uz
Feedback
የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

የጽርሐ ጽዮን ሐዋርያት ጎላ ቅዱስ ሚካኤል የፍኖተ ብርሃን ሰ/ት/ቤት (Official Channel)

Kanalga Telegram’da o‘tish

ይህ በጽ/ጽ/ሐ/ጎ/ቅ/ሚካኤል ቤ/ክ ፍ/ብ/ሰ/ት/ቤት እውቅና የተሰጠው የቴሌግራም ቻናል ነው።

Ko'proq ko'rsatish
2 639
Obunachilar
+124 soatlar
+167 kunlar
+5630 kunlar
Postlar arxiv
#ሰሙነ_ሕማማት ከሰኞ እስከ ቅዳሜ ሰሙነ ሕማማት የጾመ ሁዳዴ የመጨረሻው ሳምንት፤ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሕማም የሚታሰብበት፤ ካህናትና ምእመናን በአጸደ ቤተክርስቲያን ተሰብስበው የሕማሙን ነገር የሚያወሳውን ዜማ የሚያዜሙበት፤ ግብረ ሕማም በመባል የሚታወቀውን መጽፍ የሚያነቡበትና የሚሰሙበት፤ በነግህ፣ በሠልስት፣ በስድስት፣ በተሰዓት /ዘጠኝ /ሰዓት፣ በሰርክ /በዐስራ አንድ/ ሰዓት እየመላለሱ የሚሰግዱበትና የሚጸለዩበት ልዩ ሳምንት ነው ከሆሳዕና ማግስት እስከ ትንሳኤ። በዚህ ሳምንት በተለይ ካህናት ጥቁር ልብስ ይለብሳሉ ምክንያቱም ጌታችን የደረሰበትን መከራና ስቃይ እንዲሁም የሰው ልጅ ፭ ሺ ፭ መቶ ዘመን በጨለማ ግዞት ይኖር እንደነበር ለማዘከርም ጭምር ነው። የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራና ሕማም በጽኑ እንድናስበው ያስተማሩን ሐዋርያት ናቸው። ለእነርሱም የነገራቸው ደግሞ ራሱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። ሰሙነ ሕማማት የጌታችንን ሕማማት ከማሰብ ጋር በየዕለቱ በርካታ ድርጊቶች መፈጸማቸውን የምናስታውስበት ሳምንት ነው፦ #ሰኞ #መርገመ_በለስ_የተፈጸመበት_ሰኞ_ይባላል፦ በዚህ ዕለት ጌታችን ከቢታኒያ ሲወጣ ተራበ ቅጠል ያለባትን በለስ ተመልክቶ ወደ በለሲቱ ቢቀርብ ከቅጠል በቀር ምንም ነገር ባለማግኘቱ “ከአሁን ጀምሮ ለዘላለም ምንም ካንቺ ፍሬ አይበላ” ማር ፲፩፥፲፬ በማለት ስለረገማት መርገመ በለስ የተፈጸመበት ሰኞ ይባላል። #አንጽሖተ_ቤተ_መቅደስ_ይባላል፡- ጌታ ወደ ቤተመቅደስ ሄዶ በቤተመቅደሱ የሚሸጡትን እና የሚለውጡትን “ቤቴ የጸሎት ቤት ትባላለች” ማቴ ፳፩፥፲፫ በማለት ከቤተመቅደስ ገርፎ አስወጥቷቸዋልና። #ማክሰኞ #የጥያቄ_ቀን_ይባላል፦ ሰኞ ዕለት በቤተመቅደስ ሲሸጡ እና ሲለውጡ የነበሩትን ሁሉ እየገረፈ በማባረሩ ምክንያት ለሰው ልጅ ሹመትንና ስልጣንን የሰጠ ጌታ “በምን ስልጣን ይህንን ታደርጋለህ?” ማቴ ፳፩፥ ፳፫ ተብሎ በፈሪሳውያን ተጠይቋልና የጥያቄ ቀን ይባላል። #የትምህርት_ቀን_ይባላል፡- በዚህ ዕለት በቤተመቅደስ ረጅም ትምህርት ስላስተማረም የትምህርት ቀን ይባላል። ሉቃ ፳፩ ፥፳፰ ፣ ማር ፲፪፥፪። #ረቡዕ #ምክረ_አይሁድ_ይባላል፦ ረቡዕ እለት የአይሁድ ሊቃነ ካህናትና ጸሐፍት ጌታን እንዴት መያዝ እንዳለባቸው የመከሩበትና ውሳኔ ያሳለፉበት ቀን በመሆኑ ምክረ አይሁድ ይባላል። ወቅቱ የፋሲካን በዓል የሚያከብሩበት ቀን በመሆኑ እና ብዙ ህዝብም ጌታን ይከተለው ስለነበር ሁከት እንዳይነሳ ስጋት ነበራቸው ። ነገር ግን ከአስራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ የአስቆሮቱ ይሁዳ አሳልፎ እንደሚሰጣቸው ስለነገራቸው ሉቃ ፳፪፥፩-፮ ጭንቀታቸው ተወግዶ በጌታ መያዝ ተስማምተዋል። #የመልካም_መዓዛ_ቀንም_ይባላል፡- ጌታችን በዚህ ዕለት በለምጻሙ በሰምዖን ቤት ተቀምጦ ሳለ መላ ሕይወቷን ለዝሙት አስገዝታ ትኖር የነበረችው ማርያም እንተ እፍረት/ባለሽቶዋ ማርያም/ ዋጋው እጅግ ውድ የሆነ የአልባጥሮስ ሽቱ አምጥታ በራሱ ላይ በማርከፍከፍ ስለቀባቸው ማቴ ፳፮፥፮-፯ የመዓዛ ቀን ይባላል። #የእንባ_ቀን_ይባላል፡- ባለሽቱዋ ሴት (ማርያም እንተ እፍረት) ኃጢአቷን ይቅር እንዲላት እየለመነች በእግሩ ስር ተደፍታ በእንባዋ እግሩን አርሳለችና ማር ፲፬፥፱ የእንባ ቀን ይባላል። #ሐሙስ #ጸሎተ_ሐሙስ_ይባላል፦ ጌታችን ለአይሁድ ተላልፎ ከመሰጠቱ በፊት በጌቴሴማኒ የአትክልት ስፍራ ሲጸልይ በማደሩ ማቴ ፳፮፥፴፮ ጸሎተ ሐሙስ ይባላል።ጌታችን የደቀመዛሙርቱን እግር በፍጹም ትህትና ዝቅ ብሎ ያጠበበት ዕለት በመሆኑም ዮሐ ፲፫፥፫-፲፩ ሕጽበተ ሐሙስ ይባላል። #የምስጢር_ቀን_ይባላል፡- ከሰባቱ ምስጢራት አንዱ የቅዱስ ቁርባን ምስጢር ማቴ፳፮፥፳፮-፳፱ በዚህ ዕለት ተፈጽሟልና የምስጢር ቀን ይባላል። #የሐዲስ_ኪዳን_ሐሙስ_ይባላል፡- መሥዋዕተ ኦሪት /በእንስሳት ደም የሚቀርብ መሥዋዕት/ቀርቶ ለአለም ድኅነት ራሱን ያቀረበበት ቀን በመሆኑ ሉቃ ፳፪፥፳ የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ ይባላል። #የነጻነት_ሐሙስ_ይባላል፡- ለኃጢአትና ለዲያቢሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱን እንዲሁም የሰው ልጅ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለሆነም ዮሐ ፲፭፥ ፲፭ የነጻነት ሐሙስ ይባላል። #ዓርብ #የስቅለት_ዓርብ_ይባላል፦ ጌታችን የመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአዳምና ለልጆቹ ሁሉ ቤዛ ሆኖ በመልዕልተ መስቀል ላይ ተሰቅሎ የዋለበት ዕለት ነውና ማቴ ፳፯፥፴፭ የስቅለት ዓርብ ይባላል። #መልካሙ_ዓርብ_ይባላል፡- ከጌታ ስቅለት በፊት በተለይም በሮማውያን ህግ የወንጀለኛ መቅጫ ምልክት የነበረውን መስቀል ጌታችን በደሙ ቀድሶ የምህረት፣ የሕይወት አርማ፣ የዲያቢሎስ ድል መንሻ ስላደረገው፤ በሞቱ መልካሙን ሕይወት ስላገኘን መልካሙ ዓርብ ይባላል። #ቅዳሜ #ቀዳም_ስዑር_ትባላለች ፦ ይህች እለት ከድሮ በተለየ መልኩ የጌታችንን መከራ በማሰብ በጾም ታስባ ስለምትውል የተሻረች ቅዳሜ ይባላል። #ለምለም_ቅዳሜ_ይባላል፡- ካህናቱ ለምእመናን ለምለም ቀጤማ የሚያድሉበት ዕለት በመሆኑም ለምለም ቅዳሜ ይባላል። ምዕመናንም ይህንን ለምለም ቀጤማ እስከ ትንሣኤ ለሊት በራሳቸው ላይ ያስሩታል። #ቅዱስ_ቅዳሜ_ይባላል፡- ቅዱስ የሆነው እግዚአብሔር በጥንተ ተፈጥሮ ፍጥረታትን አከናውኖ ያረፈበት ቀን ሲሆን በዘመነ ሐዲስ ደግሞ የማዳን ስራውን ሁሉ ፈጽሞ በሥጋው በመቃብር ሲያርፍ በነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዶ ሲኦልን በርብሮ ባዶዋን ሲያስቀራት በዚያ የነበሩትን ነፍሳት የዘላለም ዕረፍትን ያወረሰበት ዕለት ስለሆነ ቅዱስ ቅዳሜ ይባላል።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_2 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሁለት በዚህችም ቀን የቃይናን ልጅ #የቅዱስ_መላልኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፣ #ቅዱስ_ክርስትፎሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_መላልኤል ሚያዝያ ሁለት በዚህችም ቀን የቃይናን ልጅ የመላልኤል የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው፡፡ መላልኤልም መቶ ስልሳ አምስት ዓመት ኖረ ያሬድንም ወለደው። መላልኤልም ያሬድን ከወለደው በኃላ ሰባት መቶ ሠላሳ ዓመት ኖረ ወንዶችና ሴቶች ልጆችን ወለደ። የመላልኤልም መላ ዘመኑ ሁሉ ስምንት መቶ ዘጠና አምስት ዓመት ነው። ቅዱስ መላልኤልም ሚያዝያ ሁለት ቀን በእሑድ ዕለት ሞተ በማከማቻም ውስጥ ቀበሩት። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ክርስቶፎሮስ (ሐዋርያና ሰማዕት) በዚችም ቀን ፊቱ እንደ ውሻ የሆነ ቅዱስ ክርስትፎሮስ በሰማዕትነት አረፈ። ይህም ቅዱስ ሰውን ይበሉ ከነበሩ ሰዎች ሀገር ነው በጦርነትም ማረኩት አባቱም በሐዋርያ ማትያስ እጅ ያመነ ነው። በማረኩትም ጊዜ ቋንቋቸውን አያውቅም ነበር የክብር ባለቤት ወደሆነ እግዚአብሔርም ማለደ ቋንቋቸውንም ገልጦለት እንደርሳቸው ተነሰገረ የክርስቲያን ወገኖችን የሚያሠቃዩአቸውንም ገሠጻቸው የጦር ሠራዊቱንም የሚመራ መኰንን ጽንዕ ግርፋትን ገረፈው። ቅዱስ ክርትፎሮስም መኰንኑን የጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ትእዛዙ ኃይሌን ባትይዘኝና ባታስታግሠኝ አንተና ሠራዊትህ ከእኔ እጅ ባልዳናችሁ ነበር አለው። መኰንኑም ስለ ርሱ ወደ ንጉሥ ላከ ከእርሱ የሆነውንም ነገረው። ንጉሡም ወደ ርሱ እንዲያመጡት ሁለት መቶ ወታደሮችን ላከለት እርሱም ያለ መፍራት ያለ ማፈግፈግ አብሮአቸው ሔደ። በእጁ በትር ነበረች በላይዋ በጸለየ ጊዜ በቀለችና አበበች። እነዚያ ወታደሮች ተርበው የሚበሉት እንጀራ በአጡ ጊዜ ቅዱስ ክርስትፎሮስ ጸለየ በእነርሱ ዘንድ እንጀራ በዝቶ ተትረፈረፈ እጅግም አድንቀው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። አባ ጳውሎስ እጅ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቁ። ወደ ንጉሡም ፊት በደረሱ ጊዜ ንጉስ ዳኬዎስ ሊያስፈራውና ሊሸነግለው ጀመረ ደግሞ እጅግ መልከ መልካም የሆኑ ሁለት አመንዝራ ሴቶችን ወደርሱ ሰደደ እነርሳቸው እንደሚያስቱትና በኀጢአት እንደሚጥሉት አስቧልና። እርሱ ግን ገሠጻቸው አስተማራቸውም በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በደማቸው ምስክር ሁኑ። እንዲሁም እነዚያ ሁለት መቶ ወታደሮች በንጉሡ ፊት በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ ራሶቻቸውንም በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የሰማዕትነትንም በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የሰማዕትነትንም አክሊል በመንግሥተ ሰማያት ተቀበሉ። ቅዱስ ክርስትፎሮስም ንጉሡን አንተ የሰይጣንን ሥራ የምትቀበል ማደሪያው የሆንክ ብሎ ዘለፈው ንጉሡም ተቆጥቶ በትልቅ ብረት ምጣድ ውስጥ እንዲጨምሩትና ከበታቹ እሳትን እንዲያነዱ አዘዘ። እንዲሁም አደረጉበት ነገር ግን ከጉዳት እንዳሰቡት ምንም የደረሰበት የለም። ጤነኛ ሆኖ ሰዎችን አስተማራቸው እንጂ። እጅግም አድንቀው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ። ቅድሱንም ከእርሷ ሊአወጡት ወደዚያች ብረት ምጣድ ቀረቡ ንጉሡም አንገቶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጧቸው አዘዘ የሕይወት አክሊልንም ተቀበሉ። ከዚያም በኃላ ታላቅ ደንጊያ በአንገቱ አንጠልጥለው ከጥልቅ ጉደረጓድ እንዲጨምሩት ንጉሡ አዘዘ በጨመሩትም ጊዜ የእግዚአብሔር መልአክ በጤንነት አወጣው። ማሠቃየቱንም በሰለቸ ጊዜ አንገቱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ ንጉሡ አዘዘ። ቅዱሱም በእግዚአብሔር መንግስት የድል አድራጊነትን አክሊል ተቀዳጀ፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

#ሆሳዕና (የዐቢይ ጾም ስምንተኛ ሳምንት) ሆሣዕና ከስምንቱ የዐቢይ ጾም እሑዶች አንዱና የመጨረሻው ሳምንት ተብሎ የሚጠራ ከትንሣኤ ቀድሞ የሚገኝ የሕማማት መገቢያ ዋዜማ ነው። ሆሣዕና አስቀድሞ ካለው ረቡዕ ጀምሮ የሚታሰብ ታላቅ የቤተክርስቲያን የበዓል ቀን እንደሆነ ይታወቃል። ይህን ስም በዚሁ ሰንበትና በዋዜማዎቹ ዕለታት የሚዘመረው ጾመ ድጓ ‘ሆሣዕና በአርያም’’ ‘ሆሣዕና ለወልደ ዳዊት’’ ‘ዕለተ ሆሣዕናሁ አርዓየ… ‘ ወዘተ. በማለት ሆሣዕና የሚለውን ቃል ቅዱስ ያሬድና ሌሎችም አባቶች በየቦታው እየጠቀሱና እየተዘመረለት በአህያ ውርንጭላ ላይ ተቀምጦ ኢየሩሳሌም የገባበትን ሁኔታ እየተረከ ስለሚዘምር ይህ ሰንበት በጌትነትና በክብር በውዳሴና ቅዳሴ ሆሣዕና በአርአያም እየተባለ በሽማግሌዎችና በሕፃናት አንደበት በድንጋዮችም ልሳን ሳይቀር እየተመሰገነ ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም በከብር ሲገባ ለሰጣቸው ለተቀደሰ ሰላሙና ፍቅሩ መታሰቢያ ሆኖ የተሰጠ ነው። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ሌላ ቀን እንደ ተራ ሰው ሆኖ ወደ ኢየሩሳሌም ይገባ ነበር፡፡ በዚህ ቀን ግን የአይሁድ ንጉሥ ሆኖ በክብር ገባ፡፡ ከቢታንያ ተነሥቶ ደብረ ዘይት ሲደርስ ከሐዋርያቱ ሁለቱን በቤተፋጌ ሰው ተቀምጦባት የማያውቅ ውርንጭላ እንዲያመጡለት ላካቸው፡፡ “በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሒዱ በዚያን ጊዜም የታሰረችን አህያ ውርንጫም ከእርሷ ጋር ታገኛላችሁ፤ ፈትታችሁም አምጡልኝ፡፡ ማንም አንዳች ቢላችሁ ለጌታ ያስፈልጉታል በሉ" አላቸው፡፡ ማቴ.21፡1-17 ወደ ቤተፋጌም ሄደው አህያዪቱን አገኙአት፡፡ ሲፈቱአትም ሳለ ባለቤቶቹ መጡባቸውና አስቆሟቸው፡፡ እነርሱም ኢየሱስ እንደፈለጋት ነገሩአቸው፡፡ ባለቤቶቹ ይህንን ሲያውቁ ተዋቸው፡፡ ሐዋርያትም የአህያዪቱን ውርንጭላ ፈትተው ወደ ኢየሱስ ወሰዱ፡፡ አጠገቡም ሲደርሱ ልብሳቸውን በአህያዪቱ ውርንጭላ ላይ አንጥፈው ኢየሱስን አስቀመጡት፡፡ #ለምን_ዘንባባ_ያዙ_ቢባል፡- ዘንባባ እሾሃም ነው ፤አንተም የኃይል የድል ምልክት አለህ ሲሉ፤በሌላም በኩል ዘንባባ እሳት ለብልቦ ይተወዋል እንጂ አይበላውም አንተም ባህርይህ አይመረመርም ሲሉ፤አንድም ዘንባባ ረጅም /ልዑል/ ነው አንተም ባሕርይህ ልዑል ነው ሲሉ ዘንባባ ይዘው ተቀብለውታል፡፡ #የተምር_ዛፍ_ዝንጣፊ_ነው_ቢሉ፡- ተምር ፍሬው አንድ ነው አንተም ባህርይህ አንድ ነው ሲሉ፡፡አንድም፤ተምር ልዑል/ረጅም/ ነው አነተም ልዑለ ባህርይ ነህ ሲሉ፡፡ አንድም፤የተምር ፍሬው በእሾህ የተከበበ ነው በቀላሉ መለቀም አይቻልም ፤ የአንተም ምስጢር አነተ ካልገለጠከው አይመረመርም ሲሉ ነው፡፡ #የወይራ_ዛፍ_ዝንጣፊ_ነው_ቢሉ፡- ወይራ ጽኑዕ/ ጠንካራ/ ነው አንተም ጽኑዓ ባህርይ ነህ ሲሉ፤አንድም ወይራ ለመስዋዕት ይሆናል፤ አንተም መስዋዕት ትሆናለህ ሲሉ፤አንድም ወይራ ዘይቱ ለመብራት ይሆናል አንተም የዓለም ብርሃን ነህ ሲሉ ይህንን ይዘው አያመሰገኑ ተቀበሉት፡፡ #ልብሳቸውንም_ማንጠፋቸው፡- እንኳን አንተ የተቀመጥክባት አህያ እንኳን መሬት መርገጥ አይገባትም ሲሉ ልብሳቸውን አነጠፉለት፡፡ እነዚያ ያላመኑ አይሁድ ለተቀመጠባት አህያ ይህንን ያህል ክብር ከሰጡ፤ በድንግልና ጸንሳ ለወለደችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ምን ያህል ክብር ልናድረግለት ይገባን ይሆን?፡፡ #የዕለተ_ሰንበት_መዝሙር (ከጾመ ድጓ) ወእንዘ ሰሙን በዓለ ፋሲካ ቀርቡ አርዳኢሁ ለአምላከ ጽድቅ ኀበ ደብረ ዘይት ሙራደ ዓቀብ ሀገረ እግዚአብሔር ወተቀበልዎ ሕዝብ ብዙኃን አዕሩግ ወሕፃናት ነሢኦሙ አዕፁቀ በቀልት እንዘ ይብሉ ሆሣዕና በአርያም ተፅዒኖ ዲበ ዕዋል ቦአ ሀገረ ኢየሩሳሌም በትፍሥሕት ወበሐሴት ይሁቦሙ ኃይለ ወሥልጣነ፡፡….. ትርጉም: “በፋሲካ በዓል ሰሞን የእውነት አምላክ ደቀ መዛሙርት ወደ ደብረ ዘይት ቀረቡ፤ በሀገረ እግዚአብሔር (ኢየሩሳሌም) አቀበቱ ላይ ብዙ አረጋውያንና ሕፃናት የዘንባባ ቅጠል ይዘው ሆሣዕና በአርያም እያሉ ተቀበሉት፣ በአህያ ውርንጫ ላይ ተጭኖ በፍጹም ደስታ ወደ ኢየሩሳሌም ገባ። ለእነዚህ ኃይልና ሥልጣንን ይሰጣቸዋል። #መልዕክታት ዕብ.8÷1-ፍጻ. ከተናገርነውም ዋናው ነገር ይህ ነው፤ በሰማያት በግርማው ዙፋን ቀኝ የተቀመጠ እንዲህ ያለ ሊቀ ካህናት አለን፡፡ እርሱም የመቅደስና የእውነተኛይቱ ድንኳን አገልጋይ ነው፤ እርስዋም በሰው ሳይሆን በእግዚአብሔር የተተከለች ናት፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ) 1ኛ ጴጥ.1÷13 ስለዚህ የልቡናችሁን ወገብ ታጥቃችሁና ነቅታችሁ ኑሩ፤ ኢየሱስ ክርስቶስም ሲገለጥ የምታገኙትን ጸጋ ፈጽማችሁ ተስፋ አድርጉ፡፡  (ተጨማሪ ያንብቡ) #ግብረ_ሐዋርያት የሐዋ.8÷26-ፍጻ. የእግዚአብሔር መልአክም ፊልጶስን ተናገረው፤ እንዲህም አለው÷ “በቀትር ጊዜ ተነሣና በደቡብ በኩል ከኢየሩሳሌም ወደ ጋዛ በሚያወርደው በምድረ በዳው መንገድ ሂድ፡፡” ተነሥቶም ሄደ፡፡” እሆም÷   (ተጨማሪ ያንብቡ) #ምስባክ "ንፍሑ ቀርነ በዕለት ሠርቅ፡፡ በእምርት ዕለት በዓልነ፡፡ እስመ ሥርዓቱ ለእስራኤል ውእቱ" መዝ.80÷3 ትርጉም፦ በመባቻ ቀን በታወቀችው በዓላችን ቀን መለከትን ንፉ፤ ለእስራኤል ሥርዐቱ ነውና÷ የያዕቆብም አምላክ ፍርድ ነውና፡፡ ወይም "እምአፈ ደቂቅ ወሕፃናት አስተዳሎከ ስብሓተ፡፡ በእንተ ጸላዒ፡፡ ከመ ትንሥቶ ለጸላዒ ወለገፋዒ፡፡" መዝ.80÷2 ትርጉም፦ ከሕፃናትና ከሚጠቡ ልጆች አፍ ምስጋናን አዘጋጀህ፡፡ ስለ ጠላት÷ ጠላትንና ግፈኛን ታጠፋው ዘንድ፡፡ #ወንጌል ዮሐ.12÷1-11 ፋሲካ ከሚውልበት ከስድስተኛው ቀን አስቀድሞ ጌታችን ኢየሱስ ከሙታን ያስነሣው አልዓዛር ወደ ነበረበት ወደ ቢታንያ መጣ፡፡ (ተጨማሪ ያንብቡ) ቅዳሴ ፡- ቅዳሴ ዘጎርጎርዮስ፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር ሚያዝያ_1 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ አንድ በዚህች ቀን ለሙሴ ወንድሙ የሆነ #የካህኑ_አሮን የእረፍቱ መታሰቢያ ሆነ፣ የከበረ አባት #አባ_ስልዋኖስ አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_አሮን_ካህን ሚያዝያ አንድ በዚህች ቀን በእስክንድርያ ከተማ በሚገኝ በግብፃውያን መፅሀፍ እንደ ተፃፈ በላዕላይ ግብፅ ያለ ግብፃዊውም እንደፃፈ ለእንበረም ልጅ ለሙሴ ወንድሙ የሆነ የካህኑ አሮን የእረፍቱ መታሰቢያ ሆነ ይላሉ። በኦሪቱ መፅሀፍ የተፃፈው ግን እስራኤል ከግብፅ ከወጡ በሁለተኛው ወር በሶስተኛው ቀን አረፈ ይላሉ። ይኸውም ግንቦት ስምንት ነበር የእስራኤል ወሮች በጨረቃ እየተቁጠሩ ዓመቱን ስለሚዞሩ በዚያች ዓመት ሚያዝያ አንድ ቀን ሆኖ ስለተገኘ። በእኛ ዘንድ ግን የኦሪት ዘኁልቁ መፅሐፍ በአምስተኛው ወር መባቻ ስለሚል መታሰቢያውን ነሐሴ አንድ ቀን እናደርጋለን። ይህም ፃድቅ ሰው የነቢያት አለቃ ለኦሪት ሕግ መምህር ለሆነ ለሙሴ ለነቢዪት ማርያምም ወንድም ነው እነርሱም ከሌዊ ነገድ ናቸው። እግዚአብሔርም በግልፅ ምድር ብዙ አስደናቂ ተአምራትን በእጆቹ አደረገ። እግዚአብሔርም እርሱንና ልጆቹን መርጦ ካህናቶቹ አድርጎ ከእስራኤል ልጆች ከገንዘባቸውና ከመሥዋዕታቸው ዐስራትን ሰጣቸው። የቆሬም ልጆች በጠላትነት በተነሱበት ጊዜ እግዚአብሄር ፈርዶ አጠፋቸው ምድርንም አዘዛት አፍዋንም ከፍታዋጠቻቸው። በበጎ ተጋድሎውና የኦሪትንም ሕግ በመጠበቅ እግዚአብሔርን ከአገለገለ በኋላ ሔደ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_ስልዋኖስ_ጻድቅ በዚህች ቀን የከበረ አባት አባ ስልዋኖስ አረፈ። ይህም አባት በአስቄጥስ ገዳም ከከበረ አባ መቃርስ ዘንድ በታናሽነቱ መነኰሰ በጠባብ መንገድ ሁሉ ተጋደለ በብዙ ፆምና ፀሎተረ በመትጋት በትሕትና በፍቅር ተወስኖ ኖረ ታላቅ አባትም ሆነ። የክብር ባለቤት ጌታችንም አምላካዊ ራእይን ይገልፅለት ነበር ድንቅ የሆኑ ነገሮችንም ይነግረዋል። ይህም እንዲህ ነው በአንዲት እለት ልቡ ተመስጦ በምድር ላይ በግምባሩ ተደፍቶ ብዙ ጊዜ ቆየ ከዚያም በኃላ ነቅቶ ራሱን ቀና አደረገ። ከእርሱ ዘንድ ያሉ ወንደረሞች መነኩሳትም በእርሱ ላይ የደረሰበትን ይነግራቸው ዘንድ ለመኑት ዝም ብሎ መሪር ልቅሶ ያለቅሳል እንጂ ሊነግራቸው አልወደደም። ከእርሱ የሆነውን ያሰረዳቸው ዘንድ ግድ ባሉት ጊዜ እንዲህ አላቸው ተድላ ወዳለበት ገነት አውጥተውኝ በዚያ የፃድቃንን መኖሪያ አየሁ ደግሞ የስቃይ ቦታዎችንም። ሁለተኛም ብዙዎች መነኮሳትን ወደ ገሀነም ብዙዎች ምእመናን ወደ መንግስተ ሰማያት ሲወስዱአቸው አየሁ እንግዲህ እኔ ለነፍሴ የማላለቅስ ለምንድነው አላቸው። ከዚያች ቀንም ጀምሮ በኃላ ወደዘላለም ጨለማ ሊወስዱኝ ዛሬ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ብርሃን ማየት አልሻም እያለ ፊቱን በቆቡ ሸፍኖ የሚያለቅስ ይህም አባት በመንፈሳዊ ስራ የተጠመደ ሆነ ደቀ መዛሙርቱንም ለምግባቸው የሚሆን ስራን ከመስራት እንዳያቋርጡ ከዕለት ምግባቸው የሚተርፈውንም እንዲመፀውቱ ያዛቸዋል። በአንዲት ቀንም አንድ ታካች የሆነ መነኮስ ወደርሱ መጣ ሽማግሌውን አባትና ደቀ መዛሙርቱን ሲሰሩ አይቶአቸው ለኃላፊ ምግብ ትሰራላችሁ ትደክማላችሁ። የዘላለም ህይወት ለሚሆን ምግብ ስሩ ድከሙ እንጂ ይህ በከበረ ወንጌል የተፃፈ አይደለምን ማርያምም የማይቀሟትን በጎ ዕድል ትምህርትን እንደመረጠች ብሎ ጠቀሰ። ሽማግሌው አባ ስልዋኖስም እንዲህ ሲናገር በሰማው ጊዜ ደቀ መዝሙሩን እንዲህ ሲል አዘዘው። ይህን መነኩስ ከእንግዳ ማሳረፊያ ቤት አስገብተህ የሚያነበው መፅሀፍ ስጠው በሩንም በላዩ ዝጋ በእርሱ ዘንድም ለመብል የሚሆን ምንም ምን አትተው። ረድኡም ሽማግሌው መምህሩ እንዳዘዘው አደረገ። ዘጠኝ ሰዓትም ሲሆን መነኰሳቱ ተሰበሰቡ ከሽማግሌው አባትም ጋር ፀሎት አድርገው ምግባቸውን ተመገቡ። ያን እንግዳ መነኰስ ግን አልጠሩትም እርሱም ቢጠሩኝ ብሎ ወደ ደጃፍ እየተመለከተ ይጠብቅ ነበር። በረኃብም በተቃጠለ ጊዜ ከበአቱ ወጥቶ ወደ አባ ስልዋኖስ ሒዶ አባቴ ሆይ መነኮሳቱ ራታቸውን በሉን አለው ሽማግሌውም አዎን በሉ ብሎ መለሰለት። ሁለተኛ ደግሞ እኔ እንግዳ ስሆን ለምን አልጠራችሁኝ አለ የከበረ አባት ስልዋኖስም አንተማ ስጋዊ መብል የማትሻ መንፈሳዊ ሰው ነህ በጎ እድልን ስለመረጥክ እኛ ግን ስጋውያን ሰዎች ለስጋዊ መብል የምንሰራ የምንደክም ነን ስለዚህም ለምግባችን የሚሆነውን በእጃችን እንሰራለን ብሎ መለሰላት። ያ መነኮስም በንግግሩ እንደበደለ አወቀ። አባ ስልዋኖስንም አባቴ ሆይ እኔ በድያለሁና ይቅር በለኝ ብሎ ሰገደለት።አባ ስልዋኖስም ማርታ በመስራት እንደ ደከመች እንድከም እንስራ ከማርያ ይልቅ ማርታ የተዘጋጀች ሁናለችና ብሎ መለሰለት። ያ ታከች የነበረ መንኰስም በዚህ አባት ትምህርት ተመክሮና ተገስፆ ሁልጊዜ የሚሰራና ከእርሱ የሚተርፈውንም ለድኆች የሚመፀውት ሆነ።ይህም አባት ስለ መንፈሳዊ ተጋድሎ ጥቅም ያላቸው ብዙ ድርሳናትንና ተግሳጳትን ደረሰ። ዕድሜውም በመልካም ሽምግልና በተፈፀመ ጊዜ የሚያርፍባትን ሰዓት እግዚአብሄር ነግሮት በእርሱ አቅራቢያ ያሉ መነኮሳትን ጠርቶ ከእርሳቸው በረከትን ተቀበለ። በፀሎታቸውም እንዲአስቡት ለመናቸው እነርሱም በእግዚአብሄር ዘንድ እንዲአስባቸው ለመኑት እርስ በርሳቸውም ተሰነባብተው በፍቅር በሰላም አረፈ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱሳን_መነኮሳት በዚችም ቀን ደግሞ በላይኛው ግብፅ ያሉ አረቦች ተሰብስበው በአስቄጥስ ያሉ አድባራትንና ገዳማትን የአባ መቃርስንም ቤተ ክርስቲያን ከበቡ በአድባራቱና በገዳማቱ ያለውንም እቃ ሁሉ ማርኩ። መነኰሳትም ተሰበሰቡ በከበሩ አባቶችም ስም ወደ እግዚአብሄር በፀሎት ማለዱ። የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም እነዚያን ዐረቦች አስደንግጦ አሳደዳቸው ያንጊዜም ማንም የተከተላቸው ሳይኖር ድል ሆነው ሸሹ። ከክብር ባለቤት ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኃይል በቀር ማንም የተከተላቸው ሳይኖር ነው።ይቅር ብሏቸዋልና ጌታችንን አመሰገኑት፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

ከዚህ በኋላም ፀንሳ ይህን ፃድቅ ሰው ወለደችው እግዚአብሔርም ባረከው የእግዚአብሔርም መንፈሰ ረድኤት አድሮበት ከኃይል ጋር ተወለደ። ሕፃኑም አድጎ ጎለመሰ በአንዲት ዕለትም አንበሳ ሊበላው በእርሱ ላይ ተነሳ የእግዚአብሔርም መንፈስ አደረበትና የፍየል ጠቦትን አንሥተው እንዲጥሉ አንሥቶ ጣለው በእጁም ውስጥ እንደ ኢምንት ሆኖ ገደለው። ሁለተኛም ስለ ሚስቱ በተቆጣ ጊዜ ሶምሶን ሂዶ በሩጫ ሦስት መቶ ቀበሮዎችን ያዘ። ችቦ አምጥቶ በጅራታቸው አሠረ በሁለቱም ጅራቶቻቸው መካከል አንድ አንድ ችቦ አደረገ። በዚያም ችቦ እሳትን አቀጣጥሎ ወደ ኢሎፍላውያን አዝመራ ሰደዳቸው። የታጨደውን ክምርና እሸቱን ነዶውንም የዘይቱንና የወይኑንም ቦታዎች አቃጠሉ። ሊጣሉትም በተነሱበት ጊዜ ጭን ጭናቸውን ሰበራቸው ብርቱ ሰልፍም ተደርጎ ብዙ ሰዎችን ገደለ ወርዶም በዋሻ ውስጥ ተቀመጠ። ስለዚህም ኢሎፍላውያን ወደ ይሁዳ ዘምተው የአህያ መንጋጋ በአለበት ሰፈሩ። የይሁዳም ሰዎች ሁሉ ወደ እኛ ለምን ዘመታችሁ አሉአቸው ኢሎፍላውያንም ሶምሶንን እናስረው ዘንድ እንዳደረገብንም እናደርግበት ዘንድ መጣን አሉ። ከይሁዳም ሦስት ሺህ ሰዎች በኤጣም ወዳለች ዋሻ ወርደው ሶምሶንን ኢሎፍላውያን እንዲገዙን አታውቅምን በእኛ ለምን እንዲህ አደረግህ አሉት። ሶምሶንም በእናንተ እንዳደረጉባችሁ እኔም በእነሳቸው እንደዚያው አደረግሁባቸው አላቸው። አሥረን ለኢሎፍላውያን ልንሰጥህ መጣን አሉት ሶምሶንም እናንተ እንዳትገድሉኝ ማሉልኝ ለእነሱ አሳልፋችሁ ስጡኝ እናንተ ግን እኔን በጠብ አትገናኙኝ አላቸው እነሱም ማሉለት። በሁለት አዲስ ገመዶች አስረው ከዚያች ዋሻ አወጡት አሳልፈውም ሰጡት ኢሎፍላውያንም ደነፉ ሊቀበሉትም ሮጡ የእግዚአብሔርም መንፈሰ ረድኤት አደረበት በክንዱ ያሉ ገመዶች ገለባ እሳት በበላው ጊዜ እንዲያር እርር ኩምትር አሉ እሥራቱም ከክንዱ ተፈታለት የአህያ መንጋጋ አጥንት በጎዳና ወድቆ አገኘ እጁን ዝቅ አድርጎ አነሣት በዚያችም ሺህ ሰዎችን ገደለባት። ከዚህም በኋላ ውኃን እጅግ ተጠማ ወደ እግዚአብሔርም ጮኸ ይህን ታላቅ ድኅነት በእኔ በባሪያህ እጅ አደረግህ አሁን ግን በውኃ ጥም እሞታለሁ በእነዚህም በቁላፋን እጅ አወድቃለሁ አለ። እግዚአብሔርም ከዚያች የአህያ መንጋጋ ውኃን አፈለቀለት ያንንም ጠጥቶ ነፍሱ ተመለሰችለት።እስራኤልንም ሃያ ዓመት አስተዳደራቸው። ከዚህም በኋላ ሶምሶን ከዚያ ተነስቶ ወደ ጋዛ ሔደ በዚያም ሚስት አግብቶ ተቀመጠ። ለጋዛም ሰዎች ሶምሶን ወደዚህ መጣ ብለው ነገሩዋቸው በከተማውም በር መላ ሌሊቱን ሁሉ ከበው ሲጠብቁት አደሩ ሌሊቱን ሁሉ ስንጠብቀው አድረን ጠዋት እንግደለው አሉ። ሶምሶንም እስከ ሌሊቱ እኩሌታ ተኛ ከዚያም በኋላ ተነስቶ በከተማው በር ያሉ የመጠበቂያውን ደጃፍ ሁለቱን የመቃን መድረኮች ያዘ ከሰዎቹ ሁሉ ጋራ በትከሻው ተሸክሞ በኬብሮን አንጻር ወዳለ ተራራ አውጥቶ በዚያ ጣላቸው። ከዚህም በኋላ በሦራህ ወንዝ አጠገብ የምትኖር ሴትን ወደደ ስምዋም ደሊላ ነው። እርሷንም አግብቶ በዚያ ተቀመጠ። የኢሎፍሊ ሹማምንትም ወደርሱዋ ወጥተው አታሊልን ኃይሉ በምን እንደሆነ በምንም እንድንችለውና እናደክመው ዘንድ በምንም እንድናሥረው ዕወቂ እኛ ሺው ሰዎች ሽህ ብር እንሰጥሻለን አሏት። ደሊላም ሶምሶንን ኃይልህ ጽኑ መሆኑ በምን እንደሆነ ንገረኝ በምንስ ቢያሥሩህ ትደክማለህ አለችው። ሶምሶንም ሦስት ጊዜ ሸነገላት ደሊላም አወድሻለሁ ልቤም ከአንቺ ጋራ ነው ለምን ትለኛለህ እነሆ ስትሸነግለኝ ይህ ሦስተኛህ ነው ኃይልህ ጽኑ መሆኑ በምን እንደሆነ አልነገርከኝም አለችው። ከዚህ በኋላ መላ ሌሊቱን በነገር ባደከመችው ጊዜ ልሙት ብሎ እስቲበሳጭ ድረስ ዘበዘበችው። በልቡ ያለውን ሁሉ ነገራት እኔ ለእግዚአብሔር የስለት ልጅ ነኝና ከእናቴ ማሕፀን ከተወለድኩ ጀምሮ ምላጭ ራሴን አልነካኝም ጠጉሬን ከተላጨሁ ኃይሌ ተለይቶኝ እደክማለሁ ከሰውም እንዳንዱ እሆናለሁ አላት። የልቡን ሁሉ እንደገለጠላት በአወቀች ጊዜ በጭኖቿ መካከል አስተኝታ ሲያንቀላፋ ጠጉር ቆራጭ ጠቀሰች ሰባቱንም የራሱን ብርጉዎች ቆርጣ ጠጉሩን ላጨች እርሱም ይደክም ጀመር ኃይልም ተነሣው። ኢሎፍላውያንም ይዘው ሁለት ዐይኖቹን አወጡአቸው ወደ ጋዛንም አውርደው በእግር ብረት አሰሩት በግዞትም ሆኖ እህልን ይፈጭ ነበር። ከዚህም በኋላ የኢሎፍሊ አለቆች ለጣዖታቸው መስዋዕት ሊሰዉ ተሰበሰቡ። ሕዝቡም በአዩት ጊዜ ጣዖታቸውን አመሰገኑት አገራችንን ያጠፋት ሬሳዎቻችንን ያበዛ ጠላታችንን በእጃችን ጣለው አሉ። ከዚህ በኋላ በልተው ጠጥተው ደስ ባላቸው ጊዜ በፊታችን ይጫወት ዘንድ ሶምሶንን ከግዞት ቤት ጥሩት አሉ ጠርተው አምጥተውም ተዘባበቱበት በሁለት ምሰሶዎች መካከልም አቆሙት። ሶምሶንም የሚመራውን ብላቴና አሳርፈኝ ይህ ቤት የቆመባቸው ምሰሶዎችንም አስጨብጠኝ ወደነሳቸውም አስጠጋኝ አለው ያም የሚመራው ብላቴና እንዳለው አደረገለት። በዚያ ቤት ወንዶችም ሴቶችም መልተው ነበር የኢሎፍሊ ሹማምንትም ሁሉ በዚያ በሰገነት ነበሩ ሶምሶን ሲጫወት ያዩት ዘንድ የተሰበሰቡ ወንዶችም ሴቶችም ሦስት ሽህ ይሆኑ ነበር። ሶምሶንም ወደ እግዚአብሔር ጮኸ አቤቱ አቤቱ አስበኝ አንዲት ነገርንም አድምጠኝ እንግዲህ ስለ ሁለቱ ዐይኖቼ ፈንታ ከኢሎፍላውያን አንዲት በቀልን ልመልስ አለ። ሶምሶንም ያ ቤት በላያቸው የተደገፈባቸው በመካከል ያሉ እነዚያን ሁለት ምሶሶዎች ያዛቸው አንዲቱን በቀኙ አንዲቱንም በግራው ይዞ ገፋቸው። ሶምሶንም ሰውነቴ ከኢሎፍሊ ሰዎች ጋራ ትሙት ብሎ በኃይሉ ነቀነቃቸው ያም ቤት በውስጡ ባሉ በሕዝቡ ላይና በኢሎፍሊ ሹማምንት ላይ ወደቀባቸው የሞቱትም እንዲህ ሆኑ ሶምሶን በሕይወቱ ሳለ ከገደላቸው ሲሞት የገደላቸው በዙ። ያባቱ ወገኖች ሁሉና ወንድሞቹ ወርደው በድኑን አነሱ ወስደውም በአባቱ በማኑሔ መቃብር ቀበሩት፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መጋቢት_30 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሠላሳ በዚህች ቀን ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለተሰጠው ስለ ክብሩ ልዕልና ለከበረ #መልአክ_ቅዱስ_ገብርኤል የወልደ እግዚአብሔርን ሰው የመሆኑን ዜና ያበሰረበት መታሰቢያ ነው፣ #የቅዱስ_ያዕቆብ_ዘግሙድ የስጋው ፍልሰት የሆነበት ነው፣ ከእስራኤል ልጆች መሳፍንት አንዱ የሆነ #የመስፍኑ_ሶምሶን መታሰቢያው ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ገብርኤል_ሊቀ_መላእክት መጋቢት ሠላሳ በዚህች ቀን ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለተሰጠው ስለ ክብሩ ልዕልና ለከበረ መልአክ ለገብርኤል የወልደ እግዚአብሔርን ሰው የመሆኑን ዜና ለምትወልደው ለድንግል ማርያም እንዲአበስራት የተገባው ስለሆነ በዓሉን ልናከብር ይገባል። ስለዚህ በዚች በከበረች ታላቅ ፀጋ በዚህ መልአክ እጅ እግዚአብሔር ይቅር ብሎናልና ፈፅሞ ልናከብረው ይገባናል። እርሱም ደግሞ ስለ ክርስቶስ መምጣትና ለዓለም ድኅነት መገደሉን ለኢየሩሳሌምም መዳኛዋ መሆኑን ስለ ወገኖቹ ከምርኮ መመለስ ሲጸልይ ለዳንኤል የነገረው ሱባዔዎችንም የወሰነለትና በሱባዔዎቹም መጨረሻ ንጹሀን የሚነጹበት የክብር ባለቤት ክርስቶስ ይመጣል ይገድሉታልም ለኢየሩሳሌምም መደኛዋ ይሆናታል ያለው ይህ መልአክ ነው። ከዚያ በኋላም ለእስራኤል ልጆች የሚደረጉ መስዋእቶችና ቁርባኖች ይሻራሉ። የክብር ባለቤት ጌታችን ስለ ዓለሙ ሁሉ ድኅነት ለእመቤታችን ማርያም ከእርስዋ መወለዱን ይነግራት ዘንድ የተገባው አድርጎታልና ስለዚህ ሁልጊዜ የበዓሉን መታሰቢያ ልናደርግ ይገባናል። ጌታ ከጠላታችን ሰይጣን እጅ ያድነን ዘንድ ስለ እኛ እንዲማልድ በበጎ ስራ ሁሉ እንዲረዳን እንለምነው ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን ለዘላለሙ አሜን። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ያዕቆብ_ዘግሙድ ዳግመኛም በዚህችም ቀን ደግሞ ለፋርስ ንጉሥ ለሳፎር ልጅ ለንጉሥ ሰክራድ ከጭፍሮቹ ውስጥ የሆነ ሕዋሳቱን የተቆራረጠ የቅዱስ ያዕቆብ ዘግሙድ የስጋው ፍልሰት የሆነበት ነው፡፡ ይህም ንጉሥ ሰክራድ እጅግ ይወደው ነበር ስለ መንግሥቱ ሥራ ሁሉ ከእርሱ ጋር ይማከር ነበርና ስለዚህም የቅዱስ ያዕቆብን ልቡና አዘንብሎ ፀሐይንና እሳትን እንዲአመልክ አደረገው፡፡ በሃይማኖቱም ከንጉሡ ጋር እንደተስማማ የተቀደሱ እናቱ ሚስቱና እኅቱ በሰሙ ጊዜ እንዲህ ብለው ጽፈው ወደርሱ ላኩ የቀናች የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ሃይማኖት ትተህ የፍጡራንን ጠባይ ለምን ተከተልክ እሊህም ፀሐይ ጨረቃ ከዋክብት እሳት ናቸው ዕወቅ ከዛሬ ጀምሮ በንጉሥ ሃይማኖት ከኖርክ እኛ ከአንተ የተለየን ነን። የመልእክታቸውንም ጽሑፍ በአነበበ ጊዜ መሪር ልቅሶን አለቀሰ በዚህም የጥፋት ምክር ጸንቼ ብኖር ከቤተ ሰቦቼና ከወገኖቼ የተለየሁ መሆኔ ነው። ደግሞስ በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ፊት እንዴት እቆማለሁ አለ ከዚህም በኋላ የቤተ ክርስቲያንን መጻሕፍቶች ማንበብ ጀመረ የንጉሡን አገልግሎትም ተወ ለንጉሡም ወዳጅህ ያዕቆብ እነሆ አገልግሎትህን አማልክቶችህንም ማምለክ ተወ ብለው ነገሩት። ንጉሡም ልኮ ወደርሱ አስቀርቦ አገልግሎትህን ለምን ተውክ አለው ቅዱስ ያዕቆብም እንዲህ አለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በከበረ ወንጌል በሰው ፊት ያመነብኝን ሁሉ እኔም በሰማያዊ አባቴ ፊት አምነዋለሁ በሰው ፊት የካደኝንም በአባቴ ፊትና በመላእክት ፊት እክደዋለሁ ብሏልና ስለዚህ አገልግሎትህን ፍቅርህን አማልክቶችህንም ማምለክ ትቼ ሰማይና ምድርን ፀሐይን ጨረቃን ከዋክብትን የሚታየውንና የማይታየውን ለፈጠረ ለሕያው እግዚአብሔር ልጅ ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ የምሰግድ ሆንኩ። ንጉሡም ይህን በሰማ ጊዜ ደሙ እንደ ውኃ በዝቶ እስቲፈስ ታላቅ ግርፋትን እንዲገርፉት አዘዘ እርሱ ግን ከበጎ ምክሩ አልተመለሰም ዳግመኛም ሕዋሳቱን በየዕለቱ እንዲቆርጡ አዘዘ የእጆቹንና የእግሮቹን ጣቶች ሃያውን ቆረጡ ክንዶቹንና እግሮቹን እስከ ጭኖቹ ድረስ ወደ አርባ ሁለት ቁራጭ በየጥቂቱ ቆረጡት። በሚቆርጡትም ጊዜ ሁሉ ጌታዬና ንጉሤ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደ ዕንጨት ቅርንጫፍ ሰውነቴን በይቅርታህ ገናናነት ተቀበል የወይን አታክልት ያለው በየሦስት ዓጽቅ ሲቆርጡለት ዓጽቆቹ በዝተው ይበቅላሉ ይሰፋሉ በሚያዝያ ወር አብቦ ያፈራልና እያለ የሚዘምርና የሚያመሰግን ሆነ። ደረቱና አካሉ እንደ ግንድ ድብልብል ሆኖ በቀረ ጊዜ ነፍሱን ለመስጠት እንደ ደረሰ አውቆ በዚያን ጊዜ በዓለም ውስጥ ያሉትን ሰዎች ሁሉንም ይምራቸው ዘንድ እግዚአብሔርን ለመነው እንዲህም አለ ለእኔ ግን ወደ አንተ የማነሣው አካል አልቀረልኝም ሕዋሳቶቼ ተቆርጠው በፊቴ የወደቁ ስለሆነ አሁንም ነፍሴን ተቀበላት አለ። በዚያንም ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጾ አረጋጋው አጸናውም ያን ጊዜ ነፍሱ ደስ አላት ነፍሱንም ከመስጠቱ በፊት ወታደሩ በፍጥነት መጥቶ የከበረች ራሱን በሰይፍ ቆረጠ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለ ሥጋውንም ምእመናን ሰዎች ወስደው በመልካም አገናነዝ ገነዙትና በንጹሕ ቦታ አኖሩት። እናቱ ሚስቱና እኅቱ በሰማዕትነት እንደሞተ በሰሙ ጊዜ እጅግ ደስ አላቸው ወደ ቅዱስ ያዕቆብም ሥጋ መጥተው ተሳለሙት አለቀሱለትም የከበሩ ልብሶችንም በላዩ አኖሩ ጣፋጮች የሆኑ ሽቱዎችንም ረጩበት። በደጋጎች ነገሥታት በአኖሬዎስና በአርቃዴዎስ በሌሎችም ዘመን አብያተ ክርስቲያን ታነፁ ገዳማትና አድባራትም ተሠሩ የሰማዕታትንም ሥጋ በውስጣቸው አኖሩ ታላላቆች ድንቆች ተአምራትም ከእሳቸው የሚታዩ ሆኑ። የፋርስ ንጉሥም ሰምቶ በቦታው ሁሉ የሰማዕታትን ሥጋ ያቃጥሉ ዘንድ አዘዘ በሚገዛውም አገር ውስጥ ምንም ምን እንዳይተው አማንያን ሰዎችም መጥተው የቅዱስ ያዕቆብን ሥጋ ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዱት ከዚያም ወደ ሀገረ ሮሀ ከሀገረ ሮሀም የከበረ ኤጲስቆጶስ ጴጥሮስ ወደ ግብጽ አገር ወደ ብሕንሳ ከተማ ወሰደው። በዚያም ጥቂት ጊዜ ኖረ ከርሱ ጋርም መነኰሳት ነበሩ ከቀኑ እኩሌታም ሲጸልዩ የቅዱስ ያዕቆብ ሥጋ ከብዙ የፋርስ ሰማዕታት ሥጋ ጋር በአለበት ሰማዕታት አብረዋቸው ዘመሩ ባረኳቸውም ቅዱስ ያዕቆብም እግዚአብሔር እንዳዘዘ ሥጋዬ በዚህ ይኑር አለ ከዚህም በኋላ ተሠወሩ። ከዚህም በኋላ የከበረ ኤጲስቆጶስ ጴጥሮስ ወደ አገሩ ሊመለስ በወደደ ጊዜ ሥጋዬ በዚህ ቦታ ይኑር ያለውን የቅዱስ ያዕቆብን ቃል ተላልፎ የቅዱስ ያዕቆብን ሥጋ ወሰደ በዚያንም ጊዜ አስቀድሞ ወደ አመለከተው ቦታ ከእጆቻቸው መካከል ተመለሰ ከሥጋውም ታላላቅ የሆኑ ተአምራት ተገለጡ ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅዱስ_ሶምሶን (መስፍነ እስራኤል) በዚህችም ዕለት ደግሞ ከእስራኤል ልጆች መሳፍንት አንዱ ሶምሶን መታሰቢያው ነው። የዚህም ፃድቅ የአባቱ ስም ማኑሄ ይባላል ከነገደ ዳን ነው እናቱም መካን ነበረች የእግዚአብሔርም መልአክ ወደርስዋ መጥቶ ከርስዋ ልጅ መወለዱን ነገራት። የወይን ጠጅ የማር ጠጅ ከመጠጣት ለመስዋዕት የማይሆን ርኲስ የሆነውን ሁሉ ከመብላት እንድትጠነቀቅ አዘዛት። ያም ሕፃን ከእናቱ ማሕፀን ከተወለደ ጀምሮ ለእግዚአብሔር የተለየ ገንዘቡ ነውና በራሱ ላይ ምላጭ አይድረስበት እርሱም እስራኤልን ከኢሎፍላውያን እጅ ሊያድናቸው ይጀምራል አላት። የእግዚአብሔር መልአክም ያላትን ለባሏ በነገረችው ጊዜ ያንን መልአክ ያሳየው ዘንድ እርሱም ወደ እግዚአብሔር ለመነ። ልመናውንም ሰማው። የእግዚአብሔርም መልአክ ተገልጦለት ለሚስትህ ያዘዝኳትን እንድትጠነቀቅ እዘዛት አለው።

ምሕረትንና ርኅራኄን የተመላች እመቤቴ የብርሃን እናት ድንግል ማርያም ይህን ስትናገረኝ እነሆ በእጃቸው የጦር መሣሪያ የያዙ ኃይለኞች ሰዎችን የተሞሉ መርከቦችን በቅርብ አየኋቸው እጅግም ፈራሁ እመቤቴ ማርያምም ተሠወረችኝ። ነገር ግን ከደመና ውስጥ ጳውሎስ ሆይ ሰዎችን አጥምቅ ማጥመቅንም አታቋርጥ የሚለኝን ቃል እሰማ ነበር። እኔም በታላቅ ቃል ፈጣሪዬ ሆይ ይህን የባሕር ውኃ ለእሊህ ለተጣሉ በጎች ሰይጣንም ለማረካቸው ጥምቀትን አድርገው ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ በዚህ ባህር ጥምቀት እሊህን ሰዎች በሦስትነትህ ስሞች የልጅነትን ክብር የሚቀበሉ አድርጋቸው በማለት አሰምቼ ተናገርኩ። እንዲህም ይህን እያልኩ ከባሕሩ ውኃ ዘግኜ ሰዎች በአሉባቸው መርከቦች በላያቸው ረጨሁት የሰዎቹም ቁጥራቸው አንድ መቶ ሃምሳ ሺህ ነው። እኔ ወደአለሁበት የባሕር ዳር በደረሱ ጊዜ ከመርከባቸው ወጥተው ፈለጉኝ እኔም እመቤቴ የብርሃን እናት እንዳዘዘችኝ በፊታቸው ቆምኩ በረድኤቷ ተማምኛለሁና አልፈራሁም። በአዩኝም ጊዜ ሁሉም በፊቴ ሰገዱ በአንድ ቃልም ቅዱስ ጳውሎስ ሆይ ፍቅር አንድነት ለአንተ ይሁን ወደአንተ ከመድረሳችን በፊት በመርከቦች ውስጥ እያለን እኛ ያየነውን አየህን አሉኝ። እኔም አዲስ የተወለዳችሁ ልጆች ሆይ ምን አያችሁ አልኋቸው የሰማይ ደጆች ተከፍተው የቀኝ እጅ እንደ እሳት ነበልባል ተዘርግታ አየን ደግሞ የፊቷ ብርሃን ከፀሐይ ሰባት እጅ የሚበራ ሴት አየን። እርሷም ከደመና በታች የምትረጨውን ውኃ ተቀብላ በላያችን ትረጨዋለች ትስመናለች ታቅፈናለችም። በራሲቻችንም ላይ የብርሃን አክሊሎችን ታደርጋለች አሉኝ። ይህንንም በሰማሁ ጊዜ ፈጽሞ ደስ አለኝ በስሙ በምንሠራው ሥራ ሁሉ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር እንዳለ ተረዳሁ። ከዚህም በኋላ ሌሎች መርከቦች መጡ ኃይለኞች ሰዎችን ከጦር መሣሪያ ጋር የተመሉ ናቸው እንዲህም እያሉ ዛቱበኝ። አንተ ሥራየኛ ጥበበኞች ሕርምስና በለንዮስ ታምራት የሚያደርጉባቸው የጠልሰም መጻሕፍቶች ከእኛ ጋራ እንዳሉ ዕወቅ በማለት እኔም ቸር ፈጣሪዬ ሆይ የቀደሙትን በጎች ይቅር እንዳልካቸውና በውስጣቸው ኃይልህን እንደገለጥክ ለእነዚህም እንዲሁ ኃይልህን ግለጥ ይቅርም በላቸው አልኩ። ከዚያም በኋላ ከባሕሩ ውኃ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ጥምቀትን ይሁናችሁ አልኩ ወዲያውኑ መርከቦች ከባሕሩ ዳር ደረሱ። ሁሉም ሰዎች ከመርከብ ወጥተው በፊቴ ሰገዱ የቸር አምላክ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ሆይ እናመሰግንሃለን አሉኝ። ይህንንም ድንቅ ተአምር ከቀደሙት ባልንጀሮቻቸው ጋራ ተነጋገሩ ዜናዬም በዚያች አገር ንጉሥ ዘንድ ተሰማ እርሱም ከሰራዊቱ ጋር ተነሳ በመርከቦችም ተጭነው ወደእኔ መጡ። እኔም ዐይኖቼን ወደ ሰማይ አቅንቼ የፈጣሪዬን ስም ጠራሁ ባሕርዋንም በመስቀል ምልክት አማተብኩባት። እንዲህም አልኳት አንቺ ባሕር በእግዚአብሔር ልጅ በጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ትከፈዪ ዘንድ አዝሻለሁ ምድሩም ይገለጥ መርከቦችም በየብስ ውስጥ ይቁሙ። ነገሬንም ሳልጨርስ ባሕርዋ ተከፈለች በውስጥዋም ዐሥራ ሦስት ጎዳናዎች ተገለጡ መርከቦቹም ውኃ በሌለው ምድር ላይ ቆሙ ይህንንም አይተው ሰይፎቻቸውን መዘዙ ዕንጨቶችም ሆነው አገኙአቸው እኔም ከሕህሩ ውኃ ዘግኜ በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ እያልኩ በላያቸው ረጨሁ። በዚያን ጊዜ እሊያ መርከቦች ነፋስ ተሸክሟቸው ያለ ውኃ ከምድር ከፍ ከፍ ብለው ተጓዙ ሰዎችም ከውስጣቸው ወጥተው ወደእኔ መጥተው ሰገዱ። ከእነሱም የቀደሙ ሰዎች ሰላምታ እንዳቀረቡልኝ ንጉሡም ከሀገር ሰዎች ሁሉ ጋር በፊቴ ሰገደ። ከዚያም በኋላ ከእርሳቸው ጋር ወሰዱኝ ወደ ከተማውም በደረቅ ያለ መርከብ ገባን በምኵራባቸውም ውስጥ በጽጌ ረዳ አክሊል ጣዖቶቻቸው ተከልለው የሥንዴ እሸትም እንደ መስዋዕት ሆኖ ተጥሎ አየሁ ይህንንም አይቼ እጅግ አዘንኩ። የአገር ሰዎችም ክብር መምህር ሆይ በዚች ዕለት ለአማልክት በዓል የምናደርግበት እንደ ነበረ ዕወቅ አሁን አንተ ለማን ታዝናለህ ለአብ እንድርገውን ወይም በወልድ ስም ወይም በመንፈስ ቅዱስ ስም በስማቸው ያጠመቅከን ስለሆነ አሉኝ። እኔም እግዚአብሔርን ያመልኩት ዘንድ የሚገባቸውን ሃይማኖትን አስተማርኳቸው መጻሕፍትንም በእጄ ጻፍኩላቸው። በአማላጅነቷ ከርኵስ ሰይጣን ተገዥነት ስለዳኑ ያንን በዓል የብርሃን እናት በሆነች በእመቤታችን በድንግል ማርያም ስም እንዲያደርጉት አዘዝኋቸው ዕለቱም የእግዚአብሔርን ልጅ እንደምትፀንሰውና በሥጋ እንደመትወልደው የመላእክት አለቃ ቅዱስ ገብርኤል ያበሠረበት ስለሆነ። እኔም አምላካዊ ትምርትን አስተማርኳቸው በቀናች ሃይማኖትም እንዲጸኑ አደረግኋቸው ውኃው በተከፈለበትም ላይ በእመቤታችን በድንግል ማርያም ስም ታላቅ ቤተ ክርስቲያን እንዲሰሩ አዘዝኳቸው። በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድንቆች የሆኑ ብዙ ተአምራቶችንም አደረኩላቸው ከዚያ በኋላ ከእነርሱ ዘንድ ወጥቼ መጣሁ። ለእግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን ።https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መጋቢት_29 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ ዘጠኝ በዚህች ቀን ለእመቤታችን #ለቅድስት_ድንግል_ማርያም #የከበረ_መልአክ_ገብርኤል የምሥራች የነገረበት ነው፣ #በመድኃኒታችን በከበረችና ልዩ በሆነች #ትንሣኤው የዓለም ድኅነት ሆነ፣ የከበረ #ሐዋርያ_ቅዱስ_ጳውሎስ የምድር ዳርቻ በሆነች አልዋሪቆን በምትባል አገር ደርሶ አስተማረ። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #በዓለ_ወልድ (#የጌታችን_ጽንሰት) መጋቢት ሃያ ዘጠኝ በዚህች ቀን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የከበረ መልአክ ገብርኤል የምሥራች የነገረበት ድኅነትን የተመላች ታላቅ በዓል ናት በዚህም የከበረ ወንጌል ምስክር ሁኗል እንዲህ ሲል፦  ኤልሳቤጥ ከፀነሰች በኋላ በስድተኛው ወር መልአኩ ገብርኤል የገሊላ ክፍል የሆነች ናዝሬት ወደምትባል አገር ከዳዊት ወገን ለሆነ ዮሴፍ ለሚባል ሰው ወደታጨች ወደ አንዲት ድንግል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተላከ። የድንግሊቱም ስም ማርያም ነው። መልአኩም ወደርሷ ገብቶ ደስተኛ የሆንሽ ደስ ይበልሽ ጸጋን የተመላሽ ሆይ እግዚአብሔር ከአንቺ ጋራ ነው አንቺ ከሴቶች ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ አላት። እርስዋም አይታ ከንግግሩ የተነሣ ደንግጣ እንዴት እንዲህ ያለ ሰላምታ ይቀበሏል ብላ አሰበች። መልአኩም እንዲህ አላት ማርያም ሆይ በእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሻልና አትፍሪ። እነሆ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ እርሱ ታላቅ ነው የልዑል እግዚአብሔር ልጅም ይባላል። እግዚአብሔር አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል ለያዕቆብ ወገንም ለዘላለም ነግሦ ይኖራል ለመንግስቱም ፍጻሜ የለውም።  ማርያምም መልአኩን ወንድ ሳላውቅ ይህ እንደምን ይሆናል አለችው።መልአኩም መልሶ እንዲህ አላት መንፈስ ቅዱስ መጥቶ ያድርብሻል የልዑል ኃይልም ያጸናሻል ከአንቺ የሚወለደው ከሶስቱ አካል አንዱ የልዑል እግዚአብሔር ልጅ ይባላል። እነሆ ዘመድሽ ኤልሳቤጥም እርስዋ ደግሞ በእርጅናዋ ፀንሳለች ወንድልጅም አገኘች ለእርስዋም መካን ትባል ለነበረችው ይህ ስድስተኛ ወር ነው ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና። ማርያምም እነሆኝ የእግዚአብሔር አገልጋይ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ አለችው። ያን ጊዜም ድንግል ስትሆን ረቂቅ ፅንስን ተቀበለች የእግዚአብሔር አካላዊ ቃል ወልድ ዋህድ ለኩነተ ሥጋ ወርዶአልና ይህም አንድ ባሕርይ አንድ ህልውና ሲሆን ከሦስቱ አካላት አንዱ ነው ከዓለም መፈጠር አስቀድሞ የነበረ በማይመረመር ድንቅ በሆነ ተዋሕዶ እንዴትም እንደሆነ በማይታወቅ በቅድስት ድንግል ማርያም ማሕፀን አደረ ፅንስ ሆኖ ኖረ። በዚያን ጊዜም የኋላ ኋላ መለየት ከቶ የሌለውን ፍጹም ሰውነት ነሥቶ ተዋሐደ መለኮቱ ከትስብእቱ ጋራ ያለ መለያየት አንድ ሆኖአልና። ይቺም ዕለት የበዓላት ሁሉ በኵር ናት በእርሷም የዓለም ድኅነት ተጀምሮዋልና። ዳመኛም በዚህች እለት የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጽንሰት በተጨማሪ የቅድስት ፍቅርተ ክርስቶስ፣የቅዱሳን አብርሃ ወአጽብሐ፣ የቅዱስ ኢያሱ ነቢይ፣ የቅዱስ ላሊበላ፣ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጽንሰታቸው ታስቦ ይውላል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #በዓለ_ትንሳኤ በዚህችም ዕለት ደግሞ በመድኃኒታችን በከበረችና ልዩ በሆነች ትንሣኤው የዓለም ድኅነት ሆነ፡፡ በረቀቀ ጥበቡ ሠላሳ ሦስት ዓመት ያህል በምድር ላይ ሥራውን ሠርቶ በፈጸመ ጊዜ በፈቃዱ ሕማማተ መስቀልን ተቀብሎ ሙቶ ከተቀበረ በኋላ በሦስተኛው በዚች ቀን በሃያ ዘጠኝ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷልና። በዚች ቀን አስቀድሞ ደጅ ለሚጠኑት በዓለም ላሉ ሰዎች ሰው በመሆኑ ድኅነታቸውን አበሠራቸው እንዲሁም ደግሞ በዚች ዕለት ከሲኦል በመዳን ሙታንና ሕያዋን ደስ አላቸው። በዚህም በጌታችንና በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ መነሣት መነሣታቸውን አረጋገጡ። የከበረ ጳውሎስ በመነሣቱ ክርስቶስ የሙታን በኵር ሆነ እንዳለ እርሱ ለሙታን በኵራቸው ነውና። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ሐዋርያ_ቅዱስ_ጳውሎስ በዚህችም ቀን የከበረ ሐዋርያ ጳውሎስ አልዋሪቆን ከምትባል አገር ደርሶ አስተማረ ይቺም የምድር ዳርቻ ናት። ራሱ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ አለ ከዚያም በእግዚአብሔር መልአክ ትእዛዝ ወደ ዚያች አገር ሔድኩ ሀገሪቱም እንደ ሮሜ አማሳል ታላቅ የሆነች እጅግ ውብ ናት ፍሬዋም የበዛ ነው። በውስጡ የሚታለፍበት ስሙ ገርጋ የሚባል ባሕር ግን አግድመቱ ሦስት መቶ ምዕራፍ ነው። መጋቢት ሃያ ሰባት ቀንም መጀመሪያ ከዚያ ከባሕሩ ዳርቻ ደረስኩ ለሀገሩም ሰዎች በዓላቸው ነበር የጽጌ ረዳ አክሊልም እየታቱ በጣዖቶቻቸው ራስ ላይ ያኖራሉ ከስንዴአቸውም አዲስ እሸትን ለጣዖቶቻቸው ያቀርባሉ። የአገር ጠባቂ የሚሉትም በጠልሰም የተቀረጸ ሥዕል በአገሩ ቅጽር ላይ ተደርጓል ወደዚያች አገር የሚመጣ እንግዳ ሰው ሲያይ በላዩ ያደረ ርኵስ መንፈስ በታላቅ ድምፅ ይጮኻል። የአገር ሰዎችም የዚያን ጠልሰም ጩኸቱን በሚሰሙ ጊዜ ወደ አገራቸው የመጣውን እንግዳ ወጥተው ይገድሉታል ሕጋቸው እንዲህ ነውና ወደ አገራቸው ይገባ ዘንድ ማንንም አይተዉም አያሰናብቱም። እኔም ወደዚያች አገር ደርሼ ወደ ባሕሩ በቀረብኩ ጊዜ ያ ጠልሰም እነሆ እንግዳ ወደ እናንተ ደረሰ ብሎ በአገራቸው ቋንቋ ጮኸ። የአገር ሰዎችም ድምፁን ሰምተው ከንጉሣቸው ጋራ ብዙ ሰራዊት መጡ በዚያን ጊዜ ስለ በዓላቸው ተሰበስበው ነበርና ፈለገኝ እኔ ግን በአየኋቸው ጊዜ ሸሽቼ የቀበሮዎችና የእሽኮኮዎች መሸሻ ወደ ሆነ ዋሻ ገባሁ። ከዚያም ገብቼ በረሀብና በጥም ስለተሠቃየሁ አለቀስኩ። በዚያን ቀን የፀሐይ ትኩሳት ከመጽናቱ የተነሣ ሐሩር ሆኖ ነበርና በዚያም እስከ ሌሊት ቆይቼ ከዚያ ወጥቼ ከባሕሩ ውኃ ጠጣሁ ቁሜም ወደ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስም ጸለይኩ። ንጋትም በሆነ ጊዜ ከዚያ ዋሻ ወጥቼ ወደ አገር ለመግባት ፈለግሁ። ያ ጠልሰም አሁንም መምጣቴን እየገለጠ ሁለተኛ እንደታላቅ ነጐድጓድ ጮኸ ለባሕሩም ልማድ አለው ጠልሰሙ በሚጮኸ ጊዜ ይታወካል ማዕበሉም ይነሣል ያን ጊዜም ያገር ሰዎች ሊገድሉኝ መጡ። ከሩቅ በአየኋቸውም ጊዜ ፈራሁ እንደቀድሞውም በዚያ ዋሻ ደግሜ ተሸሸግሁ ጌታ ክርስቶስንም እለምነው ዘንድ ጀመርኩ በአባት ጴጥሮስም ጸሎት የማፀንኩ በወንድሞቼ በሐዋርያትም ጸሎት። ይልቁንም ንጽሕት ድንግል በሆነች በብርሃን እናት በእመቤታችን ማርያም በአማላጅነቷ ተማፀንኩ በሌሊቱ ርዝመት ሁሉ ስጸልይ አደርኩ። በነጋም ጊዜ ወደ ባሕሩ ዳር ወጣሁ ያም ጠልሰም እንደ ልማዱ ጮኸ ተራራዎችም እስቲናወጹ ጩኸቱን አበዛ የባሕሩም ማእበል ታወከ። ውኃውም እንደ ደም ሆነ የአገሩም ሰዎች ከሠራዊቶቻቸው ጋራ እንደ ቀድሞው ወጡ ባሕሩም መርከቦችን ተመላ እኔም ልሠወር ሮጥኩ። በዚያን ጊዜም የብርሃን እናት እመቤታችን ድንግል ማርያምን በባሕሩ ላይ ቁማ አየኃት። ጳውሎስ ሆይ ወዴት ትሸሻለህ አምላክህ ክርስቶስ እንዲህ እንድትሸሽ አዘዘህን እርሱ ራሱ ሥጋችሁን የሚገድሉትን አትፍሩአቸው ነፍሳችሁን ግን መግደል አይችሉምና ያለ አይደለምን። አንተም በቦታህ ጸንተህ ቁም እኔም ከአንተ ጋራ አለሁ እጄንም ከአንተ አላርቅም በርታ ጠንክርም የዚችን አገር ሰዎች ሁሉንም በዚህ የባህር ውኃ እንደምታጠምቃቸው ዕወቅ በእጅህም አምነው ሙታን በሚነሡባት ዕለት ዕድላቸው ከአንተ ጋር ይሆናል ባሕሩም ቃልህን ሰምቶ ይታዘዝልሃል አለችኝ።

🔴#ስንክሳር መጋቢት_28 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም #ጻድቅ_ንጉስ_ቈስጠንጢኖስ መጋቢት ሃያ ስምንት በዚች ቀን ጻድቅ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ አረፈ። የዚህ ቅዱስ የአባቱ ስም ቍንስጣ የእናቱ ስም ዕሌኒ ነው ቊንስጣም በራንጥያ ለሚባል አገር ንጉሥ ነው መክስምያኖስም በሮሜ በአንጾኪያና በግብጽ ላይ ነግሦ ነበር። ይህም ቍስጣ አረማዊ ነበር ግን በጎ ሥራ ያለው እውነትን የሚወድ በልቡናውም ይቅርታና ርኃራኄን የተመላ ክፋት የሌለበት ነው። ወደ ሮሐ ከተማ በሔደ ጊዜ ዕሌኒን አይቶ ሚስት ልትሆነው አገባት እርሷም ክርስቲያናዊት ናት። ንጉሥ ቈስጠንጢኖስንም ፀንሳ ወለደችው ስሙንም ቈስጠንጢኖስ ብላ ጠራቸው ይህም ዝንጉርጒር ማለት ነው። ከዚህም በኋላ ንጉሥ ቊንስጣ ዕሌኒን በዚያው ትቷት ወደ በራንጥያ ከተማ ተመለሰ። እርሷም ልጇን እያሳደገች በዚያው ኖረች የክርስትናን ትምህርት አስተማረችው ይቅርታንና ርኅራኄን በክርስቲያን ወገኖች ላይ እንዲያደርግ በልቡናው ትዘራበት ነበር። እርሷ ክርስቲያን ስትሆን የክርስትና ጥምቀትን ታጠምቀው ዘንድ አልደፈረችም መንፈሳዊ ዕውቀትን ሁሉ በማስተማር አሳደገችው ዳግመኛም ለመንግሥት ልጆች የሚገባውንም ሁሉ። ከዚያም በኋላ ወደ አባቱ ሰደደችው አባቱም በአየው ጊዜ ደስ ተሰኘበት ዕውቀትን የተመላ ሁኖ ፈረስ በመጋለብም ብርቱና የጸና ሆኖ አግኝቶታልና በበታቹም መስፍን አድርጎ ሹሞ በመንግሥቱ ሥራ ላይ ሁሉ ሥልጣን ሰጠው። ከሁለት ዓመትም በኋላ አባቱ አረፈ ቈስጠንጢኖስም መንግሥቱን ሁሉ ተረከበ የቀና ፍርድንም የሚፈርድ ሆነ ከእርሱ በፊት የነበሩ ነገሥታት የጫኑባቸውን ጽኑ አገዛዝ ከሰዎች ላይ አስወገደ። አሕዛብም ሁሉ ታዘዙለት ወደዱትም የአገዛዙ ቅንነትና የፍርዱ ትክክለኛነት በአገሮች ሁሉ እስቲሰማ ተገዙለት። የሮሜ ሰዎች ታላላቆች መልእክትን ወደርሱ ላኩ ከከሀዲ መክስምያኖስ ጽኑ አገዛዝ እንዲያድናቸው እየለመኑ እርሱ አሠቃይቷቸው ነበርና። ነመልእክታቸውንም በአነበቡ ጊዜ ስለ ደረሰባቸው መከራ እጅግ አዘነ ያድናቸውም ዘንድ ምን እደሚያደርግ በዐደባባይ ተቀምጦ እያሰበ ሲያዝን እነሆ ከቀኑ በስድስት ሰዓት በቀትር ጊዜ ኅብሩ እንደ ከዋክብት የሆነ መስቀል ታየው በላዩም በዮናኒ ቋንቋ ኒኮስጣጣን የሚል ጹሑፍ አለ ትርጓሜውም በዚህ ጠላትህን ድል ታደርጋለህ ማለት ነው። የመስቀሉም ብርሃን የፀሐይን ብርሃን ሲሸፍነው በአየ ጊዜ አደነቀ። በላዩ ስለተጻፈውም አስቦ ለጭፍሮቹ አለቆችና ለመንግሥቱ ታላላቅ ባለሥልጣኖች አሳያቸው። እነርሱም ቢሆኑ ይህ መስቀል ስለምን እንደተገለጠ አላወቁም። በዚያችም ሌሊት የእግዚአብሔር መልአክ ለቈስጠንጢኖስ በራእይ ተገልጦ እንዲህ አለው በቀኑ እኩሌታ በቀትር በአየኸው በዚያ መስቀል አምሳል ላንተ ምልክት አድርግ በርሱም ጠላትህን ድል ታደርጋለህ አለው። ከእንቅልፉም በነቃ ጊዜ ልቡ ጸና የወርቅ መስቀልም አሠርቶ በነገሠበት ዘውድ ላይ አደረገው መኳንንቱንና ወታደሮቹን ጭፍሮቹን ሁሉ መስቀል ሠርተው በጦር መሣሪያቸው ላይ ያደርጉ ዘንድ አዘዛቸው እነርሱም እንዳዘዛቸው አደረጉ። ይህም የሆነው በበራንጥያ በነገሠ በሰባተኛ ዓመቱ ነው። የሮሜን ሰዎች ከሥቃያቸው ሊያድናቸው ሠራዊቱን ሰብስቦ ተነሥቶ ወጣ። መክስምያኖስም ሰምቶ በታላቅ ወንዝ ላይም ታላቅ ድልድይ ሠርቶ ወደ ቈስጠንጢኖስም ተሻግሮ ከእርሱ ጋራ ተዋጋ። የመስቀሉም ምልክት ቀድሞ በታየ ጊዜ የመክስምያኖስ ሠራዊት ድል ይሆኑ ነበር የቈስጠንጢኖስም ሠራዊት ከመክስምያኖስ ሰራዊት ብዙ ሰው ገደሉ። የቀሩትም ሸሽተው ሲሔዱ ከመክስምያኖስ ጋር ሊሻገሩና ወደ ሮሜ ሊገቡ ድልድይ ላይ ወጡ ድልድዩም ፈርሶ ፈርዖን ከሠራዊቱ ጋራ እንደ ሠጠመ እንዲሁ መክስምያኖስ ከሠራዊቱ ጋራ ሠጠመ። ቈስጠንጢኖስም ወደ ሮሜ ከተማ ሲገባ የሮሜ ሰዎች ከካህናት ጋራ መብራቶች ይዘው በእንቍ የተሸለሙ አክሊሎችን ደፍተው እምቢልታ እየነፉ ተቀበሉት የተማሩ ሊቃውንትም የከበረ መስቀልን ሲያመሰግኑት የሀገራችን መዳኛ ይሉት ነበር ለከበረ መስቀልም ሰባት ቀን በዓል አደረጉ። ቈስጠንጢኖስም ዳግመኛ በሮሜ ነገሠ ከሀዲዎች የሆኑ መክስምያኖስና ዲዮቅልጥያኖስ ስለ ክብር ባለቤት ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት ያሠሩአቸውን እሥረኞች ሁሉንም ፈታቸው ደግሞ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ ብሎ ዓዋጅ አስነገረ። ዳግመኛም ክርስቲያኖችን እንዲአከብሩአቸው እንጂ እንዳያዋርዱአቸው የጣዖታቱንም ገንዘብና ምድራቸውን ለካህናት እንዲሰጧቸው አዘዘ ክርስቲያኖች በአረማውያን ላይ እንዲሾሙ አደረገ። ዳግመኛም አባቶቻችን ሐዋርያት እንዳዘዙ ማንም ሰው በሰሙነ ሕማማት ሥራ እንዳይሠራ አዘዘ። በነገሠ በሥስራ አንድ ዓመት በሮሜ ሊቀ ጳጳሳት በሶል ጴጥሮስ እጅ የክርስትና ጥምቀትን ተጠመቀ። ሠራዊቱም ሁሉ። ይህም የከበረ መስቀል ከተገለጠለት በኋላ በአራት ዓመት ነው። ከዚህ በኋላም በእርሱ ርዳታና ድል ያገኘበትን የሚያድን ስለ ሆነ ስለ ጌታችን መስቀል ትመረምር ዘንድ እናቱ ዕሌኒን ወደ ኢየሩሳሌም ላካት። እርሷም ዐመፀኞች አይሁድ ቀብረው ከደፈኑት ቦታ አወጣችው። በዘመኑ ሃይማኖታቸው የቀና የሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ጳጳሳት የአንድነት ስብሰባ በኒቅያ ስለ አርዮስ ተደረገ። ለክርስቲያኖች መመሪያ በበጎ አሠራር ክርስቲያናዊት ሥርዓት ተሰራች። ከዚህም በኋላ በበራንጥያ ታላቅ ከተማ ሊሠራ አሰበ እንደ አሰበውም ታላቅ ከተማ ሠርቶ በስሙ ቍስጥንጥንያ ብሎ ጠራት። በውስጧም አምላክን በወለደች በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በአግያና በሶፍያም ታላቅ ቤተ ክርስቲያን ሠራ መንፈሳዊ በሆነ በመልካም ጌጥ ሁሉ አስጌጣት። በውስጥዋ ከሐዋርያት የብዙዎቹን ዓፅም ከሰማዕታትና ከቅዱሳን ጻድቃን ሥጋቸውን ስለሚሰበስብ። የክብር ባለቤት ጌታችንን ደስ አሰኝቶ መልካም ተጋድሎውን ከፈጸመ በኋላ በኒቆምድያ ከተማ ጥቂት ታሞ አረፈ። ገንዘውም በወርቅ ሣጥን አድርገው ተሸክመው ወደ ቊስጥንጥንያ አደረሱት የጳጳሳት አለቆችና ካህናቱ ከሁሉ ሕዝብ ጋር ወጥተው ተቀበሉት በብዙ ጸሎት በመዘመርና በማኅሌት በምስጋና ወደ ከበሩ ሐዋርያት ቤተ መቅደስ አስገብተው በክብር አኖሩት። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን።https://t.me/finotebirhan12

ከዚህም በኋላ የከበረ አባ መቃርስ ተመልሶ ከእርሱ አስቀድሞ በዚያ በረሀ ውስጥ ሰው እንዳለ ያይ ዘንድ ወደ በረሀው ውስጥ ዘልቆ ገባ። ዕራቁታቸውን የሆኑ ሁለት ሰዎችን አይቶ ፈራ የሰይጣን ምትሐት መስሎታልና እልቦት ቦሪቦን ብሎ ጸለየ ይህም አቡነ ዘበሰማያት ማለት ነው እነርሱም በስሙ ጠርተው መቃሪ ሆይ አትፍራ አሉት እርሱም በበረሀ የሚኖሩ ቅዱሳን እንደሆኑ አውቆ ወደ እርሳቸው ቀርቦ እጅ ነሣቸው። እነሱም በዓለም ስላሉ ሰዎች ስለ ሥራቸውም ጠየቁት እርሱም በቸርነቱ እግዚአብሔር በሁሉም ላይ አለ ብሎ መለሰላቸው። እርሱም ደግሞ የክረምት ቅዝቃዜ ይቀዘቅዛቸው እንደሆነ የበጋውም ትኩሳት ያልባቸው እንደሆነ ጠየቃቸው። እነርሱም በዚህ በረሀ እግዚአብሔር አርባ ዓመት ጠብቆናል የክረምት ቅዝቃዜ ሳይቀዘቅዘን የበጋ ትኩሳት ሳያልበን ኖርን ብለው መለሱለት ደግሞ እንደናንተ መሆን እንዴት እችላለሁ አላቸው። እነርሱም ወደ በዓትህ ተመልሰህ ስለ ኃጢአትህ አልቅስ አንተም እንደእኛ ትሆናለህ አሉት ከእነርሱም በረከትን ተቀብሎ ወደቦታው ተመለሰ። በእርሱ ዘንድ መነኰሳት በበዙ ጊዜ ጕድጓድ ቆፍረው መታጠቢያ ሠሩለት ሊታጠብ በወረደ ጊዜ ሊገድሉት ሰይጣናት በላዩ አፈረሱት መነኰሳትም መጥተው አወጡት። እግዚአብሔርም ከዚህ አለም መከራ ሊያሳርፈው በወደደ ጊዜ ሁልጊዜ የሚጐበኘውን ኪሩብን ወደርሱ ላከ። እርሱም እኔ ወደ አንተ መጥቼ እወስድሃለሁና ተዘጋጅ አለው ከዚያ በኋላ አባ እንጦንስንና የቅዱሳንን አንድነት ማኅበር ሰማያውያን የሆኑ የመላእክትንም ሠራዊት በእግዚአብሔር እጅ ነፍሱን እስከ ሰጠ ድረስ ያይ ነበር። መላ የዕድሜው ዘመን ዘጠና ሰባት ሆነ። የቅዱስ መቃርስ ነፍስ ወደ ሰማይ ስታርግ እንዳየ በዚህ ነገር ደቀ መዝሙሩ አባ በብኑዳ ምስክር ሆነ ሰይጣናትን እንደሰማቸው እየተከተሉ መቃሪ ሆይ አሸነፍከን አሸነፍከን እያሉ ሲጮኹ እስከ ዛሬ ገና ነኝ አላቸው ወደ ገነትም ሲገባ መቃሪ ሆይ አሸነፍከን ብለው በታላቅ ድምፅ ጮኹ የክብር ባለቤት ፈጣሪዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ይመስገን ስሙም ይባረክ ከእጃችሁ ያዳነኝ አላቸው ብሎ መስክሮአል። የሥጋው ፍልሰትም እንዲህ ሆነ እርሱ በሕይወት ሳለ ሥጋውን እንዳይሠውሩ ልጆቹን አዞአቸው ነበር የሀገሩ የሳሱይርም ሰዎች መጥተው ለደቀ መዝሙሩ ለዮሐንስ ገንዘብ ሰጡ። ይህንንም ስለ ገንዘቡ ፍቅር ይመክረውና ይገሥጸው የነበረ ገንዘብ ከመውደድ ተጠበቅ የሚለው ነው። እርሱም መርቶ የቅዱስ አባ መቃርስን ሥጋ አሳያቸው ወደሀገራቸው ሳሱይር ወሰዱት እስከ ዓረብ መንግሥት መቶ ስልሳ ዘመን በዚያ ኖረ ደቀ መዝሙሩ ዮሐንስ ግን ገንዘብ ስለመውደዱ ዝልጉስ ሆነ። ከዚህም በኋላ ልጆቹ መነኰሳት ወደ ሀገሩ ወደ ሳሱይር ሔዱ የከበረ አባት የአባ መቃርስን ሥጋ ሊወስዱ ፈለጉ የአገር ሰዎችም ከመኰንኑ ጋር ተነሥተው ከለከሉአቸው በዚያቺም ሌሊት የከበረ አባ መቃሪ ለመኰንኑ ተገልጦ ተወኝ ከልጆቼ ጋራ ልሒድ አለው። መኰንኑም መነኰሳቱን ጠርቶ የአባታቸውን ሥጋ ተሸክመው ይወስዱ ዘንድ ፈቀደላቸው። በዚያን ጊዜም ተሸከመው አክብረው ወሰዱት በብዙ ምስጋና በመዘመርም እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ነሐሴ ዐሥራ ዘጠኝ ቀን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት ከእርሱም ታላላቅ ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ማለድ ብለው ሲደርሱ አርፋ አገኟት፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ንጉሥ_ሰማዕት_ገላውዴዎስ በዚህችም ቀን የኢትዮጵያ ንጉሥ ሰማዕት ገላውዲዎስ አንገቱን የተቆረጠበት ቀን ነው። ይህ ቅዱስም በተግሣጽ በምክር በፈሪሀ እግዚአብሔር አደገ አባቱ ንጉሥ ልብነ ድንግል ሃይማኖቱ የቀና ነበርና በዘመኑም የእስላም ወገን የሆነ ስሙ ግራኝ የሚባል ተነሥቶ አብያተ ክርስቲያናትን አጠፋ። ከንጉሥ ልብነ ድንግል ጋር ጦርነት ገጠመ ንጉሡም ወግቶ መመለስ ቢሳነው አርበኞች ሠራዊትን እስከሚሰበስብ ከእርሱ ሸሸ በስደትም እያለ በድንገት ታሞ ሞተ። ይህም አመፀኛ የኢትዮጵያን ሀገሮች እያጠፋ ዐሥራ አምስት ዓመት ያህል ኖረ። ከኢትዮጵያም ሕዝቦች የሚበዙትን ማርኮ ከቀናች ሃይማኖት አውጥቶ የእርሱ ሃይማኖት ተከታዮች አደረጋቸው በመመካትም እንዲህ አለ። ሀገሮችን ሁሉ ግዛቶቼ ስለ አደረግኋቸው ከእንግዲህ የሚቃወመኝ የለም። ከዙህ በኋላ እግዚአበሔር ይህን ቅዱስ ገላውዴዎስን አስነሣ ከግራኝ ታላላቅ መኳንቶቹ ጋር ጦርነት ገጠማቸው ድልም አድርጎ አሳደዳቸው። ግራኝም በሰማ ጊዜ ተቆጣ ከቱርክ አርበኞች ጋርና ከአእላፍ ፈረሰኞች ጋር መጥቶ ንጉሡን ገጠመው ጌታችንም ግራኝን በንጉሥ ገላውዴዎስ እጅ ጣለው ገደለውም። ግራኝን በመፍራት የተበተኑ ሁሉ ከተማረኩበትም ሁሉ ተመለሱ የፈረሱ አብያተ ክርስቲያናትም ተመልሰው ታነፁ የክብር ባለቤት የሆነ የክርስቶስ ሃይማኖት ተቃናች። ከዚህም በኋላ ከእስላሞች ወገን አንዱ ከብዙ አርበኞች ሠራዊት ጋር መጣ በመድኃኒታችን የስቅለት በዓል ከጥቂት ሰዎች ጋራ ተቀምጦ ሳለ በድንገት ንጉሡን ተገናኘው ሰዎቹም የጦር መኰንኖች እስቲሰበሰቡ ፈቀቅ እንበል አሉት። እርሱ ግን የክርስቲያኖችን መማረክና የአብየተ ክርስቲያናትን መፍረስ አላይም ብሎ እምቢ አለ እንዲህም እያለ ወደ ውጊያው መካከል ገብቶ በርትቶ ሲዋጋ የኋላ ኋላ እስላሞች ሁሉም ከበቡት። ተረባረቡበትም በጐራዴም ጨፈጨፉት በብዙ ጦሮችም ወጉት ከፈረሱም ጣሉት የከበረች አንገቱንም ቆረጡት ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

ያን ጊዜም ተነሥቶ ጸሎት አድርጎ ወደ አረጋዊ አባ እንጦንዮስ ዘንድ እስከሚደርስ ወደምሥራቅ አቅጣጫ ተጓዘ። አባ እንጦንዮስም ከሩቅ በአየው ጊዜ እነሆ ተንኰል ሽንገላ የሌለበት እስራኤላዊ አለው በታላቅ ደስታ ተቀብሎ ሳመው። አባት ለልጁ እንደሚገልጥ ኀሳቡን ሁሉ ገለጠለት ይህ አረጋዊ አባ እንጦንዮስም የመቃርስን ራሱን ስሞ ልጄ ሆይ በዮናኒ ቋንቋ እንደ ስምህ ትርጓሜ አንተ ብፁዕ ትባላለህ። ሥራህንና ወደ እኔ መምጣትህን ፈጣሪዬ እግዚአብሔር ገልጦልኛልና ስለዚህም መምጣትህን የምጠባበቅ ሆንኩ አለው። ከዚህ በኋላ ለአባ መቃርስ የከበረች የምንኵስናን ሥርዓት ሁሉ አስተማረው መሠራቱ በሚገባ በብዙ ነገርም አጸናው። ሰይጣናት የሚዋጉት መሆናቸውን እነርሱ በሥውር በፈቲው ጦር እንዲሁም ጥፋት በሆኑ ሥራዎች ሁሉ ይዋጉህ ዘንድ አላቸው። አንተ ፍጹም ልትሆን አንተም እስከ ሞት ደርሰህ ታገሥ አሁንም እግዚአብሔር ወደ ወሰነልህ ቦታ ሒደህ ሥራህን እየሠራህ በውስጡ ታገሥ ብሎ ገለጠለት። ከአባ እንጦንዮስ ዘንድ የምንኵስናን ሥርዓት እየተማረ ጥቂት ቀኖች ከኖረ በኋላ ከተባረከ ኤጲስቆጶስ ከአባ ሰራብዮን ጋራ በተማራቸው ሕያዋን በሚያደርጉ ትምህርቶችና ሥርዓቶች ፈጽሞ ደስ እያለው ወደ ቦታው ተመለሰ። አባ መቃርስም በአባቴ በአባ እንጦንዮስ ዘንድ በነበርኩባቸው ቀኖች ሲተኛ ከቶ አላየሁትም አለ። አባ መቃርስም በምንኵስና ሥርዓት ተጠምዶ እየተጋደለ ብዙ ቀን ኖረ ያ ኪሩብም በግልጽ ይጐበኘው ነበር። በአንዲት ቀንም እንዲህ የሚለውን ቃል ከሰማይ ሰማ ቃሌንና ትእዛዜን ሰምተህ ወደዚህ መጥተህ በዚህ ቦታ ውስጥ ስለኖርክ እነሆ ቊጥር የሌላቸውን የብዙ ብዙ ወገኖችን ከነገዶች ከሀገሮች በቋንቋ ከተለያዩ ሕዝቦች እሰበስባለሁ ። እንርሱም በዚህ ቦታ ያገለግሉኛል የከበረ ስሜንም ያመሰግናሉ በበጎ ሥራቸውና ትሩፋታቸው ደስ ያሰኙኛል አንተም ተቀበላቸው ዕውነተኛ የድኅነት መንገድን ምራቸው። ይህንንም ቃል በሰማ ጊዜ ተበረታታ ልቡም ጸና። በሌሊትም በጸሎት ጊዜ ቁሞ ሳለ የክብር ባለቤት ጌታችን ጆሮውን ከፍቶለት ሰይጣናትን ሲሞክሩ ሰማቸው እንዲህም አሉ ይህን ሰው በዚህ በረሀ እንዶኖር ብንተወው የብዙ ብዙ ወገኖችን ይመራቸዋል እነርሱም በዚህ በረሀ ውስጥ ነዋሪዎች ሁነው የሰማያውያን ሀገር ያደርጉታል። እነርሱ ለዘላለም ጸንቶ በሚኖር ሕይወት ይተማመናሉና። እኛንም በሚቀጣ ጸሎታቸው ቀጥተው አሠቃይተው ያሳድዱናልና ከዚህ ቦታ ልናሳድደው እስኪ እንችል እንደሆነ ኑ ዛሬ በእርሱ ላይ እንሰብስብ ሲሉ ሰማቸው። አባ መቃርስም ይህን በሰማ ጊዜ ልቡ ጸና በሰይጣናት ላይም ተበረታታ የሰይጣናት ምክራቸውን እስከሚሰማ ጀሮውን የከፈተለት እግዚአብሔርን አመሰገነ ድካማቸውንም አወቀ። ከዚህ በኋላ ይዋጉት ዘንድ ሰይጣናት በእርሱ ላይ ተሰበሰቡ በደጁም እሳትን እያነደዱ ከእሳቱ እያነሡ ወደ በዓቱ ይጨምሩ ጀመር ያቺ እሳት ግን በጸሎቱ የምትጠፋ ሆነች። ከዚህ በኋላ እንስሳዊ በሆነ ሥራ በፈቲው ጦር ተዋጉት በዚህም ታገሠ። ትካዜን ዓላማዊ ክብር መውደድን ትእቢትን መመካትን ታካችነትን ስድብን ሃይማኖት ማጣትን ከእግዚአብሔር ዘንድ ተስፋ መቁረጥን በልቡ አሳደሩበት ከዚህም ሁሉ በሚበዛ ተዋጉት የከበረ አባ እንጦንዮስ እንደነገረው። በእሊህም አጥፊዎች በሆኑ ሥራዎች ሰይጣናት እየተዋጉት ለረጅም ጊዜ ከኖረ በኋላ ዳግመኛ ወደ አባት እንጦንዮስ ገና ከሩቅ ሳለ ለደቀ መዛሙርቱ በልቡ ሽንገላ በእውነት የሌለበት እስራኤላዊ ነው ልጆቼ ይህን የከበረ ሰው ታዩታላችሁን እርሱ ለብዙ ወገኖች የቀና የጽድቅ በትርና ረጅም አላማ ይሆን ዘንድ አለውና ከአሸናፊ እግዚአብሔር አፍ የተገኘ ጣፋጭ ፍሬም ይሆናልና አለ። ወደ ቅዱስ አባ እንጦንዮስም በቀረበ ጊዜ በምድር ላይ ሰገደለት በፍጥነትም ቀና አድርጎ ሳመው ፊቱ እንደ በሽተኛ ፊት ተለውጦ አይቶታልና ይኸውም ሰይጣናት አብዝተው ስለተዋጉት ነው። ከዚያም ጸሎት አድርገው በአንድነት ተቀመጡ አባት እንጦንዮስ ደስታ በተመላ ቃል ልጄ መቃርስ በደኅና አለህን አለው ቅዱስ መቃርስም እነሆ ከእኔ የሆነውን ሁሉ እግዚአብሔር ቀድሞ ገልጦልሃል ብሎ መለሰለት እርሱም ያን ጊዜ አስተማረው አጽናናውም እንዲህም ብሎ መከረው። መንፈሳዊ ጥበብን ለሚሹ ለብዙ ወገኖች መምህራን እንድንሆን ይቺውም ምንኵስና ናት ከጠላታችን በላያችን የሚመጣብንን መከራ ሁሉ ልንታገሥ ለእኛ የሚገባ ነው። ልጄ መቃርስ ሆይ ውኃ ለመቅዳት ስትሔድ እግዚአብሔር የነገረህን ያንን ቃል አስብ አለው። ቅዱስ መቃርስም ሰምቶ እጅግ አደነቀ። የተሠወሩ ሥራዎቹ ለከበረ አባት እንጦንዮስ የተገለጡለት እንደሆኑ አወቀ። በእርሱ ዘንድም እየተማረና በረከትንም እየተቀበለ ብዙ ቀኖች ኖረ። ከዚያም የከበረች አስኬማን ያለብሰው ዘንድ ፈለገ አባ እንጦንዮስም በላዩ ጸለየ እርሷን አስኬማዪቱን አለበሰው ስለዚህም የከበረ እንጦንዮስ አባት ተባለ። ዳግመኛም ወደዚህ ወደኔ መምጣትን ቸል አትበል እኔ ከጥቂት ቀኖች በኋላ ወደ እግዚአብሔር እሔዳለሁና አለው። አባ መቃርስም ይህን ነገር በሰማ ጊዜ ተነሥቶ ሰገደለት መንፈሳዊ በረከቱን ይቀበል ዘንድ ከእርሱ ዘንድ እንዲኖር ለመነው እርሱም ተቀመጥ አለውና ተቀመጠ። ዳግመኛም አባ እንጦንዮስ ከጥቂት ቀኖች በኋላ ሰይጣናት በእኔ ላይ እንዳደረጉት በግልጥ ከተዋጉህ በኋላ ከዚህ ከክፉ አሳብ ውጊያ እግዚአብሔር ያሳርፍሃልና በርትተህ ታገሥ። እስከ ዕድሜህ ፍጻሜ ከአንተ ጋራ ሆኖ እንዲረዳህ እግዚአብሔር ያደረገውን ጠባቂህን መልአክ እንዳታሳዝነው ተጠበቅ አለው። ከዚህ በኋላ አባ እንጦንዮስ ለአባ መቃርስ በትሩን ሰጠው በመንፈሳዊም ሰላምታ ተሰናብቶት አረፈ ሥጋውንም ማንም በማያውቀው ሥውር ቦታ ቀበረው። የከበረ አባ መቃርስም ወደ ቦታው ተመልሶ በአስቄጥስ ገዳም ተቀመጠ ዜናውም በአራቱ ማእዘን ተሰማ። እግዚአብሔርም በእጆቹ አስደናቂዎች ተአምራትን አደረገ ከእነርሱም አንዱ የአንጾኪያ ንጉሥ ርኵስ መንፈስ ያደረባትን ልጁን ወደርሱ ላካት እርሷም በጐልማሳ አምሳል ሁና ወደርሱ መጣች እርሱም አወቀ አድኖ ወደ አባትና እናቷ ሰደዳት። እርሱም ብዙ ወርቅና ብር በላከለት ጊዜ ምንም ምን አልተቀበለም። ሁለተኛውም አውሲም በሚባል አገር አንድ መነኰስ ነበር ስቶ ትንሣኤ ሙታን የለም አለ ብዙዎች ሰዎችንም አሳታቸው የአውሲም ኤጲስቆጶስም ወደ አባ መቃርስ ሔዶ የእርሱን ሕዝቦች እንዳሳታቸው ነገረው እንዲረዳውም አብዝቶ ለመነው። አባ መቃርስም ተነሥቶ ከዚያ ኤጲስቆጶስ ጋራ ወደ ሀገረ አውሲም ደርሶ ያንን ርኵስ መንፈስ ያደረበትን ባሕታዊ መንኰስ ተገናኘው ስለ ትንሣኤ ሙታንም በተነጋገረው ጊዜ ያ ባሕታዊ የሞተ ሰው ከመቃብር ካላስነሣህ እኔ አላምንም ብሎ መለሰለት። አባ መቃርስም ወደ ክብር ባለቤት ወደ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጸለየ ያን ጊዜም አንድ ምውት ከሙታን ተለይቶ ተነሣ። ሰውየውም ከቀደሙ ከሀድያን ወገን ነው ያ ባሕታዊውም አምኖ ከስህተቱ ተመለሰ እንደርሱም የሳቱ ሁሉም ተመለሱ። ያ ከሙታን ተለይቶ የተነሣውም የክርስትና ጥምቀትን ያጠምቀው ዘንድ አባ መቃርስን ለመነው እርሱም አጥምቆ የምንኵስና ልብስ አለበሰው ሰባት ዓመትም ኑሮ አረፈ።

ዳግመኛም መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከዕርገቱ በኋላ ለቅዱሳን ሐዋርያት የሞቱን መታሰቢያ እንዲያደርጉ ነግሯቸዋልና፡፡ ሕማሙንና ሞቱንም እንዲዘክሩ አዟቸዋልና አሁንም ያንን ሁሉ የመድኃኔዓለምን ሞቱን ያላሰበና የሞቱን መታሰቢያ በዓል ያላከበረና እርሱንም የማይወደው ቢኖር ዕድል ፈንታው ጽዋ ተርታው ከአይሁድ ጋር ነው፡፡ የአምላካችንን የመድኃኔዓለምን ሞቱን በሚመስል ሞት ከእርሱ ጋር ተባብረን ትንሣኤውን በሚመስል ትንሣኤ ከእርሱ ለመተባበር ያብቃን! ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_መቃርስ_ታላቁ ዳግመኛም በዚህች ቀን በገዳም ለሚፈጸም ተጋድሎ ፋና የሆነ በአስቄጥስ ገዳም ለሚኖሩ መነኰሳት ሁሉ አባት የሆነ የከበረ አባት ታላቁ አባ መቃርስ አረፈ። ይህም የከበረ አባት በግብጽ ደቡብ መኑፍ ከሚባል አውራጃ ሳሱይር ከሚባል አውራጃ መንደር ከሚኖሩ ሰዎች ወገን ነው ። ወላጆቹም ደጎች ዕውነተኞች ነበሩ። አባቱ አብርሃም እናቱም ሣራ ይባላሉ። እናቱም እንደ ኤልሳቤጥና እንደ ሣራ በእግዚአብሔር ትእዛዝ ጸንታ የምትኖር ናት አባቱም በፈሪሃ እግዚአብሔር ሁኖ ንጽሕናውንና ቅድስናውን ጠብቆ ሁልጊዜ ቤተ ክርስቲያን በማገልገል ጸንቶ ይኖራል እግዚአብሔርም በላያቸው በረከቱን አሳድሮ በሥራቸው ሁሉ ከፍ ከፍ አደረጋቸው። ለድኆችም የሚመጸውቱ ለሰው ሁሉ የሚራሩ ናቸው። በጾም በጸሎትም ተወስነው እንዲህ ባለገድል ሲኖሩ ግን ልጅ አልነበራቸውም። ለአብርሃምም በሌሊት ራእይ ከእግዚአብሔር ዘንድ በልጅ አምሳል ተገለጠለት በዓለሙ ሁሉ የሚታወቅ ብዙ መንፈሳውያን ልጆችን የሚወልድ ልጅን ይሰጠው ዘንድ እግዚአብሔር አለው ብሎ አስረዳው። ከዚህም በኋላ ይህን የከበረ ልጅ መቃርዮስን እግዚአብሔር ሰጠው። ትርጓሜውም ብፁዕ ማለት ነው በላዩም የእግዚአብሔር ጸጋ አደረበት ለወላጆቹም ይታዘዝና ያገለግል ነበር ሊያጋቡትም አሰቡ እርሱ ግን አይሻም ነበር ፈቃዳቸውን ይፈጽም ዘንድ ግድ ብለው አጋቡት ወደ ሙሽራዪቱም በገባ ጊዜ ራሱን እንደታመመ ሰው አደረገ እንዲህም ሁኖ ብዙ ቀን ኖረ። ከዚያም በኋላ አባቱን ተወኝ ወደ ገዳም ልሒድ ከበሽታዬ ጥቂት ጤና ባገኝ አለው እግዚአብሔር ወደሚወደው ሥራ ይመራው ዘንድ ሁልጊዜ በጾምና በጸሎት ሁኖ ይለምነው ነበር። ከዚህም በኋላ ወደ አስቄጥስ በረሀ ሔደ ከበረሀውም በገባ ጊዜ ራእይን አየ ስድስት ክንፍ ያለው ኪሩብ እጅና እግሩን ይዞ ወደ ተራራ ላይ እንደሚያወጣውና የአስቄጥስን በረሀ ምሥራቋን ምዕራቧን የዚያችን በረሀ አራት ማእዘንዋን አሳይቶ እነሆ ይቺን በረሀ መላዋን ላንተና ለልጆችህ ርስት አድርጎ እግዚአብሔር ሰጥቶሃል አለው። ከበረሀውም በተመለሰ ጊዜ ያቺ ብላቴና ታማ አገኛት ጥቂት ቆይታ ወዲያው በድንግልናዋ እንዳለች አረፈች። የክብር ባለቤት እግዚአብሔርንም አመሰገነው። ከጥቂት ቀኖችም በኋላ እናት አባቱ አረፉ የተዉለትንም ገንዘብ በሙሉ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጠ። የሳሱይር ሰዎች ግን ዕውነተኛነቱንና ቅድስናውን አይተው ቅስና አሾሙት። ከከተማውም ውጭ ቤት ሠሩለት ሥጋውንና ደሙን ይቀበሉ ዘንድ ወደርሱ ይሔዱ ነበር። በዚያች አገርም አንዲት ድንግል ብላቴና ነበረች ከአንድ ጐልማሳ ጋርም አመንዝራ ፀነሰች ጉልማሳውም አባትሽ ድንግልናሽን ማን አጠፋው ብሎ ሲጠይቅሽ መቃርስ የሚባለው ባሕታዊ ቄስ እርሱ ስለ ደፈረኝ ነው በዪው ብሎ መከራት። ፅንሷም በታወቀ ጊዜ አባቷ ይህን አሳፋሪ ሥራ በአንቺ ላት የሠራብሽ ማነው ብሎ ጠየቃት። እርሷም በአንዲት ቀን መቃርስ ወደሚባለው ቄስ ሒጄ ሳለሁ በኃይል ይዞኝ ከእኔ ጋራ ተኛ ስለዚህ ከእርሱ ፀነስኩ ብላ መለሰችለት። ወላጆቿና ቤተሰቦቿም በሰሙ ጊዜ እጅግ ተቆጡ ከብዙ ሰዎችም ጋራ ወደ ቅዱስ መቃርስ ሒደው ይዘው ከበዓቱ አወጡት እርሱ ግን ምን እንደሆነ አላወቀም። ለመሞት እስቲቃረብም አጽንተው ደበደቡት እርሱም ኃጢአቴ ምንድናት እናንተ ያለ ርኅራኄ ትደበድቡኛላችሁና እያለ ይጠይቃቸው ነበር። ከዚህ በኋላ በፍሕም የጠቆሩ ገሎችን በአንገቱ ላይ በገመድ አንጠልጥለው ወዲያና ወዲህ እየጐተቱ የልጃችንን ድንግልና ያጠፋ ይህ ነው እያሉ እንደ እብድ በላዩ ይጮኹ ጀመር። በዚያን ጊዜ መላእክት እንደሰው ተገልጠው የሚያሠቃዩትን ሰዎች ይህ ተጋዳይ ምን አደረገ አሏቸው። እነርሱም በልጃቸው ላይ የኀፍረትን ሥራ እንደሠራ አድርገው መልሰው ነገሩአቸው። እነዚያ መላእክትም ይህ ነገር ሐሰት ነው እኛ ይህን ሰው ከታናሽነቱ ጀምሮ እስከዚች ቀን እናውቀዋለን እርሱ የተመረጠ ጻድቅ ሰው ነውና አሏቸው የታሠረበትንም ፈትተው ከላዩ ገሎችን ጣሉ እነዚያ ክፉዎች ግን ዋስ እስከሚሰጠን ድረስ አንለቀውም አሉ። እጀ ሥራውን የሚሸጥለት አንድ ሰው መጣ ለልጅቷም በየጊዜው ምግቧን ሊሰጣት ዋስ ሆነው ከዚያ በኋላ አሰናብተው ወደ በዓቱ ተመልሶ ገባ። ከዚያቺም ቀን ጀምሮ ራሱን በራሱ መቃርስ ሆይ እንግዲህ ባለሚስትና ባለልጅ ሁነኻል ሌሊትና ቀን መሥራት ይገባሃል እያለ ያቺ ሐሰተኛ ልጅ የምትወልድበት ጊዜ እስኪደርስ ድረስ እንቅቦችን ቅርጫቶችን እየሠራ ለዚያ ወዳጅ ለሆነውና ለሚያገለግለው ወንድም ይሰጠውና ያም ሰው እየሸጠ ለዚያች ሐሰተኛ ልጅ እየሰጠ ኖረ። የምትወልድበትም ቀን ሲደርስ እጅግ አስጨነቃት በታላቅ ሥቃይም ውስጥ አራት ቀኖች ያህል ኖረች። ለሞትም ተቃረበች እናቷም ከአንቺ የሆነው ምንድነው የተሠራ ሥራ አለና ንገሪኝ አለቻት። እርሷም በእግዚአብሔር አገልጋይ ላይ ዋሽቻለሁና ያመነዘርኩት ከዕገሌ ገ ልማሳ ጋር ሲሆን በዕውነት ሞት ይገባኛል አለቻት። አባትና እናቷም በሰሙ ጊዜ ደንግጠው እጅግ አዘኑ የአገር ሰዎችም ሁሉም ተሰበሰቡ በእርሱ ላይ የሰሩትን በደል ይቅር ይላቸው ዘንድ ወደ ቅዱስ መቃርስ ሒደው ለመኑት። ያን ጊዜ በበረሀ ያየውን ያንን ራእይ አስታውሶ ይቅር አላቸው ቀድሶም ሥጋውንና ደሙን አቀበላቸው። ክንፉ ስድስት የሆነ ኪሩብ ደግሞ ተገለጠለት ትርጓሜው የልብ ሚዛን ወደተባለ ወደ አስቄጥስ ገዳም እጁን ይዞ መርቶ አደረሰው። ቅዱስ መቃርስም ያንን ኪሩብ ጌታዬ ሆይ በውስጡ የምኖርበትን ቦታ ወስንልኝ አለው። ያ ኪሩብም አልወስንልህም የእግዚአብሔርንም ትእዛዝ አትተላለፍ እነሆ ይህ ገዳም ሁለመናው ላንተ ተሰጥቷልና ወደፈለግህበት ሒደህ ተቀመጥ ብሎ መለሰለት። ቅዱስ መቃርስም የቅዱሳን ሮማውያን የመኪሲሞስና የደማቴዎስ ቦታ ወደ ሆነው ከውስጥኛው በረሀ ገብቶ ኖረ። እነርሱ ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ከእርሱ አቅራቢያ ኑረዋልና ከዕረፍታቸው በኋላ ግን ሒዶ በዚያ ቦታ እንዲኖር የእግዚአብሔር መልአክ አዘዘው። ይኸውም ዛሬ የእርሱ ገዳም የሆነው መልአኩ ይህ ገዳም በልጆችህ በመክሲሞስና በደማቴዎስ በስማቸው ይጠራል ስለ አለው እስከዚች ቀን ደብረ ብርስም ተብሎ ይጠራል ትርጓሜውም የሮም ገዳም ማለት ነው። የከበረ አባ መቃርስም ታናሽ በዓት ሠራ። በውስጥዋም ሆኖ ያለ ማቋረጥ በጾም በጸሎት በስግደትም በመትጋት ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለ። ሰይጣናትም ተገልጠው የሚመጡበትና በቀንም በሌሊትም በግልጥ የሚዋጉት ሆኑ። በጸምና በጸሎት ሲጋደል ሰይጣናት እየተዋጉት ዕረፍትን ስለ አላገኘ በልቡ አሰበ በዓለም ውስጥ ሳለሁ የቅዱስ አባ እንጦንዮስን ዜና ሰምቻለሁ የምንኵስናን ሥርዓት ያስተማረኝና ይመራኝ ዘንድ ተነሥቼ ወደርሱ ልሒድ የረከሱ ሰይጣናት የመከሩትን ምክራቸውን እገለብጥ ዘንድ እርሱ ዕውቀትንና ማስተዋልን ይሰጠኛልና አለ።

በመድኃኔዓለም ክርስቶስ ሞት በአንድነት እናለቅስ ዘንድ ቅዱሳን ሁላችሁ ኑ! መድኃኒታችን ሙቷልና ፍጥረታት ሁሉ ያለቅሳሉ፤ መያዝንና መታሠርን የተቀበለ መድኃኒታችን ሙቷልና፡፡ ጥፊንና ግርፋትን የተቀበለ መድኃኒታችን ሞተ፡፡ መደብደብንና መመታትን የታገሰ መድኃኒታችን ሞተ፡፡ ሄኖክ እግዚአብሔር ‹‹በሴም ቤት ይደር›› ብሎ አብ ስለራሱ የተናገረለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ አብርሃም ቃልኪዳን የገባልህን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ይስሐቅ ከሰይፍ ቤዛ የሆነህን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ያዕቆብ በበረሃ የታገለህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኢዮብ በደመና የታየህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ሙሴ ስለ እርሱ ‹እንደእኔ ያለ ነቢይ ይነሣል› ብለህ የተናገርኽለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዳዊት ‹‹እነሆ በኤፍራታ ሰማነው፣ በበረሃ ዛፍም አገኘነው›› ብለህ የተናገርኽለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኤርሚያስ ‹‹የክቡሩን ዋጋ ሠላሳ ብር ተቀበሉ›› ብለህ የተናገርኽለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኢሳይያስ ‹‹ወልድ ሰው ለመሆን ተገለጠልን፣ ሕፃን ተወለደልን፣ ድንቅ መካር ኃያል አምላክ›› ብለህ የተናገርኽለት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ሕዝቅኤል ‹‹አምላክ ወደ ተዘጋች ደጃፍ ገባ፣ ከተዘጋች በርም ወጣ›› ብለህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዳንኤል ነጭ ሐር ለብሶ ያየኸውን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኤልያስ ከሞት በፊት የሰወረህ በእሳት ፈረሶች ያሳረገህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ሕዝቅያስ የፀሐይ መግባቱን ያሳየህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ምናሴ ችንካሮችህን ከእግር ብረት የፈታ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኢዮስያስ ፋሲካውን ያደረግህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ አናንያ፣ አዛርያና ሚሳኤል ከእሳት ምድጃ ያዳናች የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ኑ፡፡ አብያና ሲላ ፌንቶስ ከመወለዱ አስቀድሞ ያመናችሁበት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ኑ፡፡ የቀድሞ አባቶች ነቢያት ሁላችሁ ከፋራን ተራራና ከቴማን ይመጣል ያላችሁት የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ኑ፡፡ አሞፅ በአድማስ ቅጥር ያየኸው የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዘካርያስ በተራራዎች መካከል ያየኸው የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዕዝራ በአርፋድ በረሃ ያየኸው የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ስምዖን በክንድህ የታቀፍከውን ሕፃን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ዮሴፍ እንደ አንተ የተሸጠ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ጠራቢ ዮሴፍ በትከሻህ ያዘልከው በክንድህ የተሸከምከው ሕፃን የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ መጥምቁ ዮሐንስ ከሕፃንነትህ ጀምሮ በበረሃ ያለ እናት ያለ አባት ያሳደገህ መንገዱንም እንድትጠርግለት ያዘጋጀህና መለኮትን እንድታጠምቅ የመረጠህ የመድኃኒታችንን ሞቱን ታይ ዘንድ ና፡፡ ኢያቄምና ሐና ሆይ የልጃችሁን ልቅሶዋን የልቧንም መዘንጋት ታዩ ዘንድ ኑ፡፡ ከሔዋን እስከ ፋኑኤል ልጅ እስከ ሐና ያላችሁ ሁላችሁ ቅዱሳት ሴቶች የድንግልን ልቅሶዋን ታዩ ዘንድ ኑ፣ አንድ ልጇ ሙቷልና፡፡ የለመለመ የሥጋ ሞት ሕንፃ የተጀመረበት የአቤል ተከታዩ፣ ከጎኑ የፈሰሰው ደም ሔዋንን ከጥፋት ያዳናት የተገደለ መድኃኒታችን ነው፡፡ የናቡቴ ጓደኛው የተገፋው መድኃኒታችን ነው፡፡ አቤል ስለሚስቱ ሞተ፡፡ ናቡቴም ስለ ወይኑ ቦታ ሞተ፡፡ መድኃኒታችን ግን በቀኙ ያነጻት ዘንድ ስለቤተክርስቲያን ሞተ፡፡ ነፍሳችሁን ይወስዷታልና መውረዱንም አላወቁምና ስለ ወገኖቹ ኃጢአት እስከ ሞት ደረሰ ብሎ ስለ እርሱ የተናገረ አባቱን እንስማው፡፡ ሙሴም እርሱን ያውቁት ዘንድ አላሰቡትም፣ በሚመጣበት ቀንም አላወቁትም አለ፡፡ ዕዝራ በባሕር ጥልቅ ያለውን ማወቅ እንዳይችሉ ወልድንም ማወቅ እንዲሁ ሆነባቸው አለ፡፡ ጳውሎስም ብታውቁትስ ኖሮ የክብርን ጌታ እግዚአብሔርን ባልሰቀላችሁት ነበር አለ፡፡ በመሰደድ፣ ያለምንም በደልም በፍርድ አደባባይ በመቆም መከራ መስቀልን በመሸከም አብነት የሆናችሁ ሰማዕታት ሁላችሁ ኑ የመድኃኔዓለምን የሞቱን ዕለት አስባችሁ በጋራ አልቅሱለት፡፡ ሁሉ የእርሱ ከእርሱ ለእርሱ ተፈጥሮ ሳለ በምድር ላይ ምንም ሳይኖረው ራሱን እንኳን የሚያስጠጋበት ቤት ሳይኖረው አብነት የሆናችሁ ባሕታውያንና መነኮሳት ሁላችሁ ኑ በዛሬዋ ዕለት ስለሞተው አምላካችሁ መሪር ዕንባን አልቅሱለት፡፡ ሕግ ጠብቆ፣ ሥርዓት አክብሮ፣ ነዳያንን በመመገብና ያዘኑትን በማጽናናት 33 ዓመት በምድር ላይ ኖሮ አብነት የሆናችሁ እናንት በዓለም ሆናችሁ ሕግ ጠብቃችሁ፣ አሥራት በኩራቱን አውጥታችሁ፣ ድሆችን በመርዳት የምትኖሩ ክርስቲያኖች ሁላችሁ የመድኃኔዓለምን የሞቱን ዕለት ታስቡ ኑ፡፡ ‹‹የተጠራችሁለት ለዚህ ነውና ክርስቶስ ደግሞ ፍለጋውን እንድትከተሉ ምሳሌ ትቶላችሁ ስለ እናንተ መከራን ተቀብሎአልና›› ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ እንደጻፈልን (1ኛ ጴጥ 2፡21) እርሱ ንጹሕ ባሕርይ ሲሆን ወደ መጥምቁ ቅዱስ ዮሐንስ ዘንድ ወደ ዮርዳኖስ በመሄድ ለተጠመቅን ለእኛ ለተነሣሕያን ለሁላችን አብነት የሆነን መድኃኒታችን ስለእኛ ሞቷልና ሞቱን እናስብ ዘንድ ኑ በቤቱ ተሰብስበን እናልቅስለት፡፡ መታሰያውንም እናድርግለት፡፡ ጌታችን ሞቶ ተቀብሮ ካረገ በኋላ ለቅዱሳን ሐዋርያትና ለቅዱሳን አባቶቻችን ለእነ አቡነ መባዓ ጽዮን፣ ለእነ አቡነ ዘርዐ ቡሩክ እንደነገራቸው የሞቱን መታሰቢያ የሚያደርግ ኃጠአተኛ እንኳ ቢሆን ሲኦልን አያያትም፡፡ የመድኃኔዓለምን የሞቱን መታሰቢያ የሚያድርግ ቢኖር ሲኦል ራሷ አፍ አውጥታ ‹‹ይህችን ነፍስ ወደኔ አታምጡብኝ›› ብላ ትጮሃለች እንጂ ችላ አትቀበለውም፡፡ የጌታችን ወዳጆቹ ዮሴፍ ኒቆዲሞስ በድርብ በፍታና በመቶ ወቄት ሽቱ ገንዘው በሐዲስ መቃብር ሊቀብሩት ቢሉ ጌታችን ያን ጊዜ ዐይኑን ክፍቶ ‹‹በሰውነቴ መዋቲ ብሆን በመለኮቴ ሕያው ነኝ እንጂ ምነው እንደ እሩቅ ብእሲ ዝም ብላችሁ ትገንዙኛላችሁን?›› አላቸው፡፡ ይህን ጊዜም ዮሴፍ ኒቆዲሞስ በታላቅ ድንዳጤ ሆነው ‹‹አቤቱ ጌታችን ሆይ! እንግዲያስ ምን እያልን እንገንዝህ?›› አሉት፡፡ መድኃኒታችንም እንዲህ እያላችሁ ገንዙኝ አላቸው፡- ‹‹ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተወልደ እማርያም እምቅድስት ድንግል ተሣሃለነ እግዚኦ፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተጠምቀ በዮርዳኖስ ወተሰቅለ ዲበ ዕፀ መስቀል ተሣሃለነ እግዚኦ፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ቅዱስ ኃያል ቅዱስ ሕያው ዘኢይመውት ዘተንሥአ እሙታን አመ ሣልስት ዕለት ዐርገ በስብሐት ውስተ ሰማያት ወነበረ በየማነ አቡሁ ዳግመ ይመጽእ በስብሐት ይኰንን ሕያዋነ ወሙታነ ተሣሃለነ እግዚኦ› እያላችሁ ገንዛችሁ ቅበሩኝ አላቸው፡፡›› ከዚህም በኋላ መድኃኒታችን ለወዳጆቹ ለ12ቱ ሐዋርያት፣ ለ72ቱ አርድእት፣ ለ36ቱ ቅዱሳት አንስት ‹‹እስከ ሦስት ቀን እነሣላችኋለሁ እዘኑ አልቅሱ፣ እህል ውኃ አትቅመሱ በሏቸው›› ብሎ ለዮሴፍና ለኒቆዲሞስ አክፍሎት አስተማራቸው፡፡

🔴#ስንክሳር መጋቢት27 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት 27 በዚች ቀን #ጌታችን_መድኃኒታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ ስለ ዓለም ድኅነት በሥጋ ተሰቀለ፣ የመነኰሳት ሁሉ አባት የሆነ የከበረ አባት #ታላቁ_አባ_መቃርስ አረፈ፣ የኢትዮጵያ ንጉሥ #ሰማዕት_ገላውዲዎስ አንገቱን የተቆረጠበት ቀን ነው። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #መድኃኔዓለም መጋቢት ሃያ ሰባት በዚችም ቀን የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ዓለም ድኅነት በሥጋ ተሰቀለ። ፈጣሪዋ በዕንጨት መስቀል ላይ ተዘርግቶ ተሰቅሎ በአየችው ጊዜ ፀሐይ ጨለመች እርሱም ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም የነሣትን ለባዊት ነባቢት የሆነች ነፍሱን ከሥጋው ለያት ሐዋርያ ጴጥሮስ በሥጋ ምውት ሲሆን በመለኮት ሕያው ነው እንዳለ ነፍሱ ከመለኮት ሳትለይ ከሥጋ ተለየች በዚያ ጊዜ ሥጋ ከመለኮት ሳትለይ በዕንጨት መስቀል ላይ ተሰቅሎ ነበር። እንዲሁም ነፍስ ከመለኮት ጋራ አንድ ሁና እሥረኞች ነፍሳትን ትፈታቸው ዘንድ ወደሲኦል ወረደች። መድኃኔዓለም ክርስቶስ ስለ ዓለም ሁሉ ድኅነት በሥጋ ተሰቅሏልና ሞቱን በአንክሮ እናዘክር ዘንድ የልቡናችን ዐይን ወደ ቀራንዮ እናንሳ! እነሆ ክፉዎች አይሁድ ሰይጣን ልባቸውን አስቶታልና እንደ ወረንጦና እንደ ወስፌ እንደመርፌም ያለ 300 እሾህ ያለው ስረወጽ አድርገው አክሊል ሠርተው ከፍላት አግብተው በጉጠት አንስተው ‹ኢየሱስ ናዝራዊ ንጉሥ ነህ ዘውድ ይገባሃል› ብለው በራሱ ላይ ደፉበት፡፡ ለአክሊለ ሦኩም 73 ስቁረት ነበረው፡፡ እራሳቸው እንደ መሮ፣ ወርዳቸው እንደ ሞረድ 4 ማዕዘን አሠርተው ቁመታቸውን ክንድ ከስንዝር፣ ስለታቸውን እንደ ወስፌ አድርገው 73 ችንካር ሠርተው በ73ቱ ስቁረት አግብተው በጌታችን በራሱ ላይ ቢመቱበት ሥጋ ለሥጋ ገብቶ መሐል ልቡን ወጋው፡፡ አክሊለ ሦኩን በራሱ ላይ አድርገው ሲያበቁ ከቤት ወደ አደባባይ እያመላለሱ ‹‹ንጉሥ ሆይ!...›› እያሉ ምራቃቸውን እየተፉበት ተዘባበቱበት፡፡ መስቀል አሸክመው ከሊቶስጥራ እስከ ቀራኒዮ ድረስ እያዳፉ ሲወስዱት 136 ጊዜ በምድር ላይ ጣሉት፡፡ ከኋላ ያሉት ‹‹ፍጠን›› እያሉ ገፍትረው ይጥሉታል፣ ከፊት ያሉት ደግሞ ‹‹ምን ያስቸኩልሃል?›› እያሉ መልሰው ገፍትረው ይጥሉታል፡፡ ከዚህ በኋላ ክፉዎች አይሁድ ቁመታቸውን ክንድ ከስንዝር ስለታቸው ደግሞ እንደ ወስፌ የሆኑ 5 ችንካሮችን ሠርተው ሳዶር በሚባለው ችንካር ቀኝ እጁን፣ በአላዶር ግራ እጁን፣ በዳናት ሁለት እግሮቹን፣ በአዴራ መሐል ልቡንና በሮዳስ ደረቱን ቸንክረው የአዳም ራስ ቅል ባለበት ቀራኒዮ አደባባይ ላይ ሰቅለውታል፡፡ ክፉዎች አይሁድ መድኃኔዓለም ክርስቶስን እንደያዙት የኋሊት አስረው አፍንጫውን 25 ጊዜ ቢመቱት ደሙ በመሬት ላይ እንደ ውኃ ፈሰሰ፡፡ ከጌቴሴማኒ እስከ ሐና ቤት ድረስ አስረው የፊተኞቹ ሲጎትቱት የኋለኞቹ እየለቀቁት የኋለኞቹም በተራቸው ሲጎትቱት የፊተኞቹ ይለቁታል፡፤ እንዲህ እያደረጉ 65 ጊዜ ከመሬት ጋር አጋጭተውታል፡፡ ሳውል በእግሩ ሲረግጠው ጌታችን ‹‹መመለስህ ላይቀር ለምን ትረግጠኛለህ?›› ቢለው ስለዚህ ንግግርህ ብሎ ሳውል 440 ጊዜ አስገረፈው፡፡ ክፉዎች አይሁድ መድኃኒታችንን በሁለት ግንዶች መካከል አድርገው 65 ጊዜ ከግንዱ ጋር አጋጩት፡፡ ቀያፋ በሚመረምረው ጊዜ ጌታችን ‹‹አምላነቴን አንተው ራስህ ተናገርኽ›› ቢለው አይሁድ በእጃቸው ሲመቱት እጃቸውን ቢያማቸው ድንጋይ ጨብጠው 120 ጊዜ ፊቱን ጸፉት፡፡ አይሁድ ወደ ጲላጦስ ዘንድ ሲወስዱት ‹‹ምናልባት ጲላጦስ ባይፈርድበት እንኳ እንዳይቆጨን›› ብለው 305 ጊዜ በሽመል ደብድበውታል፡፡ በአምላክነቱ ቻለው እንጂ የአንዱ ምት ብቻ በገደለው ነበር፡፡ በርባን የይሁዳ የሚስቱ ወንድም (አማቹ) ስለነበር እርሱ እንደፊታለትም ከዋጋው ከ30ው ብር ጋር አብሮ ተደራድሮበት ነበር፡፡ ሰይጣን ልባቸውን ለክፋት ያስጨከናቸው ክፉዎች አይሁድ በጲላጦስ አደባባይ የጌታችንን ፂሙን 80 ጊዜ ነጭተውታል፡፡ ጲላጦስ እንደ ሕጋቸው 41 ብቻ ገርፈው እንዲለቁት ቢያዝም ክፉዎች አይሁድ ግን ጌታችንን ሲገርፉት ‹‹አሠቃቂ ግርፋቱን አይተን ልባችን እንዳይራራ›› ብለው ሰንጠረዥ ገበጣ ሰርተው ሲጫወቱ አንዱ ተነስቶ እስከ 60 እና 70 ድረስ ይገርፍና ሲደክመው ‹‹ቆጠራችሁን?›› ብሎ ይጠይቃል፡፡ ‹‹አልቆጠርንም›› ሲሉት ከድካሙ የተነሣ ‹‹እኔው ልግረፍ እንደገና እኔው ልቁጠር›› ብሎ ትቶት ሲቀመጥ ሌላኛው ይነሣና እንደዛኛው ሁሉ በተራው 60 እና 70 ይገርፈዋል፡፡ ሁሉም እንዲህ እያሳሳቱ የራሳቸውን ሕግ እየተላለፉ አይሁድ ጌታችንን ሥጋው አልቆ አጥንቱ እንደበረዶ ነጭ ሆኖ እስኪታይ ድረስ 6666 ጊዜ ጽኑ ግርፋትን ገረፉት፡፡ በእነዚህ ሁሉ ግርፋቱ ወቅት 366 ጊዜ ሥጋው ተቆርሶ መሬት ላይ ወድቋል፡፡ የመድኃኔዓለም ወገኖች ሆይ! የጌታችን ሞቱ በፈቃዱ መሆኑንና የትዕግሥቱን ብዛት አይተን እናደንቅ ዘንድ ከመጻሕፍት ጠቅሰን እንነግራችኋለን፡፡ አይሁድ ጌታችን አብርሃም ሳይወለድ በፊት እርሱ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በአንድነት በሦስትነት የሚመሰገን አምላክ መሆኑን ቢነግራቸው ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፡፡ እሱ ግን ጊዜው ገና ነበርና ተሰውሮአቸው በመካከላቸው አልፎ ሲሄድ በፍጹም አላዩትም ነበር፡፡ በቅዱስ ወንጌል ላይ እንዲህ ተብሎ እንደተጻፈ፡- ‹‹አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤት አደረገ፥ አየም ደስም አለው። አይሁድም:- ገና አምሳ ዓመት ያልሆነህ አብርሃምን አይተሃልን? አሉት። ኢየሱስም:- እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ አላቸው። ስለዚህ ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፤ ኢየሱስ ግን ተሰወራቸው ከመቅደስም ወጥቶ በመካከላቸው አልፎ ሄደ፡፡›› ዮሐ 8፡56-59፡፡ ዳግመኛም በዮሐንስ ወንጌል ላይ እንደተጻፈው አይሁድ መድኃኔዓለምን ሊይዙት የጦር መሣሪያቸውን ሰብስበው ወደ ጌቴሴማኒ በመጡ ጊዜ ‹‹ማንን ትፈለጋላችሁ?›› ቢላቸው ‹‹የናዝሬቱን ኢየሱስን እንፈልጋለን›› ሲሉት ‹‹እኔ ነኝ›› ቢላቸው ከአንደበቱ የወጣውን መለኮታዊ ቃል ብቻ መቋቋም አቅቷቸው መሬት ላይ ወድቀው ተዘርረዋል፡፡ ይህም ክስተት በተደጋጋሚ ተከስቷል፡፡ (ዮሐንስ ወንጌል ላይ ምዕራፍ 18 ከቁጥር አንድ ጀምሮ ይመለከቷል፡፡) እናም የጌታችን ሞቱ በፍጹም ፈቃዱ ባይሆን ኖሮ በጌቴሴማኒ ሊይዙት የመጡት ክፉዎች አይሁድን እንደመጀመሪያው ሁሉ በተሠወራቸው ነበር አሊያም ከአንደበቱ በሚወጣው አምላካዊ ቃሉ ብቻ ባጠፋቸው ነበር፡፡ በመጨረሻ ግን ጌታችን ወደዚህች ምድር የመጣበትን ዓላማ ይፈጽም ዘንድ እንዲገድሉት በፈቃዱ ራሱን አሳልፎ ቢሰጣቸው ያን ሁሉ እጅግ አሠቃቂ መከራ አደረሱበትና ለመስቀል ሞት አበቁት፡፡ ወዮ ለዚህ ለመድኃኒዓለም ፍጹም ትዕግስት አንክሮ ይገባል! ዓለምን በመዳፉ የያዘ አምላክ በአይሁድ እጅ እንደሌባ ተያዘ፡፡ ሠራዊተ መላእክት ለምሥጋና በፊቱ የሚቆሙለት መድኃኔዓለም እርሱ ሊፈረድበት በፍርድ አደባባይ ቆመ፡፡ በእስራት ያሉትን የሚፈታ እርሱ በብረት ችንካር ተቸነከረ፡፡ ሰማይን በከዋክብት ምድርም በአበባ ያስጌጠ እርሱ ግን የእሾህ አክሊል በራሱ ላይ ደፋ፡፡ ዓለሙን ሁሉ በቸርነቱ የሚመግብ እርሱ ተጠማሁ አለ፡፡ ወዮ የመድኃኔዓለም የማዳኑ ምሥጢር ምንኛ ድንቅ ነው!!! ለዚህ ባሕርይው አንክሮ ይገባል፡፡

🔴#ስንክሳር መጋቢት_26 አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ ስድስት በዚህች ዕለት የክብር ባለቤት #ጌታችን_ኢየሱስ_ክርስቶስ የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ፣ የሐዲስ ኪዳንንም የቊርባን ሥርዓት አሳያቸው፣ የከበረችና የተመሰገነች #ድንግሊቱ_ኢዮጰራቅስያ አረፈች። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ምሴተ_ሐሙስ መጋቢት ሃያ ስድስት በዚህች ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችን የደቀ መዛሙርቱን እግር አጠበ እንዲህም አላቸው። እናንተም ለባልንጀሮቻችሁ እንዲሁ አድርጉ። ደግሞ የሐዲስ ኪዳንን የቊርባን ሥርዓት አሳያቸው። አሁንም በዚች ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችንን ለአይሁድ ይሁዳ አሳልፎ ሰጠው። ነቢያት ትንቢት እንደተናገሩ የሽያጩን ዋጋ ሠላሳ ብር ተቀበለ። ይቅርታው ቸርነቱ ከሁላችን የክርስቲያን ወገኖች ጋር ለዘላለሙ ይኑር አሜን። ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #ቅድስት_ኢዮዸራቅስያ በዚህች ቀን የከበረችና የተመሰገነች ድንግሊቱ ኢዮጰራቅስያ አረፈች። ይችም የተቀደሰች ብላቴና የንጉሥ አኖሬዎስ ዘመዱ ለሆነ በሮሜ ከተማ ከቤተ መንግሥት የአንድ ታላቅ መኰንን ልጅ ናት። የሚሞትበትም ቀን በደረሰ ጊዜ እርሷን ልጁን ለንጉሥ አኖሬዎስ ይጠብቃት ዘንድ አደራ ሰጠው። አባቷም ካረፈ በኋላ ለአንድ ታላቅ መኰንን ልጅ ንጉሥ አኖሬዎስ አጫት። በዚያም ወራት እናቷ የመሬቷን ግብር ልትቀበል በሏ የተወላትን የአትክልት ቦታዎቿም ያፈሩትን ይችንም ቅድስት ብላቴናዋን ከእርሷ ጋር ወሰደቻት። ዕድሜዋ ዘጠኝ ዓመት ሁኖ ሳለ አስከትላት ወደ ግብጽ ሔደች። ወደ ግብጽ አገርም በደረሱ ጊዜ ሥራቸውን እስከሚፈጽሙ በአንድ የደናግል ገዳም ውስጥ ኖሩ። በዚያ ገዳም ውስጥ የሚኖሩ ደናግል ለገድል የተጸመዱ ናቸው። የሥጋ መብልን ቅባትም ቢሆን ጣፋጭ ፍሬዎችንም ምንም ምን አይበሉም ወይንም ቢሆን ከቶ አይቀምሱም ያለ ምንጣፍም በምድር ላይ ይተኛሉ። ኢዮጰራቅስያም በዚያ ገዳም ውስጥ መኖርን ወደደች ገዳሙን ከምታገለግል መጋቢዋ ጋር ተፋቅራለችና። መጋቢዋም አንቺ ከዚህ ገዳም ወጥተሽ ተመልሰሽ እጮኛሽን ላትፈልጊ ቃል ግቢልኝ አለቻት ኢዮጰራቅስያም በዚህ ነገር ቃል ገባችላት። እናቷ ሥራዋን በፈጸመች ጊዜ ወደ አገርዋ ልትመለስ ወደደች ልጅዋ ግን እኔ የዚህን የኃላፊውን ዓለም ሙሽርነት ስለማልሻ ራሴን ለክብር ባለቤት ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰማያዊ ሙሽራ ሰጥቻለሁ ብላ ከእርሷ ጋር መመለስን አይሆንም አለች። ብላቴናዋ ከእርሷ ጋር እንደማትመለስ በተረዳች ጊዜ ገንዘቧን ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች መጽውታ ከልጁዋ ጋር በዚያ ገዳም ብዙ ዘመን ኑራ ከዚያ በኋላ አረፈችና በዚያው ቀበርዋት። ንጉሥ አኖሬዎስም የኢዮጰራቅስያ እናቷ እንደሞተች ሰምቶ ለአጫት ያጋባት ዘንድ ኢዮጰራቅስያን እንዲአመጧት መልእክተኞችን ላከ። ቅድስቲቱም ንጉሥ ሆይ እወቅ የክብር ባለቤት ለሆነ ለሰማያዊ ሙሽራ ለጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ እኔ ራሴን ሰጥቻከሁና ቃል ኪዳኔን መተላለፍ አይቻለኝም ብላ ወደ ንጉሡ ላከች። ንጉሥ አኖሬዎስም መልእክቷን በሰማ ጊዜ አደነቀ ስለርስዋም አለቀሰ እርስዋ በዕድሜዋ ታናሽ ብላቴና ናትና። ይህች የከበረች ኢዮጰራቅስያ ግን ታላቅ ተጋድሎን ተጋደለች ለመንፈሳዊ ሥራ እጅግ የተጠመደች ሆነች በየሁለት ቀን ሁለት ሁለት ቀን እያከፈለች መጾም ከዚያም በየሦስት ቀን ሦስት ሦስት ቀን ትጾም ጀመር ከዚያም በየሰባት ቀን ሰባት ሰባት ቀን የምትጾም ሆነች። በተለየች በከበረች አርባ ጾም ምንም ምን የምትበላ አልሆነችም። ሰይጣንም በእርሷ ላይ ቀንቶ አስጨናቂ በሆነ አመታት እግርዋን መታት ብዙ ቀኖችም በሕማም ኖረች ከዚያም እግዚአብሔር ራርቶላት ከደዌዋ አዳናት በሽተኞችንም ታድናቸው ዘንድ በሽተኞችን የምትፈውስበትን ሀብት ሰጣት። ለእመ ምኔቷና ለእኀቶቿ ደናግል በመታዘዝ ታገለግላቸው ነበር በእኀቶች ደናግል ሁሉ ዘንድ የተወደደች ናት። በአንዲት ዕለትም እመ ምኔቷ አክሊላትንና አዳራሾችን እንደ አዘጋጁ ራእይን አየች እርሷም እያደነቀች ከልጆቼ ለማን ይሆን ይህ የሚገባት ስትል እሊህ አክሊላትና አዳራሾች የተዘጋጁላት ለልጅሽ ለኢዮጰራቅስያ ነው እርሷም ወዲህ ትመጣለች አሏት። ይህንንም ራእይ ለደናግሎች ነገረቻቸው እግዚአብሔርም ከዚህ ዓለም መከራ ሊያሳርፋት እስከ ወደደበት ቀን ለኢዮጰራቅስያ እንዳይነግሩዋት አዘዘቻቸው። ከዚህ በኋላ በሆድ ዝማ ሕማም ጥቂት ታመመች ሁሉም ደናግል ከእመ ምኔቷ ጋር ወደ እርሷ ተሰበሰቡ ያቺ ቃል ኪዳን ያስገባቻት የምትወዳት መጋቢዋም መጣች በእግዚአብሔርም ዘንድ እንድታስባቸው ለመንዋት እርሷም በጸሎታቸው እንዲአስቧት ለመነቻቸው ከዚያም አረፈች ። የተቀደሰችና የተከበረች እርሷን እኅታቸውን አጥተዋታልና ደናግሉ እጅግ አዝነው አለቀሱ። ከዚህም በኋላ የምትወዳት የገዳሙ መጋቢ የነበረች አረፈች ከእርስዋም በኋላ እመ ምኔቷ ጥቂት ቀን ታመመች ደናግሎችንም ሰብስባ በላያችሁ የምትሾሙትን እመ መኔት ምረጡ ስለ እኔ ኢዮጰራቅስያ ለምናለችና እኔ ወደ ጌታዬ ኢየሱስ እሔዳለሁ አሁን ግን ደጁን በላዬ ዘግታችሁ ሔዱ አለቻቸው እነርሱም እነዳዘዘቻቸው አደረጉ። በማግሥቱም ማለድ ብለው ሲደርሱ አርፋ አገኟት፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳኑ ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

🔴#ስንክሳር መጋቢት_25 #ሐዋርያ_አንሲፎሮስ አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም መጋቢት ሃያ አምስት በዚች ቀን ከሰባ ሁለቱ አርድእት አንዱ የከበረና የተመሰገነ ሐዋርያ አንሲፎሮስ አረፈ። ይህም ከእስራኤል ልጆች ከቢንያም ነገድ ነው ወላጆቹም የኦሪትን ሕግ የሚጠብቁ ናቸው እርሱም ሥራዎቹን በአየ ጊዜ ትምህርቶቹንም በሰማ ጊዜ ጌታችንን ተከተለው። ድንቅ የሆኑ ተአምራቶችን እየተመለከተ ጥቂት ቀን ተቀመጠ ጌታችንም በሀገረ ናይን የመበለቲቱን ልጅ በአስነሣው ጊዜ ከዚያ ነበረ። ይህን አይቶ ወዲያውኑ አመነ ሌላ ምልክት አልሻም ብልጭ ብልጭ ሲል የነበረ የአይሁድ የሕግ ፋና ትቶ ወደ ዕውነተኛ ፀሐይ ወደ ጌታ ኢየሱስ ቀርቦ ደቀ መዝሙሩ ሆነው እንጂ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ከዐረገ በኋላ በጽዮን አዳራሽ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስ በወረደ ጊዜ ከሐዋርያት ጋራ የመንፈስ ቅዱስን ጸጋ ተቀብሎ ሐዋርያትንም በመከተል በብዙ አገሮች ውስጥ አስተማረ። ሐዋርያትም በሀገረ አቴና ኤጲስቆጶስ አድርገው ሾሙት በውስጥዋም ወንጌልን በመስበክ ብዙዎችን አሳመነ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው በትምህርቱና በምክሩ ዕውቀት እንዲአድርባቸው አደረጋቸው በትምህርቱም ከደዌ ሥጋ ከደዌ ነፍስ ፈወሳቸው። ተጋድሎውንም በፈጸመ ጊዜ በሰላም አረፈ በድል አድራጊነትም የክብር አክሊል ተቀበለ። መላ ዘመኑ ሰባ ዓመት ነው በአይሁድ ሕግ ሃያ ዘጠኝ ዓመት በክርስትና ሕግ አርባ አንድ ዓመት ኖረ። እነሆ የከበረ ሐዋርያ ጳውሎስም በመልእክቶቹ አስታውሶታል ሰላምታም አቅርቦለታል። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12

በምድርም የፈታኸው በሰማይ የተፈታ ይሁን፤ አንተን የሰማ እኔን መስማቱ ነው፤ የላከኝ አባቴንም መስማቱ ነው፡፡ አንተን እንቢ ያለ እኔን እንቢ ማለቱ ነው፡፡ የላከኝ አባቴንም እንቢ ማለቱ ነው፡፡ ይህን ሥልጣን ቀድሞ ለሐዋርያት ሰጥቻቸው ነበር፡፡ ከሐዋርያትም ሹመትን የተቀበለ ጳጳሱ ትሾምና ትሽር፣ ትተክልና ትነቅል ዘንድ ሥልጣንን ሰጠህ፡፡ ይህንንም ያደረኩልህ የጳጳሱን ቃል በመናቅ አይደለም፡፡ የፍቅሬን ጽናት ባንተ እገልጽ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ሐዋርያት ወዳልደረሱበት ሕዝብ በመምህርነት እልክህ ዘንድ በሚካኤል ቃል አዲስ ስም አወጣሁልህ፡፡ አንተም በማናቸውም ሥራ ከእነርሱ አታንስም፣ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጌሃለሁና፡፡ ሰውን ሁሉ በእኔ ስም እያስተማርክ ታሳምን ዘንድ፣ ሚካኤልም ባሰብከው ሥራ ሁሉ ረዳት ይሁንህ፣ ሁል ጊዜ ካንተ አይለይም፤ በምትሄድበትም ጎዳና ሁሉ እርሱ መሪ ይሁንህ፤ እኔም ባለ ዘመንህ ሁሉ አልለይህም›› ካላቸው በኋላ ሰላምታ ሰጥቷቸው ዐረገ፡፡ ብፁዕ አባታችንም እጅ ነሥተው ‹‹ለእኔ ለኀጥኡ የማይገባኝ ሲሆን ይህን ሁሉ ጸጋ የጠኸኝ ስምህ በሰማይ በምድር የተመሰገነ ይሁን›› አሉ፡፡ ከዚያች ቀን ጀምሮ ሀብተ ኃይልን የተመሉ ሆኑ፡፡ ወደቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ሀብት ንብረት ሁሉ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጥተው ጨረሱ፡፡ ከዚያም ‹‹አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ›› ብለው ቤታቸውን እንደተከፈተ ትተው ወንጌልን ለማስተማር ወጡ፡፡ ጻድቁ አባታችን በሀገራችን ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ ሕዝቡን ከኃጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ፣ ከክህደት ወደ ኃይማኖት ስለመለሱት በዚህም የተነሣ ለኢትዮጵያውያን ብርሃን ተብለዋል፡፡ ✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞ #አባ_መቃርስ_ሊቀ_ዻዻሳት በዚህች ቀን በእስክንድርያ ለተሾሙ አባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሀምሳ ዘጠነኛ የሆነ ቅዱስ አባት የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አባ መቃርስ አረፈ። ይህም የከበረ አባት ሳብራ ከምትባል አገር ነው ከታናሽነቱ ጀምሮ ይህን አለም ንቆትቶ የምንኲስናን ልብስ ሊለብስ ወደደ። ወደ አስቄጥስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መነኰሰ። በተጋድሎም ተጠመደ ከእርሱም በጉ ስራዎችና ትሩፋቶች ተገለፀው ታዩ። ከእርሱ አስቀድሞ የነበረ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቆዝሞስ በአረፈ ጊዜ ኤጲስቆጶሳቱ ይሾሙት ዘንድ በአንድ ምክር ተስማምተው ለእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት አድርገው ያለ ፈቃዱ ሳይወድ በግድ ሾሙት። ወደ እስክንድርያም ይዘውት ሲሄዱ እግረ መንገዱን ከተወለደባት አገር ደረሰ እናቱም በዚያ በህይወት አለች እርሷም የዚህን የኃላፊውን አለም ክብር የምትጠላ እግዚአብሔርን የምትፈራ እውነተኛ ሰው ናት። ወደ ርሷም እንደመጣ ስለርሱ በሰማች ጊዜ ልትቀበለው አልወጣችም ። ነገር ግን እርሱ ራሱ እርሷ ወዳለችበት ቤት ገባ ተቀምጣም ትፈትል ነበር በሰላምታ ልትገናኘው ያልተነሳችው ያላወቀችው መስሎት እኔ እገሌ ልጅሽ አይደለሁምን ለምን ሰላምታ አትሰጪኝም ወይስ አላወቅሺኝም አላት። እርሷም እኔስ አውቄሀለሁ ራስህን ያላወቅህ አንተ ነህ በዚህ በሊቀ ጵጵስና ክብር ሆነህ ከማይህ ሞተህ ተገንዘህ ባይህ በወደድኩ ነበር ። ከአሁን በፊት የምትጠየቀው በራስህ ኃጢአት ብቻ ነበር ከዛሬ ጀምሮ ግን በምእመናን ሁሉ ኃጢአት ነው ብላ መለሰችለት። ከዚህ በኋላ ሁለቱም በአንድነት አለቀሱ ይህም እናቱ የተናገረችው ነገር በልቡ አደረ ስለ ራሱ ድኀነትና የምእመናኑንም ነፍሳቸውን ለማዳን መፃህፍትን በማስነበብ በመምከርና በመገሰፅ እያነቃ ሲታገል ኖረ። ደግሞ በእውነተኞች ካህናት ምስክርነት በቀር ካህናትንና ኤጲስቆጶሳትን ከመሾም የሚጠነቀቅና የሚጠበቅ ሆነ። ከቤተ ክርስቲያንም ገንዘብ የማይገባውን ምንም ምን አይውስድም ነበር። ኤጲስቆጶሳትንና ቀሳውስትን ወገኖቻቸውን ጥቅም በአላቸው በቅዱሳት መፃህፍት ቃል በመምከር ይጠብቋቸው ዘንድ ያዛቸው ነበር። በሰላምና በፀጥታ ሆኖ በማርቆስ ወንበር ሀያ አመት ኖረ በሹመቱም ወራት አብያተ ክርስቲያናት ተቃንተው ተስተካክለው ያለ መቋረጥም በፀሎትና በቅዳሴ ተሰርተው አገልግሎት ሲሰጡ ኖሩ። ከዚህም በኃላ በሰላም አረፈ፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በከበሩ ቅዱሳን ጸሎት ይማረን በረከታቸውም ከእኛ ጋር ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡https://t.me/finotebirhan12