fa
Feedback
Nolawi ኖላዊ

Nolawi ኖላዊ

رفتن به کانال در Telegram

ይህ ቻናል ኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊ ትምህርቶች የሚተላለፉበት ነው። እግዚአብሔር አገልግሎቱን ያስፋ! 0911699907 ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

نمایش بیشتر
9 031
مشترکین
+1024 ساعت
+587 روز
+13730 روز
آرشیو پست ها
የእግዚአብሔር ቤተሰቦች! በዚህ ክረምት ከዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሥራዎች የመጻሕፍት ስጦታ ለተማሪዎች፣ ለእስረኞች፣ መግዛት ለማይችሉ ፣ ለቤተ መጻሕፍት ለመስጠት አስበናል። ይህን በረከት ለመሳተፍ የምትፈልጉ ቀጥሎ ባለው አካውንት የፈቀዳችሁትን መስጠት ትችላላችሁ ። ያስገባችሁበትን በቴሌግራም 0911699907 ላኩልን ! የእግዚአብሔር በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን! አሸናፊ መኰንን ወርቁ Ashenafi Mekonnen worku  የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 1000165078482

ዓለም ዋሾ እመጣለሁ ብላ ትቀራለች ፣ ቀረች ሲባል ትመጣለች ። ስትመጣ ሰላምታ ፣ ስትሄድ ስንብት አታውቅም ፣ ዓለም መግቢያና መውጫ የላትም ። ዓለም ዋሾ ! በልብ እየከዳች በአፍ መተማመኛ የምትሰጥ ፣ እወድሃለሁ ያለችውን በርግጥ የምትጠላ ፣ ያከበረችውን የምታዋርድ ፣ የናቃትን የምትሰጋ ፣ ጭር ሲል የማትወድ ፣ በሞቀበት የምትገኝ ፣ የጠገበውን እየተናነቀው የምታጎርስ ፣ የራበውን በጥይት የምትሸኝ ዓለም ዋሾ ናት ። ዓለም ዋሾ ! ሁለት ቃል የምትናገር ፣ ሁለት ቃል የምታናግር ፣ ያመሰገነችውን ሳትራገም እንቅልፍ የማይዛት ፣ ሲነጋ እንደ ባንዲራ የምትሰቅል ፣ ሲመሽ የምታወርድ ዓለም ዋሾ ናት ። ያላትን የምትደብቅ ፣ የሌላትን አለኝ የምትል ፣ ጉረኝነት የአፍ መጉመጥመጫዋ ፣ አምላክ ላትሆን ከአምላክ የምትለይ ፣ ያረጀውን ሕፃን ነህ ፣ ክርስቲያኑን ሰው እኮ ነህ እያለች ለማረድ የምታሰባ ፣ ክብርን አዋርዳ ገንዘብ የምትከፍል ፣ አካልን አርክሳ ወርቅ የምትሸልም ፣ ሬሳ አስከምራ ሥልጣን የምትሰጥ ፣ ትራስ አቅርባ እንቅልፍ የምትነሣ ፣ ቤት አድላ ደጅ የምታሳድር ፣ ጤናን ነሥታ ዝናን የምትቆልል ዓለም ዋሾ ናት ። ሲገናኙ መሳቅ ሲለዩ ቦጨቅ ፣ የሰው ሥጋ በጾም በበዓለ ሃምሳ የምታወራርድ የሐሜት ገበታ ፣ ቀን በጨለመበት ላይ መብራት የምታጠፋ ፣ በወደቀው ላይ ምሣር የምታበዛ ፣ የበለው ቤት ፣ የውርደት ቀሚስ ሰፊ ዓለም ዋሾ ናት ። ጃንሆይ ያለችውን ሌባ ሌባ የምትል ፣ ቤተ መንግሥት ያኖረችውን እስር ቤት የምትሰድ ፣ አቡነ ያለችውን ቀሚስ ገልባ የምትሰድብ ፣ ቅዱስ ያለችውን ርኵስ ብላ የምትሰቅል ፣ ሕግ ያላት ወንጀለኛ ፣ ዳኛ ያላት የፍትሕ ቀበኛ ፣ ሰገነት ላይ አውጥታ የምትከሰክስ ፣ አመሏን ለርካሾች የምታወርስ ዓለም ዋሾ ናት ። ንጋቷ ምሽት ፣ ቀትሯ እኩለ ሌሊት የሚተካው ፣ እንዳማሩ መኖር ፣ እንዳበሩ መቅረት የሌለባት ዓለም ዋሾ ናት ። ተቀጣጥረው የማይገናኙባት ፣ ተነፋፍቀው የሚጣሉባት ፣ ተዋደድኩ ብለው የሚጋደሉባት ፣ ሰርግና ሞት ያለ ወረፋ የሚገናኙባት ፣ ሙሽራው ሬሳ ሁኖ የሚቀበርባት ፣ ለደስታ የተተኮሰው ሰውን የሚገድልባት ፣ ሳቅና እንባ በጠባብ መንገድ የሚገናኙባት ፣ የክብርን ድንበር ሲጨርሱ የውርደት ከተማ የሚደርሱባት ፣ የወጣው ለመግባቱ እርግጠኛ የማይሆንባት ፣ የተኛው ለዘላለም የሚያንቀላፋባት ፣ ለሁሉ ጎዶሎ ቀንን ለመስጠት አድብታ የምትጠብቅ ዓለም ዋሾ ናት ። የመልክ ሌባ ፣ የቁንጅና ባላጋራ ፣ የጉልበት ሰራቂ ፣ የቦክሰኛው እጅ ሽባ የሚሆንባት ፣ ሯጩ በጋሪ የሚሄድባት ፣ እንዳማሩ መሞት የማይገኝባት ፣ የሰጠችውን እንደ ሕፃን ቶሎ የምትቀበል ዓለም ዋሾ ናት ። አገኘሁ ብለው ተናግረው ሳይጨርሱ ማጣት የሚንኳኳባት ፣ አፈቀርሁ ብለው ምራቅ ሳይደርቅ የሚካሰሱባት ፣ ባልና ሚስት ባላጋራ የሚሆኑባት ፣ ሬሳው ሳይወጣ እያለቀሱ ስለ ውርስ የሚያስቡባት ዓለም ዋሾ ናት ። ዓለም ዋሾ ! ከተወለዱ ቀን ጀምሮ ወደ ሞት የሚሄዱባት ፣ ጥርስ እየተሰበረ ፣ ዓይን እየደከመ ፣ እጅ እየታሰረ ፣ እግር እየዛለ በየዕለቱ ሞትን የሚለማመዱባት ፣ ማለዳዋ ወደ ሠርክ ፣ ሠርኳ ወደ ጨለማ የሚገሰግስባት ዓለም ዋሾ ናት ። ምንም ቢሰነብቱ መቅረት የሌለባት ፣ ምንም ቢያካብቱ ባዶ እጅ የሚሄዱባት ፣ ሕፃኑን በነጭ ጨርቅ ተቀብላ ፣ ሟቹን በነጭ ከፈን የምትሸኝ ዓለም ዋሾ ናት ። ጦርነትን እያወገዘች የጦር መሣሪያ የምታቀርብ ፣ በአደባባይ እየተሞናሞነች በጓዳ የምታጋድል ፣ ሕጋዊ ውሸት ያላት የዲፕሎማሲ ባለ ቀሚስ ፣ የጋራ ጥቅም እንጂ የጋራ ፍቅር የሌላት ፣ ምን አገኛለሁ እንጂ ምን እሰጣለሁ የማትል ዓለም ዋሾ ናት ። ማለፏ መድኃኒት ፣ ማለፋችን ዕረፍት ነው ። ድንኳን ናትና ዓለም ትፈርሳለች ፣ እውነተኛው ቤታችን በሰማይ ነው ። የወረት ዓለም ሲፈርስ የእውነት ዓለም ይገለጣል ። እርሱም የሰማዩ መንግሥት ነው ። ዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሐምሌ 21 ቀን 2018 ዓ.ም.

photo content

የእሑድ የማለዳ ስብከት ዛሬ አይኖረንም!

የእግዚአብሔር ቤተሰቦች! በዚህ ክረምት ከዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሥራዎች የመጻሕፍት ስጦታ ለተማሪዎች፣ ለእስረኞች፣ መግዛት ለማይችሉ ፣ ለቤተ መጻሕፍት ለመስጠት አስበናል። ይህን በረከት ለመሳተፍ የምትፈልጉ ቀጥሎ ባለው አካውንት የፈቀዳችሁትን መስጠት ትችላላችሁ ። ያስገባችሁበትን በቴሌግራም 0911699997 ላኩልን ! የእግዚአብሔር በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን! አሸናፊ መኰንን ወርቁ Ashenafi Mekonnen worku  የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ 1000165078482

2018-11-17 የታዳጊ ወጣቶች ፈተና 1.m4a40.94 MB

2:00 ትምህርታችን ይጀምራል

ዛሬ ዓርብ ሐምሌ 17 ቀን 2018 ዓ.ም. ከምሽቱ 2:00 ሰዓት  ላይ ትምህርታችን ይጀምራል :: የትምህርታችን ርእስ " የታዳጊ ወጣቶች ፈተና ሉቃ.15፥11 ማስታወሻ ብትይዙ ይመከራል። ሌሎች ወገኖቻችንንም ጋብዙ https://t.me/Nolawii

የባለጠግነት ፈተና/2 ባለጠጋ መሆን ኃጢአት አይደለም ። አብርሃም ፣ ይስሐቅ ፣ ያዕቆብ ፣ ዳዊት ፣ ሰሎሞን ፣ ኒቆዲሞስ ፣ ዮሴፍ ዘአርማትያስ ባለጠጎች ነበሩ ። እግዚአብሔር የሀብታት ባለቤት ነውና ሀብትን ለሰዎች ይሰጣል ። በምድር ላይ ያለውን መሬት ፣ ወርቅና ብር ስለ ያዙ ሰዎች ባለጠጋ ይባላሉ ። ምድርና ሞላው የእግዚአብሔር ነውና የባለጠግነታቸው ምሥጢር እርሱ ነው ። ባለጸጋ ማለትም ባለ ስጦታ ፣ ተቀባይ ፣ ባለ አደራ ፣ ተጠያቂነት ያለው ማለት ነው ። ሀብት ተጨማሪ ኃላፊነት መሆኑን ብዙ ሰዎች አያውቁም ። አብርሃም በሀብቱ እንግዶችን ይቀበልና ያስተናግድ ነበረ ፣ ዳዊት ለእግዚአብሔር ቤት መሥሪያ ያስቀምጥ ነበር ፣ ሰሎሞን መቅደሱን ሠራ ። የእስራኤል ልጆች ከግብጻውያን በበዘበዙት ብርና ወርቅ የማደሪያውን ድንኳን ተከሉ ። ብዙ ሴቶችም ጌታችንን በገንዘባቸው ያገለግሉት እንደ ነበር ተጽፎአል (ሉቃ. 8 ፡ 3) ። ቆሞ የሚሰብከውን ሰባኪ ያህል በገንዘብም ማገልገል ይቻላል ። ሰው የሚያገለግለው በተሰጠው ነገር ነው ። የተሰጠን ነገር ማገልገያችን እንጂ ራሳችንን እንደ ጌቶች የምናይበት አይደለም ። ገንዘብ አገልጋይ ባሪያ ፣ መገልገያ ቁስ ሲሆን የእግዚአብሔርን ቤት መሥራት ይችላል ። ባለጠግነት ኃጢአት ባይሆንም ለመንፈሳዊነት ፣ ለሥነ ምግባር ተጨማሪ ፈተና ሲሆን ይታያል ። ገንዘብ አመሉን የማይወስድበት ሰው የጸና አቋም ያለው ሰው ነው ። ገንዘብ መልካሙን ጠባይ ወስዶ የራሱን ክፉ ጠባይ ይሰጣል ። በማቴዎስ 19 ላይ የምናገኘው ወጣት ባለጠጋ የነበረው ፣ ሀብት ጌታን እንዳይከተል እንቅፋት ሆኖበት ነበር ። ይህን ሰው አላውቀውም ብንል ለእርሱ የተነገረውን ቃል ግን እናውቀዋለን ። “ባለጠጋ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ከሚገባ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢገባ ይቀላል” የሚለውን ሁላችንም እናውቀዋለን ። ባለጠጎች ሲያናድዱን የምንጠቅሰው ስለሆነ ነው ። በኢየሩሳሌም ትንሽ በር ነበረ ። ይህ በር የመርፌ ቀዳዳ የሚል ስያሜ ነበረው ። ግመል በዚህ በር ለማለፍ ከነጭነቱ አይችልም ፣ ራሱም ቆሞ ማለፍ አይችልም ። ስለዚህ ተንበርክኮ ማለፍ ነበረበት ፣ እየታከከ ሲያልፍም ቆሻሻውን ያራግፍ ነበር ። ግመል ወርቅ ፣ ዕጣን ፣ ሽቱ ጭኖ የሚጓዝ ነው ። እነዚህ ነገሮች ውድ ቢሆኑ እንኳ እነርሱን ተሸክሞ በዚያ በር ማለፍ አይችልም ነበር ። ራሱም መንበርከክ ነበረበት ። ሰው በሀብቱ አሊያም በትምክሕቱ ሁኖ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት አይችልም ። የሰጠውን ለሰጠው ጌታ መልሶ መስጠት አለበት ። የባለጠግነት ፈተና፡- የዝና ጥማት ሰዎች ባለጠጋ ከሆኑ በኋላ ዝናን ይፈልጋሉ ። ዝናን በሥራ ካጡት ዝነኞችን በመጠጋት ለማግኘት ይመኛሉ ። ብዙ ባለጠጎች ከድሀ ጋር ሳይሆን ከዝነኛ ጋር የሚውሉት ለዚህ ነው ። ዝነኛው ብር የለውም ፣ ባለጠጋው ዝና የለውም ። ይልቁንም ወጣት ባለጠጎች እውቀትን ይሰበስባሉ ፣ እውቀታቸው በራሱ ሀብት መሆኑን ስለማያምኑ ለገንዘብ ማግኛ ብቻ ይጠቀሙበታል ። ገንዘብ የኪስ ሀብት ፣ እውቀት የነፍስ ሀብት ቢሆንም እነርሱ ግን የነፍስ ሀብትን ለኪስ ሀብት ያስገዛሉ ። ወጣት ባለጠጎች መሽቀርቀር የሚወዱ ግን ስስታሞች ናቸው ። ወጣት ባለጠጎች ንግግር አሳማሪ ፣ የተጠና ውሸት ባለቤትና እጅግ ብልጥ ናቸው ። ማንን ቢጠጉ ምን ማግኘት እንዳለባቸው የሚያሰሉ ፣ ምን አገኛለሁ  እንጂ ምን እሰጣለሁ  ለማለት ያልታደሉ ናቸው ። የሚቆጠበውም ሲኖር ነው ፣ ቢሆንም የሚሰጡትም ሲኖር ነውና ባለጠጎች ቸር መሆን አለባቸው ። ያልራበውን ይሉኝታ ለማስያዝ ፣ የሀብትን መጠን ለማሳየት በየቀኑ በሚሊየን ሲጋብዙ ይውላሉ ፣ ለድሀ ድቃቂ ሣንቲም ለመስጠት ግን ይታመማሉ ። ቤተ ክርስቲያንንም የዝናቸው አደባባይ ለማድረግ የሚሹ አሉ ። ወንጌልን የሚገፉ ፣ ገንዘባቸውን ሊቃውንት ለማሳደድ የሚበጅቱ ያልታደሉ አሉ ። በዚያው መጠን የእግዚአብሔርን ቤት የሚሠሩ ጥቶች ይኖራሉ ። ዓለሙ ግን አንድ ማኅበረተኛ ስለሆነ ሐሰተኛው ባለጠጋ ሐሰተኛ አገልጋይን ይደግፋል ። ዝና ታዋቂነት ነው ፣ ከበሬታ በአደባባይ እጅ የመነሣት ጥማት ነው ። የብዙዎች የዕለት ርእስ መሆንን ብዙ ባለጠጎች ይመኛሉ ። ከባለጠግነት ቀጥሎ ያለው ዝና ሳይሆን የድሀ ልጆች ማሳደጊያ ፣ የአረጋውያን መጦሪያን መገንባት ነው ። ማግኘት እንዳለ ማጣት አለ ፣ በሚጠፋ ገንዘብ የማይጠፋ ሥራ መሥራት ዕድለኝነት ነው ። ገንዘብ ብንጨብጠውም ልናየው ግን ላንበላው እንችላለን ። የበዪ ተመልካች ለመሆን ፣ ለነጻ ዘበኝነት ገንዘብን መያዝ ጥቅም የለውም ። ወጣቱ ባለጠጋ ጌታ ዝነኛ ነውና በአደባባይ መምህር ሆይ ብዬ ባመሰግነው እርሱም የክብር ቃል ይሰጠኛል ብሎ የመጣ ነው ። የእገሌ ሰርግ ጳጳሳት የተገኙበት ነው ይባላል ። ሰርግን ክቡር የሚያደርገው ዓላማውና በአንዲት ክህነት መከናወኑ ነው ። ቡራኬው አንድ ነው ። የእገሌ ልቅሶ ጳጳሳት የታደሙበት ነው ይባላል ፣ ተገኙ እንጂ ሬሳውን አያሥነሡትም ። የባለጠጋ ጸሎተ ፍትሐቱ ረጅም ነው ፣ ድሀውን “አፈር ነህና ወደ አፈር ትመለሳለህ” ብለን አቻኩለን ስንሸኝ አምላካችን ይታዘበናል ። ዓለም የጥቂቶች ናት ፣ እግዚአብሔር ግን የሁሉ አምላክ ነው ! የዓለም ታሪክ የምንለው የጥቂት ግለሰቦች ታሪክ ነው ፣ የዓለም ታሪክ የማያውቃቸው በልበ ሥላሴ የተጻፉ ግን አያሌ ናቸው ። ይቀጥላል ዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሐምሌ 17 ቀን 2018 ዓ.ም.

የባለጠግነት ፈተና   “ሂድና ያለህን ሸጠህ ለድሆች ስጥ ፥ መዝገብም በሰማያት ታገኛለህ ፣ መጥተህም ተከተለኝ” የሚለው ቃል ታላቁ ቅዱስ እንጦንስ ሁሉን ትቶ ጌታን የተከተለበት ፣ በረሃ ገብቶ የመነኮሳት አባት የሆነበት ነው (ማቴ. 19 ፡ 21) ። ይህ ቃል ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ ፣ አባ ጳኵሚስና ብዙ መነኮሳት ዓለምን የናቁበት ንብረታቸውን ሸጠው ለድሆች የሰጡበት ነው ። ያላቸውን ሁሉ ሸጠው መከተል ለሁሉም ባለጠጎች የተላለፈ መልእክት አይደለም ። አንዳንዶች በሀብታቸው ለእግዚአብሔር አሥራት ፣ ለድሆች ምጽዋት እየሰጡ ለማገልገል ተጠርተዋል ። አንዱ በሰማዕትነት ፣ አንዱ በሰባኪነት ፣ አንዱ ያለውን ሁሉ ሸጦ ለድሆች በመስጠት ፣ ሌላው ከሀብቱ ላይ በመስጠት እግዚአብሔርን ያገለግላሉ ። ጥሪና አገልግሎት ለየራስ ነው ። የሚገርመው ሂድና ያለህን ሸጠህ ለድሆች ሰጥተህ ተከተለኝ የተባለው ሰው ይህን ምክር አልተጠቀመበትም ። እያዘነ ወደ ቤቱ ተመለሰ ። ለእርሱ የተነገረው ቃል የመነኮሳት አባት የሆነውን ቅዱስ እንጦንስን ከዓለም ለየ ። እኛ እየተመከርን የምናፈሰውን ቃል አጠገባችን ተቀምጦ የሚሰማው ሊታነጽበት ይችላል ።   “ከሞኝ ደጃፍ ሞፈር ይቆረጣል” እንዲሉ የእውቀት ቤት ከሆነችው ከቤተ ክርስቲያን ተቀምጦ የማይማር ፣ አሳቢ አባት ሳለው ራሱን የማይችል ፣ ሊቅ አጠገብ ተቀምጦ የሚያፌዝ ብዙ ሰው አለ ። የሩቁ የሚያከብራቸውን የቅርብ የሚንቃቸው ብዙ ታላላቅ የጸሎትና የምክር ሰዎች አሉ ። ዕድል ያልመጣችበት ጊዜ የለም ፣ ብዙ ሞኞች ግን ዕድል ታልፋቸዋለች ። አገራችንን ብንመለከት የራስዋን ሊቃውንት ታሳድዳለች ፣ የፈረንጅ አማካሪን ግን በውድ ዋጋ ትገዛለች ። ነቢዩ ኤልሳዕ ግያዝ የሚባል ደቀ መዝሙር ነበረው ፣ የሶርያው ትልቅ ባለሥልጣን ወርቅና ብር ከንቱ ነው አያድንም ብሎ ወደ ኤልሳዕ መጥቶ ተፈወሰ ። እጅ መንሻም ለኤልሳዕ መስጠት በፈለገ ጊዜ ኤልሳዕ እምቢ አለው ። ለእግዚአብሔር ሰው መስጠት ተገቢ ነው ፣ ለሠራተኛው ደመወዙ ይገባዋልና አገልጋዩም በጸሎት መቀበል አለበት ።   ንዕማን የተባለው የሶርያ ባለሥልጣን ግን ከአረማውያን ወገን ነበርና ፈውስን በገንዘቡ የገዛው  መስሎ እንዳይሰማው ፣ ክብርን ሁሉ ለእግዚአብሔር እንዲሰጥ ፣ ልቡም ለእስራኤል አምላክ እንዲማረክ ኤልሳዕ እምቢ አለው ። ከማያምን ሰው ገንዘብን ሳይሆን ልቡን መቀበል አስፈላጊ ነው ። የእግዚአብሔር ሥራ አማንያን አምነው በሚሰጡት ገንዘብ መከወን አለበት ። የሶርያው ንዕማን ብርና ወርቅን ንቆ ወደ ድሀው ነቢይ ሲመጣ ፣ የነቢዩ ደቀ መዝሙር ግያዝ ግን ብርና ወርቅን በማታለል ሲፈልግ እናያለን ። የገንዘብ ፍቅር ለምጻም ያደርጋል ፣ መልክን ያጠፋል ። ውስጥን ያዥጎረጉራል ። ሚና የሌለው ሰው ያደርጋል ። ስሙ አንቱ ፣ ሥራው ግን አንተ የሆነ ማንነትን ይሰጣል ። ከደቀ መዝሙርነት ጥሪ ያፈናቅላል ። ጌታን እንዲሸጡ ያደርጋል ። ግያዝ የኤልሳዕ ጸጋ የሚያርፍበት ተተኪ ነበረ ፣ ከጸጋ ይልቅ ገንዘብን መረጠ ። ያንን ገንዘብ አልበላውም ፣ መልኩም ጠፋ ። ይሁዳም ታንቆ ሊሞት ፣ ገንዘቡንም በሜዳ ሊበትን ጌታን ሸጠ ። ነቢዩ ኤልያስ ኤልሳዕን የመሰለ በድርብ ጸጋ የሚያገለግል ተማሪ አገኘ ፣ ኤልሳዕ ግን ተተኪ አላገኘም ። ተተኪ ማጣት እውነተኞቹ መምህራንም ይገጥማቸዋል ።   በማቴ. 19 ላይ የምናገኘው ባለጠጋ ለእርሱ የተሰጠውን ምክር በዘመናት የተነሡ አባቶች ተጠቀሙበት ። “ሂድና ያለህን ሸጠህ ለድሆች ስጥ ፥ መዝገብም በሰማያት ታገኛለህ ፣ መጥተህም ተከተለኝ” የሚለው ቃል ለነ ቅዱስ እንጦንስ የጥሪ ደወል ነበረ ። አገርን በጸሎታቸው አጥር ሁነው የጠበቅዋት ፣ ቤተ ክርስቲያንን በአገልግሎት ያስከበሩአት ብዙ መናንያን የወጡት በዚህ ቃል ነው ። ታላላቅ ዩኒቨርሲቲዎች ገዳማት የነበሩ ፣ መነኮሳት እውቀትን ያስፋፉበት ፣ ለተማሪዎች የለቀቁት ስፍራ ነው ። በአገራችንም ገዳማት የፍልስፍና ፣ የቍጥር ትምህርት ፣ የቅኔ ፣ የትርጓሜ ፣ የዜማ ፣ የሥነ ጽሑፍ ፣ የመድኃኒት ቅመማ ፣ የቅርስ ጥበቃ ፣ የደንና የእጽዋት የምርምር ጣቢያ ፣ የፊደል ማስተማርያ ፣ የሥነ ልቡና መታከሚያ ናቸው ። የትምህርት ሚኒስቴር ሳይመጣ በፊት ለሁለት ሺህ ዓመታት ትምህርት ሚኒስቴር ሁና ያገለገለች የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ናት ። ለዚህ ትልቅ አስተዋጽኦ ያደረጉት የትምህርት ማዕከል የነበሩት ገዳማት ናቸው ። ያ ወጣት ባለጠጋ አዝኖ የሄደበት ቃል ብዙዎች በደስታ ተቀብለውት ለቤተ ክርስቲያን መቀጠል ፣ ለዓለም ሥልጣኔ አስተዋጽኦ ያደረጉበት ነው ። የባለጠግነት ፈተና ምንድነው ?   ዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሐምሌ 16 ቀን 2018 ዓ.ም.

ምን መጋጠም አለው ?   “ለእግዚአብሔር ቤተ መቅደስም ከጣዖት ጋር ምን መጋጠም አለው ? እኛ የሕያው እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ነንና” (2ቆሮ. 6 ፡ 16)   የብሉይ ኪዳኑ መቅደስ በኢየሩሳሌም የተወሰነው ብቸኛ የአምልኮ ማዕከል ነበረ ። በአዲስ ኪዳን ግን የክርስቲያኖች ሰውነትና የአማንያን ኅብረት መቅደስ ተብሎ ተጠርቷል ። እግዚአብሔር በአማንያን ሰውነት ላይ ያድራል ፣ በመካከላችንም ይገኛል ። እርሱ በአማንያን ሰውነት እንዲያድር መቀደስ ፣ በምእመናን መካከል እንዲገኝ አንድ መሆን ይገባል ። እያንዳንዱ በግሉ ሲቀደስ ኅብረቱም እውነተኛ እየሆነ ይመጣል ። ኅብረቶች እውነተኛ እንዲሆኑ እንመኛለን ፣ የግል ቅድስና ሲደረግ ኅብረቱም ንጹሕ እየሆነ ይመጣል ። እያንዳንዱ ቤቱን ቢያጸዳ ከተማው ጽዱ እንደሚሆን ምእመንም በግሉ ሲቀደስ ኅብረቱ እየተቀደሰ ይመጣል ። ጽዳት ከራስ ነው የሚባለው ለዚህ ነው ። ቤተ መቅደስ የሆነው አማኝና ኅብረቱ ከጣዖታት ጋር ትብብር ሊኖረው አይገባም ። ጣዖታት የሰው እጅ ሥራ ናቸው ። ሰውም ራሱ ለሠራው ነገር መስገድ ራሱን ማዋረድ ነው ። ጣዖታት የሚታዩ ቅርጾች ብቻ ሳይሆኑ በልባችን ላይ የእግዚአብሔርን ቦታ የያዙ ነገሮች ሁሉ ጣዖታት ናቸው ።   የጣዖት አምልኮ ከጥንት እስከ ዛሬ ትውልድን ሲበክሉ ኖረዋል ። በአል የሚባል ጣዖት ነቢዩ ኤልያስ የተቃወመው የዝናብ አምላክ ተብሎ የሚጠራ ነበር ። ጣዖታት አንዳንድ ፍጥረት እንዳላቸውና አንድ ግዳጅን ብቻ እንደሚወጡ ይታሰብ ነበር ። የፀሐይ አምላክ ፣ የጦርነት አምላክ ፣ የባሕር አምላክ እየተባለ ይጠሩ ነበር ። እግዚአብሔርን አኃዜ ኵሉ ዓለም ብሎ መጥራት ፣ ሁሉን የያዘ እያሉ ማመስገን ከጣዖታት ልዩና መንፈስ መሆኑን መመስከር ነው ። ሰባቱም የእንግሊዝኛ ስያሜ የሆኑት ቀናት የጣዖት ስም አላቸው ። ሰን ዴይ- የፀሐይ ቀን ማለት ነው ። መን ዴይ የጨረቃ ቀን ማለት ነው ። የወራቱ ስያሜም ጃንዋሪ ፣ ማርች ፣ ጁን ከሮማ ጣዖታት የተወሰዱ ስያሜዎች ናቸው ። የወሩ ዕለታት በጣዖታት በመሰየማቸው ወደ ክርስትና የመጡት አሕዛብ በዚያ ቀን ትዝታው ይረብሻቸው ነበር ። ይህን የጣዖታት ትዝታ ለማጥፋት በቅዱሳን ስም ቀኖችን መሰየም እየተለመደ መጣ ። በርግጥ የራሱ የሆነ የበዓላት ሥርዓት እንዳለም የታወቀ ነው።   ከከነዓን ጣዖታት የታወቀው በአል የሚባለው የዝናብ አምላክ ነው ። የሰው መሥዋዕት ይቀርብለት ነበር ። ሞሎክ የተባለ ጣዖትም የሕፃናት ግብር ይቀርብለት ነበር ። በኤፌሶን የነበረችው ጣዖት አርጤምስ አንድ ሺህ የሚጠጉ ሴተኛ አዳሪዎች ነበሩባት ። ዝሙትንም እንደ መሥዋዕት ያቀርቡ ነበር ። ጣዖታት መጀመሪያ ላይ የእንጨትና የድንጋይ ቅርጽ ናቸው ፣ ሰዎች አምልኮ ማቅረብ ሲጀምሩ ግን የአጋንንት ማደሪያ ይሆናሉ ። ሰይጣንም በገዛ ልጅ ሳይቀር እንዲጨክኑ በማድረግ የሰውን ሕሊና ለጭንቀት ይዳርጋል ። በዚህ ዘመንም ሀብት ለማግኘት የገዛ ልጆቻቸውን ግብር የሚሰጡ ፣ ሀብት ቢያገኙም በሚከስስ አእምሮ የሚመላለሱ ብዙ ምስኪኖች አሉ ። ከእያንዳንዱ ሀብት በስተጀርባ ወንጀል አለ የሚባለው ከእውነት የራቀ አይደለም ። ሰዎች ወደ ጣዖታት ሲሳቡ ከእግዚአብሔር ይለያሉ ። ሕያውን አምላክ በግዑዝ ስለ ለወጡ ታላቅ ቍጣን ያተርፋሉ ። ጣዖት አምልኮ አገርንም ያስረግማል ። ይህም ሰማርያ እንዴት በውኃ ጥም እንደ ተቀጣች የኤልያስን ታሪክ ስናነብ ይገባናል ።   ጣዖታት የሰውን መንፈስ ይረብሻሉ ፣ የሚያመልካቸውም እንደ እነርሱ ይሆናል ። መንፈሱ ይሞታል ። በትዳር ውስጥ ሰላምን ያሳጣሉ ፣ ልጆችን ባካና ያደርጋሉ ። ለሰማይና ለምድር ሠራዊት መስገድ ብቻ ሳይሆን ዕድልን ለማወቅ ሞራ መግለጥ ፣ መዳፍ ማንበብ ፣ አዋቂ የሚባሉትን መጠየቅ ጣዖት አምልኮና እግዚአብሔር የማይታገሠው ኃጢአት ነው ። የሚገርመው አጋንንታዊ መጠበቂያ የሚያሠሩ ሰዎች ናቸው ። የፈሩት እግዚአብሔርን ነው ? እግዚአብሔርን ሰግተው አጋንንትን ጠባቂ እያደረጉ ነው ? ወይስ ከአጋንንት በአጋንንት ለመዳን አስበው ነው ? የእውነትም ይሁን የውሸት መጠበቂያ አለን እያሉ የሚያወሩና የሚያስወሩ እግዚአብሔርን ንቀዋልና ይናቃሉ ። የአስማተኞች ጻዕር/ጣር እንኳ ልክ የለውም ። ሲኦልን በምድር የጀመሩ ፣ ጠላትን አለምዳለሁ ብለው የታሰሩ ናቸው ።   “ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ማንም የለም ፤ ወይም አንዱን ይጠላል ሁለተኛውንም ይወዳል ፤ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል ፤ ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም” ይላል ። (ማቴ. 6 ፡ 24) ። ገንዘብ ጣዖት ተብሏል ። ፍላጎታችን ፣ ሀብትና ዝና ፣ ሥልጣንና የምንወዳቸው ሰዎች ጣዖት ሊሆኑብን ይችላሉ ። በአጭር ቃል እምነት ፣ ተስፋ ፣ ፍቅር የምንጥልበት ሁሉ ጣዖት ነው።   አንዳንድ ሰዎች ክብር ምስጋና ይድረሰውና ለዘመናዊነት … እያሉ ያወራሉ ። ሥልጣኔንም የሚያመልክ አለ ። ልብ አድርጉ ሰው የሚቀጣው ባመለከው ነውና ሥልጣኔውም ወደ ጥፋት እንዳያደርሰን መጠንቀቅ ይገባናል ። እገሌ ከሌለ እኔ አልኖርም ማለት ጣዖት አምልኮ ነው ። በገዥዎች መመካት ጣዖት አምልኮ ነው ። የእኔ ዘርና ቋንቋ እያሉ መናገር ፣ የራስን ዘርና የራስን ቋንቋ ተናጋሪ ብቻ መውደድ ጣዖት አምልኮ ነው ። ብዙ ሰው የተሳሰረው በዘርና በቋንቋ ነው ። አገልጋይን እንኳ የሚቀርበው የአገሬ ልጅ ብሎ ነው ። ዘረኝነት ያሳንሳል ። ማነስ የማይሰለቻቸው በመጨረሻ ደቀው ይበናሉ ። ለሰው አካልና ቁንጅና ማዜም ፣ ስንኝ መግጠም ጣዖት አምልኮ ነው ። እንደ ዳዊት ግሩምና ድንቅ ሆኜ ተፈጥሬአለሁና አመሰግንሃለሁ መባል ነበረበት ።   እኛ መቅደስ ነንና ጣዖት ሊነካን አይገባም ። ከጣዖት ጋር ንክኪ ሊኖረን አያስፈልግም ። ለእግዚአብሔር የሰገደ ጉልበት ለሌላ ሊሆን አይቻለውምና ።   ዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሐምሌ 15 ቀን 2018 ዓ.ም.

እግዚአብሔር ያልመለሰው ጸሎት/2   አይሆንም አይሰጥህም   ስብከት ለማከናወን በጣም ደስ ይለናል ። በአደባባይ ቆሞ መናገር ያረካናል ። ሰዎችም የዛሬው ትምህርት ልዩ ነው ይላሉ ። ሰባኪውም ቅድሚያ ካልተሰጠው ፣ ሰዓቱን ካሳጠሩበት እየከፋው ይመጣል ። ለመስበክ ፣ የቤተ ክርስቲያን ማስተባበሪያ ሥራዎችን ለመሥራት የምንደሰተውን ያህል ለመጸለይ ደካሞች ነን ። ጸሎት ውጫዊ ሙገሳ ፣ የሰዎችን አድናቆት አያስገኝም ። በዚህ ምክንያት ምስጋና የሚወደው ፣ የሰዎችን ውዳሴ እንደ ተጠማ የሚኖረው ምስኪኑ ሥጋችን ጸሎትን ችላ ይላል ። ቢያደርገውም ያድፋፋዋል እንጂ ከልብ አይከውነውም ። የጸሎት ሕይወታችን ደካማ የሆነው ውዳሴ ከንቱ ስለማያመጣ ነው ። ስለ አገራችን ጸልየን እግዚአብሔር ድንቅ ነገርን አምጥቶ ቢሆን ሰዎች ግን ስለ አገር በአደባባይ ያወሩትን ሰዎች ያደንቃሉ ። እነርሱንም እንደ አርበኛ ይቆጥራሉ ። ዋናውን ሥራ የሠራው ጸሎተኛው ነው ። አዎ ስለ አገሩ ካወራው ስለ አገሩ የጸለየው ይበልጣል ። መጸለዩን ግን እግዚአብሔርና ራሱ ጸሎተኛው ብቻ ያውቁታል ። ልፋቱ በሰው ዘንድ የተደበቀ የሚመስለው ፣ ዋጋውን ከምድር የሚጠብቀው ፣ ፍርፋሪ ምስጋና የሚሻው ፣ አክብሮ ከሚያዋርደው ዓለም ገና ያልተለያየው ሰው ጸሎትን አይመርጥም ።   እግዚአብሔር ጸሎታችንን የሚከለክለን ደስታችን ስለማያስደስተው አይደለም ። ሕፃን ልጅ እሳት ለመንካት በጣም ይመኛል ፣ ወላጆቹ ግን ይከለክሉታል ። በመከልከላቸውም ጠባቂ ስለሆነው ፍቅራቸው እየገለጡ ነው ። እግዚአብሔር በመከልከል ይጠብቀናል ፣ ዕድሜአችንን ያረዝምልናል ። የጸሎት መልስ ብለን የምናስበው እሺ የሚለውን ብቻ ነው ፣ አይሆንም መልስ መሆኑን አልተረዳንም ። የፈለግነው ሁሉ ቢጠን ኖሮ እንኳን የእኛ ፣ የዓለምም ዘመን አይረዝምም ነበር ። ያልተመለሱ ጸሎቶቻችን የመኖራችን ምክንያት ናቸውና መታገሥ አለብን ። አይሆንም የተባልንበትን ጉዳይ በምስጋና መቀበል ያስፈልገናል ። ለእኛ ከሚጠቅመን ነገር የሚከለክል አምላክ የለንም ። ታላላቅ የምንላቸው የእግዚአብሔር ሰዎች ለምነው ያልተፈጸመላቸው ብዙ ናቸው ። ወደ እግዚአብሔር ልብ የቀረቡ ቅዱሳን ሰዎች “ጌታ ሆይ አንተን የሚያስከብርህ ከሆነ ስጠኝ ፣ አንተ የማትከብርበት ከሆነ አትስጠኝ” ብለው ልመናቸውን ያቀርባሉ ። ወደ መንፈሳዊ ብስለት ስንመጣ እግዚአብሔር ያልፈቀደው ነገር የእሳት ጠጠር እንደማፈስ መሆኑ ይገባናል ።   ታላቁ ነቢይ ሊቀ ነቢያት ሙሴ የተስፋይቱን ምድር አትወርስም በተባለ ጊዜ እግዚአብሔር እንዲራራለት ለመነ ። የተሰጠው ምላሽ ግን አስደንጋጭ ነው ።  “እግዚአብሔር ግን በእናንተ ምክንያት ተቈጣኝ አልሰማኝምም እግዚአብሔርም አለኝ፦ ይበቃሃል በዚህ ነገር ደግመህ አትናገረኝ ። ይህን ዮርዳኖስን አትሻገርምና።” (ዘዳ. 3፡26)። ይህን የተናገረው ራሱ ሙሴ ነው ። ሙሴ የመሪ ሽኝት እንኳ አልተካሄደለትም ። የራሱን መቃብር ቆፍሮ የሞተ ሰው ነው ። የእግዚአብሔር ሰው ኑሮው እንጂ መቃብሩ ያማረ አይደለም ። ጌታችንን የቀበሩት ሁለት ሰዎች ናቸው ። ነቢዩ ዳዊት ስለ ልጁ ሕመም ጸለየ ፣ ማቅ ለብሶ አመድ ነስንሶ ፣ በታላቅ ኀዘን ቢለምንም ልጁ ሞተበት ። እግዚአብሔር ባልሰማው ጊዜ ደስተኛ ነበረ (2ሳሙ. 12 ፡ 16-20)። ጌታችን ለእኛ አርአያ ሊሆን ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ ቢልም አላለፈችም (ማቴ. 26፡39)። ኑሮአችን እንደ ፈቃዱ እንዲሆን ብቻ ሳይሆን ሞታችንም እንደ ፈቃዱ እንዲሆን መጸለይ እንደሚያስፈልገን ሊያስተምረን ነው ። ቅዱስ ጳውሎስ በሕመም ሲሰቃይ እንዲርቅለት ብዙ ጊዜ ጸለየ ። የተሰጠው መልስ ግን አስደናቂ ነው ። “ስለዚህ ነገር ከእኔ እንዲለይ ሦስት ጊዜ ጌታን ለመንሁ ። እርሱም፦ ጸጋዬ ይበቃሃል ፥ ኃይሌ በድካም ይፈጸማልና አለኝ ። እንግዲህ የክርስቶስ ኃይል ያድርብኝ ዘንድ በብዙ ደስታ በድካሜ ልመካ እወዳለሁ።” (2ቆሮ. 12፡8-9)። የዘብዴዎስ ልጆች ዮሐንስና ያዕቆብ ሹመትን በፈለጉ ጊዜ ፣ እናታቸውን ሽማግሌ አድርገው በላኩ ሰዓት የምትለምኑትን አታውቁም ተብለዋል ።   በሌላ መንገድ እከፍልሃለሁ   እግዚአብሔር ጸሎታችንን ባልመለሰ ጊዜ በሌላ መንገድ ግን ይከፍለናል ። ሙሴ ልመናው አልተሰማም ፣ መቃብሩም አልታወቀም ። እስራኤል መቃብሩን ቢያውቁ ኖሮ ሙሴ ከተቀበረበት እንኖራለን ባሉ ነበር ፣ ደግሞም በሰይጣን ማታለል መቃብሩን ያመልኩ ነበር ። ይህን ስፍራ ሰይጣንም አላወቀውም ። ሰይጣንን እንደ አዋቂ መቍጠር አለማወቅ ነው (ይሁዳ. ቁ. 9)። ሙሴ ሞቶ ለሌሎች የአምልኮ ባዕድ ምክንያት አለመሆኑ ክፍያው ነው ። ነቢዩ ዳዊት ልጅ ቢሞትበት ሰሎሞንን የመሰለ ልጅ ቀጥሎ ተሰጠው ። ጌታችን በመሞቱ ዓለም ዳነ ። ቅዱስ ጳውሎስም ሕመሙ ቢጸናበት ሌላ ጸጋ ተጨመረለት ። እግዚአብሔር በሌላ መንገድ ይከፍላል ። ችግሮች እንዲኖሩ የሚፈቀዱት የጸሎት ሰው ሊያደርጉን ነው ። ያለ ሕመም እውነተኛውን ጸሎት ማቅረብ አይቻልም ። የተሰበረ ልብ ለአምልኮ ይረዳል ።   ያላሰብነውን ይሰጠናል   እግዚአብሔር የለመነውን ብቻ ሳይሆን ያለመነውንም ይሰጠናል ። ሙሴ ያለመነውን የሕዝብ መሪነት ተሰጠው ። እግዚአብሔር ግን እያዘጋጀው ነበር ። ዛሬ የምናልፍበት ነገር ለነገ ወንበራችን የዝግጅት ጣቢያ ሊሆን ይችላል ። እመቤታችን አምላክን ለመውለድ አስባም ለምናም አታውቅም ። ወደር የሌለው ጸጋ ተሰጣት ። እግዚአብሔር ለምኜው ለምን አልሰጠኝም ሳይሆን ሳለምነው የሰጠኝ በጣም ትልቅ ነው ብለን ማሰብ አለብን ።   ከሁሉ በላይ ሞታችንን የሰላም እንዲያደርግልን መለመን ይገባናል ። ለሌላውም ሰው ሸክም ሳንሆን ሰላማዊ የእንቅልፍ ሞት እንዲሰጠን መጸለይ ብዙ ጥቅም አለው ። የበሰለ ሰው የሚጸልየው ጸሎት ይህን ነው ፣ ኑሮ እንደ ምንም ይኖራል ፣ ሰላማዊ ሞት ግን ጸጋ ነው !   ተፈጸመ ዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሐምሌ 14 ቀን 2014 ዓ.ም.

photo content

እግዚአብሔር ያልመለሰው ጸሎት የእግዚአብሔር ርኅራኄ የጀመረው ሰዎች ስለ ጸሎት ምንነት አውቀው መጸለይ ከጀመሩ በኋላ አይደለም ። ቸርነቱ ከፍጹማን አካላቱና ከዘላለማዊው ባሕርዩ ጋር ጸንቶ የኖረ ነው ። ጸሎታችን የእግዚአብሔር ቸርነት መገለጫ እንጂ እርሱን ቸር ማድረጊያ አይደለም ። አንዳንዶች የአባት ፍቅር የመጣላቸው ከወለዱ በኋላ ነው ። መውለድ የለወጠላቸው ጭካኔና ግዴለሽነት ፣ ራስ ወዳድነትና ሞልቃቃነት አለ ። እግዚአብሔር ከዘላለም እስከ ዘላለም ቸር ነው ። ጸሎት በእኛ ፍላጎትና በጌታ ቸርነት የሚፈጸም ነው ። ጸሎት በአብዛኛው የነፍሳችንን ጉዳይ የሚመለከት ነው ። ፀሐይ ባናምንም ባንጸልይም ትወጣለች ። ሥጋዊ ነገሮች ላላመኑና ላልተመለሱ ሰዎች ሲደረጉ እናያለን ። ጸሎት በዋናነት የነፍሳችንን ጥያቄ የሚፈጽም ነው ። እውነተኛውን ጸሎት መጸለይ የሚችሉት ከእግዚአብሔር የተወለዱ ናቸውና ። አባት ብሎ እግዚአብሔርን ለመጥራት መወለድ ያስፈልጋል ። እግዚአብሔር ሁሉንም ጸሎታችንን ይሰማል ፣ ሁሉንም ግን አይሰጠንም ። አልተሰጠንም ማለት አልሰማንም ማለት አይደለም ። ባለመስጠት የሚሰማቸው ሰዎች አሉ ። እግዚአብሔር ጸሎትን በተለያየ መንገድ ይመልሳል ። እነዚህም መንገዶች አራት ናቸው ። 1- እሺ እሰጥሃለሁ ፤ 2- ጠብቅ ታገኛለህ ፤ 3- አይሆንም አይሰጥህም ፤ 4- በሌላ መንገድ እከፍልሃለሁ ። ጸሎታችን በእነዚህ አራት መንገዶች ተመልሰዋል ። እኛ አንድ ነገርን ብቻ ስለምንጠብቅ ያልተመለሰ ይመስለናል እንጂ እርሱ ልመናን የሚመልሰው በተለያየ መንገድ ነው ። እሺ እሰጥሃለሁ እግዚአብሔር የብዙ ሰዎችን ጸሎት መልሶአል ። የጸሎት ደብተር ስለሌለንና ስለምንረሳ ያልተመለሰ ይመስለናል እንጂ ከለመነው ውስጥ የሚበዛው መልስ አግኝቷል ። እግዚአብሔር ጸሎታችንን የሚመልሰው ራሱ ጸልዩ ብሎ ስላዘዘና አዛኝ ስለሆነ ነው ። ሰዎች ለሰዎች ደግ ነገርን ለማድረግ ፈቃድና አቅም አንድ ጊዜ አይሟሉላቸውም ። ፈቃዱ ሲኖራቸው አቅም የላቸውም ፣ አቅሙ ሲኖራቸው ፈቃዱ የላቸውም ። በዕለታዊ ኑሮአችን የምንሰቃየው በዚህ ምክንያት ነው ። ምንም ባልነበረን ጊዜ ለሰዎች ቤት ሠርተን ለመስጠት ፣ ድሆችን ከገበታችን ለማብላት ፣ አሥራት በኵራታችንን በእጥፍ ለማውጣት እንመኝ ነበር ። አቅሙ ሲመጣ ግን ዳተኛ ሆነናል ። በብር አሥራት ያወጡ የነበሩ በዶላር ማግኘት ሲጀምሩ ለማውጣት ይሰስታሉ ። አቅሙ ሲኖር ፈቃድ ይከዳል ፣ ፈቃዱ ባለበት ዘመን ደግሞ አቅም ዘግይቷል ። እግዚአብሔር ግን የልጆቹን ልመና ለመስማት ፈቃድም አቅምም አለው ። ሰው ሊከውን የማይችለውን ለብዙዎች በማድረግ ታላቅነቱን ገልጧል ። እግዚአብሔር መኖሩን ከሚያስመሰክርበት ነገር አንዱ ሳንለምነው በሚሰጠን ሌሊትና ቀን ክረምትና በጋ እንዲሁም ለምነነው በሚቸረን ብዙ ጸጋ ነው ። ጠብቅ ታገኛለህ እግዚአብሔር በትዕግሥት ውስጥ እየተዘጋጀ ሳይሆን እኛን እያዘጋጀ ነው ። ለሚሰጠን በረከት ብቁና ስምም እንድንሆን የትዕግሥትን ዋጋ ያስከፍላል ። የሰው ልጆች በቀላሉ ያገኙትን ነገር በቀላሉ ሊጥሉት ይችላሉ ። እግዚአብሔር እንድናከብረው የሚፈልገውን ጸጋ የትዕግሥት ደጅ ጥናትን ያውጅበታል ። ጻድቁ አብርሃም ዕለቱን ለምኖ ያገኘ አይደለም ። 25 ዓመታት እግዚአብሔርን በትዕግሥት ጠብቋል ። በዚህ መሐል ብዙ መውደቅና መነሣት አለ ። እርሱም የትምህርቱ አካል ነው ። ጉዳዩ ከመለወጡ በፊት እኛ ብንለወጥ ይሻላል ። የምንመኘው ነገር አንድ ክፍተታችንን የሚሞላ ነው ፣ ትዕግሥት ግን ለሕይወት ዘመናችን ስንቅ ፣ የተዘጉ በሮችን መክፈቻ ቁልፍ ነው ። አብርሃም ስለ ልጅ ልቡ ሞቶ ነበር ፣ በ75 ዓመቱ የተኛውን ልቡን ቀስቅሶ ልጅ እሰጥሃለሁ ያለው ራሱ እግዚአብሔር ነው ። ለአብርሃም ጸሎቱንም መልሱንም የሰጠ እግዚአብሔር ነው ። የያዕቆብ ልጅ ዮሴፍ ሕልሙ እስኪፈጸም ብዙ መከራ ተቀብሏል ፣ 13 ዓመታት በስደትና በእስር ተጎድቷል ። ነገሥታትና ካህናት የሚለብሱትን ወጥ ቀሚስ አስቀድሞ በአባቱ ተሸለመ ፣ የአለቅነት ልብስ ከለበሰ በኋላ ዮሴፍ በወንድሞቹ ተቀጥቅጦ ጉድጓድ ተጣለ ፣ በሃያ ብር ተሽጦ ግብጽ ወረደ ። እግዚአብሔር ያለውን ይፈጽማል ፣ የትኛውም የጠላት መንጋ ሊያስቆመው አይችልም ። ነቢዩ ዳዊት የ15 ዓመት ብላቴና ሳለ ተቀባ ። ከተቀባ በኋላ ግን የንጉሥ ጠላት መጣበት ፣ በሕመሙ ያጽናናውና የፈወሰው ሳኦል ጠላት ሁኖ ተነሣበት ። 15 ዓመታት ተንገላቶ የተቀባበትን መንበር ጨበጠ ። እግዚአብሔር በበጎች ጥበቃ መሪነትን አሰለጠነው ፣ ለሳኦል በገና በመደርደር ደግሞ የቤተ መንግሥቱን መግቢያና መውጫ አስለመደው ። በ15 ዓመታት ስደት የዓለምን መልክ አሳየው ። በይሁዳ አንግሦ ሰባት ዓመት አሰለጠነው ። ከሰባት ዓመት በኋላ በመላው እስራኤል ላይ አንግሦ ታላቅ ንጉሥ አደረገው ። በትዕግሥት ውስጥ መሠራት አለ ። በእነዚህ ዓመታት በመታገሡ ዳዊት እስካሁን ወደር ያልተገኘለት ንጉሥ ሆነ ። ከ17ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ አይሁድ የሚጠቀሙት የተደራረበ ሦስት ማዕዘን ያለው ባለ ስድስት ጫፍ ምልክት “የዳዊት ኮከብ” የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል ። በግምት ከ15 ሚሊየን ሕዝብ በላይ “ዳዊት” በሚል ስም አሁን እየተጠራ ነው ። የእስራኤል የመከላከያ ሥርዓት “የዳዊት ወንጭፍ- David`s Sling” በመባል የሚጠራ ነው ። እስራኤል ሦስት ዋና ዋና የመከላከያ ሥርቶች አሏት ። የዳዊት ወንጭፍ የሚባለው ግን ከባድ ሮኬቶችን የአጭርና የመካከለኛ ባሊስቲክ ሚሳኤሎችንና ክሩዝ ሚሳኤሎችን እንዲሁም የአየር ስጋቶችን ለመጥለፍ የሚያስችል ነው ። የዳዊት ወንጭፍ ጎልያድን እንደ ጣለች እንዲሁም ይህ የመከላከያ ሥርዓት በእስራኤል ሰማይ ላይ የሚታዩ አጥቂዎችን የሚጥል ነው ። ዳዊት መዝሙሩ በመላው ቤተ አይሁድና ቤተ ክርስቲያን ቀንና ሌሊት ላለፉት 3 ሺህ ዓመታት ይዘመራል ። የመጠበቅ ዋጋ ከሞት በኋላም ደማቅ ኮከብ ያደርጋል ። ከሁሉ በላይ ክርስቶስ ከዳዊት ዘር መወለዱ አምላክ በትዕግሥተኞች ቤት ለማደሩ ምልክት ነው ። ይቀጥላል ዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሐምሌ 13 ቀን 2018 ዓ.ም.

photo content

photo content

2018-11-12 ልቤ በእግዚአብሔር ጸና.m4a52.31 MB

Repost from Nolawi ኖላዊ
ዛሬ እሑድ ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም. ከጠዋቱ 4:00 ሰዓት  ላይ ትምህርታችን ይጀምራል :: የትምህርታችን ርእስ " ልቤ በእግዚአብሔር ጸና 1ሳሙ. 2፥1 ማስታወሻ ብትይዙ ይመከራል። ሌሎች ወገኖቻችንንም ጋብዙ https://t.me/Nolawii

ዛሬ እሑድ ሐምሌ 12 ቀን 2018 ዓ.ም. ከጠዋቱ 4:00 ሰዓት  ላይ ትምህርታችን ይጀምራል :: የትምህርታችን ርእስ " ልቤ በእግዚአብሔር ጸና 1ሳሙ. 2፥1 ማስታወሻ ብትይዙ ይመከራል። ሌሎች ወገኖቻችንንም ጋብዙ https://t.me/Nolawii

“የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም” ክፍል 4 እመቤታችን ድንግል ማርያም በብዙ መከራና እንግልት ውስጥ አልፋለች ። የባለ መስቀሉ የኢየሱስ እናት ናትና መስቀል ተሸክማ ኖራለች ። በፅንሰትዋ ጊዜ በነበራት ስጋት ፣ በመውለጃዋ ወራት በገጠማት መገፋት ፣ በግብጽ በረሃ በደረሰባት መንከራተት ፣ በናዝሬት ኑሮዋ ባሳለፈችው አነስተኛ ኑሮ ምቾትን የሚጠይቅ ልመና አንድም ቀን ወደ ልጅዋ ስታቀርብ አናነብም ። የምስጋና እናት ናትና ምሬትም የለባትም ። በቃና ዘገሊላ ግን ስለ ሌሎች ማፈርና መጨነቅ ምልጃን አቀረበች ። እነዚያ ሰዎች ታላቅ ሐፍረት ፣ መሸማቀቅ ፣ አሁን ይህ ምን ይባላል  የሚል ግራ መጋባት ውስጥ ነበሩ ። ወደ ቤታቸው እንዳይሸሹ ችግሩ ያለው ቤታቸው ውስጥ ነው ። አንድን ሰው ስለ ችግሩ ነግረው እወቅልኝ ፣ ተረዳኝ እንዳይሉ የጠሩት የቃና ዘገሊላን ሕዝብ ነው ። ሕዝብን ማስረዳት ከባድ ነው ። በሰው መጨረሻ ላይ የሚጀምር እግዚአብሔር በዚያ ቤት ነበረ ። እመቤታችን ድንግል ማርያም የሰዎቹን ችግር አይታ ተረዳች ። መንፈሳዊ ሰው ሳይነገረው የሰዎችን ችግር የሚያውቅ ነው ። ካወቀ በኋላ እንዳይቀመጥ የሚያደርገው አዛኝ ልቡ ነው ። እመቤታችን ድንግል ማርያም በዚያ ሰርግ ላይ ብቻዋን አልሄደችም ፣ ሁልጊዜ ከሐፍረት የሚያድነውን ጌታ ይዞ መሄድ ያስፈልጋል ። ሁለተኛ በሰርግ ግርግር አልተወሰደችም ፣ የሙሽራውን ችግር ተረዳች ። መንፈሳዊ ሰው ከግርግር ወጥቶ የሰዎችን ችግር ይገነዘባል ። ያማረ ልብስ ቢለብሱ ፣ ጨዋታ ቢያበዙ እንኳ ሳቅ የሸፈነውን ብሶት ይረዳል ። ለሰዎች መማለድ የሚያስፈልገው ሲነግሩን ሳይሆን ሳይነግሩንም ነው ። ምልጃ በሰዎቹ የመከራ ጫማ ውስጥ እግርን ማጥለቅና በፍቅር ወደ ጌታ መለመን ነው ። ምልጃ ሙሉ በሙሉ ፍቅር ነውና እግዚአብሔርን ያስደስተዋል ። ደግሞም ጸሎታችን ያለ ምልጃ ሙሉ እንደማይሆን የነገረን ራሱ ባለቤቱ ነው ። አባታችን ሆይ እንጂ አባቴ ሆይ አንልም ። የዕለት እንጀራችንን ስጠን ዛሬ እንጂ የዕለት እንጀራዬን አንልም ። ጸሎት ሌላውንም ወገን ማካተት አለበት ። ራስ ወዳድነት ያለበት ጸሎት አያርግም ። እመቤታችን ድንግል ማርያም የሰዎቹን ችግር ተረድታ ዝም አላለችም ፣ ለልጅዋ አቀረበች ። የራስን ችግር ማመቅ ፣ የሰዎችን ችግር አይቶ አዝኖ መቅረት ትክክል አይደለም ። እኛ አምላክ ያለብን ሕዝቦች ነን ። በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ማቅረብ ይገባናል ። ልጅዋ ቻይ መሆኑን ታምን ነበር ። የእምነት እናቶች የሚባሉ በብሉይም በሐዲስም አሉ ። ያለ ወንድ ዘር እንደምትፀንስ ያመነች ግን እመቤታችን ብቻ ናት ። እንደ እርስዋ ያለ አማኒ አይገኝም ። እግዚአብሔር እንዲሁ መሥራት የሚችል መሆኑን ታምናለች ። በቃና ዘገሊላ ሰርግ ላይም ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታ እንዲደግስ ፣ ወይን እንዲሰጥ ጠየቀች ። ወይን ተለቅሞ ፣ በመጭመቂያ ተጨምቆ ፣ ተብላልቶ ፣ ተቀምሞ የሚቀርብ ነው ። ይህ ሁሉ ሂደት ለሰው እንጂ ለእርሱ አስፈላጊ አይደለም ብላ አመነች ። እግዚአብሔር እንደሚሰጠን ካመንን በቂ ነው ፣ እንዴት እንደሚሰጠን መመራመር ግን አስፈላጊ አይደለም ። ቢሻ ካለው ዘግኖ ቢሻ ፈጥሮ መስጠት ይችላል ። እርሱ ከጊዜ ውጭ ነውና ሰዓቱ ሠርክ ነው ፣ ጊዜው ምሽት ነው አይባልለትም። ዲያቆን አሸናፊ መኰንን ሐምሌ 11 ቀን 2018 ዓ.ም.