en
Feedback
Sinksar tube(ስንክሳር)

Sinksar tube(ስንክሳር)

Open in Telegram

እኔ ቅዱስ ነኛና ቅዱሳን ሁኑ 1ጴጥ 1:15

Show more
The country is not specifiedThe category is not specified
2 500
Subscribers
-1024 hours
+1137 days
+42130 days
Posts Archive
††† እንኳን ለታላቁ ነቢይ ቅዱስ ሳሙኤል ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† ነቢዩ ቅዱስ ሳሙኤል ††† ††† እሥራኤል ከግብጽ ባርነት ወጥተው ከነዓንን ከወረሱበት ዘመን ጀምረው መሳፍንትና ካህናት ያስተዳድሯቸው ነበር:: በወቅቱ ታዲያ ክህነት ከምስፍና ተስማምቶለት ኤሊ የተባለ ሊቀ ካህናትና ልጆቹ (አፍኒና ፊንሐስ) ያስተዳድሩ ጀመር:: በዘመኑ ደግሞ ማኅጸኗ ተዘግቶባት ዘወትር የምታለቅስ ሐና የሚሏት ደግ ሴት ነበረች:: እግዚአብሔር የእርሷን ጸሎትና የሊቀ ካህናቱን ምርቃት ሰምቷልና ቅዱስ ልጅን ሰጣት:: "ሳሙኤል" አለችው:: "ልመናየን አምላክ ሰማኝ" ማለት ነውና:: ሐና ስዕለቷን ትፈጽም ዘንድ ሳሙኤልን በሦስት ዓመቱ ለቤተ እግዚአብሔር ሰጠችው:: በዚያም ስብሐተ እግዚአብሔርን እየሰማ : ማዕጠንቱን እያሸተተ : ከደብተራ ኦሪቱ ሳይለይ በሞገስ አደገ:: የኤሊ ልጆች (አፍኒና ፊንሐስ) ግን በበደል ላይ በደልን አበዙ:: ወቅቱ የአሁኑን ዘመን ይመስል ነበር:: ሁሉም ሰው ክፋተኛ የሆነበት በመሆኑ : እግዚአብሔር ርቆ ስለ ነበር ትንቢትና ራዕይ ብርቅ ነበር:: አምላክ ተቆጥቷልና ሳሙኤልን በሌሊት ሦስት ጊዜ ጠራው:: ነቢዩም ታጥቆ የፈጣሪውን ቃል ሰማ:: በዚሕም የተነሳ ታቦተ ጽዮን ለመጀመሪያ ጊዜ በአሕዛብ ተማረከች:: ከሰላሳ አራት ሺ በላይ ሕዝብ በኢሎፍላውያን አለቀ:: አፍኒና ፊንሐስም ተገደሉ:: ኤሊም ወድቆ ሞተ:: ከዚህች ቀን በኋላ ቅዱስ ሳሙኤል በእሥራኤል ላይ ነቢይና መስፍን ሆኖ ተሾመ:: በዘመኑ ሁሉ እንደሚገባው እየኖረ : የእግዚአብሔርን ለእሥራኤል : የእሥራኤልን ለእግዚአብሔር ሲያደርስ ኑሯል:: ሕዝቡ ንጉሥ በፈለጉ ጊዜ ሳዖልን ቀብቶ አነገሠላቸው:: እርሱ (ሳዖል) እንደ ሕጉ አልሔደምና ፈጣሪ ናቀው:: ሳሙኤል ግን ደግ አባት ነውና ክፋተኛውን (ሳዖልን) ከጌታው ጋር ያስታርቅ ዘንድ ብዙ ደከመ:: አለቀሰም:: እግዚአብሔር ግን ሳሙኤልን:- "አትዘን! እንደ ልቤ የሆነ : ፈቃዴን የሚፈጽም ዳዊትን አግኝቸዋለሁና እርሱን በእሥራኤል ላይ አንግሠው" አለው:: ቅዱስ ሳሙኤልም ወደ ቤተ ልሔም ሔዶ : ከእሴይ ልጆችም መርጦ ልበ አምላክ ዳዊትን ቀባው : አነገሠውም:: ቅዱስ ሳሙኤል በተረፈው ዘመኑ ለፈጣሪው እየተገዛ ኑሯል:: ነቢዩ ዘወትር ከእጁ የሽቱ ሙዳይና የቅብዐት እቃ (ቀንድ) አይለይም ነበረ:: እነዚህም የድንግል ማርያም ምሳሌዎች ናቸውና አባ ሕርያቆስ :- "ሙዳየ ዕፍረት ወቀርነ ቅብዕ ዘሳሙኤል" ብሎ አመስግኗታል:: ነቢዩም በወገኖቹ መካከል በዚሕች ቀን አርፏል:: እሥራኤልም አልቅሰውለታል:: ††† ቅዱስ ሉክያኖስ ††† ††† ዳግመኛ በዚህ ቀን ቅዱስ ሉክያኖስ ይታሠባል:: በቀደመ ሕይወቱ ጣዖት አምላኪና አጣኝ የነበረው ቅዱሱ ማንም ሳያስተምረው ክርስቲያኖቹን በመመልከት ብቻ አምኗል:: የወቅቱ ክርስቲያኖች አኗኗራቸው : ትጋታቸው : ጽናታቸውና ፍቅራቸው እንዲሁ ይስብ ነበር:: ከእነርሱ እምነት መውጣቱን የተመለከቱ ኢ-አማንያን አታልለው ሊመልሱት ሞከሩ:: እንቢ ቢላቸው በድንጋይ ጥርሱን አረገፉት:: ደሙን አፈሰሱ:: አሁንም በሃይማኖተ ክርስቶስ በመጽናቱ በዚሕ ቀን (ሰኔ 9) ከቀኑ ስድስት ሰዓት ላይ በመስቀል ላይ ሰቅለው ገድለውታል:: ††† የቅዱሳኑን በረከት አምላካቸው ያድለን:: ††† ሰኔ 9 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ ሳሙኤል ነቢይ 2.ቅዱስ ሉክያኖስ ሰማዕት 3.ቅዱስ ዮሐንስ ††† ወርኀዊ በዓላት 1.አባ በርሱማ ሶርያዊ (ለሶርያ መነኮሳት ሁሉ አባት) 2.አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ (ኢትዮጵያዊ) 3. ሦስት መቶ አሥራ ስምንቱ ቅዱሳን ሊቃውንት (ርቱዐነ ሃይማኖት ዘኒቅያ) 4.የብሔረ ብፁዐን ጻድቃን 5.አባ መልከ ጼዴቅ ዘሚዳ (ኢትዮጵያዊ) 6.ቅዱስ ዞሲማስ ጻድቅ (ዓለመ ብፁዐንን ያየ አባት) ††† "እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ: ስለ ሶምሶንም: ስለ ዮፍታሔም: ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም: ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና:: እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ:: ጽድቅንም አደረጉ . . . " ††† (ዕብ. ፲፩፥፴፪) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††

✨️️ ✨️️️️️️️ልዩ ፍርድ ቤት✨️️️️️️️ ብዙዎቻችን ወንድሞቻችንን ለማማት የፈጠንን ነን፡፡ የራሳችንን ግንድ ትተን የሰውን ጉድፍ ለማውጣት የምንቻኮል ነን፡፡ በወንድሞቻችን ላይ ለመፍረድ፥ እኅቶቻችንን ለመኰነን የምንጣደፍ ነን፡፡
ወዳጄ ሆይ! መፍረድ የእግዚአብሔር እንጂ ያንተ ሥልጣን አይደለምና ተጠንቀቅ፡፡ እህቴ ሆይ! በአምላክ ዙፋን ላይ ለመቀመጥ አታስቢ፡፡
ወዳጄ ሆይ! መፍረድ አማረኽን? እንኪያስ ምንም ወቀሳ የሌለበት፣ ይልቁንም ብዙ ጥቅም የሚያስገኝ የፍርድ ችሎት አለልህ፡፡ በራስህ ላይ መፍረድ ትችላለህና ተቀመጥ፡፡ ከኹሉም አስቀድመህ የበደልህን መዝገብ በፊትህ አኑረው፡፡ ነፍስህ የሠራችውንም ወንጀል በሙሉ በጥንቃቄ መርምር፡፡ ከዚያም “ነፍሴ ሆይ! ይኽንና ያንን በደል የፈጸምሽው ስለምንድነው?” በላት፡፡ የበደለችበትን ምክንያት ትታ በሌሎች ላይ ለማሳበብና በሌሎች ላይ ለመፍረድ ከዠመረችም “የተከሰስሽው በራስሽ ወንጀል እንጂ በሌላ ሰው ወንጀል አይደለም፡፡ እዚኽ ፍርድ ቤት የመጣሽው ስለእነዚያ ሰዎች ለመመስከር አይደለም፡፡ ስለዚኸ ንገሪኝ! ይኽን ያኽል በደል የፈጸምሽው፣ ይኽን ያንን ኹሉ ጥፋት ያጠፋሽው ስለምንድነው?” በላት፡፡ ዘወትር ይኽን የመሰለ አስጨናቂ ጥያቄ ጠይቃት፡፡ አፍራ የምትመልሰው ከሌላትም አስፈላጊውን ፍርድ (ቀኖና) ወስንባት፡፡ ይኽን ልዩ ፍርድ ቤት ዘወትር የምትቀመጥ ከኾነ ያንን የእሳት ባሕር፣ ያ እሳቱ የማይጠፋው ትሉ የማያንቀላፋው ስቃይ በልቡናህ ይቀረጻል፡፡ ✨️️️️️️️🍂 “ወደ እኔ መጥቶ ነው፤ እርሱ አታልሎኝ ነው፤ እርሱ ፈትኖኝ ነው" እያለች በዲያብሎስ እንድታመካኝም አትፍቀድላት፡፡ ይልቁንም፡- "አንቺ ባትፈቅጂ ነው እንጂ እነዚኸ ኹሉ በአንቺ ላይ ሥልጣን የላቸውም" ብለህ ንገራት፡፡ "እኔ እኮ ሥጋ ለባሽ ነኝ፤ የምኖረውም በዚኽ ኃጢአት በሞላበት ዓለም ነው" ካለችህም "ይኽ ኹሉ ሰበብና ምክንያት ነው፡፡ ብዙዎች አንቺ የለበስሽውን ሥጋ ለብሰው በዚኽ ዓለም ኑረው ጻድቃንና ሰማዕታት ኾነዋል፡፡ አንቺ ራስሽ አንዳንድ ጊዜ መልካም ምግባራትን ስታደርጊ ይኸ አኹን የምታሳብቢበትን ሥጋ ለብሰሽ ነው" በላት፡፡ ይኽን ስትላት ቢያማትም እጅህን አታንሳባት፡፡ ምክንያቱም ቀኖናው ከሞት የሚታደጋት መንፈሳዊ ልምምድ እንጂ የሚገድላት ቅጣት አይደለምና፡፡ ስለዚኽ ምክንያት የምታበዛብህ ከኾነ “እባብ አሳተኝ" ብላ ከተጠያቂነት ያለመለጠችውን ሔዋንን አስታውሳት፡፡ ይኽን ኹሉ ስታደርግም ከአጠገብህ ማንም አይኑር፡፡ የሚረብሽህ ሰው ከአጠገብህ አይገኝ፡፡ ይልቁንም ዳኛ በፍርድ ወንበር ላይ እንደሚቀመጥ አንተም በፍርድ ወንበር ፈንታ በምቹ ጊዜና ቦታ በጽሞና ተቀመጥ፡፡ ነቢዩ “በመኝታችሁ ሳላችሁ በልባችሁ የምታስቡት ይታወቃችሁ" እንዳለው /መዝ.4፥4/ ይኽ ቦታና ጊዜ ከኹሉም ይልቅ ተስማሚ ነውና እራትህን ከበላህ በኋላ ዘወትር ይኽን የፍርድ ወንበር ወደ መኝታ ክፍልህ ይዘኸው ሒድ፡፡ ዕለት ዕለት ይኸን የምታደርግ ከኾነ ሐዋርያው “እኛ በራሳችን ብንፈርድ ኖሮ ባልተፈረደብንም ነበር" እንዲል (1ኛ ቆሮ.1፥31) በዚያ አስፈሪው የፍርድ ወንበር ፊት ያለ ፍርሐት ትቆማለህ፡፡ 📝ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ 📚ሰማዕትነት አያምልጣችሁ እና ሌሎች ✨️️️️️️️ገጽ 42-42 📝በገብረ እግዚአብሔር ኪደ የተተረጎመ ✨️️️️️️️✨️️️️️️️✨️️️️️️️🍂✨️️️️️️️✨️️️️️️️✨️️️️️️️🍂✨️️️️️️️✨️️️️️️️✨️️️️️️️🍂

በፍቅር ተመላለሱ "እንግዲህ እንደ ተወደዱ ልጆች እግዚአብሔርን የምትከተሉ ሁኑ፥ ክርስቶስም ደግሞ እንደ ወደዳችሁ ለእግዚአብሔርም የመዓዛ ሽታ የሚሆንን መባንና መሥዋዕትን አድርጎ ስለ እናንተ ራሱን አሳልፎ እንደ ሰጠ በፍቅር ተመላለሱ። ኤፌሶን 5:1

🎯 ከዘማሪያን የማንን መዝሙር ማዳመጥ ይፈልጋሉ? ┏•••••••••••••••••••••••••••••••┓ 🎤 ሊቀ መዘምራን ቴዎድሮስ ዮሴፍ 🎤 ┗•••••••••••••••••••••••••••••••┛ ┏•••••••••••••••••••••••••••••••┓ 🎤 ሊቀ መዘምራን ይልማ ኃይሉ 🎤 ┗•••••••••••••••••••••••••••••••┛ ┏•••••••••••••••••••••••••••••••┓ 🎤 ሊቀ መዘምራን ኪነጥበብ 🎤 ┗•••••••••••••••••••••••••••••••┛ ┏•••••••••••••••••••••••••••••••┓ 🎤 ዘማሪ አቤል መክብብ 🎤 ┗•••••••••••••••••••••••••••••••┛ ┏•••••••••••••••••••••••••••••••┓ 🎤ዘማሪት ሲስተር ህይወት ተፈራ🎤 ┗•••••••••••••••••••••••••••••••┛ ┏•••••••••••••••••••••••••••••••┓ 🎤ዘማሪ ዲያቆን ሙሉቀን ከበደ🎤 ┗•••••••••••••••••••••••••••••••┛ ┏•••••••••••••••••••••••••••••••┓ 🎤 ቀሲስ ምንዳዬ ብርሃኑ 🎤 ┗•••••••••••••••••••••••••••••••┛ ┏•••••••••••••••••••••••••••••••┓ 🎚 ዘማሪት ፋሲካ ድንቁ 🎚 ┗•••••••••••••••••••••••••••••••┛ 🎤 የሁሉንም ዘማሪያን መዝሙር ለማግኘት 🔔 👇 🫧🫧🫧🫧🫧🫧🫧🫧🫧🫧🫧🫧🫧🫧

††† እንኳን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ዓመታዊ በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† ††† በዓሉ ከሰላሳ ሦስቱ ዓበይት የእመቤታችን በዓላት አንዱ ሲሆን በዚሕች ቀን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል እናቱ እግር ሥር ጠበል አፍልቋል:: ††† ጥንተ ነገሩስ እንደ ምን ነው ቢሉ:- ድንግል ማርያም አምላክ ልጇን አዝላ ስደት ወጥታ ምድረ ግብጽ ትደርሳለች:: በወቅቱ ከደረሱባት ችግሮች አንዱ ደግሞ ረሃብና ጽሙ ነበር:: እንኳን ለስደተኛ በቤቱ ላለም ረሃብና ጥም እንዴት እንደሚከብድ የደረሰበት ያውቀዋል:: ††† ለዛም ነው ሊቁ በቅዳሴው:- "አዘክሪ ድንግል ረሃበ ወጽምዐ : ምንዳቤ ወኀዘነ : ወኩሎ ዐጸባ ዘበጽሐኪ ምስሌሁ" ያለው:: ታዲያ አንድ ቀን የበርሃው ፀሐይ አቃጥሏቸው ባረፉበት ድንግል እመቤታችን ውኃ ልመና ወጣች:: ብዙ ለመነች : ግን ጥርኝ እንኳ የሚሠጣት አጥታ በሐዘን ተመለሰች:: ስትመለስ ግን ይባስ ብሎ የልጇን ጫማ ሽፍቶች ወስደውት ደረሰች:: ያን ጊዜ ልጇን ታቅፋ "ውኃ ሳላገኝልሕ : ጫማሕንም አሰረቅኩብህ" ብላ ምርር ብላ አልቅሳለች:: "በከየት ወትቤ ማርያም ማዕነቅ:: እምሰብአ ሃገር አልቦ ዘየአምራ ለጽድቅ:: ሰአልክዎሙ ማየ ኢወሀሐቡኒ በሕቅ:: ወአሕጎልኩ ለወልድየ አሳእኖ ዘወርቅ::" እንዳለ ደራሲ:: ይሕንን የተመለከተ ልጇ የቆመችበትን መሬት ቢባርከው ሕይወትነት ያለው ማይ (ጠበል) ፈለቀ:: ጌታችን : እመቤታችን: ዮሴፍና ሰሎሜ ከውኃው ጠጥተዋል:: ሲሔዱ ግን ለእንግዶች ጣፋጭ (መድኃኒት) : ለአካባቢው ሰዎች ግን መራራ ሁኗል:: "ከመ ኢይስተይዋ ሰብአ ሐገር ለይእቲ ማይ አምረራ:: ወለርኁቃንሰ ፈውሰ ወጥዕምተ ገብራ::" እንዳለ መጽሐፍ:: (ሰቆቃወ ድንግል) ከመቶዎች ዓመታት በኋላም ጌታ ጠበል ያፈለቀበት : ድንግል እመቤታችን የቆመችበት ቦታ ላይ በእመ ብርሃን ስም ቤተ ክርስቲያን ታንጿል:: ቅዳሴ ቤቱም ተከብሯል:: ጠበሉም ሲባርክና ሲፈውስ ይኖራል:: ††† የጠበል በዓል ††† †††ዳግመኛ ዕለቱ የጠበል በዓል ተብሎም ይታሠባል:: ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስለ ጠበል ፈዋሽነት ሁሌ ብታስተምርም በዚህ ቀን ግን ልዩ ትኩረቷ ታደርገዋለች:: እግዚአብሔር በምክንያትም አለምክንያትም መፈወስ ይችላል:: ያለ ምክንያት በቃሉና በወዳጆቹ ቃል አድሮ "ዳን" ይላል:: ወይም ደግሞ በምክንያት በእመት (እምነት) : በጠበል : ቅዱስ ቃሉን በመስማት : በመስቀሉና በመጻሕፍት በመባረክ (በመታሸት) : በቅዱሳን አካል (በልብሳቸው : በበትራቸው : በጥላቸው በአጽማቸው . . .) ይፈውሳል:: እርሱ እግዚአብሔር ነውና በወደደውና በመረጠው አድሮ ያድናል ( ይፈውሳል):: (2ነገ. 5:10, ሐዋ. 3:6, 5:15, 19:11) ††† ዛሬ ግን የጠበል ፈዋሽነት በጉልህ ይነገራል:: (ዮሐ. 5:1, 9:7) ††† አምላከ ቅዱሳን ከደዌ ሥጋ : ከደዌ ነፍስ በምሕረቱ ይሠውረን:: ከድንግል እመቤታችን በረከትም ያሳትፈን:: ††† ሰኔ 8 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.የእመቤታችን ድንግል ማርያም ቅዳሴ ቤት 2.የቅዱስ ውኃ (ጠበል) መታሠቢያ 3.ቅድስት ትምዳ እናታችን 4.ቅዱስ አውሎጊስ 5.አባ አትካሮን ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ቅዱስ ሙሴ ሊቀ ነቢያት 2.ኪሩቤል (አርባዕቱ እንስሳ) 3.አባ ብሶይ (ቢሾይ) 4.አቡነ ኪሮስ 5.አባ ሳሙኤል ዘደብረ ቀልሞን 6.ቅዱስ ማትያስ ሐዋርያ (ከአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት) ††† "ለእግዚአብሔር ክብርን ስጡ:: ግርማው በእሥራኤል ላይ: ኃይሉም በደመናት ላይ ነው:: እግዚአብሔር በቅዱሳኑ ላይ ድንቅ ነው:: የእሥራኤል አምላክ እርሱ ኃይልን: ብርታትንም ለሕዝቡ ይሰጣል:: እግዚአብሔርም ይመስገን:::" ††† (መዝ. ፷፯፥፴፬) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር ††† 🔵TELEGRAM 🔴 YOUTUBE

†††✝✝✝ እንኳን ለጻድቅና ሰማዕት አባ ቴዎድሮስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፣ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! ††† †††✝✝✝ አባ ቴዎድሮስ †††✝✝✝ †††አባ ቴዎድሮስ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን የነበረ ግብፃዊ አባት ነው:: ተወልዶ ባደገባት የእስክንድርያ ከተማ ብሉያትንና ሐዲሳት በወቅቱ ከነበሩ አበው ሊቃውንት ተምሯል:: ጊዜው ምንም መናፍቃን የበዙበት ቢሆን በዛው ልክ እነ ቅዱስ እለ እስክንድሮስና ቅዱስ አትናቴዎስን የመሰሉ ቅዱሳን ሊቃውንት ነበሩና ከነሱ የሚገባውን ወስዷል:: አባ ቴዎድሮስ "አባ" ያሰኘው ሥራው:- ሲጀመር ገና በወጣትነቱ ድንግልናንና ምንኩስናን በመምረጡ ነበር:: ምንም እንኳ ሐብት ከእውቀት ጋር ቢስማማለትም ይሕ እርሱን ከምናኔ ሊያስቀረው አልቻለም:: ከከተማ ወጥቶ: በዓት ወስኖ በጾምና በጸሎት ተወሰነ:: በ340ዎቹ ዓ/ም አካባቢ ግን በምዕመናን ላይ ከባድ ችግር ደረሰ:: የወቅቱ ነገሥታት በስመ ክርስቲያን አርዮሳውያን ነበሩና ሕዝቡን ማስገደድ: አንዳንዴም የአርዮስን እምነት ያልተቀበለውን ማስገደል ጀመሩ:: በዚህ ምክንያትም ታላቁ የኦርቶዶክስ ጠበቃ ቅዱስ አትናቴዎስን ከመንበሩ አሳደዱት:: በምትኩም አርዮሳዊ ሰው ዻዻስ ተብሎ ተሾመ:: ይህን ጊዜ ነው እንግዲህ እውነተኛ እረኛ ያስፈለገው:: በበዓቱ የነበረው አባ ቴዎድሮስ አላቅማማም:: ቤተ ክርስቲያን ትፈልገዋለችና መጻሕፍትን ገልጾ ከቦታ ቦታ እየተዘዋወረ ምዕመናንን ያጸናቸው ጀመር:: መናፍቃኑን ተከራክሮ ምላሽ በማሳጣት ሕዝቡን ከኑፋቄ በመጠበቅ የሠራው ሥራ ሐዋርያዊ ቢያሰኘውም ለአርዮሳዊው ዻዻስ (ጊዮርጊስ ይባላል) ሊዋጥለት አልቻለም:: በቁጣ ወታደሮችን ልኮ አባ ቴዎድሮስን ተቆጣው:: እንዳያስተምርም ገሰጸው:: አባ ቴዎድሮስ ግን እሺ ባለማለቱ ግርፋት ታዘዘበት:: ወታደሮች እየተፈራረቁ ሲገርፉት ረድኤተ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነበርና ከዛ ሁሉ ግርፋት አንዲቷም አካሉ ላይ አላረፈችም:: በዚህ የተበሳጨው አርዮሳዊ ዻዻስ የአባ ቴዎድሮስን እጅና እግር ከፈረስ ጋሪ በኋላ አስረው በኮረኮንች መንገድ ላይ በፍጥነት እንዲያሮጧቸው አዘዘ:: ፈረሶቹ መሮጥ ሲጀምሩ የአባ ቴዎድሮስ አካሉ ይላላጥ ጀመር:: ትንሽ ቆይቶ ግን እጆቹ ተቆረጡ:: በኋላም ራሱ ከአንገቱ ተለይታ መንገድ ላይ ወደቀች:: አካሉ በሙሉ መሬት ላይ ተበታተነ:: እግዚአብሔር ቅድስት ነፍሱን ተቀብሎ አሳረጋት:: ††† ለቅዱሱም 3 አክሊል ከሰማይ ወርዶለታል:- 1.ስለ ፍጹም ምናኔውና ድንግልናው 2.ስለ ሐዋርያዊ የወንጌል አገልግሎቱ 3.ስለ ሃይማኖቱ ደሙን አፍስሷልና "እምአባልከ ተመቲራ ለእንተ ሠረረት ርዕስ: እግዚአብሔር አስተቄጸላ በአክሊል ሠላስ" እንዳለ መጽሐፍ:: ምዕመናን ሥጋውን ሰብስበው በዝማሬና በማኅሌት በክብር ቀብረውታል:: ††† አምላካችን ከቅዱሱ በረከት ይክፈለን:: ††† ሰኔ 6 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ አባ ቴዎድሮስ ሰማዕት 2.አባ ገብረ ክርስቶስ 3."40" ሰማዕታት ††† ወርሐዊ በዓላት 1.ቅድስት ደብረ ቁስቋም 2.አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን 3.አባታችን ኖኅና እናታችን ሐይከል 4.ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ 5.ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ 6.ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ 7.ቅድስት ሰሎሜ 8.አባ አርከ ሥሉስ 9.አባ ጽጌ ድንግል 10.ቅድስት አርሴማ ድንግል ††† "መልካሙን ገድል ተጋድያለሁ:: ሩጫውን ጨርሻለሁ:: ሃይማኖቴን ጠብቄአለሁ:: ወደ ፊት የጽድቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል:: ይህንም ጻድቅ: ፈራጅ የሆነው ጌታ ያን ቀን ለእኔ ያሰረክባል:: ደግሞም መገለጡን ለሚወዱት ሁሉ እንጂ ለእኔ ብቻ አይደለም::" ††† (2ጢሞ. 4:7) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር †††✝✝✝

††† እንኳን ለኃያሉ ሰማዕት ቅዱስ ብሶይ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። ††† ††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††
††† ቅዱስ አባ ብሶይ ሰማዕት †††
††† ቅዱሱ አባታችን ከዘመነ ሰማዕታት ጣፋጭ ፍሬዎች አንዱና ግንባር ቀደሙ ነው:: ††† ጥንተ ነገሩስ እንደ ምን ነው ቢሉ:- በ3ኛው መቶ ክ/ዘመን ማጠናቀቂያ አካባቢ ታግሕስጦስና ክሪስ የሚባሉ ክርስቲያኖች ነበሩ:: በቀናው የጽድቅ ጐዳና ቢኖሩም ከጋብቻ በኋላ ለአሥራ ሰባት ዓመታት መውለድ አልቻሉም:: የአሥራ ሰባት ዓመት ልመናቸውን የተመለከተ እግዚአብሔር ቅዱስ ገብርኤልን ልኮ አበሰራቸው:: "ሕፃኑ ለሰማዕትነት ተመርጧልና ብሶይ በሉት" አላቸው:: ብሶይ በተወለደ በሰባት ዓመቱ ወላጆቹ ይማር ብለው ወደ ገዳም ወሰዱት:: በገዳም ውስጥ መጻሕፍትን አጥንቶ ዲቁናን ተሾመ:: ወደ ዓለም ተመለስ ቢሉትም እንቢ አለ:: ከባልንጀራው ቅዱስ ጴጥሮስ ጋር ለሃያ አንድ ዓመታት በድንግልና : በተጋድሎ : ጾምና ጸሎትን እያዘወተሩ ኖሩ:: ቅዱስ ብሶይ ሃያ ስምንት ዓመት በሞላው ጊዜ መልአኩ የተናገረው የትንቢት ዘመን ደረሰ:: በርካታ ምዕመናን ክርስቲያን በመሆናቸው ብቻ ታረዱ:: ወደ እሳትም ተጣሉ:: ሞትን የፈሩ ደግሞ በየዱር ገደሉ ተሰደዱ:: ቅዱስ ብሶይም በሚያውቁት ሰዎች ተከሶ ለፍርድ ቀረበ:: ድንገት ከሰማይ ፍጡነ ረድኤት ወሊቀ መላእክት ቅዱስ ገብርኤል ደረሰለት:: "አይዞሕ! እኔ እስከ መጨረሻው ከአንተ ጋር ነኝ" አለው:: የጦር መኮንኑ ክርስቶስን እንዲክድ አባበለው:: ቅዱሱ ግን ጣዖታቱ የአጋንንት ማደሪያ መሆናቸውን በገሃድ ነገረው:: መኮንኑ ቢበሳጭ ወታደሮቹ እንዲጨምቁት አዘዘ:: ደሙ እየወረደ ገረፉት:: በፊትና በኋላ ብረት አድርገው ሥጋውን ጨፍልቀው እሥር ቤት ውስጥ ጣሉት:: ሊቀ መላእክት መጥቶ ዳስሶ አዳነው:: መኮንኑ እርሱን ማሰቃየት ደከመው:: የቅዱሳን ሕይወት ግርም ይላል:: ተገራፊው እያለ ገራፊው : ስቃዩን የሚቀበለው እያለ አሰቃዩ ይደክመዋል:: ††† ይሕንን መሰለኝ አባ ጽጌ ድንግል:- "እመዐዛ ጽጌኪ ድንግል ውስተ ዐውደ ስምዕ ዘሰክረ:: ውግረተ አዕባንኒ ይመስሎ ሐሰረ:: እሳትኒ ማየ ባሕር ቆሪረ" ያለው:: ቅዱስ ብሶይን ከአንዱ መኮንን ወደ ሌላው እያመላለሱ አሰቃዩት:: አካሉን ቆራረጡት:: ዓይኑን በጋለ ብረት አወጡት:: በምጣድ ቆሉት:: በጋን ውስጥ ቀቀሉት:: እርሱ ግን በፈጣሪው ፍቅር የጸና ነውና ሁሉን ታገሰ:: በነዚሕ ሁሉ የስቃይ ዓመታት ቁራሽ ዳቦ እንኳ አላቀመሱትም:: በረሃብ ቀጡት እንጂ:: ለእርሱ ግን ምግቡ የክርስቶስ ስም ነበር:: በመጨረሻ ንጉሡ ዲዮቅልጢያኖስ አንገቱን በሰይፍ አስመታው:: ሥጋውንና የተቆረጠ አንገቱን ገንቦ (ጋን) ውስጥ ከቶ ጣለው:: የቅዱሱን አካል የያዘችው ጋን ግን በእግዚአብሔር ቸርነት : ማንም ሳይሸከማት ከመሬት ከፍ አለች:: ለሃያ ቀናት ተጉዛ ከሶርያ ግብጽ (ቦሃ) ደረሰች:: ክርስቲያኖች ተቀብለው ሲከፍቷት የቅዱስ ብሶይ ራሱና አንገቱ ተጣብቆ ተገኝቷል:: በክብርም አሳርፈውታል:: ††† ቅዱስ ያዕቆብ ††† ††† ዳግመኛ በዚሕ ቀን ጻድቅና ተአማኒ (ታማኝ) የተባለ የምሥራቅ ሰው ቅዱስ ያዕቆብ መታሠቢያ ይደረግለታል:: ቅዱስ ያዕቆብ ቁስጥንጥንያ አካባቢ በርሃ ውስጥ ይኖር የነበረ አባት ነው:: ከቅድሰና ሕይወቱ ባሻገር በደፋርነቱ (ጥብዐቱ) ይታወቃል:: በ340ዎቹ ዓ/ም ታናሹ ቆስጠንጢኖስ አርዮሳዊ በሆነ ጊዜ ይሔ አባት በይፋ ገስጾታል:: በዚህም ምክንያት መከራን ተቀብሏል:: ታስሯል:: ተገርፏል:: እግዚአብሔርም መናፍቁን ንጉሥ ለጦርነት በወጣበት ቀስፎታል:: ቅዱሱ በዚህች ቀን ዐርፎ ወደ ወደደው ክርስቶስ ሔዷል:: ††† ቸር አምላክ ከሰማዕቱ ቅዱስ ብሶይ እና ከቅዱስ ያዕቆብ በረከት ያሳትፈን:: በምልጃቸውም ይቅር ይበለን:: ††† ሰኔ 5 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት 1.ቅዱስ አባ ብሶይ (ኃያል ሰማዕት) 2.ቅድስት ማርታ ለባሲተ ክርስቶስ (በቅድስናዋ የተወደሰች : በስደት ያረፈች እናት ናት::) 3.ቅዱስ ያዕቆብ ምሥራቃዊ 4.ቅዱስ ቢፋሞን ሰማዕት 5.ቅዱስ መቃርስ ሰማዕት 6.ቅዱስ መርቆሬዎስና ማኅበሩ (ሰማዕታት) ††† ወርኀዊ በዓላት 1.ቅዱስ ጴጥሮስ ሊቀ ሐዋርያት 2.ቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያ 3.አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ 4.ቅዱስ ዮሐኒ ኢትዮጵያዊ 5.ቅዱስ አሞኒ ዘናሒሶ 6.ቅድስት አውጋንያ (ሰማዕትና ጻድቅ) ††† "ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ : ወይስ ጭንቀት : ወይስ ስደት : ወይስ ራብ : ወይስ ራቁትነት : ወይስ ፍርሃት : ወይስ ሰይፍ ነውን? "ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን:: እንደሚታረዱ በጐች ተቈጠርን" ተብሎ እንደ ተጻፈ ነው:: በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን::" ††† (ሮሜ. ፰፥፴፭-፴፰) ††† ወስብሐት ለእግዚአብሔር ††† 🔵TELEGRAM 🔴 YOUTUBE

"አቤቱ፥ ወደ አንተ የጮኽሁትን ቃሌን ስማኝ። ማረኝና አድምጠኝ። አንተ ፊቴን እሹት ባልህ ጊዜ፡— አቤቱ፥ ፊትህን እሻለሁ ልቤ አንተን አለ። ፊትህን ከእኔ አትሰውር፥ ተቈጥተህ ከባሪያህ ፈቀቅ አትበል
"አቤቱ፥ ወደ አንተ የጮኽሁትን ቃሌን ስማኝ። ማረኝና አድምጠኝ። አንተ ፊቴን እሹት ባልህ ጊዜ፡— አቤቱ፥ ፊትህን እሻለሁ ልቤ አንተን አለ። ፊትህን ከእኔ አትሰውር፥ ተቈጥተህ ከባሪያህ ፈቀቅ አትበል፤ ረዳት ሁነኝ፥ አትጣለኝም፥ የመድኃኒቴም አምላክ ሆይ፥ አትተውኝ።"                መዝ 27÷7-9