uz
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

Kanalga Telegram’da o‘tish

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

Ko'proq ko'rsatish
2 639
Obunachilar
-224 soatlar
+37 kunlar
+5630 kunlar
Postlar arxiv
ከሰማይ እንደተመለሰ ለመጀመሪያ ጊዜ ጣዕመ ዜማውን ያሰማበት ቦታ "ሙራደ ቃል" (የቃል መውረጃ) እየተባለ ይጠራል። ይኸውም ዜማው ከሰማይ የወረደ ለመኾኑ እውነተኛ ማስረጃ ነው። ይህችንም ዜማ "አርያም" አላት። ይህም ማለት ከመላእክት ወይም ከሰማይ የተገኘች ማለት ነው። ከዚህም በኋላ ከብሉይና ከሐዲስ፣ ከሊቃውንት መጻሕፍትም ከነአትናቴዎስ፣ ቄርሎስ፣ ዮሐንስ አፈወርቅ መጻሕፍት ለምስጋናና ለጸሎት የተስማሙትን ቃላት እየመረጠና እያቀና በአራቱ ክፍለ ዘመን፣ በመፀውና በሐጋይ በጸደይና በክረምት እንዲነገር አድርጎ ወስኖ አዘጋጀ። የመጽሐፉ የድርሰቱ ስም ድጓ ተባለ። ድጓ ማለትም በትግርኛ ደጉዓ ማለት መዝሙረ ኃዘን፥ የኃዘን ዜማ፥ ማለት ነው። ሙሾ። የዜማውን ዓይነት በሦስት ክፍል ወስኖ ተናግሮታል። እነርሱም ግእዝ፣ ዕዝል፣ ዓራራይ ይባላሉ። ግእዝ ማለትም አንደኛ በመጀመሪያ የተገኘ ማለት ነው፤ ዕዝል ማለትም ሁለተኛ ሆኖ ከግእዙ ጋር ተደርቦ፣ ተጨምሮ፣ ታዝሎ የሚነገር ማለት ነው። ዓራራይ ማለትም ሦስተኛ ተጨማሪ ሆኖ አራኅራኂ፣ ርኅራኄ፣ አሳዛኝ ልብን የሚመስጥና ደስ የሚያሰኝ ማለት ነው።መንግሥቱን ይህን ድርሰቱን ያዘጋጀበት ዘመን ከ540 ዓ.ም ሲሆን የመጨረሻ ልጁ አፄ ገብረ መስቀል ወረሰ። አፄ ገብረ መስቀልና አባ አረጋዊ ቅዱስ ያሬድ እነዚህ ሦስቱ በአንድነት እንደነበሩ ታሪከ ነገሥቱና ገድለ አረጋዊ ይገልጽልናል። አቡነ አረጋዊ የደብረ ዳሞን ተራራ አቀማመጥ አይተው ደስ ስላላቸው፣ ንጉሡ አፄ ገብረ መስቀል በዚሁ ተራራ ላይ እንዲኖሩበትና እንዲጸልዩበት ፈቀደላቸው። እርሳቸውም ይህንን ተራራ ከተረከቡ በኋላ በተራራው ላይ የጸሎት ቤት ስለሌለ ንጉሡ አፄ ገብረ መስቀልን አንድ ቤተ ክርስቲያን እንዲሠራላቸው ለመኑት። ንጉሡም ቤተክርስቲያን ልሠራ የምችልበትን ሥፍራ መርጠው ያመልክቱኝ ብሎ ነገራቸው አቡነ አረጋዊም ተነሥተው ዞረው ቦታውን መርጠው አሳዩት። ከዚህ በኋላ ንጉሡ በአዋጅና በትዕዛዝ ድንጋዩና እንጨቱ እየተሰበሰበ በከብትና በሠረገላ እየተጋዘ ተሰበሰበና ከታች ወደ ተራራው ላይ ወጥቶ ተሠራና የቤተ ክርስቲያኑ ሥራ በሁለት ዓመት አለቀ። ባለቀም ጊዜ የቤተክርስቲያኑ ሥራ ተመልካቾችን አስደነቀ። ለዚሁም ቤተክርስቲያን ልዩ ልዩ የሆኑ አልባሳት፣ በወርቅ በብርና የተደጎሱና የተከፈፉ መጻሕፍትን አበረከቱ። ከማኅበረ በኩር የመጣውን የእመቤታችንን የቅድስት ድንግል ማርያምን ላይና አግብተው አቡነ አረጋዊ ባርከውና ቀድሰው ንጉሡና ጳጳሱ ቆረቡ። ከዚያም አፄ ገብረ መስቀል በተራራው ላይና በግርጌ ላሉት ሠራዊት ግብር አብልተው ነዳያን ሁሉ በንጉሡ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሬድ በአክሱም ሲያስተምር ሳለ በንጉሡ አፄ ገብረመስቀልና አቡነ አረጋዊ፥ ወደዚህ ተራራ መጥቶ ቤተክርስቲያኑን እንዲጎበኝና እንዲዘምር ተጠርቶ ሲመጣ ከተራራው ሥር ሲደርስ የአቡነ አረጋዊን ደቀመዛሙርት ማትያስና ዮሴፍ የሚባሉትን ከወንዝ ዳር ዓሣ ሲያጠምዱ አግኝቶ "ዳኅንኑ ዝስኩ አረጋዊ አቡክሙ ፤ ይህ አረጋዊ አባታችሁ ደህና ነው?" ብሎ ጠየቃቸው። እነርሱም ደኅንነታቸውን ነገሩት። ከዚያም ቅዱስ ያሬድ ወደ ተራራው ላይ ወጥቶ ከአቡነ አረጋዊ ጋር በመንፈሳዊ አምኃ በፍቅር ተገናኙ ወደ ቤተክርስቲያኑም ሄዶ 3 ጊዜ ሰግዶ ከተሳለመ በኋላ የሕንጻውን ማማር በአድናቆት ተመልክቶ ከፍ ባለ የዜማ ድምፅ እያጉረመረመ እንዲህ ሲል ዘመረ። "ይሄውፅዋ መላዕክት እንተ በሰማያት ይሄውፅዋ መላዕክት እስመ ማኅደረ መለኮት ዖድክዋ ዖድክዋ ዖድክዋ ወርኢኩ ሥነ ሕንፄሃ ለቅድስት ቤተክርስቲያን ምሥአል ወምስጋድ ወምሥትስራየ ኃጢአት ይዕቲ ቅድስት ደብተራ"። የሚለውን መዝሙር ከዘመረ በኋላ ስምንት ቀን ያህል ከአቡነ አረጋዊ ጋር ሰንብቶ ተመለሰ። ከዚህ በኋላ ንጉሡ አፄ ገብረ መስቀልና አቡነ አረጋዊ ከቅዱስ ያሬድበጣና አብረው ወደ ሌላ ጠቅላይ ግዛት ጉብኝት ሄዱ። ከዚያም በጣና በአንዱ ደሴት ላይ የቅዱስ ቂርቆስን ቤተ ክርስቲያን ሠርተው ተቀመጡ። በዚያም ቦታ ቅዱስ ያሬድ ሁለት ዓመት አስተማረ። እርሱ እራሱ ጻፈው የሚባል ድጓ ምልክት የሌለው ዛሬ በዚሁ ደሴት በጣና ቂርቆስ ይገኛል። ከዚህም ደሴት ከጣና ቂርቆስ ተነሥተው ንጉሡና አቡነ አረጋዊ ቅዱስ ያሬድም ወደ ደጋው ወደ ጋይንት ወጡ። በዚያም አንድ ትልቅ ተራራ አግኝተው መውጫው ጠፍቶባቸው ሲጨነቁ አንድ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ መጥቶ አቡነ አረጋዊን "ዑድ አባ መንገለ ምሥራቅ ወዑዳ ለዛቲ ደብር፤ ዙር አባ ወደ እርስዋም ትወጣ ዘንድ በምሥራቅ በኩል ዙር" አላቸው ወደ ምስራቅ ሲዞሩ መልአኩ ቅዱስ ዑራኤል ነጭ ሐረግ ዘረጋላቸው እርሱን ይዘው ወደ ተራራው ላይ ወጡ። በዚሁ ተራራ ላይ የእመቤታችንንአምባ ክርስቲያን ሠሩ። የተራራውም ስም እስከ ዛሬ ድረስ ዙር አምባ ተብሎ ይጠራል። በዚህ ገዳም ምሥራቃዊ አቅጣጫ ቅዱስ ያሬድን የምትዘክር "ከርሞ አይደርቅ" የምትባል ዛፍ አለች። ቅዱስ ያሬድ በዚች ዛፍ ሥር ተቀምጦ ዝማሬ መዋሥዕት የተባለውን መጽሐፍ ለሦስት ዓመት ከሦስት ወር ስላስተማረበት ይህም ቦታ ገዳም እስከ ዛሬ ድረስ የዝማሬና የመዋሥዕት ምስክር ቦታ ሆኖ ይኖራል። ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሬድ ከአኵሱም ወደ ማይኪራህ አምርቶ እመቤታችን ቅዱስ ኤፍሬምን በአካለ ነፍስ ከሶርያ አባ ሕርያቆስ ከብሕንሳ አምጥታ ውዳሴዋንና ቅዳሴዋን ንባቡን እየነገሩት በዜማ እንዲደርስላት አድርጋለች። ከዚህም አያይዞ ለሥጋ ወደሙ ጸሎት የሚያገለግሉትን ንባቡ የሌሎች ሊቃውንት ድርሰት የሆኑትን ዐሥራ አራቱን ቅዳሴዎች በዜማ አዘጋጀ። ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሬድ ወደ ሰሜን ተራሮች ጸለምት ሔዶ ምዕራፍ የተባለውን ድርሰቱን ደረሰ። ከዚህ በኋላ አገው፣ ፎገራ እና ወደ ሌሎችም ቦታዎች እየዞረ አስተማረ። ቅዱስ ያሬድ በቅድስት አኵሰም ወንበር ዘርግቶ፣ ጉባኤ አስፍቶ ደቀ መዛሙርቱን እያስተማረ ሲኖር በጾመ፵ ሱባኤ ላይ ሳለ አንድ ቀን በምኵራብ ሰሞን ስለምናኔው እያስታወሰ በተመስጦ ሲዘምር የዜማው ጣዕም እንኳን ሌላውን ራሱን እጅግ ይመሥጠው ነበር። በጣዕመ ዝማሬው ተመሥጦ ሲያዳምጥ የነበረው ኢትዮጵያዊው ንጉሥ የዐፄ ገብረ መስቀል ዐይን ዐይኑን እየተመለከተ ሳይታወቀው በመስቀል ስላጢኑ (በበትረ መንግሥቱ ዘንግ) ጫፍ የቅዱስ ያሬድን እግር ወጋው። ቅዱስ ያሬድ ግንቀጠለ፤ ከሰማያት የተገኘች ቃለ ማሕሌቱን እስኪፈጽም ድረስ ከቆመበት ሳይንቀሳቀስ ሕመሙ ሳይታወቀው ደሙም ያለማቋረጥ ፈሰሰ። ቅዱስ ያሬድ የጀመረውን በፈጸመ ጊዜ ንጉሡ ደንግጦ በትሩን ከቅዱስ ያሬድ እግያሬድን ቢነቅለው ደሙ በኃይል ይፈስ ጀመር። ያን ጊዜ ንጉሡ ዐፄ ገብረ መስቀል የቅዱስ ያሬድን ትዕግሥት ባለ ጊዜ በመደነቅ፣ በመገረምና በመደንገጥ ዝም በማለት አፉን ይዞ ቆመና ምድራዊ ዋጋ የሚፈልግ መስሎት "ካህን ያሬድ ሆይ የምትፈልገውን ዋጋ ጠይቀኝ" አለው። ቅዱስ ያሬድ መልሶ "የፈለግኹትን እንዳትከለክለኝ ቃል ኪዳን ግባልኝ" አለው። ንጉሡም የጸና ቃል ኪዳን ለቅዱስ ያሬድ ገባለት። ቅዱስ ያሬድም " ከዚህ ሐላፊ ዓለም ክብር ተለይቼ መናኝ ሆኜ እንድኖር ተወኝያሬድ አሰናብተኝ" ብሎ አሳብን ገለጸለት። ከዚህም በኋላ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል ካህን የጠየቀውን እንዳይከለክለው ከአፉ የወጣውን መሐላ አስቦ በምናኔ አሰናበተው እንጂ ሊከለክለው አልቻለም።

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_5 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ አምስት በዚች ቀን የኢትዮጵያ ብርሃኗ #ማኅሌታዊው_ቅዱስ_ያሬድ የተወለደበት ነው፤ የካህኑ የቡዝ ልጅ ታላቅ #ነቢዩ_ቅዱስ_ሕዝቅኤል አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ያሬድ ሚያዝያ አምስት በዚህች ቀን የኢትዮጵያ ብርሃኗ ማኅሌታዊው ቅዱስ ያሬድ የተወለደበት ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ከእናቱ ቅድስት ክርስቲና (ታውክልያ) ከአባቱ ከቅዱስ አብዩድ (ይስሐቅ) በአክሱም በ505ዓ.ም ሚያዝያ 5 ቀን ተወለደ። አባቱ የአክሱም ጽዮን ቄሰ ገበዝ ነበር። በዚያን ጊዜ የብሉያትና የሐዲሳት መምህራንና ተማሪዎች የሚገኙት አክሱም ጽዮን ነውና የአኵሱም ቤተ ቀጢን (ቤተ ጉባኤ) መምህር የነበረው የእናቱ ወንድም አጎቱ መምህር ጌዴዎን ይባል ነበር። ቅዱስ ያሬድ የሰባት ዓመት ብላቴና በኾነ ጊዜ አባቱ ስለ ሞተ ትምህርት ቤት ከመግባቱ በፊት በዚያ ዘመን አጠራር ለጌታው ዐደረ። ጌታውም የዐፄ ገብረ መስቀል ቢትወድድ አዛዥ ዜና ገብርኤል ይባላል። ያሬድን ዐቅሙ ለጉልበት ሥራ እንዳነሰ አይቶት "አንተ ልጅ ጋሻ ቢያስይዙህ አትችል፤ ሾተል ቢያሸክሙህ አይሆንልህ ለምን ከዚህ መጣህ?" ብሎ መለሰለት። ከዚያ በኋላ ከአጎቱ ዘንድ ሔደ። መምህሩም "ከዚህ የመጣህበት ምክንያት ምንድ ነው?" አለው። እርሱም "መጽሐፍት እማራለኹ ብዬ ነው የመጣኹት" አለው። መምህር ጌድዎንም ዐቅሙንና ዕውቀቱን በመገመት ለተማሪዎች "በሉ ፊደል አስቆጥሩት" አላቸውና ትምህርቱን ጀመረ። ኾኖም ቃለ እግዚአብሔርን የመቀበል ችሎታው ደካማ ስለነበር አብረው የሚማሩትም ሕፃናት "ሰነፍ ያሬድ ዕንጨት ስበር ውሃ ቅዳ" እያሉ አፌዙበት፤ ቀለዱበት። አጎቱ ጌዴዎንም ከትምህርቱ ድክመት የተነሣ በጨንገር (በአለንጋ) ቢገርፈው ሕፃኑ ያሬድም በዚህ ተበሳጭቶና ተስፋ ቆርጦ ከአክሱም ከተማ ወጥቶ ወደ እናቱ መንደር ወደ መደባይ ወለል ደረሰ። ለጥሙ ከምንጭ ውሃ ጠጥቶ ለድካሙ ከዛፋ ጥላ አረፈ። በምን ምክንያት ከጓደኞቹ በታች እንደኾነ ሲያስብና ሲያሰላስል ሲያዝንና ሲተክዝ ከቆየ በኋላ እግዚአብሔር አንድ የሚያጽናና ምልክት አሳየው። ይኸውም አንድ ትል የዛፏን ፍሬ ለመመገብ ፈልጎ ወደ ላይ እየወጣና እየወደቀ ተደጋጋሚ ሙከራ ሲያደርግ ከቆየ በኋላ በሰባተኛው ጊዜ ወደ ዛፋ ወጥቶ ፍሬዋን ሲመገብ ተመለከተ ተማሪ ያሬድም ከዚህ ትል ትዕግሥትን፣ ጽናትን፣ ጥረትን፣ ስኬትን ትምህርት ወስዶ እኔም እኮ ተስፋ ሳይቆርጥ ብዙ ጥረት ካደረግኹ እግዚአብሔር ያሳካልኛል ብሎ በተስፋ ተጽናንቶ እንደገና ወደ መምህሩ በመመለስ ትምህርቱን ለመቀጠል ወሰነ። ወደ መደባይ ያደረገው የነበረውን ጉዞ ሠርዞ ወደ አክሱም ከተማ ወደ መምህሩ ጌድዬን ጉባኤ ቤት ተመለሰ። በመጸጸት አጎቱን "አባቴ ስለተቆጣኸኝና ስለገረፍከኝ ተበሳጭቼ ሔጄ ነበር ፤ ነገር ግን በመንገድ ላይ እግዚአብሔር ስላስተማረኝ ተጸጽቼ መጥቻለኹ። ከእንግዲህስ ወዲህ እየተቆጣኽና እየገሠጽህ አስተምረኝ" ሲል አሳቡን ሳይደብቅ ገለጸለት። አጎቱም ያሬድ ተጸጽቶ በመመለሱ በጣም ተደስቶ ዐይነ ልቡናውን ያበራለት ዘንድ ፈጣሪውን እያለቀሰ በለመነለት ጊዜ እግዚአብሔርም ጸሎቱን ሰምቶ ለያሬድ ዕውቀትን ገለጸለት። የያሬድ ኅሊናው ተከፍቶለት መዝሙረ ዳዊትን፣ ውዳሴ ማርያምን፣ መሓልየ ነቢያት፣ መሐልየ ሰሎሞንን፣ መጻሕፍተ ብሉያትንና ሐዲሳትን ንባባቸውን እስከ አገባባቸው አወቀ። ቅዱስ ያሬድ ቅዱሳት መጻሕፍትን በቃሉ ይዞ ሲያስተምር ሳለ የትምህርቱን ጥራት፣ የሃይማኖት ጽናት፣ ደግነቱንና ትዕግስቱን፣ ትሕትናውና ተልኮውን በመምህሩና በካህናቱ ተመስክሮለት የአክሱም ጳጳሱ አባ ዮሐንስ ሢመተ ዲቁና ሾመው። ቅዱስ ያሬድ የታላቋ የአክሱም ጽዮን ቤተ ክርስቲያን አጋልጋይ ዲያቆን ኾነ። ትምህርቱን በስፋት ስለቀጠለበት የመጻሕፍት ብሉያትና ሐዲሳት፣የመጻሕፍት ሊቃውንት ትርጓሜ ሊቅ ኾነ። ቅዱስ ሬድም ለመንፈሳዊ አገልግሎት ወደ ኢትዮጵያ ከመጡት ከዘጠኙ ቅዱሳን ጋራ በቤተ ቀንጢን ጉባኤ ቤት ይውል ስለነበር ገዳማዊ ሕይወት ከእነርሱ በመማር እንደ እነ አቡነ አረጋዊ፣ አባ ገሪማ፣ አባ ጰንጠሌዎን በድንግልና ተወስኖ በንጽሕና ሲያገለግል ቆይቷል። ለቅዱስ ያሬድ ሰማያዊ ዜማ መገለጽ፦ ኅዳር5 ቀን 527ዓ.ም ከጠዋቱ በሦስት ሰዓት እግዚአብሔር ከኤዶም ገነት ሦስት አዕዋፍን (መላእክት በአዕዋፍ ተመስለው) እርሱ ወዳለበት ላከለት። እነርሱም ያሬድ ባለበት ቦታ አንጻር በአየር ላይ ረብበው በግእዝ ቋንቋ "ብፁዕ ያሬድ ብፅዕት ከርሥ እንተ ጾረተከ ወብፁዕት አጥባት እለ ሐፀናከ (የተመሰገንክና የተባረክ ያሬድ ሆይ፤ አንተን የተሸከመች ማሕፀን የተመሰገነች ናት፤ አንተን ያሳደጉ ጡቶችም የተመሰገኑ ናቸው") ብለው አወደሱት። ቅዱስ ያሬድም ይህን ቃል በሰማ ጊዜ ወደ ሰማይ አንጋጦ ሦስቱን አዕዋፍ አየና "እናንተ በሰው አንደበት የምትናገሩ ከወዴት መጣችኹ" አላቸው። ከሦስቱ አዕዋፍ አንዷም "ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይ ማሕሌትን ሰምተኽ እንድታዜም የተመረጥኽ መኾኑን እነግርህና እናበሥርህ ዘንድ ወደ አንተ ተልከን መጥተናል" አለችው። ከዚያም ቅዱሳን መላእክት በዜማ ወደሚያመሰግኑባት ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም በአካል ተነጠቀ። በዚያም ቅዱሳን መላእክት የሚታየውንና የማይታየውን የፈጠረ እግዚአብሔር በቅኔና በከፍተኛ ደምፅ ያለማቋረጥ በመንበሩ ዙሪያ ኾነው ሲያመሰግኑ እንዲሁም የእንዚራ፣ የበገና የመሰንቆ ድምፅ በሰማ ጊዜ ካለበት ሥፍራ እነርሱ ወዳሉበት ሊገባ ወደደ ነገር ግን አልተቻለውም። በመጨረሻም እነዚያ አዕዋፍ ወደ እርሱ ተመልሰው መጡ። "ያሬድ ሆይ፤ የሰማኸውን አስተውለኸዋል?" ብለው ጠየቁት እርሱም "አላስተዋልኸም" ብሎ መለሰላቸው። እንግዲያውስ አዲሱን የእግዚአብሔር ምስጋና ጥራ፤ እርሱም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስም ነው። ከእግዚአብሔር መዘምራን ከቅዱሳን መላእክት በየዐይነቱ ዜማ ያለውን ማሕሌት ትማራለኽ፤ ታጠናለኽ" አሉት። ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሬድ ማሕሌቱን በየዓይነቱ አውጥቶ "መልካምን ነገር ልቤ ተናገረ" እያለ ከቅዱሳን መላእክት ተማረ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ " ሌሎችን አገልጋዮች ሰዎች ይሾሟቸዋል፤ አንተን ግን እኔ ሢመተ ክህነት (ቅስና) ሾሜኻለሁ" አለው። ቅዱስ ያሬድም የመላእክት ሥርዓታቸው ዐይቶ፤ ማሕሌታቸውን አጥንቶ ኅዳር6 ቀን 527ዓ.ም በጠዋት ሦስት ሰዓት ወደ ቀድሞ ቦታው ተመልልሷል። ከዚያም ኾኖ ፊቱን ታቦተ ጽዮን ወዳለችበት ወደ ምሥራቅ አዙሮ እጆቹን ዘርግቶ እንዲህ ብሎ ሰማያዊ ዜማን ለመጀመርያ ጊዜ በአኵሱም አደባባይ (ዐውደ ምሕረት) ዘመረ። "ሃሌ ሉያ ለአብ፣ ሃሌ ሉያ ለወልድ፣ ሃሌ ሉያ ወለመንፈስ ቅዱስ ቀዳሚሃ ለጽዮን ሰማየ ሣረረ ወበዳግም አርአዮ ለሙሴ ዘከመ ይገብር ግብር ግብራ ለደብተራ። ብሎ በዓራራይ ዜማ አዜመ። ይህም ማለት ዓለም ሳይፈጠር ለነበረ ዓለምን አሳልፎ ለዘለዓለም ለሚኖር አሁንም ላለ ለአብ ምስጋና ይገባል፤ ለወልድም ምስጋና ይገባል፤ ለመንፈስ ቅዱስም ምስጋና ይገባል፤ ከጽዮን አስቀድሞ ሰማይን ፈጠረ፤ ዳግመኛም ደብተራ ኦሪትን እንዴት አድርጎ መሥራት እንዳለበት ለሙሴ አሳየው ማለት ነው። ስለምን በዓራራይ ዜማ ጀመረ ቢሉ ቋንቋን የሚያናግር ምስጢር የሚያስተረጉም መንፈስ ቅዱስ የገለጠልኝ ዜማ ነው ሲል ነው። ምክንያቱም ዓራራይ ዜማ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ነውና።

አብርሃ ወአጽብሓ ከመንግሥት አስተዳደሩ ጋር ክርስትናንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በመላ ኢትዮጵያ በማዳረስ እጅግ ከፍተኛ አስተዋፅዖ አድርገዋል፡፡ ካህናትንና ዲያቆናትን ይዘው በመላ ኢትዮጵያ ሐዋርያዊ ጉዞ በማድረግ ሕዝቡን ሁሉ እያስተማሩ፣ ሃይማኖትን እያጸኑ፣ ሥርዓተ ጥምቀትን እያስፋፉ ብዙ አብያተ ክርስቲያናትን አንጸዋል፡፡ በሀገራችን በአራቱም አቅጣጫ ወንጌልን አስፋፍው ሕግ ሠርተዋል፡፡ የከበሩ ቅዱሳን ነገሥት አብርሃ ወአጽብሓ በእንዲህ ዓይነት ግብር ጸንተው በመኖር እግዚአብሔርንም ሰውንም አገልግለው ለሀገራችንም ብርሃን አብርተውላት ነው ያለፉት፡፡ ታላቁ አብርሃ በ364 ዓ.ም ጥቅምት 4 ቀን እሁድ ዕለት ዐረፉ፡፡ ከ13 ዓመት በኋላ ታናሹ አጽብሓ በ379 ዓ.ም ጥቅምት 4 ቀን ዐረፉ፡፡ ልደታቸውም ሆነ ሞታቸው አንድ ቀን ነው-የዕረፍታቸው ዓመቱ ይለያይ እንጂ፡፡ የተቀበሩበት ቦታም አንድ ነው፡፡ የንግሥና ስማቸው ኢዛናና ዛይዛና ይባላል፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_4 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ አራት በዚች ቀን #የከበሩ_ፊቅጦር_ዳኬዎስና_ኤርሞ በሰማዕትነት ሞቱ፣ #ቅዱሳን_ነገሥታት_አብርሃ_ወአጽብሓ መታሰቢያቸው ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_ፊቅጦር_ዳኬዎስና_ኤርሞ ሚያዝያ አራት በዚች ቀን የከበሩ ፊቅጦርና ዳኬዎስ ኤርሞ ሌሎችም ብዙዎች ሰዎች ሴቶችና ወንዶች ደናግሎች በሰማዕትነት ሞቱ። እሊህም ቅዱሳን በታላቁ ቈስጠንጢኖስና በልጁ ዘመነ መንግሥት የጣዖታትን ቤቶች አፍርሰው ጣዖታትንም ሰብረው አቃጥለው በቦታቸውም አብያተ ክርስቲያናትን ሠርተው አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በሌሎችም በብዙዎች ቅዱሳን ስም ታቦቱን ሰይመው ነበር። ከሀዲ ዮልያኖስም በነገሠ ጊዜ የጣዖትን አምልኮ አቆመ። የጣዖቱንም ካህናቶች አከበራቸው ብዙዎች ክርስቲያኖችንም አስገደለ። የእሊህ ቅዱሳን ዜናቸው አስቀድሞ በጣዖታት ቤቶች ላይ ያደረጉት ጣዖታትን እንደሰበሩ ሁሉ ተሰማ። ይዘውም ጽኑ ሥቃይን አሠቃዩአቸው ብዙ ቀንም ሲሰቅሏቸውና ሲገርፉአቸው ቆዳቸውንም በሾተል ሲነጥቁ ኑረው በኋላም ቸብቸቧቸውን በሰይፍ ቆረጡ። በመንግሥተ ሰማያትም የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበሉ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_ነገሥታት_አብርሃ_ወአጽብሓ ዳግመኛም በዚህ ቀን ቅዱሳን ነገሥታት አብርሃ ወአጽብሓ መታሰቢያቸው ነው። አባታቸው ታዜር እናታቸው ሶፍያ (አህየዋ) ይባላሉ፡፡ መንትዮች የሆኑት እነዚህ ቅዱሳን የተወለዱት ጌታችን በተወለደባት ዕለት በታኅሣሥ 29 ቀን 312 ዓ.ም ነው፡፡ በታላቁ አባት በአቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን እየተማሩ አድገው በእሳቸው እጅ በ330 ዓ.ም መጋቢት 29 ቀን ተጠመቁ፡፡ በእነርሱም ጊዜ አማናዊው ጥምቀትና ቁርባን መጣልን፡፡ በሀገራችን 154 አብያተ ክርስቲያናትን ያሠሩ ሲሆን 44ቱ ፍልፍል ናቸው፡፡ በተለይም ገርዓልታ ያለው ቀመር ዓርባዕቱ እንስሳ ፍልፍል ቤተ መቅደስ በሩ በራሱ ጊዜ ይከፈታል ይዘጋል እንጂ ሰው አይከፍተውም አይዘጋውም፡፡ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን በአክሱም ሲኖሩ ከሳምንቱ ቀናት ውስጥ ቅዳሜና እሁድ ብቻ የዛፍ ቅጠሎችን ከመመገብ በቀር ሌላ ምግብ ባለመመገብ በታላቅ ተጋድሎ ይኖሩ ነበር፤ አህልም አይቀምሱም፤ በየቀኑም አምስት ሺህ ስግደትን ይሰግዳሉ፡፡ በእርሳቸውም የተጋድሎ ዘመን ደጋግ የሆኑ ቅዱሳን ነገሥታት አብርሃና አጽብሓ ነገሡ፡፡ ነገሥታቱም ሆኑ የኢትዮጵያ ሕዝብ አቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃንን እጅግ በጣም ይወዷቸው ነበር፡፡ አባታችንም በእንዲህ ዓይነት ተጋድሎ ሲኖሩ ከዕለታት በአንደኛው ቀን የብርሃን እናቱ ድንግል ወላዲተ አምላክ ለአቡነ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ተገልጣላቸው ‹‹ዲቁናና ቅስናን መቀበል ይገባሃል፣ ለጵጵስና ተዘጋጅ፣ እግዚአብሔር ይህችን ከፍ ያለችውን ማዕረግ ሰጥተሃልና የልጄ ወዳጅ ሆይ በጸሎትህና በልመናህ በስብከትህም የኢትዮጵያ ሰዎች ሁሉ ይድናሉ፣ በእጅህ ጥምቀትንና ሥጋ ወደሙን ይቀበላሉ›› አለችው፡፡ ጌታችንም እንዲሁ ተገልጦላቸው ‹‹ወደ ሊቀ ጳጳሳት ወደ አትናቴዎስ ሄደህ ከፍ ያችውን ማዕረግ ተቀብለህ የኢትዮጵያን ሰዎች አጥምቅልኝ፣ ነቢዩ ዳዊት ስለ እነርሱ ‹ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች› ብሎ ተናግሯልና›› አላቸው፡፡ ነገሥታቱ አብርሃንና አጽብሓ ነገረ ክርስቶስን እያሰቡ ስለ ጥምቀት ልጅነት ይጨነቁ ነበር፡፡ ከሊቀ ካህናቱም ጋር በዚህ ጉዳይ ሲጨዋወቱ ሊቀ ካህናቱ ስለ አቡነ ሰላማ ነገሯቸው፡፡ ነገሥታቱም አቡነ ሰላማን አስጠርተው ስለነገረ ክርስቶስ ምሥጢር እንዲያስረዷቸው ጠየቋቸው፡፡ አባታችንም ‹‹ነቢያት በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝተው አካላዊ ቃል እግዚአብሔር ወልድ ይወለዳል ካሉበት ጀምሮ የልደቱን፣ የትምህርቱን የጥምቀቱን፣ የስቅለቱን፣ የሞቱን፣ የትንሣኤውንና የእርገቱን ነገር ሌላውንም ሁሉ ተንትነው አስተማሯቸው፡፡ ሐዋርያትም በጌታ ተሾመው ዓለምን ዞረው ማስተማራቸውን እንዲሁ ተረኩላቸው፡፡ ነገሥታቱም ይህንን በሰሙ ጊዜ እጅግ ደስ ብሏቸው ፍሬምናጦስን ‹‹ወንድማችን ሆይ! ይህን ሥርዓት በሀገራችን እንድታስፋፋ›› አሏቸው፡፡ አባታችን ግን ‹‹ለዚህ የሚያበቃ ሥልጣን ያለው እንጂ ለእኔ አይቻለኝም›› አሉ፡፡ ነገሥታቱም ‹‹ይህን የሚችል ማነው?›› ብለው ቢጠይቋቸው ‹‹በእስክንድርያ ጳጳሳትን፣ ቀሳውስትንና ዲያቆናትን የሚሾም አባት አለ አሏቸው፡፡ ከዚህም በኋላ ነገሥቱ ወደ እስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ወደ ቅዱስ አትናቴዎስ ደብዳቤ በመጻፍ ‹‹አባታችንና መምህራችን ሆይ! የምንጠይቅህን እሺ በጀ በለን ይኸውም ወደ ጽድቅ ጉዳና የሚመራንን ጳጳስ ሹምልን›› በማለት ብዙ ወርቅና ብር ገጸ በረከት አስይዘው ከብዙ ሊቃውንት ጋር ፍሬምናጦስን ወደ እስክንድርያ ላኳቸው፡፡ ከዚህም በኋላ አባታችን ከነገሥታቱ አብርሃና አጽብሓ ጋር ተማክረው ወደ እስክንድሪያ ሄደው በቅዱስ አትናቴዎስ እጅ በአገራችን ላይ ሊቀ ጳጳስ ሆነው ታኅሳስ 18 ቀን ተሾሙ፡፡ ቅዱስ አትናቴዎስ ከሾሟቸውና ከመረቋቸው በኋላ ለአቡነ ሰላማና አብረውት ለነበሩ ሊቃውንት መጻሕፍተ ብሉያትን፣ መጻሕፍተ ሐዲሳትንና ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን፣ ታቦተ ማርያምን፣ ታቦተ ሚካኤልንና ታቦተ ገብርኤልን አስይዘው ለነገሥታቱም ደብዳቤ ጽፈው ከብዙ ገጸበረከት ጋር በታላቅ ክብር ሸኟቸው፡፡ ቅዱሳን የሚሆኑ ሁለቱ ነገሥታትም አቡነ ሰላማ ከእስክንድርያ ተሾመው መምጣቸውን በሰሙ ጊዜ ‹‹የኢትዮጵያ ሰዎች ሁላችሁ እስከ 40 ቀን ተሰብሰቡ›› ብለው አዋጅ አስነገሩ፡፡ አባታችንንም በደብረ ሲናም ሄደው አገኟቸውና ከዚያች ቀን ጀምሮ ሕዝቡም ሁሉ እስከ 40 ቀን ድረስ ተጠመቁ፡፡ በዚያችም ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያች በደብረ ሲና አገር ላይ ወረደና ሕዝቡን ሁሉ ባረኮ ተመልሶ ሲያርግ ከአባ ሰላማ በቀር ያየው አልነበረም፡፡ ወደ አክሱምም ሄደው ቅዱሳን ነገሥታቱም የአድባራት ሁሉ የበላይ የምትሆን የቅድስት ጽዮንን ቤተ ክርስቲያን በወርቅና በዕንቊ ሠሯትና አባ ሰላማ ባርከው ቀደሷት፡፡ ታቦተ ጽዮንም ከድንኳን ወጥታ ማንም ካህን ሳይሸከማት አብርሃና አጽብሓ ወዳሠሩላት ቤተ መቅደስ ራሷ በመንፈስ ቅዱስ ገብታ ተገኘች፡፡ አባታችን በእመቤታችንም በዓለ ዕረፍት ጥር 21 ቀን በውስጧ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲቀድሱ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤል በግራ በቀኝ እየተራዷቸው እርሳቸውም ከምድር ሦስት ክንድ ከፍ ብለው ሥርዓተ ቅዳሴውን ፈጽመው ለነገሥታቱና ለሕዝቡም ሁሉ አቆረቧቸው፡፡ የዚያን ዕለትም እጅግ ታላቅ በዓልን አደረጉ፡፡ እነዚህም ቅዱሳን ነገሥታት ትምህርተ ወንጌልን እየሰጡ በአክሱም ቤተ መንግሥታቸው ሳሉ ከዕለታት አንደኛው ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መላእክቱን አስከትሎ መጥቶ በአክሱም ‹‹ማይ ኰኩሐ›› በሚባል ተራራ ላይ ቁሞ አብርሃ ወአጽብሓን ጠርቶ ‹‹በዚህች ቦታ ላይ ቤተ መቅደሴን አንጹልኝ›› አላቸው፡፡ እነርሱም ቦታው ባህር ላይ ነው በየት እናንጽልህ?›› አሉት፡፡ ጌታችንም በጥበቡ ከገነት ጥቂት አፈር አምጥቶ በባሕሩ ላይ ቢበትንበት ባሕሩ ደርቆ ሜዳ ሆነ፡፡ በዚህ ጊዜ ጌታችን ‹‹ቤተ መቅደሴን በዚህ ሥሩ›› ብሏቸው ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡ ጌታችንም በቆመባት ዓለት ላይ የእግሩ ጫማ ቅርጽ እስከ አሁን ሳይጠፋ በግልጽ ይታያል፡፡ ቦታውም ከዚያ ወዲህ ‹‹መከየደ እግዚእ›› እየተባለ ይጠራል፡፡

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_3 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሦስት በዚች ቀን የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ የከበረ አባት #አባ_ዮሐንስ አረፈ፣ የከበረ አባት በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባ አንደኛ የሆነ #አባ_ሚካኤል አረፈ፣ ክርስቲያናዊ ነጋዴ #ቅዱስ_መርቄ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ዮሐንስ ሚያዝያ ሦስት በዚች ቀን የኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ የከበረ አባት አባ ዮሐንስ አረፈ። የዚህም ቅዱስ ወላጆቹ የኦሪት ምሁራን የሆኑ አዋቂዎች ነበሩ የኦሪትን ሕግ ትምህርቶችንም እያስተማሩት አሳደጉት። ክርስቲያኖችን በጸና ልቡና የሚከራከራቸውና የሚጣላቸው ነበር መጻሕፍትን አዘውትሮ ከመመርመሩ የተነሣ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም እንደመጣና ሰውም እንደሆነ በሞቱም ዓለምን እንደአደነ አመነ። እርሱም የባሕርይ አምላክ እንደሆነ አምኖ በኢየሩሳሌም ኤጲስቆጶስ በአባ ዮስጦስ እጅ ተጠመቀ ዲቁናም ሾመው ከዚያም በኢየሩሳሌም ሀገር ኤጲስቆጶስነት ለመሾም እስቲገባው ድረስ በበጎ ስራና በዕውቀት አደገ። ኤልያስ የሚባለው እንድርያኖስም በነገሠ ጊዜ ከኢየሩሳሌም ሀገር የፈረሰውን ሕንፃ ሁሉ እንዲያንፁና በስሙ ኤልያስ ተብሎ እንዲጠራ አዘዘ። ከዚህም በአይሁድ ምኲራብ ደጃፍ ላይ ታላቅ ግምብ ሠሩ ከከበረ ድንጊያም ሠሌዳ ሠርቶ በላዩም ስሙን ኤልያስን ጽፎ በመግቢያው አኖረው በዘመኑም ኢየሩሳሌም አሕዛብንና አይሁድን ተመላች ሠለጡኑባትም። ክርስቲያኖችም ሊጸልዩ ወደ ጎልጎታ ሲመጡ በአዩአቸው ጊዜ አሕዛብ ይከለክሉአቸው ነበር በዚያ ዝሁራ በሚባል ኮከብ ስም መስጊድ ሠርተው ነበርና። ስለዚህም ክርስቲያኖችን በዚያ እንዳያልፉ ይከለክሏቸው ነበር። በዚህም አባት ላይ ከአሕዛብ ታላቅ መከራና በምድር ላይም ጐትተውታልና አጐሳቁለውታልና እርሱም ነፍሱን ወደርሱ ይቀበል ዘንድ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመነው ጌታም ልመናውን ሰምቶ በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ሚካኤል_ዘእስክንድርያ በዚህችም ቀን ደግሞ የከበረ አባት በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሰባ አንደኛ የሆነ አባ ሚካኤል አረፈ። ይህ አባት ከታናሽነቱ ጀምሮ የምንኲስና ልብስ ሊለብስ ወደደ በአስቄጥስ ገዳም በአባ መቃርስ ቤተ ክርስቲያን መንኲሶ እስከ ሸመገለ ድረስ በዚያ ኖረ። በብዙ መነኰሳትም ላይ አበ ምኔት ሆኖ ተሾመ በዘመኑ ሁለየ መልካም ተጋድሎ በመጋደል እግዚአብሔርን ደስ አሰኘው። በወንጌላዊው ማርቆስ ወንበር ላይ ሊቀ ጵጵስና ለመሾም እስቲገባው ድረስ ፍጹም ተጋድሎ በመጋደል ደከመ። ከእርሱ በፊት የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ገብርኤል በአረፈ ጊዜ የወንጌላዊ ማርቆስ ወንበር ያለ ሊቀ ጳጳሳት አራት ወር ኖረ ለዚች ሹመት የሚሻል ሲመረምሩና ሲመርጡ ብዙ ደከሙ። ከብዙ ድካምም በኃላ ሦስት የገዳም ሰዎችን መርጠው ስማቸውን በሦስት ክርታስ ጻፉ የክብር ባለቤት የጌታችንን ኢየሱስ ክርስቶስንም ስም በአንዲት ክርታስ ጽፈው እየአንዳንዳቸውን አሽገው በመሠዊያው ውስጥ አኖሩአቸው። ቸር ጠባቂ ይሾምላቸው ዘንድ ኤጲስቆጶሳቱና ካህናቱ እስከ ሦስት ቀን እየጸለዩና እየቀደሱ እግዚአብሔርን በመማለድ ኖሩ። ከሦስት ቀኖችም በኃላ አንድ ታናሽ ብላቴና ጠርተው ከእነዚህ ከሦስቱ ስሞች አንዱን አንሥተህ ስጠን አሉት። ያም ብላቴና የዚህን አባት የአባ ሚካኤል ስም ያለበትን ያንን ክርታስ አወጣ። ሁሉም እግዚአብሔር እንደመረጠው አውቀው ይገባዋል ይግባዋል ይገባዋል እያሉ ሊቀ ጵጵስና ሾሙት እርሱም በሹመቱ ላይሆኖ እንደሚገባ በመልካም አመራር ሥራውን መራ። የሚጽፍለትም ጸሐፊ መረጡለት ስለ ምእመናን አጠባበቅና ስለማስተማር ወደ ሀገሮች ሁሉና ወደ ኤጲስቆጶሳቱ መልእክትን ይልክ ነበር። እርሱም ከኃጢአታቸው ተመልሰው ንሰሐ እንዲገቡ ሕዝቡን ይመክራቸውና ይገሥጻቸው ነበር እግዚአብሔርን ይፈሩት ዘንድ። ንጽሐ ነፍስ ንጽሐ ልቡና ያለው ሆነ የዚህን አለም ጣዕም ያለውን ምግብ አይሻም አይመኝም ክብሩንም ቢሆን ወይም ጥሪቱን ድኆችንና ችግረኞችን አስቦ ይመጸውታቸው ነበረ እንጂ፡፡ ከእነርሱ የሚተርፈውንም ለቤተ ክርስቲያን ማሠሪያ ያደረገው ነበር። ይህ አባት ሙሉ ዓመት አልኖረም ከዚያ የሚያንስ ነው እንጂ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞https://t.me/finotebirhan12

🔴#ኒቆዲሞስ (የዐቢይ ጾም ሰባተኛ ሳምንት) ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ በነበረው በኒቆዲሞስ የተሰየመ ሰንበት ነው፡፡ የአይሁድ አለቆች አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን “ምልክት አሳየን” እያሉ ይፈታተኑት ነበር፡፡ ስለሞቱና ትንሣኤው በምሳሌ ቢነግራቸው አልገባቸውም፡፡ ሲያስተምር ብዙዎች ያምኑ ነበር፡፡ ለአይሁድ አለቆች ግን ጭንቅ ነበር፤ የታመሙ ሲፈወሱ ሕጋችን ተሻረ ይሉ ነበር፡፡ በዚህ ሁሉ ተአምራትና ትምህርት የአይሁድ አለቆች ክርስቶስን ለመክሰስ በሚፈልጉበት ወቅት ከአይሁድ አለቆች አንዱ ኒቆዲሞስ በቀን እንዳያደርገው አይሁድን ፈርቶ አንድም ጊዜ አላደርሰው ብሎ እንደ አይሁድ አለቆች ኢየሱስን መቃወሙን ትቶ በሌሊት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ሄደ፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነፍስ የታመሙትን በቃሉ በሥጋ የታመሙትን በተአምራቱ ሲፈውስ፤ ኒቆዲሞስ ሰምቶና ተመልክቶ “መምህር ነኝ” ብሎ በመምህርነቱ ሳይኮራ አለቅነቱን መመኪያ ሳያደርግ፡፡ በልቦናው የተሳለውን እውነትን የመፈለግ ስሜት አንግቦ ጌታው መምህሩ ዘንድ በሌሊት ገሠገሠ ዮሐ.3÷1ደርሶም ምስክርነቱን እንዲህ ሲል መስጠት ጀመረ “መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና” ዮሐ.9÷24፣ የሐዋ.ሥራ 10÷38 በማለት መመስከር ሲጀምር ጎዶሎን የሚሞላ፡፡ አላዋቂነት በአዋቂነት የሚለውጥ፡፡ ከምድራዊ እውቀት ወደ ሰማያዊ ምስጢር የሚያሸጋግር አምላክ፡፡ “ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” ዮሐ.3÷6 ,1ጴጥ.1÷23 በማለት የአይሁድ መምህር ለሆነው ኒቆዲሞስ ቢያስተምረው ስለዳግመኛ መወለድ ከመጽሐፍ ቢያገኘውም ምስጢሩ አልተገለጠለትምና “ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?” በማለት ጥያቄ አቅርቧል፡፡ “እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዝአበሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ኤፌ.5÷26 ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፡፡ በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቢያስረዳው ምስጢሩ ከአቅሙ በላይ የሆነበት ኒቆዲሞስ እንደምን ይቻላል? በማለት ጠይቋል፡፡ አበ ብዙኀን አብርሃም ከአምላኩ ሞገስን አግኝቶ፤ የሰዶምና ገሞራ ጥፋት እንዳይደርስ እያማለደ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር እንደ ነበረ፤ ኒቆዲሞስም አላዋቂነቱን አምኖ ያልገባውን ምስጢር አምላኩን የመጠየቅ ዕድል በማግኘቱ ሲጠይቅ፣ ኢየሱስ ክርስቶስም “አንተ የእስራኤል መምህራቸው ነህ ግን ይህን ነገር አታውቅምን? በምድር ያለውን ስንነግራቸው ካላመናችሁ በሰማይ ያለውን ብንነግራችሁ እንደምን ታምናላችሁ? ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም፡፡ ሙሴ ምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለ የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀላል፡፡ ያመኑበት ሁሉ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ እንዲኖር እንጂ እንዲጠፉ አይደለም…..” ዮሐ.3÷14፡፡ እያለ ለድኅነተ ዓለም እንደ መጣ ሰው በመብል፣ አምላኩን ከድቶ ልጅነቱን ትቶ ከእግዚአብሔር ቢለይም የሰው ልጅ ያጣውን ልጅነት ለመመለስ ስመ ግብርና ሀብተ ወልድን ለመስጠት መምጣቱን አስረዳው። “ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ፡፡ አመከርከኒ ወኢተረከ በዓመፃ በላዕሌየ፡፡ ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ እጓለ እመሕያው፡፡ ልቤን ፈተንከው በሌሊትም ጎበኘኸኝ ፈተንከኝም ምንም አላገኘህብኝም፡፡ የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው” መዝ.16÷3 እንዳለ ቅዱስ ዳዊት ምስጢረ ሥጋዌን የድኅነት ምስጢር ገልጾለታል፡፡ በሌሊት ከአምላኩ ተምሮ ምስጢሩ የተገለጸለት ኒቆዲሞስ ፍርሃት ርቆለት ቀድሞ በአደባባይ ሄዶ መማርን የፈራ ምስጢሩ ሲገለጽለት አይሁድ በሰቀሉት ዕለት ሳይፈራ ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ ለመቅበር በቃ “ወአልቦ ፍርሃት ውስተ ተፋቅሮትነ፡፡ ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል ማቴ.27÷58፣ 1ዮሐ.4÷18 እንዲል፡፡ ያመነ የተጠመቀ ይድናል፡፡ ያላመነ ያልተጠመቀ ይፈረድበታል ማር.16÷16፡፡ ባለው አማናዊ ቃል ኪዳን መሠረት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አምላክነቱ አምነን ለመንግሥቱ ዜጋ እንድንሆን ለኒቆዲሞስ ምስጢሩን ጥበቡን የገለጸ አምላክ ለኛም ይግለጽልን፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴ስንክሳር #ሚያዝያ_2 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሁለት በዚህችም ቀን የቃይናን ልጅ #የቅዱስ_መላልኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ ፊቱ እንደ ውሻ የሆነ #ቅዱስ_ክርስትፎሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_መላልኤል ሚያዝያ ሁለት በዚህችም ቀን የቃይናን ልጅ የመላልኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ መላልኤልም መቶ ስልሳ አምስት ዓመት ኖረ ያሬድንም ወለደው። መላልኤልም ያሬድን ከወለደው በኃላ ሰባት መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። የመላልኤልም መላ ዘመኑ ሁሉ ስምንት መቶ ዘጠና አምስት ዓመት ነው። ቅዱስ መላልኤልም ሚያዝያ ሁለት ቀን በእሑድ ዕለት ሞተ በማከማቻም ውስጥ ቀበሩት። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ክርስቶፎሮስ (ሐዋርያና ሰማዕት) በዚችም ቀን ፊቱ እንደ ውሻ የሆነ ቅዱስ ክርስትፎሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ ሰውን ይበሉ ከነበሩ ሰዎች ሀገር ነው በጦርነትም ማረኩት አባቱም በሐዋርያ ማትያስ እጅ ያመነ ነው። በማረኩትም ጊዜ ቋንቋቸውን አያውቅም ነበር የክብር ባለቤት ወደሆነ እግዚአብሔርም ማለደ ቋንቋቸውንም ገልጦለት እንደርሳቸው ተነሰገረ የክርስቲያን ወገኖችን የሚያሠቃዩአቸውንም ገሠጻቸው የጦር ሠራዊቱንም የሚመራ መኰንን ጽንዕ ግርፋትን ገረፈው። ቅዱስ ክርትፎሮስም መኰንኑን የጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ትእዛዙ ኃይሌን ባትይዘኝና ባታስታግሠኝ አንተና ሠራዊትህ ከእኔ እጅ ባልዳናችሁ ነበር አለው። መኰንኑም ስለ ርሱ ወደ ንጉሥ ላከ ከእርሱ የሆነውንም ነገረው። ንጉሡም ወደ ርሱ እንዲያመጡት ሁለት መቶ ወታደሮችን ላከለት እርሱም ያለ መፍራት ያለ ማፈግፈግ አብሮአቸው ሔደ። በእጁ በትር ነበረች በላይዋ በጸለየ ጊዜ በቀለችና አበበች። እነዚያ ወታደሮች ተርበው የሚበሉት እንጀራ በአጡ ጊዜ ቅዱስ ክርስትፎሮስ ጸለየ በእነርሱ ዘንድ እንጀራ በዝቶ ተትረፈረፈ እጅግም አድንቀው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። አባ ጳውሎስ እጅ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቁ። ወደ ንጉሡም ፊት በደረሱ ጊዜ ንጉስ ዳኬዎስ ሊያስፈራውና ሊሸነግለው ጀመረ ደግሞ እጅግ መልከ መልካም የሆኑ ሁለት አመንዝራ ሴቶችን ወደርሱ ሰደደ እነርሳቸው እንደሚያስቱትና በኀጢአት እንደሚጥሉት አስቧልና። እርሱ ግን ገሠጻቸው አስተማራቸውም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በደማቸው ምስክር ሁኑ። እንዲሁም እነዚያ ሁለት መቶ ወታደሮች በንጉሡ ፊት በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ ራሶቻቸውንም በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የሰማዕትነትንም በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። ቅዱስ ክርስትፎሮስም ንጉሡን አንተ የሰይጣንን ሥራ የምትቀበል ማደሪያው የሆንክ ብሎ ዘለፈው ንጉሡም ተቆጥቶ በትልቅ ብረት ምጣድ ውስጥ እንዲጨምሩትና ከበታቹ እሳትን እንዲያነዱ አዘዘ። እንዲሁም አደረጉበት ነገር ግን ከጉዳት እንዳሰቡት ምንም የደረሰበት የለም። ጤነኛ ሆኖ ሰዎችን አስተማራቸው እንጂ። እጅግም አድንቀው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ቅድሱንም ከእርሷ ሊአወጡት ወደዚያች ብረት ምጣድ ቀረቡ ንጉሡም አንገቶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጧቸው አዘዘ የሕይወት አክሊልንም ተቀበሉ። ከዚያም በኃላ ታላቅ ደንጊያ በአንገቱ አንጠልጥለው ከጥልቅ ጉደረጓድ እንዲጨምሩት ንጉሡ አዘዘ በጨመሩትም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ በጤንነት አወጣው። ማሠቃየቱንም በሰለቸ ጊዜ አንገቱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ ንጉሡ አዘዘ። ቅዱሱም በእግዚአብሔር መንግስት የድል አድራጊነትን አክሊል ተቀዳጀ፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_1 ሚያዝያ አንድ በዚህች ቀን ለሙሴ ወንድሙ የሆነ #የካህኑ_አሮን የእረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፣ የከበረ አባት #አባ_ስልዋኖስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አሮን_ካህን ሚያዝያ አንድ በዚህች ቀን በእስክንድርያ ከተማ በሚገኝ በግብፃውያን መፅሀፍ እንደ ተፃፈ በላዕላይ ግብፅ ያለ ግብፃዊውም እንደፃፈ ለእንበረም ልጅ ለሙሴ ወንድሙ የሆነ የካህኑ አሮን የእረፍቱ መታሰቢያ ሆነ ይላሉ። በኦሪቱ መፅሀፍ የተፃፈው ግን እስራኤል ከግብፅ ከወጡ በሁለተኛው ወር በሶስተኛው ቀን አረፈ ይላሉ። ይኸውም ግንቦት ስምንት ነበር የእስራኤል ወሮች በጨረቃ እየተቁጠሩ ዓመቱን ስለሚዞሩ በዚያች ዓመት ሚያዝያ አንድ ቀን ሆኖ ስለተገኘ። በእኛ ዘንድ ግን የኦሪት ዘኁልቁ መፅሐፍ በአምስተኛው ወር መባቻ ስለሚል መታሰቢያውን ነሐሴ አንድ ቀን እናደርጋለን። ይህም ፃድቅ ሰው የነቢያት አለቃ ለኦሪት ሕግ መምህር ለሆነ ለሙሴ ለነቢዪት ማርያምም ወንድም ነው እነርሱም ከሌዊ ነገድ ናቸው። እግዚአብሔርም በግልፅ ምድር ብዙ አስደናቂ ተአምራትን በእጆቹ አደረገ። እግዚአብሔርም እርሱንና ልጆቹን መርጦ ካህናቶቹ አድርጎ ከእስራኤል ልጆች ከገንዘባቸውና ከመሥዋዕታቸው ዐስራትን ሰጣቸው። የቆሬም ልጆች በጠላትነት በተነሱበት ጊዜ እግዚአብሄር ፈርዶ አጠፋቸው ምድርንም አዘዛት አፍዋንም ከፍታዋጠቻቸው። በበጎ ተጋድሎውና የኦሪትንም ሕግ በመጠበቅ እግዚአብሔርን ከአገለገለ በኋላ ሔደ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ስልዋኖስ_ጻድቅ በዚህች ቀን የከበረ አባት አባ ስልዋኖስ አረፈ። ይህም አባት በአስቄጥስ ገዳም ከከበረ አባ መቃርስ ዘንድ በታናሽነቱ መነኰሰ በጠባብ መንገድ ሁሉ ተጋደለ በብዙ ፆምና ፀሎተረ በመትጋት በትሕትና በፍቅር ተወስኖ ኖረ ታላቅ አባትም ሆነ። የክብር ባለቤት ጌታችንም አምላካዊ ራእይን ይገልፅለት ነበር ድንቅ የሆኑ ነገሮችንም ይነግረዋል። ይህም እንዲህ ነው በአንዲት እለት ልቡ ተመስጦ በምድር ላይ በግምባሩ ተደፍቶ ብዙ ጊዜ ቆየ ከዚያም በኃላ ነቅቶ ራሱን ቀና አደረገ። ከእርሱ ዘንድ ያሉ ወንደረሞች መነኩሳትም በእርሱ ላይ የደረሰበትን ይነግራቸው ዘንድ ለመኑት ዝም ብሎ መሪር ልቅሶ ያለቅሳል እንጂ ሊነግራቸው አልወደደም። ከእርሱ የሆነውን ያሰረዳቸው ዘንድ ግድ ባሉት ጊዜ እንዲህ አላቸው ተድላ ወዳለበት ገነት አውጥተውኝ በዚያ የፃድቃንን መኖሪያ አየሁ ደግሞ የስቃይ ቦታዎችንም። ሁለተኛም ብዙዎች መነኮሳትን ወደ ገሀነም ብዙዎች ምእመናን ወደ መንግስተ ሰማያት ሲወስዱአቸው አየሁ እንግዲህ እኔ ለነፍሴ የማላለቅስ ለምንድነው አላቸው። ከዚያች ቀንም ጀምሮ በኃላ ወደዘላለም ጨለማ ሊወስዱኝ ዛሬ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ብርሃን ማየት አልሻም እያለ ፊቱን በቆቡ ሸፍኖ የሚያለቅስ ይህም አባት በመንፈሳዊ ስራ የተጠመደ ሆነ ደቀ መዛሙርቱንም ለምግባቸው የሚሆን ስራን ከመስራት እንዳያቋርጡ ከዕለት ምግባቸው የሚተርፈውንም እንዲመፀውቱ ያዛቸዋል። በአንዲት ቀንም አንድ ታካች የሆነ መነኮስ ወደርሱ መጣ ሽማግሌውን አባትና ደቀ መዛሙርቱን ሲሰሩ አይቶአቸው ለኃላፊ ምግብ ትሰራላችሁ ትደክማላችሁ። የዘላለም ህይወት ለሚሆን ምግብ ስሩ ድከሙ እንጂ ይህ በከበረ ወንጌል የተፃፈ አይደለምን ማርያምም የማይቀሟትን በጎ ዕድል ትምህርትን እንደመረጠች ብሎ ጠቀሰ። ሽማግሌው አባ ስልዋኖስም እንዲህ ሲናገር በሰማው ጊዜ ደቀ መዝሙሩን እንዲህ ሲል አዘዘው። ይህን መነኩስ ከእንግዳ ማሳረፊያ ቤት አስገብተህ የሚያነበው መፅሀፍ ስጠው በሩንም በላዩ ዝጋ በእርሱ ዘንድም ለመብል የሚሆን ምንም ምን አትተው። ረድኡም ሽማግሌው መምህሩ እንዳዘዘው አደረገ። ዘጠኝ ሰዓትም ሲሆን መነኰሳቱ ተሰበሰቡ ከሽማግሌው አባትም ጋር ፀሎት አድርገው ምግባቸውን ተመገቡ። ያን እንግዳ መነኰስ ግን አልጠሩትም እርሱም ቢጠሩኝ ብሎ ወደ ደጃፍ እየተመለከተ ይጠብቅ ነበር። በረኃብም በተቃጠለ ጊዜ ከበአቱ ወጥቶ ወደ አባ ስልዋኖስ ሒዶ አባቴ ሆይ መነኮሳቱ ራታቸውን በሉን አለው ሽማግሌውም አዎን በሉ ብሎ መለሰለት። ሁለተኛ ደግሞ እኔ እንግዳ ስሆን ለምን አልጠራችሁኝ አለ የከበረ አባት ስልዋኖስም አንተማ ስጋዊ መብል የማትሻ መንፈሳዊ ሰው ነህ በጎ እድልን ስለመረጥክ እኛ ግን ስጋውያን ሰዎች ለስጋዊ መብል የምንሰራ የምንደክም ነን ስለዚህም ለምግባችን የሚሆነውን በእጃችን እንሰራለን ብሎ መለሰላት። ያ መነኮስም በንግግሩ እንደበደለ አወቀ። አባ ስልዋኖስንም አባቴ ሆይ እኔ በድያለሁና ይቅር በለኝ ብሎ ሰገደለት።አባ ስልዋኖስም ማርታ በመስራት እንደ ደከመች እንድከም እንስራ ከማርያ ይልቅ ማርታ የተዘጋጀች ሁናለችና ብሎ መለሰለት። ያ ታከች የነበረ መንኰስም በዚህ አባት ትምህርት ተመክሮና ተገስፆ ሁልጊዜ የሚሰራና ከእርሱ የሚተርፈውንም ለድኆች የሚመፀውት ሆነ።ይህም አባት ስለ መንፈሳዊ ተጋድሎ ጥቅም ያላቸው ብዙ ድርሳናትንና ተግሳጳትን ደረሰ። ዕድሜውም በመልካም ሽምግልና በተፈፀመ ጊዜ የሚያርፍባትን ሰዓት እግዚአብሄር ነግሮት በእርሱ አቅራቢያ ያሉ መነኮሳትን ጠርቶ ከእርሳቸው በረከትን ተቀበለ። በፀሎታቸውም እንዲአስቡት ለመናቸው እነርሱም በእግዚአብሄር ዘንድ እንዲአስባቸው ለመኑት እርስ በርሳቸውም ተሰነባብተው በፍቅር በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_መነኮሳት በዚችም ቀን ደግሞ በላይኛው ግብፅ ያሉ አረቦች ተሰብስበው በአስቄጥስ ያሉ አድባራትንና ገዳማትን የአባ መቃርስንም ቤተ ክርስቲያን ከበቡ በአድባራቱና በገዳማቱ ያለውንም እቃ ሁሉ ማርኩ። መነኰሳትም ተሰበሰቡ በከበሩ አባቶችም ስም ወደ እግዚአብሄር በፀሎት ማለዱ። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እነዚያን ዐረቦች አስደንግጦ አሳደዳቸው ያንጊዜም ማንም የተከተላቸው ሳይኖር ድል ሆነው ሸሹ። ከክብር ባለቤት ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል በቀር ማንም የተከተላቸው ሳይኖር ነው።ይቅር ብሏቸዋልና ጌታችንን አመሰገኑት፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን https://t.me/finotebirhan12፡፡

🔴#ስንክሳር መጋቢት_30 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሠላሳ በዚህች ቀን ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለተሰጠው ስለ ክብሩ ልዕልና ለከበረ #መልአክ_ቅዱስ_ገብርኤል የወልደ እግዚአብሔርን ሰው የመሆኑን ዜና ያበሰረበት መታሰቢያ ነው፣ #የቅዱስ_ያዕቆብ_ዘግሙድ የስጋው ፍልሰት የሆነበት ነው፣ከእስራኤል ልጆች መሳፍንት አንዱ የሆነ #የመስፍኑ_ሶምሶን መታሰቢያው ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ገብርኤል_ሊቀ_መላእክት መጋቢት ሠላሳ በዚህች ቀን ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለተሰጠው ስለ ክብሩ ልዕልና ለከበረ መልአክ ለገብርኤል የወልደ እግዚአብሔርን ሰው የመሆኑን ዜና ለምትወልደው ለድንግል ማርያም እንዲአበስራት የተገባው ስለሆነ በዓሉን ልናከብር ይገባል። ስለዚህ በዚች በከበረች ታላቅ ፀጋ በዚህ መልአክ እጅ እግዚአብሔር ይቅር ብሎናልና ፈፅሞ ልናከብረው ይገባናል። እርሱም ደግሞ ስለ ክርስቶስ መምጣትና ለዓለም ድኅነት መገደሉን ለኢየሩሳሌምም መዳኛዋ መሆኑን ስለ ወገኖቹ ከምርኮ መመለስ ሲጸልይ ለዳንኤል የነገረው ሱባዔዎችንም የወሰነለትና በሱባዔዎቹም መጨረሻ ንጹሀን የሚነጹበት የክብር ባለቤት ክርስቶስ ይመጣል ይገድሉታልም ለኢየሩሳሌምም መደኛዋ ይሆናታል ያለው ይህ መልአክ ነው። ከዚያ በኋላም ለእስራኤል ልጆች የሚደረጉ መስዋእቶችና ቁርባኖች ይሻራሉ። የክብር ባለቤት ጌታችን ስለ ዓለሙ ሁሉ ድኅነት ለእመቤታችን ማርያም ከእርስዋ መወለዱን ይነግራት ዘንድ የተገባው አድርጎታልና ስለዚህ ሁልጊዜ የበዓሉን መታሰቢያ ልናደርግ ይገባናል። ጌታ ከጠላታችን ሰይጣን እጅ ያድነን ዘንድ ስለ እኛ እንዲማልድ በበጎ ስራ ሁሉ እንዲረዳን እንለምነው ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ያዕቆብ_ዘግሙድ ዳግመኛም በዚህችም ቀን ደግሞ ለፋርስ ንጉሥ ለሳፎር ልጅ ለንጉሥ ሰክራድ ከጭፍሮቹ ውስጥ የሆነ ሕዋሳቱን የተቆራረጠ የቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ የስጋው ፍልሰት የሆነበት ነው፡፡ ይህም ንጉሥ ሰክራድ እጅግ ይወደው ነበር ስለ መንግሥቱ ሥራ ሁሉ ከእርሱ ጋር ይማከር ነበርና ስለዚህም የቅዱስ ያዕቆብን ልቡና አዘንብሎ ፀሐይንና እሳትን እንዲአመልክ አደረገው፡፡ በሃይማኖቱም ከንጉሡ ጋር እንደተስማማ የተቀደሱ እናቱ ሚስቱና እኅቱ በሰሙ ጊዜ እንዲህ ብለው ጽፈው ወደርሱ ላኩ የቀናች የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት ትተህ የፍጡራንን ጠባይ ለምን ተከተልክ እሊህም ፀሐይ ጨረቃ ከዋክብት እሳት ናቸው ዕወቅ ከዛሬ ጀምሮ በንጉሥ ሃይማኖት ከኖርክ እኛ ከአንተ የተለየን ነን። የመልእክታቸውንም ጽሑፍ በአነበበ ጊዜ መሪር ልቅሶን አለቀሰ በዚህም የጥፋት ምክር ጸንቼ ብኖር ከቤተ ሰቦቼና ከወገኖቼ የተለየሁ መሆኔ ነው። ደግሞስ በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ፊት እንዴት እቆማለሁ አለ ከዚህም በኋላ የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍቶች ማንበብ ጀመረ የንጉሡን አገልግሎትም ተወ ለንጉሡም ወዳጅህ ያዕቆብ እነሆ አገልግሎትህን አማልክቶችህንም ማምለክ ተወ ብለው ነገሩት። ንጉሡም ልኮ ወደርሱ አስቀርቦ አገልግሎትህን ለምን ተውክ አለው ቅዱስ ያዕቆብም እንዲህ አለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከበረ ወንጌል በሰው ፊት ያመነብኝን ሁሉ እኔም በሰማያዊ አባቴ ፊት አምነዋለሁ በሰው ፊት የካደኝንም በአባቴ ፊትና በመላእክት ፊት እክደዋለሁ ብሏልና ስለዚህ አገልግሎትህን ፍቅርህን አማልክቶችህንም ማምለክ ትቼ ሰማይና ምድርን ፀሐይን ጨረቃን ከዋክብትን የሚታየውንና የማይታየውን ለፈጠረ ለሕያው እግዚአብሔር ልጅ ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የምሰግድ ሆንኩ። ንጉሡም ይህን በሰማ ጊዜ ደሙ እንደ ውኃ በዝቶ እስቲፈስ ታላቅ ግርፋትን እንዲገርፉት አዘዘ እርሱ ግን ከበጎ ምክሩ አልተመለሰም ዳግመኛም ሕዋሳቱን በየዕለቱ እንዲቆርጡ አዘዘ የእጆቹንና የእግሮቹን ጣቶች ሃያውን ቆረጡ ክንዶቹንና እግሮቹን እስከ ጭኖቹ ድረስ ወደ አርባ ሁለት ቁራጭ በየጥቂቱ ቆረጡት። በሚቆርጡትም ጊዜ ሁሉ ጌታዬና ንጉሤ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ዕንጨት ቅርንጫፍ ሰውነቴን በይቅርታህ ገናናነት ተቀበል የወይን አታክልት ያለው በየሦስት ዓጽቅ ሲቆርጡለት ዓጽቆቹ በዝተው ይበቅላሉ ይሰፋሉ በሚያዝያ ወር አብቦ ያፈራልና እያለ የሚዘምርና የሚያመሰግን ሆነ። ደረቱና አካሉ እንደ ግንድ ድብልብል ሆኖ በቀረ ጊዜ ነፍሱን ለመስጠት እንደ ደረሰ አውቆ በዚያን ጊዜ በዓለም ውስጥ ያሉትን ሰዎች ሁሉንም ይምራቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ለመነው እንዲህም አለ ለእኔ ግን ወደ አንተ የማነሣው አካል አልቀረልኝም ሕዋሳቶቼ ተቆርጠው በፊቴ የወደቁ ስለሆነ አሁንም ነፍሴን ተቀበላት አለ። በዚያንም ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ አረጋጋው አጸናውም ያን ጊዜ ነፍሱ ደስ አላት ነፍሱንም ከመስጠቱ በፊት ወታደሩ በፍጥነት መጥቶ የከበረች ራሱን በሰይፍ ቆረጠ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ ሥጋውንም ምእመናን ሰዎች ወስደው በመልካም አገናነዝ ገነዙትና በንጹሕ ቦታ አኖሩት። እናቱ ሚስቱና እኅቱ በሰማዕትነት እንደሞተ በሰሙ ጊዜ እጅግ ደስ አላቸው ወደ ቅዱስ ያዕቆብም ሥጋ መጥተው ተሳለሙት አለቀሱለትም የከበሩ ልብሶችንም በላዩ አኖሩ ጣፋጮች የሆኑ ሽቱዎችንም ረጩበት። በደጋጎች ነገሥታት በአኖሬዎስና በአርቃዴዎስ በሌሎችም ዘመን አብያተ ክርስቲያን ታነፁ ገዳማትና አድባራትም ተሠሩ የሰማዕታትንም ሥጋ በውስጣቸው አኖሩ ታላላቆች ድንቆች ተአምራትም ከእሳቸው የሚታዩ ሆኑ። የፋርስ ንጉሥም ሰምቶ በቦታው ሁሉ የሰማዕታትን ሥጋ ያቃጥሉ ዘንድ አዘዘ በሚገዛውም አገር ውስጥ ምንም ምን እንዳይተው አማንያን ሰዎችም መጥተው የቅዱስ ያዕቆብን ሥጋ ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዱት ከዚያም ወደ ሀገረ ሮሀ ከሀገረ ሮሀም የከበረ ኤጲስቆጶስ ጴጥሮስ ወደ ግብጽ አገር ወደ ብሕንሳ ከተማ ወሰደው። በዚያም ጥቂት ጊዜ ኖረ ከርሱ ጋርም መነኰሳት ነበሩ ከቀኑ እኩሌታም ሲጸልዩ የቅዱስ ያዕቆብ ሥጋ ከብዙ የፋርስ ሰማዕታት ሥጋ ጋር በአለበት ሰማዕታት አብረዋቸው ዘመሩ ባረኳቸውም ቅዱስ ያዕቆብም እግዚአብሔር እንዳዘዘ ሥጋዬ በዚህ ይኑር አለ ከዚህም በኋላ ተሠወሩ። ከዚህም በኋላ የከበረ ኤጲስቆጶስ ጴጥሮስ ወደ አገሩ ሊመለስ በወደደ ጊዜ ሥጋዬ በዚህ ቦታ ይኑር ያለውን የቅዱስ ያዕቆብን ቃል ተላልፎ የቅዱስ ያዕቆብን ሥጋ ወሰደ በዚያንም ጊዜ አስቀድሞ ወደ አመለከተው ቦታ ከእጆቻቸው መካከል ተመለሰ ከሥጋውም ታላላቅ የሆኑ ተአምራት ተገለጡ ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞https://t.me/finotebirhan12

ምሕረትንና ርኅራኄን የተመላች እመቤቴ የብርሃን እናት ድንግል ማርያም ይህን ስትናገረኝ እነሆ በእጃቸው የጦር መሣሪያ የያዙ ኃይለኞች ሰዎችን የተሞሉ መርከቦችን በቅርብ አየኋቸው እጅግም ፈራሁ እመቤቴ ማርያምም ተሠወረችኝ። ነገር ግን ከደመና ውስጥ ጳውሎስ ሆይ ሰዎችን አጥምቅ ማጥመቅንም አታቋርጥ የሚለኝን ቃል እሰማ ነበር። እኔም በታላቅ ቃል ፈጣሪዬ ሆይ ይህን የባሕር ውኃ ለእሊህ ለተጣሉ በጎች ሰይጣንም ለማረካቸው ጥምቀትን አድርገው ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በዚህ ባህር ጥምቀት እሊህን ሰዎች በሦስትነትህ ስሞች የልጅነትን ክብር የሚቀበሉ አድርጋቸው በማለት አሰምቼ ተናገርኩ። እንዲህም ይህን እያልኩ ከባሕሩ ውኃ ዘግኜ ሰዎች በአሉባቸው መርከቦች በላያቸው ረጨሁት የሰዎቹም ቁጥራቸው አንድ መቶ ሃምሳ ሺህ ነው። እኔ ወደአለሁበት የባሕር ዳር በደረሱ ጊዜ ከመርከባቸው ወጥተው ፈለጉኝ እኔም እመቤቴ የብርሃን እናት እንዳዘዘችኝ በፊታቸው ቆምኩ በረድኤቷ ተማምኛለሁና አልፈራሁም። በአዩኝም ጊዜ ሁሉም በፊቴ ሰገዱ በአንድ ቃልም ቅዱስ ጳውሎስ ሆይ ፍቅር አንድነት ለአንተ ይሁን ወደአንተ ከመድረሳችን በፊት በመርከቦች ውስጥ እያለን እኛ ያየነውን አየህን አሉኝ። እኔም አዲስ የተወለዳችሁ ልጆች ሆይ ምን አያችሁ አልኋቸው የሰማይ ደጆች ተከፍተው የቀኝ እጅ እንደ እሳት ነበልባል ተዘርግታ አየን ደግሞ የፊቷ ብርሃን ከፀሐይ ሰባት እጅ የሚበራ ሴት አየን። እርሷም ከደመና በታች የምትረጨውን ውኃ ተቀብላ በላያችን ትረጨዋለች ትስመናለች ታቅፈናለችም። በራሲቻችንም ላይ የብርሃን አክሊሎችን ታደርጋለች አሉኝ። ይህንንም በሰማሁ ጊዜ ፈጽሞ ደስ አለኝ በስሙ በምንሠራው ሥራ ሁሉ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር እንዳለ ተረዳሁ። ከዚህም በኋላ ሌሎች መርከቦች መጡ ኃይለኞች ሰዎችን ከጦር መሣሪያ ጋር የተመሉ ናቸው እንዲህም እያሉ ዛቱበኝ። አንተ ሥራየኛ ጥበበኞች ሕርምስና በለንዮስ ታምራት የሚያደርጉባቸው የጠልሰም መጻሕፍቶች ከእኛ ጋራ እንዳሉ ዕወቅ በማለት እኔም ቸር ፈጣሪዬ ሆይ የቀደሙትን በጎች ይቅር እንዳልካቸውና በውስጣቸው ኃይልህን እንደገለጥክ ለእነዚህም እንዲሁ ኃይልህን ግለጥ ይቅርም በላቸው አልኩ። ከዚያም በኋላ ከባሕሩ ውኃ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጥምቀትን ይሁናችሁ አልኩ ወዲያውኑ መርከቦች ከባሕሩ ዳር ደረሱ። ሁሉም ሰዎች ከመርከብ ወጥተው በፊቴ ሰገዱ የቸር አምላክ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሆይ እናመሰግንሃለን አሉኝ። ይህንንም ድንቅ ተአምር ከቀደሙት ባልንጀሮቻቸው ጋራ ተነጋገሩ ዜናዬም በዚያች አገር ንጉሥ ዘንድ ተሰማ እርሱም ከሰራዊቱ ጋር ተነሳ በመርከቦችም ተጭነው ወደእኔ መጡ። እኔም ዐይኖቼን ወደ ሰማይ አቅንቼ የፈጣሪዬን ስም ጠራሁ ባሕርዋንም በመስቀል ምልክት አማተብኩባት። እንዲህም አልኳት አንቺ ባሕር በእግዚአብሔር ልጅ በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ትከፈዪ ዘንድ አዝሻለሁ ምድሩም ይገለጥ መርከቦችም በየብስ ውስጥ ይቁሙ። ነገሬንም ሳልጨርስ ባሕርዋ ተከፈለች በውስጥዋም ዐሥራ ሦስት ጎዳናዎች ተገለጡ መርከቦቹም ውኃ በሌለው ምድር ላይ ቆሙ ይህንንም አይተው ሰይፎቻቸውን መዘዙ ዕንጨቶችም ሆነው አገኙአቸው እኔም ከሕህሩ ውኃ ዘግኜ በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ እያልኩ በላያቸው ረጨሁ። በዚያን ጊዜ እሊያ መርከቦች ነፋስ ተሸክሟቸው ያለ ውኃ ከምድር ከፍ ከፍ ብለው ተጓዙ ሰዎችም ከውስጣቸው ወጥተው ወደእኔ መጥተው ሰገዱ። ከእነሱም የቀደሙ ሰዎች ሰላምታ እንዳቀረቡልኝ ንጉሡም ከሀገር ሰዎች ሁሉ ጋር በፊቴ ሰገደ። ከዚያም በኋላ ከእርሳቸው ጋር ወሰዱኝ ወደ ከተማውም በደረቅ ያለ መርከብ ገባን በምኵራባቸውም ውስጥ በጽጌ ረዳ አክሊል ጣዖቶቻቸው ተከልለው የሥንዴ እሸትም እንደ መስዋዕት ሆኖ ተጥሎ አየሁ ይህንንም አይቼ እጅግ አዘንኩ። የአገር ሰዎችም ክብር መምህር ሆይ በዚች ዕለት ለአማልክት በዓል የምናደርግበት እንደ ነበረ ዕወቅ አሁን አንተ ለማን ታዝናለህ ለአብ እንድርገውን ወይም በወልድ ስም ወይም በመንፈስ ቅዱስ ስም በስማቸው ያጠመቅከን ስለሆነ አሉኝ። እኔም እግዚአብሔርን ያመልኩት ዘንድ የሚገባቸውን ሃይማኖትን አስተማርኳቸው መጻሕፍትንም በእጄ ጻፍኩላቸው። በአማላጅነቷ ከርኵስ ሰይጣን ተገዥነት ስለዳኑ ያንን በዓል የብርሃን እናት በሆነች በእመቤታችን በድንግል ማርያም ስም እንዲያደርጉት አዘዝኋቸው ዕለቱም የእግዚአብሔርን ልጅ እንደምትፀንሰውና በሥጋ እንደመትወልደው የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ያበሠረበት ስለሆነ። እኔም አምላካዊ ትምርትን አስተማርኳቸው በቀናች ሃይማኖትም እንዲጸኑ አደረግኋቸው ውኃው በተከፈለበትም ላይ በእመቤታችን በድንግል ማርያም ስም ታላቅ ቤተ ክርስቲያን እንዲሰሩ አዘዝኳቸው። በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድንቆች የሆኑ ብዙ ተአምራቶችንም አደረኩላቸው ከዚያ በኋላ ከእነርሱ ዘንድ ወጥቼ መጣሁ። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መጋቢት_29 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ ዘጠኝ በዚህች ቀን #ለእመቤታችን_ለቅድስት_ድንግል_ማርያም #የከበረ_መልአክ_ገብርኤል የምሥራች የነገረበት ነው፣ ደግሞ #በመድኃኒታችን በከበረችና ልዩ በሆነች #ትንሣኤው የዓለም ድኅነት ሆነ፣ የከበረ #ሐዋርያ_ቅዱስ_ጳውሎስ የምድር ዳርቻ በሆነች አልዋሪቆን በምትባል አገር ደርሶ አስተማረ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #በዓለ_ወልድ (#የጌታችን_ጽንሰት) መጋቢት ሃያ ዘጠኝ በዚህች ቀን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የከበረ መልአክ ገብርኤል የምሥራች የነገረበት ድኅነትን የተመላች ታላቅ በዓል ናት በዚህም የከበረ ወንጌል ምስክር ሁኗል እንዲህ ሲል፦ ኤልሳቤጥ ከፀነሰች በኋላ በስድተኛው ወር መልአኩ ገብርኤል የገሊላ ክፍል የሆነች ናዝሬት ወደምትባል አገር ከዳዊት ወገን ለሆነ ዮሴፍ ለሚባል ሰው ወደታጨች ወደ አንዲት ድንግል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተላከ። የድንግሊቱም ስም ማርያም ነው። መልአኩም ወደርሷ ገብቶ ደስተኛ የሆንሽ ደስ ይበልሽ ጸጋን የተመላሽ ሆይ እግዚአብሔር ከአንቺ ጋራ ነው አንቺ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ አላት። እርስዋም አይታ ከንግግሩ የተነሣ ደንግጣ እንዴት እንዲህ ያለ ሰላምታ ይቀበሏል ብላ አሰበች። መልአኩም እንዲህ አላት ማርያም ሆይ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሻልና አትፍሪ። እነሆ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ እርሱ ታላቅ ነው የልዑል እግዚአብሔር ልጅም ይባላል። እግዚአብሔር አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል ለያዕቆብ ወገንም ለዘላለም ነግሦ ይኖራል ለመንግስቱም ፍጻሜ የለውም። ማርያምም መልአኩን ወንድ ሳላውቅ ይህ እንደምን ይሆናል አለችው።መልአኩም መልሶ እንዲህ አላት መንፈስ ቅዱስ መጥቶ ያድርብሻል የልዑል ኃይልም ያጸናሻል ከአንቺ የሚወለደው ከሶስቱ አካል አንዱ የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ይባላል። እነሆ ዘመድሽ ኤልሳቤጥም እርስዋ ደግሞ በእርጅናዋ ፀንሳለች ወንድልጅም አገኘች ለእርስዋም መካን ትባል ለነበረችው ይህ ስድስተኛ ወር ነው ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና። ማርያምም እነሆኝ የእግዚአብሔር አገልጋይ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ አለችው። ያን ጊዜም ድንግል ስትሆን ረቂቅ ፅንስን ተቀበለች የእግዚአብሔር አካላዊ ቃል ወልድ ዋህድ ለኩነተ ሥጋ ወርዶአልና ይህም አንድ ባሕርይ አንድ ህልውና ሲሆን ከሦስቱ አካላት አንዱ ነው ከዓለም መፈጠር አስቀድሞ የነበረ በማይመረመር ድንቅ በሆነ ተዋሕዶ እንዴትም እንደሆነ በማይታወቅ በቅድስት ድንግል ማርያም ማሕፀን አደረ ፅንስ ሆኖ ኖረ። በዚያን ጊዜም የኋላ ኋላ መለየት ከቶ የሌለውን ፍጹም ሰውነት ነሥቶ ተዋሐደ መለኮቱ ከትስብእቱ ጋራ ያለ መለያየት አንድ ሆኖአልና። ይቺም ዕለት የበዓላት ሁሉ በኵር ናት በእርሷም የዓለም ድኅነት ተጀምሮዋልና። ዳመኛም በዚህች እለት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጽንሰት በተጨማሪ የቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ፣የቅዱሳን አብርሃ ወአጽብሐ፣ የቅዱስ ኢያሱ ነቢይ፣ የቅዱስ ላሊበላ፣ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጽንሰታቸው ታስቦ ይውላል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #በዓለ_ትንሳኤ በዚህችም ዕለት ደግሞ በመድኃኒታችን በከበረችና ልዩ በሆነች ትንሣኤው የዓለም ድኅነት ሆነ፡፡ በረቀቀ ጥበቡ ሠላሳ ሦስት ዓመት ያህል በምድር ላይ ሥራውን ሠርቶ በፈጸመ ጊዜ በፈቃዱ ሕማማተ መስቀልን ተቀብሎ ሙቶ ከተቀበረ በኋላ በሦስተኛው በዚች ቀን በሃያ ዘጠኝ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷልና። በዚች ቀን አስቀድሞ ደጅ ለሚጠኑት በዓለም ላሉ ሰዎች ሰው በመሆኑ ድኅነታቸውን አበሠራቸው እንዲሁም ደግሞ በዚች ዕለት ከሲኦል በመዳን ሙታንና ሕያዋን ደስ አላቸው። በዚህም በጌታችንና በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ መነሣት መነሣታቸውን አረጋገጡ። የከበረ ጳውሎስ በመነሣቱ ክርስቶስ የሙታን በኵር ሆነ እንዳለ እርሱ ለሙታን በኵራቸው ነውና። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሐዋርያ_ቅዱስ_ጳውሎስ በዚህችም ቀን የከበረ ሐዋርያ ጳውሎስ አልዋሪቆን ከምትባል አገር ደርሶ አስተማረ ይቺም የምድር ዳርቻ ናት። ራሱ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ አለ ከዚያም በእግዚአብሔር መልአክ ትእዛዝ ወደ ዚያች አገር ሔድኩ ሀገሪቱም እንደ ሮሜ አማሳል ታላቅ የሆነች እጅግ ውብ ናት ፍሬዋም የበዛ ነው። በውስጡ የሚታለፍበት ስሙ ገርጋ የሚባል ባሕር ግን አግድመቱ ሦስት መቶ ምዕራፍ ነው። መጋቢት ሃያ ሰባት ቀንም መጀመሪያ ከዚያ ከባሕሩ ዳርቻ ደረስኩ ለሀገሩም ሰዎች በዓላቸው ነበር የጽጌ ረዳ አክሊልም እየታቱ በጣዖቶቻቸው ራስ ላይ ያኖራሉ ከስንዴአቸውም አዲስ እሸትን ለጣዖቶቻቸው ያቀርባሉ። የአገር ጠባቂ የሚሉትም በጠልሰም የተቀረጸ ሥዕል በአገሩ ቅጽር ላይ ተደርጓል ወደዚያች አገር የሚመጣ እንግዳ ሰው ሲያይ በላዩ ያደረ ርኵስ መንፈስ በታላቅ ድምፅ ይጮኻል። የአገር ሰዎችም የዚያን ጠልሰም ጩኸቱን በሚሰሙ ጊዜ ወደ አገራቸው የመጣውን እንግዳ ወጥተው ይገድሉታል ሕጋቸው እንዲህ ነውና ወደ አገራቸው ይገባ ዘንድ ማንንም አይተዉም አያሰናብቱም። እኔም ወደዚያች አገር ደርሼ ወደ ባሕሩ በቀረብኩ ጊዜ ያ ጠልሰም እነሆ እንግዳ ወደ እናንተ ደረሰ ብሎ በአገራቸው ቋንቋ ጮኸ። የአገር ሰዎችም ድምፁን ሰምተው ከንጉሣቸው ጋራ ብዙ ሰራዊት መጡ በዚያን ጊዜ ስለ በዓላቸው ተሰበስበው ነበርና ፈለገኝ እኔ ግን በአየኋቸው ጊዜ ሸሽቼ የቀበሮዎችና የእሽኮኮዎች መሸሻ ወደ ሆነ ዋሻ ገባሁ። ከዚያም ገብቼ በረሀብና በጥም ስለተሠቃየሁ አለቀስኩ። በዚያን ቀን የፀሐይ ትኩሳት ከመጽናቱ የተነሣ ሐሩር ሆኖ ነበርና በዚያም እስከ ሌሊት ቆይቼ ከዚያ ወጥቼ ከባሕሩ ውኃ ጠጣሁ ቁሜም ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስም ጸለይኩ። ንጋትም በሆነ ጊዜ ከዚያ ዋሻ ወጥቼ ወደ አገር ለመግባት ፈለግሁ። ያ ጠልሰም አሁንም መምጣቴን እየገለጠ ሁለተኛ እንደታላቅ ነጐድጓድ ጮኸ ለባሕሩም ልማድ አለው ጠልሰሙ በሚጮኸ ጊዜ ይታወካል ማዕበሉም ይነሣል ያን ጊዜም ያገር ሰዎች ሊገድሉኝ መጡ። ከሩቅ በአየኋቸውም ጊዜ ፈራሁ እንደቀድሞውም በዚያ ዋሻ ደግሜ ተሸሸግሁ ጌታ ክርስቶስንም እለምነው ዘንድ ጀመርኩ በአባት ጴጥሮስም ጸሎት የማፀንኩ በወንድሞቼ በሐዋርያትም ጸሎት። ይልቁንም ንጽሕት ድንግል በሆነች በብርሃን እናት በእመቤታችን ማርያም በአማላጅነቷ ተማፀንኩ በሌሊቱ ርዝመት ሁሉ ስጸልይ አደርኩ። በነጋም ጊዜ ወደ ባሕሩ ዳር ወጣሁ ያም ጠልሰም እንደ ልማዱ ጮኸ ተራራዎችም እስቲናወጹ ጩኸቱን አበዛ የባሕሩም ማእበል ታወከ። ውኃውም እንደ ደም ሆነ የአገሩም ሰዎች ከሠራዊቶቻቸው ጋራ እንደ ቀድሞው ወጡ ባሕሩም መርከቦችን ተመላ እኔም ልሠወር ሮጥኩ። በዚያን ጊዜም የብርሃን እናት እመቤታችን ድንግል ማርያምን በባሕሩ ላይ ቁማ አየኃት። ጳውሎስ ሆይ ወዴት ትሸሻለህ አምላክህ ክርስቶስ እንዲህ እንድትሸሽ አዘዘህን እርሱ ራሱ ሥጋችሁን የሚገድሉትን አትፍሩአቸው ነፍሳችሁን ግን መግደል አይችሉምና ያለ አይደለምን። አንተም በቦታህ ጸንተህ ቁም እኔም ከአንተ ጋራ አለሁ እጄንም ከአንተ አላርቅም በርታ ጠንክርም የዚችን አገር ሰዎች ሁሉንም በዚህ የባህር ውኃ እንደምታጠምቃቸው ዕወቅ በእጅህም አምነው ሙታን በሚነሡባት ዕለት ዕድላቸው ከአንተ ጋር ይሆናል ባሕሩም ቃልህን ሰምቶ ይታዘዝልሃል አለችኝ።

🔴#ስንክሳር መጋቢት_28 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #ጻድቅ_ንጉስ_ቈስጠንጢኖስ መጋቢት ሃያ ስምንት በዚች ቀን ጻድቅ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ አረፈ። የዚህ ቅዱስ የአባቱ ስም ቍንስጣ የእናቱ ስም ዕሌኒ ነው ቊንስጣም በራንጥያ ለሚባል አገር ንጉሥ ነው መክስምያኖስም በሮሜ በአንጾኪያና በግብጽ ላይ ነግሦ ነበር። ይህም ቍስጣ አረማዊ ነበር ግን በጎ ሥራ ያለው እውነትን የሚወድ በልቡናውም ይቅርታና ርኃራኄን የተመላ ክፋት የሌለበት ነው። ወደ ሮሐ ከተማ በሔደ ጊዜ ዕሌኒን አይቶ ሚስት ልትሆነው አገባት እርሷም ክርስቲያናዊት ናት። ንጉሥ ቈስጠንጢኖስንም ፀንሳ ወለደችው ስሙንም ቈስጠንጢኖስ ብላ ጠራቸው ይህም ዝንጉርጒር ማለት ነው። ከዚህም በኋላ ንጉሥ ቊንስጣ ዕሌኒን በዚያው ትቷት ወደ በራንጥያ ከተማ ተመለሰ። እርሷም ልጇን እያሳደገች በዚያው ኖረች የክርስትናን ትምህርት አስተማረችው ይቅርታንና ርኅራኄን በክርስቲያን ወገኖች ላይ እንዲያደርግ በልቡናው ትዘራበት ነበር። እርሷ ክርስቲያን ስትሆን የክርስትና ጥምቀትን ታጠምቀው ዘንድ አልደፈረችም መንፈሳዊ ዕውቀትን ሁሉ በማስተማር አሳደገችው ዳግመኛም ለመንግሥት ልጆች የሚገባውንም ሁሉ። ከዚያም በኋላ ወደ አባቱ ሰደደችው አባቱም በአየው ጊዜ ደስ ተሰኘበት ዕውቀትን የተመላ ሁኖ ፈረስ በመጋለብም ብርቱና የጸና ሆኖ አግኝቶታልና በበታቹም መስፍን አድርጎ ሹሞ በመንግሥቱ ሥራ ላይ ሁሉ ሥልጣን ሰጠው። ከሁለት ዓመትም በኋላ አባቱ አረፈ ቈስጠንጢኖስም መንግሥቱን ሁሉ ተረከበ የቀና ፍርድንም የሚፈርድ ሆነ ከእርሱ በፊት የነበሩ ነገሥታት የጫኑባቸውን ጽኑ አገዛዝ ከሰዎች ላይ አስወገደ። አሕዛብም ሁሉ ታዘዙለት ወደዱትም የአገዛዙ ቅንነትና የፍርዱ ትክክለኛነት በአገሮች ሁሉ እስቲሰማ ተገዙለት። የሮሜ ሰዎች ታላላቆች መልእክትን ወደርሱ ላኩ ከከሀዲ መክስምያኖስ ጽኑ አገዛዝ እንዲያድናቸው እየለመኑ እርሱ አሠቃይቷቸው ነበርና። ነመልእክታቸውንም በአነበቡ ጊዜ ስለ ደረሰባቸው መከራ እጅግ አዘነ ያድናቸውም ዘንድ ምን እደሚያደርግ በዐደባባይ ተቀምጦ እያሰበ ሲያዝን እነሆ ከቀኑ በስድስት ሰዓት በቀትር ጊዜ ኅብሩ እንደ ከዋክብት የሆነ መስቀል ታየው በላዩም በዮናኒ ቋንቋ ኒኮስጣጣን የሚል ጹሑፍ አለ ትርጓሜውም በዚህ ጠላትህን ድል ታደርጋለህ ማለት ነው። የመስቀሉም ብርሃን የፀሐይን ብርሃን ሲሸፍነው በአየ ጊዜ አደነቀ። በላዩ ስለተጻፈውም አስቦ ለጭፍሮቹ አለቆችና ለመንግሥቱ ታላላቅ ባለሥልጣኖች አሳያቸው። እነርሱም ቢሆኑ ይህ መስቀል ስለምን እንደተገለጠ አላወቁም። በዚያችም ሌሊት የእግዚአብሔር መልአክ ለቈስጠንጢኖስ በራእይ ተገልጦ እንዲህ አለው በቀኑ እኩሌታ በቀትር በአየኸው በዚያ መስቀል አምሳል ላንተ ምልክት አድርግ በርሱም ጠላትህን ድል ታደርጋለህ አለው። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ልቡ ጸና የወርቅ መስቀልም አሠርቶ በነገሠበት ዘውድ ላይ አደረገው መኳንንቱንና ወታደሮቹን ጭፍሮቹን ሁሉ መስቀል ሠርተው በጦር መሣሪያቸው ላይ ያደርጉ ዘንድ አዘዛቸው እነርሱም እንዳዘዛቸው አደረጉ። ይህም የሆነው በበራንጥያ በነገሠ በሰባተኛ ዓመቱ ነው። የሮሜን ሰዎች ከሥቃያቸው ሊያድናቸው ሠራዊቱን ሰብስቦ ተነሥቶ ወጣ። መክስምያኖስም ሰምቶ በታላቅ ወንዝ ላይም ታላቅ ድልድይ ሠርቶ ወደ ቈስጠንጢኖስም ተሻግሮ ከእርሱ ጋራ ተዋጋ። የመስቀሉም ምልክት ቀድሞ በታየ ጊዜ የመክስምያኖስ ሠራዊት ድል ይሆኑ ነበር የቈስጠንጢኖስም ሠራዊት ከመክስምያኖስ ሰራዊት ብዙ ሰው ገደሉ። የቀሩትም ሸሽተው ሲሔዱ ከመክስምያኖስ ጋር ሊሻገሩና ወደ ሮሜ ሊገቡ ድልድይ ላይ ወጡ ድልድዩም ፈርሶ ፈርዖን ከሠራዊቱ ጋራ እንደ ሠጠመ እንዲሁ መክስምያኖስ ከሠራዊቱ ጋራ ሠጠመ። ቈስጠንጢኖስም ወደ ሮሜ ከተማ ሲገባ የሮሜ ሰዎች ከካህናት ጋራ መብራቶች ይዘው በእንቍ የተሸለሙ አክሊሎችን ደፍተው እምቢልታ እየነፉ ተቀበሉት የተማሩ ሊቃውንትም የከበረ መስቀልን ሲያመሰግኑት የሀገራችን መዳኛ ይሉት ነበር ለከበረ መስቀልም ሰባት ቀን በዓል አደረጉ። ቈስጠንጢኖስም ዳግመኛ በሮሜ ነገሠ ከሀዲዎች የሆኑ መክስምያኖስና ዲዮቅልጥያኖስ ስለ ክብር ባለቤት ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ያሠሩአቸውን እሥረኞች ሁሉንም ፈታቸው ደግሞ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ ብሎ ዓዋጅ አስነገረ። ዳግመኛም ክርስቲያኖችን እንዲአከብሩአቸው እንጂ እንዳያዋርዱአቸው የጣዖታቱንም ገንዘብና ምድራቸውን ለካህናት እንዲሰጧቸው አዘዘ ክርስቲያኖች በአረማውያን ላይ እንዲሾሙ አደረገ። ዳግመኛም አባቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙ ማንም ሰው በሰሙነ ሕማማት ሥራ እንዳይሠራ አዘዘ። በነገሠ በሥስራ አንድ ዓመት በሮሜ ሊቀ ጳጳሳት በሶል ጴጥሮስ እጅ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ። ሠራዊቱም ሁሉ። ይህም የከበረ መስቀል ከተገለጠለት በኋላ በአራት ዓመት ነው። ከዚህ በኋላም በእርሱ ርዳታና ድል ያገኘበትን የሚያድን ስለ ሆነ ስለ ጌታችን መስቀል ትመረምር ዘንድ እናቱ ዕሌኒን ወደ ኢየሩሳሌም ላካት። እርሷም ዐመፀኞች አይሁድ ቀብረው ከደፈኑት ቦታ አወጣችው። በዘመኑ ሃይማኖታቸው የቀና የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ጳጳሳት የአንድነት ስብሰባ በኒቅያ ስለ አርዮስ ተደረገ። ለክርስቲያኖች መመሪያ በበጎ አሠራር ክርስቲያናዊት ሥርዓት ተሰራች። ከዚህም በኋላ በበራንጥያ ታላቅ ከተማ ሊሠራ አሰበ እንደ አሰበውም ታላቅ ከተማ ሠርቶ በስሙ ቍስጥንጥንያ ብሎ ጠራት። በውስጧም አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በአግያና በሶፍያም ታላቅ ቤተ ክርስቲያን ሠራ መንፈሳዊ በሆነ በመልካም ጌጥ ሁሉ አስጌጣት። በውስጥዋ ከሐዋርያት የብዙዎቹን ዓፅም ከሰማዕታትና ከቅዱሳን ጻድቃን ሥጋቸውን ስለሚሰበስብ። የክብር ባለቤት ጌታችንን ደስ አሰኝቶ መልካም ተጋድሎውን ከፈጸመ በኋላ በኒቆምድያ ከተማ ጥቂት ታሞ አረፈ። ገንዘውም በወርቅ ሣጥን አድርገው ተሸክመው ወደ ቊስጥንጥንያ አደረሱት የጳጳሳት አለቆችና ካህናቱ ከሁሉ ሕዝብ ጋር ወጥተው ተቀበሉት በብዙ ጸሎት በመዘመርና በማኅሌት በምስጋና ወደ ከበሩ ሐዋርያት ቤተ መቅደስ አስገብተው በክብር አኖሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

ዳግመኛም መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከዕርገቱ በኋላ ለቅዱሳን ሐዋርያት የሞቱን መታሰቢያ እንዲያደርጉ ነግሯቸዋልና፡፡ ሕማሙንና ሞቱንም እንዲዘክሩ አዟቸዋልና አሁንም ያንን ሁሉ የመድኃኔዓለምን ሞቱን ያላሰበና የሞቱን መታሰቢያ በዓል ያላከበረና እርሱንም የማይወደው ቢኖር ዕድል ፈንታው ጽዋ ተርታው ከአይሁድ ጋር ነው፡፡ የአምላካችንን የመድኃኔዓለምን ሞቱን በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ተባብረን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ከእርሱ ለመተባበር ያብቃን!https://t.me/finotebirhan12 ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

በመድኃኔዓለም ክርስቶስ ሞት በአንድነት እናለቅስ ዘንድ ቅዱሳን ሁላችሁ ኑ! መድኃኒታችን ሙቷልና ፍጥረታት ሁሉ ያለቅሳሉ፤ መያዝንና መታሠርን የተቀበለ መድኃኒታችን ሙቷልና፡፡ ጥፊንና ግርፋትን የተቀበለ መድኃኒታችን ሞተ፡፡ መደብደብንና መመታትን የታገሰ መድኃኒታችን ሞተ፡፡ ሄኖክ እግዚአብሔር ‹‹በሴም ቤት ይደር›› ብሎ አብ ስለራሱ የተናገረለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ አብርሃም ቃልኪዳን የገባልህን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ይስሐቅ ከሰይፍ ቤዛ የሆነህን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ያዕቆብ በበረሃ የታገለህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኢዮብ በደመና የታየህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ሙሴ ስለ እርሱ ‹እንደእኔ ያለ ነቢይ ይነሣል› ብለህ የተናገርኽለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዳዊት ‹‹እነሆ በኤፍራታ ሰማነው፣ በበረሃ ዛፍም አገኘነው›› ብለህ የተናገርኽለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኤርሚያስ ‹‹የክቡሩን ዋጋ ሠላሳ ብር ተቀበሉ›› ብለህ የተናገርኽለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኢሳይያስ ‹‹ወልድ ሰው ለመሆን ተገለጠልን፣ ሕፃን ተወለደልን፣ ድንቅ መካር ኃያል አምላክ›› ብለህ የተናገርኽለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ሕዝቅኤል ‹‹አምላክ ወደ ተዘጋች ደጃፍ ገባ፣ ከተዘጋች በርም ወጣ›› ብለህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዳንኤል ነጭ ሐር ለብሶ ያየኸውን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኤልያስ ከሞት በፊት የሰወረህ በእሳት ፈረሶች ያሳረገህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ሕዝቅያስ የፀሐይ መግባቱን ያሳየህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ምናሴ ችንካሮችህን ከእግር ብረት የፈታ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኢዮስያስ ፋሲካውን ያደረግህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ አናንያ፣ አዛርያና ሚሳኤል ከእሳት ምድጃ ያዳናች የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ኑ፡፡ አብያና ሲላ ፌንቶስ ከመወለዱ አስቀድሞ ያመናችሁበት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ኑ፡፡ የቀድሞ አባቶች ነቢያት ሁላችሁ ከፋራን ተራራና ከቴማን ይመጣል ያላችሁት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ኑ፡፡ አሞፅ በአድማስ ቅጥር ያየኸው የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዘካርያስ በተራራዎች መካከል ያየኸው የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዕዝራ በአርፋድ በረሃ ያየኸው የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ስምዖን በክንድህ የታቀፍከውን ሕፃን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዮሴፍ እንደ አንተ የተሸጠ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ጠራቢ ዮሴፍ በትከሻህ ያዘልከው በክንድህ የተሸከምከው ሕፃን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ ከሕፃንነትህ ጀምሮ በበረሃ ያለ እናት ያለ አባት ያሳደገህ መንገዱንም እንድትጠርግለት ያዘጋጀህና መለኮትን እንድታጠምቅ የመረጠህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኢያቄምና ሐና ሆይ የልጃችሁን ልቅሶዋን የልቧንም መዘንጋት ታዩ ዘንድ ኑ፡፡ ከሔዋን እስከ ፋኑኤል ልጅ እስከ ሐና ያላችሁ ሁላችሁ ቅዱሳት ሴቶች የድንግልን ልቅሶዋን ታዩ ዘንድ ኑ፣ አንድ ልጇ ሙቷልና፡፡ የለመለመ የሥጋ ሞት ሕንፃ የተጀመረበት የአቤል ተከታዩ፣ ከጎኑ የፈሰሰው ደም ሔዋንን ከጥፋት ያዳናት የተገደለ መድኃኒታችን ነው፡፡ የናቡቴ ጓደኛው የተገፋው መድኃኒታችን ነው፡፡ አቤል ስለሚስቱ ሞተ፡፡ ናቡቴም ስለ ወይኑ ቦታ ሞተ፡፡ መድኃኒታችን ግን በቀኙ ያነጻት ዘንድ ስለቤተክርስቲያን ሞተ፡፡ ነፍሳችሁን ይወስዷታልና መውረዱንም አላወቁምና ስለ ወገኖቹ ኃጢአት እስከ ሞት ደረሰ ብሎ ስለ እርሱ የተናገረ አባቱን እንስማው፡፡ ሙሴም እርሱን ያውቁት ዘንድ አላሰቡትም፣ በሚመጣበት ቀንም አላወቁትም አለ፡፡ ዕዝራ በባሕር ጥልቅ ያለውን ማወቅ እንዳይችሉ ወልድንም ማወቅ እንዲሁ ሆነባቸው አለ፡፡ ጳውሎስም ብታውቁትስ ኖሮ የክብርን ጌታ እግዚአብሔርን ባልሰቀላችሁት ነበር አለ፡፡ በመሰደድ፣ ያለምንም በደልም በፍርድ አደባባይ በመቆም መከራ መስቀልን በመሸከም አብነት የሆናችሁ ሰማዕታት ሁላችሁ ኑ የመድኃኔዓለምን የሞቱን ዕለት አስባችሁ በጋራ አልቅሱለት፡፡ ሁሉ የእርሱ ከእርሱ ለእርሱ ተፈጥሮ ሳለ በምድር ላይ ምንም ሳይኖረው ራሱን እንኳን የሚያስጠጋበት ቤት ሳይኖረው አብነት የሆናችሁ ባሕታውያንና መነኮሳት ሁላችሁ ኑ በዛሬዋ ዕለት ስለሞተው አምላካችሁ መሪር ዕንባን አልቅሱለት፡፡ ሕግ ጠብቆ፣ ሥርዓት አክብሮ፣ ነዳያንን በመመገብና ያዘኑትን በማጽናናት 33 ዓመት በምድር ላይ ኖሮ አብነት የሆናችሁ እናንት በዓለም ሆናችሁ ሕግ ጠብቃችሁ፣ አሥራት በኩራቱን አውጥታችሁ፣ ድሆችን በመርዳት የምትኖሩ ክርስቲያኖች ሁላችሁ የመድኃኔዓለምን የሞቱን ዕለት ታስቡ ኑ፡፡ ‹‹የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሎአልና›› ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ እንደጻፈልን (1ኛ ጴጥ 2፡21) እርሱ ንጹሕ ባሕርይ ሲሆን ወደ መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ዘንድ ወደ ዮርዳኖስ በመሄድ ለተጠመቅን ለእኛ ለተነሣሕያን ለሁላችን አብነት የሆነን መድኃኒታችን ስለእኛ ሞቷልና ሞቱን እናስብ ዘንድ ኑ በቤቱ ተሰብስበን እናልቅስለት፡፡ መታሰያውንም እናድርግለት፡፡ ጌታችን ሞቶ ተቀብሮ ካረገ በኋላ ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለቅዱሳን አባቶቻችን ለእነ አቡነ መባዓ ጽዮን፣ ለእነ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ እንደነገራቸው የሞቱን መታሰቢያ የሚያደርግ ኃጠአተኛ እንኳ ቢሆን ሲኦልን አያያትም፡፡ የመድኃኔዓለምን የሞቱን መታሰቢያ የሚያድርግ ቢኖር ሲኦል ራሷ አፍ አውጥታ ‹‹ይህችን ነፍስ ወደኔ አታምጡብኝ›› ብላ ትጮሃለች እንጂ ችላ አትቀበለውም፡፡ የጌታችን ወዳጆቹ ዮሴፍ ኒቆዲሞስ በድርብ በፍታና በመቶ ወቄት ሽቱ ገንዘው በሐዲስ መቃብር ሊቀብሩት ቢሉ ጌታችን ያን ጊዜ ዐይኑን ክፍቶ ‹‹በሰውነቴ መዋቲ ብሆን በመለኮቴ ሕያው ነኝ እንጂ ምነው እንደ እሩቅ ብእሲ ዝም ብላችሁ ትገንዙኛላችሁን?›› አላቸው፡፡ ይህን ጊዜም ዮሴፍ ኒቆዲሞስ በታላቅ ድንዳጤ ሆነው ‹‹አቤቱ ጌታችን ሆይ! እንግዲያስ ምን እያልን እንገንዝህ?›› አሉት፡፡ መድኃኒታችንም እንዲህ እያላችሁ ገንዙኝ አላቸው፡- ‹‹ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተወልደ እማርያም እምቅድስት ድንግል ተሣሃለነ እግዚኦ፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተጠምቀ በዮርዳኖስ ወተሰቅለ ዲበ ዕፀ መስቀል ተሣሃለነ እግዚኦ፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተንሥአ እሙታን አመ ሣልስት ዕለት ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ ዳግመ ይመጽእ በስብሐት ይኰንን ሕያዋነ ወሙታነ ተሣሃለነ እግዚኦ› እያላችሁ ገንዛችሁ ቅበሩኝ አላቸው፡፡›› ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን ለወዳጆቹ ለ12ቱ ሐዋርያት፣ ለ72ቱ አርድእት፣ ለ36ቱ ቅዱሳት አንስት ‹‹እስከ ሦስት ቀን እነሣላችኋለሁ እዘኑ አልቅሱ፣ እህል ውኃ አትቅመሱ በሏቸው›› ብሎ ለዮሴፍና ለኒቆዲሞስ አክፍሎት አስተማራቸው፡፡

🔴ስንክሳር#መጋቢት_27 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት 27 በዚች ቀን #ጌታችን_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ስለ ዓለም ድኅነት በሥጋ ተሰቀለ፣ የመነኰሳት ሁሉ አባት የሆነ የከበረ አባት #ታላቁ_አባ_መቃርስ አረፈ፣ የኢትዮጵያ ንጉሥ #ሰማዕት_ገላውዲዎስ አንገቱን የተቆረጠበት ቀን ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #መድኃኔዓለም መጋቢት ሃያ ሰባት በዚችም ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዓለም ድኅነት በሥጋ ተሰቀለ። ፈጣሪዋ በዕንጨት መስቀል ላይ ተዘርግቶ ተሰቅሎ በአየችው ጊዜ ፀሐይ ጨለመች እርሱም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የነሣትን ለባዊት ነባቢት የሆነች ነፍሱን ከሥጋው ለያት ሐዋርያ ጴጥሮስ በሥጋ ምውት ሲሆን በመለኮት ሕያው ነው እንዳለ ነፍሱ ከመለኮት ሳትለይ ከሥጋ ተለየች በዚያ ጊዜ ሥጋ ከመለኮት ሳትለይ በዕንጨት መስቀል ላይ ተሰቅሎ ነበር። እንዲሁም ነፍስ ከመለኮት ጋራ አንድ ሁና እሥረኞች ነፍሳትን ትፈታቸው ዘንድ ወደሲኦል ወረደች። መድኃኔዓለም ክርስቶስ ስለ ዓለም ሁሉ ድኅነት በሥጋ ተሰቅሏልና ሞቱን በአንክሮ እናዘክር ዘንድ የልቡናችን ዐይን ወደ ቀራንዮ እናንሳ! እነሆ ክፉዎች አይሁድ ሰይጣን ልባቸውን አስቶታልና እንደ ወረንጦና እንደ ወስፌ እንደመርፌም ያለ 300 እሾህ ያለው ስረወጽ አድርገው አክሊል ሠርተው ከፍላት አግብተው በጉጠት አንስተው ‹ኢየሱስ ናዝራዊ ንጉሥ ነህ ዘውድ ይገባሃል› ብለው በራሱ ላይ ደፉበት፡፡ ለአክሊለ ሦኩም 73 ስቁረት ነበረው፡፡ እራሳቸው እንደ መሮ፣ ወርዳቸው እንደ ሞረድ 4 ማዕዘን አሠርተው ቁመታቸውን ክንድ ከስንዝር፣ ስለታቸውን እንደ ወስፌ አድርገው 73 ችንካር ሠርተው በ73ቱ ስቁረት አግብተው በጌታችን በራሱ ላይ ቢመቱበት ሥጋ ለሥጋ ገብቶ መሐል ልቡን ወጋው፡፡ አክሊለ ሦኩን በራሱ ላይ አድርገው ሲያበቁ ከቤት ወደ አደባባይ እያመላለሱ ‹‹ንጉሥ ሆይ!...›› እያሉ ምራቃቸውን እየተፉበት ተዘባበቱበት፡፡ መስቀል አሸክመው ከሊቶስጥራ እስከ ቀራኒዮ ድረስ እያዳፉ ሲወስዱት 136 ጊዜ በምድር ላይ ጣሉት፡፡ ከኋላ ያሉት ‹‹ፍጠን›› እያሉ ገፍትረው ይጥሉታል፣ ከፊት ያሉት ደግሞ ‹‹ምን ያስቸኩልሃል?›› እያሉ መልሰው ገፍትረው ይጥሉታል፡፡ ከዚህ በኋላ ክፉዎች አይሁድ ቁመታቸውን ክንድ ከስንዝር ስለታቸው ደግሞ እንደ ወስፌ የሆኑ 5 ችንካሮችን ሠርተው ሳዶር በሚባለው ችንካር ቀኝ እጁን፣ በአላዶር ግራ እጁን፣ በዳናት ሁለት እግሮቹን፣ በአዴራ መሐል ልቡንና በሮዳስ ደረቱን ቸንክረው የአዳም ራስ ቅል ባለበት ቀራኒዮ አደባባይ ላይ ሰቅለውታል፡፡ ክፉዎች አይሁድ መድኃኔዓለም ክርስቶስን እንደያዙት የኋሊት አስረው አፍንጫውን 25 ጊዜ ቢመቱት ደሙ በመሬት ላይ እንደ ውኃ ፈሰሰ፡፡ ከጌቴሴማኒ እስከ ሐና ቤት ድረስ አስረው የፊተኞቹ ሲጎትቱት የኋለኞቹ እየለቀቁት የኋለኞቹም በተራቸው ሲጎትቱት የፊተኞቹ ይለቁታል፡፤ እንዲህ እያደረጉ 65 ጊዜ ከመሬት ጋር አጋጭተውታል፡፡ ሳውል በእግሩ ሲረግጠው ጌታችን ‹‹መመለስህ ላይቀር ለምን ትረግጠኛለህ?›› ቢለው ስለዚህ ንግግርህ ብሎ ሳውል 440 ጊዜ አስገረፈው፡፡ ክፉዎች አይሁድ መድኃኒታችንን በሁለት ግንዶች መካከል አድርገው 65 ጊዜ ከግንዱ ጋር አጋጩት፡፡ ቀያፋ በሚመረምረው ጊዜ ጌታችን ‹‹አምላነቴን አንተው ራስህ ተናገርኽ›› ቢለው አይሁድ በእጃቸው ሲመቱት እጃቸውን ቢያማቸው ድንጋይ ጨብጠው 120 ጊዜ ፊቱን ጸፉት፡፡ አይሁድ ወደ ጲላጦስ ዘንድ ሲወስዱት ‹‹ምናልባት ጲላጦስ ባይፈርድበት እንኳ እንዳይቆጨን›› ብለው 305 ጊዜ በሽመል ደብድበውታል፡፡ በአምላክነቱ ቻለው እንጂ የአንዱ ምት ብቻ በገደለው ነበር፡፡ በርባን የይሁዳ የሚስቱ ወንድም (አማቹ) ስለነበር እርሱ እንደፊታለትም ከዋጋው ከ30ው ብር ጋር አብሮ ተደራድሮበት ነበር፡፡ ሰይጣን ልባቸውን ለክፋት ያስጨከናቸው ክፉዎች አይሁድ በጲላጦስ አደባባይ የጌታችንን ፂሙን 80 ጊዜ ነጭተውታል፡፡ ጲላጦስ እንደ ሕጋቸው 41 ብቻ ገርፈው እንዲለቁት ቢያዝም ክፉዎች አይሁድ ግን ጌታችንን ሲገርፉት ‹‹አሠቃቂ ግርፋቱን አይተን ልባችን እንዳይራራ›› ብለው ሰንጠረዥ ገበጣ ሰርተው ሲጫወቱ አንዱ ተነስቶ እስከ 60 እና 70 ድረስ ይገርፍና ሲደክመው ‹‹ቆጠራችሁን?›› ብሎ ይጠይቃል፡፡ ‹‹አልቆጠርንም›› ሲሉት ከድካሙ የተነሣ ‹‹እኔው ልግረፍ እንደገና እኔው ልቁጠር›› ብሎ ትቶት ሲቀመጥ ሌላኛው ይነሣና እንደዛኛው ሁሉ በተራው 60 እና 70 ይገርፈዋል፡፡ ሁሉም እንዲህ እያሳሳቱ የራሳቸውን ሕግ እየተላለፉ አይሁድ ጌታችንን ሥጋው አልቆ አጥንቱ እንደበረዶ ነጭ ሆኖ እስኪታይ ድረስ 6666 ጊዜ ጽኑ ግርፋትን ገረፉት፡፡ በእነዚህ ሁሉ ግርፋቱ ወቅት 366 ጊዜ ሥጋው ተቆርሶ መሬት ላይ ወድቋል፡፡ የመድኃኔዓለም ወገኖች ሆይ! የጌታችን ሞቱ በፈቃዱ መሆኑንና የትዕግሥቱን ብዛት አይተን እናደንቅ ዘንድ ከመጻሕፍት ጠቅሰን እንነግራችኋለን፡፡ አይሁድ ጌታችን አብርሃም ሳይወለድ በፊት እርሱ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በአንድነት በሦስትነት የሚመሰገን አምላክ መሆኑን ቢነግራቸው ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፡፡ እሱ ግን ጊዜው ገና ነበርና ተሰውሮአቸው በመካከላቸው አልፎ ሲሄድ በፍጹም አላዩትም ነበር፡፡ በቅዱስ ወንጌል ላይ እንዲህ ተብሎ እንደተጻፈ፡- ‹‹አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤት አደረገ፥ አየም ደስም አለው። አይሁድም:- ገና አምሳ ዓመት ያልሆነህ አብርሃምን አይተሃልን? አሉት። ኢየሱስም:- እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ አላቸው። ስለዚህ ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፤ ኢየሱስ ግን ተሰወራቸው ከመቅደስም ወጥቶ በመካከላቸው አልፎ ሄደ፡፡›› ዮሐ 8፡56-59፡፡ ዳግመኛም በዮሐንስ ወንጌል ላይ እንደተጻፈው አይሁድ መድኃኔዓለምን ሊይዙት የጦር መሣሪያቸውን ሰብስበው ወደ ጌቴሴማኒ በመጡ ጊዜ ‹‹ማንን ትፈለጋላችሁ?›› ቢላቸው ‹‹የናዝሬቱን ኢየሱስን እንፈልጋለን›› ሲሉት ‹‹እኔ ነኝ›› ቢላቸው ከአንደበቱ የወጣውን መለኮታዊ ቃል ብቻ መቋቋም አቅቷቸው መሬት ላይ ወድቀው ተዘርረዋል፡፡ ይህም ክስተት በተደጋጋሚ ተከስቷል፡፡ (ዮሐንስ ወንጌል ላይ ምዕራፍ 18 ከቁጥር አንድ ጀምሮ ይመለከቷል፡፡) እናም የጌታችን ሞቱ በፍጹም ፈቃዱ ባይሆን ኖሮ በጌቴሴማኒ ሊይዙት የመጡት ክፉዎች አይሁድን እንደመጀመሪያው ሁሉ በተሠወራቸው ነበር አሊያም ከአንደበቱ በሚወጣው አምላካዊ ቃሉ ብቻ ባጠፋቸው ነበር፡፡ በመጨረሻ ግን ጌታችን ወደዚህች ምድር የመጣበትን ዓላማ ይፈጽም ዘንድ እንዲገድሉት በፈቃዱ ራሱን አሳልፎ ቢሰጣቸው ያን ሁሉ እጅግ አሠቃቂ መከራ አደረሱበትና ለመስቀል ሞት አበቁት፡፡ ወዮ ለዚህ ለመድኃኒዓለም ፍጹም ትዕግስት አንክሮ ይገባል! ዓለምን በመዳፉ የያዘ አምላክ በአይሁድ እጅ እንደሌባ ተያዘ፡፡ ሠራዊተ መላእክት ለምሥጋና በፊቱ የሚቆሙለት መድኃኔዓለም እርሱ ሊፈረድበት በፍርድ አደባባይ ቆመ፡፡ በእስራት ያሉትን የሚፈታ እርሱ በብረት ችንካር ተቸነከረ፡፡ ሰማይን በከዋክብት ምድርም በአበባ ያስጌጠ እርሱ ግን የእሾህ አክሊል በራሱ ላይ ደፋ፡፡ ዓለሙን ሁሉ በቸርነቱ የሚመግብ እርሱ ተጠማሁ አለ፡፡ ወዮ የመድኃኔዓለም የማዳኑ ምሥጢር ምንኛ ድንቅ ነው!!! ለዚህ ባሕርይው አንክሮ ይገባል፡፡

🔴#ስንክሳር መጋቢት_26 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ ስድስት በዚህች ዕለት #የክብር_ባለቤት_ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ፣ የሐዲስ ኪዳንንም የቊርባን ሥርዓት አሳያቸው፣ የከበረችና የተመሰገነች #ድንግሊቱ_ኢዮጰራቅስያ አረፈች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ምሴተ_ሐሙስ መጋቢት ሃያ ስድስት በዚህች ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ እንዲህም አላቸው። እናንተም ለባልንጀሮቻችሁ እንዲሁ አድርጉ። ደግሞ የሐዲስ ኪዳንን የቊርባን ሥርዓት አሳያቸው። አሁንም በዚች ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችንን ለአይሁድ ይሁዳ አሳልፎ ሰጠው። ነቢያት ትንቢት እንደተናገሩ የሽያጩን ዋጋ ሠላሳ ብር ተቀበለ። ይቅርታው ቸርነቱ ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋር ለዘላለሙ ይኑር አሜን። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ኢዮዸራቅስያ በዚህች ቀን የከበረችና የተመሰገነች ድንግሊቱ ኢዮጰራቅስያ አረፈች። ይችም የተቀደሰች ብላቴና የንጉሥ አኖሬዎስ ዘመዱ ለሆነ በሮሜ ከተማ ከቤተ መንግሥት የአንድ ታላቅ መኰንን ልጅ ናት። የሚሞትበትም ቀን በደረሰ ጊዜ እርሷን ልጁን ለንጉሥ አኖሬዎስ ይጠብቃት ዘንድ አደራ ሰጠው። አባቷም ካረፈ በኋላ ለአንድ ታላቅ መኰንን ልጅ ንጉሥ አኖሬዎስ አጫት። በዚያም ወራት እናቷ የመሬቷን ግብር ልትቀበል በሏ የተወላትን የአትክልት ቦታዎቿም ያፈሩትን ይችንም ቅድስት ብላቴናዋን ከእርሷ ጋር ወሰደቻት። ዕድሜዋ ዘጠኝ ዓመት ሁኖ ሳለ አስከትላት ወደ ግብጽ ሔደች። ወደ ግብጽ አገርም በደረሱ ጊዜ ሥራቸውን እስከሚፈጽሙ በአንድ የደናግል ገዳም ውስጥ ኖሩ። በዚያ ገዳም ውስጥ የሚኖሩ ደናግል ለገድል የተጸመዱ ናቸው። የሥጋ መብልን ቅባትም ቢሆን ጣፋጭ ፍሬዎችንም ምንም ምን አይበሉም ወይንም ቢሆን ከቶ አይቀምሱም ያለ ምንጣፍም በምድር ላይ ይተኛሉ። ኢዮጰራቅስያም በዚያ ገዳም ውስጥ መኖርን ወደደች ገዳሙን ከምታገለግል መጋቢዋ ጋር ተፋቅራለችና። መጋቢዋም አንቺ ከዚህ ገዳም ወጥተሽ ተመልሰሽ እጮኛሽን ላትፈልጊ ቃል ግቢልኝ አለቻት ኢዮጰራቅስያም በዚህ ነገር ቃል ገባችላት። እናቷ ሥራዋን በፈጸመች ጊዜ ወደ አገርዋ ልትመለስ ወደደች ልጅዋ ግን እኔ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ሙሽርነት ስለማልሻ ራሴን ለክብር ባለቤት ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰማያዊ ሙሽራ ሰጥቻለሁ ብላ ከእርሷ ጋር መመለስን አይሆንም አለች። ብላቴናዋ ከእርሷ ጋር እንደማትመለስ በተረዳች ጊዜ ገንዘቧን ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች መጽውታ ከልጁዋ ጋር በዚያ ገዳም ብዙ ዘመን ኑራ ከዚያ በኋላ አረፈችና በዚያው ቀበርዋት። ንጉሥ አኖሬዎስም የኢዮጰራቅስያ እናቷ እንደሞተች ሰምቶ ለአጫት ያጋባት ዘንድ ኢዮጰራቅስያን እንዲአመጧት መልእክተኞችን ላከ። ቅድስቲቱም ንጉሥ ሆይ እወቅ የክብር ባለቤት ለሆነ ለሰማያዊ ሙሽራ ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እኔ ራሴን ሰጥቻከሁና ቃል ኪዳኔን መተላለፍ አይቻለኝም ብላ ወደ ንጉሡ ላከች። ንጉሥ አኖሬዎስም መልእክቷን በሰማ ጊዜ አደነቀ ስለርስዋም አለቀሰ እርስዋ በዕድሜዋ ታናሽ ብላቴና ናትና። ይህች የከበረች ኢዮጰራቅስያ ግን ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለች ለመንፈሳዊ ሥራ እጅግ የተጠመደች ሆነች በየሁለት ቀን ሁለት ሁለት ቀን እያከፈለች መጾም ከዚያም በየሦስት ቀን ሦስት ሦስት ቀን ትጾም ጀመር ከዚያም በየሰባት ቀን ሰባት ሰባት ቀን የምትጾም ሆነች። በተለየች በከበረች አርባ ጾም ምንም ምን የምትበላ አልሆነችም። ሰይጣንም በእርሷ ላይ ቀንቶ አስጨናቂ በሆነ አመታት እግርዋን መታት ብዙ ቀኖችም በሕማም ኖረች ከዚያም እግዚአብሔር ራርቶላት ከደዌዋ አዳናት በሽተኞችንም ታድናቸው ዘንድ በሽተኞችን የምትፈውስበትን ሀብት ሰጣት። ለእመ ምኔቷና ለእኀቶቿ ደናግል በመታዘዝ ታገለግላቸው ነበር በእኀቶች ደናግል ሁሉ ዘንድ የተወደደች ናት። በአንዲት ዕለትም እመ ምኔቷ አክሊላትንና አዳራሾችን እንደ አዘጋጁ ራእይን አየች እርሷም እያደነቀች ከልጆቼ ለማን ይሆን ይህ የሚገባት ስትል እሊህ አክሊላትና አዳራሾች የተዘጋጁላት ለልጅሽ ለኢዮጰራቅስያ ነው እርሷም ወዲህ ትመጣለች አሏት። ይህንንም ራእይ ለደናግሎች ነገረቻቸው እግዚአብሔርም ከዚህ ዓለም መከራ ሊያሳርፋት እስከ ወደደበት ቀን ለኢዮጰራቅስያ እንዳይነግሩዋት አዘዘቻቸው። ከዚህ በኋላ በሆድ ዝማ ሕማም ጥቂት ታመመች ሁሉም ደናግል ከእመ ምኔቷ ጋር ወደ እርሷ ተሰበሰቡ ያቺ ቃል ኪዳን ያስገባቻት የምትወዳት መጋቢዋም መጣች በእግዚአብሔርም ዘንድ እንድታስባቸው ለመንዋት እርሷም በጸሎታቸው እንዲአስቧት ለመነቻቸው ከዚያም አረፈች ። የተቀደሰችና የተከበረች እርሷን እኅታቸውን አጥተዋታልና ደናግሉ እጅግ አዝነው አለቀሱ። ከዚህም በኋላ የምትወዳት የገዳሙ መጋቢ የነበረች አረፈች ከእርስዋም በኋላ እመ ምኔቷ ጥቂት ቀን ታመመች ደናግሎችንም ሰብስባ በላያችሁ የምትሾሙትን እመ መኔት ምረጡ ስለ እኔ ኢዮጰራቅስያ ለምናለችና እኔ ወደ ጌታዬ ኢየሱስ እሔዳለሁ አሁን ግን ደጁን በላዬ ዘግታችሁ ሔዱ አለቻቸው እነርሱም እነዳዘዘቻቸው አደረጉ። በማግሥቱም ማለድ ብለው ሲደርሱ አርፋ አገኟት፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

..............ገብር ኄር.............. ስድስተኛው ሳምንት ‹ገብር ኄር› የሚል ስያሜ አለው፡፡ ‹ገብር ኄር› ማለት ‹በጎ፣ ታማኝ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ ስያሜው ከማቴዎስ ወንጌል ፳፭፥፲፬ የተወሰደ ሲኾን፣ ታሪኩም እግዚአብሔር በሰጠው ጸጋ በታማኝነት ማገልገል የሚያስገኘውን ዋጋ ያስረዳል፡፡ አንድ ሰው አገልጋዮቹን ጠርቶ ወጥተው፣ ወርደው፣ ነግደው እንዲያተርፉ ለአንዱ አምስት፤ ለአንዱ ሁለት፤ ለአንዱ ደግሞ አንድ መክሊት ሰጣቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው በተሰጠው መክሊት ነግዶ፣ ሌላ አምስት መክሊት አትርፎ፣ ዐሥር አድርጎ፣ ‹‹ጌታዬ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ ወጥቼ ወርጄ አምስት አትርፌአለሁ›› ብሎ ለጌታው አቀረበ፡፡ ጌታውም ‹‹አንተ ጎበዝ እና ታማኝ ባሪያ! በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ፣ ወርዶ፣ አትርፎ አራት አድርጎ አቀረበ፡፡ እርሱንም ጌታው ‹‹አንተ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃልና ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ አንድ የተቀበለው ሰው ግን መክሊቱን ወስዶ ቀበራት፡፡ ጌታው በተቈጣጠረው ጊዜም የቀበራትን መክሊት አምጥቶ ‹‹አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ እንደ ኾንኽ ዐውቃለሁ፡፡ ስለዚህ ፈራሁና የሰጠኸኝን መክሊት ቀበርኳት፤ እነሆ መክሊትህ!›› ብሎ ምንም ሳያተርፍ መክሊቱን ለጌታው መልሶ አስረከበ፡፡ ጌታውም ‹‹አንተ ክፉና ሐኬተኛ ባሪያ! ወርቄን በጊዜው አታስረክበኝም ነበር? ነግዶ ለሚያተርፍ እሰጠው ነበር፡፡ ይህን ክፉና ሐኬተኛ ባሪያ እጅ እግሩን አስራችሁ ጨለማና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ሥፍራ ውሰዱት! መክሊቱን ቀሙና ለባለ ዐሥሩ ጨምሩለት!›› ብሎ አዘዘ፡፡ በዚህ ታሪክ እንደምናየው በተሰጠው መክሊት ያተረፈ ሰው (ክርስቲያን) ዋጋ አለው፡፡ በፈጣሪው ዘንድ መልካም፣ በጎ፣ ታማኝ ባሪያ ተብሎ ይሸለማል፡፡ ባያተርፍ ደግሞ ሐኬተኛ ባሪያ (አገልጋይ) ይባላል፤ ቅጣቱንም ይቀበላል፡፡ እንግዲህ እኛም ታማኝ አገልጋይ መኾን ይጠበቅብናል፡፡ ሳምንቱ ይህ መልእክት የሚተላለፍበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ዘመን በመክሊታቸው የሚያተርፉ እንዳሉ ዅሉ፣ መክሊታቸውን (ጸጋቸውን) ዝገት እስከሚያጠፋው ድረስ የሚቀብሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ መክሊትን (ጸጋን) መቅበር ዋጋ የማያሰጥ መኾኑን ተገንዝበን በቻልነው መጠን ለማትረፍ መትጋት እና ታማኝ አገልጋይ መኾን እንደሚገባን ከገብር ኄር ታሪክ እንማራለን፡፡ https://t.me/finotebirhan12