ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Kanalga Telegram’da o‘tish
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Ko'proq ko'rsatish636
Obunachilar
Ma'lumot yo'q24 soatlar
-47 kunlar
-1130 kunlar
Postlar arxiv
❤ ሊቀ ጳጳሳቱም ለመኰንኑ ይህንን ሃያ ሺህ የወርቅ ዲናር ሰጠው መኰንኑም ዐሥር ዐሥር ሺህ የወርቅ ዲናር እንደ ግብር ሆኖ በየዓመቱ እንዲከፈል ጽፊ አስፈረመው ጊዜውም ሲቀርብ ይህ አባት አባ ሚካኤል ከምዕመናን ሊሊምን ተነስቶ ወጣ በልበይስ ወደተባለም አገር ደርሶ አንድ ቀን ዋለ። ወደርሱም አንድ ምስኪን ድሃ መነኵስ ገባ ከሊቀ ጳጳሳቱም ቡራኬ ተቀቡሎ ተመልሶ በበር አጠገቡ ከረድኡ ጎን ቆሞ "አትዘን በልብህም አትተክዝ ከዛሬይቱ ዕለት እስከ አርባ ቀኖች ትድናለህ በላይህ ያለውን የእዳ ደብዳቤ ትቀበላለህና ለመኰንኑም ምንም አትስጠውም ብለህ ለአባት ሊቀ ጳጳሳት ንገረው" አለው። ያ ረድኡም እንዳለው ነገረው ደሃውንም መነኵስ ፈለጉት ግን አላገኙትም አርባ ቀኖችም ሳይፈጸሙ ያ መኰንን በክፉ አሟሟት ሞተ። በእርሱ ፋንታም ልጁ ተሾመ ለዚህም አባት ያንን የእዳ ደብዳቤ መለሰለት። ይህም አባት ድሃው መነኰስ ትንቢት እንደ ተናገረ ደብዳቤውን ተቀብሎ ቀደደው ከዕዳም ዳነ።
❤ ይህም አባት በታላቅ መከራና በኀዘን በሹመቱ ዘመን ሃያ ዘጠኝ ዓመት ከኖረ በኋላ መጋቢት20 ቀን በፍቅር በሰላም ዐረፈ። በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት20 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለሑረትከ_እግዚአብሔር_ኬንያ። እምኢየሩሳሌም ለቢታንያ። ከመ ታንሥእ በድኖ #ለአልዓዛር_እኅወ_ማርያ። ትሴፈወከ ነፍስየ ወትጸንከ ነያ። እሞተ ኃጢአት ታሕይዋ በዝንቱ አርአያ። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት_20።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦"እስመ በእንቲአሁ ይቀትሉነ ኵሎ አሚረ። ወኮነ ከመ አባግዕ ዘይጠብሑ። ንቃህ እግዚኦ ለምንት ትነውም"። መዝ 43፥22። የሚነበቡት መልዕክታት ፊል 1፥12፣18 ያዕ 5፥8-14 እና የሐዋ ሥራ 24፥10-22። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 11፥17-46። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጐድጓድ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።
ተአምኆ ቅዱሳን ወግጻዌ (የቅዱሳን ሰላምታ) Teamho Kidusan Wegtsawe (Yekidusa Selamta):
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፳ (20) ቀን።
❤ እንኳን #ለክብር_ባለቤት_ለጌታችን_ለአምላካችን #ለመድኃኒታችን_ለኢየሱስ_ክርስቶስ የሚወደው ጻድቅ ሰው #ቅዱስ_አልዓዛርን ከሞተ በኋላ በአራተኛው ቀን ከሙታን ለይቶ አስነስቶት ነበርና ስለዚች ምልክት ገናናነት ብዙዎች በጌታችን ላመኑበት በዓል፣ ለተጋዳይም በተአምራቷ ከ5,685 በላይ ሰዎችን በጌታችን እንዲያም ላደረገ #ለቅድስት_አስጠራጦኒቃ ሰማዕትነት ለተቀበለችበት ለዕረፍቷ በዓልና ለእስክንድርያ ሃምሳ ሰባተኛ ሊቀ ጳጳሳት #ለአባ_ሚካኤል ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ ከተጋዳይዋ #ከቅድስት_ጽጌ_ሥላሴ ከመታሰቢያዋና #ከቅዱስ_አስቃራን ቤተ ክርስቲያኑ ከከበረችበት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ በዚች ዕለት የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ_ጻድቅ_ሰው_አልዓዛርን ከሞተ በኋላ በአራተኛው ቀን ከሙታን ለይቶ አስነስቶት ነበርና ስለዚህ ምልክት ገናናነት ብዙዎች አመኑበት። ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቸር አባቱና ሕይወት ከሆነ መንፈስ ቅዱስ ጋር ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅድስት_አስጠራጦኒቃ፦ የዚች ቅድስት አባቷ ጣዖት አምላኪ ነው እርሷ ግን በክብር ባለቤት በክርስቶስ የምታምን ናት ሥጋዋም እስቲከሣና እስቲደርቅ መልኳም እስቲለወጥ ድረስ በሥውር ትጾማለች ትጸልያለችም።
❤ ዐሥራ አምስት ዓመት በሆናት ጊዜ እናትና አባቷ "ምነው ያከሣሻል?" አሏት፡፡ እርሷም "እኔስ ኃጢአቴን ይቅር ይለኝ ዘንድ የክብር ባለቤት ወደሆነ ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እጸልያለሁ" አለቻቸው፡፡ አባቷም በሰማ ጊዜ ወደ ጢባርዮስ ሒዶ የልጁን ሥራ ነገረው እርሱም ወታደሮች ልኮ ወደ ርሱ አመጣት። ለጣዖትም እንድትሰግድ መኰንኑ አባበላት እምቢ በአለችም ጊዜ ወደ ወህኒ ቤት አስገቧት እናቷም ክርስቲያናዊት ናት እየመጣች በክብር ባለቤት በክርስቶስ እምነት ታበረታታት ነበር።
❤ ከዚህ በኋላ የብረት የሆነ የሰሌዳ ክርታስ ይሠሩላት ዘንድ በእሳትም አግለው ክንዶቿ ከወገቦቿ ጋራ አንድ እስቲሆኑ እንዲያጣብቋት አዘዘ። ይህንንም በአደረጉባት ጊዜ ያንን የብረት ክርታስ ሰብራ በድኅና ወጣች ሕዝቡም ይህን አይተው በክብር ባለቤት በክርስቶስ አራት ሺህ ሰባት መቶ ያህል አምነው በሰማዕትነት ሞቱ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበሉ።
❤ ሁለተኛም ደግመው ከእሥር ቤት አስገቧት ጥፍሮች ያሉት የብረት በሬ ሠሩላት ሆዷን ያስወጓት ዘንድ ሊሰቅሏትም ወርሷ አቀረቡት ይህንንም በአደረጉባት ጊዜ በጌታ ኃይል በሬው ወዲያና ወዲህ ተከፈለ ሕዝቡም ይህን በአዩ ጊዜ በክብር ባለቤት በጌታችን ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አምስት ያህል ሰው አምነው በሰማዕትነት ዐረፋ።
❤ ከዚህም በኋላ መርዝን ከተመሉ እባቦች ጒድጓድ ውስጥ ጨመሯት በጸየለች ጊዜ እንደ ትቢያ ሆኑ። ሁለተኛም አራት ሰዎች የሚሸከሙትን ከባድ ደንጊያ አምጥተው በአንገቷ ላይ ሰቀሉ በጸለየችም ጊዜ ደንጊያው ወደ ሦስት ተከፈለ። ብዙዎች አረማውያንም በክርስቶስ አምነው በሰማዕትነት ዐረፉ።
❤ ለቅድስቲቱ ግን የብረት ምንቸት አዘጋጁላት በውስጡ የፈላ እርሳስ በላይዋ ያፈሱባት ዘንድ በነኩት ጊዜ በላያቸው ተሰብሮ የሚያሰቃዩአትን ገዳላቸው።
ንጉሡም አይቶ ተቆጣ ራሷንም በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ። ምስክርነቷን ከምትፈጽምበት ቦታም በደረሰች ጊዜ ወደ እግዚአብሔር ጸለየች "አስጠራጦኒቃ ሆይ አንቺ ብፅዕት ነሽ ስምሽ በሕይወት መጽሐፍ ተጽፏልና" የሚል ቃል መጣላት ከዚያም በኋላ በሰይፍ አንገቷ ተቆረጠች። በቅድስት አስጠራጦኒቃ በጸሎቷ የሚገኝ በረከቷ ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ሚካኤል፦ ይህም አባት በእስክድርያ ከተሾሙ አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃምሳ ሰባተኛ የሆነ ነው። በሹመቱ ወራት ብዙ ኀዘንና መከራ ደረሰበት። ጎሕ በሚባል አገር የተሾመ የዚህን ኃላፊውን ዓለም ክብር የሚወድ አንድ ክፉ ኤጲስቆጶስ ነበር። በአገረ ስብከቱም ውስጥ ደነውስር በሚባል አገር ያሉ ምዕመናን የቤተ ክርስቲያናቸውን ሕንፃዋን አደሱ ሊያከብሩዋትም በፈለጉ ጊዜ የአገር ታላላቆች ከእርሳቸውም ሊባረኩ ወደው ሊቀ ጳጳሳት ልኮ እንዲያመጣቸውና ይህን ክፉ ኤጲስቆጶስ ለመኑት እርሱ ግን አምቢ አላቸው ልመናቸውን መቀበል አልወደደም እነርሱም በራሳቸው ፈቃድ ይህ ክፉ ኤጲስቆጶስ ሳይፈቅድ ሊቀ ጳጳሳቱንና ኤጲስቆጶሳቱን ሁሉ ልከው አስመጧቸው ሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤልና ኤጲስቆጶሳቱ ሁሉ በመጡ ጊዜ ምሳ አዘጋጅላችኋለሁ ብሎ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ትቷቸው ሄደ "ማርታ ማርታ ብዙ በማዘጋጀት ብዙ ትደክሚያለሽ ግን ጥቂቱ ይበቃል" ያለውን የጌታችን ቃል አላሰበም በቁርባን ጊዜ ሊያልፍ ስለሆነ ሊቃውንቱና ኤጲስቆጶሳቱን የቅዳሴውን ሥርዓት ይጀምር ዘንድ ሊቀ ጳጳሳቱን ለመኑት ግድ ባሉት ጊዜ በሊቀ ጵጵስና ማዕረግና ክብር ተሰይሞ ተነሳ እርሱ ለሁሉ አባት የሆነ ስልጣኑም ከስልጣናቸው በላይ ነውና የቅዳሴውን ሥርዓት ጀመረ ያክፉ ኤጲስቆጶስም በሰማ ጊዜ በልቡ ሰይጣን አደረበትና ተቆጥቶ መጣ መስዋዕቱንም ከመቅደስ ገብቶ ከጻህሉ ውስጥ ነጥቆ መደ ምድር ወረወረው ሊቀ ጳጳሳቱም ሌላ መስዋዕት አምጡ ብሎ አዘዘ። አምጥተውለትም ቀድሶ ለሕዝቡ ሥጋውና ደሙን አቀበላቸውና አሰናበታቸው።
❤ በማግስቱም ይህ አባት አባ ሚካኤል ሕዝቡ ሰበሰበ ከእርሱ ጋራ ያሉትንም ኤጲስቆጶሳት ካህናቱንና የምዕመናን አንድነት ሰብስቦ ይህን ክፉ ኤጲስቆጶስ ከሹመቱ ሽረው በእርሱ ፋንታ ሌላ ኤጲስቆጶስ ሾሙ። ይህም የአስቆሮቱ ሰው ለይሁዳ ሁለተኛው የሆነ የምስርን አገር ወደሚገዛ ስሙ አህመድ ወልደ በጥሎን ወደተባለው ሹም ሆደ ይህንን አባት አባ ሚካኤልን እንዲህ ሲል ነገር ሰራበት "በሊቀ ጳጳሳቱ ዘንድ ብዙ የወርቅና የብር ገንዘብ እንዳለ እንዲሁም አብያተክርስቲያናት የወርቅና የብር ነዋየ ቅድሳትን የተመሉ እንደሆኑ መኰንን ሆይ እወቅ" አለው። መኰንኑም ይህን አባት ወደ እርሱ አስቀርቧ ነዋየ ቅድሳቱን እንዲሰጠው ፈለገ እርሱም "ሥጋዬን እንደፈለገህ አድርግ ነፍሴ ግን በእግዚአብሔር እጅ ናት" ብሎ ከለከለው። እጆቹንና እግሮቹን አስረው በእስር ቤት እንዲጥሉት አዘዘ። በእስር ቤትም ከአንድ ዓመት በላይ ኖረ። በእስር ቤት ውስጥ በኖረበት ዘመን ከለምለም እንጀራና ከጨው ከበሰለ አተር በቀር ሳይባላ ሁል ጊዜ ይጾም ነበር።
❤ ከዚህ በኋላ አንድ ጸሐፊ ምዕመን ዮሐንስ የሚባል መጥቶ ለዚህ ለከበረ አባት አባ ሚካኤል ዋስ ሆነው ለመኰንኑም አባ ሚካኤል ሃያ ሺህ የወርቅ ዲናር እንዲሰጠው ሆኖ ከወህኒ ወቶ ወደ ቤቱ ሄደ ጥቂት ቀንም ተቀመጠ። ታላላቆች ምዕመናንና የአስቄጥስ ገዳም መነኰሳት ዐሥር ሺህ የወርቅ ዲናር ሰበሰቡ ደግሞ የእስክንድርያ አገር ሰዎች ከምድራቸው አንዱን ለዐሥራ ሺህ ዲናር ሸጡ ሃያ ሺህ እስኪሞላ ሰበሰቡ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት (፲፱) 19 ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት ለአንዱ ለሐዋርያው #ቅዱስ_ጳውሎስ ደቀ መዝሙር #ለቅዱስ_አርስጥቦሎስ ለዕረፍት በዓል፣ #ለቅዱስ_አሰከናፍርና_ለሚስቱ ማርታ፣ ለልጆቹ #አርቃድዮስና_ዮሐንስ ለዕረፍታቸው በዓልና #ለሰባቱ_ሰማዕታት ለዕረፍታቸው መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_አርስጥቦሎስ፦ እርሱም ጌታችን ከመረጣቸውና ከመከራው በፊት ወንጌልን እንዲሰብኩ ከላካቸው ከሰባ ሁለቱ አርድእት ውስጥ የተቈጠረ ነው።
❤ በሃምሳኛው ቀን በዓልም መንፈስ ቅዱስ በላዩ በወረደ ጊዜ ከሐዋርያት ጋራ ጸጋንና ኃይልን ተመልቶ ሕይወት በሚገኝበት በወንጌል ትምህርት ሐዋርያትን ተከትሎ በመሔድ አገለገላቸው። ብዙዎችንም ወደ ድኅነት መንገድ መልሶ የክብር ባለቤት ወደ ሆነ ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ሃይማኖት አስገባቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጥቆ የአምላክን ሕግና ትዕዛዝ ከማስጠበቁ የተነሣ ነፍሳቸውን አዳነ።
❤ አባቶቻችን ሐዋርያትም ይህን ቅዱስ አብራጣብያስ በሚባል አገር ላይ ኤጲስቆጶስነት ሾሙት። ወደርሷም ሒዶ በውስጥዋ ወንጌልን ሰበከ ብዙዎቹንም በቀናች ሃይማኖት እግዚአብሔር ወደ ማወቅ መለሳቸው። በፊታቸው ድንቆች ተአምራትን በማድረግ በሃይማኖት አጸናቸው ነገር ግን ከአይሁድና ከዮናናውያን ብዙ መከራ ደረሰበት። ብዙ ጊዜም ወደ ፈራጆች አደባባይ ወስደው በደንጊያ ወገሩት ጌታችንም ከመከራው ሁሉ ጠብቆ አዳነው መልካም ተጋድሎውንም በፈጸመ ጊዜ መጋቢት19 በሰላም በፍቅር ዐረፈ።
❤ እነሆ ለሮሜ ሰዎች በጻፈው መልክቱ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ አስታውሶታል። ከቅዱስ አርስጥቦሎስ በጸሎቱ የምትገኝ በረከት ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱሳን_አሰከናፍርና_ሚስቱ_ማርታ፣ ልጆቹ #አርቃድዮስና_ዮሐንስ፦ ይህም አስከናፍር ብዙ ገንዘብ ያለው ባለጠጋ ነው። ለእግዚአብሔር ሕግ የሚጠነቀቅ ነበር ልጆቹንም መንፈሳዊ ምክርና ተግሣጽ በማስተማር አሳደጋቸው። በአደጉም ጊዜ የጥበብንና የተግሣጽን ትምህርት እንዲማሩ ተይሩት ወደምትባል አገር ሰደዳቸውና ትምህርታቸውን በፈጸሙ ጊዜ ሊድራቸውና በሰርጋቸው ደስ ሊለው ሽቶ ያመጧቸው ዘንድ ላከ በመርከቡም ሁነው ሲመጡ ማዕከል ተነሥቶ መርከቡ ተሰበረ። እግዚአብሔርም ከሰጥመት አድኖ በየብስ አወጣቸው ዮሐንስ የተባለውን በአንድ ቦታ ማዕከል አውጥቶ ጣለው።
❤ ዮሐንስም ተስፋ በቆረጠ ጊዜ ወደ ቅዱሳን ገዳም ሒዶ መነኰሰ።ስለ ወንድሙ ስለ አርቃድዮስም እንተሞተ ተጠራጥሮ በጾም በጸሎትና በስግደትም ሥጋውን አደከመ። አርቃድዮስም ወደ ዮርዳኖስ ገዳም ገብቶ ከአንድ ቅዱስ አረጋዊ ሰው ዘንድ መንኵሶ እየተጋደለ ሦስት ዓመት ኖረ።
❤ አስከናፍር ግን ልጆች በማዕበል እንደ ሰጠሙ በሰማ ጊዜ ከሚስቱ ጋራ ማቅ ለብሰው አመድ አንጥፈው እያለቁሱ ተቀመጡ። በአንዲት ሌሊትም አስከናፍር በሕልሙ ልጁ ዮሐንስ በራሱ ላይ ከዕንቊ የተሠራ አክሊል ተቀዳጅቶ መስቀል ይዞ አየው። አርቃድዮስንም በኮከብ አምሳል የሆነ አክሊል በራሱ ላይ ደፍቶ አየ ከእንቅልፉም ነቅቶ ለሚስቱ ያየው ነገራት።
❤ ከዚህም በኋላ በየአድባራቱና በየገዳማቱ የልጆቻችንን ወሬ እንመርምር ዘንድ ተነሺ እንሒድ አላትና ወደ ዮርዳኖስ ሒደው ከመጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ገዳም ደረሱ። ልጃቸውን አርቃድዮስን ያመነኰሰውን አረጋዊ አባትን አገኙት ችግራቸውን ነገሩት እርሱም "የክርስቶስ ወዳጆች አትዘኑ ወደ ቤተ መቅደስ ስትመለሱ ልጆቻችሁን በሕይወት ታገኛላችሁ" አላቸው ደስ እያላቸውም ተመለሱ።
❤ ዮሐንስም በመስቀል በዓል ሊሳለም መጣ አረጋዊውም ጠርቶ ከአርቃድዮስ ከወንድሙ አገናኘው ተያይዘውም አለቀሱ። ደግሞ አስከናፍርን ከሚስቱ ጋራ ጠርቶ ከልጆቻቸው ጋር አገናኛቸውና በላያቸው ወድቀው እየሳሟቸው አለቀሱ።
❤ ከዚህ በኋላ ከዚያ አረጋዊ ዘንድ የምንኵስና ልብስ ለበሱ ሚስቱን ማርታንም ከሴቶች ገዳም አስገባት አገልጋዮችንም ነፃ አውጥቶ አሰናበተ። ገንዘቡንም ለድኆችና ለችግረኆች በተነ ከገዳምም ገብቶ በጾም በጸሎት ተወሰነ እንዲሁም የተባረኩ ልጆቹ በገድል በትሩፋት የተጠመዱ ሁነው ኖሩ ጌታችንንም ደስ አሰኙት በፍቅር በአንድነት መጋቢት19 ዐረፉ። የቅዱሳን አሰከናፍርና የሚስቱ ማርታ፣ የልጆቹ አርቃድዮስና ዮሐንስ በረከታቸው ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰባቱ_ሰማዕታት፦ እነርሱም የግብጽ ሰው እለእስክንድሮስና እስክንድሮስ፣ ከጋዛ መንደር አጋብዮስ፣ ከቡንጥስ ከተማ ኒሞላስ ከጠራልብስ፣ ዲዮናስዮስ፣ ሮሜሎስና ተላስዮስ ከግብጽ አውራጃዎች የሆኑ ናቸው።
❤ እነርሱም በመንፈሳዊ ፍቅር ጸንተው ስለ ሃይማኖት ምስክሮች ሊሆኑ ተስማሙ። በፍልስጥዔም ውስጥ ወደ አለው ቂሣርያ ደርሰው በመኰንኑ ፊቱ ቆሙ። በከሀዲው ከዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማመናቸውን ገለጡ መኰንኑም በጹኑ ሥቃይ አሠቃይቶ መጋቢት19 ገደላቸው። የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። በረከታቸው ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት 19 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለአርስጦቦሎስ_ዘተፈነወ_ለምሮ። ምስለ ሐዋርያት በጽዮን ውኂዘ መንፈስ ሰኪሮ። ጽሒፎ በእዱ እም አምኀ ማኅበሮ። እንዘ ያስተበፅዕ ወይዌድስ ግብሮ። በውስተ መልእክቱ ዘሮሜ ጳውሎስ ዘከሮ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት_19።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦"ወይርአዩ አሕዛብ በቅድመ አይንቲነ። በቀለ ደሞሙ ለአግብርቲከ ዘተክዕወ። ይባእ ቅድሜከ ገዓሮሙ ለሙቁሓን"። መዝ 78፥10-11። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 16፥3-17፣ 1ኛ ጴጥ 3፥7-15 እና የሐዋ ሥራ 22፥22-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-21። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል።ለሁላችንም ይሁንልን።
ጨረቃንና ፀሐይን በእጃቸው እየያዙ ይጸልዩ ነበር፡፡ በጠገሮ፣ በአዘሎ፣ በፍርኩታና በሌሎቹም ታላላቅ ቦታቦዎች ላይ
በእያንዳንዱ ገዳም ሃምሳ ሃምሳ ዓመት በጸሎት ኖረው በአጠቃላይ በ500 ዓመታቸው ነው ያረፉት፡፡ ዐፅማቸው መንዝ ከአርባ ሐራ መድኃኔዓለም አጠገብ ፍርኩታ ኪዳነ ምሕረት ገዳም ውስጥ ይገኛል፡፡
ከአባታች ከእጨጌ አቡነ ዮሐንስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸውም ይማረን። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን ከሚለው መጽሐፍ።
ተአምኆ ቅዱሳን ወግጻዌ (የቅዱሳን ሰላምታ) Teamho Kidusan Wegtsawe (Yekidusa Selamta):
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፰ (18) ቀን።
❤ እንኳን #ለታላቁ_አባት በፀሐይ ላይ 50 ዓመት፣ በጨረቃ ላይ 50 ዓመት፣ በደመና ላይ 50 እንዲሁም ዓለምን በክንፋቸው በመዞር በደመና ላይ 50 ለኖሩ ከሰው ተወልደው ከመላእክት ለተደመሩ ጻድቅ #ለእጨጌ_እጨ_አቡነ_ዮሐንስ_ዘጠገሮ_ለፍልሰተ አጽማቸው በዐል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #እጨጌ_እጨ_አቡነ_ዮሐንስ_ዘጠገሮ፦ ጻድቁ አባታችን የተወለዱት በኢየሩሳሌም አውራጃ ልዩ ስሙ ሳሬራ በሚባል ቦታ ነው፡፡ የካቲት 28 ቀን ተፀንሰው ህዳር 29 ተወለዱ፡፡ አባታቸው ድላሶር እናታቸው እምነ ጽዮን ይባላሉ፡፡ ሲወለዱ በወላጆቻቸው ቤት ውስጥ ብርሃን ወርዷል፡፡ ወላጆቻቸውም እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ አባታችን ገና በተወለዱ በ5 ዓመታቸው ወላጆቻቸው ወደ እግዚአብሔር ቤት ይዘዋቸው የእመቤታችንን ሥዕል ተመልክተው በደስታ ተመልተው ሳቁ፡፡ አምላክን የወለደች የብርሃን እናቱ እመቤታችንም ከምሥሉ ወጥታ "በምን አውቀኸኝ ነው?" ብላ አቅፋ ሳመችውና "ከእንግዲ ወዲህ የልጄ አገልጋይ ትሆናለህ ኑሮህም እንደ መላእክት ይሆናል በአንተ ምክንያት ብዙ ሰዎች ይድናሉ በምድር ላይም 500 ዓመት ትኖራለህ…" ብላ ባርካው ተሰወረች፡፡
❤ ከዚያችም ቀን ጀምሮ አባ ዩሐንስ ለክርስቶስ ተላልፎ ተሰጠ፡፡ 50 ዓመትም በበረሃ ሲጋደል ኖሮ ከ50 ዓመት በኋላ በደመና ተጭኖ በመልአኩ በቅዱስ ገብርኤል መሪነት ወደ ቅድስት ሀገር ኢትዮጵያ መጡ፡፡ ጻድቁ አባታችን በአቡነ ተክለሃይማኖት ዘመን መጨረሻ የመጡ ሲሆን ምንኵስና ከደብረ ሊባኖስ ገዳም ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ተቀብለው በዚያው በድብረ ሊባኖስ ገዳም ለ50 ዓመት በጾምና በጸሎት በተጋድሎ ኖዋል፡፡ ከዚኽም በኋላ አባ ዮሐንስ ወደ ተዘጋጀላቸው ምድር በቅዱስ ገብርኤል አሳሳቢነት ወደ ጠገሮ መጡ፡፡ ይኽም ጠገሮ ያለው ገዳማቸው በሰሜን ሸዋ በመንዝና ይፋት ክልል መዘዞ በሚባል ቦታ ሲደርሱ በእግር አንድ ሰዓት ከተጓዙ በኃላ ይገኛል፡፡
❤ ሕዝቡ በተለምዶ እጨ ዮሐንስ እያለ ይጠራቸዋል እንጂ ስማቸው እጨጌ ዮሐንስ ነው፡፡ አቡነ እጨጌ ዮሐንስ መስቀል ከሰማይ የወረደላቸው ታላቅ አባት ናቸው፡፡ መስቀሉም ሁልጊዜ ተአምር ይሠራል፡፡ በልደታቸው ቀን ኅዳር 29 ቀን መስቀሉ ከመቅደሱ ወጥቶ በካህናቱ ታጅቦ ወደ ጸበሉ ሲወርድ ከየት እንደመጣ ሳይታሰብ ደመና መጥቶ ከመስቀሉ ላይ ብቻ እረቦና እንደ ጃንጥላ ተዘርግቶ አብሮ ወደ ጸበሉ ይወርዳል፡፡ እዛው ቆይቶ መስቀሉ ሲመለስም አብሮ አጅቦ ይመለስና መስቀሉ ቤተ መቅደስ ውስጥ ሲገባ ደመናው ወዴት እንደተበተነ ሳይታወቅ ይጠፋል፡፡ ይህ በዘመናችንም ጭምር እየታየ ያለ ታላቅ ተአምር ነው፡፡
❤ አባታችን በታላቀ ተጋድሎ ሣሉ ሰይጣን የሀገሩን ሰዎች በጠላትነት እንዲነሡባቸው አደረገ፡፡ ሰዎቹም አባታችንን እንዴት እንደሚያጠፏቸው ይማከሩ ጀመር፡፡ ሊገድሏቸው ፈልገው ቅድስናቸው በሁሉ ዘንድ የታወቀ ነውና ፈሩ፡፡ ከዚህም በኋላ "ለምን ከመንደራችን ከወንድ ያረገዘች ሴት ፈልገን እሳቸው አስረገዟት ብለን በሐሰት እንከሳቸው?" ብለው ተማከሩ፡፡ ብዙ ወርቅና ብርም ለአንዲት ሴት ሰጥተው በሐሰት ከእርሱ አርግዣለሁ ብላ እንድትመሰክር አደረጓት፡፡ አባታችንም በሕዝብ ፊት በሐሰት ተከሰሱ፡፡ ጻድቁም "አንቺ ሴት ከእኔ ነው ያረገሽው?" አሏት እርሷም "አዎ ከአንተ ነው ልትክድ ነው እንዴ?" አለቻቸው፡፡ አባታችንም በዚህ አዝነው "በአንቺና በእኔ መካከል እግዚአብሔር ይፍረድ" ሲሉ ያች ሴት ወዲያው ለሁለት ተሰንጥቃ ሞተች፡፡ የአገሩ ሰዎችም እጅግ ፈሩ፡፡ አባታችንም ምድሪቱን እረገሟት፡፡ "የተዘራው ዘር አይብቀልብሽ፣ የተተከለው አይፅደቅ፣ ብርድና ውርጭ ይፈራረቅብሽ" ብለው እረግመዋት በደመና ተጭነው ወደ ሰሜን ጎንደር እስቴ ጉንደ ተክለተሃማኖት ሔዱ፡፡
❤ አቡነ ዮሐንስ በመላው ኢትዮጵያ ወንጌልን እየተዘዋወሩ ያስተማሩ ሲሆን ከቅድስናቸው የተነሣ በፀሐይ ላይ 50 ዓመት፣ በጨረቃ ላይ 50 ዓመት፣ በደመና ላይ 50 እንዲሁም ዓለምን በክንፋቸው በመዞር በደመና ላይ 50 የኖሩ ከሰው ተወልደው ከመላእክት የተደመሩ ታላቅ ጻድቅ ናቸው፡፡ በይፋት ጠግሮ በዓለወልድ፣ በአፋር አዘሎ፣ በመንዝ ፍርኩታ ኪዳነምሕረት፣ በደብረ ሊባኖስ፣ በጎንድ ተክለ ሃይማኖት በሌሎችም ቦታዎች በመዘዋወር በታላቅ ተጋድሎ ኖረዋል፡፡
❤ አባታችን ከሰማይ መስቀል የወረደላቸው ሲሆን ዛሬም በገዳማቸው የሔደ ሰው በወረደው በእጃቸው መስቀል እየተዳበሰ ቆመው በጸለዩበት ባሕር በጠበላቸው ይጠመቃል፡፡ በተጨማሪም ይይዙት በነበረውም መቋሚያቸው በመዳበስ በረከትን ማግኘት ይቻላል፡፡ ቆመው ከጸለዩበት ባሕር ውስጥ ደረቅ አሸዋ ይወጣል፡፡ አባ ዮሐንስ 500 ዓመት ከኖሩ በኋላ ዕረፍተ ዘመናቸው ሲደርስ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከ15 ነቢያት፣ ከ12 ሐዋርያት፣ ሄሮድስ ያስፈጃቸው ከመቶ አርባ አራት ሺ ሕፃናት፣ ከአብርሃም ከይስሐቅ፣ ከዕቆብ ጋር ሁሉንም ነገደ መላእክትን፣ ጻድቃን ሰማዕታትን ሁሉ አስከትሎ መጥቶ ታላቅ ቃልኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ "ስምህን የጠራ ገዳምህን የረገጠ፣ መባ የሰጠ፣ ቤተ ክርስትያንህን የሠራ ያሠራ የረዳ፣ ገድልህን የሰማ ያሰማ ያስተረጎመ፣ መታሰቢያን ያደረገ እስከ 10 ትውልድ እምርልሀለው፤ ንስሀ ሳይገባ አይሞትም፣ ልጅ መውለድ ባይችል እኔ ልጅ እሰጠዋለሁ፤ ገድልህን በቤትህ ያስቀመጠ እርኩስ መንፈስ፣ ክፉ አጋንንት ቸነፈር ወባ መልአከ ጽልመት አይነካውም፡፡ በገዳምህ መነኵሴ ቢቀበር በሰማይ ክንፍ አበቅልለታለሁ፤ አይሁድም አረማዊም ያላመነ ያልተጠመቀ በገዳምህ መጥቶ ቢያርፍ ይቅር እልልሃለሁ፣ እንደ መቃብሬ ጉልጎታ እንደተቀበረ አድርጌ እቆጥርልሃለሁ…" የሚል ቃል ኪዳን ከሰጣቸው በኋላ ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡
❤ ቅዱስ አባታችንም በ 500 ዓመታቸው ሐምሌ 29 ቀን ዐርፈው በጎንድ ተክለ ሃይማኖት ተቀብረዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር የሚገኘውን ይህንን ገዳም ጻድቁ ራሳቸው ናቸው የመሠረቱት፡፡ ነገር ግን የገዳሙን ስያሜ በአባታቸው በአቡነ ተክለ ሃይማኖት ስም አድርገውታል፡፡ አቡነ ዮሐንስ ካረፉ በኋላ በእርግማናቸው መሠረት በመንዝና በይፋት ብርዱ ድርቁ ስለበዛባቸው አንድ ብቁ ባሕታዊ ከበዓታቸው ወጥተው "በሐሜታችሁ ምክንያት እጨ ዮሐንስ ስለረገማችሁ ነው የእርሱን ዐፅም ካላመጣችሁ ብርዱ ውርጩ ድርቁም አይጠፋላችሁም" አሏቸው፡፡ ሕዝቡም አባታችን በጉንድ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከተቀበሩ ከ 134 ዓመት በኋላ በቅዱሳን እየተመሩ ሄደው በሌሊት ግማሽ ዐፅማቸውን አምጥተው በሀገራቸው አምጥተው ስላስቀመጡ ብርዱና ውርጩ በመንዝ እየቀነሰላቸው መጥቷል፡፡
❤ ዛሬም በሀገሩ ብርዱና ውርጭ ሲበዛ የጻድቁን ታቦት ሲያወጡ ውርጩ ይጠፋል፡፡ ጠገሮ በሚባለው ገዳማቸው ውስጥ የሚገኘው ጠበላቸው እጅግ አስደናቂ ነው፡፡ ግማሽ ዐፅማቸውን ከጉንደ ተክለሃይማኖት አምጥተው አርባ ሐራ መድኃኔዓለም አጠገብ በላይ በፍሩክታ ኪዳነምሕረት መጋቢት 18 ፍልሰተ ዐፅማቸው ተከናወነ፡፡ ምድሪቷም ተባረከች፣ የዘሩትንም አበቀለች፣ ውርጩም ብርዱም ቀነሰ፣ ዝናብ አልዘንብ ሲል ወይም ሰብል የሚጨርስ አንበጣ ሲመጣ ታቦታቸው ወጥቶ ምህላ ይያዛል ወድያውም መቅሰፍት ይርቃል፣ ዝናብም ይዘንባል፡፡ ጻድቁ ደመናን፣
Repost from ማኅበረ ቅዱሳን ( Mahibere Kidusan )
+6
11ኛው ዙር ሐዊረ ሕይወት ወደ ቦንባስ ፍ/ሰ/ቅ/ ማርያም ቤ/ክ መካሄዱን ማኅበረ ቅዱሳን የጅግጅጋ ማእከል አስታወቀ ።
መጋቢት ፲፭/፳፻፲፯ ዓ.ም
ማኅበረ ቅዱሳን የጅግጅጋ ወረዳ ማእከል ከማእከሉ ጋር በመተባበር በሀገረ ስብከቱ ለ11ኛ ጊዜ የተዘጋጀውን ሐዊረ ሕይወት ወደ ቦንባስ ፍ/ሰ/ቅ ማርያም ቤተ ክርስቲያን መጋቢት 14/2017 ዓ.ም አካሂዷል።
በመርሐ ግብሩ የሶማሌ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅና የማእከሉ የሐዊረ ሕይወት አምባሳደር ክቡር ሊቀ ካህናት ቀሲስ ኢዮብ ወንድሙ ፣ የር/አ/ወገ/ደ/መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል ቤ/ክ አስተዳዳሪ ቀሲስ ኢ/ር ዮሐንስ ንጋቱ፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እና በርካታ የሐዊረ ሕይወት ቤተሰቦች ተሳትፈዋል ።
በዕለቱም ትምህርተ ወንጌል እና ምክረ አበው በተጋበዙት መምህራን መጋቤ ብርሃናት ቀሲስ ሙሉቀን ብርሃኑ እና የኔታ ዳንኤል ብርሃኑ የተሰጠ ሲሆን የዝማሬ አገልግሎትም በጅግጅጋ ማእከል የመዝሙር ክፍል አባላት ቀርቧል።
በተጨማሪም ተጓዥ ምእመናንም ደብሩ እያከናወነ ለሚገኘው የልማት እንቅስቃሴ እገዛ ይሆን ዘንድ የገንዘብ ድጋፍ አድረገው መርሐ ግብሩ በሰላም በስኬት ተጠናቋል።
✝ ✝ ✝
❤ #አናጒንስጢስ_ቅዱስ_ቴዎቅሪጦስ፦ ይህም ቅዱስ የሮሜ አገር ሰው ነው። ዐላውያንም ለጣዖት እንዲሠዉ ክርስቲያኖችን ይዘው በአስገደዷቸው ጊዜ ከእርሱ ጋር ያዙት ወደ ንጉሥም አቀረቡት ያንጊዜ የዐሥራ አምስት ዓመት ልጅ ነበር።
❤ ንጉሥም "በማመጣብህ ሥቃይ ትፈተናለህን ወይስ ለአማልክት ትሠዋለህ" አለው። ቅዱስ ቴዎቅሪጦስም እኔስ ለክብር ባለቤት ለጌታዬ ለፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እሠዋለሁ" አለው። ንጉሡም "ቴዎቅሪጦስ ሆይ በክፉ አሟሟት እንዳትሞት ለአማልክት መሥዋዕት አቅርብ" አለው። እርሱም "ንጉሥ ሆይ መሥዋዕቴን እንድታይ ና" አለው ንጉሡም ወደ ጣዖቱ ቤት እንዲወስዱትና በዚያ እንዲሠዋ አዘዘና እርሱም በበር ቆመ። ቅዱሱም በጸለየ ጊዜ ንውጽውታ ሁኖ አጽቀላጽዮስ የሚሉት አምላካቸው ተሰበረ። ንጉሡም እንደ ዘበተበት አይቶ አፍንጫውን ቆርጠው አሥረው በወህኒ ቤት እንዲያስገቡት አዘዘ። በማግሥቱም አውጥተው በብረት ምጣዶች ውስጥ ጨመሩት ደግመው ጥልቅ ጉድጓድ ቆፈሩ በውስጡም እንጨት ረብርበው ሥጋው ከመለያያው እስቲቦጫጨቅና ቅልጥሙም ከአጥንቶቹ እስቲፈስ ድረስ ወረወሩት። በዚህም ሊያጠቁት አልቻሉም የመንፈስ ቅዱስ ኃይል ከእርሱ ጋር አለና።
❤ ከዚህ በኋላም አማልክቶቻቸው የሚበቀሉት መስሏቸው ከአማልክቶቻቸው ቤት አስገብተው በዚያ ዘጉበት ቅዱስ ቴዎቅሪጦስ ግን ከጣዖታቱ ላይ ያለውን ወርቅ ቀጥቅጦ በሥውር ይዞ እየወጣ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች መጸወተው። ተመልሶ ሲገባም በደጃፉ እንደ ቀድሞው ራሱ ይዘጋል።
❤ በስምንተኛውም ቀን ንጉሥ መጣ5 ከደጃፍም ሁኖ አየ አማልክቶቹም ተጥለው ተሰባብረው የከበረ ቅዱስ ቴዎቅሪጦስ ሲዘብትባቸው አገኛቸው። እውነተኛ ቅዱስ ቴዎቅሪጦስንም የሆድ ዕቃው እስኪታይ እንዲሰነጣጥቁት አዘዘ። ደግመው ወደ ጨዋታ ቦታ እንዲያስገቡትና በላዩ አንበሶችን እንዲያስገቧቸው አዘዘ። አንበሶችም ቁስሎቹን ላሱለት። ዳግመኛም ሕዋሳቱ ከሚያጣብቅ ቦታ እንዲያስገቡት መላ አካላቱም ታጥፎ እስቲቆለመም እንዲያሠቃዩት አዘዘ። በዚህም ተሽብሮ አላሸነፉትም ንጉሡም ብርታቱን አይቶ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡት አዘዘ።
❤ የከበረ ኤጲስቆጶስ ኤሞሬዎስና ሕዝቡ ሁሉ በጸሎት እየተራዱት ቅዱስ ቴዎቅሪጦስን ተከተሉት በቅዱሳን ሰላምታ ተሳልመውት ተሰናበቱት ባለወግ ወታደርም ሰይፉን አንሥቶ መጋቢት17 አንገቱን ቆረጠው ምስክርነቱንም ፈጸመ። የአናጒንስጢስ ቅዱስ ቴዎቅሪጦስ አማላጅነቱ በረከቱም ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት17 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለጊዮርጊስ_ወተላስስ_ዳግማዊ። ወኤጲስቆጶስ ዮሴፍ ዘመርዔተ ክርስቶስ ኖላዊ። ጸዋዕኩክሙ ትርድኡኒ እምሥገርተ አርዌ ነዓዊ። ወትፈውሱኒ በጸሎትክሙ ማሕየዊ። እስመ ቀሳውስተ ይጼውዕ ዘይደዊ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት_17።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወሰምዐኒ እምደብረ መቅደሱ። አንሰ ሰከብኩ ወኖምኩ። ወተንሣእኩ እስመ እግዚአብሔር አንሥአኒ"። መዝ 3፥4-5። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 15፥14-ፍ.ም፣ ያዕ 5፥14-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 2፥22-25። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 11፥1-17። የሚቀደሰው ቅዳሴ ቅዳሴ እግዚእነ ነው። መልካም የጾም ወራትና በዓል። በሁላችንም ይሁንልን።
ተአምኆ ቅዱሳን ወግጻዌ (የቅዱሳን ሰላምታ) Teamho Kidusan Wegtsawe (Yekidusa Selamta):
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፯ (17) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊ_ጻድቅ ከመቃብራቸው እስከ አሁን ድረስ ለበሽተኞች የሚሆን #ፈዋሽ_ቅባ_ቅዱስ_ለሚያፈልቁት ኤርትራ አገር የሚገኙ አምስት ታላላቅ ገዳማትን ለመሰረቱ #ለታላቁ_አባት_ለአቡነ_ዮናስ ለዕረፍት በዓል መታሰቢያ ቀን እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ዮናስ፦ ከአባታቸው ንዋየ እግዚእ ከእናቻው ሂሩተ ማርያም ሕዳር 17 በ1357ዓ.ም በጉናጉና ቤተ መስቀል ተወለዱ ስመ ክርስትናቸው ሀብተ እግዚእ ተባሉ። ሀብተ እግዚእ ገና ልጅ እያሉ የበጎች እረኛ ሆነው እየጠበቁ ሳለ መንፈስ ቅዱስ መልአኩን ልኮ 70 መዝሙረ ዳዊት አስተማራቸው ፍላጎታቸውም ወደ መንፈሳዊ ትምህርት እና ምናኔ ነበር። ከዛም ከተወለዱበት ቦታ ተነስተው ወደ ደብረ ሲና የምትባል ገዳም ሄዱ ከዛ የእናታቸው የሥጋ ወንድም አጎታቸውን አገኙ። አቡነ ዲያምኖስ የሚባሉ በጣም ትልቅ ባለጸጋ አባት አገኙ ከዛም በኋላ የመጡበትን ምንክንያት ለምናኔ መሆኑን ካወቁ በኋላ ሐዲስ ኪዳን እና ብሉይ ኪዳን እና ስርዓተ ምንኩስናን ከተማሩዋቸው በኋላ በ14 ዓመታቸው በ371ዓ.ም ስርዓተ ምንኲስናን ተቀበሉ የምንኲስናቸውም ስም አቡነ ዮናስ ተባሉ። ዮናስ ማለት የዋህ ልክ እንደ ርግብ ማለት ነው። ባሕር ውስጥ ገብተው እየጸለዩ በቀን 5 የዛፍ ፍሬ ዋርካ ወይም 5 ፍሬ እየተመገቡ በከባድ ጾምና በጸሎት በመንፈስዊ ተጋድሎ ይኖሩ ነበር።
❤ አቡነ ዮናስ ያደረጉት ተአምር።
1. ሶስት ሙታን አስነስትዋል።
2. ከኤርትራ በደመና ተጭነው ወደ ኢሩሳሌም ሄደው ቀድሰው ወደ ደብረ ጽጌ ገዳም ተመልሰው መክፈልት ይቀምሱ ነበር።
3. ዕረፍታቸው ቀን ሲደርስ በ5ቱ ገዳም የሚገኙ ልጆቻቸው ሰብስበው እኔ የዕረፍቴ ቀን እየደረሰ ነው ከእኔ በኋላ ልክ እንደእኔ አባት የሚኖናችሁ አባ ጳውሎስ ናቸው። እና ለእርሳቸው ልክ እንደ እኔ ታዘዙ አሏቸው። ልጆቻቸውም ይህን ሲሰሙ በጣም አዘኑ መጋቢት 17 ቀን 1452 በ92 ዓመታቸው በዐቢይ ጾም ውስጥ ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ። የዕረፍት በዓላቸው የሚከበረው ግን ጥር21 ቀን ነው። ልጆቻቸውም ከሀዘን ብዛት የተነሳ በትንሣኤ ቀን ምንም ሳያደርጉ ዝም አሉ። ከዚያም አቡነ ዮናስ ተገልጸው "ልጆቼ ከእኔ ሀዘን የጌታዬ ትንሣኤ ይበልጣል። እና አሁን ትንሣኤውን አድርጉ" አሏቸው ልጆቻቸውም ደግሞ "እኛ ምንም ነገር የለንም እና እንዴት እናደርግ" አሉ ጻድቁ አቡነ ዮናስ "ሦስት አጋዘኖች ወደ እናንተ ይመጣሉ እና እነርሱን አርዳችሁ በዓሉን አሳልፉ እንቢ ቢሏችሁ እንኳን በአቡነ ዮናስ ስም ገዝቷቸው" አሉ። ከዛ ጻድቂ እንዳሉ ሦስት አጋዘኖች መጡ ሁለቱ ታረዱ አንዱ ደግሞ ሊሮጥ ብሎ "በጻድቁ አቡነ ዮናስ ስም ቁም" ብለው ሲገስጹት ቆመ።
4 ጻድቁ አቡነ ዮናስ ካረፉ በኋላ በአምስቱም ገዳማት ዘይት ፈልቋል። በአሁን ጊዜ ግን በመቃብራቸው ብቻ ነው የሚገኘው።
5 ጻድቁ አቡነ ዮናስ የአምስቱ ገዳማት አባት ናቸው። 1.ደብረ ጽጌ 2.ደብረ ድሁሃን 3.ደብረ ሳህል 4.ደብረ ጽዮን 5.ደብረ ጸሪቅ በኢትዮጵያና በኤርትራ አገር ውስጥ ይገኛል።
6. ጻድቁ ባህር ውስጥ ገብተው ሲጸልይ እጃቸውም ልክ እንደ ጸሐይ ያበራ ነበር።
❤ #ቃል_ኪዳናቸው፦ በዚህ ከባድ መንፈሳዊ ተጋድሎአቸው ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ከቅዱሳን መላእክት ጋር ወርደው ለአባታችን አቡነ ዮናስ እንደዚህ የሚል ትልቅ ቃልኪዳን ገባላቸው "ወዳጄ ዮናስ ሆይ ጾምህንና ጸሎትህን ተቀብዬልሀለው ከአሁን በኋላ ገድልህን የሰማ፣ ያሰማ፣ ያነበበ አስኬማህንና ቆብህን በስምህ የተቀበለ የ135 ሺ ከእናንተ ጋር የሚነግሱ ዓስራት አድርጌ ሰጥቼሀለው፤ በስምህ እና በጸሎትህ የተማጸነ ያለ ቁጥር እንደ ክረምት ዝናብ ምሬልሀለሁ ዝክርህን የዘከረ መጽሐፍ ገድልህን የጻፈ ያጻፈ፣ ለገዳሙ ዘቢብ፣ ዕጣን ፣ ስንዴ፣ ጧፍ፣ ሻማ፣ ንዋየ ቅድሳት የሰጠ፣ ገዳሙን ያነፀ፣ በስምህ የተማጸነ፣ ገዳምህን የረገጠ፣ እንደነጭ ሀር አነጻዋለሁ። ኃጢያቱ ልክ እንደ ቁራ ቢጠቁርም እንደነጭ በረዶ አነጸዋለሁ ብሎ ትልቅ ቃልኪዳን ሰጣቸው። ከአባታች አቡነ ዮናስ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን። በጸሎታቸውም ይማረን። ምንጭ፦ ገዳሙ ካሳተመው ከአቡነ ዮናስ ስዕል ጀርባ የተወሰደ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፯ (17) ቀን።
❤ እንኳን #ጌታችን_አምላካችን_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ይወደው ለነበረው #ለቅዱስ_አልዓዛር ጌታችን ከሞት ከማስነሳቱ በፊት መጀመርያ ለዐረፈበት መታሰቢያ ቀንና #ለአጒንስጢስ_ለቅዱስ_ቴዎቅሪጦስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከታጋዩ #ከቅዱስ_ጊዮርጊስና ከሰማዕቱ #ከቅዱስ_ተላስስ፣ #ከኤጲስቆጶስ_ዮሴፍ ከመታሰቢያቸውና #ከሊቀ_ካህናት_ኒቆር ከሥጋው ፍልሰት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ጌታችን_ቅዱስ_አልዓዛር_ከሙት_እንዳስነሳው፦ ይህም ጻድቅ ሰው ከእስራኤል ልጆች ውስጥ ነው። ማርያምና የተባሉ ሁለት እኅቶች አሉት። ማርያም የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሽቱ የቀባችው ናት። እርሱም በጌታ ደቀመዛሙርቶቹ ናቸው ስለ ምግባራቸውም ጌታችን ይወዳቸዋል ሁሉም ያላገቡ ደናግል ናቸው።
❤ ለሰው ወገን ሁሉ ላይ የተቆረጠውና የተወሰነው ሰዎችም ሊጠጡት ያላቸው የሞት ጽዋን እጁን ለሞት የሚሰጥበት ለዚህ ጻድቅ ጊዜው ሲደርስ እርሱም እጁን በመስጠት ዐረፈ።
❤ የክብር ባለቤት ጌታችን ግን የሚሠራውን ያውቃልና መጀመሪያ ከሞት አላዳነውም ጠርቶ እስከሚያስነሳው ድረስ ሙቶ በመቃብር አራት ቀን እንዲኖር በዚህ በአራት ቀንም የጻድቃንን ማደሪያዎችንና የኃጥአንን የሥቃይ ቦታዎች እንዲያይ ተወው እንጂ አላዳነው ያን ጊዜም ታላቅ ምልክት ትሆናለች።
❤ ከአራት ቀኖችም በኋላ የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ እርሱ መጥቶ "አልዓዛር አልዓዛር ና ውጣ" ብሎ ከመቃብር ውስጥ ጠራው ያን ጊዜ እጆቹና እግሮቹ እንደታሠሩ ሙታኖችንም እንደሚጠቀልሏቸው በሰብን ፊቱ ተጠቅልሎ ወጣ። እጆቹና እግሮቹ እንደ ተጠቀለሉና እንደ ታሠሩ ከመቃብር የመውጣቱ ምክንያት ሰዎች ሁሉ መሞቱን እንዲረዱ ሌሎችም ይህ በመካከላቸው በስምምነት የሆነ ነው ብለው እንዳያስቡ። ስለዚህም እንደ ገነዙት ሁኖ እንዲወጣ ጌታችን አዘዘው ይችም ምልክት እንድትሆን። ከሀዲዎችም በመቃብር ውስጥ ሕያው እንደነበር ቢያስቡም እጆቹና እግሮቹ ፊቱም እንደ ተጠቀለሉ እንዴት ይወጣ ነበር እኛ የክርስቲያን ወገኖች ግን የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ ከአራት ቀኖች በኋላ አልዓዛርን ያስነሳው እርሱ እንደሆነ እናምናለን እንታመናለንም እርሱ በሥራው ሁሉ ላይ ችሎታ አለውና።
❤ ለጌታችንና ለፈጣሪያችን ለመድኃኒታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ ከቸር አባቱና ሕይወት ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ክብር ስግደት ይሁን ለዘላለሙ አሜን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት፲፮ (16) ቀን።
❤ እንኳን #ለእስክንድርያ_አርባ_ሰባተኛ ሊቀ ጳጳሳት በተሾሙ ጊዜ ለሦስት ቀናት ስለ ቅድስናቸው እግዚአብሔር ዝናብን ላዘነበላቸው፤ በግብፅ አገር አሕዛብ በእሥራትና በስደት ብዙ ላሠቃዩአቸውና #የኢትዮጵያው_ንጉሥ_ሦስት_መቶ_ሺህ_ሠራዊት አዝምቶ ከዚህ ሥቃያቸው ታድጎ ነፃ ላወጣቸው ለከበሩ አባት #ለአባ_ሚካኤል ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ሚካኤል፦ ይህም አባት በእስክንድርያ ከተሾሙ አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት አርባ ሰባተኛ ነው፡፡ በአስቄጥስ በአባ መቃርስ ገዳም መንኰሶ ኖረ ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎድሮስ በዐረፈ ጊዜ በላዩ የትንቢት መንፈስ ያደረበት አንድ ጻድቅ ሰው እስከ ሚያስረዳቸው ድረስ ለዚች ሹመት ስለሚሻል ሲመክሩና ሲመረምሩ ብዙ ቀኖች ኖሩ።
❤ ከዚህም በኋላ ያ ሰው እኔ በአባ መቃርስ ገዳም በነበርኩ ጊዜ ስጸልይ "የሊቀ ጵጵስና ሹመት ለሚካኤል ይገባዋል ለዚች ሹመት የሚሻል እሱ ነውና የሚል ቃልን ከሰማይ ሰማሁ" አላቸው። ሁሉም ስለ ትሩፋቱ ተናገሩ ስለ እርሱም ተስማምተው ከገዳሙ ወደ እስክንድርያ ሊያመጡት ከምስር ገዥ ዘንድ ደብዳቤ አጽፈው ያዙ። ሊያመጡትም ሲሔዱ ስለ ገዳሙ አገልግሎት ከሽማግሌዎች መነኰሳት ጋራ ወደ ጋዛ ከተማ ሲመጣ በመንገድ አገኙት ይዘውም አሠሩት። ወስደውም በመስከረም17 ሊቀ ጵጵስና ሾሙት ያቺም ዕለት በጌታ ደም የከበረ መስቀል በዓሉ የሚከበርባት ናት።
❤ ይህም የሆነው ከዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በኋላ የሐሚድ ልጅ እልሲድ በሚገዛበት ዘመን ነው። በሹመቱ ወራትም መርዋን አልጋዲን ነገሠ። የእስክንድርያም አገር ሰዎች ከጥቂት ካፊያ በቀር ብዙ ዝናብ ሳይዘንብላቸው ብዙ ዓመታት ኖሩ። በዚች እርሱ በተሾመባት ቀን በሁለተኛውም በሦስተኛውም ብዙ ዝናብ ዘንቦላቸው እጅግ ደስ አላቸው።
❤ በዚህም አባት ዘመን በክርስቲያን ወገኖች ላይ ታላቅ መከራ ደረሰ ከምዕመናንም ብዙዎች ሸሹ የክብር ባለቤት ክርስቶስም የካዱት ሰዎች ቁጥራቸው ሃያ አራት ሺህ ሆነ። ለዚህለመለካውያን ነገር ምክንያት የሆነውን ከእርሱ እግዚአብሔር እስከአጠፋው ድረስ ይህ አባት ስለዚህ በታላቅ ኀዘን ውስጥ ነበር።
❤ ዳግመኛም በዚህ አባት ዘመን ቆዝሞስ ሊቀ ጵጵስና ተሹሞ ሳለ የክብር ባለቤት ስለሆነ ስለ ክርስቶስ ተዋሕዶ ከዚህ አባት ከአባ ሚካኤል ጋራ ተከራክሮ ይህ አባት አባ ሚካኤል እንዳስረዳው አመነ። እንዲህም ብሎ በእጁ ጻፈ "የክብር ባለቤት ክርሰቶስ በተዋሕዶ በኋላ ሊቀ ጳጳሳት ቄርሎስ እንደተናገረ የመለኮቱና የትስብእቱ አንድ ባሕርይ በመሆን ጸንቶ ይኖራል ሲል ኤጲስቆጶሳቱም እንዲሁ ከተዋሕዶ በኋላ ክርስቶስ የተለያዩ ሁለት ባሕርያት ሁለት ገጻት አሉት ይሉ ዘንድ የሚገባ አይደለም" ሲሉ ጻፈ። ሐዋርያትም በሰበሰቧት በከበረች በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በአንድነት ጸንተው ሊኖሩ ተስማሙ።
❤ ከዚህም በኋላ ከእስክንድርያ ሰዎች መለካዊ የሆነ ስሙ አንስጣስዮስ የሚባል ሰው በላያቸው ጥፋትን አመጣ እርሱ ኤጲስቆጶስነት እንዲሾሙት ሽቶ አልሾሙትምና። ስለዚህ ወደ እስላሞች ንጉሥ ሒዶ በአባ ሚካኤል ነገር ሠራበት ከዐመፀኞች የነገሥታትም ብዙ መከራ ደረሰበት ጽኑዕ የሆነ ሥቃይም አሠቃዩት ብዙ ግርፈትም ገርፈው ለረጂም ጊዜ በእግር ብረት አሠሩት። አንገቱንም በሰይፍ ሊቆርጡ ወደ መኰንኑ አቅርበውት ነበር ስለ መንጋዎቹም ጥበቃ እግዚአብሔር አዳነው።
❤ ዳግመኛም በመዋርዋን አልጋዲ ዘመነ መንግሥት የሙሴ ልጅ በሆነ በንጉሥ አገልጋይ አደባባይ ታላቅ ሥቃይ አሠቃዩት፡፡መኰንኑም ገንዘብ እንዲሰጠው ሽቶ ሊቀ ጳጳሳቱን አባ ሚካኤል አሠረው ሰዎች መጥተው ዋስ ሁነው አወጡት። ምጽዋትም ጠይቆ ለመኰንኑ ብዙ ገንዘብ አምጥቶ እንዲሰጠው ወደ ላይኛው ግብጽ ወሰዱት። ይህ አባትም ወደ ላይኛው ግብጽ በሔደ ጊዜ በዚያ ብዙ ተአምራትን አድርጎ የክብር ባለቤት ክርስቶስ የካዱትን ምዕመናን ብዙዎቹን ወደቀናች ሃይማኖት መልሶ አስገባቸው።
❤ የኢትዮጵያ ንጉሥም ይህን አባት የእስላሞች መኳንንት እንዳሠቃዩት በሰማ ጊዜ ፍጹም ኀዘንንም አዘነ። መንፈሳዊ ቅናትንም ቀንቶ ወደ ግብጽ አገር ዘምቶ ከላይኛው ግብጽ ደረሰ። ከርሱ ጋርም መቶ ሺህ ፈረሰኞች አርበኞች፣ መቶ ሺህ በበቅሎ የተቀመጡ አሁንም በግመል የተቀመጡ መቶ ሺህ አርበኞች ነበሩ ብዙ አገሮችንም አጠፋ ብዙዎችንም ማረካቸው።
❤ የግብፁ ንጉሥም ይህ ሁሉ የሆነው ስለ ሊቀ ጳጳሳቱ ስለ አባ ሚካኤል እንደሆነ ዐውቆ ከእስራቱ ፈታው፡፡ ታላቅ ክብርንም አከበረው፡፡ የክርስቲያንን ወገኖች ሁሉ እጅግ አከባረቸው። ከዚህም በኋላ ለኢትዮጵያ ንጉሥ ደብዳቤ ጽፎ ይልክ ዘንድ ወደ አገሩም እንዲመለስ ያዝዘው ዘንድ የግብጽ ንጉሥ ይህን አባት አባ ሚካኤል ለመነው።
❤ ይህም አባት ወደ ኢትዮጵያ ንጉሥ እርሱንና መኳንንቱን መሳፍንቱንና ሠራዊቱን እየባረከና እየመረቀ ደብዳቤ ጽፎ ላከ። እንዲህም አለው "እንሆ በአንተ ምክንያት ከአሥራትና ከሥቃይ ሁሉ እግዚአብሔር አድኖናልና አሁን ወደ አገርህ በሰላም በፍቅር ተመለስ ስለ እኔና ስለ ክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ስለ ደከምክ መልካም ዋጋ እግዚአብሔር በመንግሥተ ሰማያት ይስጥህ"። የኢትዮጵያ ንጉሥም የዚህን አባት የሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤልን ደብዳቤ በአነበበ ጊዜ ፈጥኖ ተነሥቶ ወደ አገሩ በሰላም በፍቅር አንድነት ተመለሰ።
❤ አባ ቆዝሞስና ወገኖቹም ከሊቀ ጳጳሳት አባ ሚካኤል ጋር በተስማሙ ጊዜ አባ ቆዝሞስ በውዴታው ለምስር ኤጲስቆጶስ ሁኖ ተሹሞ ከዚህ አባት ከአባ ሚካኤል ሥልጣን በታች ሆነ።
❤ ይህም አባት መልካም ተጋድሎውን በፈጸመ ጊዜ ወደ ወደደው እግዚአብሔር መጋቢት16 ሔደ። የአባ ሚካኤል አማልጅነቱ በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ይሁን አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት16 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ዝርዎሙ ለአሕዛብ እለ ይፈቅዱ ቀተለ። ይምጽኡ ተናብልት እምግብፅ። ኢትዮጵያ ታበጽሕ እደዊሃ ኀበ እግዚአብሔር"። መዝ 67፥30-31። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ጢሞ 4፥1-ፍ.ም፣ 2ኛ ጴጥ 1፥12-19 እና የሐዋ ሥራ 11፥23-27። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 14፥28-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታችን የማርያም ወይም የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ወራትና በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፭ (15) ቀን።
❤ እንኳን #ለከበረች_ተጋዳይ_ለመነኰሳዪት ሰይጣንን በትሕትና ድል ላደረገች #ለቅድስት_ሣራ ዘላዕላይ ግብጽ ለዕረፍት በዓልና #ለቅድስት_አስጠራጦኒቃ እጮኛዋ ለሆነ #ለቅዱስ_ሰለፍኮስ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ ናህስ ከሚባል አገር ከሆኑ ከሰማዕቱ ከከበረ #ከአባ_ሕልያስ_ከሰፍንዮስና_ከሐዲስ_ቅዱስ_ጊዮርጊስ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅድስት_ሣራ፦ ይቺም ቅድስት ከላይኛው ግብጽ ናት ወላጆቿም የክብር ባለቤት ክርስቶስን የሚያመልኩ ክርስቲያን ናቸው። እጅግም ባለጸጎች ነበሩ። ነገር ግን ከእርስዋ በቀር ልጆች የሏቸውም በመልካም አስተዳደግም አሳደጓት ለክርስቲያን የሚገባ ትምህርትን ሁሉ አስተማሩዋት ደግሞም ጽሕፈትን አስተማራት ሁሉጊዜም የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍት ታነባለች ይልቁንም የመነኰሳትን ዜና ታነብ ነበር። መጻሕፍትንም አዘወትራ ስለምታነብ የምንኵስና ልብስ ለመልበስ ፈለገች በላይኛው ግብጽ ከሚገኙ ገዳማትም ወደ አንዱ ገዳም ሒዳ ገባች ብዙ ዘመናትም ደናግልን እያገለገለች ኖረች።
❤ ከዚህም በኋላ የምንኵስና ልብስን ለበሰች ሰይጣንን ድል እስከ አደረገችው ድረስ። ሰይጣን የሚያመጣውን ሥጋዊ ፍትወት እየታገለች ዐሥራ ሦስት ዓመት ኖረች። ንጽሕናን ከመውደዷ ጽናት በተሸነፈ ጊዜ በትዕቢት ሊጥላት ወዶ በቤት መዛነቢያ ልትጸልይ ቁማ ሳለች ተገልጦ "ሣራ ሆይ ሰይጣንን ድል አደረግሽዋልና ደስ ይበልሽ" አላት እርሷም መልሳ "እኔ ደካማ ሴት ነኝ ከክብር ባለቤት ከጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ በቀር ድል አድርጌ ላበረው አልችልም" አለችው።
❤ ይህችም ቅድስት አብረዋት ላሉ ደናግል ጥቅም ያላቸውን ብዙ ትምህርቶችን ታስተምራቸው ነበር። እንዲህም ትላቸዋለች "ከቀን ብዛት ጠላት እንዳያስተኝ እኔ እንደምሞት አስቀድሜ ሳላስብ እግሬን ከአንዱ መወጣጫ ደረጃ ወደ ሁለተኛዋ አውጥቼ አላኖራትም"። ዳግመኛም "ለሰው ርኅራኄ ማድረግ በተሻለው ነበር ይህንንም በሚያደርግ ጊዜ የኋላ ኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድ ውስጥ ይኖራል" በዜና አረጋውያን መነኰሳት መጽሐፍ ውስጥ የተጻፉ ሌሎች ብዙ ቃሎችንም ተናግራለች።
❤ ታላቅ ተጋድሎም እየተጋደለች በዓቷም በባሕር ዳርቻ ሁኖ ሰባት ዓመት ኖረች አንዲት ቀን እንኳን ከሰው አንዱም አላያትም እርሷ ግን ሁሉን ታይ ነበር። ሸምግላ እስከ ሰማንያ ዓመት በደረሰች ጊዜ ከዚህ ዓለም የሕይወት ማሠሪያ ተፈትታ የዘላለም ተድላ ደስታ ወደሚገኝበት መጋቢት15 ቀን ሔደች። የቅድስት ሣራ ጸሎቷ በረከቷ ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ሰለፍኮስ፦ የዚህን ቅዱስ ዜና ክርስቲያን እንደሆነ ከሃዲ ንጉሥ በሰማ ጊዜ ያመጡት ዘንድ አዘዘ ወደርሱም ሲቀርብ "የአስጠራጦኒቃ እጮኛዋ ሰለፍኮስ የተባልክ አንተ ነህን" አለው "አዎን ነኝ" አለ። ዳግመኛም "ማንን ታመልካለህ" አለው እርሱም እኔ የክብር ባለቤት የሆነ ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስን አመልከዋለሁ" ብሎ መለሰ። ንጉሡም መርዝ ያላቸው እባቦች ወዳሉበት እንዲጨምሩት አዘዘ እግዚአብሔርም አዳነው።
❤ ከዚህም በኋላ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡት አዝዞ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊል ተቀበለ። የቅዱስ ሰለፍኮስ በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት15 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለሕልያስ_ሰማዕት_ሐዲስ። ዘአገረ ናህስ። ብቊዓኒ ሊተ በእንተ ክርስቶስ። ከመ ተሀበኒ መድኃኒት ሥጋ ወነፍስ። እምነ ብዕልከ እስእል ጽኑስ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት_15።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ጻድቃንሰ ይወርስዋ ለምድር። ወይነብሩ ውስቴታ ለዓለመ ዓለም። አፉሁ ለጻድቅ ይትሜሐር ጥበበ"። መዝ 36፥29-30። የሚነበቡት መልዕክታት ኤፌ 5፥21-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 5፥14-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 26፥1-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥19-25። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም ወራት ጊዜና በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።
Repost from የግ/ደ/ቅ/አርሴማ ፍኖተ ብርሃን ሰ/ቤት መዝሙር ክፍል
+9
🔴✨🔴✨🔴✨🔴✨🔴✨🔴✨🔴
በዕለተ ሰንበት የጠዋጥ ጉባዔ በደብራችን ስብከተ ወንጌል ክፍል ሀላፊ እና በተጋባዥ ዘማሪ ወንድማችን በዚህ ሁኔታ በዓለ ደብረዘይትን አክብረናል እግዚአብሔር አምላክ ለትንሳኤው ብርሃን ያድርሰን።🙏🙏🙏
ከፍኖተ ብርሃን ሚዲያና ዕቅበተ ዕምነት ክፍል የምስል ማህደር በጥቂቱ ይህን ይመስላል
✨✨✨ ሰናይ ዕለተ ሰንበት ✨✨✨
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ቄርሎስ፦ ይህም አባት የእስክንድርያ ሰባ አምስተኛ ሊቀ ጳጳሳት ነው። እርሱም በምግባሩ ፍጹም ዐዋቂ ሆነ በአገሩ ፍዩም ይባላል በእርሷም ቅስና ተሹሞባት ነበር። ከዚያም ለቆ ወደ አባ ፊቅጦር ገዳም ደረሰ እርሱም ከምስር ከተማ ውጭ የኢትዮጵያውያን ዐዘቅት የዐባይ ግድብ በአለበት ነው። በዚም ታላቅ ገድልን እየተጋደለ ብዙ ዘመናትን ኖረ። ብዙ መጻሕፍትንም ተምሮ ትርጓሜያቸውንና ምሥጢራቸውን ጠንቅቆ ዐወቀ። አሸናፊ ወደሚባለውም ንጉሥ አደባባይ ቀርቦ የእስላሞች ታላላቅ ሊቃውንቶቻቸውና ከምሁራኖቻቸው ውስጥ መምህሮታቸውን ተከራከሩት። ጠቃሚ የሆነ ዕውቀት የተመላበትን መልስ አገኙ የሚጠይቁትንም ሁሉ በመልካም አመላለስ ነገራቸው ከዚህ በኋላ የዕውቀቱና የቅድስናው ዜና በተሰማ ጊዜ ያለ ፈቃዱ ይዘው በእስክንድርያ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት መንጋውንም ጠበቀ በጸሎትና በቅዳሴ ያገለግሉ ዘንድ ለካህናት ሥርዓትንና መመሪያን ሠራ።
❤ ይህም አባት በሊቀ ጵጵስናው ሰባት ዓመታት ከዘጠኝ ወር ከዐሥር ቀኖች ኖረ። ከቀኑም በሦስት ሰዓት መጋቢት14 ቀን ዐረፈ። በምስክርነት አደባባይም ተቀበረ። ከአባ ቄርሎስ በጸሎቱ የምትገኝ በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ የከበሩ #ቅዱሳን_አጋንዮስ_አውንድርያኖስና_ብንድዮስ፦ እሊህም ቅዱሳን ከአባቶቻቸው ጀምሮ ክርስቲያኖች ናቸው። አምላካዊ ትምህርትንም ሁሉ የተማሩ ናቸው።
❤ በእግዚአብሔርም ሕግ ጸንተው ሲኖሩ የኢየሩሳሌም ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አርሞስ መርጦ ኤጲስቆጶሳት አድርጎ ሾማቸው ግን በታወቁ ቦታዎች ላይ አይደለም በብዙዎች አገሮች ውስጥ እንዲሰብኩ ላካቸው እንጂ። በአገሮችም ያሉ ከሀድያን ያዟቸው ያለርህራሄም አብዝተው ገረፏቸው በደንጊያም ወገራቸው መጋቢት 14 ቀን ነፍሳቸውንም በጌታች እጅ ሰጡ። የከበሩ ቅዱሳን አጋንዮስ፣ አውንድርያኖስና ብንድዮስ በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን። ምንጭ፦ የመጋቢት14 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለቶማስ_እንዘ_ይገብር_መድምመ። እምነ ብእሲት አግኂሦ ትድምርተ ጋኔን ኅሡመ። መንጽሔ ኃጢአት መጠዋ ሥጋ ወደመ። በጊዜ ትቤሎ ሀበኒ ማሕተመ። ከመ ላዕሌየ ኢይግባእ ዳግመ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመጋቢት14።
ተአምኆ ቅዱሳን ወግጻዌ (የቅዱሳን ሰላምታ) Teamho Kidusan Wegtsawe (Yekidusa Selamta):
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #መጋቢት ፲፬ (14) ቀን።
❤ እንኳን #ለሐዋያው_ለቅዱስ_ቶማስ ሰባት ዓመት ያህል የጋኔን ግንኑኙነት በአስቸገራት በአንዲት ሴት ላይ ተአምራትን ላደረገበት በዓል፣ ለአረጋውያን ፍጹማን መነኰስ አመንዝራ ሴቶች ብር እየሰጠ በጥበብ ለትዳርና ምንኵስና ላበቃ #ለአባ_ባጥል ለዕረፍት በዓል፣ ለቅዱስ አባት #ለአባ_ሲኖዳ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍት በዓል፣ ለእስክድርያ ሰባ አምስተኛ ሊቀ ጳጳሳት #አባ_ቆርሎስ ለዕረፍት በዓል፣ ለከበሩ #ቅዱሳን_አጋንዮስ_ለአውንድርያኖስና_ለብንድዮስ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ቶማስ ሰባት ዓመት ያህል የጋኔን ግንኑኙነት በአስቸገራት በአንዲት ሴት ላይ ያደረው ተአምራትን ይህ ነው፦ ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስንም በአየችው ጊዜ "የክርስቶስ ሐዋርያው ሆይ እጅግ ከሚያሠቃየኝ ጠላት አድነኝ" ብላ ወደርሱ ጮኸች። እርሱም "በምን ምክንያት አገኘሽ" አላት። እርሷም "ከመታጠቢያ ከውሽባ ቤት ስወጣ እንደ ሰው ድው ድው እያደረገ በመታወክ መጣ ድምጡም ሰላላና ቀጭን ነው በሴትና በወንድ ሥራ ሁሉ ነይ እርስበርሳችን አንድ እንሁን አለኝ በተኛሁም ጊዜ በሌሊት መጥቶ ከእኔ ጋር አንድ ሆነ ብሸሽም አይተወኝም መጥቶ ያሠቃየኛል እንጂ እኔም ከጸሎትህ የተነሣ አጋንንት እንደሚንቀጠቀጡ አውቃለሁና ጸልይልኝ አድነኝም" አለችው።
❤ ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስም ሰምቶ ጸለየ ጋኔኑንም ከእርሷ እንዲወጣ አዘዘው ያንጊዜም በእሳትና በጢስ አምሳል ከሴቲቱ ላይ ወጥቶ ተበተነ ከዚህ በኋላ በክርስቶስ መስቀል በላይዋ አማተበ ሥጋውንና ደሙንም አቀበላት ወደ ዘመዶቿም አሰናበታት። የሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ልዩ የሆነች በረከቱም በሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ላይ ትደር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ባጥል፦ ይህም ቅዱስ ሰው ከአባ ዮሐኒ የተባለ አበ ምኔት በመነኰሳት ላይ ነገረ ሠሪን እንደሚቀበል በሰማ ጊዜ በዓቱን ትቶ ወደ እስክንድርያ መጥቶ የሴት አዳሪዎችንና የአመንዝራዎችን ሁሉ ስማቸውን ጻፈ። ከኪራይ ሠራተኞችም ጋራ ሲሠራ ይውላል። ደመወዙን በተቀበለ ጊዜ የሽንብራ ቂጣ ገዝቶ ይበላል የቀረውንም ገንዘብ ይዞ ወደ አንዲቱ ሒዶ ይሰጣታል "በዚች ቀን ከአንቺ ጋራ አድራለሁና ራስሽን ለእኔ አዘጋጂ" ይላታል። ከኀጢአትም ሊጠብቃት ከእርስዋ ዘንድ ያድራል ሌሊቱን ሁሉ ተነሥቶ ሲጸልይና ሲሰግድ እግዚአብሔር ሲለምን ያድራል ሲነጋም ሥራውን ለማንም እንዳትገልጥ አምሏት ወደ ተግባሩ ይሔዳል።
❤ በየዕለቱም ወደ የአመንዝራዎቹ እየሔደ እንዲህ ያደርግ ነበር አንዲቱም ሴት ምሥጢሩን ገለጠች ጋኔንም ይዞ አሳበዳት። ሰዎችም ስለዚህ ክፉ ሽማግሌ ክፉ ሥራ የለበትም ብላ ወሽታለችና እግዚአብሔር መልካም አደረገባት ተባባሉ። እርሷም "እንዳናመነዝር ገንዘብ በመስጠት ከኃጢአት ይጠብቀናል እንጂማ ነውር የለበትም" ብላ ነበርና። የቀሩት አመንዝራዎች በእርሷ ላይ የሆነውን በአዩ ጊዜ ደነገጡ እንደርሷም እንዳያብዱ እውነቷን ነው ማለትን ፈሩ። እርሱም "ይችስ በእገሌ ዕለት ትጠብቀኛለች" ይል ጀመረ ሰዎችም ሁሉ ያሙት ጀመር እርሱም "እንደ ሰው ሁሉ ሥጋ የለኝምን ወይስ እግዚአብሔር መነኰሳትን ተቆጥቶ በፍትወት ተቃጥለው እንዲሞቱ ትቷቸዋልን" አላቸው። እነርሱም "ልብስህን ለውጠህ ሚስት አግባ ይህ ይሻልሃልና" አሉት። እርሱም "አዎን ብወድ በሚስቴ እጠነቀቃለሁ በዚህም በክፉ አኗኗር እኖራለሁ እናንተ ግን ከእኔ ዘንድ ሒዱ ምን ትሻላችሁ በእኔ ላይ እግዚአብሔር ፈራጆች አድርጓችኋልን ይልቁንስ እናንተ እንዳይፈረድባችሁ ለራሳችሁ አስቡ ፈራጅ አንድ ነውና ዕለቲቱም አንዲት ናትና" አላቸው።
❤ ይህም ቅዱስ በእግዚአብሔር ዘንድ ተቀባይነት አገኘ በሰው ዘንድ ግን የተናቀ ሁኖ ኖረ። ከእርሱ ጥቅም የአገኙ አመንዝራዎችም ዝሙታቸውን ተዉ። ከእርሳቸውም ሕጋዊ ጋብቻ ተጋብቶ የኖረ አሉ ወደ ገዳምም ገብቶ መንኵሶ በጾም በጸሎት ተወስኖ የኖሩ አሉ።
❤ በአንዲት ዕለትም ከአንዲት አመንዝራ ቤት ሲወጣ ያቺን ሴት አስቀድሞ የለመዳት አንድ ሰው አገኘውና "ይህ ሽማግሌ እስከ መቼ ድረስ በዚህ በክፉ ሥራ ይኖራል" ብሎ ፊቱን በጥፊ መታው።
❤ ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን በበዓቱ ውስጥ ሰግዶ ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ውስጥ ሰጥቶ በቤቱም መድረክ "የዚች አገር ሰዎች ጊዜው ሳይደርስ በማንም ላይ አትፍረዱ እንዳይፈረድባችሁ" የሚልም ጽሑፍ ተጽፎ ተገኘ። ከአባ ባጥል በጸሎቱ የሚገኝ በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ይኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ሲኖዳ፦ እርሱም በግብጽ አገር ከብሕንሳ ነው። ወደ መክስምያኖስም ክርስቲያናዊ ሲኖዳ "አማልክትን የሚያመልክ ነው" ብለው ነገር ሠሩበት። እርሱም አስቀርቦ ስለ ሃይማኖቱ ጠየቀው በንጉሡም ፊት በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ እርሱም ዕውነተኛ አምላክ እንደ ሆነም መሰከረ።
❤ መክስምያኖስም ይህን የከበረ አባ ሲኖዳን በምድር ላይ ዘርግተው በበትሮች እንዲደበድብት አዘዘ። ዐጥንቶቹ እስቲሠነጠቁ ደሙም በምድር ላይ እንደ ውኃ እስቲፈስ እንዲሁ አደረጉበት። ከዚህም በኋላ እግሩን ይዘው ጐትተው ወስደው ሽታው በሚከረፋ በጨለማ ወህኒ ቤት ጣሉት የእግዚአብሔር መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ተገለጠለት። ቊስሎቹንም አድኖ ጤነኛ አደረገው አበረታውም "በርታ አትፍራ ስለ መከራህም የክብር አክሊል ተዘጋጅቶልሃልና ደግሞም በጽኑዕ ሥቃይ ትሠቃይ ዘንድ አለህ እግዚአብሔር እንዳዘዘኝ እኔም ከአንተ ጋራ እኖራለሁ" አለው። ከዚያም ከእርሱ ተሠወረ።
❤ በነጋ ጊዜም "የነገሥታትን ትዕዛዝ የሚተላለፍ ያንን ዓመፀኛ ሒዳችሁ እዩት ሙቶም ከሆነ ለውሾች ጣሉት" ብሎ መክስምያኖስ ወታደሮቹን አዘዘ። ወደርሱም በደረሱ ጊዜ ቁሞ ሲጸልይ አግኝተውት "ያለምንም ጥፋት ጤነኛ እንደሆነና በሥጋውም ውስጥ የሕማም ምልክት እንደሌለ እርሱም ከቶ ምንም ሥቃይ እንዳላገኘው ጤነኛና ደስ እንዳለው ሰው ተግቶ እንደሚጸልይ" ስለርሱ ለንጉሡ ነገሩት። ንጉሡም ወደርሱ አስመጣው ከሕይወቱም የተነሣ አደነቀ ልብሶቹንም አስወልቆ ያለጉዳት ጤነኛ እንደሆነ ሥጋውን አየ ደግጦም "ይህ ያየሁት ሥራይ ታላቅ ነው" አለ። ከዚያም ዘቅዝቀው ሰቅለው ከታቹ እሳትን እንዲያነዱ አዘዘ። ይህንንም አደረጉበት ደግሞ በመንኰራኵር አሠቃዩት በአለንጋዎችም አብዝተው ገረፉት ደበደቡትም።
❤ ማሠቃየቱንም በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ ቆርጠው ለውሾች እንዲጥሉት አዘዘ ውሾች ግን ፈጽሞ አልቀረቡትም ሌሊትም ሲሆን ምዕመናን መጥተው ሥጋውን ወሰዱ በአዳዲሶች ልብሶችና በጣፋጭ ሽቶዎች ገነዙት በሣጥንም አድርገው ቀበሩት። ከሥጋው ብዙዎች አስደናቂዎች ተአምራቶች ተደረጉ። የአባ ሲኖዳ በረከቱ ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።
