977
Subscribers
No data24 hours
-27 days
-730 days
Posts Archive
#ጥያቄ__አለኝ ነቢይ❗️ ህያውነት ያልፋል ወይ⁉️
➖
ይሄ ምን አማርኛ ነዉ፣ ፌዙ ለጆሮ የከፋ
ምን ያለስ ልብስ ሰፊ ነዉ፣ ሞትን በልኬ እሚሰፋ?
ሞት ከአረጋዊ ቢያረጅም፣ ከሰዉ የባሰ ክፉ ነዉ
በተለይ ደራሲ ሲያገኝ፣ ሲስገበገብ ለብቻዉ ነዉ
(ነቢይ መኮንን ለበዓሉ ግርማ)
የቆሙትን ብቻ ሳይሆን፣ ያለፉትንም ሰንዶ ህያው አድራጊው ጥበበኛ ነው ያለፈው። ያረፈው። ግን ግን ነቢይ አንዲት ጥያቄዬን ማን ይመልስልህ?
አንተንስ እንዳንተ ማን ይሰንድህ?
ሰዎቻችንንስ ማን ይሰንድና ህያው ያድርጋቸው?
በኔ ጥያቄ ውስጥም ግን ህያው መልስ፣ ህያው ነቢይ አለ። በዚህ እውነትና ስራህ ውስጥ ህያውነትህ ተፅፏል።
አሁንም ቢሆን ለስንብቴ እሱኑ ነው የምጠራው።👇🏾
ከሞት ጋር ተቃጥረን
ከሞት ጋር ተቃጥረን፥ የቆራጥ ቀጠሮ
ካምናም ብሶበታል ዘገየ ዘንድሮ።
ወትሮም እንዲህ ነዉ የአበሻ ቀጠሮ!!
ሞት ለካ አበሻ ነዉ?!
ግና ምን ሆኖ ነዉ?
እንዴት ቢንቀኝ ነዉ?
እንዴት ቢፈራኝ ነዉ?
መንገዱ ረዘመ ወይ መንገዱ ጠፋዉ?
የህይወትን አጥር፥ ዳር ዳሩን ይዞራል!
ዕድሜን ደጅ ይጠናል።
ሞትም እንደሰዉ ልጅ ቀን ይጐድልበታል?
በለስ የቀናት ለት
ህይወት እንደዚህ ናት
ሞትን መገነዣ፥ ስዉር ስፌት አላት!!
"Death is not extinguishing the light; it is only putting out the lamp because the dawn has come." Rabindranath Tagore
(ለወንድሜ ነቢይ መኮንን)
+1
#መቻል__ለኢትዮጵያ❗️
መቻል እኮ ነው። ስሙ በራሱ እልፍ ማብራሪያ ነው።
ምንም ማብራሪያ አያሻውም።
በቃ መቻል ነው።
ደግሞም ለማን?
ለኢትዮጵያ!
ለኢትዮጵያ፣ ስለ ኢትዮጵያ መቻል ስለቆማችሁ፣ ክብራችን ወደር የለውም።
ሁላችንም ስለ ኢትዮጵያ እንቻልበት!
ሰናይ እሁድ!🙏🙏
+8
#ሌላድንቅቀን❗️
ከሳር ቤት እስከ ላንቻ ... #ከቡልጋሪያ እስከ #ቦስተን
በለሊት ከሰው ጋር ተቃጥራቹ ታውቃላቹ?
ከልዩው ወንድሜ ጋር የተገናኘነውና ስራችንን፣ ወጋችንን፣ ወካችንን የጀመርነው፣ 12 ሰአት ከመሆኑ በፊት ነበር።
አቤት እቺን ቀን፣ ይህንን ሰው: ደግሞም ይህንን ተግባርና ሙከራ ለስንት አመት ጠበቅኳቸው መሰላቹ?! ይኸው ዛሬ ሞላልን። ከሳር ቤት የጀመረው ወክና ወጋችን: 2:30 በላንቻ ተጠናቀቀ። እጅግ በጣም አመሰግናለሁ ወንድሜ ሄኒ!🙏🙏
ብዙ ጊዜ የወል ስም፣ የብሔር ስም፣ የሀይማኖት ስም ሲጠራ፣ አንድ ሰው ትዝ የሚላቸው ሰዎች አሉ።
“እንትን ብሔርን አልወደውም፣ እንትን ብሄረሰብን ስወደው ...” የሚሉ ሰዎች፣ የሚወዱት ወይም የሚጠሉት፣ ከዚያ ብሔር ወይም ህዝብ መካከል ቀድመው የሚያውቁትን፣ የጎዳቸውን ወይም የጠቀማቸውን፣ አንድ ግለሰብ ሊሆን ይችላል።
ሙሉ ህዝብ ለመውደድ ወይም ለመጥላት ያበቃቸው፣ ከአንድ ግለሰብ ጋር ያላቸው ቅያሜ ወይም ውለታ ሊሆን ይችላል።
አንድ ወንዝ በየደጃችን ሲያልፍ፣ የፈለቀበትን አካባቢ ውሃ ብቻ ይዞ የመጣ ይመስለናል። በየመንገዱ የተቀላቀሉትን ብዙ ጅረቶች አናስተውልም። በየደረሰበት አፍሶ ያመጣው አፈር እና ድንጋይ እንዳለ አንረዳም። ባለፈበት ተሸክሞ ያመጣው ግንድ እና ጉድፍ ሁሉ፣ አብሮት የተፈጠረ ይመስለናል። ጉልበቱና እልሁ ... ባለፈበት ተራራና ሸለቆ፡ የተፈጠረ መሆኑን እንዘነጋለን።
ወንዝ ስለፈለቀበት አካባቢ እውነቱን የሚናገር ይመስለናል። ግን ተሳስተናል! ስለአካባቢው ማወቅ የፈለገ፣ ወንዙን ትቶ ሀይቁን ይጠይቅ።
ችግሩ ከአንድ አካባቢ የመጣ ሰው፣ ህዝቡን የማይወክል ማንነት የሚያንፀባርቅበት እድል፣ በጣም ሰፊ ነው። ከአንድ የማህበረሰብ ክፍል ወጥቶ፣ ወደ መኖሪያ አካባቢያቸው በመጣ ሰው ምክንያት፣ ሙሉ ማህበረስቡን ጠልተው የኖሩ፣ በኋላም በአጋጣሚ ወደ ጠሉት ሰው አካባቢ ሄደው፣ ማህበረሱን ካዩ በኋላ “እንዲህ አልመሰለኝም ነበር!” ብለው የተፀፀቱ ሰዎች መስማት የተለመደ ነው።
ሮፍናን እንዳለው፣ ወንዙ ወደ መድረሻው እንጂ ወደ መነሻው አይፈስም። ማወቅ የፈለገ ከወንዙ ጋር አብሮ መሯሯጡን አቁሞ ወደ መነሻው መዞር አለበት። እዚያ ነው የጥያቄው ሁሉ መልስ ያለው።
📍እዚያ ነው “የዓባይን ምንጭ እናስስ!" ብለው የመጡ ጠላቶቻችን ዓይን ያለው።
📍እዚያ ነው የተቀበረ ታሪካችን ያለው።
📍እዚያ ነው የተቀበረ ታሪካችንን አፈር አራግፈን ለማስነሳት እየታገልን ያለነው።
📍እዚያ ነው የጦሩ ግንባር።
📍እዚያ ነው ያላየናቸው አርበኞቻችን እየታገሉ ያሉት።
የእኔም ጉዞ አንዱ ዓላማ ይሄ ነው። ወንዙ ለዘመናት የነገረኝን ትቼ፣ የሀይቁን እውነት በዓይኔ ለማየት! ለእያንዳንዱ ችግር ሐይቁን ተጠያቂ ያደረግነውን፣
ወንዙ ሲጥለቀለቅ የሃይቁ ጥፋት የመሰለንን ሁሉ፣
ወንዙ ሲደርቅ ሰብሎቻችን ደርቀው ሲቀሩ፣ የሐይቁ ክፋት የመሰለንን ሁሉ ላጠራም ጭምር ነበር ጉዞዬ።
(ለሌላ ዓላማ የታሰበ ጉዞ፣ ለሌላ ስራ የተሰናዳ ተጓዥ ቢሆንም፣ እኔ ግን ይህንን እድል ለዚህ ዋነኛ አብሰልስሎቴ ስንቅ አደረግኩት። በውስጤ ለብቻዬ አፈንኩት። በጋራ ጉዟችንና ስራችን ውስጥ፣ ወሰድ እያደረገኝ ተንፈስ፣ ቀልቀል ማድረጌ ባይቀርም።)
እናም ሄድኩኝ። ስሰማና ሳነበው ብቻ የኖርኩበትን አየሁት። ዳሰስኩት። እውነታው ግን ሌላ ነው። ግሩም ነው።
ሀይቁ ላይ ቀዝፌ፣ እጆቼን ወደ ቀዝቃዛው ሐይቅ ዘልቄ አስገባሁ። ዝምተኛው ሀይቅ፣ በርቀት የዛለ መንፈሴን የሚያድስ፣ በቁጭት የደከመ አካሌን አነቃቃው።
ከሁሉም በላይ ግን ... ትናንታችን የተቀበረበት ቦታ ላይ ... ነጋችንን ለማነፅ የሚተጉ ብርቱዎች አይቼ፣ እጄን አፌ ላይ ጫንኩኝ።
ከዚያ የተረጋጋ ሀይቅ የወጣ ወንዝ ያመጣቸው ግንዶች ባህር ማዶ ተሻግረው፣ ከጠላቶቻችን ጋር ተናብበው፣ ከየጢሻው ተጠራርተው ፌስቡክ ላይ ተንጋግተው የሚጮኹት፣ የዚያን ታላቅ ህዝብ ጩኸት እንዳልሆነ በአይኔ በብረቱ አይቼ አረጋግጬ ተመለስኩ። ግን ደግሞም አልተመለስኩም። ተመላለስኩበት እንጂ። እናም መመላለሴን እቀጥላለሁ።
ሁሉንም በዝርዝር እስከምናወጋ፣ የዛሬውን ዳርዳርታዬን ... በሎሬት ጸጋዬ ቃል ልቋጨው።
"ሀይቅ ዳር ተሰብስበው እንቁራሪቶች አብዝተው ስለጮሁ ሀይቁ የእንቁራሪቶቹ ነው ማለት አይደለም ፤ ለክብራቸው ሲሉ ዝም ያሉ ብዙ ዓሳዎች ሀይቁ ውስጥ አሉ።"
ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን
አደራ! #ዓባይን__እንዳትሰሙት❗️
(የዓባይ ማዶ ወግ ((የቀጠለ))
➖
“ዓባይን ብከተል ሰጠኝ ለፈርዖን
መጨረሻው ሀዘን ያንቺ አፍቃሪ መሆን”
#ሮፍናን
“አፋር” ሲባል መጀመሪያ አዕምሯችሁ ላይ የሚመጣ ሰው ይኖር ይሆን?
“አማራ” ሲባልስ ቀድሞ ትውስ የሚላችሁ ማን ነው?
“ኦሮሞ” ሲባልስ ማን ቀድሞ ትውስ ይላችኋል?
"ኦርቶዶክስስ?"
“ሙስሊምስ?” …??
+5
አልሃምዱሊላህ❗️ሰላም ነው❗️
➖
📍ለአመታት ከታሪካዊ ባላንጣዎቻችን ጋር፣ ስለግድባችን ወጥሮ የተሟገተው!
📍በገዛ ቴሌቪዥን ጣብያቸው፣ በቋንቋቸው፣ ዘወትር ስለ ኢትዮጵያ የሚከራከረው።
📍”ምን አይታችሁ! ገና ከ100 በላይ ግድቦች እንገነባለን!” የሚለው።
📍የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል የሆነው።
📍የውሀ እና ኤነርጂ ሚኒስቴር አማካሪ።
📍የአዲስ ዋልታ የስትራቴጂ የክብር አምባሳደር።
ወንድማችን፣ ጀግናችን፣ መሀመድ አልአሩሲ ታመመ ሲባል፣ የምር ደንግጫለሁ! ዛሬ ሄጄ ስለጎበኘሁት በጣም ደስ ብሎኛል!
ይህን ጀግና ማየት፣ ኢትዮጵያን ማየት ነው! ይህን ወንድም ማቀፍ፣ የሚወዳት አገሩን ማቀፍ ነው! እናም በወንድሜ በኩል ሀገሬን አቀፍኳት።
እንኳን ተሻለህ ወንድሜ!🙏🙏
#Mohammed Al-arusi
https://www.facebook.com/share/VPnj91LTc9o3BaJX/?mibextid=LQQJ4d
በሌላ ወቅትም ተመሣሣይ ወንጀል ተፈፀመ።
"ፋራግ ፎዳ" የተባሉ ደራሲን የገደለ ግለሰብ ተይዞ ለችሎት ቀረበ።
“ደራሲው ለመሞት ያበቃቸው ምክንያት ምንድነው ትላለህ?”
“እምነት አልባ በመሆኑ!”
“እስቲ አንድ ማስረጃ ስጠኝ”
“ቀላል ነው። መፅሐፎቹን በማንበብ ማረጋገጥ ይችላሉ። አንድም ቦታ ፈጣሪን አይጠቅስም!”
ዳኛው ጥቂት አሰላሰሉ። አንድ ማረጋገጫ ማግኘት ስላለባቸው … መስቀለኛው ጥያቄ ቀጠለ:-
“አንተ ሥንቶቹን አንብበሃቸዋል?”
“አንዱንም አላየሁም”
“ለምን ?!.”
“ማንበብና መፃፍ ስለማልችል!”
ሁሉም ተከሳሾች ወንጀሉን የፈፀሙት ሳያረጋግጡ ነው። ሲባል በሰሙት ብቻ!! ነገርግን ሁሉም በጥላቻ ተሞልተዋል። ግድያ ለመፈፀም የተነሳሱበት ምክንያት በሌሎች ግፊት ነው።
ዳኛው -- ጭፍን ጥላቻ የሚሰራጭበት፣ ቁጣ ፈጥሮ ጥፋት የሚያስከትልበትን አንድ ጉልህ ምክንያት የተረዱ መሰላቸው።
“ማመዛዘንና መመርመር ካለበት …ዕውቀት ጭፍን ጥላቻን ያግዳል። ራስንም ሆነ ሌሎችን በከፋ ሁኔታ የሚጎዳው... አለማወቅና መረዳት አለመፈለግ ነው። ማወቅ ሚዛናዊ ያደርጋል። ጠይቆ መረዳትም ከመጥፎ ሥህተት ያድናል...” ሲሉ አሰቡ። በመጨረሻም በአንድ ቃል ቋጩት:- “ዕውቀት ጥላቻን ያለዝባል!!”
ይህ አፍሪካዊ ወግ ነው። እኛም ብንጨዋወትበት አይከፋም። ለምን ቢሉ;-
ጥላቻ ፀብን ያፀናል … ምክክር ሠላም ያሰፍናል!
(በዚህች አጭር ወግ ውስጥ የታጨቀው የእያንዳንዳችን እውነትም ይመስለኛል። ለኔ በግል በብዙ ትርጉም ይሰጠኛል። የኔን ተመሳሳይ ጉዳይ ለሌላ ጊዜ ላቆየው። ግን ግን መፅሀፍንም፣ መፅሀፋችንንም ሳይገልጡ፣ በመፃፋችን እና በመፅሀፋችን ብቻ ከመኮነን መንጋነት ይሰውረን! ይፈውሰን! አሚን!)
#አጭር ወግ #ግዙፍ_ሀቅ❗️
‘ለመሆኑ "ጥላቻ"ከምን ይመነጫል’ ቢባል መነሻው ብዙ ነው።
አንዱን ነጥብ እናገኝበት ከሆነ፣ ከአንድ ግብፃዊ ዳኛ የፍርድ ሂደት ጋር ለአፍታ ቆይታ እናድርግ።
#ዳኛው እና #ተከሳሾች⁉️
አንድ ወቅት … በአንዋር ሣዳት ነፍስ ግድያ እጁ የተያዘ ሰው ችሎት ፊት ቀረበ። ተከሳሹ ምንም ጥፋት ያልፈፀመ ዓይነት በተረጋጋ ሁኔታ ቆሟል። የወንጀል ድርጊቱን አልካደም።
“መግደልህን አምነሃል?” ዳኛው ተጠርጣሪውን ጠየቁ:-
“በትክክል … የተባለውን ፈፅሜያለሁ!”
“ምክንያትህ ምንድነው?”
“ናስር እውነተኛ ኃይማኖተኛ አልነበረም”
“አማኝ አለመሆኑን በምን አወቅህ” “ሲነገር ሠምቻለሁ” ገዳይ ኮራ ብሎ መለሰ፤ ተገቢ እርምጃ እንደወሰደ ተሰምቶታል።
ዳኛው ቀጠሉ:-
“ሰምቻለሁ ነው ያልከው?!”
“አብዛኛው ሠው ይናገራል'ኮ!”
“አንተስ ሟችን በቅርበት ታውቃቸዋለህ?”
“በፍፁም!!”
በሌላ ጊዜም እንዲሁ አንድ "የአሸባሪ ቡድን አባል" የተባለ ሰው -- የኖቤል ተሸላሚ በሆኑት የግብፅ ደራሲ ናጂብ ማህፉዝ ላይ የነፍስ ማጥፋት ሙከራ አደረገ … በጩቤ በመውጋት። ዳኛ ፊት ቀርቧል:-
“ደራሲውን ለመግደል ምን አነሳሳህ?”
“መፅሐፍ በመፃፋቸው
“መፅሐፍ መድረስ'ኮ ሥራቸው ነው”
“እሱን አውቃለሁ!”
“እና ለምን ስለት መዘዝክ?!”
“ኃይማኖትን የሚፃረር ነገር በመፃፋቸው - እምነቴን ለማስከበር ስል ነው!”
“አስቲ - እምነትህን የነኩት በየትኛው መፅሐፍ ላይ እንደሆነ ግለፅልኝ”
“እ ..." የገባላዊ ልጆች" በተባለው ላይ!”
ዳኛው ፈጠን አሉና አንድ ጥያቄ አቀረቡ … እርሱም ለመልሱ አልዘገየም።
“የትኛው ገፅ ላይ ነው ኃይማኖቱን ያንቋሸሹት?”
“እሱን እንኳን አላውቅም !”
“እንዴት ነው "አላውቅም" ማለት?!”
“መፅሐፉን ገልጬ አላየሁትም!”
+9
#ይህ_ብሄራዊ_ጣቢያችን_ነው❗️
ዛሬ ከልጆቼ ጋር ወጣ ብለን ያየነው ነገር በጣም ደስ ይላል። ያየነው በሀገር ልክ ነው። የኛ ብቻ ሳይሆን፣ የኢትዮጵያውያን ሁሉ ቤት የሆነውን ኢቢሲ። እንኳንም ቀና ብላን የምናየው ብሄራዊ ጣቢያ ኖረን። ብሄራዊ ጣቢያችን ነውና።
ከሁሉ በላይ ግን፣ ሚዲያ ሲተባበር ደስ ይላል! ሚዲያ ሲተጋገዝ፣ ለአገር ይበጃል። ሚዲያ እንዲህ ሲተያይ፣ ህዝብን ይጠቅማል። ወደፊት እሱ የበለጠ እንዲጠናከር እናፍቃለው።
ልምድ እንለዋወጥ!
ለትልቁ ግብ እንስራ!
ከሁሉም በላይ፣ አገራችንን እናስቀድም!
ኢቢሲዎች አመሰግናለሁ!! በርቱ! እንበርታ!🙏
#ebc #addiswalta #Ethiopia 🇪🇹
“ልጅህን መስዋእት አድርግልኝ!”የትኛውንም አባት የሚያስጨንቅ ፈተና ነው። ነቢዩ ኢብራሂም፣ ለልጃቸው ሳይሳሱ፣ ይህን ፈተና ተራምደው አልፈው፣ ኢድ አልአድሀን አበረከቱልን።
አረፋ ወይም ኢድ አል አድሀ፣ ልጅን የሚያህል ትልቅ ጸጋ፣ ከትልቅም ለሚበልጠው ፈጣሪ ለመሰዋት በመፍቀድ፣ የእምነት ጽናትን የምናከብርበት በአል ነው።
ነቢዩ ኢብራሂም፣ በእምነታቸው እና በልጃቸው እንደተፈኑት ሁሉ፣ ኢትዮጵያውያንም፣ በአገራችን ተፈትነናል። ጥንታዊቱን ትልቅ አገር፣ ከድህነት ለማውጣት። ከኋላ ቀርነት ለማላቀቅ፣ ከልመና፣ ከተረጂነት ለመገላገል፣ ወዘተ ከባድ ትግል መግጠም ነበረብን። ትግሉን ባንጨርስም፣ እያጋመስነው ነው።
ከአድማሱ ባሻገር፣ ብርሀን በድምቀት ይታያል። ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ ጠንካራ ከሚባሉት፣ አንዱን ኢኮኖሚ እየገነባች ነው። በነፍስ ወከፍ ገቢ፣ በአፍሪካ ሀብታም ከተባሉ አገሮችም አንዷ አገራችን ነች።
በአፍሪካ ሳይሆን በአለም፣ ወደፊት ጠንካራ ኢኮኖሚ ይገነባሉ ከተባሉ ጥቂት አገሮች አንዷ፣ አሁንም ኢትዮጵያ ነች።ከ10 ለቴክኖሎጂ ከተመቹ የአፍሪካ ከተሞች 2ኛዋ፣ መናገሻችን አዲስ አበባ ነች።
ይህ የምታነቡት፣ የብልጽግና ፓርቲ ሪፖርት አይደለም። የገንዘብ ሚኒስቴር ያወጣው መግለጫም አይደለም።
የጠቅላይ ሚኒስትሩ ጽህፈት ቤት፣ ወይም የመንግስት ኮሙኒኬሽን የሰጡት ማብራሪያም አይደለም።
ይህን ሁሉ እውነት ያገኘነው፣ ከአለም ባንክ፣ ከአለም የገንዘብ ድርጅት፣ ከአፍሪካ ልማት ባንክ እና ከመሳሰሉት፣ ገለልተኛና አለምአቀፍ ተቋማት ነው።
ይህን ሁሉ ያሳካነው ደግሞ፣ ከድህነቱ በተጨማሪ፣ ድርቁን፣ ጦርነቱን፣ አንበጣውን፣ ኮቪዱን፣ ስጋ የለበሰውን አንበጣ እና መጋኛ ሁሉ ተዋግተን አሸንፈን ነው።
የነቢዩን ፈተና እና በጽናት ያገኙትን ስናስታውስ፣ ኢትዮጵያውያን ያደረጉትን ተጋድሎ እና ያሳኩትን ድልም አንርሳ።
ወደፊትም፣ ብዙ ፈተና፣ በርካታ የምናሳካቸው ድሎች ይጠብቁናል።
የዛሬው ኢድ አል አድሀ፣ የበለጠውን ፈተና ለማሸነፍ ቃል የምንገባበት ቀን ይሁን! ነቢዩ ኢብራሂም፣ ለሚወዱት ልጃቸው ባለመሳሳት፣ ፈተናቸውን በክብር ተወጥተው አልፈውታል።
ኢትዮጵያውያንም፣ ፈተናችንን ተጋፍጠን አልፈን፣ አገራችንን ለክብር፣ ህዝባችንን ለትልቅነት እናብቃ
መልካም አረፋ!
+5
#መሬት__ላይ...❗️❗️
ባህር ዳር ላይ ... ጣና ላይ ... ዳጋ እስጢፋኖስ ላይ ... ጎንደር ላይ
... ላይ ... ላይ ...
ቁጭት ነው! ተስፋ ነው! ብርሀን ነው! እውነት ነው!
ለማነኛውም ይህ የመሬት ላይ እውነት ነው! አይ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ ያለ ሰው! እውነትሽም ሰላምሽም ይብዛልን አቦ!
#ሰናይቅዳሜ!
ከጦርሜዳ ባሻገር … #የዘመኑ_ኮከብ⁉️
ከቀደሙ ጅማሮዎችና እንማር!
➖
በጥንታዊው የትግል ሜዳ ባህላችን
በዘመነኛው የኳስ ሜዳ ውሏችን ለዘመናት ታገልን።
ለዘመናት ደማችን ፈሰሰ። ወንድሞቻችን ሕይወታቸውን አጡ። ትግላችን መራራ ያደረገው የሜዳው ባህሪይ ነው።
ከሁለቱ ተፋላሚዎች አንዱ ወይ ሕይወቱን ወይ ክብሩን ወይ ስሙን ያጣል። ችግሩ ከተፋላሚው ሳይሆን ከሜዳው ነበር።
ግን አንድ ሜዳ ይቀራል!
የሐሳብ፣ የሙግት፣ የምክክር ሜዳ።
ተፈላሚዎች ሁሉ ሳይወድቁ የሚነሱበት።
አብረው ከፍ የሚሉበት ምናልባትም ብቸኛው ሜዳ።
🚩የቀደሙ ጅማሮዎች እና አዲሱ ጅምር⁉️
በርግጥ ምክክርና የሀሳብ ትግል ጅማሮ ነበረን። ከቀደመው ጅማሮአችን የዛሬን ስንቅ መፈለግም አይከፋም።
አዎ ቀድሞም ጥቃቅን ጅማሮዎች ነበሩን! ለምሳሌ ... በአስራ አምስተኛው ክፍለዘመን፣ መካከለኛው ኢትዮጵያ ላይ የነገሰው አፄ ዘርአ ያዕቆብ፣ እሷና ብዙሃኑ የኢትዮጵያ ክርስቲያኖች እንደሰንበት የሚቆጥሩትን እሁድን የሚቃወሙና፣ ትክክለኛዋ ሰንበት ‘ቅዳሜ’ ናት የሚሉ “ደቂቀ ኤዎስጣቴዎሳውያን” በተነሱ ጊዜ፣ የክርክር መድረክ እንዲዘጋጅ አደረገ። በውይይቱም ሁለቱም ወገኖች ሀሳባቸውን እንዲገልጡና ልዩነታቸውን እንዲያስረዱ የሚፈቅድ የሀሳብ ገበታ ነበረ፤ አሁን ቤተክርስቲያኗ ሁለቱንም ሰንበታት የምታከብራቸው በዚያ የተነሳ ነው፤ በዚህ ግብሩ ንጉሱ የሀሳብ ልዩነትን በማሳለጡ ታሪክ በበጎ ያስታውሰዋል።
🚩ምን ዋጋ አለው⁉️
በእርሱው ዘመን ከተነሱና ሌሎች ስነመለኮታዊ ልዩነቶች፣ ከንጉሱና ከአብዛኛው የወቅቱ ክርስቲያን ጋር ከነበራቸው ደቂቀ እስጢፋኖሳውያን ጋራ የነበረው መስተጋብር ግን የታሪካችን ጠባሳ ነው፤ በርግጥ የሀሳብ ልዩነታቸውን የሚያስረዱበት መድረክ ተመቻችቶ ንጉሱ ራሱ በተከራካሪነት የተሳተፈበት ሙግት ነበረ፤ ከሙግቱ በኋላ ግን፣ በሃሳብ ከርሱ የተለዩትን ወገኖች ኢሰብዓዊ በሆነ መልኩ እንዲሰቃዩ፣ እንዲጋዙና እንዲገደሉ አዘዘ፤ ምናልባትም ያኔ ሊወለድ ይችል የነበረ የሆደ ሰፊነት ስብዕና በሽል ወረደ።
ከዛሬ የቀደመው ሙከራችን ይህ ብቻም አይደለም። በመጋቢት 18 ቀን 1870 ዓ.ም በቦሩ ሜዳ የገበያ ሜዳ በተጠራው ስብሰባ፣ በ‘ፀጋ ልጆች’ ና በተዋህዶ መካከል ያሉ ልዩነቶችን ለመስማት በተጠራ ጉባኤ ላይ፣ ውይይቱ መልካም ሆኖ ሳለ፣ ውይይቱ እንደጥንታዊው የሮማውያን የሞት ፍልሚያ፣ አንዱ ብቻ እንዲተርፍ መደረጉ፣ ብሎም የወሎ መኳንንት የኢስላም ሀይማኖትን እንዳይከተሉ መከልከሉ፣ እስከዘመናችን ድረስ ለተራዘምው ውስብስብ ማህበራዊ ችግሮቻችን፣ ምናልባትም በር ከፋች አጀንዳ ነው።
አሁንም የቀረነው እኛ ነን። እድል ያለንም እኛው።
አያቶቻችን ሞክረው ባልገፉት፣
አባቶቻችን ወዳልደፈሩት ሜዳ እንሂድ። ወደሀሳብ፣ ምክክር ሜዳ። እናም ዘመናዊውን ድል በጋራ እንጎናፀፍ!
የዘመናችን ዘመናዊ ኮከብ ለመሆን ጨክነን እንነሳ!
#ኢትዮጵያችንትምከር #ኢትዮጵያእየመከረችነው
#የኢትዮጵያ_አየር_መንገድ፣ የኢትዮጵያ ምልክት🇪🇹🇪🇹
➖Let”s be FAIR❗️
1 #ቅሬታ ተቀብለናል!
ቅሬታን ማስተናገድ፣ ምንጊዜም ቅድሚያ ሊሰጠው ስለሚገባ፣ በቅሬታ ልጀምር።
🚩አየር መንገድ ውስጥ፣ መንገደኛ ሊጉላላ ይችላል?
ያለ ጥርጥር አዎ!
🚩አየር መንገድ ውስጥ፣ ሰራተኛ መንገደኛውን በትህትና ላያስተናግደው ይችላል?
አዎ ይችላል!
🚩 አየር መንገድ ውስጥ፣ የመንገደኛ እቃ ሊጠፋ ይችላል?
ለምን አይችልም!
🚩አየር መንገድ ውስጥ፣ በረራ ሊዘገይ ይችላል?
በደንብ ይችላል!
🚩 ጉምሩክ አካባቢ፣ ጸጥታ አስከባሪዎች አካባቢ፣ መንገደኞችን የሚያስቀይሙ ሊኖሩ ይችላሉ? ላይኖሩም አይችሉም!
እስኪ በእርጋታ እናስብ።
ይህ እኮ፣ በኢትዮጵያ አይደለም፣ በአፍሪካም ትልቁ አየር መንገድ ነው።
🚩በዓመት እስከ 13 ሚሊየን መንገደኛ የሚያጓጉዝ። 230 ሺህ ቶን ጭነት የሚያመላልስ ትልቅ ተቋም ነው።
🚩ከተቋቋመ 77 አመታት ያለፈው፣ በፍጥነት በማደግ ላይ የሚገኝ፣ የኢትዮጵያ ምልክት የሆነ ግዙፍ ድርጅት ነው።
እንኳን ይህን የሚያህል ግዙፍ ድርጅት ውስጥ፣ ትንሽ ካፊቴሪያ ውስጥ፣ ደንበኛ ቅር የሚሰኝበት ጊዜ የለምን?!
ትእቢተኛ አስተናጋጅ አያጋጥምም?
እንኳን አየር መንገድ ውስጥ፣ ባጃጅ ውስጥ፣ መንገደኛ የሚጉላላበት ጊዜ የለም? (እንዲያውም የማይጉላላበት ጊዜ የለም!)
- አየር መንገድ ውስጥ ይቅርና፣ ሸማቾች ሱቅ ውስጥ፣ ሁሉም ተገልጋይ በትህትና ይስተናገዳል?
- እንኳን አየር መንገድ ውስጥ፣ ቤተ መንግስት ውስጥ እቃ አይጠፋም?
- እንኳን የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን፣ የአሜሪካው ፕሬዚደንት አውሮፕላን፣ የAir Force 1 በረራ፣ ሊዘገይ አይችልም?
ይችላል!
ባይሆን ይመረጣል እንጂ፣ መልሱ ይችላል! ይችላል! ይችላል! ይችላል! ነው።
የሁሉም ምኞት፣ መንገደኛ ባይጉላላ፣ ደንበኛ በትህትና እንዲስተናገድ፣ እቃ እንዳይጠፋ፣ በረራ እንዳይዘገይ፣ ሸማቾችጋ ስኳር እንዳይጠፋ፣ ሲመጣም በትክክል እንዲከፋፈል፣ ሁሉም እንዲደሰት ነው።
ምኞት ግን ሁሌ አይሞላም። የትም፣ መቸም፣ ሞልቶ አያውቅም።
ለአየር መንገድም፣ ለሸማቾችም፣ ለኤር ፎርስ ዋንም እውነቱ ይኸው ነው ጀለሴ!
2 #ነገር_በምሳሌ⁉️
ጉዳያችን፣ አየር መንገዳችን ስለሆነ፣ ሌሎቹን ለቀቅ፣ እሱን ጠበቅ! ይሻላል።
🚩አየር መንገድ፣ እድሜ የዋጠ፣ በአልግሎቱም የተመሰገነ ስለሆነ፣ ለ6 አመታት በተከታታይ፣ ምርጥ የአፍሪካ አየር መንገድ የሚል ሽልማት ተቀዳጅቷል።
🚩ምርጥ የቢዝነስ ክላስ ያለው የአፍሪካ አይር መንገድ የሚለውን ሽልማት፣ ለ4 ተከታታይ አመታት አሸንፏል።
🚩ምርጥ የኢኮኖሚ ክላስ ያለው የአፍሪካ አይር መንገድ የሚለውን ሽልማት፣ 4 አመታት፣ በተከታታይ አሸንፏል።
🚩ምርጥ የቢዝነስ ክላስ፣ የበረራ ላይ አገልግሎት (Onboard Catering) ያለው የአፍሪካ አየር መንገድ ተብሎ የተሸለመውም፣ ይኸው አየር መንገዳችን ነው።
🚩የነዳጅ ዋጋ ቢጨምርም፣ የሩሲያ እና የዩክሬን ጦርነት ብዙ ችግር ቢያስከትልም፣ የአየር መንገዱ፣ የ2022/2023 አመታዊ ገቢ፣ በ20 ከመቶ አድጎ፣ 6.1 ቢሊየን ዶላር አግኝቷል።
🚩146 ቦዪንግ፣ ኤር ባስ እና ዴ ሀቪለንድ አውሮፕላኖች ያሉት አየር መንገዳችን፣ በአሁኑ ጊዜ በ80 አገሮች፣ የበረራ አገልግሎት ይሰጠል።
🚩118ቱ፣ አለም አቀፍ በረራዎች ሲሆኑ፣ አየር መንገዱ በአገር ውስጥ፣ ወደ 22 ቦታዎች ይበርራል።
🚩ከአውሮፕላኖቹ መሀል፣ እጅግ ዘመናዊ የሚባሉት ቦዪንግ 737s, 777s, 787s, እንዲሁም ኤር ባስ A350-900 እና ቦምባርዲየር ዳሽ 8-400 ያሉት ሲሆን፣ እነዚህን ሁሉ በማሰማራት፣ አየር መንገዱ፣ በአፍሪካ የመጀመሪያው ነው።
🚩 ራእይ 2025 የተባለውን ስትራቴጂክ እቅድ፣ ከጊዜው በፊት አሳክቶ፣ ሌላ 15 አመት የሚፈጅ፣ ራእይ 2035 የተባለ ስትራቴጂክ እቅድ ነድፎ፣ ከ20 ምርጥ የአለም አየር መንገዶች አንዱ ለመሆን፣ እየበረረ ያለ ተቋም ነው።
🚩 እና ይህ አየር መንገድ ያልተሸለመ፣ ሌላ ማን ሊሸለም ነበር!
🚩ለዚህ አስደናቂ ግስጋሴው፣ አየር መንገዱ በቅርቡ፣ ከኢትዮጵያ ምርጥ ተቋማት አንዱ ሆኖ፣ ከጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ፣ እጅ ሽልማት ተቀብሏል።
3 #ምርቃትና_ዱዐ
ባለፈው ረቡእ እለት፣ የምክክር ኮሚሽኑ ታሪካዊ ስብሰባ፣ በምንድነው የተጀመረው?
በምርቃት እና በዱዐ!
የአፍሪካ ኩራት እና የኢትዮጵያ ምልክት የሆነው አየር መንገዳችን፣ አሁን የሚያስፈልገው፣ ምርቃት እና ዱዐ ነው።
ልጅህ፣ ሲያጠፋ ትመክረዋለህ! ሲያበላሽ ትገስጸዋለህ! ወዘተ
ዱዐና ምርቃትህ ግን አይለየውም። አየር መንገድም እንደዚያው ነው። አንዴ አንዱ ሰራተኛ ገላመጠኝ ብለህ ስትረግመው፣ ትንሽ አይደብርህም?! እንደውም ደፈር ካልን "ብቸኛ" ልጃችን ነው። እና አንድ ልጅና አንድ አይን ያለው በእርግማንና በአፈር ይጫወታል ወይ?! አረ ሼም ነው! ይላል አራዳ! አዎ ሼም ነው! ሼ በል!
ቢያንስ ግን ጨዋ እንሁን!
እሺ ዱዐውም፣ ምርቃቱም ይቅር። ግን
Let’s be fair! (at least!!!)
መልካም እሁድ! መልካም በረራ!
#ethiopianairlines🇪🇹
ሁላችንም፣ ለሁላችንም እናስፈልጋለን❗️
➖
በአለም ላይ፣ የመጀመሪያው የስልክ ግንኙነት የተደረገው፣ የዛሬ 148 አመት፣ በዚህ በያዝነው የግንቦት ወር ውስጥ ነበር።
ደዋዩ፣ ስልክን የፈለሰፈው ዝነኛው የስኮትላንድ ሳይንቲስት፣ አሌክዛንደር ግራም ቤል ነበር። ግራም ቤል፣ ስልክ የደወለው፣ ረዳቱ እና ጓደኛው ለሆነው፣ ቶማስ ዋትሰን ነበር። ግራም ቤል፣ ኒው ዮርክ ነበር። ጓደኛው ዋትሰን ደግሞ፣ ቺካጎ ነበር። የዛሬ 148 አመት፣ በ1876 በአለም የመጀመሪያው የስልክ ግንኙነት ተደረገ። ኒው ዮርከ እና ቺካጎ፣ በቀጭኗ ሽቦ ተገናኑ።
ሰው እና ሰው ተገናኘ።
ህዝብ እና ህዝብ ተቀራረበ።
ባህል ከባህል ጋር ተገናኘ።
ግንኙነቱ፣ እንዲህ እየሰፋ፣ እየሰለጠነ ሄዶ፣ እነሆ አለም አንድ መንደር ለመሆን በቃች። ኢትዮጵያ፣ የዚህ ትልቅ መንደር፣ አንድ ሰፈር ነች። እርስ በርስ ብቻ ሳይሆን፣ ከአለም ጋር ተገናኝተናል።
የትልቁ መንደር፣ አንድ አባል ሆነናል።
ታላቁ ሳይንቲስት ግራም ቤል በመጀመሪያው ጥሪ፣ ለጓደኛው እንዲህ ነበር ያለው።
“ወዳጄ ዋትሰን!ታስፈልገኛለህ፣ እዚህ ና!” እውነቱን ነው! እንኳን ለሱ፣ እንኳን ያኔ፣ አለም መንደር በሆነችበት በዚህ ዘመንም፣ ከመቸውም ጊዜ ይልቅ፣ ሁላችንም ለሁላችንም እናስፈልጋለን!
"Come here, Mr.Watson, I need you!"
+8
ደሞ ዛሬም ከህልመኞቹ ጋር❗️ከላንቻ እስከ ፒያሳ❗️
➖
ከዘመኔ ዘመነኞች፣ ትጉዎች፣ ህልም ያላቸው ሁለት ወጣትና ጎበዝ አመራሮች ጋር መከርን። ከቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታዋ ሌንሳ መኮንን/ አይዳ እና የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም ዋና ዳይሬክተር እና የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር ምክትል ዋና ዳይሬክተር ዮዳሄ አርአያስላሴ ጋር። የሀገራችንን ሁለቱ ቁልፍ ዘርፎች የሚመሩት ሀላፊዎች ጉብኝች: ለኛ ትርጉሙ የላቀ ነበር።
በዝናቡም ውስጥ ቢሆን ቢሮውን፣ ጓሮውን፣ ሰፈሩን፣ ስቱዲዮውን፣
የሬዲዮ ጊቢውን ስናይ ከላንቻ እስከ ፒያሳ አካለልን።
ከይዘት እስከ የስራ አከባቢ ስራዎቻችን ድረስ የዘለቀ ውይይትና ጉብኝት ነበር።
በመጨረሻም በኛው ካፌዎች ምሳችንን በላን!
ቡናችንን ጠጣን።
መሰል የዘመን ተጋሪዎች ናቸው ተስፋችንን የሚያለመልሙት።
የሚያላዝኑትና የሚያስለቅሷት ብቻ ሳይሆኑ፡ የሚተጉላት ወጣቶችም ስላሏት ነው: ኢትዮጵያችን ነገዋ ብሩህ የሚሆነው። ቀጥ ብሎ ወደፊት ከመጓዝ ውጪ አማራጭ የለንም።
ከውድ ጊዜአችሁ ሰውታችሁ፡ ስለተወያየን፣ ስለጎበኛችሁን፣ ወደፊትም ረዥም ለመጓዝ ስለወጠንነው ሁሉ ከልብ አመሰግናለሁ።
ክበሩልኝ! 🙏🙏
#ኑ__እንውጣ❗️
➖
ውረድ እንውረድ በቁልቁለቱ፣
የሞተው ይሙት ታልቅስ እናቱ!
ዘራፍ!” ...
ለዘመናት ካለፍንባቸው ሜዳዎች ያሸነፍንበት አንድም የለም።
በርግጥ ብዙ ውጊያዎችን አሸንፈናል። ጦርነቱ ግን አሁንም አላለቀም። ሜዳ ካልቀየርን በቀር አናሸንፍም።
ረዥሙን ዘመን ያሳለፍነው በጦር ሜዳና በትግል ሜዳ ነው።
ቋንቋችን ዘራፍ አካኪ ዘራፍ!
ውረድ እንውረድ በቁልቁለቱ፣
የሞተው ይሙት ታልቅስ እናቱ!
ዘራፍ!”
የምን ቀስ ነው የምን ዝምታ፣
ጥለን እንውደቅ የመጣው ይምጣ!”
“ውረድ እንውረድ” ተባብሎ ወደ ትግልና ጦር ሜዳ ከሚወርደው የሚመለሰው ግፋ ቢል አንዱ ብቻ ነው።
"ውረድ እንውረድ" ሳይሆን “ውጣ እንውጣ” ተባብለው አሸናፊም ተሸናፊም፣ ከነህይወትና ሙሉ አካላቸው የሚመለሱበት፣ ብሎም ባዋጡት ሀሳብ፡ ከነርሱ አልፎ ወገኖቻቸውን የሚያሻግሩበት ብቸኛ ሜዳ “ የውይይት፣ የንግግር፣ የምከረክር፣ የሀሳብ ሜዳ” ነው።
ኑ... ! ወደዚህ የዘመናችን ዘመናዊ አምባ እንውጣ። ከጦርነቱም: ወደሀሳቡም እንውጣና በጋራ እናሸንፍ!
ከጦርሜዳ ወደ ሀሳብ ሜዳ”
#ሰናይቅዳሜ ለሁላችን🙏🙏
Repost from Abiy Ahmed Ali 🇪🇹
ጦርነትን ኖረንበታል። የተወሰኑ ችግሮቻችንን ፈትተንበታል።
አብዮትን ደጋግመነዋል። የተወሰኑ ችግሮችን ፈትተንበታል።
በሁለቱም ያልተፈቱትን ችግሮች ለመፍታት የቀረን መንገድ ምክክር ነው።
ምክክርን ግን አልተጠቀምንበትም።
ጦርነትና አብዮት የተሟላ መፍትሔ የማያመጡት አሸናፊ እና ተሸናፊ ስለሚያስከትሉ ነው።
ቢዘገይም የተሸነፈው ለማሸነፍ ይታገላል። ያሸነፈውም ድሉን ለመጠበቅ ይዋጋል።
ምክክር ግን ሁሉንም አሸናፊ ያደርጋል። ከተሸነፍንም ሁላችንም ለሀገራችን ብለን ነው የምንሸነፈው።
ይሄ የምክክር ሂደት ሦስት ነገሮች ያስገኝልናል።
1. ሁሉንም ባይሆን እንኳን ዋና ዋና ችግሮችን ይፈታል
2. ከጦርነት ይልቅ ምክክር ባህል እንዲሆን ያደርጋል
3. በተቃራኒ ኃይሎች መካከል መቀራረብና መግባባት ይፈጥራል። ይሄንን መቀራረብ በመጠቀምም ወደፊት በጉዳዮች እየተነጋገርን ለመቀጠል ያስችለናል። በመሆኑም ይኽንን እድል ሳናበላሽ ወደ ተሟላ ድል እንድናሸጋግረው እጠይቃለው።
