ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Kanalga Telegram’da o‘tish
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Ko'proq ko'rsatish636
Obunachilar
Ma'lumot yo'q24 soatlar
-47 kunlar
-1230 kunlar
Postlar arxiv
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ጳጒሜን ፫ (3) ቀን።
❤ እንኳን #ለሊቀ_መላእክት_ለቅዱስ_ሩፋኤል ለተሾመበት፣ #ቅዱስ_ጦቢትን_ዐይኑን_ለአበራለትና ልጁ #ቅዱስ_ጦብያን_ለረዳበት፣ የራጉኤልን ልጅ #ሣራን_ተቆራኝቷት_የነበረው_አስማንድዮስ_ጋኔን ላወጣላት በዓል (ታሪክ በጽሐፈ ጦብት ላይ ያንብቡ)ና #ለሊቀ_ካህን_ለኢየሱስ_ክርስቶስ ምሳሌ ለሆነ #ለካህኑ_ቅዱስ_መልከፄዴቅ ለመታሰቢያ በዓሉ በሰላም አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ሰንዱን ከሚባል አገር #ከቅዱስ_ሰራጵዮን ዕረፍት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሊቀ_መላእክት_ቅዱስ_ሩፋኤል፦ እርሱም ከመላእክት አለቆች ሦስተኛ የሆነ ነው። ደግሞም ከእስክንድርያ ውጭ በደሴት የታነፀች ቤተ ክርስቲያኑ በከበረ ሊቀ ጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን በውስጧ ተአምር የተገለጸባት የከበረችበት ነው።
❤ ይህም እንዲህ ነው ሀብታም ሴት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ መጥታ ሳለ ከእርሷ ጋርም ብዙ ሰው ነበረ። ከባሏም የወረሰችው ብዙ ገንዘብ አላት በሊቀ ጳጳሳቱ ቤት አንጻር ያለውን ኮረብታ አስቆፈረችው በጥቅምት ወር ዐሥራ ስምንት ቀን እንደጻፍን የወርቅ መዝገብ ተገለጠ። በዚያም ወርቅ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትን አነፀ ከእርሳቸውም አንዲቱ የመላእክት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ ሩፋኤል በስሙ የታነፀች ይህች ናት። ሥራዋንም በፈጸመ ጊዜ እንደዛሬው በዚች ቀን አከበራት።
❤ ብዙ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጸች ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና። የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው። ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔርም በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮኹ ያን ጊዜ ይህ የከበረ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ እንዲህ አለው "እግዚአብሔር አዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጽ ጸጥ ብለህ ቁም"። አንበሪውም ጸጥ ብሎ ቆመ አልታወከም በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆነ።
❤ ይቺም ቤተ ክርስቲያን እስላሞች እስከተነሡበት ዘመን ኖረች ከዚህም በኋላ ሁለተኛ ያ አንበሪ ተናወጸ ደሴቲቱም በላይዋ ከሚኖሩ ብዙ ሕዝብ ጋራ ሠጠመች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን የመልአክ ቅዱስ ሩፋኤል በረከቱ ከእኛ ጋራ ይኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ዳግመኛም_የቊስጥንጥንያ_ሊቀ_ጳጳሳት #አባ_ዮሐንስ_ጻድቅ_ለሆነ_ንጉሥ_አኖሬዎስ_ተናገረው፦ እንዲህም አለው "ንጉሥ ሆይ እኛ ወዳንተ ልንመጣ በመርከብ እንደተሳፈርን ዕወቅ በጒዞ ላይ ሳለንም በቀዳሚት ሰንበት ቀን በደሴት ውስጥ ታናሽ ቤተ ክርስቲያን አየን ወደ ወደቡም ደርሰን በዕለተ እሑድ ሥጋውን ደሙን እንቀበል ዘንድ ወደርሷ ሔድን።
❤ ለዚያች ቤተ ክርስቲያንም በጐኗ ታናሽ ገዳም አገኘን በውስጧም ወንድሞች መነኰሳት አሉ በክብር ባለቤት ጌታችንም ፈቃድ ወደ ርሳቸው ደረስን። መነኰሳቱንም "በቀደሙ አባቶች ዘመን የተጻፈ አሮጌ መጽሐፍ በእናንተ ዘንድ እንዳለ እጽናናበት ዘንድ እርሱን ሰጡኝ" አልኳቸው።
❤ እንዲህም ብለው መለሱልኝ "እኛ ትርጓሜያቸውን የማናውቀው መጻሕፍቶች በዕቃ ቤት አሉ"። እኔም "አያቸው ዘንድ ወደዚህ አምጡልኝ" አልኳቸው። በአመጡአቸውም ጊዜ መረመርኳቸው ጌታችንም በደቀ መዛሙርቱ ፊት ያደረጋቸውን ኃይሎችና ድንቆች ተአምራቶችን ስለ ሰማይና ምድርም ጥንተ ተፈጥሮ አገኘሁ።
❤ ሁለተኛም ስመረምር ስለ ሰባቱ ሊቃነ መላእክት ሹመትና መዐርግ አባቶቻችን ንጹሐን ሐዋርያት የጻፉትን አገኘሁ ይኸውም ጌታችን በደብረ ዘይት ከእሳቸው ጋራ እያለ የመለኮቱን ምሥጢር በገለጠላቸው ጊዜ። ሐዋርያትም እንዲህ ብለው እንደለመኑት "ጌታችንና ፈጣሪያችን ሆይ የከበረ የሩፋኤልን ክብሩን ታስረዳን ዘንድ እንለምንሃለን በየትኛው ዕለት በየትኛው ወር ሾምከው"። ከባልንጀሮቹ የመላእክት አለቆችም ትክክል ነውን የበዓሉን መታሰቢያ ያደርጉ ዘንድ በዓለም ውስጥ ስለርሱ እንድናስተምር እርሱም በመከራቸው ጊዜ ይረዳቸው ዘንድ በአማላጅነቱም በአንተ ዘንድ ይቅርታን ያገኙ ዘንድ።
❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዘዘና ከሦስተኛው ሰማይ ሦስቱ የመላእክት አለቆች ሚካኤል፣ ገብርኤልና ሩፋኤል መጡ በታላቅ ደስታም ለክብር ባለቤት ለጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰገዱ። ጌታችንም ሩፋኤልን እንዲህ አለው "የክብርህን ገናናነት የባልንጀሮችህንም ልዕልናቸውን እንዲያውቁ ለሐዋርያት ንገራቸው"። ያን ጊዜም ለጌታችን ሰገደ ይነግራቸውም ዘንድ ጀመረ እንዲህም አላቸው "ደገኛው የመላእክት አለቃ ሚካኤል ለሁሉም መላእክት አለቃቸው ነው ስሙም ይቅር ባይ ይባላል"።
❤ "ሁለተኛም የመላእክት አለቃ ገብርኤል የስሙ ትርጓሜ አገልጋይም ጌታም የሆነ የዓለሙ ሁሉ እመቤት የሆነች አምላክን የወለደች ቅድስት ድንግል ማርያምን ያበሠራት ነው"። "የእኔም ስሜ ሩፋኤል ነው ይህም ደስ የሚያሰኝ ቸር መሐሪ ቅን የዋህ ማለት ነው እኔም ኃጢአተኞችን በእግዚአብሔር ዘንድ አልከሳቸውም ከኃጢአታቸው በንስሓ እስኪመለሱ ስለ ቅንነቴ በእነርሱ ላይ እታገሣለሁ እንጂ። በሃያ ሦስቱ የመላእክት ነገድ ሠራዊት ላይ እግዚአብሔር የሾመኝ እኔ ሩፋኤል ነኝ እግዚአብሔር አብን ይቅር ባይ ልጁን አጽናኝና አዳኝ የሆነ መንፈስ ቅዱስን እናመሰግነው ዘንድ።
❤ በደብረ ጽዮን በሚደረገው የሺህ ዓመት ተድላ ደስታ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የክብር ጽዋን በሚሰጣቸው ጊዜ ለቅዱሳኖቹ በጎ ነገርን እንድሰጣቸው እግዚአብሔር ያዘዘኝ ሩፋኤል እኔ ነኝ። ደግሞም በዚች ቀን ከዕፀ ሕይወት ዐጽቅ ወስጄ ለተመረጡ ክርስቲያኖች በእጄ እንድሰጣቸው እግዚአብሔር ያዘዘኝ ሩፋኤል እኔ ነኝ። የሰማያት መዛግብትም ከእጄ በታች ተጠብቀው የሚኖሩ እኔ ሩፋኤል ነኝ። እኔም እግዚአብሔር እንዳዘዘኝ እከፍታቸዋለሁ እዘጋቸዋለሁም።
❤ በምድር ሰው ለባልንጀራው ስለ ስሜ በጎ ነገር ቢያደርግ እኔ በመከራው በችግሩ ረዳዋለሁ ወይም የሹመቴን ነገር የሚጽፍ ወይም ከቅዱሳን ጋራ ስሜን የሚያስብ ወይም በስሜ ለቊርባን የሚሆነውን የሚሰጥ ወይም በበዓሌ ቀን ምጽዋትን የሚሰጥ ይኸውም እግዚአብሔር በሊቃነ መላእክት ክብር የሾመኝና ያከበረኝ ጳጕሚን ሦስት ቀን ነው። ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት እስከማስገባው በብርሃን ሠረገላ እኔ እሸከመዋለሁ በምድር ላይ ከቶ እንደርሱ ያለ የማይገኝ መዐዛው እጅግ ጣፋጭ በሆነ ሽቱ ነፍሶቻቸው እርሱን በማሽተት ደስ እንዲላቸው አደርጋለሁ።
❤ ሐዋርያት ሆይ በእግዚአብሔር ፊት እስከምትቆሙ እጠብቃችሁ ዘንድ ከእኔ ርዳታን ሹ። የዚህ የመላእክት አለቃ የከበረ መልአክ ሩፋኤል ተአምራቶቹ ብዙ ናቸው ስለእኛ ይማልድ ዘንድ የበዓሉን መታሰቢያ ልናደርግ ይገባናል። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በመልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል አማላጅነት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ጳጒሜን ፪ (2) ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት አንዱ ለሆነው ሐዋርያው #ቅዱስ_ጳውሎስ_መልእክት_ለጻፈለት ለከበረ #ለሐዋርያው_ለቅዱስ_ቲቶ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሐዋርያው_ቅዱስ_ቲቶ፦ የዚህም ቅዱስ ትውልዱ ቀርጤስ ከሚባል አገር ነው። እርሱም ለዮናናውያን ወገን ለሆነ ለአገረ ገዥው እኅት ልጅዋ ነው። ከታናሽነቱም የዮናናውያንን ትምህርትና ፍልስፍና ተምሮ እጅግ አዋቂ ሆነ በጠባዩም ቅን ሥራው ያማረ ለድኆችና ለችግረኞች መራራት የሚወድ ነው። ከሌሊቶችም በአንዲቱ "ቲቶ ሆይ ስለ ነፍስህ ድህነት ተጋደል ይህ ዓለም አይጠቅምህምና" የሚለውን በሕልሙ አየ። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ደነገጠ ምን እንደሚሠራም አላወቀም።
❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት በተሰማ ጊዜ ብዙዎች ሰዎችም ተአምራቱን እርስበርሳቸው ተነጋገሩ የአክራጥስ መኰንንም ሰምቶ አደነቀ ዕውነት እንደሆነ ወይም እንዳልሆነ ወይም የሥራይ እንደሆነ ሊያውቅ ሽቶ የሚልከው ብልህ ሰው ፈለገ የእኅቱንም ልጅ ቲቶንን መረጠው ከእርሱ የሚሻል የለምና። ሲልከውም ታላቅና ጥልቅ የሆነ ምርመራ እንዲመረምር አዘዘው።
❤ ቲቶም ከይሁዳ ምድር በደረሰ ጊዜ የመድኃኒታችንን ድንቆች የሆኑ ተአምራቶቹን አየ ሕይወትነት ያላቸው ትምህርቶቹንም ሰማ። ከዮናናውያንም በትምህርታቸውና በሥራቸው መካከል ታላቅ የሆነ መራራቅን አግኝቶ የዮናናውያን ሃይማኖታቸው የቀናች እንዳልሆነች ለይቶ ዐወቀ።
❤ ከዚህም በኋላ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ አመነ፤ ደቀ መዝሙሩም ሁኖ ተከተለው። ወደ እናቱ ወንድም ወደ አገረ ገዥውም መልእክትን ላከ የክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተምረውና የሚሠራው ዕውነት እንደሆነ ነገረው።
❤ ጌታችንም ከሰባ ሁለቱ ደቀ መዛሙርቱ ውስጥ የተቆጠረ አደረገው ከዕርገቱም በኋላ ከሐዋርያት ጋር የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀብሎ ከእሳቸው ጋር በሀገሮች ሁሉ ዙሮ አስተማረ። ጌታችንም ጳውሎስን ጠርቶ ሐዋርያው በአደረገው ጊዜ ያን ጊዜ ሐዋርያ ጳውሎስን ተከተለው በብዙ አገሮችም ወንጌልን ሰበከ።
የከበረ ቅዱስ ጳውሎስም በሮሜ ከተማ ምስክር ሆኖ ከሞተ በኋላ ቅዱስ ቲቶ ወደ ሀገረ አክራጥስ ተመለሰ ቤተ ክርስቲያንም ሠርቶ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን ሾመላቸው በዙሪያቸው ላሉ አገሮችም እንዲሁ አደረገ።
❤ ከዚህም በኋላ ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ፈጽሞ ወደ ወደደው እግዚአብሔር ጳጒሜን 2 ቀን ሔደ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለከ_ቲቶ_መስተሳልም። ለእከ ጳውሎስ ዘኮንከ እንበለ ድካም። ከመ ገሠጸከ በቃል ወይቤለከ በሕልም። ተጋደል በእንተ ነፍስከ በገድለ ሃይማኖት ፍጹም። ኢይበቊዓከ ዝንቱ ኃላፊ ዓለም"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጳጒሜን_2።
+3
❤ #ብፁዕ_ወቅዱስ_አቡነ_ማትያስ_ፓትርያርክ ሐዋርያዊ አገልግሎታቸውን ጨርሰው #ዛሬ_ጳጒሜን_1_ቀን 2017 ዓ.ም በሰላም አዲስ አበባ ገቡ።
❤ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት #ሐምሌ_1_ቀን_2017 ዓ.ም ወደ አሜሪካ ያቀኑ ሲሆን በዛሬው ዕለት ማለት ጳጒሜን 1 ወደ ኢትዮጵያ ተመልሰዋል።
❤ ቅዱስነታቸው ወደ ኢትዮጵያ መመለሳቸውን ተከትሎ ክብረ አበውን አሠረ ሐዋርያትን መሠረት በማድረግ ከቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ጀምሮ በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የእንኳን ደህና መጡ አቀባበል ተደርጎላቸዋል።
❤ የብፁዕ ወቅዱስ አባታችን የአቡነ ማትያስ ቡራኬ አይለየን።
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ እንኳን #ለጾመ_ዮዲት_ለጾመ፤ የኢትዮጵያ ንጉሥ #ዐፄ_ናኦድ_ስምንተኛው_ሺህ እንዳያዩት ለጾሙት (የፈቃድ ጾም) እግዚአብሔር አምላከ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ "ሰብአ ነነዌ #ጸዊሞሙ_ተማኅሊሎሙ ድኅኑ እሞቶሙ" ትርጉም፦ የነነዌ ሰዎች #ጾመውና_ምሕላ ይዘው ከሞት ዳኑ። #ሊቁ_ቅዱስ_ያሬድ_በጾመ_ድጓው_ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ አምላከ ቅዱሳን ልዑል እግዚአብሔር ጾሙን፣ ጸሎቱንና ምሕላውን ተቀብሎ በአዲሱ ዓመት በዘመነ ቅዱስ ማርቆስ በአገራችን ኢትዮጵያዊ ያለውን የእርስ በእርስ ጦርነት አስወግዶ ሰላም፣ ፍቅርን፣ አድነትንና መተሳሰብን ይላክል፤ በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖታችን በቅዱስ ሲኖዶስ በአባቶችን ዘንድ ያለው መከፍፈል አስወግዶ አንድ ያድርግልን። መልካም የጾም፣ የጸሎትና የምሕላ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #የተባረከ_የጳጒሜን_ወር_ባተ።
❤ #ጳጒሜን ፩ (1) ቀን።
❤ እንኳን #ለወንጌላዊው_ለቅዱስ_ዮሐንስ ረድእ #ለሐዋርያውና_ለሰማዕቱ_ለከበረ_ቅዱስ_ዑቲኮስ ለዕረፍት በዓል፣ #ለአባ_ሖር_ወንድም ለሰማዕቱ #ለቀሲስ_ቅዱስ_አባ_ብሶይ_ለዕረፍት በዓል አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ ከከበሩ #ከአባ_ጳኩሚስና_ከአባ_ሰራብዮን ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #በዚች_ቀን_መጥምቀ_መለኮት_ቅዱስ_ዮሐንስ ሄሮድስን የወንድምህን የፊልጶስን ሚስት ሄሮድያዳን ማግባት የለብህም ብሎ ይገስጸው ስለነበር በሳምንቱ በልደቱ ቀን መስከረም 2 እስኪገለው በዛሬው ዕለት ወደ እስር ቤት ያስገባበት ነው።
✝ ✝ ✝
❤ #የሐዋርያው_የቅዱስ_ዮሐንስ_ረድእ_ቅዱስ_ዑቲኮስ፦ ይህም ቅዱስ ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስን ሲያገለግለውና ሲታዘዘው ኖረ። ከዚያም ከሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ ጋራ ሔደ እርሱም የክብር ባለቤት በሆነ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም እንዲሰብክ አዘዘው በአረማውያንና በዮናናውያንም መካከል ሰበከ። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስንም ወደማወቅ ብዙዎችን መለሳቸው የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው።
❤ የጣዖታት ቤቶችን አፍርሶ አብያተ ክርስቲያናትን ሠራ። ከሀድያንም ብዙ መከራ ደረሰበት መታሠርና ብዙ ቀኖች ግርፋቶችን በመቀበል የእግዚአብሔርም መልአክ ወደ እሥር ቤት ከምግብ ጋር መጥቶ ይመግበዋል።
❤ ከዚህም በኋላ ከእሳት ውስጥ ጣሉት እሳቱም ከቶ አልነካውም ሁለተኛም ለአንበሶች ጣሉት እነርሱም እንደ በጎች ሆኑለት።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ ቊስጥንጥንያ አገር ሔደ ሲሔድም የእግዚአብሔር መልአክ ይመራውና ያጸናናው ነበር ተጋድሎውንም ፈጽሞ በበጎ ሽምግልና ጳጉሜን 1 ቀን ወደ እግዚአብሔር ሔደ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሐዋርያው ቅዱስ ዑቱኮስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #የአባ_ሖር_ወንድም_ቀሲስ_ቅዱስ_ብሶይ፦ ይህም ቅዱስ ከአንጾኪያ አገር ክብር ካላቸው ወገኖች ውስጥ ነው ስለ ዕውቀቱና ስለ ሃይማኖቱ ጽናት ቅስና ተሾመ።
❤ ወንድሙ አባ ሖርና እናቱ ወደ ግብጽ አገር ሒደው በሰማዕትነት ከሞቱ በኋላ እርሱም ተነሥቶ ወደ እስክንድርያ ሥጋቸውን ያይ ዘንድ ሔደ። ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች ሰጠ ከሦስት እንጀራና ከሚመረጐዛት ከአንዲት የሰኔል በትር በቀር ምንም አልያዘም ነበር።
❤ ወደ እስክንድርያ አገርም በደረሰ ጊዜ የዘመዶቹ በድን ወዳለበት ሰዎች መርተው አደረሱት የእናቱንና የወንድሙንም ሥጋ በአየ ጊዜ ከእርሳቸው ስለ መለየቱ መሪር ልቅሶን አለቀሰ።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ መነኰንኑ ሒዶ በፊቱ ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። ለመኰንኑም የአባ ሖር ወንድም እንደሆነ ነገሩት መኰንኑም ታላቅ የደንጊያ ምሰሶ በሆዱ ላይ እንዲአቆሙበት አዘዘ ይህንንም በአደረጉበት ጊዜ ነፍሱን በእግዚአብሔር እጅ ውስጥ ሰጠ።
❤ ከዚህም በኋላ ደግሞ ሥጋውን ከወንድሙና ከእናቱ ሥጋ ደግሞ ቊጥራቸው ሰማንያ ስምንት ከሆነ ከሌሎች ሰማዕታት ሥጋ ጋር በአንድነት ያቃጥሉ ዘንድ መኰንኑ አዘዘ ወደ እሳት በጨመሩአቸውም ጊዜ ከቶ እሳቱ አልነካቸውም።
❤ ምዕመናን ሰዎችም መጥተው የከበሩ የአባ ሖርና የወንድሙ የአባ ብሶይን የእናታቸውንም ሥጋ ወሰዱ። አገርዋ ዲብቅያ የሚባል የቅድስት ዳሞንንም ሥጋ አገሩ በረሞን ከሚባል የቅዱስ ቢማኮስም ሥጋ ጡልያ ከሚባል አገር የመጣ የውርሱኑፋን ሥጋም አብስላሲ ወደሚባል አገር እስከሚያደርሷቸው በመርከብ ጫኗቸው። የስደቱ ወራት እስከሚፈጸም አክብረው ወስደው በመልካም ቦታ አኖሩዋቸው።
❤ ከዚህም በኋላ አብያተ ክርስቲያን ተሠርቶላቸው ሥጋቸውን በውስጣቸው አኖሩ ከእርሳቸውም ተአምራት ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆኑ። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በእሊህ ሰማዕታት ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የጳጕሜን 1 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለዑቲኮስ_ዘተሰምየ_ሱታፎ። ለወንጌላዊ ዮሐንስ ለንጹሐ መላእክት ዘተዐጽፎ። መኰንን ዕልው አመ ውስተ እሳት ገደፎ። ካዕበኒ እምህየ ለአናብስት አኅለፎ። በአናብስት ስእኑ ይግሥሥዎ ወእሳት ይልክፎ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የጳጒሜን_1።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ ጽድቀ ወምጽዋተ ያበድር እግዚአብሔር። እግዚአብሔር ይሁብ ክብረ ወሞገሰ። እግዚአብሔር ኢያስተፄንሶሙ እምበረከቱ ለእለ የሐውሩ በየዋሃት"። መዝ 83፥11። የሚነበቡት መልዕክታት ፊል 1፥12-25፣ 1ኛ ዮሐ 5፥1-6 እና የሐዋ ሥራ 18፥21-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 14፥1-7። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ ወልደ ነጎድጓድ ቅዳሴ ነው። መልካም የጾም ጊዜና በዓል ለሁላችን ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፴ (30) ቀን።
❤ እንኳን #ከዐሥራ_ሁለቱ_ደቂቀ_ነቢያት አንዱ ለሆነው ለታላቁ ነቢይ #ለቅዱስ_ሚልክያስ_ለዕረፍት በዓል፣ #ጌታችን በባሕር ውስጥ በሊቀ ሐመር አምሳል ለሐዋርያው #ቅዱስ_እንድርያስ_ለተገለጠለትና ድንቅ ተአምር ላደረገበት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰበው፦ ከሀገረ ፈርማ ኤጲስቆጶስ #ከአባ_ሙሴ_ዕረፍት እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ነቢዩ_ቅዱስ_ሚልክያስ፦ ይህም ነቢይ የእስራኤል ልጆች ከተሰደዱበት ከባቢሎን ሀገር በተመለሱ ጊዜ የእግዚአብሔርን ትእዛዝ በመተላለፋቸው ገሥጿቸዋል።
❤ ሁለተኛም ነቋር ስለሆነ መሥዋዕት ስለ አሥራትና በኵራት ገሥጿቸዋል። በዚህ ነቢይ አንደበት እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ተናግሯልና "ርኅራኄ አድርጋችሁ ምጽዋትን መጽውቱ፣ ዐሥራቴንና በኵራቴንም አስገቡና እስቲ ፈትኑኝ እኔ ከሰማይ ዝናሙን ባላወርድላችሁ በረከትንም አስቲበቃችሁ ባልጨምርላችሁ የምድራችሁንም ፍሬ ነቀዝና መሰክ እንዳይበሉት እከለክላለሁ"።
❤ ዳግመኛም ከክብር ባለቤት መድኃኒታችን ክርስቶስ አስቀድሞ መጥምቁ ዮሐንስ ስለ መምጣቱ ስለ ነቢዩ ኤልያስም ተናገረ። ደግሞ ስለ አይሁድ የሥርዓተ ክህነት ፍጻሜ ተናገረ በአሕዛብም አገር ውስጥ ለእግዚአብሔር የሚቀበላቸውን መሥዋዕት የሚያሳርጉ ዕውነተኞች ንጹሐን ካህናት እንዳሉ ገለጠላቸው።
❤ በበጎ ተጋድሎውም እግዚአብሔርን ከአገለገለ በኋላ ከዚህ ዓለም በመፍለስ በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በነቢዩ ቅዱስ ሚልክያስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፴ (30) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊቷ_ጻድቅ ጌታችን በዕለተ አርብ የጠጣው መራራ ሐሞት በማሰብ #በቅል_ውስጥ_የሚገኘውን_መራራ_ፍሬ_ከኮሶ ጋር #በአንድነት_ደርጣ (አዋህዳ) ትመመገብ ለነበረች ለታላቋ እናት #ለቅድስት_ዜና_ማርያም_ለዕረፍቷ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ጻድቋ_ቅድስት_ዜና_ማርያም፦ ከአባቷ ከቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ከእናቷ ከቅድስት አመተ ማርያም በ11 መቶ ክፍለ ዘመን በቅዱስ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት በምድ ነጋሲ በጎጃም ምድር ግንቦት 30 ቀን የተወለደች ሲሆን ለአቅመ ሔዋን በደረሰች ጊዜ በንፅህ ድንግልና በምድረ ሂንፍራንስ ጣራ ገዳም አካባቢ በሚገኘው በአቡነ እንድርያስ ዋሻ ለ25 ዓመት በጾም በፀሎት ምንም አይነት የላመ የጣፈጠ እህል ሳትቀምስ በቅል ውስጥ የሚገኘውን መራራ ፍሬ ከኮሶ ጋር በአንድነት ደርጣ (አዋህዳ) በመዘፍዘፍ ከ3 ቀን በኃላ በመመገብ እስከ ሕይወቷ ፍጻሜ ድረስ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቀራንዮ አደባባይ ላይ የቀመሰውን መራራ ሐሞትን በማሰብ ሙሉ ሕይወቶን እየተመገበች ታላቅ ተጋድሎዋን ፈፅማለች፡፡ ከዚህ የተነሳ ሸክላ ማርያም ተብላ ትጠራ የነበረችው ቦታ ስያሜ ተቀይሮ ደሪጣ ዜና ማርያም ዋሻ ተብሎ እስከ አሁን ድረስ በስሞ እየተጠራ ይገኛል፡፡
❤ ከአቡነ እድርያስ ዋሻ በመቀጠል ከአዲስ አበባ ተነስተን ስንጓዝ አዲስ ዘመን ከተማ በስተቀኝ በኩል ተገንጥለን 15 ኪሜ ያክል የጥርጊያ መንገድ እንደተጓዝን በስሟ የተሰየመውን ደሪጣ ጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም ገዳም ላይ ቀሪ ሕይወቶን ምንም አይነት ዋሻ ባልነበረበት በከፍተኛ ተራራ ላይ እጅግ አስቸጋሪ ቀዝቃዛ አየር ባለበት ብርዱን፣ ፀሐዩን፣ ቁሩን፣ ረኃቡንና ጥሙን በመቋቋም ራቁቶን በመሆን መራራ ምግቦችን አዋህዳ በመመገብ በጾም በፀሎት በመትጋት አስቸጋሪ የሆነውን ተጋድሎዋን በመፈፀም በዚሁ በተቀደሰ ስፍራ ነሐሴ 30 ቀን በታላቅ ክብር አርፋለች፡፡
❤ በዚህም ወቅት ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያምና ከእልፍ አላፋት ቅዱሳ መላዕክት ጋር እንዲሁም ከሐዋርያት ፣ ከሰማዕታት ፣ ከጻድቃን ፣ ከደናግል ጋር በመሆን ከሰማይ በመውረድ በታላቅ ክብር ዕረፍቷን አክብሮላታል ታላቅ ኪዳንም ገብቶላታል፡፡
❤ በዚሁ በተቀደሰ ስፍራ ላይ ወይንም በአሁኑ ሰዓት መቃብሯ በሚገኝበት ዋሻ ቤተመቅደስ አካባቢ በተጋድሎዋ ጊዜ ራቁቷን በሆነች ሰዓት መላ ገላዋን የሸፈነላት ፀጉር በእየ ዛፎቹ ላይ እስከ አሁን ድረስ አለ፡፡ ይህም የጸጉር አምሳያ ከገዳሙ በመውሰድ ብዙ ሰዎች በቤታቸው በመታጠን ከአስም እንዲሁም ከተለያዩ በሽታዎች እየተፈወሱና እየዳኑ ሲሆን ታላላቅ ታምራትን እያደረገ ይገኛል፡፡
❤ በዚህ ገዳም ከሌሎች ገዳማት ለየት የሚያደርገው ታሪክ ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችንን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሰማይ በመውረድ ራሱ የባረከው ልዩ ታሪክ ያለው ጠበል የሚገኝ ሲሆን ይህም ጠበል በቦታው ላይ ሆኖ የተጠመቀ ፣ የጠጣ ፣ አልያም በአለበት ቦታ ሆኖ የተጠቀመ እስከ አሁን ድረስ መካን የሆኑ ሰዎች በፍጥነት ልጅ የሚያገኙ ከመሆናቸው ባሻገር ከማንኛውም ከተለያዩ በሽታዎች በመፈወስ ታላላቅ ታምራትን እየሰራ ይገኛል፡፡
❤ በ11ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ቅዱስ ላሊበላ በጌታችን በአምላካችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትዕዛዝ መሰረት ወደዚሁ ታላቅ ስፍራ በመምጣት የጻድቋ ማረፈያ መታሰቢያ ዋሻ ቤተ መቅደስ በመፈልፈል የሰራላት ሲሆን በመቀጠል አፄ ይስሐቅ በ14ተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ይህን ገዳም በስሟ በመገደም በዚሁ ዋሻ ውስጥም የጻድቋ የቅድስት ዜና ማርያም መቃብሯ እንዲሁም የመታሰቢያዋ ፅላት የሚገኝ ከመሆኑ አንጻር በአካባቢው ያሉት ሕዝበ ክርስትያን ከካህናት ጋር በመሆን ሥርዓተ አምልኮ በመፈፀም እየተገለገሉበት ይገኛሉ፡፡
❤ ይህ ዋሻም አስቀድሞ ሦስቱ ቅዱሳን ማለትም አቡነ እንድርያስ ዘጣራ ገዳም ፣አቡነ ተክለኃይማኖት ዘደብረ ሊባኖስ፣ ጻድቋ ቅድስት ዜናማርያም ዘደሪጣ ውስጥ ለውስጥ በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት በፀጋ እግዚአብሔር ይገናኙበት የነበረ ሲሆን በአሁን ሰዓትም እግዚአብሔር የመረጣቸው ቅዱሳን ይመላለሱበታል፡፡
❤ ለጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም የተሰጠ ቃል ኪዳን እግዚአብሔር አምላክ መርጦና ፈቅዶ በጻድቋ አማላጅነት ካለበት ስፍራ ተነስቶ የጻድቋ ደጃን የረገጠ ለ3 ግመል ጭነት ጤፍ ወይም የሦስት አህያ ጤፍ ያህል ነፍሳትን እምርልሻለሁ፤ ከሲዖልም እሳት ነፍሳትን አወጣልሻለሁ የሚል ቃል ኪዳን ለጻድቋ ቅድስት ዜና ማርያም ተሰቶታል። ከእናታችን ቅድስት ዜና ማርያም ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎቷም ይማረን!። ምንጭ፦ ማኅበረ ቅድስት ዜማ ማርያም ካዘጋጁት በራሪ ወረቀት የተወረደ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፯ (27) ቀን።
❤ እንኳን #ከሰባቱ_ሊቃነ_መላእክት_አራተኛ ለሆነው ለመላእክት አለቃ #ለቅዱስ_ሱርያል ለበዓሉ መታሰቢያ፣ ለአባቶቻችን #ለዐሥራ_ሁለቱ_ለቅዱስ_ያዕቆብ_ልጆች ለመታሰቢያቸው በዓል፣ በሊቀ ካህናት ኤሊ ዘመን #ለነቢዩ_ቅዱስ_ሳሙኤል_ለመጠራቱ ለመታሰቢያው በዓልና ሰብሲር ከሚባል አገር ለሆነ #ለቅዱስ_ብንያሚንና_ለእኅቱ_ለቅዱስ_አውዶክስያ ሰማዕትነ ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል በሰላም አደረሰን። በጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከእሰክድርያው_ቅዱስ_ፊቅጦርና #ከእናቱ_ሣራ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #የነገደ_ሥልጣናት_አለቃ_ቅዱስ_ሱርያል፦ ያላቸው ከኤረር መኻከል በኹለተኛዋ በራማ ውስጥ ከሚኖሩት፡፡ ከ፴ው ነገድ ውስጥ ሲኾኑ፤ ስለነዚኽ ነገደ መላዕክት ሊቁ ኤጲፋንዮስ በአክሲማሮስ ላይ ሲገልጽ "ወለሣልስ ጾታ ዐሠርቱ ስሞሙ ሥልጣናት ወሊቆሙ ሱርያል መልአክ ወአንበሮሙ በሣልስ ሰማይ እሉ እሙንቱ እለ ይጸውሩ አብዋቀ ብርሃን ወያደምፁ ለመላእክት በጊዜ ቅዳሴሁ ወስባሔሁ ለእግዚአብሔር ለዘክሮቱ ይደሉ ሰጊድ" ይላል ለስም አጠራሩ ስግደት ይግባውና ልዑል እግዚአብሔር ሦስተኛ ዐሥሩን ነገድ ሥልጣናት ሲላቸው አለቃቸው መልአኩ ሱርያል ይባላል፤ እነዚኽም የብርሃን ነጋሪት የሚይዙ ሲኾኑ መላእክትን በስባሔ ሲያነቁ ሲያተጉ የሚኖሩ እነዚኽ መላእክት ሲኾኑ፤ በራማ በሦስተኘው ከተማ አስፍሯቸዋል። ምንጭ፦ ዶክተር ሮዳስ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ተአምኆ ቅዱሳን በተረጎመበት ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ በዚችም ቀን ዳግመኛ አባቶቻችን #ዐሥራ_ሁለቱን_የያዕቆብን_ልጆች_ያስቧቸዋል። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን በረከታቸውም ትድረሰን ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ በዚችም ቀን #በሊቀ_ካህናት_ኤሊ_ዘመን #ነቢይ_ቅዱስ_ሳሙኤል ለመጠራቱ መታሰቢያ ሆነ። ይህንንም ነቢይ ተኝቶ ሳለ እግዚአብሔር ጠራው በኤሊም ፈንታ ነቢይና ካህን አድርጎ ለእስራኤል ልጆች ሾመው። የነቢዩ ቅዱስ ሳሙኤል በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሰማዕታት_ቅዱስ_ብንያሚንና_እህቱ #ቅድስት_አውዶከስያ፦ የእነዚህም ቅዱሳን ወላጆቻቸው እንግዳና መጻተኛን የሚወዱ ደጎች ክርስቲያኖች ናቸው ደግሞ ለክርስቲያኖች በሚገባ በበጎ ሥራ ሁሉ የተጠመዱ ቅድስና ያላቸው ናቸው። እሊህንም ቅዱሳን በወለዱዋቸውና በአሳደጓቸው ጊዜ ክርስቲያናዊት ትምህርትን አስተማሩአቸው።
❤ ከዚህም በኋላ ወደዚያች አገር ከሀዲ መኰንን መጣ ቅዱስ ብንያሚንም በሰማ ጊዜ የክብር ባለቤት ስለሆነ ክርስቶስ ደሙን ያፈስ ዘንድ ወደደ። በመኰንኑም ፊት ቁሞ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ ጽኑ የሆነ ሥቃይንም አሠቃይቶ ከዚያ በኋላ አሠረው። ወላጆቹና እኅቱ በሰሙ ጊዜ ወደርሱ መጡ አለቀሱ እጅግም አዘኑ እርሱም "የዚህ ዓለም ኑሮ እንደ ጥላ ፈጥኖ ያልፋል የወዲያኛው ኑሮ ግን ፍጻሜ የለውም" እያለ ያጽናናቸው ጀመረ።
❤ እኅቱ አውዶክስያም ይህን መልካም ትምህርቱን ከወንድሟ ሰምታ "ወንድሜ ሆይ ካንተ እንዳልለይ እግዚአብሔር ሕያው ነው አንተ የምትሞተውንም ሞት እኔም ከአንተ ጋራ እሞታለሁ" አለችው። ይህንንም ብላ ወደ መኰንኑ ሒዳ በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመኰንኑ ፊት ታመነች መኰንኑም ያሠቃያት ጀመረ። ከዚህ በኋላም ያለ መብልና ያለ መጠጥ በጨለማ ቤት ሃያ ቀን ከወንድሟ ጋር አሥረው እንዲያኖሩዋት አዘዘ።
❤ ከዚህም በኋላ ከዚያ አውጥቶ ከባድ የሆኑ ደንጊያዎችን በአንገታቸው አንጠልጥሎ ከጥልቅ ባሕር ጣላቸው የእግዚአብሔር መልአክም ወርዶ ከአንገታቸው ደንጊያዎቹን ፈታላቸው እነርሱም ከወደብ እስቲደርሱ በባሕሩ ላይ ዋኝተው ብጥራ ከምትባል ቦታ ደረሱ አንዲት ብላቴና ድንግልም አግኝታቸው ስባ አወጣቻቸው።
❤ ያን ጊዜም ወደ መኰንኑ ሔደው እርሱንና የረከሱ አማልክቶቹን ረገሙ ብዙ ቀኖችም ጭንቅ የሆነ ሥቃይን አሠቃያቸው። ሥቃያቸውም በአደከመው ጊዜ ራሳቸውን በሰይፍ እንዲቆርጧቸው አዘዘና ቆረጡአቸው። የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በሰማዕታት ቅዱስ ብንያሚንና በእህቱ ቅድስት አውዶከስያ በጸሎታቸው ይማረን። በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የነሐሴ 27 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለከ_ብንያሚን_ሰማዕት። ምቱረ ክሣድ በመጥባሕት። ወእለእኅትከ #ሰላም_አውዶክስያ_ኅሪት። እንዘ ትብል ሰሚዓ ዘትቤ ከመ ጽላሎት ንብረት። በትምህርትከ አጥባዕካ ለሞት"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የነሐሴ_27።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ወሳሙኤልኒ ምስለ እለ ይጼውዑ ስሙ። ይጼውዕዎ ለእግዚአብሔር ውእቱኒ ይሰጠዎሙ። ወይትናገሮሙ በዐምደ ደመና"። መዝ 98፥6-7። የሚነበቡት መልዕታት ዕብ 5፥1-10፣ 1ኛ ጴጥ 3፥14-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 3፥17-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 12፥26-31። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ቅዳሴ ነው። መልካም የመልአኩ የቅዱስ ሱርያል በዓልና የአቡነ ዘርዐ ቡሩክ የልደት በዓል። ለሁላችንም ይሁንልን።
ክርስቲያን ቀን ቀን ሕዝቡን ሲያስተምሩ በመዋል ሲመሽ ወደ ሐይቁ በመግባት ሲጸልዩ ያድሩ ነበር፡፡ በሐይቅ እስጢፋኖስና በዙርያው ለነበሩ አበው ማታ ማታ አንድ ብርሃን ወደ ሐይቁ ሲገባ ጠዋት ጠዋትም ሲወጣ ይታያቸው ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ አባታችን በገዳሙ አባቶች ልመናና በልዑል እግዚአብሔር ትዕዛዝ ወደ ሐይቅ ገዳም ገብተው አበምኔት ሆኑ፡፡
❤ ሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም ከደሴ 30 ኪሎ ሜትር ርቆ የሚገኝ ሲሆን የመሠረቱት ካልዕ ሰላማ የተባሉ ግብፃዊ ጻድቅ ናቸው፡፡ ሐይቅን አባ ሰላማ ካልዕና ዐፄ ድል ነአድ በ862 ዓ.ም ነው የቆረቆሩት። ገዳሙን ካቀኑት በኋላ "የማንን ታቦት እናስገባ?" ብለው ሲያስቡ ቶራ የምትባል እንስሳ ጭነት ተጭና ከመካከላቸው ተገኘች፤ ጭነቱን አውርደው ቢያዩት በሐር ጨርቅ የተጠቀለለ የቅዱስ እስጢፋኖስንና የቅዱስ ጊዮርጊስን ሁለት ታቦት አገኙ፡፡ በላዩም ላይ "ይህንን ታቦት በኢየሩሳሌም የሚኖሩ የተሰወሩ ቅዱሳን ከእግዚአብሔር ታዘው የላኩት ነው" የሚል ጽሑፍ አገኙ፡፡ ይህ ከሆነ ከ 400 ዘመን በኋላ ነው አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ወደዚህ ቦታ የመጡት፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ለ52 ዓመት ቀን ቀን መንፈሳዊ ሥራቸውን እየሠሩ ሌሊት ሌሊት ሐይቁ ውስጥ ቆመው ሲጸልዩ ያድራሉ፡፡
❤ አባ ኢየሱስ ሞዐ በሐይቅ እስጢፋኖስ በአበ ምኔትነት በቆዩባቸው 45 ዓመታት ከየገዳማቱ ቅዱሳን መጻሕፍትን በመገልበጥና በማሰባሰብ የመጀመርያው ዘመናዊ የቤተ ክርስቲያን ቤተ መጻሕፍት በሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳም እንዲቋቋም አድርገዋል፡፡ በዚሁ ገዳም ውስጥ የመጀመርያውን የቤተ ክርስቲያን ቋሚ ትምህርት ቤት በማቋቋም 800 መነኰሳትን በትምህርተ ሃይማኖት አሠልጥነው በንቡረ ዕድነት ማዕረግ ሾመው በመላ ሀገራችን እንዲሠማሩ አድርገዋቸዋል፡፡ ከእነዚህም ተማሪዎቻቸው መካከል አቡነ ተክለ ሃይማኖት (ደብረ ሊባኖስ)፣ አቡነ ኂሩተ አምላክ (ጣና ሐይቅ ዳጋ እስጢፋኖስ)፣ አቡነ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ (ቦረና)፣ አባ በጸሎተ ሚካኤል (ቦረና)፣ አቡነ ገብረ እንድርያስ (ቦረና)፣ አቡነ ሕዝቅያስ (ቦረና)፣ አቡነ እስትንፋሰ ክርስቶስ (ዳውንት)፣ አቡነ አሮን (መቄት)፣ አቡነ ተክለ ኢየሱስ ሞዐ (ሐይቅ)፣ አቡነ አላኒቆስ (ትግራይ)፣ አቡነ በግዑ (ሐይቅ)፣ አቡነ ሠረቀ ብርሃን (ሐይቅ)፣ አቡነ ብስጣውሮስ (ሐይቅ)፣ አቡነ ዮሴፍ (ላስታ) ዋና ዋናዎቹና በጣም ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ ጻደቁን ንጉሥ ዐፄ ይኩኖ አምላክንም በትምህርተ ሃይማኖት አንጸውና ኮትኩተው ያሳደጉት ጻድቁ አባታችን ናቸው፡፡
❤ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ መጥተው በሐይቁ ዳር ቆመው ሳለ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ በእግሩ በውኃው ላይ እየሄደ እያሳያቸው ተከትለውት እንዲሄዱ ነገራቸው። አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖትም ሐይቁን በእግራቸው ጠቅጥቀው ተራምደው ተሻግረው አቡነ ኢየሱስ ሞዐን አገኟቸው፡፡ እርሳቸውም አቡነ ተክለ ሃይማኖት ወደ እርሳቸው እየመጡ እንደሆነ በመንፈስ ዐውቀው ነበርና ሲያገኟቸው በጣም ተደስተው ከተቀበሏቸው በኋላ አመነኵሰዋቸዋል፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ እጅግ በጣም ብዙ መነኰሳትን አፍርተዋል፡፡ የመጀመሪያው መነኩሴ አባ እንጦንስ ነው፡፡ እንጦንስ መቃርስን፣ መቃርስ ጳኵሚስን፣ ጳኵሚስ ቴዎድሮስን፣ አቡነ አረጋዊንና 8ቱን ቅዱሳን አመነኰሱ፡፡ አቡነ አረጋዊም ወደ ኢትዮጵያ በ460 ዓ.ም መጥተው ክርስቶስ ቤዛን፣ አባ ክርስቶስ ቤዛም መስቀለ ሞዐን፣ መስቀለ ሞዐም አባ ዮሐኒን፣ አባ ዮሐኒም አባ ኢየሱስ ሞዐን፣ አባ ኢየሱም ሞዐም አቡነ ተክለ ሃይማኖትን አመነኰሱ፡፡ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ምን ያህል ቀደምትና ባለ ታሪክ አባት እንደሆኑ ከዚህ መረዳት ይቻላል፡፡
❤ በዮዲት ጉዲት እጅጉን ተጐድታ የነበረችው አገራችን ዳግም የወንጌሉ ብርሃን እንዲበራባት ሊቃውንት፣ እንዳይታጡባት፣ ቅዱሳት መጻሕፍት እንዳይቆነጻጸሉ፣ መነኰሳት አባቶች ወደ ደቡብ ኢትዮጵያ ወርደው ገዳማትን እንዲያስፋፉ ያደረጉት አቡነ ኢየሱስ ሞዐ ለቤተ ክርስቲያናችንና ለአገራችን ትልቅ ባለውለታ ናቸው፡፡ በተለይም በሐይቅ እስጢፋኖስ ያፈሯቸውን 800 ሊቃውንት መነኰሳት በመላዋ ኢትዮጵያ በመሰማራታቸው ዛሬ የምናያቸውን አብዛኛዎቹን ገዳማትና ቅዱሳት መጻሕፍት አቆይተውልናል፡፡ አባታችን ለ45 ዓመታት ሐይቅ እስጢፋኖስ ገዳምን በአበ ምኔትነት እያስተዳደሩ ከቆዩ በኋላ ኅዳር 26 ቀን 1292 ዓ.ም በዕለተ እሑድ ዐርፈዋል፡፡ ከአባታች ከአቡነ ኢየሱስ ሞዐ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ መዝገበ ቅዱሳን ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፮ (26) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጲያውያኑ_ጻድቃን ለአባታችን #ለአቡነ_ሀብተ_ማርያምና ታላቁ ገዳም ሐይቅ እስጢፋኖስ ላቀኑ #ለአቡነ_ኢየሱስ_ሞዐ ለጽንሰታቸው ዓመታዊ መታሰቢያ በዓል በዓል በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ሀብተ_ማርያም_ጽንሰት፦ " የኢትዮጵያ ንጉሥ እስክንድር በነገሠ በሺህ አራት መቶ ሰማንያ ስድስት ዓመተ ምሕረት ቅዱስ ፍሬ ብሩክ የሚባል አንድ ሰው በዚያች ሀገር ውስጥ ነበር፤ ይኸውም ከከበሩም ሰዎች ተለይቶ ብዙ ገንዘብ ያለው ባለ ጸጋ ነበር። በሕጋዊው ጋብቻ ስሟ ቅድስት ዮስቴና የምትባል ሴት አገባ፤ ይኽችውም ሴት በደግ ሥራ ሁሉ የተሸለመች ያጌጠች ነበረች።
❤ ብዙ ደግቷንና ትሩፋቷን ኋላ እንነግራችኋለን፤ ነገር ግን አስቀድመን በዚህ ዓለም ከሕጋዊ ባሏ ጋር በንጽሕ ጋብቻ እግዚአብሔር በመፍራት ምጽዋትን በመስጠት የውሃትንና ትሕትናን ገንዘብ አድርጋ በትግሥት በበጎ ሥነ ምግባር ሁሉ ጸንታ እንደኖረች እነግራችኋለን።
❤ እንዲህ ባለ ሥራ ሳለች መንፈሳዊ ሐሳብ እንዲህ ሲል ተነሳባት፤ "ለአንቺ በዚህ ዓለም መኖር ምን ይረባሻል የሚል መጣባት፤ ዛሬ የሚያልፍ የሚጠፋ ነውና፤ ጌትነቱ የሚመሰገንበት ለዘለዓለም የሚኖር የማያልፍ ሌላ ዓለም ይገለጣልና"፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በወንጌል "ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢገዛ ቢነዳ በነፍሱ ከተጎዳ ምን ይጠቅመዋል ምን ይረባዋል" እንዳለ።
❤ "ለአንቺ ግን በሰማይ ጸንቶ መኖርና ሁለተኛዋን ሀገር መያዝ ይሻላል" የሚል ሐሳብ መጣባት፤ ይህን ካሰበች በኋላ ፈጥና ተነሥታ በሌሊት ከቤቷ ወጥታ፤ በሀገሯ አንጻር ትይዩ ወደ ሆነው በረሃ ሄደች፣ በውስጡ ከሰው ወገን የማይኖርበት ቦታ መካከሉ ምድረ በዳ ወደ ሆነው በረሃ ደረሰች። ከጅቦች፣ ከነብሮች፣ ከዓሣሞች፣ ከጦጦችና ከዝንጆሮች በስተቀር ምንም ምን የማይኖርበት በረሃ ነበር።
❤ በዚያችም ቦታ ደጃፏ ያልተዘጋች ትንሽ ዋሻ አገኘች ምንም ምንም ሳትናገር ከዋሻው ውስጥ ገባች። በዋሻው ውስጥ ቁሞ በትጋት መዝሙረ ዳዊትን በአንክሮ በተደሞ የሚደግም ክቡር ባሕታዊን አየች፤ ባየችውም ጊዜ ደነገጠች። እርሱም ሴቲቱን ባያት ጊዜ ፍርሃት መንቀጥቀጥ በላዩ ላይ ወረደበት፣ በመስቀል ምልክትን አማተበ። ይህም ቅዱስ ባሕታዊ ፊቱን በአማተበና ስመ እግዚአብሔርንም በጠራ ጊዜ እንዳልሸሸች ስለአየ ይህች ሴት ክርስቲያን መሆኗን አወቀ።
❤ መጀመሪያ ስትገባ የጋኔን ምትሐት መስላው ነበርና፤ ሰው መሆኗን ባወቀና በተረዳ ጊዜ ተቆጣት። "አንቺ ዘማዊት ሴት ምንኵስናየን ታፈርሽ ዘንድ ከየት መጣሽ" አላት። "ወይም ደግሞ ሰይጣን በልብሽ ገብቷልን"። "ጌታዬ እኔስ የሕያው እግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው የኢየሱስ ክርስቶስ አገልጋይ ነኝ እንጅ አንተ እንደምትለኝ ዘማዊት አይደለሁም" አለችው። "ነገር ግን ቤቴን ንብረቴን ያለኝን ትቼ መጥቻለሁ፣ በዓለም ውስጥ ያለውን ሁሉ ንቄ እመንን ዘንድ እወዳለሁና ስለዚህም ወደዚህ ምድር በዳ መጣሁ። በዚህም ገዳም ወይም በረሃ ሰው እንዳለ አላውቅሁም ነበር፤ ሰውን የሚባሉ አራዊት ብቻ የሚኖሩበት ይመስለኝ ነበር" አለችው።
❤ ይህም ባሕታዊ በትሕትና በፈሪሃ እግዚአብሔር ይህን የሚያስደንቅ መልካም መልስ በመለሰችለት ጊዜ። አንድ ሰዓት ያኽል ካሰበ በኋላ "በፍቅር አንድነት ወደ ቤትሽ ተመለሽ" ብሎ በሰላም ተናገራት። እርሷም "ወደዚህ ቦታ ዳግመኛ አልመጣም እንጅ ካንተ ዘንድ ተለይቼ እሄዳለሁ። ነገር ግን ወደ ቤቴ ተመልሼ አልሄድም። ከገዳማት በአንድ ቦታ መንኵሼ መኖር እወዳለሁ እንጅ" አለችው። ጌታ "በወንጌል እርፍን በእጁ ይዞ ወደ ኋላ የሚያርስ የለም" እንዳለ ወደ ዓለም አልመለስም" አለችው።
❤ ያም ባሕታዊ "ምንኵስናስ የለሽም አልታዘዘልሽም፤ ነገር ግን በሰላም ወደ ቤትሽ ወደ ሕጋዊ ባልሽ ተመለሽ። የተፈቀደልሽንስ እነግርሻለሁ ከሕጋዊ ባለቤትሽ ወንድ ልጅን ትወልጃለሽ እርሱም ለዓለም ሁሉ የሚጠቅም ይሆናል። የገድሉና የትሩፋቱ ዜና እስከ ዓለም ዳርቻ ይደርሳል፤ በሕይወተ ሥጋ ሳለ በፈጣሪው በእግዚአብሔር ፈቃድ የብዙዎቹን ሰዎች ነፍሳት ከሲኦል ያወጣል። እንደ መላእክትም ክንፈ ጸጋ ተሰጥቶታል። በሰው አካል በሥጋ ሁኖ ሳለ በተመሥጦ ወደ ሰማይ ወጥቶ የሥላሴን የአንድነትን የሦስትነት ምሥጢር ያያል"።
❤ ቅድስት ዮስቴናም ከአረጋዊ ባሕታዊ ይህን ነገር ሰምታ አደነቀች፤ "የፈጣሪየ ፈቃድ ከሆነ ወደ ቤቴ እመለሳለሁ" አለች፤ ይህን ብላ ተመልሳ ወደ አገሯ ወደ ቤቷ ገባች፤ ቤተሰቦቿም መውጣቷንም መግባቷንም ምንም አላወቁባትም፤ ከዚያም በነሐሴ 26 ቀን ጸነሰች። ከዘጠኝ ወራትም ከቆየች በኋላ፤ መልኩ እንደ በረዶ ነጭ እንደ ጽጌ ረዳም ብሩህ ቀይ የሆነ መልከ መልካም ልጅ ወለደች ሁለተናውም ጨረቃ የጉለቱ ምልዓት 15 ሌሊት ሁኖ በብሩህ ብርሃን በምልዓት በሚያድርበት ጊዜ እንደሚያበራው መልካም ብርሃን ገጹ ብሩህ የሆነ ልጅ ወለደች፤ ይህ ሕፃን በግንቦት ወር በ 26 በተወለደ ጊዜ በአባቱና በእናቱ ቤት ታላቅ ደስታን ሆነ፤ ሜሉን ገቹን አርደው ዘመዶቻቸውን ጎረቤቶቻቸውን አማቾቻቸውን ምርዓቶቻቸውን ጠርተው ለበዓሉ እንደሚገባ መብሉንና መጠጡን ሰጥተው በሚገባ አጠገቡዋቸው፤ ...ካህኑም ተቀብሎ አጠመቀው ከአጠመቀውም በኋላ ለነፍሱ ዋስ (ለክርስትና አባቱ) አሳልፎ ሰጠው ስሙንም ሀብተ ማርያም ብሎ ሰየመው። ከአባታችን ከአቡነ ሀብተ ማርያም እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን!። ምንጭ፦ ገድለ አቡነ ሀብተ ማርያም።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_ኢየሱስ_ሞዐ፦ አገራቸው ጎንደር ክፍለ ሀገር ስማዳ ወረዳ ሲና ዳኅና በሚባል ቦታ ነሐሴ 26 ቀን ተፀንሰው ግንቦት 26 ቀን 1210 ዓ.ም ከአባታቸው ከቅዱስ ዘክርስቶስና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ክብራ ተወለዱ፡፡ የተወለዱትም በቅዱስ ነአኲቶ ለአብ ዘመነ መንግሥት ነው፡፡
❤ አቡነ ኢየሱስ ሞዐ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት የቆብ አባት ሲሆኑ ታላቁን ሐይቅ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገዳም የቆረቆሩ ደገኛ አባት ናቸው፡፡ ዕድሜያቸው 30 ዓመት እስከሚደርስ ድረስ ከቤተሰቦቻቸው ትምህርተ ሃይማኖትንና ግብረ ገብን ሲማሩ ከቆዩ በኋላ በ1240 ዓ.ም ይህንን ዓለም በመተው ወደ ደብረ ዳሞ ገዳም ገቡ፡፡ በደብረ ዳሞ ገዳም መነኰሳቱን እየረዱ፣ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እያጠኑ፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን እየገለበጡ ለሰባት ዓመታት ከቆዩ በኋላ የደብረ ዳሞ 3ኛ አበ ምኔት ከሆኑት ከአባ ዮሐኒ እጅ ምንኲስናን በ1247 ዓ.ም ተቀበሉ፡፡
❤ አንድ ቀን ሌሊት መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ወደርሳቸው መጥቶ "የስምህ መክበርያ ወደሆነው ሐይቅ ወደ ተባለው ሥፍራሂድ" አላቸው፡፡ አባታችንም "ቦታውን እንዴት ዐውቀዋለሁ?" በማለት መልአኩን ቢጠይቁት "ተነሥ! ጉዞህን ጀምር ቦታውን እኔ አሳይሃለሁ" አላቸው፡፡ አባ ኢየሱስ ሞዐ በመልአኩ እንደታዘዙት ከበዓታቸው ተነሥተው ተከተሉት፡፡ የብዙ ወራት መንገድ የሆነውን ጐዳናም በስድስት ሰዓት አደረሳቸው፡፡ በዚያን ወቅት ከሐይቅ ገዳም በስተ ሰሜን ወደነበረው የቅዱሳን ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ደረሱ፡፡ ወደ ሐይቅ እስጢፋኖስ ከመግባታቸው በፊት ለ 6 ወራት ያህል በቅዱሳን በጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን አገልግለዋል፡፡ ያገለግሉበት በነበረው ቤተ
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፭ (25) ቀን።
❤ እንኳን #ለአባ_እንጦንስ_ደቀ_መዝሙር_ለሆነ ታላላቅ ተአምራቶችን ላደረገ ለታላቁ አባት #ለአባ_ቢጻርዮን_ለዕረፍት_በዓል፣ #ለቅዱስ_እንድርያኖስና_ሃያ_አራቱ_ባልንጀሮቹ ሰማዕታት ለዕረፍታቸው በዓል በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከኤልያኖስ_ከእኅቱ_አውዶክስያ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_እንድርያኖስና_ሃያ_አራቱ_ባልንጀሮቹ ሰማዕታት፦ ይህም እንድርያኖስ ከመክስምያኖስ መኳንንቶች አንዱ ነበር እርሱም የጐልማሶች አለቃ ነበረ። ለጣዖት መስገድን እምቤ ስለአሉ ንጉሡ ምእምናንን ሲአሠቃያቸው ቅዱስ እንድርያኖስ የሰማዕታትን የልባቸውን ቆራጥነትና በመከራቸው ላይ መታገሣቸውን ተመልክቶ አደነቀ።
❤ እንዲህም አላቸው "ይህን ያህል ስትታገሡ ምን ታገኛላችሁ?" ቅዱሳን ሰማዕታትም "የሚጠብቀንን ተሰፋ ለመናገር አንደበታችን አይችልም" አሉት ስለ ዓለም ድኅነትም ክርስቶስ መከራ እንደ ተቀበለ ከብሉይና ከሐዲስ መጽሐፍ ነገሩት። እንድርያኖስም በሰማ ጊዜ ጽሕፈትን ወደ ሚያውቁ ብልሆች ሰዎች ሔደና "እኔ ከዛሬ ጀምሮ ክርስቲያን ነኝ ስሜን ከገድለኞቹ ጋራ ጻፉ" አላቸው።
❤ ለንጉሥ መክስምያኖስም እንዲህ እንዳለ በነገሩት ጊዜ ጠርቶ "እንድርያኖስ ሆይ አበድክን" አለው እንድርያኖስም "ከቀድሞው እብደቴ ተመለስኩ እንጂ እኔ አላበድኩም" ብሎ መለሰለት። ንጉሡም ሰምቶ ወደ ወህኒ ቤት ከንጹሐን ሰማዕታት ጋራ እንዲጨምሩት አዘዘ። ከአገልጋዮቹም አንዱ ሒዶ ለሚስቱ እንጣልያ ነገራት በሰማችም ጊዜ ደስ እያላት ወደ ወህኒ ቤት ሔደች ሃያ አራቱ ቅዱሳን ሰማዕታት የታሠሩበትን ማሠሪያቸውን ሳመች በሥቃዩ እንዲታገሥ የባሏን ልብ ያጽናኑ ዘንድ ለመነቻቸው። እርሱንም እንዲህ አለችው "ላህይህ ደምግባትህም ርስትህም ጥሪትህም አያስትህ ሁሉም ከንቱ ነውና ነገር ግን በእርሱ ዘንድ የማያልፍ መንግሥትን ትወርስ ዘንድ የክብር ንጉሥ ክርስቶስን ተከተለው" ይህንንም ብላ ወደቤቷ ገባች።
❤ ከዚህም በኃላ እንድርያኖስ ለፍርድ እንደ ሚአቀርቡት በአወቀ ጊዜ ሊሰናበታት ወደ ሚስቱ ሔደ መምጣቱንም ሰምታ የሸሸ መሰላት ደጇንም ዘግታ በውስጥ ሁና እንዲህ እያለች ዘለፈችው "ትላንት ሰማዕት ተብለኽ ዛሬ ክርስቶስን ካድከውን" እንድርያኖስም ሰምቶ የሃይማኖቷን ጽናት አደነቀ እንዲህም አላት "እኅቴ ሆይ እንድሰናበትሽ ክፈችልኝ" አላት። በሰማችም ጊዜ ከፈተችለት ከዚህም በኋላ ሁሉን እያነጋገራት እስከ እሥር ቤት ወሰዳት እንጣልያም ከዚያ በደረሰች ጊዜ የታሠሩትን ቅዱሳን ተሳለመቻቸው ቅስላቸውንም አጠበች።
❤ ከዚህም በኃላ ንጉሡ ቅዱሳኑን ከእሥር ቤት እንደአመጧቸው አዘዘ በመጡም ጊዜ ከሥቃይ ብዛት የተነሣ እንደደከሙ አያቸው። እንድርያኖስንም በፊቱ አቁሞ ለአማልክት ሠዋ አለው ቅዱሱም እርሱንና የረከሱ አማልክቶቹን ረገመ ንጉሡም የሆድ ዕቃው እስኪፈስስ ሆዱን እንዲደበድቡት አዘዘ በዚያን ጊዜም የእንድርያኖስ ዕድሜው ሃያ ስምንት ዓመት ነበር።
❤ ከዚህም በኃላ እንድርያኖስን ከባልንጀሮቹ ሰማዕታት ጋራ ወደ እሥር ቤት መለሱት እንጣልያም መጥታ የቅዱሳንን ደማቸውን ጠራረገችላቸው። እሊህ ቅዱሳንም እንድርያኖስን እንዲህ ብለው ተሳለሙት "እንድርያኖስ ሆይ ስምህ ተሳለሙት በሕይወት መጽሐፍ ተጽፎአልና ደስ ይበልህ"።
❤ ንጉሡም መስፍ አምጥተው የቅዱሳኑን ሁሉ ጭናቸውን በድጅኖ ይሰብሩ ዘንድ አዘዘ እንጣልያም የእንድርያኖስን እጆቹንና እግሮቹን በመስፍ ላይ ለማኖር ቀደመች ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ እስከ ሰጠ ድረስ የእንድርያኖስን ዐጥንቶቹን ወታደሮች ቀጠቀጡ የቅዱሳኑንም ሁሉ ጭናቸውን ሰብረው ወደ እሳት ወረወሯቸው እሳቱ ግን ከቶ አልነካቸውም። ምእመናንም መጥተው በጭልታ ወደ ሌላ ቦታ ወሰዱአቸው የመከራውም ወራት እስቲያልፍ ሠወሩአቸው። እንጣልያም የእንድርያኖስን የእጁን ቁራጭ ወስዳ በትርአሷ ውስጥ አኖረችው።
❤ ከዚህም በኋላ የሀገሩ ገዥ እንጣልያን ሊአገባት ወደደ በአወቀችም ጊዜ የባሏን የእጅ ቁራጭ ይዛ በመርከብ ሸሸች የቅዱሳኑ ሥጋ ወዳለበትም ደርሶ ወደ እነርሱ ይቀበሏት ዘንድ ለመነች ጌታችንም ልመናዋን ተቀብሎ አሳረፋት ከእነርሱም ጋራ ተቀበረች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ እንድርያኖስና በሃያ አራቱ ባልንጀሮቹ ሰማዕታት አማላጅነት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ቢጻርዮን፦ የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ እግዚአብሔርን የሚፈሩ ምእመናን ነበሩ። በአደገም ጊዜ የምንኵስና ልብስን ለብሶ እግዚአብሔርን ሊአገለግል ወደደ ዓለምንም ንቆ ወደ አባ እንጦንስ ሔደ ለእርሱም ደቀ መዝሙር ሆኖ ብዙ ዘመናት አገለገለው።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ አባ መቃርስ ሒዶ ቅዱሳን አረጋውያን መነኰሳትንም አገለገላቸው። በአስቄጥስም ገዳም ይዘዋወር ነበር በቤት ውስጥም አያድርም ነበር። ምንጣፍና ልብስ እስኪአጣ ድረስ ምንም ምን ጥሪት አልነበረውም መነኰሳቱም የማቅ ጨርቅ ይሰጡት ነበር። ወገቡንም ታጥቆ በመነኰሳቱ መንደር ይዞር ነበር በቤቶቻቸውም ደጃፍ እያለቀሰ ይቀመጥ ነበር።
❤ የማያውቀውም ወደርሱ በደረሰ ጊዜ "አባቴ ሆይ ምን ያስለቅስሃል" ይለው ነበር። እርሱም "ንብረቴን ስለዘረፉኝ እንዳልሞት ሸሸሁ ከወገኔም ክብር ተለይቼ በጉስቁልና ወደቅሁ" ይለው ነበር። የቃሉንም ምልክት የማያውቅ የጠፋውን ገንዘብህን እግዚአብሔር ይመልስልህ ብሎ ካለው ይሰጠው ነበር። እርሱም ተቀብሎ ይሔድና ለሌለው ይሰጥ ነበር። የቃሉን ምልክት የሚያውቅ ግን በፈቃደ ነፍስ የሚሠሩ ትሩፋትን ሰይጣን ከሰዎች የማረካቸው መሆኑን ልብ ብሎ ያስተውል ነበር። አባቶችም ጭንቅ የነበረ ተጋድሎውን ስለርሱ ይናገሩ ነበር። እርሱ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ከቶ ሳይተኛ ቁሞ ኖሮአልና ።
❤ በምንኵስናውም ወራት ብዙ ጊዜ በየአርባ ቀን ጾመ እነሆ እንዲህ እየተጋደለ ድንቆችንም እያደረገ ኀምሳ ሰባት ዓመታት ኖረ። ቅዱሳን አባ ዱላስና አባ ዮሐንስም ከተአምራቱ ተናገሩ እነርሱ ከርሱ ጋር ወደ ኤርትራ ባሕር ዳርቻ ሔዱ። እጅግም በተጠሙ ጊዜ እንደተጠሙ አውቆ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ መራራውንም ውኃ ጣፋጭ አድርጎላቸው ጠጥተዋል።
✝ በሁለተኛም ጊዜ ወደ ፈሳሽ ውኃ ደርሶ መሸጋገሪያ አጣ ወደ ጌታችንም ጸለየ ያን ጊዜም እንደ የብስ በባሕሩ ላይ ሔደ። በአንዲት ቀንም የከበሩ አባቶች በጸሎታቸው ያድኑት ዘንድ ጋኔን ያደረበትን ሰው ወደ አስቄጥስ ገዳም ሰዎች አመጡ አባቶችም እርስ በርሳቸው እንዲህ ተባባሉ እርሱ ከከንቱ ውዳሴ ስለሚሸሽ ብንነግረው ይህን ጋኔን የያዘውን አያድነውም ።
❤ አባ ቢጻርዮን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለጸሎት ወደሚቆምበት ቦታ ያንን ጋኔን ያደረበትን ሰው አስተኙት። አባ ቢጻርዮንም በገባ ጊዜ ያን ጋኔን ያደረበትን ሰው ተኝቶ አገኘውና ቀሰቀሰው እጁንም ይዞ "ተነሥ" አለው ያን ጊዜም ድኖ ተነሣ አእምሮውም ተመለሰ። ያዩትም እጅግ አደነቁ ለሚፈሩት ስለሚሰጠው ጸጋውም እግዚአብሔርን አመሰገኑት።
❤ የዚህም ቅዱስ ተአምራቶቹ ከነገርናችሁ የበዙ ናቸው እግዚአብሔርንም አገልገሎ በሰላም አረፈ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ቢጻርዮን ጸሎት ይማረን። በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የነሐሴ 25 ስንክሳር።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፬ (24) ቀን።
❤ እንኳን #የኢትዮጽያ_ብርሃን_ለተባሉት ለታላቁ አባት ለከበረ ሐዲስ ሐዋርያ ለትሩፋትም መምህር ለሆነ #ለአቡነ_ተክለ_ሃይማኖት_በዓለ_ለዕረፍትና ለታላቁ አባት ለክርስቶስ ምስክር ለሐዋርያው ለመርዓስ አገር ኤጲስ ቆጶስ ለተጋዳይ #ለቅዱስ_አባት_ቶማስ በዓለ ለዐረፍት በዓል በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከአብርሃም_ከይስሐቅና_ከያዕቆብ ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ነሐሴ ፳፬ (24) ቀን።
❤ እንኳን #ለታላቋ_የሰላምና_የምሕረት (የይቅርታ) እናት ለሆነችው ሰይጣንን ከእግዚአብሔር ጋር ለማስታረቅ ለሞከረችው ለእናታችን #ለቅድስት_ክርስቶስ_ሠምራ_በዓለ_ዕረፍት፣ ለታላቁ ሰማዕት #ለአቡነ_ጊዮርጊስ_ዘግሽ ለበዓላቸው መታሰቢያቸው በሰላም አደረሰን።
+6
ብፁዕነታቸው !
" ሰው እንደ እናት እቅፍ የሚያምነው መሬት ሲከዳው ምንኛ ያሳዝናል፤ በደጉ ገበሬ ላይ በደረሰው ድንገተኛ አደጋ አዝኛለሁ " - ብፁዕ አቡነ ገሪማ
➡️ " ከሁሉ ነገር ስብዕና ይቀድማል !! "
በጌዴኦ ዞን የተከሰተውን የመሬት መንሸራተት አደጋ ተከትሎ የጌዴኦ፣ ኮሬና ቡርጂ ዞኖች ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ገሪማ በረጴ ወረዳ ጫራቃ ቀበሌ ድረስ ተገኝተው በመሬት ናዳ ምክንያት የሚወዷቸውን የተነጠቁና በሀዘን የተሰበሩ ቤተሰቦችን አፅናንተዋል፤ አስክሬን ፍለጋውንም ከሕዝቡ ጋር አብረዉ አግዘዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ ብፁዕ አቡነ ገሪማን ከስፍራዉ ሲመለሱ ያነጋገራቸው ሲሆን " ሰው እንደ እናት እቅፍ የሚያምነዉ መሬት ሲከዳው ምንኛ ያሳዝናል፤ በደጉ ገበሬ ላይ በደረሰው ድንገተኛ አደጋ አዝኛለሁ " ሲሉ ገልፀዋል።
" የሞቱት ሰዎች ናቸው ስብዕና ደግሞ ከሁሉ ይቀድማል" ያሉት ብፁዕነታቸው " የሞቱት እግዚአብሔር በአምሳሉ የፈጠራቸዉ ክቡራን የሰዉ ልጆች ስለሆኑ ብቻ ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ከየየመምሪያ ኃላፊዎች ጋር በመሆን ወደ ቦታዉ በማቅናት ሕዝቡን አፅናንተናል ፀሎትም አድርገናል " ብለዋል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ ያነጋገርናቸው የአከባቢው ነዋሪዎች ብፁዕነታቸው ቦታው ድረስ መገኘታቸውና ሕዝቡን ማፅናናታቸው እንዲሁም ከሕዝቡ ጋር እየቆፈሩ አስክሬን መፈለጋቸው ትልቅ መፅናናት እንደፈጠረላቸው ተናግረዋል።
በጌዴኦ ዞን ረጴ ወረዳ ጫራቃ ተብሎ በሚጠራዉ አከባቢ ተከስቶ ለ9 ሰዎች ሕይወት መጥፋት ምክንያት ከሆነው የመሬት መንሸራተት አደጋ በተጨማሪ በዚሁ ዕለት በዞኑ ቡሌ ወረዳ አጋምሳ ተብሎ በሚጠራዉ አከባቢ ሌላ አደጋ ተከስቶ 17 ሰዎች እስካሁን አለመገኘታቸው ተገልጿል።
