Nolawi ኖላዊ
Open in Telegram
ይህ ቻናል ኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊ ትምህርቶች የሚተላለፉበት ነው። እግዚአብሔር አገልግሎቱን ያስፋ! 0911699907 ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
Show more9 270
Subscribers
+624 hours
+347 days
+14430 days
Posts Archive
9 270
“ከተማይቱን አይቶ አለቀሰላት” /7
አንዳንዴ ገና ከእንቅልፋችን ስንነሣ እንባ እንባ ይለናል ። ማልደን ስንወጣ ከተማይቱን ስናይ አልቅሱ አልቅሱ የሚል ስሜት ይጋፋናል ። የሚገርመው ግን ይህ ልውጣ ልውጣ የሚለው የእንባ ትግል ስለ ራሳችንና ስላልተሳኩ ጉዳዮቻችን ነው ። ስለ ራሳችን ኃጢአት ስለ ወገኖቻችንም ስህተት እንባ እንባ አይለንም ። ለራሳችን ስህተት ብዙ ሰበብና አመክንዮ እናቀርባለን ። “መሆን ስለ ነበረበት ሆነ ፣ የተሰማኝ ስሜት ነው ምንም ማድረግ አልችልም” ብለን ለራሳችን ይቅርታ እናደርግለታለን ። ያንን ስህተት ስንፈጽም ሰዎች ነበርን ፣ አሁን ለራሳችን ይቅርታ ስናደርግ ግን አምላክ ነኝ እያልን ነው ። ስለ ወገኖቻችንም ኃጢአት ማልቀስ ተገቢ ነበር ። እኛ ግን በምናውቀውም በማናውቀውም መንገድ እንፈርዳለን ። ሥልጣን የተሰጠው ፍርድ ቤት እንኳ ጥፋተኛ ነው ለማለት ዓመታት ይወስዱበታል ፣ ሥልጣን የሌለን እኛ ግን ሰምተን ሳንጨርስ እንፈርዳለን ።
ዛሬ ላይ የምናጭደው መከራ በአብዛኛው የዘራነውን ፍርድ ነው ። እገሌ ይህ በሽታ መጣበት ፣ ጨዋ ይመስል ነበር ብለናል ፣ ዛሬ የሚበዛው በሽተኛ ሆኗል ። እገሌ ሃይማኖቱን ለውጧል ፣ ኑሮም ቀብርም አይገባውም ብለን ነበር ፣ ዛሬ የገዛ ቤተሰባችን ላይ ሲደርስ አቅፈን ተቀምጠናል ። እገሌ ይህ ነውር አለበት በእሳት መቃጠል ይገባዋል ብለናል ፣ ያ ነውር ልጆቻችን ላይ ሲመጣ አፍረን ተቀምጠናል ፣ አፍ እያለን ዱዳ ሆነናል ፤ የጽድቅ ጠበቃ ነኝ ስንል ነበር አሁን የራሳችን ሰው ጋ ሲደርስ ጭምት ሆነናል ። እነ እገሌ መወገድ አለባቸው ብለን ለጦርነት ሆ ብለናል ፣ ሞት ዛሬ በየቤታችን ሲያንኳኳ ደንግጠናል ። ሩቅ ሲያጠፋ ጎበዝ ያልነው የቅርብ በር እየመታ ነው ። ድንጋይ ላይ ተቀምጠው ሱስ በሚወስዱ ወጣቶች ላይ ብዙ ጥቆማ አድርገናል ፣ የገዛ ልጆቻችን አልጋቸው ላይ ሆነው አደንዛዥ ዕፅ ሲስቡ ግን ጸሎት ይዘናል ። ትላንት የዘራነውን መራራ ዘር እያጨድን ነው ፣ የእኛ የፍርድ ኃጢአት ለልጆቻችንና ለቅርቦቻችንም ተርፎአል ። ቃሪያ የዘራ ብርቱካን አይለቅምም ። የዘራነውን የሚመስል እናጭዳለን ፣ ከዘራነው በላይ እናጭዳለን ።
ጌታችን ከተማይቱን ባያት ጊዜ ያለቀሰው ስለ ኃጢአተኞች ነው ። በመስቀል ላይም ስለ ሰቀሉት ወገኖች ማለደ ። በዚህ በሆሳዕና ዕለት ይቃወሙታል ፣ ኃጢአት ያድጋልና በዕለተ ዓርብ ደግሞ ይሰቅሉታል ። እግዚአብሔር ራሱ በሥጋ እንግድነት መጥቶ ሲጎበኛቸው ላላወቁ ሕዝቦች አለቀሰ ። ኢየሩሳሌም የቀራት አንድ ዓይንዋ እግዚአብሔር ነበረ ። ዓለም ሁሉ ተባብሮ ጠልቷት ነበር ። አንድ ዓይንዋን ለምታጠፋው ከተማ አለቀሰ ። የከተማው ኑሮ ማስመሰል ያለበት ነው ። ከተማው ብዙ ቤቶች አሉበት ፣ በትክክል የሚኖር ግን ጥቂት ነው ። ብዙ ሰው አለበት ፣ ብቸኝነት ግን እንደ ጥቅምት ውርጭ የሚገርፍበት ነው ። ረሀብ አለ ፣ በነጭ ልብስ የተሸፈነ ነው ። ዛሬም ከዚህች ከተማ ቢመጣ ጌታ ያለቅሳል ። ድሆችዋ መድረሻ የላቸውም ። ቤት አጦች እልፍ ናቸው ። ልጆቻቸው ያመፁባቸው ወላጆች ልክ የላቸውም ። ሥራ አጦች ማለዳ በባዶ አንጀታቸው ወጥተው ሲዞሩ ይውላሉ ። ውኃ ስጡኝ እንዳይባል በሮች ሁሉ ዝግ ናቸው ። በጫካ ከመጥፋት በላይ በአርማታ ጫካዎች በፎቁ መሐል የጠፋ ፣ የሕይወት ውሉ የተሰወረበት ብዙ ሰው አለ ። አግኝተው ደስታ ላጡ ፣ ኖረው መኖሪያ ለተቸገሩ ከተሜዎች ጌታ ዛሬም ያለቅሳል ። መኖርም መሞትም በማይቻልባት ከተማ ፣ ያልሰማ በሚጎርፍባት ደማቅ ቀዬ ብዙ ድብቅ እንባ አለ ። ነጠላ የለበሰ ወንበዴና ፀጉሩን ያጎፈረ ጻድቅ በከተማ አለ ። ነጭ ለብሶ የሚራብና ድሪቶ ለብሶ የሚጠግብ በከተማ አለ ። ጌታ ዛሬ ቢመጣ ለብዙ ደማቅ የዓለማችን ከተሞች ያለቅሳል ። የውሸት እየሳቁ የእውነት የሚያለቅሱ በከተማው ሞልተዋልና ። ባለጠጋ ዘመድ እያላቸው በረሀብ የሚገረፉ ፣ በራስ ወዳድነት መተያየት ያቃታቸው የከተማው ምንዱባን አያሌ ናቸው ።
ጌታችን ለኢየሩሳሌም ያለቀሰው ፍርድ ከመጣ የቍጣውን ጽዋ እስከ መጨረሻው መጨለጥ ግድ ስለሆነ ነው ። ከቀኑ በፊት አለቀሰ ። በቀኑ ለማልቀስም ኢየሩሳሌም ጊዜ አላገኘችም ። እዬዬ ለማለትም ድሎት ያስፈልጋል ። ድል አድራጊ ነህ ሲሉት ዘንባባ እያነጠፉለት ነበር ። ጌታችን ግን በሆሳዕና በአርያም ዝማሬ መካከል አለቀሰ ። በምድር ላይ ሰፊ ሀብት የፈሰሰበት መቅደሱ ነው ። ያ መቅደስ አስቀድሞ በዳዊት ሊሠራ ሲል ዳዊት ተከለከለ ። ቅዱስ ዳዊት ያልቻለውን የእግዚአብሔር ቤት መሥራት ፣ ወንጌልን ማስፋፋት ዕድሉ መጥቶለት የሚዘገይ ያልታደለ ሰው ነው ። የመቅደሱ ንድፍ በራሱ በእግዚአብሔር የተቀረጸ ነው ። ይህ መቅደስ ለሁለተኛ ጊዜ እንደሚፈርስ ባሰበ ጊዜ ጌታ አለቀሰ ።
የመጀመሪያው መቅደስ የሰሎሞን መቅደስ ይባላል ። ሁለተኛው መቅደስ የዘሩባቤል መቅደስ ይባላል ። ይህ መቅደስ በጌጠኛነቱ ከመጀመሪያው በላይ አይደለም ። የመቅደሱ ምርቃት ቀን የተሰጠ ተስፋ ነበር ። “ከፊተኛው ይልቅ የዚህ የሁለተኛው ቤት ክብር ይበልጣል ፥ ይላል የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር።” (ሐጌ. 2 ፡ 9)። ከፊተኛው መቅደስ ይልቅ የሁለተኛው ቤት በክብር የበለጠው ክርስቶስ ቆሞ ስላስተማረበት ነው ። ይህ መቅደስ እንደሚፈርስ ባሰበ ጊዜ ጌታ አለቀሰ ። ብዙ ሞኝ ሰው አለ ። አገሬ አትፈርስም ይላል ። ቤተ ክርስቲያኔ ምንም አትሆንም እያለ ተኝቶ የሚፎክር ቍጥር የለውም ። ኢትዮጵያ የሚለው ስም በመጽሐፍ ቅዱስ አርባ ጊዜ ያህል ስለ ተጠቀሰ ኢትዮጵያ ምንም አትሆንም ብሎ የሚያስብ ምስኪን አለ ። ከኢትዮጵያ በላይ ሶርያ ተጠቅሳለች ፣ ግን ፈርሳለች ። ኢየሩሳሌምን ኃጢአትና ግፍ ፣ አለማመንና መከፋፈል ካፈረሳት እኛ የተለየን አይደለንም ። ዛሬም ጌታ ቢመጣ ለአገራችን ያለቅስላታል ። ምንም እርግጠኛ ነገር የለንም ። ገደል አፋፍ ላይ ቆመን እየታገልን ነው ። ገደል አፋፍ ላይ እንኳን ጠቡ ፍቅሩም አያስደስትም ። ፈጥነን ራሳችንን ማየት የሚያስፈልገን ጊዜ ላይ ነን ።
ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጳጉሜን 2 ቀን 20148 ዓ.ም.
9 270
ዛሬ እሑድ ጳጉሜን 1 ቀን 2018 ዓ.ም. ከጠዋቱ 4:00 ሰዓት ላይ ትምህርታችን ይጀምራል ::
የትምህርታችን ርእስ "
በየመንደሩም ያልፍ ነበር
ሉቃ. 8፥1
ማስታወሻ ብትይዙ ይመከራል።
ሌሎች ወገኖቻችንንም ጋብዙ
https://t.me/Nolawii
9 270
ዛሬ ዓርብ ነሐሴ 29 ቀን 2018 ዓ.ም. ከምሽቱ 2:00 ሰዓት ላይ ትምህርታችን ይጀምራል ::
የትምህርታችን ርእስ "
አቤቱ ንጹሕ ልብን ፍጠርልኝ
መዝ. 50፥10
ማስታወሻ ብትይዙ ይመከራል።
ሌሎች ወገኖቻችንንም ጋብዙ
https://t.me/Nolawii
9 270
“ከተማይቱን አይቶ አለቀሰላት” /6
ጌታችን በኢየሩሌም ውስጥ ካለው የበዓል ሁካታ ፣ በከተማዋ ውስጥ ከሚፈጸመው ግፍ አልፎ የሚመጣውን ሮማዊ የጦር ጀነራል ቲቶስን አሰበ ። ጌታችን፡- “ይህን ሁሉ ታያላችሁን ? እውነት እላችኋለሁ ፥ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሳይፈርስ በዚህ አይቀርም” ያለው ትንቢት የተፈጸመው በቲቶስ ነበር ። (ማቴ. 24 ፡ 2) ። ጌታችን ይህን ትንቢት ሲናገር ቤተ መቅደሱ በልዩ ጌጥ እየታደሰ ነበር ። ከደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሁኖ የመቅደሱን ውበት ማየት ይቻል ነበረ ። ጌታችን ከዛሬው ውበት የሚመጣውን ጥፋት አየ ። የመጨረሻው ዘመን የሚናበበው በሦስት ነገሮች ነው ። በእስራኤል ፣ በኢየሩሳሌምና በመቅደሱ ነው ። የእስራኤል መፍረስና መመለስ ፣ የኢየሩሳሌም ጥፋትና የስበት ማዕከል መሆን ፣ የመቅደሱ መፍረስና ለሦስተኛ ጊዜ መሠራት የመጨረሻው ዘመን ማሳያ ነው ። ጌታችን ስለ ኢየሩሳሌም ሲናገር ስለ መላው ዓለም ጥፋትም አብሮ ተናግሯል ። ሁለተኛውን መቅደስ ያደሰውና ያፈረሰው ሮማዊ ሲሆን ሦስተኛውን መቅደስ የሚሠራውና የሚያፈርሰውም ሐሣዊ መሢሕ ሮማዊ ነው ። ይህም፡- “እንግዲህ በነቢዩ በዳንኤል የተባለውን የጥፋትን ርኩሰት በተቀደሰችው ስፍራ ቆሞ ስታዩ ፥ አንባቢው ያስተውል” የተባለው ትንቢት ነው (ማቴ. 24 ፡ 15) ።
የሰባ ዓ.ም. ጥፋትና የመጨረሻው ቀን በጣም ይመሳሰላሉ ። ጌታችን በደብረ ዘይት ተራራ ላይ እየመጣ ስላለው መከራ ሲናገር ክርስቲያኖች ምልክቱን አይተው እንዲሸሹ አስጠንቅቆ ነበር ። “ኢየሩሳሌም ግን በጭፍራ ተከባ ስታዩ በዚያን ጊዜ ጥፋትዋ እንደ ቀረበ እወቁ” ብሎ ነበር ። (ሉቃ. 21 ፡ 20) ። በ66 ዓ.ም ከተማዋ ስትከበብ የጌታን ቃል ያስታወሱት ክርስቲያኖች በዮርዳኖስ ምሥራቅ ወደምትገኝ ፔላ ወደ ተባለች ከተማ ሸሹ ። በዚህም ከጥፋት ዳኑ ። በመጨረሻው ቀንም የመጨረሻው ጽዋ ሊደፋ ሲቃረብ ክርስቲያኖች ይነጠቃሉ ። ከመከራውም ይድናሉ ። በዚህም የጌታን ስም የሚጠራ ይድናል የሚለው ቃል ኪዳን ይፈጸማል ።
የሰባ ዓ.ም ጥፋት እስከ ዛሬዋ ቀን ድረስ ተጽእኖ አለው ። እስራኤል መሥዋዕተ ኦሪትን ማቅረብ ያቆሙበት ነው ። አሁንም መቅደሱ አልተሠራምና መሥዋዕትን ማሳረግ ቢፈልጉም አይቻላቸውም ። መቅደሱን ለሦስተኛ ጊዜ ሲሠሩ ግን የዓለም ፍጻሜ እየተቃረበ ይመጣል ። የሚገርመው መቅደሱን በአንድ ቀን ውስጥ ለመሥራት ዝግጅቱና ቁሳቁሱ አልቋል ። መቅደሱ የሚሠራው በቀድሞ ቦታው አሁን አል-አቅሳ መስኪድ በተሠራበት ላይ በመሆኑ ታላቅ ሁከት በዓለም ላይ የሚያስነሣ ርእስ ነው ። የመጀመሪያው የሰሎሞን መቅደስ የፈረሰው በነሐሴ አካባቢ ነው ። ከ400 ዓመታት አገልግሎት በኋላ በ586 ዓመት ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በባቢሎናውያን ፈረሰ ። በአስገራሚ ሁኔታ ሁለተኛው መቅደስም የፈረሰው በነሐሴ ወር ነው ። በዚህ ጥፋት ከአንድ ሚሊየን በላይ አይሁድ ሞተዋል ። ከ97 ሺህ በላይ የሚሆኑ ተማርከዋል ። ለባርነት ተሽጠዋል ። ገዥዎች እምቢ ሲሉ ምርቃት ይሁናችሁ ተብለው ተሰጥተዋል ። በ70 ዓ.ም. ከአገራቸው የወጡ አይሁድ 1900 ዓመታት ያህል ቆይተው የተመለሱት በ1948 እአአ ነው ። ዘመናዊት እስራኤል የሰባ ስምንት ዓመት ዕድሜ ያላት አገር ናት ። ሰባ ዓ.ም. ኢየሩሳሌም በሙሉነት የፈረሰችበት ነው ።
በ66 ዓ.ም. ሮማዊው አስተዳዳሪ ጌሲየስ ፍሎሩስ የመቅደሱን ገንዘብ ወሰደ ። በዚህም ታላቅ ሕዝባዊ ቍጣ ተነሣ ፣ የተዋጊ ቡድኖች ተፈጠሩ ። ዓመፁን ለማስቆም ኔሮ የሮም ንጉሠ ነገሥት የሆነው ቬስፓስያን የተባለ የጦር ጄነራልና ልጁን ቲቶስን ወደ ኢየሩሳሌም ላከ ። እስከ 69 ዓ.ም. በኢየሩሳሌም ምድር የቆየው ቬስፓስያን በሮም በተነሣው የፖለቲካ ሽኩቻ ምክንያት ሲመለስ ልጁን ቲቶስን ተክቶ ነበር ። ቬስፓስያን 79-81 ዓ.ም የሮም ንጉሠ ነገሥት ሆኗል ። ጄነራል ቲቶስ ያመፁትን አይሁድ ዙሪያቸውን በመክበብ በረሀብ ቀጣቸው ። ከበባው ከ66 - 70 ዓ.ም ድረስ የዘለቀ ነበር ። ከረሀቡ ጽናት የተነሣ ልጆቻቸውን እስከ መብላት ደርሰው እንደ ነበር ዮሴፍ ወልደ ኮርዮን ይገልጣል ። ከበባው ባመጣው ችግር ረሀብና በሽታ ሕዝቡን ጨረሰ ። የእርስ በርስ መከፋፈልም ተከሰተ ። ምዕራብ ኢየሩሳሌምን አንዱ ቡድን ፣ የመቅደሱን ዙሪያ ሌላው ቡድን ተቀራመተ ። ለማምለጥ የሚሞክረውን አይሁዳዊ በጭካኔ ይገድሉት ነበር ። በ70 ዓ.ም ሮማዊው የጦር ጀነራል ቲቶስ ከበባውን ሰብሮ ገባ ። ኢየሩሳሌምን አፈረሰ ። ለ600 ዓመታት ያገለገለውን የዘሩባቤል መቅደስን አቃጠለው ።
ጌታችን ከደብረ ዘይት ተራራ ቁልቁል ሲወርድ ለኢየሩሳሌም ያለቀሰው ይህን ቀን አይቶ ነው ። በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ቁጭ ብሎም በማቴዎስ 24 ላይ የሰፈረውን ትንቢት ተናገረ ። ይህ ትንቢትም የኢየሩሳሌም ጥፋትና የመጨረሻውን ቀን በሕብር የገለጠበት ነው ።
ኢየሩሳሌም ለምን ጠፋች የመጀመሪያው መሢሑን መቀበል ባለመቻልዋ ነው ። ብዙ የሃይማኖት ቡድኖች በመነሣታቸው ሕዝቡ ተከፋፈለ ። የእርስ በርስ ክፍፍልም ለውጭ ጠላቶች አቅም ሆነ ። መቼም ሞተን ካልጠበቅነው የሚገድለን የለም ። መከፋፈል ጠላትን ሞቶ መጠበቅ ነው !
ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ነሐሴ 29 ቀን 2018 ዓ.ም.
9 270
“ለተረሳ ኀዘን ትኩስ ዕንባህን አታፍስስ”
የከረመው ልቅሶ ዛሬ ለሰማው ሰው አዲስ ነው ። ደንቆሮ የሰማ ቀን ያብዳል ይባላል ። ቢሆንም ለተረሳ ኀዘን ትኩስ ዕንባን ማፍሰስ አይገባም ። ሰዎች ያለፈውን አሰቃቂ ጉዞአቸውን የነገሩን እግዚአብሔር እንዴት እንዳዳናቸው አስበን ለምስጋና እንድንቆም እንጂ ትኩስ ኀዘን እንድናቀርብ አይደለም ። ባለፈ ክረምት ቤት እንደማይሠራ ባለፈ ኀዘን ላይ መቆየት አይገባም ። ሰው ወደፊት የሚዘረጋው የትላንቱን እየተወ ነው ። መከራን በመካሪነቱ መቀበል ፣ በትምህርቱ መደሰት እንጂ ከቀዝቃዛ ስፍራ እያወጡ ማሞቅ ተገቢ አይደለም ። አንድ ሕዝብ የሚያድገው የትላንት ክፉ ገጠመኙን ለዕድገት ሲጠቀምበት ብቻ ነው ።
አንዳንድ ቀሊል ሰዎች የደረሰባቸውን አጋነው ያወራሉ ፣ ያልደረሰባቸውን ፈጥረው የቀጥታ ስርጭት ያህል አሁንነትን ሰጥተውት ይናገራሉ ። የውሸት እያለቀሱ የእውነት የማስለቀስ አቅም አላቸው ። እነዚህ ሰዎች ጉዳታቸውን የሚናገሩት የሰውን ልብ ለመያዝና ለመሄድ ቢያስብ እንኳ በይሉኝታ ታስሮ እንዲቀር ነው ። ያንን ሁሉ ነግሬህ እንዴት ጥለኸኝ ትሄዳለህ ለማለት አሳዛኝ ድርሰታቸውን ሌሎችን በጥፋተኝነት ስሜት ለማሰቃየት ይጠቀሙበታል ። ትላንትን ልንተርከው እንችላለን ፣ ልንኖረው ግን አይገባንም ። ዛሬ ላለንበት ነገር የትላንቱ መሰላል ነበረ ።
ከደረሰብን ክፉ ነገር በላይ የደረሰልን እግዚአብሔር ይበልጣል ። የልጅነት ስብራታቸውን ያልረሱ ሰዎች ዛሬ ዕረፍታቸውን ማጣጣም አልቻሉም ። ዛሬ እየበሉ የተራቡበትን ዘመን እያሰቡ ትኩስ ዕንባ የሚያፈሱ ፣ ብዙ ቤት ይዘው ጥገኛ ሆነው የኖሩበትን ዘመን እያስታወሱ የሚተክዙ አያሌ ናቸው ። እነዚህ ሰዎች ሌሊትን አልፈው ብርሃን ያገኙ ናቸው ። ሌሊት ያልቀደመበትን ብርሃን እየፈለጉ ነው ። በጥንተ ተፈጥሮም ሌሊት ይቀድማል ፣ ብርሃን ይከተላል ። የቀደሙት ነገሥታት በድለው አጥፍተው ይሆናል ። እንኳን በሩቅ ያሉት መሪዎች ቤተሰብ ይጎዳዳል ፣ እናትና ልጅም ይካሰሳል ። አውሮፓውያን በአፍሪካና በእስያ ፣ በደቡብ አሜሪካ የፈጸሙትን ዛሬ እንኑረው ቢባል ዲፕሎማሲ በዓለም ላይ አይኖርም ነበር ። በቅርብ ዘመናት ጥቁርና ነጭ አንድ ላይ የማይሳፈሩበት ታሪክ በአሜሪካ ነበረ ። የቆሙትና መልካም ለማድረግ አጋጣሚ ያላቸው እየበደሉ ሙታንን መውቀስ ተገቢ አይደለም ። የትላንቱን ክፉ ነገር እኛ እንዳንደግመው መማር እንጂ እርሱን ዛሬ ላይ አምጥተን መኖር አይገባም ።
ንጉሥ ሳኦል በድህነት የኖረ ነበረ ፣ ዳዊትም እረኛ ሁኖ በስቃይ አሳልፏል ። ሐዋርያው ጴጥሮስ ጌታውን ክዶ እንደገና ለአደራ በቅቷል ፣ ጳውሎስ እስጢፋኖስን አስገድሎ የቤተ ክርስቲያን አባት ሁኗል ። እግዚአብሔር ዘንድ ስንጠጋ የምናገኘው ትልቅ ጸጋ የትላንትን ክፉ ገጠመኝ መርሳት ነው ። ከመጠን በላይ ልታይ ልታይ ማለት የትላንትን ኑሮ አለመርሳትና በበታችነት ስሜት መሰቃየት ነው ። ብዙ ሰው ትልቅነትን ለራሱ ከሚፈልገው በላይ ትንሽ አድርገው ላዩት ሰዎች ለማሳየት ይከጅለዋል ።
ያለፈን ነገር መልሰን ማስተካከል ካልቻልን በዚያ ውስጥ ማለፍ ስለነበረብን ሆኗል ። ለማይመለሱ ቀኖች ራስን በትኩስ ዕንባ ማቃጠል ተገቢ አይደለም ። ንስሐ ትላንትን መካሻ ነው ። በፍቅር የፈጠረን በይቅርታ እንደገና ይቀበለናል ። የደረቀን ዕንባ በአዲስ ዕንባ ማርጠብ ላለመደሰት መጣር ነው ። ሕይወት ከእኛ ቁጥጥር ውጭ የምትሆንበት ጊዜ ብዙ ነው ። ጥላን አትከተለኝ ማለት አንችልም ፣ እንዲመራን ግን መፍቀድ የለብንም ። የተቀበረን ኀዘን መክፈት ቁስልን ማፋፋም ነው ። ትላንትን እያስታወሱ ሊያውኩን ከሚፈልጉ ሰዎች መራቅ ተገቢ ነው ። የተጽናናን ሰው በማወክ የሰውን ቀን እንዳንሰርቅ መጠንቀቅ ይገባል ። ቁስል ይጠግጋል ፣ ይድናል ። እንደገና ካመረቀዘ የበለጠ ይጎዳል ። እኛ የረሳነውን ጉዳት መርሳት ያቃታቸው ሰዎች አጠገባችን ካሉ ታመዋል ማለት ነው ። የዛሬው ዕንባ ትላንትን መካስ ካልቻለ ፣ በትላንት ኀዘን ዛሬን ማጣት አይገባንም ። አልኖርኩትም ብለን ስለ ትላንት እያዘንን ዛሬም እያመለጠችን ነው ። ካለፈው ኀዘን የሚመጣው ተስፋ ይበረታል ። እግዚአብሔር ሞትን በኀዘን ለውጦልን ከኖርን ዕድለኞች ነን ። ያጣነውን ሳይሆን የተቀበልነውን የምስጋና ርእስ ማድረግ ብልህነት ነው ። የዳነን ቁስል በስንጥር መቆጥቆጥ ትኩስ ዕንባን ያመጣል ።
የዛሬ አቅም ለዛሬ እንጂ ለትላንት አይሆንም ። የትላንቱን ከተማርንበት ለነገ የእውቀት ስንቅ ነው ። የራስን ጉዳት ብቻ ከማሰብ በጣም የተጎዱትን ማሰብ አስፈላጊ ነው ። ዛሬ የመጣውን ሰውና ዕድል እንዳናይ ዕንባ ሸፍኖናል ። ኀዘነተኛን ሰው ሁሉም ይርቀዋል ። ደስታ ግን እንደ ሽቱ ከሩቅ ይጠራል ። ደግሞም ኀዘን ኀዘንን ፣ ደስታ ደስታን ይጠራል ። ፈገግ ስትሉ ሰው ሁሉ ፈገግ ይላል ። የዘራችሁትን ታጭዳላችሁና ደስታን ዘርታችሁ ሐሤትን እጨዱ ።
ቀናችሁ ይባረክ !
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ነሐሴ 28 ቀን 2018 ዓ.ም.
9 270
“ከተማይቱን አይቶ አለቀሰላት” /3
ጌታችን ወደ ኢየሩሳሌም የገባው በፋሲካ ሰሞን ነው ። በዓል ሊያከብሩ የመጡ ፣ የተስፋ አገራቸውን ናፍቀው የተሰበሰቡ አይሁድ ዘመዶቻቸውን በማግኘት በዚህ ሁሉ ደስታ ውስጥ ነበሩ ። ምንም እንኳ በሮማውያን ቅኝ ገዥነት ልባቸው ቅሬታ ቢኖረውም ጎዳናዎቹንና ሕንፃዎቹን እያዩ ይዘናጉ ነበር ። ከተማይቱ በታላቅ ምቾት ውስጥ ብትመስልም ከፊት ለፊት ግን የተደገሰላትን ሞት ነዋሪዎችዋ አልተረዱም ነበር ። ሕንፃዎች ተደጋግፈው የሚቆሙት ሰዎች ኅብረት ሲኖራቸው ብቻ ነው ። ማኅበረሰብ ሲፈርስ ሕንፃዎችም በግድ ይፈርሳሉ ። ሰው ሲፈርስ ለሰው የሆነው ሁሉ አብሮ ይፈርሳል ። መገዛዛት ፣ አንዱ የአንዱን ድርሻ በቅሚያ መብላት ፣ ገዥዎችን ተጠግቶ ሌላውን ማጥቃት በዚያች ከተማ ትልቅ ቂም አርግዞ ነበር ። ጌታችን ባሻገር ያለውን አየ ። ስለዚህም ከቀኑ በፊት ለከተማይቱ አለቀሰላት ። በቀኑ የሚያለቅሱ የቅርቡን ብቻ የሚያዩ ሰዎች ናቸው ። የሩቁን የሚያዩ ግን ቀድመው ያለቅሳሉ ። አዋቂ ሰው ችግሩን ሳይሆን የችግሩን ጥላ ቀድሞ ያያል ። ጥበብ ችግርን መፍታት ብቻ ሳይሆን መጪውን ችግር ማየትም ነው ። ዝናቡ ከመምጣቱ በፊት የሚጠለል ሰው አለ ፣ ዝናቡ ካባራበት በኋላ ጥላ የሚፈልግ አለ ። ያቺ ከተማ በጸጥታ ግድያ ውስጥ ነበረች ። በሞትዋ ላይ ተኝታ ነበርና ጌታ አለቀሰላት ። መላ አጥተው የሚሞቱ በትንሹ ያስለቅሳሉ ፣ መላ እያላቸው የሚሞቱ ግን በብዙ ያስለቅሳሉ ። አባ መላ ክርስቶስ ነው ።
ጌታችን ቁልቁል ከደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሁኖ ሲመለከት የበጎች በር ይታየው ነበር ። ይህ በር ለዓመታት ለመሥዋዕት የሚሆኑ በሮች የሚገቡበት ነበር ። በዚህ በር ሰዎች አይገቡም ነበር ። ጌታችን ግን በዚህ በር ገብቶ እንደ ነበር እናነባለን (ዮሐ. 5 ፡ 2) ። እርሱ ለመሥዋዕትነት ስለ መጣ ፣ በሚሰብር አውሬ ሳይሆን በሚታረድ በግ መልክ ስለ መጣ በዚህ በር ገባ ። በዕለተ ሆሳዕናም የበጎችን በር ሲያይ ለዓለም የሚሠዋበት ጊዜ ቀርቦ ነበር ። ለራሱ ለማዘን ፣ ትንሽም ለመተከዝ ምክንያት ነበረው ። እርሱ ግን ዘመኑን በሙሉ መስቀሉን ተሸክሞ ኖረ ። የዚህ ሕመም ከፍ ያለ ነው ። እንደሚሞቱ የተነገራቸው ፣ ዓመት ቀራችሁ ፣ ወራት የሚባልላቸው ሰዎች ምን ያህል ጉዳት እንደሚያስተናግዱ ይታወቃል ። የሚሞትበትን ቀን ያውቀዋልና ዘመኑን በሙሉ በመስቀል ሕመም ውስጥ ኖሮአል ። ቀራንዮን ማዶ እያየ የእኛን መዳን አስቦ ይደሰት ነበር ። ዕለተ ሞቱን እንደ ሽልማት ቀን ናፈቃት ። የኢየሩሳሌምን ሞት ባሰበ ጊዜ አለቀሰ ። ከተማ ሰው ነው ፣ ሰው ከተማ ነው ። ሰው ከሌለበት ከተማው ቆንጆ የመቃብር ስፍራ ነው ። ደግሞም የአራዊት መፈንጫ ፣ ጭውታው የፍርሃት ምንጭ ነው ።
በመስቀሉ ጥላ ውስጥ ቢሆንም ለተደላደለችውና ለምትስቀው ከተማ አለቀሰ ። በርግጥም የጥፋትዋ መንስኤ አዳኙን አለመቀበል ነው ። ፍቅርን የማይቀበል ጭካኔን ይቀበላል ። ዛሬ የምናሳልፈው ችግር ምናልባት ትላንት የቀለድንበት በረከት ግፍ ይሆናል ። ዛሬ በሚጠሉን እጅ የወደቅነው የሚወዱንን አሰቃይተን ሊሆን ይችላል ። እንኳን የፍቅር የውኃም ጡር አለው ። ቀራንዮ የሞሪያ ተራራ ነው ። በዚህ ተራራ ላይ ይስሐቅ በአባቱ ሊሠዋ ነበር ። እግዚአብሔር ግን ለአብርሃም ራርቶ ነጭ በግ አዘጋጀለት ። ያ በግም የይስሐቅ ቤዛ ሆነ ። ያ በግ የአዳምን ምሳሌ የሆነው የይስሐቅ ቤዛ ነበር ። በዚያ በግ ውስጥ አብርሃም ባለ መስቀሉን ኢየሱስን አየው ። ሁለት ሺህ ዓመታት የሚጨባበጡበት ጊዜ እየደረሰ ነው ። የኦርና አውድማ በዚሁ በቀራንዮ ነበር ። የመጣው መቅሰፍት እንዲመለስ ዳዊት መሠዊያ የሠራበት ስፍራ ነው ። ይህ ስፍራ ከኦርና በገንዘብ የተገዛ ነው ። (2ዜና 3፡1፤ 2ሳሙ. 24፡18-25)። በዚህ ስፍራ ማለትም በቀራንዮ ሰሎሞን መቅደሱን ሠራ ። ለስርየተ ኃጢአት ብዙ መሥዋዕቶች በዚህ ስፍራ ላይ ቀርበዋል ። ጌታችንም በመጨረሻ ሳምንት ወደዚህ ስፍራ ገሰገሰ ። እርሱ የመሥዋዕቶች ሁሉ መደምደሚያ ነው ።
ለይስሐቅ የሰጠውን ተስፋ እያሰበ ነው ፣ ሕዝቡን በመቈጠሩ ምክንያት በዳዊት ላይ ቍጣ መጥቶ ነበር ። ይህን ያህል ወገን አለኝ ብሎ ለመመካት ባደረገው ነገር እግዚአብሔር አዝኖበት ነበር ። በኦርና አውድማ በቀረበው መሥዋዕት መዓቱን የከለከለው ጌታ ዛሬ በለቢሰ ሥጋ ያንን ስፍራ እያየ ነው ። መሥዋዕቱና መራራውን ምርጫችንን ለማጣፈጥ የሚጤሰውን ዕጣን አሰበ ። እነዚያ ወገኖች ግን መታደላቸውን አላወቁትም ። አንድን ግዙፍ ዋርካ ተሸክሞ ከግብጽ ነቅሎ ከነዓንን ላይ ተከለ ። ይህን ያህል ዘመን ተሸክሞ ሳይደርቅ በኢየሩሳሌም ላይ ተከለው ። እነርሱ ግን የመጨረሻውን ተስፋቸውን አጨለሙት ። በሰማይና በምድር ያሉትን ስጦታዎች ሁሉ የሚጠቀልል አንድ ስጦታ አለ ፣ እርሱም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው ። የሚገርመው ይህን ስጦታ እምቢ ላለች ከተማ አለቀሰ ። ማልቀስ ምክርን ለናቀ ሰው ነው ።
የሚገርመው ከነዓንን ሲያወርሳቸው ጣዖታውያንን ነቅሎ ነው ። አሁን ግን እኔነታቸውን የሚወዱ ጣዖታውያን ሆነዋል ። ያ የከነናውያን ጽዋ እንደሚደርስባቸው ዘነጉ ። በነቢያት የሚያፌዙ ፣ ቅዱሳንን የሚገድሉ ሆኑ ። ይህን ሁሉ ደግሞ የሚያደርጉት እግዚአብሔርን ለማስከበር እንደሆነ ያስቡ ነበር ። ክርስቶስን በቅጽበት ራእይ ቢያዩት ፣ በሕልም ቢመለከቱት ሲነቁ ያስደነግጣል ። ደስታውም ፍርሃትን ይታገላል ። 33 ዓመት ከ3 ወር ሥጋ ለብሶ ቢያዩት አልደነገጡም ። ፍቅሩና ውለታው የማያስደነግጠን የእኛ ወኪሎች ነበሩ ። ኔሮን ቄሣር መግደል ቢታክተው ምነው የሰው ሁሉ አንገት አንድ በሆነልኝ አለ ይባላል ፣ ኢየሱስ ግን የሰውን ሁሉ ሞት ይወስዳል ። ከቁምነገር ይልቅ ዋዛን ለመረጡት አለቀሰላቸው ። ዛሬም የዘላለም ሞት እየጠበቃቸው የሳቅ ኮክቴል ለሚሹት ይህ ልቅሶ ይመለከታቸዋል ። በእውነት ወደ ክርስቶስ መጥቶ በባዶ የተመለሰ የለም ።
ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ነሐሴ 27 ቀን 2018 ዓ.ም.
9 270
የእግዚአብሔር ቤተሰቦች
ዛሬ የቀጥታ ስርጭት አይኖረንም።
አሁን ትምህርት ይለቀቃል አዳምጡ!
የትምህርት ርእስ :- ክርስቶስ በኦሪት ዘፍጥረት
ክፍል 4
ይህን ትምህርት በደንብ ተከታተሉ
የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ከሁላችን ይሁን!
9 270
በዛሬው የዓርብ መርሐ ግብር የሚለቀቀውን ትምህርት እንድትሰሙ እንጋብዛለን!
ክርስቶስ በኦሪት ዘፍጥረት
ክፍል 2
አሁን ያለቀቃል ፣ አድምጡ
https://t.me/Nolawii
