uz
Feedback
ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ

Kanalga Telegram’da o‘tish

ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።

Ko'proq ko'rsatish
636
Obunachilar
Ma'lumot yo'q24 soatlar
-47 kunlar
-1230 kunlar
Postlar arxiv
🌼 ሌላው የገዳሙ ታሪክ ሲወሳ አብሮ የሚነሣው የአቡነ ክርስቶደሉ ታሪክ ነው። አቡነ ክርስቶደሉ የዐፄ ሱስንዮስ ጳጳስ ሲሆኑ ያስመጡዋቸውም ከኢየሩሳሌም ነው። ጳጳሱ መንፈስ ቅዱስ ተገልጾላቸው ትንቢት በመናገር ዴንሳ ውስጥ ግንብ በተባለ ቦታ ሲኖሩ ዕለተ ሞታቸው ደረሰ። አንድ ቀን ከቀኑ 10 ሰዓት ላይ "ዕረፍቴ ደርሷልና እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ ስብሐተ እግዚአብሔር ከማይታጎልበት ገዳም ጎንጂ ውሰዱና ቅበሩኝ" ብለው በዙሪያቸው ለሚገኙ ሰዎች ይናገራሉ። ሰዎችም "አባታችን አሁን የፀሓይ መግቢያ ሰዓት ነውኮ" ቢሏቸው ጻድቁም "ፀሓይን ገዝቻታለሁ" ብለው ተናገሩ። በቃላቸውም ግዝት መሠረት ፀሓይ ባለችበት ቆመች። እርሳቸውም ዐርፈው ሰዎቹ ይዘዋቸውና አስከሬናቸው ጎንጂ ደርሶ ከተቀበሩ በኋላ ኀዘንተኛው ወደ ዴንሳ እስኪመለስ ድረስ ፀሓይ ብርሃኗ አልጠፋም ነበር። ከዴንሳ እስከ ጎንጂ የአንድ ቀን መንገድ ያህል ያስኬዳል። 🌼 በአሁኑ ወቅት የኢየሩሳሌሙ ጳጳስ የአቡነ ክርስቶደሉ መቃብር ደዌ ያለባቸውን ሰዎች እየፈወሰ በደብረ ጥበብ ጎንጂ ቴዎድሮስ ገዳም ውስጥ ይገኛል። ዐፄ ቴዎድሮስ በንግሥና ዘመናቸው ምንም እንኳን ያን ያህል የተረጋጋ መቀመጫ ባይኖራቸውም በአንጻሩ ይባባ(ጎጃም) ውስጥና ደብረታቦር (በጌምድር) መቀመጫቸው ነበሩ። ንጉሡ ከይባባ ይልቅ ደብረ ታቦርን ይመርጡ ነበርና በአንድ ወቅት ጎጃም የሚገኘውን ጎንጅ (ደብረ ጥበብ) የሰማዕቱ የቅዱስ ቴዎድሮስ ጽላት መኖሩን ያውቁ ስለነበር ጽላቱን ወደ ደብረ ታቦር ለመውሰድ አሉላ የሚባል ሰው ልከው ነበር፤ ነገር ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ ስላልነበር አሉላና ጭፍሮቹ ጽላቱን ይዘው ዓባይ ወንዝ እንደደረሱ አሉላን ከነበቅሎው ጭፍሮችን ጨምሮ ዓባይ ወሰዳቸው። 🌼 የሰማዕቱ ጽላትም ተመልሶ ወደ ጎንጅ ቴዎድሮስ ቤተ ክርስቲያን ይገባል። ወሬው በሀገሩ ኹሉ ተወርቶ ከተሰማ ከወራት በኋላ ከእነማይ (ከጎጃም) ጽላቱ እንደተሰረቀና የደረሰበትም ለጊዜው እንደጠፋ አንዱ የእነማይ ባለቅኔ፦  የጎንጁ ቴዎድሮስ የአሉላው ገዳይ እንዲህ ወደ እነማይ ብቅ አትልም ወይ ሲል እንደተቀኘ በታሪክ ይነገራል። ምንጭ፦ ዝክረ ቅዱሳን በእንተ ቅዱሳን ኅሩያን።

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼           🌼 #መስከረም ፲ (10) ቀን። 🌼 እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ ገበያተኛውን ሕዝብ አስተምረው ሲጨርሱ ድንጋዩን ዳቦ እያደረጉ ሕዝቡን ይመግቡ ለነበሩት ለታላቁ አባት #አቡነ_ግርማ_ሥሉስ_ለዕረፍታቸው_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #አቡነ_ግርማ_ሥሉስ፦ አባታቸው ነገደ ኢየሱስ እናታቸው ትኩና ለጽዮን የሚባሉ ሲሆን ትኩና ለጽዮን የዐፄ ሰይፈ አርእድ ልጅ ናት። ስለዚኸም አቡነ ግርማ ሥሉስ ትውልዳቸው ከመንግሥት ወገን ቢሆንም "በዓለም ነግሦ መኖርን አልፈልግም" በማለት የዓለምን ጣዕም ንቀው ገዳም የገቡ ጻድቅ ናቸው። ክቡር ዐፅማቸው ያረፈው በጎንጅ ደብረ ጥበብ ቅዱስ ቴዎድሮስ ገዳም ነው። ገዳሙ በአማራ ክልል ምዕራብ ጎጃም ዞን ጎንጅ ቆለላ ወረዳ ከባሕር ዳር 70 ኪ.ሜ ርቀት ላይ ከጥንታዊቷ የጎንጅ አነስተኛ የገጠር ከተማ ላይ ይገኛል። በጊዜው አወቃቀር የዞኑ ዋና ከተማ ፍኖተ ሰላም ነው። ምንም እንኳን ጎንጂ ቆላላ ለባሕር ዳርና ለአዴት ቅርብ ቢሆንም በአወቃቀር ደረጃ በምዕራብ ጎጃም ዞን ውስጥ ተካትቷል። 🌼 ጎንጅ ቴዎድሮስ ወይም ጎንጅ ደብረ ጥበብ ገዳም ከክርስቶስ ልደት በፊት በ4518 ዓመተ ዓለም በሊቀ ካህናቱ ዘካርያስ አማካይነት ተመሠረተ። እስከ ልደተ ክርስቶስ ድረስ የኦሪት መሥዋዕት ሲሠዋበት ኖሯል። ደብረ ጥበብ የሚለው ስያሜው ከጠቢቡ ተዋነይ ጠቢብነት ጋር ይያያዛል፤ ይኸውም በአሁኑ አጠራር ጎንጅ ደብረ ጥበብ የተባለበት ምክንያት በገዳሙ ታዋቂ የነበረው የቅኔ ሊቅ ተዋነይ የተባለው ሊቅ መወደስ የተባለውን ቅኔ ከተቀኘ በኋላ በደመና ተጭኖ በተመሳሳይ ሰዓት ጎንደር ከተማ ዕጣነ ሞገር የተባለውን ቅኔ በመቀኘቱ እንደሆነ ታሪክ ያስረዳል። 🌼 ሊቁ ተዋነይ ከዚኸ ዋርካ ሥር ተደግፎ ለ20 ዓመታት ግስ ገስሶበታል፣ የቅኔ ቀመር ቀምሮበታል፣ መወድስ ዘርፎበታል፣ ተፈላስፎበታል። የአካባቢው ሕዝብ በእምነት የሚኖር አስገራሚና የዋህ ሕዝብ ነው፣ የሀገሬው ሰው አዲስ ልብስ ገዝቶ ከመልበሱ በፊት እሑድ ቀን ወደ ቤተ ክርስትያን ወስዶ አስባርኮ ነው የሚለብሰው። 🌼 በገዳሙ ውስጥ 44 ታቦታት የሚገኙ ሲሆን ከእነዚኸ ታቦታት ውስጥ አንዱ የቅዱስ ባስልዮስ ታቦተ ነው። የጎንጅ ደብረ ጥበብ ካህናት ከ44ቱ ታቦታት ቀድመው የሚጠቅሱት ታቦተ ቅዱስ ባስልዮስን ነው። ምክንያቱም ታቦተ ቅዱስ ባስልዮስ በሌላ ቦታ ሳይኖር በጎንጅ ደብረ ጥበብ ብቻ መኖሩን ለማመልከት ነው። ከቤተ ክርስቲያኑ 50 ሜትር ያህል ከቅጽሩ ደግሞ 25 ሜትር ፈቀቅ ብሎ ትልቁ የተዋነይ ዋርካ በሰባት አክናፍ እንደዣንጥላ ተዘርግቶ ይገኛል። በወረዳው ከጎንጅ ደብረ ጥበብ የቅኔ ትምህርት ቤት በተጨማሪ ታዋቂው የቅኔ ትምህርት ቤት ዋሸራ ማርያም በዚኹ ወረዳ ይገኛል። 🌼 ጎንጅ ገዳም የሚገኘው ትልቅ ተራራ ሥር ሲሆን ሰይጣን ከተራራው ጫፍ ላይ ወጥቶ ድንጋዩን ገደሉን እየናደ ሲጥለው ድንጋዩ እየተፈነቀለ ሲወርድ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ሊያፈርስ ሲል ጻድቁ በቃላቸው ድንጋዩን እንዳትንቀሳቀስ ብለው ገዝተው አቁመውታል። በዚያ ትልቅ ገደል ላይ የድንጋዮቹ አቋቋም ላያቸው እጅግ ያስደንቃሉ። 🌼 የገዳሙ አስተዳዳሪ ቄስ መልካም በዜ ስለገዳሙ አመሠራረት በቃለ መጠይቅና በጽሑፍ በሰጡት ማስረጃ መሠረት የደብረ ጥበብ ጎንጅ ቴዎድሮስ ገዳም የኦሪት መሥዋት ሲሠዋበት የኖረ መሆኑ፣ ከዋሸራና ከጽላሎ በፊት በእነ ጠቢቡ ተዋናኝ ቅኔ የተዘረፈበትና አሁንም ያለበት መሆኑ፣ ጥንታዊ የብራና መጻሕፍትና ዕድሜ ጠገብ የብራና የመቃ ላይ ሥዕላትና በርካታ ቅርሶች የሚገኙበት ከመሆኑም በላይ ጻድቁ አቡነ ግርማ ሥሉስ የጸለዩበትና ዐፅማቸው ያረፈበት በመሆኑ ልዩና ታሪካዊ ገዳም ያደርገዋል። 🌼 ጻድቁ አቡነ ግርማ ሥሉስ ለ40 ዓመት ያህል እሙይት በተባለው ወንዝ አካባቢ ሲጸልዩ ከኖሩ በኋላ በራእይ ተነግሯቸው ወደ ጎንጅ ደብረ ጥበብ ቴዎድሮስ ገዳም በሚሔዱበት ጊዜ ድንጋዮች ተከትለዋቸው ሔደዋል። ተከትለዋቸው ከሔዱት ድንጋዮች መካከል አንዱ ግዝት ድንጋይ እየተባለ የሚጠራው በአሁኑ ወቅት ከገዳሙ 200 ሜትር ርቀት ላይ በደቡብ በኩል ይገኛል። ከላይ የተከማቸው ድንጋይ ወደ ገዳሙ ለመውረድ ሲንከባለል ተገዝቶ ቆሞ ላየው ይደንቃል። ድንጋዩ ከከተማው እስከ ገዳሙ ድረስ አልፎ አልፎ ተንጠባጥቦ ይታያል። 🌼 ጻድቁ ወንጌልን ሊያስተምሩ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ሲዘዋወሩ ዛፎችና ድንጋዮች ሁሉ ይከተሏቸው ነበር። አቡነ ግርማ ሥሉስ ገበያተኛውን ሕዝብ አስተምረው ሲጨርሱ ድንጋዩን ዳቦ እያደረጉ ሕዝቡን ይመግቡ የነበሩ ታላቅ አባት ናቸው። ጻድቁ የተወለዱት በተኣምራት በአካላቸው ላይ ማዕተብ አድርገው፣ በእጃቸው መስቀል ይዘው እና ተገዝረው ነው። ከልጅነታቸው ጀምረው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ተምረው ከጨረሱ በኋላ አበምኔትና መምህር በመሆን በገዳሙ ለ40 ዘመን በመምህርነት አገልግለዋል። 🌼 በተጋድሏቸውም ወቅት እሙይት ከተባለው ባሕር ውስጥ ገብተው ሲጸልዩ ያድሩ ነበር። በኋላ ከእሙይት ባሕር ወደገዳማቸው ቦታ ሲመለሱ ድንጋዮች "ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ አቡነ ግርማ ሥሉስ" እያሉ ከእሙይት ባሕር እስከ ጎንጂ ድረስ ተከትለዋቸዋል። በኋላም ወደ ገዳሙ ሊወርዱ ሲሉ አብዛኛው ድንጋይ በጻድቁ ቃለ ግዝት ከአፋፍ በላይ ሲቀር፣ ሦስቱ ድንጋዮች ግን አባታችንን "ከወደቁበት እንወድቃለን" ብለው ተከትለዋቸው ሲወርዱ "አይሆንም ተመለሱ" ብለው አዘዟቸው። ድንጋዮቹም ካለበት ቦታ ላይ ቆመው በመቅረታቸው "ግዝት ድንጋዮች" ተብለው እስከዛሬ ድረስ ይጠራሉ። 🌼 ድንጋዮቹ የቆሙበት ቦታ ከታች ቁልቁለታማ ገደል ቢሆንም ምንም ሳይሆኑ በጻድቁ ቃለ ግዝት እንደቆሙ ቀርተዋል። ከአፋፍ በላይ የቀሩት ሌሎቹ ደንጋዮች በአሁኑ ወቅት ከጎንጂ ቆለላ ከተማ ከገበያው መሐል ይገኛሉ። ቦታው ከጊዜ በኋላ ገበያ እንደሚቆምበት የታያቸው አቡነ ግርማ ሥሉስ ከባሕር ውስጥ ወጥተው "ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ አቡነ ግርማ ሥሉስ" እያሉ የተከተሏቸውን ድንጋዮች ባሉበት ቦታ ላይ እንዲቆሙ ጻድቁ በቃላቸው ሲያዟቸው "ከጊዜ በኋላ ከዚኸ ቦታ ላይ ገበያ ይቆማል፣ የደጋውና የቆላው ወገኔ ለገበያ በሚገናኙበት ጊዜ ማረፊያና የሸቀጣሸቀጡ መቀመጫ ትሆናላችሁ" ብለው ስላሏቸው በአሁኑ ወቅት በቍጥር ከ60 በላይ የሚሆኑ ድንጋዮች በገበያው ቦታ ላይ በየቦታው በመደዳ ተሰድረው ለገበያተኛው ሕዝብ አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛሉ። 🌼 አቡነ ግርማ ሥሉስ የትውልድ ሀገራቸው ጎጃም ሲሆን በተወለዱ ጊዜ ብርሃን ከሰማይ ወርዶላቸዋል። አስቀድመን እንደጠቀስነው የዐፄ ሰይፈ አርእድ የልጅ ልጅ ቢሆኑም ንግሥናን ትተው ዓለምን ንቀው ስለመነኑ መጽሐፍ "መናኔ መንግሥት ወብእሲት" ይላቸዋል። በአሁኑ ወቅት ከደብረ ጥበብ ገዳም ከፍ ብሎ በአቡነ ግርማ ሥሉስ ስም የተሰየመ ጠበል ፈልቆ ሕሙማን በየጊዜው እየተፈወሱበት ይገኛሉ። መስከረም 10 ቀን በገዳማቸው በዓለ ዕረፍታቸው በደማቅ ሁኔታ ይከበራል። ከአባታችን አቡነ ግርማ ሥሉስ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከት ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!።

                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ወዘሕጎ ያነብብ መዓልተ ወሌሊተ። ወይከውን ከመ ዕፅ እንተ ትክልት ኀበ ሙኃዘ ማይ። እንተ ትሁብ ፍሬሃ በበጊዜሃ"። መዝ1፥2-3። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 12፥33-38።                             ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ወትቀውም ንግሥት በየማንከ። በአልባሰ ወርቅ ዑፅፍት ወኁብርት። ስምዒ ወለትየ ወርእዪ ወአፅምዒ እዝነኪ"። መዝ 44፥9-10። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 3፥1-ፍ.ም፣ ያዕ 3፥13-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 1፥12-15። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 1፥46-57 ወይም ማቴ 25፥1-14። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታች ማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የፄዴንያ ማርያም በዓልና የመስቀሉ በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።                

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼           🌼 #መስከረም ፲ (10) ቀን። 🌼 እንኳን #ለእመቤታች_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም #በፄዴንያ_አገር_በማርታ_ቤት ሥጋ የለበሠች ከምትመስል #ከእመቤታች_ሥዕል ከሠሌዳዋ #ቅባት_እየተንጠፈጠፈ ተአምር ለሠራችበት ቀን መታሰብያ በዓል፣ #አምላክን_ለወለደች_ለእመቤታችን #ለቅድስት_ድንግል_ማርያም_ለተወለደችበት_ለልደቷ በዓል መታሰቢያ (ይህም የአስቄጥስ ገዳም የከበረ አባ መቃርስ በጻፈው መጽሐፈ ግጻዌ ተጽፎል እንዲሁም ደግሞ በላዕላይ ግብጽ በሚገኝ መጽሐፈ ግጻዌ የከበረች ድንግል እመቤታችን የከበረች ሐና በታኅሣሥ ወር በዐሥራ ሰባት እንደፀነሰቻትና መስከም በዐሥር ቀን እንደወለደቻት ተጽፍአል)፣ ለከበረች  ሰማዕትነት ለተቀበለችበት #ለቅድስት_መጥሮንያ_ሰማዕትነት ለተቀበለችበት በዓል ዕረፍት፣ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪም በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #የጌታችን_የአምላካችን_የመድኃኒታችን_የኢየሱስ_ክርስቶስ #ቅዱስ_መስቀል_ወደ_አገራችን_ኢትዮጵያ ድንበር ከደረሰበት (ተቀጽል ጽጌ) አፄ መስቀል) ቀን ለመታሰቢያ በዓልና ከከሀዲው #ሆሎፎርኒስ እጅ በጥበቧ እስራኤልን ካዳነቻቸው ከጥበበኛ ከከበረች #ከቅድስት_ዮዲት በዓለ ዕረፍትና #ከቅድስት_አትናስያና_ሦስት_ልጆቿ_ከመታሰቢያቸው በረከትና ረድኤትን ያሳትፈን።                                                       ✝ ✝ ✝ 🌼 #በዚህች_ቀን_ጼዴንያ በምትባል አገር ሥጋ የለበሰች ከምትመስል ሥዕል ከሠሌዳዋ ቅባት እየተንጠፈጠፈ #አምላክን_የወለደች_የእመቤታችን_የድንግል_ማርያም_ተአምር ተገለጠ። ይቺንም ሥዕል የሣላት ወንጌላዊ ሉቃስ ነው ይባላል። ወደ ጼዴንያ አገርም የመጣችበት ምክንያት አንዲት ስሟ ማርታ የሚባል መበለት ሴት ነበረችና ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች ናት። አምላክን የወለደች እምቤታችን ድንግል ማርያምንም እጅግ ትወዳት ነበር። በሚቻላትም ሁሉ ታገለግላታለች። 🌼 በአንዲት ቀንም ስሙ ቴዎድሮስ የሚባል መነኵሴ ከእርሷ ዘንድ እንግድነት አደረ በመልካም አቀባበልም ተቀበለችው በማግሥቱም ስተሸኘው "አባት ሆይ የምትሔደው ወዴት ነው" አለችው። እርሱም "በከበሩ ቦታዎች ውስጥ ልሰግድ ወደ ኢየሩሳሌም እሔዳለሁ" አላት እርሷም "ከእኔ ገንዘብ ወስደህ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ግዛልኝና በመመለሻህ ጊዜ አምጣልኝ" አለችው። እርሱም በራሴ ገንዘብ ገዝቼ አመጣልሻለሁ አላት። 🌼 ከዚህም በኋላ ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ ከቅዱሳት መካናት ተባረከና ሥዕሏን ሳይገዛ ወደ ጎዳናው ተመለሰ። ያን ጊዜም "ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ" የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰማ ወደ ገቢያም ተመልሶ ላሕይዋና መልኳ ያማረና የተወደደ የሆነ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል አግኝቶ ገዛት በሐርና በንጹሕ ልብስም ጠቀለላት። በጎዳናውም እየተጓዘ ሳለ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ወንበዴዎች ተነሡበት ሊሸሽም ወደደ ከዚያቺም ሥዕል "መንገድህን ሒድ የሚል ቃል ወጣ" የተከተለውም ሳይኖር መንገዱን ተጓዘ። ሁለተኛም ነጥቆ ሊበላው አንበሳ ተነሣበት ያን ጊዜም ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረው። 🌼 አባ ቴዎድሮስም ይህን ሁሉ ድንቅ ተአምር ባየ ጊዜ ያቺን ሥዕል ወደ አገሩ ሊወስዳት ወደደ ግዛልኝ ላለችው መበለት ይሰጣት ዘንድ አልፈለገም። ✝ ከዚህም በኋላ በመርከብ ተሳፍሮ በሌላ አቅጣጫ ሲጓዝ ታላቅ ነፋስ ተነሣበት ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያም ወሰደው ከመርከቡም ወርዶ ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ሔደ ማንነቱንም አልገለጠላትም እርሷም አላወቀችውም። በማግሥቱም ተሠውሮ ወጥቶ ወደ አገሩ ሊሔድ በፈለገ ጊዜ የቅጽሩን ደጃፍ አጥቶ ሲያጥመሰምስ ዋለ በመሸ ጊዜም ወደ ማደሪያው ተመለሰ። ያቺም መበለት በአየችው ጊዜ ታደንቃለች እንዲህም ሁኖ እስከ ሦስት ቀን ኖረ በመሸ ጊዜ በሩን ያየዋል ነግቶ መሔድን ሲሻ የበሩ መንገድ ይሠወረዋል። ያቺም መበለት ያዝ አድርጋ "አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን ስትቅበዘበዝ አይሀለሁና ምን ሆነህ ነው" አለችው። 🌼 ከዚህም በኋላ ከዚያች ሥዕል የሆነውን ሁሉ ነገራት ራሱንም ገለጠላት። ያቺንም ሥዕል ሰጣት ተቀብላም የተጠቀለለችበትን ልብስ ፈታች ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች። ከደስታዋም ብዛት የተነሣ የዚያን መነኩሴ እጆቹንና እግሮቹን ሳመች። 🌼 ከዚህም በኋላ ያቺን ሥዕል ወደ ጸሎት ቤቷ ወስዳ በታላቅ ክብር የምትቀመጥበትን አዘጋጅታ አኖረቻት ማንም እንዳይዳስሳትም የነሐስ መስኮትን ሠራችላት በቀንና በሌሊትም የሚበሩ መቅረዞችን በፊቷ ሰቀለች ከመቅረዞችም ውጭ የሐር መጋረጃን ጋረደች። ከሥዕሊቱ በታችም ከሥዕሊቱ እየተንጠፈጠፈ የሚወርደው የወዝ ቅባት የሚጠራቀምበት ከዕብነ በረድ የተሠራ ወጭት አኖረች ያም መነኰስ እስከሚሞትበት ቀን ድረስ የእመቤታችንን ድንግል ማርያምን ሥዕል እያገለገለ ኖረ። 🌼 የሀገሩም ሊቀ ጳጳሳት የዚያችን ሥዕል ዜና በሰማ ጊዜ ከኤጲስቆጶሳትና ከካህናት ከሕዝቡም ሁሉ ጋር መጣ በሠሌዳውም ውስጥ በአዩዋት ጊዜ ሥጋ የለበሰች ሁና አገኙዋት ከዚህ ከአምላካዊ ግብር የተነሣ አደነቁ ከዚህም ቅባት ቀድተው ለበረከት በተካፈሉ ጊዜ ወዲያውኑ በወጭቱ ውስጥ ይመላል። ወደ ሌላ ቦታም ሊወስዷት በፈለጉ ጊዜ ንውጽውጽታ ሆኖ ብዙዎች በድንጋጤ ወደቁ ሥዕሊቱም እስከ ዛሬ በዚያች አገር ትኖራለች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በእናቱ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                             ✝ ✝ ✝ 🌼 #ሰማዕቷ_ቅድስት_መጥሮንያ፦ ይቺም የከበረች መጥሮንያ ለአንዲት አይሁዳዊት ሴት አገልጋይዋ ናት። ይችም አይሁዳዊት እመቤቷ ከክርስትናዋ አፍልሳ ትክክል ወደ አልሆነ ሃይማኖቷ ልታስገባት ትሻ ነበር ስለዚህም ታጉሳቁላታለች በላይዋም የአገልግሎት ሥራን ታከብድባታለች ። 🌼 ከዚህም በኋላ በአንዲት ቀን አይሁዳዊት እመቤቷን ተከትላ ወደ አይሁድ ምኵራብ ሔደች ተመልሳም ወደ ከበረች ቤተ ክርስቲያን ገብታ ጸለየች። ወደ ቤት በገቡም ጊዜ "ወዴት ሒደሽ ነበር ወደእኛ ምኩራብ ለምን አልገባሽም" ብላ ጠየቀቻት ቅድስት መጥሮንያም "ከእናንተ ምኵራብ እግዚአብሔር ርቋል እኮን እንዴት ወደርሱ እገባለሁ። በውስጧ ልገባባት የሚገባኝ ቦታዬ ግን ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ በከበረ ደሙ የዋጃት ይህች ቤተ ክርስቲያን ናት" ብላ መለሰችላት። እመቤቷም ይህ ነገር በሰማች ጊዜ ተቆጣቻት እጅግም ደብደባ በጨለማ ቤት ውስጥ አሠረቻት ያለ መብልና መጠጥም አራት ቀን ኖረች። 🌼 ከዚህም በኃላ ከእሥር ቤት አውጥታ በጅራፍ ታላቅ ግርፋትን ገርፋ ሁለተኛ ወደ እሥር ቤት መልሳ አሠረቻት በዚያም ዐረፈች። እመቤቷም በድኗን አንሥታ ከቤቷ ደርብ ላይ አውጥታ በውጭ ወደታች ጣለቻት። ወድቃ የሚያዩዋት ሰዎች በገዛ ፈቃድዋ እንደወደቀች አድርገው እንዲናገሩ ብላ ነው ስለ መገደሏ ዳኞች እንዳይመራመርዋት ፈርታለች። 🌼 በዚያንም ጊዜ በዚያች አይሁዳዊት ሴት ላይ የእግዚአብሔር ቁጣ ወረደ ከደርቧ ላይ ስትወርድም በድንገት ወድቃ ሞተች ወደ ዘላለማዊም እሳት ሔደች ይህች የከበረች መጥሮንያ ግን የሰማዕታትን አክሊል ተቀብላ ወደ ዘላለም ሕይወት ሔደች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በቅድስት መጥሮንያ በረከቷም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የመስከረም 10 ስንክሳር።

Ovozli xabar00:36

Ovozli xabar01:41

Ovozli xabar03:16

+1
የሰርግ መዝሙሮች ስብስብ.pdf6.77 KB

🌼 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼           🌼 #መስከረም ፱ (9) ቀን። 🌼 እንኳን #በሮሜ_አገር ፍሩምያ በምትባል ከተማ #በመላእክት_አለቃ_በቅዱስ_ሚካኤል በስሙ በተሠራ ቤተ ክርስቲያን #ላደረገው_ተአምር መታሰቢያ በዓል፣ ከኃላፊው #ከዚኽ_ዓለም_መንግሥቱ_መንኖ ተጋድሎውን በዛፍ ላይ ኹኖ ለፈጸመ፤ የደረቀውን ግንድ ላለመለ፣ ለጽጌ፣ ለፍሬ ለአደረሰ ላሳየ እግዚአብሔርን ደስ ላሰኘ #ለንጉሥ_ለቅዱስ_ለአባ_ያሳይ ለዕረፍት በዓልና ለመጺል ለምትባል አገር ኤጲስቆጶስ ለሆነ #ለቅዱስ_አባት_ለአባ_ቢሶራ_ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቅዱስ_ፋሲለደስ_ጋር_ዐሥራ_አራት_ሺህ_ሰባት መቶ #ሠላሳ_ወንዶችና_ሰባት_ሴቶችም በሰማዕትነት ከዐረፉ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                               ✝ ✝ ✝ 🌼 በዚህች ቀን #በሮም_አገር_ፍሩምያ በምትባል ከተማ ለሆነው ተአምር መታሰቢያ ሆነ። ይህም እንዲህ ነው የሰማይ ሠራዊት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ #በቅዱስ_ሚካኤል_ቤተ_ክርስቲያን ውስጥ በሚታዩ ድንቆችና ተአምራቶች ምክንያት ዮናናውያን ሰዎች ሰይጣናዊ ቅናትን እንደ ቀኑ ከመቅናታቸውም ብዛት የተነሣ በዚያ አካባቢ የሚወርደውን የወንዝ ውኃ በዚያች ቤተ ክርስቲያን ላይ ሊመልሱትና ከሚጠብቃት መጋቢዋ ጋር በውኃ ስጥመት ሊአጠፉአት ፈልገው መለሱት። 🌼 የሰማያውያን ሠራዊት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልም ለቤተ ክርስቲያኑ መጋቢ ለናርጢኖስ ተገለጠለት ወደርሱም ቀርቦ "ጽና አትፍራ" አለው ይህንን ብሎ በእጁ ውስጥ ባለ በትር አለቱን መታው አለቱም ተሰንጥቆ እንደ በር ሆነ የዚያ ወንዝ ውኃም በውስጡ አልፎ ሔደ። 🌼 ይህንንም ያዩ ምስጉን እግዚአብሔርን አመሰገኑት የመላእክት አለቃ ቅዱስ ሚካኤልንም አከበሩት። ከዚያች ቀን እስከ ዛሬ የወንዙን ውኃ በዚያች በተሠነጠቀች አለት ውስጥ አልፎ ሲሔድ ያዩታል ወደ መላእክት አለቃ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ከቶ አይቀርብም። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ሚካኤል አማለጅነት ይማረን ለዘላለሙ አሜን።                                                    ✝ ✝ ✝ 🌼 #ንጉሥ_ቅዱስ_አባ_ያሳይ፦ ይህም ቅዱስ ከኃላፊው ከዚኽ ዓለም መንግሥቱ መንኖ ተጋድሎውን በዛፍ ላይ ኹኖ የፈጸመ ነው፤ የደረቀውን ግንድ ከልምላሜ፣ ከጽጌ፣ ከፍሬ አድርሶ ያሳየ፤ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኘ በቅዱስ ነው። ከንጉሥ ከቅዱስ (አባ) ያሳይ ያሳይ በጸሎቱ የምትገኝ በረከቱ ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                            ✝ ✝ ✝ 🌼 #የመጺል_አገር_ኤጲስቆጶስ_አባ_ቢሶራ፦ ይህም ቅዱስ በግብጽ አገር እግዚአብሔርን በምትወድ መጺል በምትባል ከተማ ኤጲስቆጶስ ሆነ። ዲዮቅልጥያኖስም ነግሦ ክርስቲያኖችን በሚያሠቃያቸው ጊዜ ክብር ይግባውና በክርስቶስ ስም ደሙን ያፈስ ዘንድ ይህ አባት ወደደ። 🌼 ሕዝቡንም ሀሉ ሰብስቦ በቤተ መቅደሱ ፊት በዐውደ ምሕረቱ አቆማቸው ሊጠብቁት የሚገባውን ለጽድቅ የሚያበቃቸውን ትእዛዝ ሁሉ አዘዛቸው። ከዚህም በኋላ ክብር ይግባውና በክርስቶስ ስም ደሙን ማፍሰስ እንደሚሻ ነገራቸው ይህንንም በሰሙ ጊዜ ታላቆችም ታናሾችም በላዩ አለቀሱ። "የሙት ልጆች እንሆን ዘንድ የምትተወን ምን ያደርግልሃል እኛስ እንድትሔድ አንለቅህም" አሉት ሊይዙትም ቃጡ ግን አልተቻላቸውም ተውትም እርሱም ወደ ክብር ባለቤት ክርስቶስ አደራ አስጠበቃቸውና ሰላምታ ሰጥቷቸው ከእነርሱ ዘንድ ወጥቶ ተጓዘ። እነርሱም መሪር ልቅሶን እያለቀሱ ሸኙት። 🌼 ስማቸው ቢስኮስ ፊናቢክስ ቴዎድሮስ የሚባሉ ኤጲስቆጶሳት አብረውት ሔድ መኰንኑ ወደ አለበት አገርም ደርሰው የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ። እርሱም መኰንኑ አሠቃያቸው ኤጲስቆጶሳትም እንደሆኑ አውቆ ሥቃያቸውን አበዛ እሊህ አባቶች ግን በታላቅ ትዕግሥት የጸኑ ናቸው። ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ ያጸናቸዋልና። 🌼 ከዚህም በኋላ መኰንኑ ራሶቻቸውን በሰይፍ ይቆርጧቸው ዘንድ አዘዘ የሕይወት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። የቅዱስ ቢሶራ ሥጋው ግን ንሲል በሚባል አገር እስከ ዛሬ ይኖራል። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።                                                ✝ ✝ ✝ 🌼 "#ሰላም_እብል_ለዓቢይ_መንክሩ። ዘተክሥተ ዮም በውስተ ዳቤሩ። ፈለገ ማይ ይሚጡ እንዘ ይመክሩ። ተሠጥቀ ኰኵሕ እንተ ዐላውያን አንበሩ። #ሶበ_ሚካኤል_ዘበጦ_በበትሩ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የመስከረም_9።                             ✝ ✝ ✝ 🌼 #የዕለቱ ምስባክ፦ "ደምፁ ወተሐምገ ማያቲሆሙ። ወአድለቅለቁ አድባር እምኃይሉ። ፈለገ ዘይውኅዝ ያስተፌሥሕ ሀገረ እግዚአብሔር"። መዝ 45፥3-4። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 8፥35-ፍ.ም፣ ያዕ 1፥2-13 እና የሐዋ ሥራ 20፥16-22። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 7፥24-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ያዕቆብ ዘሥሩግ ቅዳሴ ነው። መልካም የቅዱስ ሚካኤል የተአምራት በዓል፣ የንጉሥ ቅዱስ ያሳይ የዕረፍት በዓል ለሁላችንም ይሁንልን።                 

🌼 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼                            ✝ ✝ ✝ 🌼 "#ሰላም_ለሙሴ_ሊቀ_ነቢያት ዘርእየ ሱራኄሁ ለጸባኦት፤ ዘተመጠወ እምእደዊሁ ኦሪተ በጾም ወበጸሎት"። ትርጉም፦ የሠራዊት ጌታን የብርሃን ወገግታ ያየ፤ በጾምና በጸሎት ከእጆቹም ኦሪትን (ሕግን) ለተቀበለ #ለሊቀ_ነቢያት_ለቅዱስ_ሙሴ ሰላምታ ይገባል። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_በተአምኆ_ቅዱሳን_ላይ።          

🌼 "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼                           ✝ ✝ ✝ 🌼 "#ሰላም_ለዘካርያስ_ካህን_ወነቢይ ዘርእዮ ለካህን ዐቢይ #ዘስሙ_ዮሴዕ ዘይነብር ውስተ ምሥዋዒሁ ለእግዚብሔር"። ትርጉም፦ በእግዚአብሔር መሠዊያ ውስጥ #ስሙ_ዮሴዕ የሚባል ታላቁን ካህን ተቀምጦ ላየው #ለካህኑና_ለነቢዩ_ለቅዱስ_ዘካርያስ ሰላምታ ይገባል። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ_በተአምኆ_ቅዱሳን_ላይ።                 

🌼 "በስመ አብ ወወልደ  ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። 🌼            🌼 #መስከረም ፰ (8) ቀን። 🌼 እንኳን #ለመጥምቀ_መለኮት_ለቅዱስ_ዮሐንስ አባት ለበራክዩ ልጅ ለካህንና ለነቢዩ ለሆነ ለከበረ #ለቅዱስ_ዘካርያስ_በንጉሥ_ሄሮድስ_እጅ_ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍቱ በዓልና #ለእግዚአብሔ_ሰው ለሆነ፣ ለየዋሁ፣ ለቅኑ፣ ለጻድቁ፣ ለነቢያት አለቃ #ለቅዱስ_ሙሴ_ለዕረፍት_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከከበረ_ቅዱስ_ዲማድዮስ ከግብጽ ደቡብ ደንጡ ከሚባ አውራጃ በሰማዕትነት ከዐረፈ፣ ምግቡ የአጋዝን ወተት ከሆነ በዕረፍቱም ጊዜ ብዙ ተአምራትን ከአደረገ ከከበረ #ከገዳማዊ_ከቅዱስ_ቂርቆስ ዕረፍት፣ #ከሰማዕቱ_ቅዱስ_ሉክዮስ ከመታሰቢያው፣ #ከቅዱስ_ኤርምያስና_ከቅዱስ_ዮሐንስ፣ #ከቅዱስ_አንዲዎና_ከቅዱስ_ኤልያኖስና ከመነኰስ #አሞንም_ከመታሰቢያቸወ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።                                                                                                      ✝ ✝ ✝ 🌼 #በዚች_ቀን_የዓመቱ_ወሮች_መቊጠራያ የሚሆን የመጀመሪያ ኮከብ ይወጣ ይኸውም መናዝል የሚለው ነው የዐሥራ ሁለቱ ወር ኮከቦች ከእልሐመል እስከ ሑት ያሉ መገብተ አውኅራ አሉ ምግብናቸውን ፈጽመው በዚች ቀን እንደገና አንድ ብለው የሚጀምሩበት ነው።                                                               ✝ ✝ ✝ 🌼 #ካህን_ወነቢይ_የበራክዩ_ልጅ #ቅዱስ_ዘካርያስ፦ ይህም ካህን ስለ ልጁ ዮሐንስ መወለድ የመላእክት አለቃ ገብርኤል በነገረው ጊዜ ነገሩን አምኖ አልተቀበለም። ስለዚህም ሕፃኑ እስቲወለድ ዲዳ ትሆናለህ አለው። በተወለደም ጊዜ አንደበቱ ተፈትቶ እግዚአብሔርን አመሰገነው የልጁንም ስም ዮሐንስ ነው ብሎ ጻፈ። እርሱና ሚስቱ በእግዚአብሔር ሕግ ያለ ነቀፋ የጸኑ ደጎች እንደሆኑ የከበረ ወንጌል ስለዚህ ምስክር ሆኗል። 🌼 ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስም በተወለደ ጊዜ ሊሰግዱለት የጥበብ ሰዎች መጡ። ሄሮድስም ስለ መንግሥቱ ፈራ ደነገጠም። ስለዚህም ጭፍሮቹን ልኮ በይሁዳ አገር የቤተ ልሔምንና የገሊላን ሁሉንም ሕፃናት ዕድሜያቸው ሁለት ዓመት የሚሆናቸውን ከዚያም የሚያንሱትን ገደላቸው ሰነፍ የሆነ ሄሮድስ ክርስቶስን ከሕፃናት ጋር እንደ ሚገድለው አስቦ ነበርና። 🌼 ከዚህም በኋላ የእግዚአብሔር መልአክ ለዮሴፍ በሕልም ተገልጾለት ስለአዘዘው ጌታችን ሕፃኑንና እናቱን እመቤታችንን ድንግል ማርያምን ይዞ ወደ ግብጽ አገር መጡ። ኤልሳቤጥ ግን ሕፃኗን ዮሐንስን ይዛ ወደ ዱር ወጣች ወደ ሲና በረሃም ሸሸች በዚያም ሕፃኗን እያሳደገች ሰባት ዓመት ኖረች ከዚህም እርሷ አረፈች ሕፃኑም በመምህርነት ለእሥራኤል እስከሚገለጥበት ጊዜ ድረስ በበረሀ ውስጥ ብቻውን ኖረ። 🌼 ሕፃናትንም ከገደላቸው በኋላ ዮሐንስ ክርስቶስ እንደሆነ ሄሮድስ አሰበ ተጠራጠረ ከአባቱ ከዘካርያስ ዘንድ ሕፃኑን ይሹ ዘንድ ወታደሮቹን ላከ ዘካርያስም "ሕፃኑ ያለበትን ወይም እናቱ ያለችበትን እኔ አላውቅም" አለ። ሄሮድስም ልጅህን "ካላመጣህልኝ እኔ እገድልሃለሁ" አለው። ዘካርያስም ከእርሱ ዛቻ የተነሣ አልፈራም ወታደሮቹንም አዝዞ በቤተ መቅደሱና በመሠዊያው መካከል ገደሉት ክብር ይግባውና እግዚአብሔርም ሥጋውን ሠወረ ደሙ ግን እንደ ደንጊያ ሆነች። 🌼 ካህናቱና ሕዝቡ እንደ ልማዳቸው ለጸሎት በመጡ ጊዜ ከካህናት አንዱ ወደ ቤተ መቅደስ ውስጥ ገባ። የረጋ ደምን አገኘ ከመጠዊያውም እንዲህ የሚል ቃልን ሰማ "እነሆ የበራክዩ ልጅ ዘካርያስ ተገደለ የሚበቀልም እስሚመጣ ደሙ ስትጮኽ ትኖራለች"። 🌼 እንዲህ የሚልም አለ ከዐሥራ ሁለቱ ደቂቀ ነቢያት የሆነ የበራክዩ ልጅ ዘካርያስ ይህ አይደለም ያ አልተገደለም በዕድሜው ኡረት በሚባል አገር ሞተ እንጂ ሥጋውም በዚያ ያለ ጥፋት ተገኝቶ ቤተ ክርስቲያን ሠርተውለታል። የዚህ ዘካርያስ ግን ሥጋው አልተገኘም ስለ መገደሉ የደሙ ድምፅ ምስክር ሆነ እንጁ። 🌼 ደግሞ እንዲህ ተባለ ሄሮድስ ሕፃናትን በገደላቸው ጊዜ ከአይሁድ አንድ ሰው መጥቶ "የእግዚአብሔር መልአክ ትወልዳለህ" ብሎ ነግሮት ለዘካርያስ ልጅ ተወልዶለታል "ምናልባት እርሱ ክርስቶስን ይሆን" አለው። ስለዚህ ሄሮድስ ሕፃኑን ዮሐንስን ይገድሉት ዘንድ ወታደሮችን ላከ። 🌼 ዘካርያስም ወታደሮችን እንዲህ አላቸው "ሕፃኑን እኔ ወደሌላ ቦታ ወስጄዋለሁ ከእኔ ጋራ መጥታችሁ ራሳችሁ ከዚያ ቦታ ውሰዱት" ወደ ቤተ መቅደስም እስከ አስገባቸው ድረስ ወታደሮቹ አብረውት መጡ። እርሱም ሕፃኑን ልጁን በመሠዊያው ጠርዝ ላይ አኑሮ ጸለየበት ይህም የልጁን መወለድ የእግዚአብሔር መልአክ ለእርሱ የነገረበት ነው። 🌼 ያን ጊዜም የእግዚአብሔር መልአክ ሕፃኑን ዚፈታ ወደሚባል በረሀ ነጥቆ ወሰደው ሕፃኑንም ባላገኙት ጊዜ አባቱን ዘካርያስን ገደሉት። ስለዚህም ጌታችን አይሁድን "በቤተ መቅደሰ መካከል የገደላችሁት የዘካርያስ ደም በላያችሁ ይደርሳል" አላቸው ለመገደሉ ምክንያት አይሁድ ናቸውና እንዲህ አለ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በካህኑ ቅዱስ ዘካርያስ ጸሎት ይማረን በረከቱም  ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።

የጅት ባሕር አምባ ቅዱስ ገብርኤል ቤተከርስቲያን በመሬት መንሸራተት ከፍተኛ ጉዳት ደረሰበት። በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት አዋበል ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር የሚገኘው የጅት ባሕር አምባ ቅዱስ ገብርኤል
+2
የጅት ባሕር አምባ ቅዱስ ገብርኤል ቤተከርስቲያን በመሬት መንሸራተት ከፍተኛ ጉዳት ደረሰበት። በምሥራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት አዋበል ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር የሚገኘው  የጅት ባሕር አምባ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በደረሰበት የመሬት መንሸራተት ምክንያት  ከአገልግሎት ውጭ መሆኑን ተገልጿል። ቤተ ክርስቲያኑ ባሳለፍነው 2017 ዓ.ም እድሳት ላይ እንደነበር የተገለጸ ሲሆን በያዝነው 2018ዓ.ም ለምረቃ ይበቃል ተብሎ ቢጠበቅም በደረሰበት ጉዳት  በውስጡ የነበሩት ንዋየ ቅድሳትን ጨምሮ የጉዳቱ ሰለባ መሆናቸውም ተመላክቷል። የቅዱስገብርኤል ና የጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ታቦታት ጉዳት ሳይደርስባቸው  የቤተክርስቲያኑ አገልጋዮች  ወደ ሌላ ቦታ በማሸሽ መታደግ እንደተቻለም ታውቋል። የመሬት ናዳው በዙሪያው በሚገኝ  የምዕመናን የሰብል  ላይም  ከፍተኛ ጉዳት ማድረሱ ተገልጿል። ለወደፊቱም ሀገረ ስብከቱም ሆነ ወረዳ ቤተክህነቱ ጉዳት የደረሰባቸውን ንዋያተ ቅድሳት እንዲሟሉ ምዕመናን ከደረሰባቸው ልቅሶና ሀዘን እንዲጽናኑ ለወደፊቱም ከስጋት ነፃ በሆነ ቦታ እንዲሰፈሩ ከሚመለከታቸው አጋር አካላት ጋር መስራት እንደ አለበት ሲሉ አስበዋል። © EOTC MK TV

🌼 #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኀይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝጰ83፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 13፥13-22፣ 1ኛ ጴጥ 3፥ 14-18 እና የሐዋ ሥራ 16፥16-22። የሚነበበው ወንጌል ማር 1፥23-29። የሚቀደሰው ቅዳሴ የእመቤታች ማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም በዓል የቅድስት ሐና የልደት በዓልና የአባ ዲዮስቆሮስ የዕረፍት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።