ (በድያለሁ ብለህ ንስሐ የምትገባ ከኾነ ግን) ይህን (ዲያብሎስ ሊወቅስህ እንደሚችል) አስቀድመህ አስብ፡፡ …
ስለዚህ ክብርህን እንዳይወስድብህ ለምን አትከለክለውም? ለቅጽበት ያህልስ እንኳን የማይተኛ ከሳሽ እንዳለህ ዐውቀህ ለምን በደልህን ተናዝዘሃት አታስወግዳትም?
ኃጢአት ሠርተሃልን? እንግዲያውስ ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተህ እግዚአብሔርን “በድያለሁ” ብለህ ንገረው፡፡ እኔ ከዚህ ውጪ ከአንተ የምፈልገው ሌላ ምንም ነገር የለኝም፡፡
መጽሐፍ ቅዱስም፡- “ንግር አንተ ኃጣውኢከ ቅድመ ከመ ትጽደቅ - ትከብር ዘንድ አንተ አስቀድመህ ኃጢአትህን ተናገር” ይላል (ኢሳ.43፡26)፡፡ ስለዚህ ኃጢአትህን ታስወግዳት ዘንድ ተናዘዛት፡፡
ይህን ለማድረግ ውጣ ውረድ የለውም፤ ዙሪያ ጥምጥም የቃላት ድርደራም አያሻህም፤ ገንዘብ መክፈል አያስፈልግህም፤ ወይም እነዚህን የመሰሉ ሌሎች ነገሮች አያስፈልጉህም፡፡ አንዲት ቃል ተናገር፤ በደልህን በአንቃዕድዎ አስባት፤ “በድያለሁ” ብለህም ተናዘዛት፡፡
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)
#ኹሉንም_ነገር_ለእግዚአብሔር_እንስጠው
ወርቅን የሚያነጥር ሰው አንዲትን የወርቅ ቅንጣት ወደ እሳት ውስጥ ጨምሮ እጅግ ንጹህ እስክትኾን ድረስ ይጠብቃታል፡፡ እግዚአብሔርም ልክ እንደዚሁ ሰዎች እስኪነጹ፣ እስኪለወጡና ባገኛቸው ነገር ጥቅም እስኪያገኙ ድረስ ፈተና ውስጥ እንዲቆዩ ይፈቅዳል፡፡ ይህ ደግሞ ከጥቅምም እጅግ ከፍ ያለ ጥቅም ነው፡፡
ስለዚህ ፈተና ሲገጥመን ውስጣችን ሊረበሽ ወይም ተስፋ ሊቈርጥ አይገባውም፡፡ ያ ወርቅን የሚያነጥር ሰው በእሳት ውስጥ የጨመራትን የወርቅ ቅንጣት እዚያ ውስጥ ምን ያኽል ጊዜ መቆየት እንዳለባት ያውቃል፤ መቼ ከእሳቱ ሊያወጣት እንደሚገባውም ያውቃል፡፡ እንዲሁ እስከ መጨረሻው በእሳቱ ውስጥ ተጥላ እንድትቀርና በዚያ እንድትቃጠል አይፈቅድም፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ይህን ከወርቅ አንጣሪው በላይ ያውቃል፡፡ መቼ ከርኵሰታችን እንደምንነጻ ያውቃል፡፡ በመኾኑም ራሳችንን በመጣልና ተስፋ በመቁረጥ በክፋት ላይ ክፋት እየጨመርን እንዳንሔድ ሽቶ መቼ ከዚያ ፈተና እንደሚያወጣን ያውቃል፡፡ ስለዚህ ድንገት ያላሰብነው ነገር ቢገጥመን በፍጹም የምናማርር፣ ወይም ተስፋ የምንቈርጥ ልንኾን አይገባንም፡፡ ከዚህ ይልቅ የእነዚህ ነገሮች ምንነትን የሚያውቅ እግዚአብሔርን መጠበቅ፣ እርሱ እስከ ፈቀደው ጊዜ ድረስም ልቡናችንን በእሳት እንዲፈተን ማድረግ ይገባናል፡፡ ምክንያቱም ይህ ነገር በእኛ ላይ እንዲኾን የፈቀደው ለእኛ ጥቅምና በዚያ ውስጥ ኾነን በምናሳየው ጥረት ይበልጥ ሊያከብረን ስለሚወድ ነው፡፡
ይህን በማስመልከትም ጠቢቡ ሰው እንደዚህ ሲል መክሮናል፡- “ልጄ ሆይ! ለእግዚአብሔር ትገዛ ዘንድ ብትሔድ ሰውነትህን ለመከራ አዘጋጅ፤ ልብህን አቅና፤ ኹልጊዜ ታገሥ፤ አታወላውልም፤ በመከራ ብትጨነቅም አትጠራጠር” /ሲራ.2፥1-2/፡፡ “ኹሉንም ነገር ለእግዚአብሔር ስጠው፡፡” ለምን? እግዚአብሔር ከዚያ መከራ መቼ እኛን ማውጣት እንዳለበት ያውቃልና፡፡ ስለዚህ ኹሉንም ለእርሱ ልንሰጥ፣ ዘወትር እርሱን ልናመሰግን፣ ኹሉንም ነገር - ጥቅምም ይኹን ቅጣት - በአኰቴት ልንቀበል ይገባናል፤ ይህም ቢኾን ለእኛ ረብሕ የሚኾን ነውና፡፡ አንድ ሐኪም፥ ሐኪም የሚባለው ታካሚውን ገላዉን ሲያጥበውና ሲመግበው እንዲሁም ደስ ወደሚያሰኝ ስፍራ ሲወስደው ብቻ አይደለም፤ በእርሱ (በታማሚው) ሰውነት ላይ የቀዶ ጥገና ምላጭና ቢላ ሲያሳርፍም ጭምር ሐኪም ነው፡፡ አባትም አባት የሚባለው ልጁን ሲንከባከብ ብቻ አይደለም፤ የገዛ ልጁን ከቤት ሲያስወጣው፣ ሲገሥጸው፣ ሲገርፈውም ያው አባት ነው፡፡ ስለዚህ እኛም እግዚአብሔር ከሐኪሞችም በላይ ሰውን ወዳጅ እንደ ኾነ በማወቅ፥ ምን ዓይነት የሕክምና ዓይነት እንደሚሰጠን በጥልቀት አንጠይቅ፤ ወይም ደግሞ ለደረሰብን መከራ እርሱን ተጠያቂ አናድርግ፡፡ ከዚህ ይልቅ እርሱ የወደደውን ነገር - ቅጣትም ይኹን ቅጣት የሌለው ነገር - ብቻ ምንም ይኹን ምን በአኰቴት ልንቀበል ይገባናል፡፡ በየትኛውም መንገድም ቢኾን የእርሱ ፈቃድ እኛ እንድንድንና ከእርሱ ጋር አንድ እንድንኾን ነውና፡፡ የትኛው መንገድ ለእኛ እንደሚጠቅምም እርሱ ያውቋል፡፡ እያንዳንዱ ሰው የትኛው መንገድ ወደ እርሱ እንደሚመልሰው ያውቃል፡፡ ኹላችንም እንዴትና በምን ዓይነት መንገድ ልንድን እንደምንችል ያውቃል፡፡ በመኾኑም የሚመራን በዚህ እኛ በምንድንበት መንገድ ነው፡፡ ስለዚህ ወደየትኛውም መንገድ ቢወስደንም - ልክ እንደ መጻጉዑ - እርሱ እንደሚያዘ’ን ተከትለን መሔድ እንጂ ትልቁ ጉዳያችን በለስላሳና በቀላል አልያም ደግሞ በከባድና በሸካራ ጎዳና እንድንሔድ የሚያዘ’ንን ትእዛዝ መኾን የለበትም (ልንሔድበት የሚገባ’ው መንገድ እርሱ ስለሚያውቀው እንዲሁ መታዘዝ እንጂ የመንገዱን ከባድነት ወይም ቀላልነት የእኛ አጀንዳ ሊኾን አይገባውም፡፡)
#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
#ወደ_ኦሎምፒያስ_የተላኩ_መልእክታት መጽሐፍ
#በገብረ_እግዚአብሔር_ኪደ ከተተረጎመው
🔮 ምክረ ቃል 🔮
🔅 አንድ ሰው በጾም ወራት በየዕለቱ ጥሩ ጥሩ ምግቦች እየበላና የሚናፍቀውን ምግብ ለሰውነቱ እየሰጠ የሥጋውን ፈቃድ እንዴት ሊቆጣጠር ይችላል? አይችልም። መንፈሳዊው ሰው የጾም ትክክለኛ ፍቺ ሥጋን በማዋረድ የምግብን ፋላጎት ድል ለማድረግ ካበቃ በኋላ ከቁሳዊው ዓለም በላይ ከፍ የሚያደርግ መሆኑን ያውቃል። በመሆኑም የጾም ምግቦችን መብላት ብቻ መሆን የለበትም እርሱ በሚጾምበት ጊዜ ግድ የሚለው መታቀብ ነው ። ይህም ማለት የሚመገበው ሙሉ ለሙሉ የጾም ምግብ ቢሆንም ሥጋው ሊያገኛቸው የሚናፍቃቸውን ነገሮች በሙሉ መከልከል ማለት ነው ።
🔅 ብዙ ሰዎች የሚጾሙት በልምድ ወይም በፊደል ስለሆነ ምንም የሚጠቀሙት ነገር የለም ። እነዚህ ሰዎች ጾምን መለኮታዊ ዓላማውን በመገንዘብ ስለማይጀምሩት ወደ ጾም መንፈሳዊነት ወይም ስለ ትእዛዙ መንፈሳዊነት ሊገቡ አይችሉም። በመሆኑም ሰውነታቸው ይጹም እንጂ መንፈሳቸው አይጾምም።
✨💧✨💧✨💧✨💧
✍ አቡነ ሸኖዳ
“#መንፈሳዊው_ገበሬ”
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)
“አንድ ገበሬ ዘር መዝራት ስላለበት ብቻ እንዲሁ አይዘራም፡፡ አስቀድሞ መሬቱን ማረስ፣ ማለስለስ አለበት፡፡ ካረሰ ካለሰለሰ በኋላ ዘሩን ይዘራዋል፡፡ አሁንም ግን መዝራቱ ብቻ በቂ አይደለም፡፡ የዘራውን ዘር አፈር ሊያለብሰው ይገባዋል፡፡ እንዲያ ካላደረገ ወፎች መጥተው ይለቅሙታልና፡፡
ልክ እንደዚሁ እኛ ክርስቲያኖችም በእኛ ላይ የተዘራውን ዘር (ቃለ እግዚአብሔር) በየጊዜው እንደ ገበሬው የማንከታተለው ከሆነ በአየር ላይ እንደተዘራ ዘር ይሆንብናል፡፡ ሰይጣን ይለቅምብናል፤ የራሳችን ስንፍና እንዲጠወልግ ያደርጓል፤ ፀሐይ ያደርቋል፤ ጐርፍ ይወስዷል፤ እሾክ አንቆ ይይዟል፡፡
ስለዚህ ዘር ዘርቶ ዞር ማለት አያስፈልግም ማለት ነው፡፡ በየጊዜው መኮትኮት፣ ወፎችን ማባረር፣ የበቀለ አረም ካለ ማረም፣ ጭንጫ የበዛበት አከባቢ ካለ የለሰለሰ አፈር መጨመር፣ በየጊዜው መከታተል፣ አጥር ማጠር፣ እንዲሁም ማንኛውም የተዘራውን እህል ሊያበላሹ የሚችሉ ነገሮችን ማስወገድ ያስፈልጋል፡፡ ምናልባት በሰብሉ እርሻ የገበሬው ትጋት ብቻ አስፈላጊ ሊሆን ይችላል፡፡ ምክንያቱም መሬቱ ግዑዝ ነገር ስለሆነ፡፡
በመንፈሳዊው እርሻ ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ኃላፊነቱ የገበሬው ማለትም የመምህሩ ብቻ አይደለም፡፡ ከግማሽ ወይም ከዚያ በላይ የደቀመዝሙሩ (የምእመኑ) ኃላፊነት ነው፡፡ በርግጥ መምህሩ ዘሩን መዝራት አለበት፡፡ ነገር ግን ደቀ መዝሙሩ የተነገረውን ቃል ሁል ጊዜ መስማት ብቻ ሳይሆን ማድረግም አለበት፤ በግብር ፍሬ ማፍራት አለበት፤ የበቀሉ አረሞች ካሉ በየጊዜው መንቀል አለበት፡፡…የገበሬ ልጆች በሰብሉ መካከል የበቀለ አረም ካለ እንዲሁ ጫፍ ጫፉን ብቻ አይቈርጡትም፡፡ ከሥር ይነቅሉትና በመጨረሻም በእሳት ያቃጥሉታል እንጂ፡፡ በእኛ ላይ የበቀሉ አረሞችም (ጥርጥሮች፣ ክሕደቶች፣ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ማነቆ የሆኑብንን ነገሮች…) ከሥራቸው ነቅለን ልናቃጥላቸው ይገባናል።
በዓለ መንፈስ ቅዱስ / ጰራቅሊጦስ
ይህች ታላቅ ዕለት ከቅድስት ሥላሴ አንዱ አካል የሆነው እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ለቅዱሳን ሐዋርያት፣ ለቅዱሳን አርድእትና ለቅዱሳት አንስት የተገለጠባት ዕለት ናት፡፡ እነዚህ ሁሉ በጸሎት ተግተው በሚጸልዩበት ወራት መንፈስ ቅዱስ በተከፋፈሉ የእሳት ልሳን አምሳል የወረደበት ቅዱስ ቀን ነው፡፡ አስቀድሞ ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት ደብረ ዘይት በተባለ ታላቅ ተራራ ላይ ሳሉ እንዲህ ብሎ አስተምሯቸው ነበር “ኃይልን ከአርያም እስክልክላችሁ ድረስ በኢየሩሳሌም በጸሎት ቆዩ፡፡”/ሉቃ 24፡36/ መቶ ሃያው ቤተሰብም በኢየሩሳሌም ሀገር በምትገኝ በቤተ መቅደስ በአንድነት ሆነው በጸሎት በመትጋት ቆዩ፡፡ 120ው ቤተሰብ የሚባሉት 12ቱ ሐዋርያት፣ 72ቱ አርድእት/አገልጋዮች/ እና 36ቱ ቅዱሳን አንስት/ሴቶች/ ናቸው፡፡
ከዕርገት በኋላ በአሥረኛው ቀን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ሐዋርያት ወዳሉበት፣ በጸሎትና በምሥጋና ወደ ሚተጉበት ሥፍራ በእሳት አምሳል /ምሳሌ/ ወርዶ በእያንዳንዳቸው ላይ ተቀመጠባቸው፡፡ ይሄንንም ሁኔታ ተከትሎ ምስጢር ተገለጠላቸው፣ ይፈሩ የነበሩት ሐዋርያትም ወንጌልን ለማስተማር ደፋሮች ሆኑ፣ በተለያየ ቋንቋዎች እንዲናገሩ እውቀት ተሰጣቸው፤ የእግዚአብሔርንም ጸጋ ተቀበሉ፡፡ ይህንን ታላቅ ኀይል እና ሰማያዊ ስጦታን የሰጣቸውን እግዚአብሔርን በታላቅ ዝማሬና እልልታ አመሰገኑት፡፡
በዚያም ዕለት በዓለ ሃምሳ የሚባለውን የአይሁድን በዓል ለማክበር ከተለያዩ ሀገራት የመጡ ቁጥራቸው በብዙ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች የሐዋርያቱን ታላቅ የዝማሬና የእልልታ ድምፅ ሰሙ፡፡ ከመቶ ሃያው ቤተሰብ መካከል አንዱ የሆነው ቅዱስ ጴጥሮስ የተሰበሰቡት ሁሉም እንዲሰሙት ድምፁን ከፍ አድርጎ ቃለ እግዚአብሔርን እንዲህ ብሎ አስተማራቸው፡፡ “እናንተ የእስራኤል ሰዎች ሆይ እኛን የሰው ልጆችን ለማዳን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደ ምድር መጥቶ ከክፉ ሥራ ተመለሱ፣ ኀጢአትን አታድርጉ፣ በቅድስና ኑሩ፣ ወደ እኔም ተመለሱ ቢላችሁ፤ እናንተ ግን ምንም በደል ሳይኖርበት ገረፋችሁት፣ አንገላታችሁት፣ በመስቀል ላይም ሰቀላችሁት፡፡ እርሱ ግን እግዚአብሔር ነውና ሞትን ድል አድርጎ ተነሣ፡፡ እርሱ ግን አሁንም ይቅር ባይ ነውና ከኀጢአታችሁ ተመለሱ ንስሐም ግቡ፡፡” በማለት አስተማራቸው፡፡ የተሰበሰቡት ሰዎች ሁሉ ተገረሙ፡፡ ምክንያቱም ሐዋርያት በፊት የሚያውቁት አንድ ቋንቋ ብቻ ነበረ፡፡ በዚህ ሰዓት ግን ሰባ ሁለት ቋንቋን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ገልጦላቸው ለሁሉም በየቋንቋቸው አስተማሯቸው፡፡ ይህንንም ድንቅ ተአምር ከተመለከቱት ብዙዎች እግዚአብሔርን አመሰገኑት፡፡ ወደ ሐዋርያትም ቀርበው “አባቶቻችን እናንተ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ናችሁና ምከሩን፡፡ እንደ እናንተ የእግዚአብሔር ልጆች እንድንሆንና በቅድስና እንድንኖር ምን እናድርግ?” በማለት ጠየቁ፡ በዚያች ቀን ቁጥራቸው ሦስት ሺ ያህል ሰዎች በቅዱስ ጴጥሮስ ትምህርት አምነው ክርስቲያን ለመሆን ቀረቡ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም እንዲህ አላቸው፡፡ “እነሆ ሁላችሁም ንስሐ ግቡ፡፡ በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምናችሁ ተጠመቁ፡፡” አላቸው በዚያው ዕለትም ሦስት ሺ ሰዎች ወደ ሐዋርያት በመቅረብ ኀጢአታቸውን ተናገሩ፤ ሐዋርያትም እግዚአብሔር ይፍታችሁ እያሉ ልጅነትን የሚያሰጣቸውን ጥምቀት አጠመቁዋቸው፡፡
ከዚያ ቀን ጀምሮም በየዓመቱ ይህችን ታላቅ የቤተ ክርስቲያን የልደት ቀን የምትባለውን በዓለ ጰራቅሊጦስን ክርስቲያኖች በታላቅ ደስታና ምሥጋና እናከብራታለን፡፡
በጽርሐ ፅዮን የወረደው የአብ በረከት፣ የወልድ ፍቅር ፣ የመንፈስ ቅዱስ አንድነት ከሁላችንም ጋር ይሁን!!!
✝✞✝ እንኩዋን ለሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ ✝✞✝
+"+ ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ +"+
=>ከ12ቱ ቅዱሳን ሐዋርያት አንዱ የሆነው ቅዱስ ቶማስ ብዙ መከራን በማሳለፉና የጌታችንን ጐን በመዳሰሱ ይታወቃል::
+ቅዱስ ቶማስ እንደ ሌሎቹ ሐዋርያት በእሥራኤል ተወልዶ በዚያውም በሥርዓተ ኦሪት አድጐ ገና በወጣትነቱ የሰዱቃውያንን ማሕበር ተቀላቅሏል:: ሰዱቃውያን ሰው ከሞተ በሁዋላ አይነሳም (አልቦ ትንሳኤ ሙታን) የሚሉ ናቸው::
+መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማስተማር ሲጀምር ግን ቅዱስ ቶማስ ከነበረበት ማሕበር ወጥቶ ጌታችንን ተከተለ:: ጌታችንም ከ12ቱ ሐዋርያት አንዱ ይሆን ዘንድ ሾመው:: የቀደመ ስሙ ዲዲሞስ ሲሆን ጌታችን ቶማስ ብሎታል::
+ቅዱስ ቶማስ ጌታ አልዓዛርን ለማስነሳት በሔደ ጊዜ ሌሎች ሐዋርያት ጌታን "አይሁድ ይገድሉሃል ቅር" ሲሉት እርሱ ግን "እንሒድና አብረን እንሙት" ሲል ፍቅሩን አሳይቷል:: (ዮሐ. 11:16)
+ጌታችን ትንሳኤውን ለደቀ መዛሙርቱ በገለጠ ጊዜ ያልነበረው ቶማስ ካላየሁ አላምንም አለ:: ምክንያቱም:-
1.ለጌታችን ከነበረው ፍቅር የተነሳ እውነት አልመስልህ ቢለው
2.አንድም ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሳኤውን አየን እያሉ ሲያስተምሩ እኔ ግን ሰማሁ ብየ ማስተማሬ ነው ብሎ በማሰቡ ነበር::
+ለጊዜው ጌታ ተገልጾ ቢገስጸው "እግዚእየ ወአምላኪየ (ጌታየና አምላኬ)" ብሎ ፍጹም ሃይማኖቱን ገልጿል:: ለፍጻሜው ግን የጌታችንን ጎን (መለኮትን) ይዳስስ ዘንድ ባለቤቱ እንዳደለው ያጠይቃል:: መለኮትን የዳሰሰች ይሕቺ ቅድስት እጁ ዛሬም ድረስ ሕያው ናት:: በሕንድ ቤተ ክርስቲያን ውስጥም በክብር ተቀምጣለች::
+ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ተቀብለው ሐገረ ስብከት ሲከፋፈሉ ለቅዱስ ቶማስ ሕንድና በዙሪያዋ ያሉ ሃገራት ደረሱት:: ከዚህ በሁዋላ ነው እንግዲህ ዘርዝረን የማንጨርሰውን ተጋድሎ የፈጸመው:: ቅዱሱ በነበረው ፍጹም ትጋት አባቶቻችን "ዘአሠርገዋ ለብሔረ ሕንደኬ (ሕንድን በወንጌል ያስጌጣት)" ሲሉ ያከብሩታል::
+ቅዱስ ቶማስ ንጉሥ ሉክዮስንና የሃገሩን ሕዝብ ለማሳመን በችንካር መሬት ላይ ወጥረው ቆዳውን ገፈውታል:: ቆዳውንም እንደ ገና ሰፍተው: አሸዋ ሞልተው አሸክመውታል::
+በየመንገዱ የተገፈፈ ገላውን ጨው ቢቀቡት በጎች መጥተው ግጠው በልተውታል:: በዚሕ ምክንያት:-
"ኩሉ የአኪ እንዘ የአኪ ዘመኑ:
አባግዒሁ ለቶማስ እስመ አራዊተ ኮኑ" ብለዋል ሊቃውንቱ::
+በሁዋላ ግን ከፎቅ ወድቃ የሞተችውን የንጉሡን ሚስት በተገፈፈ ቆዳው በማዳኑ ሁሉም አምነው ተጠምቀዋል::
+ቅዱሱ ሐዋርያ ልክ እንደ ቅዱስ ዻውሎስ አንዳንዴ በፈሊጥ: ሌላ ጊዜም በመከራ ለወንጌልና ለቤተ ክርስቲያን ተጋድሏል:: ያለ ማቁዋረጥም ከሕንድ እስከ ሃገራችን ኢትዮዽያ ድረስ ለ38 ዓመታት ወንጌልን ሰብኩዋል::
+በመጨረሻም በ72 ዓ/ም በዚሕች ቀን በሰማዕትነት አርፏል:: መቃብሩና ቅድስት እጁ ዛሬ ድረስ ሕንድ ውስጥ አሉ:: ከኘሮቴስታንቶች በቀር መላው ዓለም ያከብረዋል::
+እንደ አባቶቻችን ትርጉም ቶማስ (ቶማስስ) ማለት ጸሐይ (ኦርያሬስ) እንደ ማለት ነው:: በተሰጠው የወንጌል ጸጋ በሃገረ ስብከቱ አብርቷልና::
=>ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአገልጋዩ ቅዱስ ቶማስ ጸጋ በረከት ይክፈለን::
=>ግንቦት 26 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት=
1.ቅዱስ ቶማስ ሐዋርያ (ከ12ቱ ሐዋርያት)
2.ቅድስት አርሶንያ (የቅዱስ ቶማስ ተከታይ)
3.አቡነ ሐብተ ማርያም ጻድቅ
=>ወርሐዊ በዓላት
1.አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ዘሐይቅ
2.ቅዱሳን ሰማዕታተ ናግራን
3.አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን
=>+"+ ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ:: በመካከላቸውም ቆሞ "ሰላም ለእናንተ ይሁን" አላቸው:: ከዚያም በሁዋላ ቶማስን "ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ:: እጅህንም አምጣና በጐኔ አግባው:: ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን" አለው:: ቶማስም "ጌታዬ አምላኬም" ብሎ መለሰለት:: ኢየሱስም "ስላየኸኝ አምነሃል:: ሳያዩ የሚያምኑ ብጹዓን ናቸው" አለው:: +"+ (ዮሐ. 20:26-29)
<<< ወስብሐት ለእግዚአብሔር >>>
ሰው ሆይ! የሚጎዳህ ሀብትህ አይደለም፤ ድኽነትህም አይደለም። ሰውን የሚጎዳው ክፉ ልብ ነው። ክፉ ልብ ደግሞ በሀብትም፣ ሀብት በማጣትም የሚመጣ አይደለም። ክፉ ልብ ሌሎች ክፉ ልቦችን ይወልዳል። እሳት እሳትን እየወለደ ብዙ እንጨቶችን እንደሚበላ ኹሉ ክፉ ልብም እንደዚህ ነው።
አንተ ሰው! ይህን ማወቅ ትወዳለህን? ክፉ ምግባር ወይም በጎ ምግባር በተፈጥሮ የሚገኙ አይደሉም። እነዚህ ኹለቱ ከክፉ ልብ ወይም ከመልካም ልብ የሚገኙ ናቸው።
(ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ
አምስቱ የንስሓ መንገዶች፥ ገጽ 9)
ጾም ሙሽሪትን ትመስላለች፤ ሙሽሪትን በሠርግ አዳራሽ ኾነው የሚቀበሏት ሰዎች ቤቱን ያስጌጡታል፤ ይሸልሙታል፡፡ ወደ ሠርጉ አዳራሽ የሚገባውን ሰው የሠርግ ልብስ ለብሶ እንደኾነ፣ የቆሸሸ እንዳልኾነ አይተው ያስገቡታል፡፡
እኛም እንዲኽ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ልቡናችንን በማንጻት፣ ልል ዘሊል ከመኾን በመራቅ፣ የክፋት እርሾን በማስወገድ፣ ከጾም ጋር አብረው የሚመጡትን የሚያጅቧትን መልካም ምግባራትንም ለመቀበል የልቡናችንን ውሳጤ በመክፈት የምግባር እናት፣ የማስተዋል እንዲኹም ለሌሎች ምግባራት ኹሉ ንግሥት የምትኾን ጾምን ልንቀበላት ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡ ይኽን ያደረግን እንደኾነ ታላቅ ሐሴት እናደርጋለን፤ ርሷም ቁስለ ነፍሳችንን ትፈውስልናለች፡፡
በሌላ አገላለጽ ብነግራችኹ ሐኪሞች በአንድ ታማሚ ሰውነት ውስጥ ያለውን ቆሻሻ፣ መርዘኛ ፈሳሽን ማስወገድ ሲፈልጉ መጀመሪያ የሚያደርጉት ነገር ቢኖር ታማሚው ምግብ ከመውሰድ እንዲቆጠብ ነው፡፡ ታማሚው ለጊዜው ምግብን ከመብላት ካልተከለከለ ሐኪሞቹ የሚሰጡት መድኃኒት እንደተፈለገው ውጤት አይሰጥም፡፡ እኛም ቁስለ ነፍስ ቁስለ ሥጋ የምትፈውሰውን ጾም ስንቀበላት ከዚኽ በላይ ልንኾን ይገባናል ብዬ እነግራችኋለኹ፡፡
ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስን የምንሻ ከኾነ ልቡናችንን ንጹሕና ንቁ በማድረግ ልንወስዳት (ልንቀበላት)ይገባናል፡፡ እንዲኽ ካልኾነ ግን ከጥቅሟ ይልቅ ጉዳቷ ያመዝናል፡፡
#ቅዱስ_ዮሐንስ_አፈወርቅ
🔮 ምክረ ቃል 🔮
🔅 በሕይወታችን ውስጥ እግዚአብሔር የራቀ ፣ ሌላው ቀርቶ ከእኛ አጠገብ የማይገኝ የሚመስልበት ጊዜ አለ። እነዚህ ጊዜያት እምነታችን ደካማ የሚመስልበት እና እግዚአብሔር ለእኛ በእውነት እንደሚያስብልን ለማመን የምንታገልበት ወይም ምናልባት እግዚአብሔር መኖሩን እንኳን መጠራጠር የምንጀምርበት ጊዜ ነው። በምዕራባዊው የክርስትና ባህል እነዚህ ጊዜያት ብዙውን ጊዜ የነፍስ ጨለማ ምሽት(The dark night of the soul) ብለው ይጠሩታል።እግዚአብሔር ከእኛ የራቀ ይመስላል እኛም ከእምነታችን ጋር እንታገላለን።
🔅 በእንደዚህ ዓይነት ጊዜያት እግዚአብሔር ከራሳችን እስትንፋስ ይልቅ ወደ እኛ እንደሚቀርብ እና እኛ ብቻ ግን እሱ እንደሌለ እንደሚሰማን ማስታወሱ ጥሩ ነው። እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ባለን ግንኙነት ውስጥ እንድንሠራ ለማድረግ እንዲህ ያሉትን ወቅቶች በሕይወታችን ይጠቀማል። ስንታገል እንጠነክራለን። እግዚአብሔር ራሱን ያገለለ በሚመስልበት ጊዜ አንድ ህፃን በእግሩ ቆሞ እንዲሄድ ጥቂት ርቀት ላይ ሆኖ እንደሚጠብ ወላጅ አይነት ነው። ልጁ የመጀመሪያውን እርምጃውን ብቻውን እንዲራመድ ያበረታዋል። ወላጁም ህፃኑ ከወደቀበት ለመድረስ ዝግጁ ነው። ነገር ግን ህፃኑ የመጀመሪያውን እርምጃ እንዲራመድ ወላጅ መፍቀዱ ለልጁ እድገት አስፈላጊ ነው። በሕይወታችን ውስጥ የእግዚአብሔርን መገኘቱ የምንገነዘበው በትጋትና ተጋድሎ ነው ነው፣ እና የበኩላችንን እስካደረግን ድረስ፣ የእግዚአብሔር ጸጋ በብዛት ይፈስልናል።
✨💧✨💧✨💧✨💧✨
✍ አባ ትሪፎን
