ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
الذهاب إلى القناة على Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
إظهار المزيد613
المشتركون
+124 ساعات
-37 أيام
-1130 أيام
أرشيف المشاركات
በአዋጅ ነጋሪ ቃልም ይሰበሰባሉ፡፡ ይህቺ ሀገር ትልቅ ናትና እስከ ዓርብም ያስተምራቸዋል፡፡ በዚያን ጊዜ ሰይጣን ቀና፡፡ አባ ሐዊም እንደልማዱ በዕለተ ዓርብ ወደ ሰማይ በሄደ ጊዜ ያ ሰይጣን በመቀመጫው ተቀምጦ በእርሱ በሐዊ ተመስሎ በቀዳሚት ሰንበት ቀንም ተገልጦ "ፈጣሪያችን የሚወዳትን ነገር እነግራችሁ ዘንድ ሁላችሁም ተሰብሰቡ" አለ፡፡ ሁላቸውም ተሰበሰቡ፡፡ "አባት ሆይ! ያለ ልማድህ ዛሬ ለምን መጣህና ጠራኸን?" አሉት፡፡ ያ ጠላት ዲያብሎስም "ጌታዬ ለሕዝቦቼ የዚያችን በቤትህ አንፃር ያለችውን እንጨት ቅጠል በጥርሳቸው ይጨምሩ ዘንድ፣ በአፋቸውም ያጤሱ ዘንድ ዛሬ ካልነገርሃቸው ወዳጄ አይደለህም አለኝ" አላቸው፡፡ ይህችንም እንጨት ባያት ጊዜ እንዲህ አደረገ፣ ሔዋንን በእንጨት እንዳሳታት አሳታቸው፡፡ ዛሬ እንደሚያደርጉትም የጥንባሆ ዕቃን አደረጉ፡፡ ቅጠሏንም አምጥተው ቀጥቅጠው በእሳት አጢሰው ትንሹም ትልቁም፣ የከበረውም የጎሰቆለውም ሁላቸውም ጠጡ፡፡
❤ ሐዊም በሰማይ ሳለ በጸጋ አውቆ አዘነ፣ ነገር ግን ስለ ሰንበታት ክብር ብሎ አደረ፡፡ ሰኞ በነግህም ሐዊ መጣ፣ ሰይጣንም እንደ ጢስ በኖ ጠፋ፡፡ እርሱም ሰዎቹን ሰብስቦ "ይህን ማን አስተማራችሁ?" አላቸው፡፡ "አንተ ነህ" አሉት፡፡ "ሰይጣን ነው እንጂ እኔ አይደለሁም፣ ከዛሬ ጀምሮ ተው" አላቸው፡፡ "ትናንት ጠጡ፣ ዛሬ ተው" ይለናል ብለው እምቢ አሉት፡፡ እርሱም አወገዛቸው፡፡ "በእርሻው የዘራት፣ በአፉም የጠጣት፣ በእጁም የያዛት የተረገመ ይሁን" አላቸው፡፡ ጋኔኑም በቅሉ ውስጥ ሆኖ ይነጋገራል፣ በውጭ ያሉትንም አጋንንት ይጠራቸዋል፡፡ በዚህን ሰዓት የተውም አሉ፣ እምቢም ያሉ አሉ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ያቺ እንጨት ተረገመች፡፡ ሰውም በጠጣት ጊዜ የአምስት ቀፎ ሙሉ ንቦችን የሚያህሉ አጋንንት ይመጣሉ፡፡ በሁለቱ ዓይኖቹ ውስጥ፣ በሁለቱ አፍንጫዎቹም፣ በሁለቱ ጆሮዎቹም፣ በአፉም፣ በታች በሰገራ መውጫም በእነዚህ ሁሉ እንደ ቀፎ ንብ ይገባሉ፣ ይወጣሉ፡፡ ትምክህትን፣ ትዕቢትን፣ መግደልን፣ ሥርቆትንም፣ ክፉውንም ሁሉ ይመሉታል፡፡ ወሶበ ይሰትያ ብእሲ ይመጽኡ አጋንንት ዘየአክሉ መጠነ ፭ቱ ቀፈዋት ዘመልኡ አንህብት ወይበውኡ ውስቴቱ፡፡ በ፪ አዕይንቲሁ፣ ወበ፪ አዕናፊሁ፣ ወበ፪ አዕዛኒሁ ወበመንፈሱ ዘታህት በአፉሁ በዝንቱ ኵሉ ከመ ንህብ ዘቀፎ ይበውኡ ወይወጽኡ፡፡ ወይመልእዎ ትምክህተ፣ ወትዕቢተ፣ ቀትለ፣ ወሠሪቀ ወኵሎ ዕከያተ እንዲል መጽሐፍ፡፡
❤ አባታችን ዘርዓ ቡሩክም ይህን ሰምቶ እጆቹን በትከሻው አመሳቅሎ አለቀሰ፣ በሥዕሉም አለ፣ በዚያን ጊዜ ወደ ዓለም ወጣ፡፡ ይህችን የተረገመች እንጨት እንዲህ ብሎ አወገዛት፡- "በአፉ የጠጣት፣ በእጁም የያዛት፣ የዘራት፣ የሸጣት፣ የገዛትም የጥምቀት ልጅ አይደለም፤ በሥጋው አይጠቀምም፣ ነፍሱም ወደ ሲዖል ትወርዳለች፡፡ ልጄ የሆነ ግን መድኃኔዓለምንና ኪዳነ ምሕረትን ያክብር፡፡ ጥንባሆንም አይጠጣ› አለ፡፡ የዚህ ጻዲቅ በረከቱ ያልታዘዝንውን ከመብላት ይጠብቀን አሜን" በማለት ተአምረ መድኃኔዓለም ወገድለ መባዓ ጽዮን ነገረ ጥንባሆን በሰፊው ዘግቦታል፡፡ በሌላም በኩል ትንባሆን በተመለከተ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ለአቡነ ዘርዐ ቡሩክ የሰጣቸው ቃልኪዳን በራሳቸው በዘርዐ ቡሩክ ገድል ላይ የተጻፈውን ወደፊት እናያለን፡፡ እንዲሁም ይህችን የተረገመች ዕፅ የሚጠቀሙባት ሁሉ የሰይጣን ማደሪያዎች እንደሚሆኑና ክፉውንም ሁሉ እንደሚያሠሩት በሌላም ቦታ በአቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ገድል ላይ በሰፊው ተጽፏል፡፡ ከአባታች ከአቡነ ዘርዐ ቡሩክ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸውም ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን።
❤ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ ሳይጠመቁ ለሚሞቱ አሕዛብም ጭምር ትልቅ ቃልኪዳን የተሰጣቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ ይኸውም በቅዱስ ገድላቸው ላይ እንዲህ ተብሎ ተጽፏል- "በሥራው ሁሉ ፍጹም የሆነና ገድሉ ያማረ ቅዱስ አባታችንን በአድማስ ራስ ቆሞ ምሥራቁንና ምዕራቡን፣ ሰሜኑንና ደቡቡን እንዲባርክ በአፉ እስትንፋስም የምሕረት እስትንፋስን እፍ እንዲል እስትንፋሱንም ከአድማስ እስከ አድማስ ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይደርስ ዘንድ እግዚአብሔር አዘዘው፡፡ በእግዚአብሔር በቅዱስ ስሙ ያልተጠመቁ አሕዛብ በእስትንፋሱ ምክንያትና የምሕረት እስትንፋስን እፍ እንዲል እስትንፋሱንም ከአድማስ እስከ አድማስ ጽንፍ እስከ ጽንፍ ይደርስ ዘንድ እግዚአብሔር አዘዘው፡፡ በእግዚአብሔር በቅዱስ ስሙ ያልተጠመቁ አሕዛብ በእስትንፋሱ ምክንያት ልጅነት አግኝተው እንዲከብሩ በቃል ኪዳኑ ተማፅነው ሳይጠመቁ በሚሞቱበት ጊዜ "ይህ ከእኔ የተቀበልከው ቃልኪዳን ከጎኔና ከሰውነቴ እንደፈሰሰው ደሜ ይሁንላቸው" በማለት ለዓለም መድኃኒት አድርጎ ቃልኪዳን ሰጠው፡፡
❤ ዳግመኛም በቅዱስ አባታችን ዘርዐ ቡሩክ ስም ከእግዚአብሔር ምሕረትን ለምነው በሚሞቱበት ጊዜ በውኃና በመንፈስ ቅዱስ እንደተጠመቁ ይሁንላቸው ብሎ ነገረው፡፡ በከበረና በገናና ስሙ የተጠመቁ ሕዝቡም በኃጢአታቸው በወደቁ ጊዜ በሥራቸውም በረከሱ ጊዜ በጻድቁ ጸሎት ቢማጸኑ በቃልኪዳኑ ቢያምኑ ይህ እስትንፋሱ የኃጢአት ማስተሠርያ ይሁናቸው ብሎታል፡፡ ጻድቁ አባታችንም የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በሰማ ጊዜ ከዚያ በፊት ለሌሎች ያልተሰጠ ቃልኪዳን ተቀብሎ በአድማስ ላይ ቆመ፡፡ በዚያም ቆሞ መንፈሳዊ እስትንፋሱን በምድር ላይ እፍ አለ፡፡ ያም የሕይወት እስትንፋስ በአራቱ ማዕዘን ደርሶ በኃጢአታቸው መከራ የተቀበሉ ለበደላቸውም የተገዙ ሰዎች በፈጣሪያቸው ስም እንዲከብሩ ዓለሙን ሁሉ ባረከ" ይላል ቅዱስ ገድላቸው፡፡ ይህም የሚያሳያየው መድኃኔዓለም ክርስቶስ የሰውን ልጆች ምን ያህል እንደወደዳቸውና በትንሽ ምክንያት የመዳንን መንገድ ያዘጋጀላቸው መሆኑን ነው፡፡
❤ ሌላው አቡነ ዘርዐ ቡሩክ እሳቸው በባረኳት ምድርና በልጆቻቸው ላይ ችግርና ርኀብ እንደማይደርስባቸው ቃልኪዳን የተሰጣቸው ድንቅ አባት ናቸው፡፡ ይኸውም በቅርቡ እንኳን በ1977ቱ የርሃብ ዘመን በግልጽ ስለታየ ታሪክ ይመሰክረዋል፡፡ በዚህ ወቅት ከወሎና ከሌሎችም ቦታዎች በርሃብ ተሰዶ ጎጃም ለመጣው የሀገራችን ሕዝብ የአቡነ ዘርዐ ቡሩክ በረከት ከበቂ በላይ ነበር፡፡
❤ ጻድቁ በጎጃም ባሕር ዳር አካባቢ ሁለት ቤተ ክርስቲያን አላቸው፡፡ የዓባይ ምንጭ መነሻ የሆነው ፈለገ ግዮን ግሽ ዓባይ ከባሕር ዳር ከተማ 174 ኪ.ሜ የሚርቅ ሲሆን ከባሕር ዳር ቲሊሊ፣ ከቲሊሊ ሠከላ በመሳፈር በቦታው ላይ ለብዙ ዘመን ቆመው በመጸለይ ታላቅ ቃልኪዳን የተቀበሉበትን እጅግ ተአምረኛና ፈዋሽ የሆነውን ጸበላቸውን ማግኘት ይቻላል፡፡ ቦታው መጽሐፋቸውን ለዓባይ ወንዝ አደራ የሰጡበት ነው፡፡
❤ ሌላኛው ቤተ ክርስቲያናቸው ከባሕር ዳር የሁለት ሰዓት የመኪና መንገድ ርቀት ላይ በምትገኘውና አዴት በምትባለው ቦታ የሚገኘው ነው፡፡ የአቡነ ዘርዐ ቡሩክ መካነ መቃብራቸውና ከሰማይ የወረደላቸው መስቀል እዚህ ይገኛሉ፡፡ ቦታውን የረገጠ ሁሉ ከመካነ መቃብራቸው ላይ እምነት ይወስዳል፣ በመስቀሉም ይባረካል፡፡ ነገር ግን ጻድቁ በቃል ኪዳናቸው መሠረት በዚህ መስቀላቸው የተባረከ ሁሉ ዲቁናን፣ ክህነትን መቀበል ስለሚችል ሴቶች አይባረኩበትም፡፡ መካነ መቃብራቸው ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ከመቅደሱ ውጭ የሚገኝ ሲሆን ከመቃነ መቃብራቸው ላይ ያለው አፈር ሁልጊዜ እየፈላ መጠኑ ይጨምራል፡፡ ይህን የእምነቱን አፈር ቢዝቁት አያልቅም፣ ባዶ እንኳን ቢደረግ በተአምራት ሞልቶ ይገኛል፡፡ ለብዙ ሕመምተኞች ፍጹም ፈውስ የሆነው ይህ እምነት አጠቃላይ ሁኔታው ለዕይታ አመቺ ስለሆነ ይህንን ማንኛውም ሰው ወንዶችም ሆኑ ሴቶች ማየትና እምነቱን ወስደው መጠቀም ይችላሉ፡፡
❤ ጻድቁ አባታችን በ482 ዓመታቸው በዚህች ዕለት ጥር 13 ቀን በታላቅ ክብር ያረፉበት በዓላቸው በድምቀት ይከበራል፡፡ በዕረፍታቸው ዕለት ከቤተ ክርስቲያኑ አደባባይ ላይ አትሮንስ ወጥቶ ገድላቸው ይነበባል፡፡ ገድላቸው ሲነበብም ከአትሮንሱ ሥር ሰባት ጠርሙሶችና አንድ ማሰሮ ይቀመጥና በጠርሙሶቹ ውስጥ አንድ አንድ ስኒ ውኃ ይደረግባቸዋል፡፡ የአባታችን ቅዱስ ገድላቸው ሲነበብ ውኃው ይፈላል፣ ገድሉ ተነቦ እንዳለቀ ጠርሙሶቹና ማሰሮው በተአምራት ተሞልተው ይገኛሉ፡፡
❤ ጌታችን ለአቡነ ዘርዐ ቡሩክ ትንባሆን ስለሚጠጡ ሰዎች ታላቅ ምሥጢርን እንደነገራቸው በቅዱስ ገድላቸው ላይ ተጽፏል፡፡ ቅዱስ አባታችን በየቀኑ ለሰባት ሰዓት ያህል በሲኦል ውስጥ ቆመው በመጸለይ ብዙ ነፍሳትን ከእሳት ያወጡ ነበር፡፡ አንድ ቀን ብዙ ነፍሳትን ካወጡ በኋላ አንዲት ነፍስ ግን ከሲኦል ግደግዳ ጋር እንደ ሰም ተጣብቃ እምቢ አለቻቸው፡፡ አባታችንም ያቺን ነፍስ አወጣለሁ ሲሉ ቆመው ይጸልዩበት የነበረው የሲኦል እሳት አሁን ያችን ነፍስ አወጣላሁ ባሉ ሰዓት ግን አቃጠላቸው፡፡ እሳቸውም ያችን ነፍስ እዚያው ሲኦል ጥለው በመውጣት ጌታችንን "የዚያች ነፍስ ኃጢአቷ ምንድን ነው?" አሉት፡፡ የዚህን ጊዜ ነው ጌታችን ትንባሆን ስለሚጠጡ ሰዎች ታላቅ ምሥጢርን የነገራቸው፡፡ ይኸውም አባ ሐዊ የሚባሉ ጻድቅ ያስተላለፉትን ውግዘትና ግዝት የጸና እንደሆነ ነው ጌታችን ለአቡነ ዘርዐ ቡሩክ የነገራቸው፡፡
❤ ዝርዝር ታሪኩም በድርሳነ መድኃዓለም ላይ እንዲህ ተጽፎ ይገኛል፡- ትንባሆ የሚጠጡ ሰዎች ለምን ለማቆም እንደሚቸገሩና መጨረሻቸውም ምን እንደሆነ፡- "ይቅርታውና ምሕረቱ ከሁላችን የጥምቀት ልጆች ጋር ይሁንና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መድኃኔዓለም ያደረገው ተአምር ይህ ነው፡- አባታችን ዘርዓ ቡሩክ መድኃኔዓለምን እንደወደደውና በየወሩ በሃያ ሰባት ቀን በዓሉን እንደሚያከብር በአሥራ ስድስት ቀንም ኪዳነ ምሕረትን እንደሚያከብር እነሆ እንነግራችኋለን፡፡ ባለሟልነትን ባገኘ ጊዜና መድኃኔዓለም የእሳት ፈረስንና የመስቀል ምልክት ያለበት የወርቅ በትርን በሰጠው ጊዜ "ወደ ሲዖል ሂድና መሸከም የምትችለውን ያህል ነፍሳትን አውጣ› አለው፡፡ ሄዶም ወደ ሲዖል ገባ፣ ነፍስ በነፍስ ላይ እንደ ንብ እየተጨናነቁ በሰውነቱ ላይ ታዘሉ፡፡ ነፍሳትንም ይዞ ሲወጣ አንድ ኃጢአተኛ ‹ዘርዓ ቡሩክ ብቻዬን ቀረሁ፣ አውጣኝ" አለው፡፡ ዘርዓ ቡሩክም ወደ እርሱ ተመልሶ ሳበው፡፡ ሰም ከፈትል ጋራ እንደሚጣበቅ ከሲዖል ጥልቅ ጋራ ተጣብቆ እምቢ አለው፡፡ የእሳቱ ነበልባልም ዘርዓ ቡሩክን አቃጠለው፣ እርሱም ተወው፡፡ ክብር ይግባውና እነዚያን ነፍሳት ይዞ ወደ ጌታው ወደ መድኃኔዓለም ሄደ፡፡
❤ ሄዶም "ጌታዬ ሆይ! አንዲት ነፍስ ስሜን እየጠራች ቀርታለች ማርልኝ" አለው፡፡ መድኃኔዓለምም "ዘርዓ ቡሩክ ሆይ! በእኔ ዘንድ ባለሟልነትን ብታገኝ ትንባሆ የሚጠጣውን ማርልኝ ትለኛለህን?" አለው፡፡ እርሱም "ጌታዬ ሆይ! ይህቺ እንጨት በምን ትከፋለች?፣ ከሁሉ ኃጢአትስ በምን ትበልጣለች?" አለው፡፡ ወይቤሎ መድኅን ኢሰማዕከኑ ግብራ ለዛቲ ዕፅ ዘከመ ዘርዓ ሰይጣን ውስተ ገራህተ ዓለም፡፡ መድኃኔዓለምም "የዚህችን እንጨት ሥራ በዓለም እርሻ ሰይጣን እንደዘራት አልሰማህምን?" አለው፡፡ እነሆም እንነግራችኋለን፣ ስሙ ሐዊ የሚባል የፈጣሪውንም ሕግ የሚጠብቅ አንድ መምህር ነበረ፡፡ በዓርብ ቀንም ወደ ሰማይ ይሔዳል፤ በቀዳሚት ሰንበትና በእሑድ ከፈጣሪው ጋር ይነጋገራል፡፡ በሰኞ ቀንም ወደ ቦታው ይመለሳል፡፡ ለሀገር ሰዎችም በጉባኤ ይነግራቸዋል፣
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፯ (27) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ ሲዖል ውስጥ ገብተው ይጸልዩ ለነበሩት ለታላቁ አባት #ለአቡነ_ዘርዐ_ብሩክ_ለልደታቸው_በዓል እግዚአብሔር አምላክ ሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ዘርዐ_ቡሩክ፦ ከመወለዳቸው አስቀድሞ ትንቢት ተነግሮላቸው ነበር፡፡ አባታቸው ደመ ክርስቶስ ዐይነ ሥውር የነበረ ሲሆን አቡነ ዘርዐ ቡሩክ በተወለዱ ጊዜ ግን የአባታቸውን ዐይን አብርተውለታል፡፡ አባታችን ዘርዐ ቡሩክ ገና በሰባት ዓመታቸው ነው ረቡዕና ዓርብ መጾም የጀመሩት፡፡ በዚሁ በሰባት ዓመታቸውም "ይህን ዓለም ክፋቱን እንዳላይ ዐይኖቼን አሳውርልኝ" በማለት ዐይናቸውን እንዲያጠፋላቸው አምላካቸውን ለምነው እንደፈቃዳቸው ዐይነ ሥውር ሆነዋል፡፡ ነገር ግን ከሰባት ዓመት በኋላ በ12 ዓመታቸው ጌታችን "ለዓለም የምታበራ ብርሃን አደርግሃለሁና ዐይንህም ይብራ" በማለት ዐይነ ብርሃናቸውን መልሶላቸው እንዲያዩ አድርጓቸዋል፡፡ በዚህም ዕድሜያቸው (በ12 ዓመታቸው) ሰባቱንም አጽዋማት ይጾሙ ነበር፡፡
❤ ከዚህም በኋላ ጌታችን የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ሁሉ ገለጠላቸው፡፡ መጻሕፍተ ብሉያትን፣ መጻሕፍተ ሐዲሳትን፣ መጻሕፍተ ሊቃውንትን፣ መጻሕፍተ መነኮሳትን፣ አዋልድ መጻሕፍትን ሁሉ ገልጦላቸዋል፡፡ ከሟርት መጻሕፍት በቀር ያስቀረባቸው ነገር አልነበረም፤ የቅዱስ ያሬድንም ዜማ እንዲሁ ገለጠላቸው፡፡
❤ ጻድቁ ከሁሉ ቅዱሳን በበለጠ ሁኔታ ዐሥራ ሁለት ክንፍ የተሰጣቸው ሲሆን በ12 ክንፎቻቸውም የሰማይን ደጆች ሁሉ ገሃነመ እሳትንም አልፈው በመሄድ ቀጥታ በሥሉስ ቅዱስ ዙፋን ፊት ይቆሙ እንደነበር ቅዱስ ገድላቸው ይናገራል፡፡ እጅግ በሚደንቅና ከአእምሮ በላይ በሆነ ሁኔታ አባታችን ለሰባት ቀናት በየቀኑ ለሰባት ሰዓት ያህል በሲኦል ውስጥ ቆመው ይጸልዩ ነበር፡፡ ብዙዎቹ ቅዱሳን በምልጃቸው ነፍሳትን ከሲኦል ሲያወጡ ነው የምናውቀው እንጂ እንደ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ በሲኦል ውስጥ ገብቶ ጸሎት የጸለየ ጻድቅ እስካሁን እኔ አላጋጠመኝም፡፡
❤ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ እንደ አባታችን ተክለሃይማኖት ለጸሎት በመቆም ብዛት አንድ እግራቸው እስኪሰበር ድረስ በብዙ መከራ ተጋድለዋል፡፡ ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ጋር መንበሩን ያጥኑ ዘንድ ከፈጣሪአቸው ታዘው አጥነዋል፡፡ ጌታችን ለአቡነ ዘርዐ ቡሩክ ፍጥረታትን ከመፍጠር በቀር ያልሰጣቸው ሥልጣን የለም፡፡ "እግዚአብሔር ብፁዕና ቅዱስ ለሚሆን አባታችን ዘርዐ ቡሩክ "እኔ ከሥልጣኔ ሥልጣንን፣ ከክብሬም ክብርን፣ ከጥበቤም ጥበብን፣ ከተአምራቴም ተአምራትን፣ ከስጦታዬም ስጦታን፣ ከትዕግስቴም ትዕግስትን፣ ከፍቅሬም ፍቅርን፣ ከትሕትናዬም ትሕትናን፣ ከባለሟልነቴም ባለሟልነትን ሰጥቼሃለሁና ሁሉ ከሥልጣንህ በታች ሆኖ ይታዘዝልህ" የሚል እጅግ ድንቅ ቃልኪዳን ነው የሰጣቸው፡፡ ልዩ ልዩ ሀብታትን ሁሉ ሰጣቸው፡፡ "ለሥላሴ ከሚገባ ከስግደትና በቃልና በሥልጣን ፍጥረታትን ለመፍጠር በቀር ምንም ያልሰጠሁህ የለም" ብሎ ጌታችን በማይታበል ቃሉ እንደነገራቸውና ቃል እንደገባላቸው በቅዱስ ገድላቸው ላይ ተጽፏል፡፡ (የአባታችን ገድላቸው ከመጥፋቱ የተነሣ በአሁኑ ሰዓት አንዳንድ ነጋዴዎች አንዱን ፍሬ ከ3 ሺህ ብር በላይ እየሸጡት ነበር፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ ቲሊሊ የሚገኘው ገዳማቸው በድጋሚ አሳትሞታል፡፡
❤ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ በወቅቱ በነበረው ገዥ ፊት በሐሰት ተከሰው ለ5 ዓመታት ያህል በእስርና በእንግልት ሲኖሩ በእነዚህ ጊዜያት ሁሉ ምግብ የሚባል አይቀምሱም ነበርና ከእስር ሲፈቱ አምስት ዓመት ሙሉ ሲሰጣቸው ያጠራቅሙት የነበረው ምግብ ትኩስ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ያሳሰራቸውንም ንጉሥ ገና ሕፃን ሳለ እናቱ ልታስባርከው ወደ አባታችን ዘንድ ወስዳው ነበር፡፡ አቡነ ዘርዐ ቡሩክም ሕፃኑን ከባረኩት በኋላ ለእናቱ "ይህ ልጅሽ ወደፊት ይነግሣል በንግሥናው ዘመንም እኔን ያስርና ያንገላታኛል" ብለው ይህ እንደሚሆን አስቀድመው ትንቢት ተናግረው ነበር፡፡ እንዳሉትም ልጁ አድጎ ሲነግሥ ጭፍሮቹ "ንጉሥ ሆይ አንተን የማይወድ ለቃልህም የማይታዘዝ አንድ መነኩሴ አለ" በማለት ምንም እንኳን ንጉሡ ባያውቃቸውም በሐሰት ነገር ስለከሰሱለት በግዞት እንዲኖሩና እንዲታሰሩ አድርጓቸዋል፡፡ ጻድቁ በግዞት ሲወሰዱ "እነዚህን መጻሕፍቶቼን ለሰዎች አደራ ብሰጣቸው ይክዱኛል፣ ቤተ ክርስቲያን ባስቀምጣቸው ይጠፉብኛል" በማለት ሰባት መጽሐፎቻቸውን ለግዮን (ለዓባይ) ወንዝ አደራ የሰጡ ሲሆን ከ5 ዓመት በኋላ ከእስር ተፈተው ሲመለሱ በወንዙ አጠገብ እንደደረሱ ጸሎት ካደረጉ በኋላ "ግዮን ሆይ በእግዚአብሔር ፊት በአደራ የሰጠሁሽን መጽሐፎቼን ግሺ (ትፊ)" ብለው እጃቸውን ወደ ወንዙ ሰደው መጽሐፎቻቸው ሳይረጥቡና ሳይበሰብሱ ከወንዙ ውስጥ አውጥተዋቸል፡፡ እንዲያውም አቧራውን ከመጻሕፍቶቻቸው ላይ እፍ ብለው አራግፈውታል፡፡
❤ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተጠቀሰው የጠለቀው ምሳር እየተንሳፈፈ ወደ ኤልሳዕ እንደመጣ ሁሉ አሁንም እንዲሁ የቅዱስ አባታችን መጽሐፎች አብሯቸው ከነበረውና ዘሩባቤል ከሚባለው ደቀ መዝሙራቸው ጋር ወዳሉበት ተንሳፈው ሊመጡ ችለዋል፡፡ መጽሐፎቻቸውንም አብሯቸው ለነበረው ደቀ መዝሙራቸው ካሳዩት በኋላ እንዲይዛቸው ሰጥተውታል፡፡
❤ የግዮን ወንዝ "ግሺ ዓባይ" ወይም "ዓባይ" እየተባለ መጠራት የጀመረው አቡነ ዘርዐ ቡሩክ "ግዮን ሆይ በእግዚአብሔር ፊት በአደራ የሰጠሁሽን መጽሐፎቼን ግሺ (ትፊ)" ብለው እጃቸውን ወደ ወንዙ ሰደው መጽሐፎቻቸው ሳይረጥቡና ሳይበሰብሱ ከወንዙ ውስጥ ካወጡበት ጊዜ ጀምሮ ነው፡፡ አባታችን በቦታው ላይ 30 ዓመት ሙሉ ቆመው ጸልየው ቦታውን የባረኩት ሲሆን ጌታችንም በቦታው ላይ ትልቅ ቃልኪዳን ሰጥቷቸዋል፡፡ "ብፁዕ አባታችን ለግዮን ወንዝ መጽሐፎቹን በአደራ ሰጥተው በኋላም ከደቀ መዝሙራቸው ከዘሩባቤል ጋር መጽሐፎቹን ከግዮን ምንጭ ውስጥ ከተቀበለ በኋላ "በግዮን ውኃ ውስጥ ሳይረጥቡ በደረቅ መጽሐፎቼን የጠበቀ እግዚአብሔር ይመስገን" ብሎ ፈጣሪውን አመሰገነ፡፡ "ያንጊዜም በውስጥሽ ታላቅ ድኅነት ይደረግብሽ፣ ሕመምተኞች ሁሉ ይዳኑብሽ፣ መካኖች ይውለዱብሽ" ብሎ ግዮንን በቃሉ መረቃት፣ በእጁም ባረካት፡፡ ብፁዕ አባታችንም በዚህች ቦታ ላይ ፈውስ፣ ረድኤት፣ በረከት ይደረግብሽ ብሎ ብዙ ዘመን ቆሞ ጸለየ፡፡ እግዚአብሔርም ጸሎቱን ሰምቶ "ይህ በረከት፣ ረድኤት፣ ሀብት፣ ፈውስ እንደወደድህ እስከዘለዓለሙ በዚህ ቦታ ይሁንልህ" አለው" ተብሎ ነው በቅዱስ ገድላቸው ላይ የተጻፈው፡፡
❤ ጻድቁ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ ሌላው የሚታወቁበት "ብሄሞትና ሌዋታን" የተባሉ እጅግ ግዙፍ የሆኑ ሁለት ዘንዶዎችን ጥርሳቸውን ቆጥረው ምላሳቸው ሲጣበቅ የዓለም ፍጻሜ እንደሚሆን አስቀድመው ያወቁ ድንቅ ነቢይ የሆኑ አባት በመሆናቸው ነው፡፡ እነዚህም እጅግ ግዙፍ የሆኑ ሁለት እንስሳት ሴትና ወንድ ሆነው ምድርን እንደመቀነት ከበው የያዙ ናቸው፡፡ ዝርዝር ታሪካቸው በመጽሐፈ አክሲማሮስ (ሥነ ፍጥረትን በሚያስረዳው መጽሐፍ) ላይ በስፋት ተጠቅሰዋል፡፡
🌿🌿🌿🌿 የዕለቱን ወንጌል እናንብብ! 🌿🌿🌿🌿
ዕለተ ረቡዕ! ነሐሴ 27 ቀን 2018 ዓ.ም
የዮሐንስ ወንጌል ም 12 ቁ 26 - 31
——————————————————————————
²⁶ የሚያገለግለኝ ቢኖር ይከተለኝ፥ እኔም ባለሁበት አገልጋዬ ደግሞ በዚያ ይሆናል፤ የሚያገለግለኝም ቢኖር አብ ያከብረዋል።
²⁷ አሁን ነፍሴ ታውካለች ምንስ እላለሁ? አባት ሆይ፥ ከዚህ ሰዓት አድነኝ። ነገር ግን ስለዚህ ወደዚህ ሰዓት መጣሁ።
²⁸ አባት ሆይ፥ ስምህን አክብረው። ስለዚህም፦ አከበርሁት ደግሞም አከብረዋለሁ የሚል ድምፅ ከሰማይ መጣ።
²⁹ በዚያ ቆመው የነበሩትም ሕዝብ በሰሙ ጊዜ፦ ነጐድጓድ ነው አሉ፤ ሌሎች፦ መልአክ ተናገረው አሉ።
³⁰ ኢየሱስም መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ ይህ ድምፅ ስለ እናንተ መጥቶአል እጂ ስለ እኔ አይደለም።
🔴ይህን ግሩፕ ✨pin ✨እንዲሁም✨ unmute ✨ ማድረጎን አይርሱ ❗️❗️❗️
✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨✨
√ የዩቲዩብ ገጻችንን
https://youtube.com/@FinoteBirhanzkidistarsema?feature=shared
√ ፌስቡክ ገጻች
https://www.facebook.com/finotebirhanzekidistarsema
√ የቴሌግራም ገጻችንን
https://t.me @Z_FINOTE_BIRHAN
√ የኢንስታግራም ገጻችን
https://www.instagram.com/ FINOTE BIRHAN Z KIDIST ARSEMA
√ የቲክ ቶክ ገጻችንን
tiktok.com/@finotebirhanzkidstarsema
✨✨ፎሎ በማድረግ ቤተሰብ ይሁኑ ✨✨
✨✨✨✨ሰናይ ዕለት✨✨✨
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፮ (26) ቀን።
❤ እንኳን #ለአብርሃም_ሚስት ለተመሰገነች ለእናታችን #ለቅድስት_ሣራ ለበዓሏ ለመታሰቢያዋ ቀንና ለከበሩ #ለአባ_ሞይስስና ከእኅቱ #ቅድስት_ሣራ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ ከዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ በከሀዲው ሉልያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ከዐረፉ #ከመነኰሳት_አጋቦስና_ቴክላ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤት በረከት፡ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #በዚህች_ቀን_ለቅዱስ_አብርሃም ሚስት ለተመሰገነች #ቅድስት_ሣራ መታሰቢያዋን እናደርግ ዘንድ የቤተ ክርስቲያን መምህራን አባቶች አዘዙ።
❤ ይቺንም ክብርተ ማሕፀን የሆነች ጡቶቿም የተባረኩ ክብርት ሣራን የጌራራ ንጉሥ አቤሜሌክ ባል እንዳላት ሳያውቅ በወሰዳት ጊዜ እንዳይቀርባት እግዚአብሔር ገሠጸው በደዌም ቀሠፈው ባሏ አብርሃምም በጸለየለት ጊዜ ከደዌው ተፈወሰ ከዚህም በኋላ ከብዙ ገንዘብ ጋራ ወደ ባሏ መለሳት።
❤ ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር በሦስትነቱ ተገልጦ ወደ ቤቷ እንግድነት በመጣ ጊዜ ለአብርሃምም የይስሐቅን መወለድ በነገረው ጊዜ ሣራም በድንኳኑ ውስጥ ሳቀች እንዲህ ስትል "እስከ ዛሬ ገና ነኝን ጌታዬም አርጅቷል"። እግዚአብሔርም አብርሃምን እንዲህ አለው "ሣራን ለብቻዋ ምን አሳቃት እስከ ዛሬ ገና ነኝን ጌታዬም አርጅቷል እኔም አሁን አርጅቻለሁ ብላ በውኑ ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር አለን"።
❤ ከዚህም በኋላ ሣራ ፀንሳ እግዚአብሔር ባለው ወራት በርጅናዋ ለአብርሃም ወንድ ልጅን ወለደች። ይስሐቅም በአደገ ጊዜ ልጅዋ ይስሐቅን ከእስማኤል ጋራ ሲጫወት አየችው። አብርሃምንም ሣራ እንዲህ አለችው "ይቺን ባሪያ ከነልጅዋ አባራት የባሪያ ልጅ ከልጄ ከይስሐቅ ጋራ አይወርስምና"። ይህም ነገር ለአብርሃም ስለ ልጁ እስማኤል እጅግ ጭንቅ ሆነበት።
❤ እግዚአብሔርም አብርሃምን እንዲህ አለው "የዚህ ልጅ የዚችም ባሪያ ነገር በፊትህ ጭንቅ አይሁንብህ የምትልህን ሁሉ ሣራን ስማት ከይስሐቅ ዘር ይተካልሃልና"።
❤ ይህም ነገር ታላቅ ምሥጢር አለው የተመሰገነ ጳውሎስ ቅድስት ሣራን የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ አድርጓታልና። ከዚህም በኋላ በበጎ እርጅና በአረፈች ጊዜ ከኬጢያዊ ኤሞር ልጆች በገዛው ቦታ ቀበራት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በከበረች እናታችን ቅድስት ሣራ በጸሎቷ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰማዕታት_አባ_ሞይስስና_እህቱ_ቅድስት_ሣራ፦ የእሊህም ቅዱሳን ወላጆቻቸው ደጎች እጅግም ባለጸጎች ናቸው። የከበረ ሞይስስ ወላጆቹ ከዐረፉ በኋላ እኅቱ ሣራን ሊአጋባትና ወላጆቹ የተዉትን ገንዘብም ሊሰጣት እርሱም ወደ ገዳም ሒዶ ሊመነኵስ አሰበ። ይህን አሳቡንም በነገራት ጊዜ እንዲህ ብላ መለሰችለት "እኔን ልታጋባኝ ከወደድክ አስቀድሞ አንተ አግባ" እርሱም እንዲህ አላት "እኔ ብዙ ኃጢአት ሠርቻለሁ ስለዚህ ኃጢአቴን ለመደምሰስ እመነኵስ ዘንድ እሻለሁ ማግባት አይቻለኝም የነፍሴን መዳኛ አስባለሁ እንጂ"።
❤ ሁለተኛም እንዲህ ብላ መለሰችለት "አንተ ነፍስህን ስታድን እኔን በዓለም ወጥመድ ውስጥ እንዴት ትጥለኛለህ"። እርሱም እንዲህ አላት "ምንኵስና ከፈለግሽ ስለ ራስሽ የምታውቂ አንቺ ነሽ እኔም የወደድሺውን አደርግልሻለሁ"። እንዲህም አለችው "ለነፍስህ የምታደርገውን ለኔም እንዲሁ አድርግ እኛ ሁለታችን ከአንድ ባሕርይ ከአንድ አባት ከአንዲት እናት የተገኘን ነንና" የልቧንም ቆራጥነት አይቶ ወዲያውኑ ከእርሷ ጋራ ተነሣ ገንዘባቸውንም ሁሉ ለድኆችና ለምስኪኖች በተኑ።
❤ ከዚህም በኋላ እኅቱ ሣራን ወሰዳት ከእስክንድርያ ከተማ ውጭ ወዳለ የደናግል ገዳም ውስጥ አስገባት እርሱም ከወንዶች ገዳም ገብቶ በዚያ ተጋድሎን ተጋደለ። እንዲሁ እኅቱም ጽኑዕ በሆነ ገድል ተጠምዳ እየተጋደለች ሁለቱም ሳይገናኙ ዐሥር ዓመት ኖሩ።
❤ በሊቀ ጳጳሳት አባ ድሜጥሮስ የሹመት ዘመን ሳዊርያኖስ የሚባል ከሀዲ ተነሥቶ የክርስቲያንን ወገኖች ማሠቃየት ጀመረ። ከመነኰሳት ገዳማትም ብዙዎች በሰማዕትነት ሞቱ። አባ ሞይስስም ተነሣ ሊሰናበታትም ወደ እኅቱ ሣራ ላከ በሰማዕትነት መሞት እንደሚሻም ነገራት። ሣራ እኅቱም በሰማች ጊዜ ወዲያውኑ ተነሣች ሒዳ በሰማዕትነት ትሞት ዘንድ እንድታሰናብታት እመ ምኔቷን ለመነቻት እመ ምኔቷም ጸለየለችላት ሰላምታም ሰጥታ አሰናበተቻት እርሷም ደናግሉን ሁሉ ተሰናበተቻቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ ወንድሟ ሔደች በጐዳናም አገኘችውና እርስ በርሳቸው ሰላም ተባባሉ ወደ እስክንድርያ ከተማም ገብተው በመኰንኑ ፊት ቁመው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ መኰንኑም ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃያቸው ከዚህም በኋላ ራሳቸውን በሰይፍ አስቆረጠ። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰማዕታት_መነኰሳት_አጋቦስና_ቴክላ፦ እሊህም ቅዱሳን በከሀዲው ሉልያኖስ ዘመን መከራ በመቀበል ተጋደሉ። ከመኳንንቶቹም አንዱ ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃያቸው። ሥቃያቸውም በአሰለቸው ጊዜ ለአንበሶች ጣላቸውና ገድላቸውን ፈጽመው የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ። የመነኰሳት አባ አጋቦስና እህቱ ቅድስት ቴክላ በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
+ + +
❤ "#ሰላም_ለክሙ_ሣራ_ወሞይሰስ። ወለቴክላ ሰላም ወአጋቦስ። ዘኀበርክሙ መዊተ በእንተ ክርስቶስ። እትሜነይ በደምክሙ ነጺሐ እምርኵስ። ወበብዕልክሙ እብዓል ጽኑስ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የነሐሴ_26።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ብፁዕ አንተ ወሠናይ ለከ። ብእሲትከ ከመ ወይን ሥሙር ውስተ ጽርሐ ቤትከ። ወውሉድከ ከመ ተክለ ዘይት ሐዲስ ዓውደ ማዕድከ"። መዝ 127፥2-3። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 11፥8-17፣ 1 ጴጥ 3፥1-10 እና 16፥1-16። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 5፥27-33። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የአቡነ ሀብተ ማርያምና የአቡነ ኢየሱስ ሞዐ የፅንሰት በዓልና የቅስት ሣራ የዕረፍት በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
ክርስቲያን ቀን ቀን ሕዝቡን ሲያስተምሩ በመዋል ሲመሽ ወደ ሐይቁ በመግባት ሲጸልዩ ያድሩ ነበር፡፡ በሐይቅ እስጢፋኖስና በዙርያው ለነበሩ አበው ማታ ማታ አንድ ብርሃን ወደ ሐይቁ ሲገባ ጠዋት ጠዋትም ሲወጣ ይታያቸው ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ አባታችን በገዳሙ አባቶች ልመናና በልዑል እግዚአብሔር ትዕዛዝ ወደ ሐይቅ ገዳም ገብተው አበምኔት ሆኑ፡፡
❤ ሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም ከደሴ 30 ኪሎ ሜትር ርቆ የሚገኝ ሲሆን የመሠረቱት ካልዕ ሰላማ የተባሉ ግብፃዊ ጻድቅ ናቸው፡፡ ሐይቅን አባ ሰላማ ካልዕና ዐፄ ድል ነአድ በ862 ዓ.ም ነው የቆረቆሩት። ገዳሙን ካቀኑት በኋላ "የማንን ታቦት እናስገባ?" ብለው ሲያስቡ ቶራ የምትባል እንስሳ ጭነት ተጭና ከመካከላቸው ተገኘች፤ ጭነቱን አውርደው ቢያዩት በሐር ጨርቅ የተጠቀለለ የቅዱስ እስጢፋኖስንና የቅዱስ ጊዮርጊስን ሁለት ታቦት አገኙ፡፡ በላዩም ላይ "ይህንን ታቦት በኢየሩሳሌም የሚኖሩ የተሰወሩ ቅዱሳን ከእግዚአብሔር ታዘው የላኩት ነው" የሚል ጽሑፍ አገኙ፡፡ ይህ ከሆነ ከ 400 ዘመን በኋላ ነው አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ወደዚህ ቦታ የመጡት፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ለ52 ዓመት ቀን ቀን መንፈሳዊ ሥራቸውን እየሠሩ ሌሊት ሌሊት ሐይቁ ውስጥ ቆመው ሲጸልዩ ያድራሉ፡፡
❤ አባ ኢየሱስ ሞዐ በሐይቅ እስጢፋኖስ በአበ ምኔትነት በቆዩባቸው 45 ዓመታት ከየገዳማቱ ቅዱሳን መጻሕፍትን በመገልበጥና በማሰባሰብ የመጀመርያው ዘመናዊ የቤተ ክርስቲያን ቤተ መጻሕፍት በሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም እንዲቋቋም አድርገዋል፡፡ በዚሁ ገዳም ውስጥ የመጀመርያውን የቤተ ክርስቲያን ቋሚ ትምህርት ቤት በማቋቋም 800 መነኰሳትን በትምህርተ ሃይማኖት አሠልጥነው በንቡረ ዕድነት ማዕረግ ሾመው በመላ ሀገራችን እንዲሠማሩ አድርገዋቸዋል፡፡ ከእነዚህም ተማሪዎቻቸው መካከል አቡነ ተክለ ሃይማኖት (ደብረ ሊባኖስ)፣ አቡነ ኂሩተ አምላክ (ጣና ሐይቅ ዳጋ እስጢፋኖስ)፣ አቡነ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ (ቦረና)፣ አባ በጸሎተ ሚካኤል (ቦረና)፣ አቡነ ገብረ እንድርያስ (ቦረና)፣ አቡነ ሕዝቅያስ (ቦረና)፣ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ (ዳውንት)፣ አቡነ አሮን (መቄት)፣ አቡነ ተክለ ኢየሱስ ሞዐ (ሐይቅ)፣ አቡነ አላኒቆስ (ትግራይ)፣ አቡነ በግዑ (ሐይቅ)፣ አቡነ ሠረቀ ብርሃን (ሐይቅ)፣ አቡነ ብስጣውሮስ (ሐይቅ)፣ አቡነ ዮሴፍ (ላስታ) ዋና ዋናዎቹና በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ጻደቁን ንጉሥ ዐፄ ይኩኖ አምላክንም በትምህርተ ሃይማኖት አንጸውና ኮትኩተው ያሳደጉት ጻድቁ አባታችን ናቸው፡፡
❤ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ መጥተው በሐይቁ ዳር ቆመው ሳለ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ በእግሩ በውኃው ላይ እየሄደ እያሳያቸው ተከትለውት እንዲሄዱ ነገራቸው። አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ሐይቁን በእግራቸው ጠቅጥቀው ተራምደው ተሻግረው አቡነ ኢየሱስ ሞዐን አገኟቸው፡፡ እርሳቸውም አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ እርሳቸው እየመጡ እንደሆነ በመንፈስ ዐውቀው ነበርና ሲያገኟቸው በጣም ተደስተው ከተቀበሏቸው በኋላ አመነኵሰዋቸዋል፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ እጅግ በጣም ብዙ መነኰሳትን አፍርተዋል፡፡ የመጀመሪያው መነኩሴ አባ እንጦንስ ነው፡፡ እንጦንስ መቃርስን፣ መቃርስ ጳኵሚስን፣ ጳኵሚስ ቴዎድሮስን፣ አቡነ አረጋዊንና 8ቱን ቅዱሳን አመነኰሱ፡፡ አቡነ አረጋዊም ወደ ኢትዮጵያ በ460 ዓ.ም መጥተው ክርስቶስ ቤዛን፣ አባ ክርስቶስ ቤዛም መስቀለ ሞዐን፣ መስቀለ ሞዐም አባ ዮሐኒን፣ አባ ዮሐኒም አባ ኢየሱስ ሞዐን፣ አባ ኢየሱም ሞዐም አቡነ ተክለ ሃይማኖትን አመነኰሱ፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ምን ያህል ቀደምትና ባለ ታሪክ አባት እንደሆኑ ከዚህ መረዳት ይቻላል፡፡
❤ በዮዲት ጉዲት እጅጉን ተጐድታ የነበረችው አገራችን ዳግም የወንጌሉ ብርሃን እንዲበራባት ሊቃውንት፣ እንዳይታጡባት፣ ቅዱሳት መጻሕፍት እንዳይቆነጻጸሉ፣ መነኰሳት አባቶች ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ ወርደው ገዳማትን እንዲያስፋፉ ያደረጉት አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለአገራችን ትልቅ ባለውለታ ናቸው፡፡ በተለይም በሐይቅ እስጢፋኖስ ያፈሯቸውን 800 ሊቃውንት መነኰሳት በመላዋ ኢትዮጵያ በመሰማራታቸው ዛሬ የምናያቸውን አብዛኛዎቹን ገዳማትና ቅዱሳት መጻሕፍት አቆይተውልናል፡፡ አባታችን ለ45 ዓመታት ሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳምን በአበ ምኔትነት እያስተዳደሩ ከቆዩ በኋላ ኅዳር 26 ቀን 1292 ዓ.ም በዕለተ እሑድ ዐርፈዋል፡፡ ከአባታች ከአቡነ ኢየሱስ ሞዐ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፮ (26) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጲያውያኑ_ጻድቃን ለአባታችን #ለአቡነ_ሀብተ_ማርያምና ታላቁ ገዳም ሐይቅ እስጢፋኖስ ላቀኑ #ለአቡነ_ኢየሱስ_ሞዐ ለጽንሰታቸው ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል በዓል በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ሀብተ_ማርያም_ጽንሰት፦ " የኢትዮጵያ ንጉሥ እስክንድር በነገሠ በሺህ አራት መቶ ሰማንያ ስድስት ዓመተ ምሕረት ቅዱስ ፍሬ ብሩክ የሚባል አንድ ሰው በዚያች ሀገር ውስጥ ነበር፤ ይኸውም ከከበሩም ሰዎች ተለይቶ ብዙ ገንዘብ ያለው ባለ ጸጋ ነበር። በሕጋዊው ጋብቻ ስሟ ቅድስት ዮስቴና የምትባል ሴት አገባ፤ ይኽችውም ሴት በደግ ሥራ ሁሉ የተሸለመች ያጌጠች ነበረች።
❤ ብዙ ደግቷንና ትሩፋቷን ኋላ እንነግራችኋለን፤ ነገር ግን አስቀድመን በዚህ ዓለም ከሕጋዊ ባሏ ጋር በንጽሕ ጋብቻ እግዚአብሔር በመፍራት ምጽዋትን በመስጠት የውሃትንና ትሕትናን ገንዘብ አድርጋ በትግሥት በበጎ ሥነ ምግባር ሁሉ ጸንታ እንደኖረች እነግራችኋለን።
❤ እንዲህ ባለ ሥራ ሳለች መንፈሳዊ ሐሳብ እንዲህ ሲል ተነሳባት፤ "ለአንቺ በዚህ ዓለም መኖር ምን ይረባሻል የሚል መጣባት፤ ዛሬ የሚያልፍ የሚጠፋ ነውና፤ ጌትነቱ የሚመሰገንበት ለዘለዓለም የሚኖር የማያልፍ ሌላ ዓለም ይገለጣልና"፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል "ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ ቢነዳ በነፍሱ ከተጎዳ ምን ይጠቅመዋል ምን ይረባዋል" እንዳለ።
❤ "ለአንቺ ግን በሰማይ ጸንቶ መኖርና ሁለተኛዋን ሀገር መያዝ ይሻላል" የሚል ሐሳብ መጣባት፤ ይህን ካሰበች በኋላ ፈጥና ተነሥታ በሌሊት ከቤቷ ወጥታ፤ በሀገሯ አንጻር ትይዩ ወደ ሆነው በረሃ ሄደች፣ በውስጡ ከሰው ወገን የማይኖርበት ቦታ መካከሉ ምድረ በዳ ወደ ሆነው በረሃ ደረሰች። ከጅቦች፣ ከነብሮች፣ ከዓሣሞች፣ ከጦጦችና ከዝንጆሮች በስተቀር ምንም ምን የማይኖርበት በረሃ ነበር።
❤ በዚያችም ቦታ ደጃፏ ያልተዘጋች ትንሽ ዋሻ አገኘች ምንም ምንም ሳትናገር ከዋሻው ውስጥ ገባች። በዋሻው ውስጥ ቁሞ በትጋት መዝሙረ ዳዊትን በአንክሮ በተደሞ የሚደግም ክቡር ባሕታዊን አየች፤ ባየችውም ጊዜ ደነገጠች። እርሱም ሴቲቱን ባያት ጊዜ ፍርሃት መንቀጥቀጥ በላዩ ላይ ወረደበት፣ በመስቀል ምልክትን አማተበ። ይህም ቅዱስ ባሕታዊ ፊቱን በአማተበና ስመ እግዚአብሔርንም በጠራ ጊዜ እንዳልሸሸች ስለአየ ይህች ሴት ክርስቲያን መሆኗን አወቀ።
❤ መጀመሪያ ስትገባ የጋኔን ምትሐት መስላው ነበርና፤ ሰው መሆኗን ባወቀና በተረዳ ጊዜ ተቆጣት። "አንቺ ዘማዊት ሴት ምንኵስናየን ታፈርሽ ዘንድ ከየት መጣሽ" አላት። "ወይም ደግሞ ሰይጣን በልብሽ ገብቷልን"። "ጌታዬ እኔስ የሕያው እግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ ነኝ እንጅ አንተ እንደምትለኝ ዘማዊት አይደለሁም" አለችው። "ነገር ግን ቤቴን ንብረቴን ያለኝን ትቼ መጥቻለሁ፣ በዓለም ውስጥ ያለውን ሁሉ ንቄ እመንን ዘንድ እወዳለሁና ስለዚህም ወደዚህ ምድር በዳ መጣሁ። በዚህም ገዳም ወይም በረሃ ሰው እንዳለ አላውቅሁም ነበር፤ ሰውን የሚባሉ አራዊት ብቻ የሚኖሩበት ይመስለኝ ነበር" አለችው።
❤ ይህም ባሕታዊ በትሕትና በፈሪሃ እግዚአብሔር ይህን የሚያስደንቅ መልካም መልስ በመለሰችለት ጊዜ። አንድ ሰዓት ያኽል ካሰበ በኋላ "በፍቅር አንድነት ወደ ቤትሽ ተመለሽ" ብሎ በሰላም ተናገራት። እርሷም "ወደዚህ ቦታ ዳግመኛ አልመጣም እንጅ ካንተ ዘንድ ተለይቼ እሄዳለሁ። ነገር ግን ወደ ቤቴ ተመልሼ አልሄድም። ከገዳማት በአንድ ቦታ መንኵሼ መኖር እወዳለሁ እንጅ" አለችው። ጌታ "በወንጌል እርፍን በእጁ ይዞ ወደ ኋላ የሚያርስ የለም" እንዳለ ወደ ዓለም አልመለስም" አለችው።
❤ ያም ባሕታዊ "ምንኵስናስ የለሽም አልታዘዘልሽም፤ ነገር ግን በሰላም ወደ ቤትሽ ወደ ሕጋዊ ባልሽ ተመለሽ። የተፈቀደልሽንስ እነግርሻለሁ ከሕጋዊ ባለቤትሽ ወንድ ልጅን ትወልጃለሽ እርሱም ለዓለም ሁሉ የሚጠቅም ይሆናል። የገድሉና የትሩፋቱ ዜና እስከ ዓለም ዳርቻ ይደርሳል፤ በሕይወተ ሥጋ ሳለ በፈጣሪው በእግዚአብሔር ፈቃድ የብዙዎቹን ሰዎች ነፍሳት ከሲኦል ያወጣል። እንደ መላእክትም ክንፈ ጸጋ ተሰጥቶታል። በሰው አካል በሥጋ ሁኖ ሳለ በተመሥጦ ወደ ሰማይ ወጥቶ የሥላሴን የአንድነትን የሦስትነት ምሥጢር ያያል"።
❤ ቅድስት ዮስቴናም ከአረጋዊ ባሕታዊ ይህን ነገር ሰምታ አደነቀች፤ "የፈጣሪየ ፈቃድ ከሆነ ወደ ቤቴ እመለሳለሁ" አለች፤ ይህን ብላ ተመልሳ ወደ አገሯ ወደ ቤቷ ገባች፤ ቤተሰቦቿም መውጣቷንም መግባቷንም ምንም አላወቁባትም፤ ከዚያም በነሐሴ 26 ቀን ጸነሰች። ከዘጠኝ ወራትም ከቆየች በኋላ፤ መልኩ እንደ በረዶ ነጭ እንደ ጽጌ ረዳም ብሩህ ቀይ የሆነ መልከ መልካም ልጅ ወለደች ሁለተናውም ጨረቃ የጉለቱ ምልዓት 15 ሌሊት ሁኖ በብሩህ ብርሃን በምልዓት በሚያድርበት ጊዜ እንደሚያበራው መልካም ብርሃን ገጹ ብሩህ የሆነ ልጅ ወለደች፤ ይህ ሕፃን በግንቦት ወር በ 26 በተወለደ ጊዜ በአባቱና በእናቱ ቤት ታላቅ ደስታን ሆነ፤ ሜሉን ገቹን አርደው ዘመዶቻቸውን ጎረቤቶቻቸውን አማቾቻቸውን ምርዓቶቻቸውን ጠርተው ለበዓሉ እንደሚገባ መብሉንና መጠጡን ሰጥተው በሚገባ አጠገቡዋቸው፤ ...ካህኑም ተቀብሎ አጠመቀው ከአጠመቀውም በኋላ ለነፍሱ ዋስ (ለክርስትና አባቱ) አሳልፎ ሰጠው ስሙንም ሀብተ ማርያም ብሎ ሰየመው። ከአባታችን ከአቡነ ሀብተ ማርያም እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ አቡነ ሀብተ ማርያም።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ኢየሱስ_ሞዐ፦ አገራቸው ጎንደር ክፍለ ሀገር ስማዳ ወረዳ ሲና ዳኅና በሚባል ቦታ ነሐሴ 26 ቀን ተፀንሰው ግንቦት 26 ቀን 1210 ዓ.ም ከአባታቸው ከቅዱስ ዘክርስቶስና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ክብራ ተወለዱ፡፡ የተወለዱትም በቅዱስ ነአኲቶ ለአብ ዘመነ መንግሥት ነው፡፡
❤ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት የቆብ አባት ሲሆኑ ታላቁን ሐይቅ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገዳም የቆረቆሩ ደገኛ አባት ናቸው፡፡ ዕድሜያቸው 30 ዓመት እስከሚደርስ ድረስ ከቤተሰቦቻቸው ትምህርተ ሃይማኖትንና ግብረ ገብን ሲማሩ ከቆዩ በኋላ በ1240 ዓ.ም ይህንን ዓለም በመተው ወደ ደብረ ዳሞ ገዳም ገቡ፡፡ በደብረ ዳሞ ገዳም መነኰሳቱን እየረዱ፣ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያጠኑ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን እየገለበጡ ለሰባት ዓመታት ከቆዩ በኋላ የደብረ ዳሞ 3ኛ አበ ምኔት ከሆኑት ከአባ ዮሐኒ እጅ ምንኲስናን በ1247 ዓ.ም ተቀበሉ፡፡
❤ አንድ ቀን ሌሊት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ወደርሳቸው መጥቶ "የስምህ መክበርያ ወደሆነው ሐይቅ ወደ ተባለው ሥፍራሂድ" አላቸው፡፡ አባታችንም "ቦታውን እንዴት ዐውቀዋለሁ?" በማለት መልአኩን ቢጠይቁት "ተነሥ! ጉዞህን ጀምር ቦታውን እኔ አሳይሃለሁ" አላቸው፡፡ አባ ኢየሱስ ሞዐ በመልአኩ እንደታዘዙት ከበዓታቸው ተነሥተው ተከተሉት፡፡ የብዙ ወራት መንገድ የሆነውን ጐዳናም በስድስት ሰዓት አደረሳቸው፡፡ በዚያን ወቅት ከሐይቅ ገዳም በስተ ሰሜን ወደነበረው የቅዱሳን ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ደረሱ፡፡ ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ ከመግባታቸው በፊት ለ 6 ወራት ያህል በቅዱሳን በጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን አገልግለዋል፡፡ ያገለግሉበት በነበረው ቤተ
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለቢጻርዮን_እምሐውዘ_ዓለም ዘተኅግሡ። እንዘ ኢያጠሪ ሎቱ መንጸፈ ወልብሰ። እምኀበ አምላክ አድምዐ ወተጸገወ ሞገሰ። በምድረ ምቅዋሙ ዘአስከቡ እስከ ድውየ ፈወሰ። እስከ ማየ ባሕር ኬደ ከመ ይከይድ የብሰ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የነሐሴ_25።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወይእዜኒ መኑ ተስፋየ አኮኑ እግዚአብሔር። ወትዕግሥትየኒ እምኀቤከ ውእቱ። ወእምኵሉ ኃጢአትየ አድኀንከኒ"። መዝ38፥7-8። የሚነበቡት መልዕክታት ኤፊ 6፥10-19፣ 1ኛ ጴጥ 3፥1-10 እና የሐዋ ሥራ 12፥12-20። የሚነበበው ወንጌል ማር 3፥7-13። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፭ (25) ቀን።
❤ እንኳን #ለአባ_እንጦንስ_ደቀ_መዝሙር_ለሆነ ታላላቅ ተአምራቶችን ላደረገ ለታላቁ አባት #ለአባ_ቢጻርዮን_ለዕረፍት_በዓል፣ #ለቅዱስ_እንድርያኖስና_ሃያ_አራቱ_ባልንጀሮቹ ሰማዕታት ለዕረፍታቸው በዓል በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከኤልያኖስ_ከእኅቱ_አውዶክስያ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_እንድርያኖስና_ሃያ_አራቱ_ባልንጀሮቹ ሰማዕታት፦ ይህም እንድርያኖስ ከመክስምያኖስ መኳንንቶች አንዱ ነበር እርሱም የጐልማሶች አለቃ ነበረ። ለጣዖት መስገድን እምቤ ስለአሉ ንጉሡ ምእምናንን ሲአሠቃያቸው ቅዱስ እንድርያኖስ የሰማዕታትን የልባቸውን ቆራጥነትና በመከራቸው ላይ መታገሣቸውን ተመልክቶ አደነቀ።
❤ እንዲህም አላቸው "ይህን ያህል ስትታገሡ ምን ታገኛላችሁ?" ቅዱሳን ሰማዕታትም "የሚጠብቀንን ተሰፋ ለመናገር አንደበታችን አይችልም" አሉት ስለ ዓለም ድኅነትም ክርስቶስ መከራ እንደ ተቀበለ ከብሉይና ከሐዲስ መጽሐፍ ነገሩት። እንድርያኖስም በሰማ ጊዜ ጽሕፈትን ወደ ሚያውቁ ብልሆች ሰዎች ሔደና "እኔ ከዛሬ ጀምሮ ክርስቲያን ነኝ ስሜን ከገድለኞቹ ጋራ ጻፉ" አላቸው።
❤ ለንጉሥ መክስምያኖስም እንዲህ እንዳለ በነገሩት ጊዜ ጠርቶ "እንድርያኖስ ሆይ አበድክን" አለው እንድርያኖስም "ከቀድሞው እብደቴ ተመለስኩ እንጂ እኔ አላበድኩም" ብሎ መለሰለት። ንጉሡም ሰምቶ ወደ ወህኒ ቤት ከንጹሐን ሰማዕታት ጋራ እንዲጨምሩት አዘዘ። ከአገልጋዮቹም አንዱ ሒዶ ለሚስቱ እንጣልያ ነገራት በሰማችም ጊዜ ደስ እያላት ወደ ወህኒ ቤት ሔደች ሃያ አራቱ ቅዱሳን ሰማዕታት የታሠሩበትን ማሠሪያቸውን ሳመች በሥቃዩ እንዲታገሥ የባሏን ልብ ያጽናኑ ዘንድ ለመነቻቸው። እርሱንም እንዲህ አለችው "ላህይህ ደምግባትህም ርስትህም ጥሪትህም አያስትህ ሁሉም ከንቱ ነውና ነገር ግን በእርሱ ዘንድ የማያልፍ መንግሥትን ትወርስ ዘንድ የክብር ንጉሥ ክርስቶስን ተከተለው" ይህንንም ብላ ወደቤቷ ገባች።
❤ ከዚህም በኃላ እንድርያኖስ ለፍርድ እንደ ሚአቀርቡት በአወቀ ጊዜ ሊሰናበታት ወደ ሚስቱ ሔደ መምጣቱንም ሰምታ የሸሸ መሰላት ደጇንም ዘግታ በውስጥ ሁና እንዲህ እያለች ዘለፈችው "ትላንት ሰማዕት ተብለኽ ዛሬ ክርስቶስን ካድከውን" እንድርያኖስም ሰምቶ የሃይማኖቷን ጽናት አደነቀ እንዲህም አላት "እኅቴ ሆይ እንድሰናበትሽ ክፈችልኝ" አላት። በሰማችም ጊዜ ከፈተችለት ከዚህም በኋላ ሁሉን እያነጋገራት እስከ እሥር ቤት ወሰዳት እንጣልያም ከዚያ በደረሰች ጊዜ የታሠሩትን ቅዱሳን ተሳለመቻቸው ቅስላቸውንም አጠበች።
❤ ከዚህም በኃላ ንጉሡ ቅዱሳኑን ከእሥር ቤት እንደአመጧቸው አዘዘ በመጡም ጊዜ ከሥቃይ ብዛት የተነሣ እንደደከሙ አያቸው። እንድርያኖስንም በፊቱ አቁሞ ለአማልክት ሠዋ አለው ቅዱሱም እርሱንና የረከሱ አማልክቶቹን ረገመ ንጉሡም የሆድ ዕቃው እስኪፈስስ ሆዱን እንዲደበድቡት አዘዘ በዚያን ጊዜም የእንድርያኖስ ዕድሜው ሃያ ስምንት ዓመት ነበር።
❤ ከዚህም በኃላ እንድርያኖስን ከባልንጀሮቹ ሰማዕታት ጋራ ወደ እሥር ቤት መለሱት እንጣልያም መጥታ የቅዱሳንን ደማቸውን ጠራረገችላቸው። እሊህ ቅዱሳንም እንድርያኖስን እንዲህ ብለው ተሳለሙት "እንድርያኖስ ሆይ ስምህ ተሳለሙት በሕይወት መጽሐፍ ተጽፎአልና ደስ ይበልህ"።
❤ ንጉሡም መስፍ አምጥተው የቅዱሳኑን ሁሉ ጭናቸውን በድጅኖ ይሰብሩ ዘንድ አዘዘ እንጣልያም የእንድርያኖስን እጆቹንና እግሮቹን በመስፍ ላይ ለማኖር ቀደመች ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ እስከ ሰጠ ድረስ የእንድርያኖስን ዐጥንቶቹን ወታደሮች ቀጠቀጡ የቅዱሳኑንም ሁሉ ጭናቸውን ሰብረው ወደ እሳት ወረወሯቸው እሳቱ ግን ከቶ አልነካቸውም። ምእመናንም መጥተው በጭልታ ወደ ሌላ ቦታ ወሰዱአቸው የመከራውም ወራት እስቲያልፍ ሠወሩአቸው። እንጣልያም የእንድርያኖስን የእጁን ቁራጭ ወስዳ በትርአሷ ውስጥ አኖረችው።
❤ ከዚህም በኋላ የሀገሩ ገዥ እንጣልያን ሊአገባት ወደደ በአወቀችም ጊዜ የባሏን የእጅ ቁራጭ ይዛ በመርከብ ሸሸች የቅዱሳኑ ሥጋ ወዳለበትም ደርሶ ወደ እነርሱ ይቀበሏት ዘንድ ለመነች ጌታችንም ልመናዋን ተቀብሎ አሳረፋት ከእነርሱም ጋራ ተቀበረች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ እንድርያኖስና በሃያ አራቱ ባልንጀሮቹ ሰማዕታት አማላጅነት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ቢጻርዮን፦ የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ምእመናን ነበሩ። በአደገም ጊዜ የምንኵስና ልብስን ለብሶ እግዚአብሔርን ሊአገለግል ወደደ ዓለምንም ንቆ ወደ አባ እንጦንስ ሔደ ለእርሱም ደቀ መዝሙር ሆኖ ብዙ ዘመናት አገለገለው።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ አባ መቃርስ ሒዶ ቅዱሳን አረጋውያን መነኰሳትንም አገለገላቸው። በአስቄጥስም ገዳም ይዘዋወር ነበር በቤት ውስጥም አያድርም ነበር። ምንጣፍና ልብስ እስኪአጣ ድረስ ምንም ምን ጥሪት አልነበረውም መነኰሳቱም የማቅ ጨርቅ ይሰጡት ነበር። ወገቡንም ታጥቆ በመነኰሳቱ መንደር ይዞር ነበር በቤቶቻቸውም ደጃፍ እያለቀሰ ይቀመጥ ነበር።
❤ የማያውቀውም ወደርሱ በደረሰ ጊዜ "አባቴ ሆይ ምን ያስለቅስሃል" ይለው ነበር። እርሱም "ንብረቴን ስለዘረፉኝ እንዳልሞት ሸሸሁ ከወገኔም ክብር ተለይቼ በጉስቁልና ወደቅሁ" ይለው ነበር። የቃሉንም ምልክት የማያውቅ የጠፋውን ገንዘብህን እግዚአብሔር ይመልስልህ ብሎ ካለው ይሰጠው ነበር። እርሱም ተቀብሎ ይሔድና ለሌለው ይሰጥ ነበር። የቃሉን ምልክት የሚያውቅ ግን በፈቃደ ነፍስ የሚሠሩ ትሩፋትን ሰይጣን ከሰዎች የማረካቸው መሆኑን ልብ ብሎ ያስተውል ነበር። አባቶችም ጭንቅ የነበረ ተጋድሎውን ስለርሱ ይናገሩ ነበር። እርሱ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ከቶ ሳይተኛ ቁሞ ኖሮአልና ።
❤ በምንኵስናውም ወራት ብዙ ጊዜ በየአርባ ቀን ጾመ እነሆ እንዲህ እየተጋደለ ድንቆችንም እያደረገ ኀምሳ ሰባት ዓመታት ኖረ። ቅዱሳን አባ ዱላስና አባ ዮሐንስም ከተአምራቱ ተናገሩ እነርሱ ከርሱ ጋር ወደ ኤርትራ ባሕር ዳርቻ ሔዱ። እጅግም በተጠሙ ጊዜ እንደተጠሙ አውቆ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ መራራውንም ውኃ ጣፋጭ አድርጎላቸው ጠጥተዋል።
✝ በሁለተኛም ጊዜ ወደ ፈሳሽ ውኃ ደርሶ መሸጋገሪያ አጣ ወደ ጌታችንም ጸለየ ያን ጊዜም እንደ የብስ በባሕሩ ላይ ሔደ። በአንዲት ቀንም የከበሩ አባቶች በጸሎታቸው ያድኑት ዘንድ ጋኔን ያደረበትን ሰው ወደ አስቄጥስ ገዳም ሰዎች አመጡ አባቶችም እርስ በርሳቸው እንዲህ ተባባሉ እርሱ ከከንቱ ውዳሴ ስለሚሸሽ ብንነግረው ይህን ጋኔን የያዘውን አያድነውም ።
❤ አባ ቢጻርዮን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለጸሎት ወደሚቆምበት ቦታ ያንን ጋኔን ያደረበትን ሰው አስተኙት። አባ ቢጻርዮንም በገባ ጊዜ ያን ጋኔን ያደረበትን ሰው ተኝቶ አገኘውና ቀሰቀሰው እጁንም ይዞ "ተነሥ" አለው ያን ጊዜም ድኖ ተነሣ አእምሮውም ተመለሰ። ያዩትም እጅግ አደነቁ ለሚፈሩት ስለሚሰጠው ጸጋውም እግዚአብሔርን አመሰገኑት።
❤ የዚህም ቅዱስ ተአምራቶቹ ከነገርናችሁ የበዙ ናቸው እግዚአብሔርንም አገልገሎ በሰላም አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ቢጻርዮን ጸሎት ይማረን። በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የነሐሴ 25 ስንክሳር።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ እንኳን #ለማዕከለ_ክረምት ለዕጒ(ጓ) #ለቋዓትና_ደስያት ለሚታሰብበት ሳምንት ዕለተ እሑድ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዚህ_ሳምንት_መዝሙ፦ ሃሌ ሉያ በ፫ "#ይሁበነ_ዝናመ በጊዜሁ ይሁበነ ዝናመ በጊዜሁ ወይሁበነ እክለ በረከት፤ አዝ፣ ያርኁ ክረምተ ይገብር ምሕረተ ወይሁበነ ዝናመ በረከት፤ አዝ፣ ከሢቶ ዐይኖ ሰፊሖ የማኖ ይፌኑ ሣህሎ ወበዘአእመረ ይሴባሕ፤ አዝ፣ #ወሠርዐ_ሰንበት_ለሰብእ_ዕረፍተ ወብውህ ሎቱ ይኅድግ ኀጢአተ፤ አዝ፣ #ዐይነ_ኵሉ_ነፍስ_ይሴፎ_ኪያሁ #ይሁቦሙ_ሲሳዮሙ_በጊዜሁ"። ትርጉም፦ #ዝናመ_ምሕረቱን_በጊዜው_ይሰጠናል፤ እክለ በረከቱንም በጊዜው ያድለናል፤ አንቀጸ ክረምትን ይከፍታል (ያመጣል) ምሕረትንም ያደርጋል፤ የበረከት ዝናምንም ይሰጠናል፤ የፍቅር ዓይኖቹ ከፍቶ የምሕረቱን ቀኝ እጁን ዘርግቶ ቸርነቱን ይቅርታውን ይልካል፤ እርሱ ባወቀ ይመሰገናል፤ ለሰው ልጅ ዕረፍት እንዲሆን #ሰንበትን_ሠራ_ኃጢአትን_ይቅር ይል ዘንድ #የሁሉም_ዓይን_አንተን_ተስፋ_ያደርጋል፤ እርሱም #በጊዜው_ምግባቸውን_ይሰጣቸዋል። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በድጓው_ላይ።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ዕጕ(ጓ)ለ ቋዓት፦ ይህ ክፍለ ክረምት ከነሐሴ 10 እስከ ነሐሴ 27 ቀን ድረስ ያሉት ዕለታት የሚጠሩበት ነው። በዚህ ክፍል ክረምት ፍጥረታትና በባሕር የተከበቡ ደሴቶች የሚታወሱበት ሲሆን ወቅቱም ዕጕ(ጓ)ለ ቋዓት ይባላል። ዕጕ(ጓ)ለ ቋዓት የሚለው ቃል ቁራን ሲያመለክት፤ ቁራ ሲወለድ ያለ ፀጉር (ያለላባ) በሥጋ ብቻ ይወለዳል። እናትና አባቱም እነርሱን ባለመምሰሉ ደግንጠው ይሸሻሉ፤ በዚህ ጊዜ የሚንከባከበው ያጣል፤ ምግብ በሚያስፈልገው ሰዓት አፉን ከፈት ያደርጋል፤ እግዚአብሔር በረድኤት ተሕዋስያንን ብር ትር እያደረገ ከአፉ ያስገባለታል ይመግባል።
❤ አባታች ኢዮብ "ልጆቹ ወደ እግዚአብሔር ሲጮኹ የሚበሉትም አጥተው ሲቅበዘበዙ ለቁራ መብልን የሚሰጠው ማን ነው?" ኢዮ 38፥41 ብሎ እንደ ገለጠው ያ ዕጕ(ጓ)ለ ቋዓት እግዚአብሔር የሰጠውን እየተመገበ ቆይቶ ሲጠነክር እንደ እናቱና እንደ አባቱ ፀጉር ያወጣል። በዚህ ጊዜ እናትና አባቱ ቀርበው ይንከባከቡታል።
❤ በሥነ ፍጥረት አቆጣጠር በክንፍ የሚበሩ የሰማይ አዕዋፍን ሁሉ ይወክላል። ይህን አምላካችን እግዚአብሔር ለፍጥረት ሁሉ የሚያስብ በመሆኑ ርኅርኄ ለተመላው አምላክነቱና ከሃሊነቱ መታሰቢያ እንዲሆን ይህን ወቅት ቤተ ክርስቲያን "ዕጒ(ጓ)ለ ቋዓት" በማለት ታስታውሰዋለች።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ደስያት፦ ማለት በውኃ የተከበቡ ቦታዎች ማለት ነው። እነዚህን ቦታዎች በውኃ እንዲሸፈኑ አድርጎ በውስጣቸው ያሉትን ሰዎች፣ እንስሳት፣ አራዊትና አዕዋፍ ሁሉ የሚጠብቃቸው፤ በወርኃ ክረምት የወንዞች ሙላት የአብሕርትና የውቅያኖስ መነዋወጥ አይሎ እንዲያጠፋቸው ሁሉም ከልኩ እንዳያልፍ በማድረግ በደስያት ውስጥ የሚኖሩትን ፍጥረታት በተስፋና በእምነት አበርትቶ የሚያኖራቸው እግዚአብሔር ነው። ይህን ድንቅ ሥራ ያዩ ሰዎች እግዚአብሔርን ያመሰግናሉ፤ ከሃሊነቱን ያደንቃሉ።
❤ እንደዚሁ በደሴት (በቤተ ክርስቲያን) የተጠጉ ሁሉ ከሞተ ሥጋና ከሞተ ነፍስ ይጠበቃሉ። በዚህ ወቅት ክፍለ ክረምቱ እንደተገባደደ ውኃው እየጠራ፣ መሬቱ እየረጋ፣ ደመናውና ጉሙ እየቀለለ፣ የወንዙ ሙላት እየጎደለ፣ የክረምት ምግባቸውን ይዘው በየዋሻው የከረሙ ጭልፊቶችና አሞራዎች ድምፃቸውን እያሰሙ ምግብ ፍለጋ ሲወጡ የሚታዩበት ወቅት ነው። ምንጭ፦ ኆኅተ ስብከት ዘቅዱስ ያሬድ ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዚህ_ሳምንት_የዕለቱ_ምስባክ፦ "ዐይነ ኵሉ ነፍስ ይሴፎ ኪያከ። እንተ ትሁቦሙ ሲሳዮሙ በጊዜሁ። ትሰፍሕ የማነከ ወታጸግብ ለኵሉ እንስሳ ዘበሥርዓትከ"። መዝ 144፥15-16። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 3፥1-ፍ.ም፣ ያዕ 5፥1-12፣ የሐዋ.ሥራ 22፥1-22። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 6፥41-ፍ.ም። የሚቀደሰው የቅዱስ ኤጲፋንዮስ ቅዳሴ ቅዳሴ ነው። መልካም ዕለተ ሰንበት ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ በዚህም በኋላ መጠጊያ ሠርቶ በፊቱ በኋላው በቀኙ በግራው የተሳሉ ፍላጻዎችን ተከለ ይህንም ማድረጉ በመደገፍና በመተኛት እንዳያርፍ ነው በዚያም እግሩ ከቅልጥሙ እስቲሰበር ሰባት ዓመት ቆመ። በዚያም ወራት ምንም የዕንጨት ፍሬ ወይም ቅጠል ሳይቀምስ ውኃም ሳይጠጣ ኖረ።
❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርቶስ ወደርሱ መጣ ከእርሱም ጋራ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ደግሞ የከበሩ ነቢያትና ሐዋርያት ሁሉም ሰማዕታትና ጻድቃን የጳጳሳት አለቆች የመላእክት አለቆችም ከሠራዊቶቻቸው ጋራ አሉ።
❤ መድኃኒታችንም እንዲህ አለው "ወዳጄ ሆይ አንተ በመከራዬ መሰልከኝ እኔም በመንግሥቴ ከእኔ ጋራ እንድትመስለኝ አደርግሃለሁ። እነሆ የዚህ ዓለም ድካምህ ተፈጸመልህ በእኔ ዘንድም የምቀበለው ሆነ ከእንግዲህስ መንግሥተ ሰማያትን ትወርስ ዘንድ ና። እነሆ ስምህን ለሚጠራ መታሰቢያህን ለሚያደርግ ገድልህን ለሚጽፍ ለሚያነበውና ለሚሰማውም ቤተ ክርስቲያንህን ለሚሠራ በስምህ መባ ለሚሠጥ ለድኆችም በስምህ ለሚመጸውት በመታሰቢያህም ቀን ለሚቆርብ ስለ አንተ በጎ ሥራ ለሚሠራ ሁሉ እኔ እስከ ዐሥር ትውልድ እምርልሃለሁ"። አባታችንም እጅግ ደስ አለው ለጌታችንም ሰገደ ጌታችንም ከእርሱ ዘንድ በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ።
❤ ከዚህም በኋላ አባታችን በንዳድ በሽታ ታመመ ዕድሜውም ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከስምንት ወር ከአንድ ቀን ሆኖት በለመለመ ዕርጅና ነሐሴ 24 ቀን ዐረፈ። በመዘመርና በማመስገን አክብረው ገንዘው በዋሻው ውስጥ ቀበሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባታችን ተክለ ሃይማኖት ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ቶማስ_ዘመርዓስ፦ የዚህንም አባት ትሩፋቱንና ገድሉን ሰው ተናግሮ ሊፈጽመው አይችልም እርሱ አስቀድሞ በጾም በጸሎት በሰጊድ ቀንና ሌሊትም በመራራት ተጠምዶ የሚኖር ነው ። ከዚህም በኃላ መርዓስ ለሚባል አገር ኤጲስቆጶስ ይሆን ዘንድ የክብር ባለቤት ጌታችን መረጠው መንጋውንም እንደ ሐዋርያት ጠበቀ ። ከሀዲ ዲዮቅልጥያኖስም በነገሠ ጊዜ ክርስቲያኖችን ያሠቃያቸው ዘንድ ከመኳንቶቹ አንዱ ወደዚያች አገር ደረሰ እርሱም ቅዱስ ቶማስን ወደርሱ ያቀርቡት ዘንድ ጭፍሪቹን ላከ እነርሱም እየደበደቡ በምድር ላይ እየጎተቱ ወሰዱት ደሙም እንደውኃ ፈሰሰ።
❤ ከዚህም በኃላ መኰንኑ ቅዱስ ቶማስን "ለአማልክት ስገድ" አለው ቅዱሱም እንዲህ ብሎ መለሰለት "እኔ ከሕያው እግዚአብሔር ልጅ ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ለረከሱ ጣዖታት የሚሰግድ ሁሉ የተረገመ ነውና"። መኰንኑም ተቆጥቶ እጅግ የበዛና ዕፁብ ድንቅ የሆነ ሥቃይን አሠቃየው የነዳጅ ድፍድፍና አፍልተው በላዩ በአፉና በአፍንጫው ውስጥ ጨመሩ እንዲህም እያደረጉበት እስከ ብዙ ዘመናት ኖረ።
❤ የእሊህ ከሀዲያን ልባቸው እንደ ድንጊያ የጸና ስለሆነ ቅዱስ ቶማስ ቶሎ እንዲሞት አልፈለጉም። ሌሎች ብዙዎች ሰዎችን ያሰፈሩአቸው ዘንድ የክብር ባለቤት ክርስቶስንም ይክዱት ዘንድ የሥቃዩን ዘመን አስረዘሙ እንጂ። እርሱ የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል የጸና ነውና ማሠቃየቱን ከሀድያን በተቸነፉ ጊዜ ስለ ስሕተታቸውም ይዘልፋቸው ስለነበር ስለዚህ በጨለማ ቦታ ጣሉት በዚያም ሃያ ሁለት ዓመት ኖረ።
❤ ከሀድያንም በየዓመቱ ወደርሱ ገብተው ከሕዋሳቱ አንዱን ይቆርጣሉ። በዚያም ቦታ አፍንጫውን ከንፈሮቹን ጆሮዎቹን እጆቹንና እግሮቹን ቆረጡ መንጋዎቹም ያረፈ መስሏቸው በየዓመቱ መታሰቢያውን ሲያደርጉ ኖሩ። ነገር ግን አንዲት ክርስቲያናዊት ሴት በጣሉት ጊዜ ስለአየችው ቦታውን ታውቅ ነበር እርሷ በሌሊት ወደርሱ ተሠውራ በመሔድ ትመግበዋለች ። ጻድቅ ቁስጠንጢኖስም እስከ ነገሠና የቀናች የክርስቶስን ሃይማኖት ክብር እስከ ገለጠ ድረስ እንዲህ ሲሠቃይ ኖረ። ይህም ንጉሥ ክርስቶስን በመታመን የታሠሩ እሥረኞችን ሁሉ በሀገሮች ሁሉ በወህኒ ቤት ያሉትን ይፈቷቸው ዘንድ አዘዘ።
❤ ይችም ሴት ሒዳ ስለ ቅዱስ ቶማስ ከእርሱ የሆነውን ሃያ ሁለት ዓመት ተጥሎ እንደኖረ ለካህናቱ ነገረቻቸው በውስጡ ወደሚኖርበትም ቦታ መራቻቸው። እነርሱም አንሥተው ተሸከሙት እየዘመሩና እያመሰገኑ ወደ ቤተ ክርስቲያን አደረሱት በቤተ መቅደሱም ፊት ለፊት በወንበሩ ላይ አስቀመጡት ምእመናንም ሁሉ ወደርሱ እየመጡ ከእርሱ ይባረኩና የተቆረጡ ሕዋሳቱን ይሳለሙ ነበር።
❤ ንጉሥ ቂስጠንጢኖስም የከበሩ የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ኤጲስቆጶሳትን የአንድነት ጉባኤን በኒቅያ አገር በሰበሰበ ጊዜ ይህ የከበረ ቶማስ ከእሳቸው አንዱ ነው። ንጉሡም ወደ እነርሱ ገብቶ ሰላምታ ሰጣቸውና ከእርሳቸውም ቡራኬ ተቀበለ። የዚህ የቅዱስ ቶማስን ተጋድሎውን በነገሩት ጊዜ ወደርሱ ቀርቦ ሰገደለት ሕዋሰቱም ከተቆረጡበት ላይ ተሳለመው አዝኖና እጅግም አድንቆ ሕዋሳቱን ዳሠሠው ፊቱንና ዐይኖቹን አሻሸው።
❤ ከሀዲ አርዮስንም ተከራክረው ከረቱ በኃላ አውግዘው ለይተው ከወገኖቹ ጋር ከቤተ ክርስቲያን አሳደዱት። ከዚህም በኃላ መንፈስ ቅዱስ እንደ አስተማራቸውና እንደመራቸው የሃይማኖትን ትምህርት በአንደበታቸው ተናገሩ ሕግና ሥርዓትን ሥጋዊና መንፈሳዊ ፍርድንም ሠሩ።
❤ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ቶማስ ወደ መንበረ ሢመቱ ሔደ ካህናቱንና መንጋዎቹን ሁሉ ሰብስቦ አነበበላቸው እርሱንም እንዲአስተውሉት እንዲጠብቁትም በመጠበቅም እንዲጸኑ አዘዛቸው። ጥቂት ዘመናትም ከኖረ በኃላ በሰላም በፍቅር ነሐሴ 24 ቀን ዐረፈ የሹመቱም ዘመን አርባ ዓመት ነው በዚህም እግዚአብሔርን አገለገለው። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በተጋዳይ በአቡነ ቶማስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የነሐሴ 24 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለቶማስ_ዘአባላቲሁ_ግሙድ። እስከ አስተርአየ ኅብሩ በአምሳለ ውዑይ ጉንድ። እስከ አንከረ ንጉሥ በነጽሮ ገድለ ፍድፋድ። ወሰላም ለዘምስሌሁ ሙቁሐነ ዕድ። አእላፈ ክርስቶስ ፱ቱ በፍቅድ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የነሐሴ_24።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኃይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ83፥6-7። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 10፥1-22።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባኩ፦ "እስመ በእንቲአሁ ይቀትሉነ ኵሎ አሚረ። ወኮነ ከመ አባግዕ ዘይጠብሑ። ንቃህ እግዚኦ ለምንት ትነውም"። መዝ 43፥22። የሚነበቡ መልዕክታት ሮሜ 8፥35-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 5፥1-6 እና የሐዋ ሥራ 20፥28-31። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 10፥16-42። የሚቀደሰው ቅዳሴ የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የአባታች ተክለ ሃይማኖትና የእናታችን የቅድስት ክርስቶስ ሠምራ የዕረፍታቸው በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፬ (24) ቀን።
❤ እንኳን #የኢትዮጽያ_ብርሃን_ለተባሉት ለታላቁ አባት ለከበረ ሐዲስ ሐዋርያ ለትሩፋትም መምህር ለሆነ #ለአቡነ_ተክለ_ሃይማኖት_በዓለ_ለዕረፍትና ለታላቁ አባት ለክርስቶስ ምስክር ለሐዋርያው ለመርዓስ አገር ኤጲስ ቆጶስ ለተጋዳይ #ለቅዱስ_አባት_ቶማስ በዓለ ለዐረፍት በዓል በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከአብርሃም_ከይስሐቅና_ከያዕቆብ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሐዲስ_ሐዋርያ_አቡነ_ተክለ_ሃይማኖት፦ የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም ጸጋ ዘአብ የእናቱ ስም እግዚእ ኀረያ ነው እሊህም ቅዱሳን ለኢትዮጵያ የሃይማኖት ብርሃንን ላበሩ ካህናት ከወገኖቻቸው የሆኑ ናቸው። እግዚእ ኀረያም መካን ስለሆነች ልጅን ይሰጣቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር እያዘኑ ሲጸልዩ ኖሩ። በዚህም ነገር እያሉ የዳሞት ገዥ ሞተለሚን ሰይጣን አነሣሣው የሸዋን አውራጃዎች እስከ ጅማ እስከ ገዛ ድረስ። የሀገር መኳንንቶችም በየተራቸው ሚስቶቻቸውን ይሰጡታል። ከማረከውም ደምግባት ያላቸውን ሴቶች ያገኘ እንደሆነ ቁባቶች ያደርጋቸዋል።
❤ በዚያም ወራት ወደ ጽላልሽ ደርሶ ብዙ ክርስቲያኖችን ገደለ ከእርሳቸውም የሚበዙትን ማረከ ጸጋ ዘአብም ከግድያ ፍርሃት የተነሳ ሸሸ አንድ ወታደርም ተከተለው እርሱም ወደ ባሕር ተወርውሮ ገባ በእግዚአብሔርም ፈቃድ በባሕሩ ውስጥ ተሸሸገ። ሚስቱን እግዚእ ኀረያንም ወታደሮቹ ማረኳት ወደ ሞተለሚም አደረሷት ባያትም ጊዜ ውበቷንና ላህይዋን አደነቀ በልቡም እጅግ ደስ ብሎት ብዙ ሽልማትን ጌጥን ሰጥቷት በሽልማትና በጌጥ ሁሉ ሸለማት አስጌጣትም የጋብቻ ሥርዓትንም ማዘጋጀት ጀመረ ለሠርጉም እንዲሰበሰቡ ወደመኳንንቶቹ ሁሉ ላከ።
❤ እግዚእ ኀረያም ይህን በሰማች ጊዜ ከአረማዊ ጋር አንድ ከመሆን ያድናት ዘንድ በብዙ ልቅሶ ወደ እግዚአብሔር ጸሎትን አደረገች። ያን ጊዜም የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል በብርሃናዊ ክንፉ ተሸክሞ ከዳሞት አገር ወደ ምድረ ዞራሬ አድርሶ ወዲያውኑ ወደ ቤተ መቅደስ አስገብቶ በሴቶች መቆሚያ አቆማት። ባሏ ጸጋ ዘአብም ከማዕጠንት ጋራ በወጣ ጊዜ እንደተሸለመች ቁማ አያት አድንቆ በልቡ "ይቺ ሴት ምንድን ናት ወደዚህስ ማን አመጣት" አለ። የማዕጠንቱንም ሥራ ጨርሶ ወጣ በጠየቃትና በመረመራት ጊዜ እርሷ ሚስቱ እግዚእ ኀረያ እንደሆነች አገኛት እርሷም ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው እግዚአብሔር ያደረገላትን ነገረችው።
❤ ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ በአንዲት ሌሊት ተገለጠላቸው የዜናው መሰማት በዓለሙ ሁሉ የሚደርስ የተባረከ ልጅ ይወልዱ ዘንድ እንዳላቸው ነገራቸው አበሠራቸው። ከጥቂት ቀኖችም በኋላ ይህ ቅዱሱ ተፀንሶ በታኀሣሦ ወር በሃያ አራት ተወለደ በጸጋ ዘአብና በእግዚእ ኀረያ ቤታቸው ታላቅ ደስታ ሆነ ከዘመዶቻቸውና ከጐረቤቶቻቸው ጋራ ደስ አላቸው።
ለክርስትና ጥምቀትም በአስገቡት ጊዜ ፍሥሓ ጽዮን ብለው ሰየሙት። ሕፃኑም አደገ ድንቅ ተአምራትንም እያደረገ ዕውቀትንና ኃይልንም ተመልቶ በመንፈስ ቅዱስ ጸና።
❤ ከዚህም በኋላ ዲቁና ይሾመው ዘንድ አባ ጌርሎስ ወደ ተባለ ጳጳስ ወሰዱት በዚያንም ዘመን በዛጔ መንግሥት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ ብንያሚን ነበር። ወደ ጳጳሱም በአደረሱት ጊዜ "ይህ ልጅ የተመረጠ ዕቃ ይሆናል" ብሎ ትንቢት ተናገረለት። የዲቁና ሹመትንም ተቀብሎ ወደ ሀገሩ ተመለሰ።
❤ ጐልማሳ በሆነ ጊዜ አራዊትን ሊያድን ወደ ዱር ሔደ። ቀትር ሲሆንም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መልኩ የሚያምር ጐልማሳ አምሳል በቅዱስ ሚካኤል ክነፍ ላይ ተገለጠለትና እንዲህ አለው "ወዳጄ አትፍራ እንግዲህ የኃጢአተኞችን ነፍስ ወደ ሕይወት የምታጠምድ ትሆናለህ እንጂ አራዊትን የምታድን አትሆንም ስምህም ተክለ ሃይማኖት ይሁን እንደ ኤርምያስና እንደ አጥማቂው ዮሐንስ እኔ ከእናትህ ማኀፀን መርጬ አከብሬሃለሁና እነሆ በሽተኞችን ትፈውስ ዘንድ ሙታንንም ታሥነሣ ዘንድ ሥልጣንን ሰጠሁህ ርኩሳን አጋንንትንም ከሁሉ ቦታ ታሳድዳቸዋለህ"። ወደ ቤቱም በተመለሰ ጊዜ ገንዘብን ሁሉ ለድኆችና ለምስኪኖች በተነ "ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱንም ቢያጠፋ ለሰው ምን ይጠቅመዋል" እያለ ቤቱን እንደ ተከፈተ ትቶ ምርኩዙን ይዞ በሌሊት ወጣ።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ ጳጳስ ሔዶ የቅስና ሹመት ተቀብሎ ለሸዋ አገር ሁሉ ወንጌልን መስበክ ጀመረ። ዐሥራ ሁለት ሽህ ሦስት መቶ ነፍስ ያህል አጠመቀ ለጣፆት የሚሠውበትን ሁሉ ሻረ በውስጡ የሚኖሩ አጋንንት እስከሸሹ ድረስ ዐፀዶቻቸውን ሁሉ ቆረጠ።
❤ ሁለተኛም ወደ ዳሞት ምድር ሔዶ ብዙ ሟርተኞችንና አስማተኞችን ጠንቋዮችን አሳመነ ከሀዲ ሞተለሚም ብዙ ወራት ተቃወመው በጉማሬ ማጥመጃ ውስጥ በመጨመር ብዙ ጊዜ ወደ ገደል ወረወረው እርሱ ግን በደኀና ይመለሳል ደግሞ ሊወጋው ጦር ወረወረ ጦሩም ተመልሶ እጁን ወግቶ ተጠመጠመበት በተሠቃየም ጊዜ አባታችንን ለመነው እርሱም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አሳምኖ አዳነው የተጠመጠመበትንም ጦር ፈታለት ቀናውን መንገድ የሚያጣምሙ ሟርተኞችንም አጠፋቸው።
❤ ከዚህም በኋላ በክብር ባለቤት ጌታችን ስም ያደረገውን ድንቅ ተአምራቱን አይተው የአገር ሰዎች ሁሉም ከንጉሣቸው ጋራ አመኑ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው ቤተ ክርስቲያንም ሠርቶላቸው የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት አስተማራቸው በቀናች ሃይማኖትም አጸናቸው ከዚህም ሁሉ ጋራ በጾም በጸሎት በስግደት ሁልጊዜ ያለ ማቋረጥ ተጠምዶ ይጋደል ነበር። ዜናውንም ሰምተው ወደርሱ የሚመጡትን የነፍሳቸውን ድኀነት ያስተምራቸዋል የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችን ኢየሱስን በማመን ያጸናቸዋል።
❤ ከዚህ በኋላ በኤልያስ ሠረገላ ተቀምጦ ወደ አምሐራ ሀገር ሔደ በገድል ተጸምዶ ወደሚኖር መነኰስ ወደ አባ በጸሎተ ሚካኤል በአንዲት ቀን ደርሶ በዚያ እንደባሪያ ሲያገለግል ኖረ በአንድነት የሚኖሩ መነኰሳትንም ያገለግላቸው ነበር የሞተውንም እስከማንሳት ድረስ ከደዌያቸው ይፈውሳቸው ነበር።
❤ በዚያም ዐሥራ ሁለት ዓመት ከሆነው በኋላ ሐይቅ በሚባል ቦታ ወደሚኖር ወደ ኢየሱስ ሞዓ የእግዚአብሔር መልአክ እንዳዘዘው ሔዶ ከእርሱም የምንኲስና ልብስ ቀሚስና ቅናትን ተቀበለ። ከዚያም ወደ ደብረ ዳሞ ሔዶ ለአቡነ አረጋዊ አራተኛ ከሆነ ከአባ ዮሐኒ ዘንድ ቆብንና አስኬማን ተቀበለ። ሁለተኛም ወደ ኢየሩሳሌም ሒዶ ከከበሩ ቦታዎችና ከሊቀ ጳጳሳቱ ቡራኬን ተቀበለ።
❤ በዚያም ወደ ሸዋ ምድር ተመልሶ የአባቱ ወንድም ልጅ የሆነ አባ ዜና ማርቆስን አገኘው በወግዳ በረሀም በአንድነት ኖሩ ከዚያም ግራርያ ወደ ሚባል አገር ሒዶ በኰረብታ መካከል ዋሻ አዘጋጅቶ ተቀመጠ በቀንም በሌሊትም ከዚያ አይወጣም ነበረ ከጥቂት ቅጠልም በቀር እህልን አይቀምስም መጠጡም ጥቂት ውኃ ነው። ብዙ ወንዶችና ሴቶች ወደርሱ መጥተው መነኲሳቶች ሆኑ በአንድ ቤት ውስጥ በአንድ መኝታ ላይ ተኝተው ያድራሉ እርስበርሳቸውም አይተዋወቁም እነርሱም እንደ ሕፃናት ናቸው በጸሎትና በቅዳሴ ጊዜም በአንድነት ይቆማሉ በዘመኑ ሰይጣን ስለ ታሠረ ወንዱ ሴቷን ሴት እነደሆነች አያውቅም እንዲሁም ሴቷ ወንዱን ወንድ እንደሆነ አታውቅም።
❤ ከዚህ በኋላ ጌታ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራን እናቴ ማርያምን ወደ ምትኖርበት ውሰዳት" አለው። ቅዱስ ሚካኤልም "ጌታ ወደ አዘዘልሽ ቦታ እንሒድ" አላት። ቅዱስ ሚካኤልም ይዟት ሲሔድ እጅግ የሚያስደነግጥና ከፀሐይ ከጨረቃ ከዋክብት ብሃርን ይልቅ ብርሃኑ የሚያበራ መንበር አየች። ይህን መንበር በአየችውም ጊዜ በጣም አድርጋ ወደደችው።
❤ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም "ክርስቶስ ሠምራ ምን ትመለከቻለሽ" አላት። "ያን ቡሩህ የሆነ መንበር እመለከታለሁ" አለችው። "ይህ መንበር ለአንቺ ቢሆን ትወጃለሽን" አላት። "አዎን ጌታዬ ለእኔ ቢሆን እወዳለሁ" አለችው። "እንግዲያውስ ለአንቺ የተዘጋጀ ነው" አላት። በዚያ ጊዜ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል "ጌታዬ መኖርያሽ እናቴ ከማርያም ጋር ነው ብሎኝ አልነበረምን"። ታዲያ እንዴት ይህ መንበር ለአንቺ የተዘጋጀ ነው ትለኛለህ" አለችው። መላአኩም "ክርስቶስ ሠምራ ሆይ ለምን ቸኮልሽ" አላት። ይህን ካአለ በኋላ ወደ እመቤታችን ወደ ድንግል ማርያም መኖርያ ወስዶ አደረሳትና። "ክርስቶስ ሠምራ ሆይ እግዲህ ተመልከች" አላት። በተመለከተቻት ወይም ባየቻት ጊዜም ማርያም ወይም ሰው አልነበረችም ነገር ግን ከፍታዋ ወይም ቁመቷ የላቀ ተራራ ነበረች እንጂ።
❤ ቅዱስ ሚካኤልም "ማርያም ነች ብኸኝ አልበረምን ታዲያ እንዴት ተራራ ልትሆን ቻለች" አለችው። ያን ጊዜ ምሥጢሯ እስኪገለጽልሽ ድረስ ትንሽ ታገሽ" አላት። ከዚያም ቀና ብላ ብትመለከት እመቤታችን ድንግል ማርያምን አየቻትና እንደአሞራ በራ አንገቷን አቅፋ ሳመቻት። እመቤታችንም "ክርስቶስ ሠምራ ሆይ አንቺ የተባረክሽ ነሽ አንቺንም የሚያፈቅር የገድልሽን ዜና የሚሰሙ ሁሉ የተባርኩ የተመሰገኑ ናቸው" በማለት ሳመቻት። ይህንም ከአለቻት በኋላ በቀኟ አስቀመጠቻት...።
❤ ከዚህ ሁሉ ነገር በኋላ አባ ይስሐቅ የሚባል መነኵሴ ከእናታችን ከክርስቶስ ሠምራ ዘንድ ቢሄድ ሥጋዋ ብቻ ወይም አስከሬኗ በጉድጎድ ውስጥ እንደተተከለ ምሰሶ ወይም ዓምድ ቆሞ አገኘው። ነፍስዋ ከሥጋዋ ያልተለየች ወይም በሕይወት ያለች መስሎት ነበርና "እናታችን ክርስቶስ ሠምራ ሆይ ባርኪኝ" አላት። የሚመልስለት ቢያጣ ወደ ወደርስዋ ቀረበና ሥጋዋን ዳሰሰው። እንደ ዐረፈችም በአወቀ ጊዜ ፈጽሞ ደነገጠ ከመሬት ላይ እየወደቀ እየተነሣ መራራ ልቅሶ አለቀሰ።
❤ መነኰሳቱን ሁሉ ያለቅሱላት ዘንድ ጠራቸው። መነኰሳቱም እየተሽቀዳደሙና እየተሯሯጡ መጥተው አርፋ አገኙአት። በዚህ ጊዜ "አንቺን የተሸከመች ማኅፀን የተባለገች ነች አንቺንም ያጠቡ ጡቶች የተመሰገኑ ናቸው" እያሉ ጽዕኑና መራራ ልቅሶን አለቀሱ።
✝ ከዚህ በኋላ አባ ይስሐቅ ሥጋዋን ወይም አስከሬኗን በንጹሕ በፍታ ገንዞ በሳጥን አድርጎ በቤተ መቅደሱ ውስጥ ቀበራት። መነኰስ ይስሐቅም ወደ በዓቱ መመለሱ ቀርቶ በዚያው ቤተ ክርስቲያኖ በስተ ምሥራቅ በኩል በቁመቱ ልክ ጎድጎድ አስቆፍሮ በውስጧ ገባ።
❤ ከዚያም ከጎድጎዱ ውስጥ ገብቶ "ከእንግዲህ እስክሞት ድረስ እንደ እናቴ ክርስቶስ ሠምራ ከዚህ ጎድጎድ አልወጣም" በማለት ወሰነ። ይህንንም ካአለ በኋላ መሪር እንባ እያለቀሰ እህል ሳይቀምስ እስከ 40 ቀን ተቀመጠ። ከ 40 ቀን በኋላ ነፍሱ ከሥጋው ተለየችና በእናታችን በክርስቶስ ሠምራ አማላጅነትና ልመና ፍጹም መንግሥተ ሰማያትን ወረሰ።
❤ እናታችን ክርስቶስ ሠምራ በዚህ ዓለም በሕይወተ ሥጋ የኖረችው ሦስት መቶ ሰባ አምስት (375) ነው። ከእናታችን ከቅድስት ክርስቶስ ሠምራ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎቷም ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ጊዮርጊስ_ዘግሽ፦ ሀገራቸው ጎጃም ግሽ ዓባይ ሲሆን የታላቁ ጻድቅ አባት የአቡነ ዘርዐ ቡሩክ የአክስት ልጅ ናቸው። የተፀነሱትም ሆነ የተወለዱት በመልአክ ብሥራት ነው፡፡ ሰማዕትነት ለመቀበል ወደ ፋርስ በመሄድ ለ9 ሺህ ሰማዕታት መሪ ሆነው ጣዖትን ካጠፋ በኋላ በሰይፍ ተሰይፈው ሰማዕት የሆኑ ታላቅ አባት ናቸው። እመቤታችን ለዐፄ ካሌብ ተገልጻ የጻድቁን ዐፅም ወደ ሀገራችን እንዲመጣው ስላዘዘችው ዐፄ ካሌብም ዐፅማቸውን አስመጥቶ በጣና ቂርቆስ አስቀምጦታል። ከአባታችን አቡነ ጊዮርጊስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸም ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳንና ቅዱሳን በዓላት።
ፈጣሪሽን ስለተከተልሽው ነው" አላት። ይህንንም በአላት ጊዜ እጅግ አድርጋ ተደሰተች ሁሉን ማድረግ የሚችል እግዚአብሔርንም ፈጽማ አመሰገነች።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ስለ_እናታችን_ቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ ዕረፍት፦ ከዚህ በኋላ በአዲስ ተጋድሎ ጀመረች። ደናግሉን ልጆቿን ሰበሰበችና "ከእግዲህ እርስ በራሳችሁ በመፈቃቀር ኖሩ እግዚአብሔርም በመፍራት ተቀመጡ" አለቻቸው። ይህንንም ከአለች በኋላ በ1079 ደናግል ወይም መነኰሳት አስተዳዳሪ እመ ምኔት ሾመችላቸው። "ከወሰንኩላችሁ ሕግ ወይም ከሰራሁላች ሥርዓት አትተላለፉ ከእግዲህ ከዛሬ በስተቀር በመንፈስ እንጂ በሥጋ አንገናኝም እና" አለቻቸው። ይህንንም ተናግራ ከእነርሱ ስትለይ አንዲት መነኵሲት ወይም መበለት ጠርታ ሹል የሆኑ ብረቶች አምጭልኝ" ብላ አዘዘቻትና አመጣችላት።
❤ ከዚያም በእናታችን ክርስቶስ ሠምራ በቁመቷ ልክ ጎድጎድ አስቆፈረችና በውስጡ ዕፀ ከርካዕ ወይም የሎሚ እንጨት አስተከለችበት። ዳግመኛ "ከእግዲህ እግዚአብሔር ይቅር እስከ አለኝ ድረስ ከዚህ አልወጣም" ብላ ከጎድጎዱ ውስጥ ገባች። ሦስት የተሳሉ ጦርች በፊቷ ሦስት ጦር በኋላዋ፣ ሦስት ጦር በቀኝ ጎና፣ ሦስት ጦር በግራዋ ጎን ተከለች። መበለቲቱም የፊጢኝ ወይም የኋሊት በገመድ አሰረቻት። ከዚህም በኋላ ስለ ዓለሙ ሁሉ ሕዝብ ይልቁንም ለኢትዮጵያ ሰዎች አጥብቃ ትጸልይና ታዝን ጀመር።
❤ በዚህ አይነት ተጋድሎ ሰውነቷን ወይም ሥጋዋን በልዩ ልዩ ፀዋትወ መከራ ስትፈትና ኖረች። ፈጥና በክንፈ ረድኤት ወደ በዓቷ የምትመለስበት ጊዜ አለ። በዚህ አይነት ግብር ለብዙ ዘመን ኖረች። በምትሰግድበት ጊዜ ወደፊት ስትል ደረቷን ወደኋላ ስትል ጀርባዋን ወደቀኝ ስትል ቀን ጎኗን ወደግራ ስተል ግራ ጎኗን ጦሩ እየወጋት ከቊስሉ የተነሣ ጦሩ የወጋት ገመዱ የከረከራት መላ ሰውነቷ ሸቶ ተልቶ ለዐሥራ ሁለት ዓመት ተጋድሎ አደረገች።
❤ እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ግን እግዚአብሔር ኃይል ጸንታለችና ከጉድጉዳ ወጥታ በጣና ባሕር ውስጥ ገብታ እንድትጸልይ የእግዚአብሔር መልአክ አዘዛት ከዚያም በባሕሩ ውስጥ እየጸለየች ሦስት ዓመት ተቀመጠች።
❤ ከሦስት ዓመት በኋላ እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ በጣና ባሕር ውስጥ ሳለች ለጌትነቱ ክብር መሰገድ የሚገባው ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ወደእስዋ መጣ። ከሱም ጋር ቅዱሳን ሚካኤል፣ ገብርኤልና ሩፋኤል እናቱ ማርያም መጡ። ዐሥራ አምስቱ ነቢያት ዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ሰባ ሁለቱ አርድእት ጻድቃን ሰማዕታት ደናግልና መነኰሳት ሌሎች ሁሉም በየሥርዓታቸውና በየማዕረጋቸው በየነገዳቸው መጡ። ኄሮድስ ያስፈጃቸው ሕፃናት አለቃቸው ሕፃኑ ቂርቆስን ተከትለው እደዚሁም ዘጠና ዠጠኙ ነገደ መላእክት በየነገዳቸውና በየወገናቸው መጡ።
❤ ከነዚህ ሁሉ በኋላ የእስራኤል ንጉሥ ዳዊት መጥቶ "ልጄ ሆይ ስሚ ጆሮሽን አዘንብይ ወገንሽንና ያባትሽንም ቤት እርሺ ንጉሥ ውበትሽን ይወዳል እርሱ ጌታሽ ነውና" እያለ በገናውን ይደረድር ነበር። እንዲህም እያለ በሚዘምርበት ጊዜ በዚያ ያሉ ቅዱሳኖች በሙሉ "የእግዚአብሔር ባለሟል ወይም ወዳጅ ይህች ክርስቶስ ሠምራ በእውነት ብፅዕት ነች" እያሉ ዘመሩ።
❤ በዚያን ጊዜ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ ዛሬ ከዚህ ከሚያልፈው ዓለም ወደማያልፈው ዓለም ላስተላልፍሽ መጥቻለሁ" አላት። "ድካምሽ ወደዕረፍት ኃዘንሽ ወደ ደስታ ችግርሽ ወደ ብልጽግና ተለውጦልሻል። እውነት በእውነት እልሻለሁ ወይም እነግርሻለሁ በፍጹም ደስታ መታሰቢያሽን ያደረገ በመንግሥተ ሰማያት አስደስተዋለሁ። በችግሩ ወይም በጭንቁ ጊዜ በመታመን ስምሺን ቢጠራ እኔ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ አድነዋለሁ።
❤ የገድልሽን ዜና የሚናገረውን መጽሐፍ የጻፈ ወይም ያጻፈ እኔ ስማቸውን በሕይወት መጽሐፍ እጽፍላቸዋለሁ። ቤተ ክርስቲያንሽን የሠራ ወይም ያሠራ ያሣነፀ ወይም ያነፀ እኔ በመንግሥተ ሰማያት ንጹሕ አዳራሽ አዘጋጅለታለሁ። በስምሽ ለተራበ ያበላ እኔ በዕለተ አርብ ከተቆረሰው ሥጋየ አበላዋለሁ። በስምሽ ለተጠማው እፍኝ ውሃ ያጠጣ እኔ በዕለተ አርብ ከጎኔ በሰሰው ደሜ አረካዋለሁ። በዓልሽ በሚከበርበት ዕለት ጧፍ፣ ዕጣን፣ ወይም ዘይት ንጹሕ ስንዴ የመሰለውንም ሁሉ መባ ያገባ መሥዋዕቱን እንደ አብርሃምና እንደ መልከ ጼዴቅ መሥዋዕት አድርጌ እቀበልለታለሁ" አላት
❤ በዚህ ጊዜ "አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እኔ ባርያህ ባለሟልነትን በፊትህ ካገኘሁስ አንድ ጊዜ እናገር ዘንድ ፍቀድልኝ" አለችው። እርሱም "ትናገሪ ዘንድ ፈቅጄልሻለሁ" አላት። " አቤቱ ሥጋዬ የሚቀበርበትን ወይም የሚያርፍበት ቦታ ወዴት ታዝዛለህ" አለችው። መቃብርሽ በዚች ጓንጒት በምትባል ደሴት ውስጥ ነው" አላት። "ነገር ግን ሥጋሽ በመሬት ውስጥ ይቀበራል ስላልኩሽ ኀዘን አይግባሽ በኋለኛው ዕለት እኔ አስነሣዋለሁና" አላት።
❤ "አቤቱ እንዲህ ከሆነ መታሰቢያየን እያደረገ ስሜን እየጠራ በስሜ በታነጸው ቤተ ክርስቲያን ቅጥር ግቢ የሚቀበረውን እስከ ስንት ትውልድ ድረስ ትምርልኛለሁ" አለችው። "እስከ ዐሥር ትውልድ ድረስ እምርልሻለሁ" አላት። ይህንም ቃል ኪዳን በሰጣት ጊዜ ፈጽማ ተደሰተች።
❤ ዳግመኛም "ይህች ደሴት እንደ ደብረ ታቦርና ደብረ ዘይት ስሟ የተጠራ ይሁን" አላት። "እንደዚሁ ይህችን ሥጋሽ የምታርፍበትን ቦታ ቀደስኳት አከበርኳት። መጽሐፍ የተናገረውን አልሰማሽምን ቦታ ሰውን የሚያከብረው አይደለም ሰው ቦታን ያስከብረዋል እንጂ። ስለዚህ ነገር ስላንቺ ይቺን መካነ መቃብርሽን ቀደስኳት አከበርኳት። ስሟም ደብረ ፍቅር ደብረ ምሕረት ተብሎ ይሰየም ወይም ይጠራል። እውነት እውነት እልሻለሁ ሥጋሽ ከተቀበረበት ሄዶ መካነ መቃብርሽን የተሳለመ የእናቴን የማርያምን መካነ መቃብር እንደተሣለመ ይቆጠርልታል። እውነት እውነት እልሻለሁ አንቺን ያከበረ ሁሉ እኔ በሰማያዊ መንግሥቴ አከብረዋለሁ። አንቺን የወደደ ወይም ያፈቀረሽን እኔ አፈቅረዋለሉ።
❤ ዳግመኛም "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ይህ የዛሬው በዓልሽ የደስታና የተድላ ቀን ነው" አላት። ይህንንም ብሎ በብዙ ወገን ወይም ሠራዊት ላይ ሾማት። "ክብሮሽ ከአሮንና ከሙሴ፣ ከጴጥሮስና ከጳውሎስ፣ ሰይጣን ድል ከአደረገው ከሕፃኑ ቂርቆስ፣ ከእንጦንስና ከመቃርስ፣ ከፀሐየ ልዳ እየተባለ ከሚጠራ ከጊዮርጊስ ጋር ክብር ጋር ትክክል ነው" አላት።
❤ በደብረ ጽዮን ከሊቀ ዲያቆናት እስጢፋኖስ ጋር ትዘምሪ ዘንድ በክብር ተካከልሽ። በእውነት አንቺን የሚያፈቅሩ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው" አላት። ነቢዩ ዳዊት "አቤቱ እግዚአብሔርን ከሚያከብሩ ወይም ከሚፈሩ በስተቀር በድንኳንህ ውስጥ ማን ያድራል በተቀደሰውስ ተራራ ላይ ማን ይኖራል" ብሎ ተናግሯልና። ስለዚህም አንቺን የሚያከብሩ ሁሉ አንቺን ከአለሽበት ቦታ ገብተው ከአንቺ ጋር ይደሰታሉ"።
❤ ከዚህም አምላካዊ ቃል ጋራ በነሐሴ 24 ቀን የአባታች ተክለ ሃይማኖት በዓል የሚከበርበት ዕለት ነፍሷ ከሥጋዋ ተለየች። በዚህ ጊዜ የነጎድጎድ ብልጭልጭታ ሆነ ነቢዩ ዳዊት "በመፍራትና በመንቀጥቀጥ ለእግዚአብሔር እልል በሉ" ብሎ እንደተናገረ የመላእክት ሠራዊትና ጻድቃን ሰማዕታትም ሁሉ እልል እያሉ አመሰገኑ። እርሷም ከነርሱ ጋር እየተደሰተች አመሰገነች። ከዚያም መላእክት ኢየሩሳሌም ሰማያዊት አድርሰዋት ወይም አሳርገዋት በሸናፊው በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት ሰገደች።
ስትደርስ የራስ ፀጒራን ይዛው በነበረ ምላጭ ላጨች ልብሷንም አውልቃ ለነዳያን አከፋፈለች የያዘችውንም ገንዘብ በመንገድ ላይ ላገኘችው ሁሉ መፅውታ ጨረሰች። ከዚያም አስቀድማ ያዘጋጀችውን ልብስ ምንኵስና ማለት ቀሚስዋን አጥልቃ አጽፋን ተጐናጽፋ ቆቧን ደፍታ ደብረ ሊባኖስ ከሴቶች ገዳም ደረሰች። የገዳሙ መነኰሳትም በታላቅ ክብር ተቀብለው ወደበዓታቸው አስገቧት ...
❤ እናታችን ቅድስት ክርስቶስ ሠምራ ለሳጥናኤል ምሕረት እንደለመነች፦ ከዕለታት በአንድኛው ቀን እናታችን ክርስቶስ ሠምራ ጓንጉት በምትባል ደሴት ውስጥ ዓርብ ዕለት ከቀኑ በስድስት ሰዓት ላይ ስለሰው ልጆች ስትጸልይ ሣለ። ዓለሙ ሁሉ ከንቱ እንደሆነና የሰውም ልጅ ሕይወት እንደጥላ ኃላፊ ጠፊ መሆኑን ፈጽማ ተመለከተች። ነቢዩ ዳዊት "ሰው ከንቱ ነገርን ይመስላል ዘመኑ ወይም ሕይወቱ እንደጥላ ያልፋል" ሲል ተናግሯልና። ዳግመኛም "ሰው ክብር እንኳ ቢሆን ሊኖር አይችልም እንደሚጠፋ ወይም ማስተዋል እንደሌለው እንስሶች መሰለ... አለ ክቡር ዳዊት። ስለዚህም ሁሉ ነገር አቤቱ ማራቸው ይቅርም በላቸው መፃተኛዋ ባሪያህንም ኃጢአቷን አታስብባት እያለች ወደፈጣሪዋ መሪር ዕንባን አለቀሰች። ያን ጊዜ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ በታላቅ ግርማ ወደስዋ መጣ። በታላቅ ግርማ ሆኖ ባየችውም ጊዜ ደነገፀች ከእግሩ ሥርም ወደቀች። ከዚህ በኋላ ነውር በሌለባቸው ንዑዳት ክቡራንና ንጹሐን በሆነ እጆቹ አነሣት። ቀጥሎም "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ አትደንግጭ ነገር ግን የልብሽን ሃሳብ ንገሪኝ" አላት። እስዋም "አቤቱ ባሪያህንስ በባለሟልነት ካሠለጠንካት አባታችን አዳምን በአርአያህና በአምሣልህ ስለምን ፈጠርከርው። በእንጨት መስቀልስ ላይ ለምን ተሰቀልክ ስለአዳምና ስለልጆቹ አይደለምን?" አለችው። "አዋን ስለነሱ ስል ተሰቅያለሁ" አላት። "እግዲያውስ መሰቀልህ ወይም የተሰቀልከው ስለነሱ ከሆነ ከአቤል ጀምሮ እስከ ዛሬ የሞቱን ከዛሬም በኋላ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ የሚሞቱትን አቤቱ ማራቸው ይቅርም በላቸው" አለችው። "አንተ ቸር ይቅር ባይ መዓትህ የራቀ ምሕረትህ የበዛ ነህና ከአንተ ሌላ አምላክ የሌለ እውነተኛ አምላክ ነህ ሁሉ ይቻልሃልና የሚሣንህ ነገር ከቶ የለምና ዓለም በጠቅላላዋ በእፍኝህ አትሞላም" በማለት እያለቀሰች ለመነችው። በዚያ ጊዜ ጌታ መልሶ "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ እስኪ አንቺ ራስሽ ፍረጅ አዳም ከነልጆቹ ከሠራው ኃጢአት እና እኔ በጰንጤናዊው በጲላጦስ ዘመን በቀያፋና በሐና አደባባይ በዕለተ ዓርብ ከተቀበልኩት ሕማማተ መስቀል ቢመዘን የትኛው ይመዝን ይመስልሻል?" አላት። ይህንም ባላት ጊዜ ደነገጠችና ከመሬት ላይ ወደቀች። በዚህ ጊዜ ቅዱሳት በሆኑ እጆቹ ከወደቀችበት አነሣትና "እንግዲህ ይህን ሁሉ መከራ የተቀበልኩ ለማን ወይም በማን ምክንያት ይመስልሻል" አላት።...
❤ ጌታም "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ እስኪ የልብሽን ሃሳብ ወይም ፍላጐትሽን ንገሪኝ" አላት። በዚህን ጊዜ "አቤቱ ፈጣሪየ ፈቃድህስ ቢሆን የአዳም ልጆች ከሥቃይ ከኵነኔ ይድኑ ዘንድ ዲያብሎስን ይቅር ትለው ወይም ትምረው ዘንድ እለምንሃለሁ። የኃጥእን መመለሱን እንጂ ጥፋቱን አትወድምና" አለችው። "የምለምንህ ወይም ማረው የምልህ ዲያብሎስን ወድጄው አይደለም ነገር ግን እርሱ ከተማረ በአዳም ልጆች ላይ ሥቃይና ኵነኔ ሊኖር አይችልም ብየ በመገመት እንጂ። የነሱ ሥጋ ሥጋየ እንደሆመኑ መጠን የኔም ሥጋ ሥጋህ ነውና" አለችው። ይህንም ባለችው ጊዜ ጌታ ፍግግ ብሎ "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ ሌሎች ካንቺ በፊት የነበሩ ካንቺም በኋላ የሚነሱ የማያስቡትን እጅግ የሚያስደንቅ ልመና አቀረብሽ" አላት። ይህንም ካለ በኋላ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል ጠርቶ "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ዲያብሎስን ማርልኝ ስትል ልመና አቅርባለችና እሺ ካላት ታወጣው በንድ ወደሲዖል ይዘሃት ሂድ" ብሎ አዘዘው። በዚህ ጊዜ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል እሺ ብሎ ሰግዶ እጅ ነሥቶ ወደሲዖል ይዞአት ሄደ። አብረው በሚጓዙበትም ጊዜ "እንግዲህ ዲያብሎስ ከታረቀ ወይም ከተማረ የሰው ልጆች ሁሉ ያርፋሉ" እያለች ለመላእክት አለቃ ለቅዱስ ሚካኤል ታሳስበው ነበር። ይህን አምላክነትን ሲሻ ከክብሩ የተዋረደ ዲያብሎስ ምሕረት ለማግኘት ይሻ መስሏት ነበርና።
❤ ከሲዖል አፋፍ በደረሱም ጊዜ የተመለከተችው ሥቃይ ተነግሮ የማያልቅ ነው ሰዎች ከሰዎች ጋር እንደውሻ ይናከሱ ነበር። የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል "ምሕረት የሚፈልግ ከሆነ እስኪ በይ ዲያብሎስ ብለሽ ጥሪው" አላት። በዚህ ጊዜ በመላእክት ቋንቋ ሦስት ጊዜ "ሣጥናኤል ሣጥናኤል ሣጥናኤል" በማለት ጠራችው። ዲያብሎስም "ከዚህ በብዙ ሠራዊት ላይ ነግሼ ከምኖርበት አገር ማን ነው እሱ የሚጠራኝ" እያለ በታላቅ ቃል አሰምቶ ተናገረ። ከዚህም በኋላ "ለብዙ ዘመን ስፈልግሽ ወይም ሳድንሽ ቆይቼ ነበር ዛሬ ግን ከምኖርበት ቤቴ ድረስ መጣሽን" አላት። እርሷም "ጌታ ይቅርታ አድርጓልሃልና ከዚህ ከሥቃይና ከመከራ ቦታ ከወገኖችህ ጋራ ና ፈጥነህ ውጣ" አለችው። ይህንም በለችው ጊዜ ልቡ እንደ እሳት ነደደ አፈፍ ብሎ ተረማምዶ በግራ እጁዋን ይዞ ከሲዖል ረግረግ ውስጥ ወረወራት። በዚያን ጊዜ የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤል የእሳት ሰይፍ ይዞ ከኋላ ከኋላዋ ይከተላት ነበርና ይህን ምሕረት የሌለው ዕቡይ ዲያብሎስ በያዘው ሰይፍ ቢቀጣው የሲዖል ደጃፍ ተከፈተች። በዚህ ሰዓት ታላቅ ጨኸትና ውካታ ወይም መደበላለቅ ሆነ በሲዖል ያሉ የሰዎች ነፍሳት እንደንብ ከበቧት ወይም ሠፈሩባት። በዚያን ጊዜ በቅዱስ ሚካኤል ክንፍና በስዋም በተሰጣት ክንፈ ረድኤት ከሲዖል የወጡት ነፍሳት ቁጥር ዓሥር ሺህ ያህል ነበር። እነዚህ ከመከራ ያመለጡ ከሥቃይ የወጡ ነፍሳትን ባየች ጊዜ እጅግ አድርጋ ተደሰተች ከደስታዋም ብዛት የተነሣ የእናቱን ጡት እየጠባ እንደሚዘል እምቦሳ ጥጃ በመካከላቸው ትዘል ነበር።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ ፈጣሪዋ ሄዳ "አቤቱ ፍርድህ ከቶ እንደዚህ ነውን?" እያለች አደነቀች። ጌታም "ወዳጄ ክርስቶስ ሠምራ ሆይ ዲያብሎስን ድል አድርገሽ ጥቂት ምርኮን አገኘሽን" አላት። እስዋም "አዋ ጌታዬ በኃይልህና በቸርነትህ አገኘሁ" አለችው። ከዚህ በኋላ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሚካኤል ጠርቶ "እሊህን ነፍሳት ዓለም ሳይፈጠር ወደ አዘጋጀሁላት ወደ ክርስቶስ ሠምራ መኖሪያ ቦታ ውሰዳቸው" አለው። በዚህ ጊዜ "አቤቱ ፈጣሪየ የእኔ መኖሪያየ ወዴት ነው?" አለችው። ጌታም "መኖሪያሽ ከእናቴ ከድንግል ማርያም ጋራ ነው እነሆ በትረ ማርያም ብየ ሰየምኩሽ መቀመጫሽን ወይም ደረጃሽን ከእርስዋ ቀጥሎ ሁለተኛ አደረግሁልሽ የባለሟልነት ግርማ አጐናጸፍኩሽ አንቺን የሚወዱ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው" አላት። ይህንም ባላት ጊዜ ፈጽማ ደስ ተሰኘች ወደ ኋላዋም መለስ ብላ ብትመለከት ለዓይን የሚያንፀባርቁ ዓሥር አክሊላት አየች። በየአንዳንዳቸው አክሉል ላይ ዐራት ከዋክብት አሉ ባቸው የእሊህ ከዋክብት ቊጥራቸው ሲደመር አርባ ይሆናል። በዚህ ጊዜ ከስዋ ጋራ የነበረውን መልአክ "እሊህ በላያቸው ብርሃናውያን ከዋክብት ያሉባቸው አክሊላት ለማን የተዘጋጁ ናቸው ሰውነቴ እጅግ አድርጋ ወዳቸዋለችና" አለችው። የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም "ላንቺ ቢሆን ደስ አይልሽምን?" አላት። እርስዋም "አዎን ጌታየ ለኔ ቢሆን እወዳለሁ" አለችው። "እንግዲያስ ላንቺ የተዘጋጁ ናቸው" አላት። "በምን ሥራዬ ለኔ ተሰጡኝ" አለችው። "ዐሠርቱ ቃላት ኦሪትን ስድስቱን ቃላተ ወንጌል ጠብቀሽ ቤትሽን ጥለሽ ይህን ዓለም ንቀሽ አጥቅተሽ የክርስቶስን ቀምበር ተሸክመሽ
