ፍኖተ ብርሃን ዘ ቅድስት አርሴማ
Відкрити в Telegram
ይህ በግራር ደ/አባይ ቅድስት አርሴማ ቤ/ክ ፍኖተ ብርሀን ሰንበት ት/ቤት የተዘጋጀ :- ለምዕመናን : ትምህርትን , ዝማሬዎችን , ኪናዊ ዝግጅቶችን, የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ዜናዎችንና በአላትን(ንግስ, ልዮ ልዮ የሰርክ ጉባኤያት ..ወዘተ) በምን መልኩ እንደተከበሩ ለምዕመናን ተዘጋጅቶ የሚተላለፍበት ገፅ ነው።
Показати більше638
Підписники
-224 години
-57 днів
-1130 день
Архів дописів
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፰ (8) ቀን።
❤ እንኳን ለአስቄጥስ ገዳም አበ ምኔት የወፍጮ ድንጊያ ለሚሰራው ለአውሎጊስ ተውሶ ለምኖ ከእግዚአብሔር ወርቅ እንዲያገኝ ላደረገው ለታላቁ ለገድለኛው አባት #ለአባ_ዳንኤል ለዕረፍት በዓልና ስንሑት ከሚባል አገር ለሆነ #ለቅዱስ_ዮሐንስ ለምስክርነቱ ፍጻሜ ለዕረፍቱ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡ፦ #ከቅዱስ_ዮሐንስ ማኅበር #ከሁለት_መቶ_ሃያ_ሁለት_ሰማዕታት፣ #ከሱሲስና+ከንቡረ_እድ_ማትያስ በምስክርነት ራሳቸውን ከተቆረጡ፣ #ከከበረ_ታጋዳ_ማክሲምስ ምስክር ሁኖ ከዐረፈ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ዳንኤል፦ ይህም ቅዱስ ዕውነተኛ ንጹሕ ፍጹም ነው ዜናው በሁሉ ቦታ በተሰማ ጊዜ ሹመት ያላት ቅድስት አንስጣስያ የመኳንንቶችን ልብስ ለብሳ ወደርሱ መጥታ ከእርሱ መነኰሰች። በእርሱ አቅራቢያም ሃያ ስምንት ዓመት በበዓት ውስጥ ኖረች እርሷ ሴት እንደሆነች ማንም አላወቀም።
❤ ይህም ቅዱስ ስሙ አውሎጊስ የሚባለውን ሰው አየው ይህም አውሎጊስ የወፍጮ ድንጋይ እየወቀረ ለግርሽ እየሸጠ ሁል ጊዜ በመጠኑ እየተመገበ ለድኆችንና ጦም አዳሪዎችን ይመግባቸዋል የተረፈውንም ፍርፋሪ ለውሾች ይጥላል ለነገ ብሎ ምንም አያሳድርም። አባ ዳንኤልም ይህን መልካም ሥራውን አይቶ በርሱ ደስ አለው እጅግም አማለው ለአውሎጊስም የዚህን ዓለም ብልጽግና እንዲሰጠውና ለድኆች የሚመጸውተው እንዲጨመርለት ወደ እግዚአብሔር ለመነ።
❤ ለአውሎጊስም ዋስ ሆነው የሚወቅረውንም ደንጊያ ሲፈነቅል በሸክላ ዕቃ የተደፈነ ወርቅን አገኘ ወደ ከቊስጥንጥንያ ከተማ ሒዶ የንጉሥ የሠራዊት አለቃ ሁኖ ተሾመበት የሚሠራውንም የቀደመ በጎ ሥራውን ተወ። አባ ዳንኤልም ስለርሱ ሰምቶ ወደርሱ በሔደ ጊዜ የንጉሥ ሠራዊት አለቃ ሆኖ በፈረስ ላይም ተቀምጦ ብዙ ሠራዊት አጅቦት እርሱም በትዕቢት ተመልቶ የቀድሞ በጎ ሥራውንና ለድኃ መመጽወቱንም ትቶ አገኘው። አባ ዳንኤልም አይቶ አዘነ ስለርሱ በመለመኑ ተጸጸተ።
❤ ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለፍርድ እንደ መጣ አባ ዳንኤልንም እንዲሰቅሉት ሲያዝ የአውሎጊስንም ነፍስ ከእርሱ እንዲሹ በእርሱ ምክንያት ጠፍቷልና የከበረች ድንግል እመቤታችን ማርያምም የክብር ባለቤት ጌታችንን ልጅዋ ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ አባ ዳንኤል እንደ ለመነችው በሌሊት ራእይ አባ ዳንኤል ራሱ አየ። በነቃም ጊዜ ደነገጠ አውሎጊስንም ወደ ቀድሞ ሥራው ይመልሰው ዘንድ በጸሎትና በምሕላ በመትጋት ወደ እግዚአብሔር እየለመነ ግብር ገባ ሱባኤ ያዘ። ከዚህ በኋላ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ተገለጸለት "በፍጥረቱ ላይ በሚያደርገው በእግዚአብሔር ፍርድ ውስጥ ለመግባት በመድፈሩ ገሠጸው"።
❤ በዚያንም ወቅት አውሎጊስን የሾመው ንጉሥ ሞተ ሌላ ንጉሥም ነገሠ በአውሎጊስም ላይ ተነሥቶ ገንዘቡን ሁሉ ወረሰ። ደግሞም ሊገድለው ፈለገው አውሎጊስም ነፍሱን ለማዳን ከንጉሡ ሸሽቶ ወደ አገሩ ደረሰ እንደ ቀድሞውም ደንጊያ ይወቅር ጀመረ አባ ዳንኤልም ወደርሱ ተመልሶ ስለርሱ ያየውን ሁሉ ስለ ርሱም እንደሰቀሉትና ነፍሱንም ከእርሱ እንደፈለጉ ነገረው።
❤ በዚህ በአባ ዳንኤል የትንቢት መንፈስ አድሮበት ነበር ከእርሱም ብዙዎች ታላላቅ ታምራት ተገለጡ። መናፍቃን አርዮሳውያንም ከቀናች ሃይማኖት ሊያወጡት በፈለጉ ጊዜ እንቢ አለ። ያቺንም የክህደት ደብዳቤ ተቀብሎ ቆራረጣት የአርዮሳዊ ንጉሥ ወታደርም ይዞ ብዙ ሥቃይን አሠቃየው።
❤ በአንዲት ዕለትም ቅዱሳት ደናግል ወደ ሚኖሩበት ወደ ሲሐት ገዳም አባ ዳንኤልን ተመስሎ ሽፍታ ገባ። ደናግሉም በደስታ ተቀብለው እግሩቹን አጠቡ። እነርሱም አባ ዳንኤል እንደሆነ አምነው የወንበዴውን የእግር እጣቢ ውኃ በረከቱን ለማግኘት በላያቸው ረጩት። በዚያም አንድ ዐይኗ የታወረ ነበረች ውኃው በነካት ጊዜ ዐይኗ በርቶላት አየች። ወንበደውም አይቶ ደነገጠ ሥራውንም ገለጠ ንስሐ ገብቶም መነኰሰ በበጎ ገድል ሁሉ ተጠምዶ እግዚአብሔርን አገለገለው።
❤ ጌታችንም ከዚህ ዓለም ድካም ሊአሳርፈው በወደደ ጊዜ መልአኩን ልኮለት ከዓለም የሚወጣበትን ጊዜ አስረዳው። መነኰሳቱንም ሰብስቦ በበጎ ሥራ እንዲጸኑ አዘዛቸው አጽናናቸው አረጋጋቸውም። ከዚህም በኋላ ግንቦት 8 ቀን በሰላም ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ በአባ ዳንኤል ጸሎት ይማረን በረከቱም ትድረሰን ለዘለዓለሙ አሜን።
❤ #ቅዱስ_ዮሐንስ፦ የዚህም ቅዱስ የአባቱ ስም መቃርስ የእናቱም ስም ሐና ነው። እርሱም የአባቱን በጎች ሲጠብቅ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦ የብርሃን አክሊልን አሳየው። "እነሆ ተጋድሎ ተዘርግቶ በክርስቶስ ስም ለሚጋደል አክሊላት ተዘጋጅተው ሳሉ አንተ ለምን ከዚህ ተቀመጥክ። አሁንም ወደ አገረ አትሪብ ሒድ የክብር ባለቤት ስለሆነ ስለ ክርስቶስ ስም ተጋደል" አለው። ከዚያም ሰላምታ ሰጥቶት ከእርሱ ዘንድ ሔደ።
❤ በዚያም ወቅት ቅዱስ ዮሐንስ ተነሣ እናቱንና አባቱንም ተሰናብቶ ወደ አትሪብ ከተማ ሔደ መኰንኑንም በውሽባ ቤት አገኘውና በወጣ ጊዜ በፊቱ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ። መኰንኑም ለአንድ ወታደር ሰጥቶት ምናልባት ከምክሩ ተመልሶ ቢታዘዝለት አስቦ እንዲአባብለው ወታደሩን አዘዘው። ከዚህ በኋላ መኰንኑ ወደ ሥራው ሔደ ወታደሩም ቅዱስ ዮሐንስን ወደ ቤቱ ወሰደው። ቅዱሱም ተአምራትን አደረገ ያ ወታደርም በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ አመነ። መኰንኑም በተመለሰ ጊዜ ያ ወታደር በክብር ባለቤት በጌታችን በመኰንኑ ፊት ታመነ የሰማዕትነትንም አክሊል ተቀበለ።
❤ ከዚህም በኋላ ቅዱስ ዮሐንስን እንዲአሠቃዩት መኰንኑ አዘዘ በየአይነቱ በሆነ ሥቃይም አሠቃዩት። እግዚአብሔርም ያጽናውና ያስታግሠው መልአኩንም ልኮ ቊስሎቹን አድኖ ያለ ጉዳት በደኅና ያነሣው ነበር።
❤ ከዚህም በኋላ ወደ እንዴናው ከተማ ላከው በዚያም ታላቅ ሥቃይን አሠቃዩት። መኰንኑም ማሠቃየቱን በሰለቸ ጊዜ ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የሰማዕትነትንም አክሊል ግንቦት 8 ቀን ተቀበለ። የአቅፍሐሲ ዮልዮስም ሥጋውን ወስዶ ገነዘው ወደ አገሩ ስንሑትም ላከው። የአገሩ ሰዎች ሁሉም ወጥተው በፍጹም ደስታ ተቀበሉት ከማዕጠንት ጋራ እየዘመሩና እያመሰገኑ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አኖሩት ከሥጋውም ብዙዎች ድንቆች ተአምራት ተገለጡ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ ዮሐንስ በአማላጅነቱ ያድነን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት8 ስንክሳር።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለዮሐንስ_ጸጋዊተ_ምጽዋት_እዱ። ባዝግና ብርሃን ጽሩየ እስከ አጥርየ በዐውዱ። አመ አነዳሁ ዘሐቁ ወሌለዩ እምነ ድዱ። አፍሐመ እሳት ላዕሌሁ አንደዱ ወዕብን ቀይሕ ሥጋሁ በርደዱ"። #ሊቁ_አርከ_ሥሉስ (አርኬ) #የግንቦት_8።
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፰ (8) ቀን።
❤ እንኳን ለክብር ባለቤት #ለጌታችን_ለአምላካችን_ለመድኃኒታችን_ለኢየሱስ_ክርስቶስ_ለጥንት_ለዕርገቱ_በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ "#ሰላም_ለዕርገቱ_መድምም እንዘ ያንበለብል ጸዳሉ ግሩም"። ትርጉም፦ አስፈሪ ብርሃኑ እያንበለበለ (ቦግ ቦግ እያለ) ለተደረገ #ድንቅ_ዕርገቱ_ሰላምታ_ይገባል። #ሊቁ_አባ_ጊዮርጊስ_ዘጋስጫ በተአምኆ ቅዱሳን ላይ።
✝ ✝ ✝
❤ በዚች ዕለት የክብር ባለቤት ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእኛ በነሣው ሥጋ ከአባቱና ከመንፈስ ቅዱስ ጋራ ወደአለው የአንድነት አኗኗሩ ከሰማያት በላይ ያገረበት ሆነ።
❤ እርሱም በረቀቀ ጥበቡ በመከራው በሞቱና በመነሣቱ ሥራውን ከፈጸመ በኋላ አርባው ቀን ሲፈጸም በነፋሳት ክንፍ ላይ ሁኖ ዐረገ። ያን ጊዜ በኪሩቤል ላይ ተቀምጦ ወጣ በነፋሳትም ክንፎች ላይ ሁኖ ወጣ ያለው የዳዊት ትንቢት ተፈጸመ።
❤ በዚህም ዕርገቱ የሚያምኑበት በልዕልና ወደሚኖሩበት የሚዐርጉ መሆናቸው ተረዳ ተረጋገጠ ራስ በአለበት ሕዋሳት ሊኖሩ ይገባልና። አዳም አስቀድሞ በምድራዊ ርስቶች በሲኦልም እንደኖረ መኖርንም እንደቀደመ እንዲሁ ዳግማዊ አዳም ጌታ በመንግሥተ ሰማያት ርስት መኖርን ቀደመ።
❤ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ዕርገቱን ከትንሣኤው አከታታትሎ ወዲያውኑ አላደረገም መናፍቃን ዕርገቱ ምትሐት ናት ብለው እንዳያስቡ። ጌታችንም በረቀቀ ጥበቡ የደቀ መዛሙርቱን ተሽብሮ የነበረ ልቡናቸውን እያጽናና መነሣቱንም እያስረዳቸው ከትንሣኤው በኋላ አርባ ቀን ኖረ።
❤ በጌታችንም ዕርገት የቅዱስ ዳንኤል ትንቢት ተፈጸመ እንዲህ የሚል "ሌሊት በራእይ አየሁ እንሆ ታላቅ እንደ ሰው ልጅ የሆነ መጣ ዘመናትን ወደሚያስረጃቸው ደረሰ ከፊቱም አቀረቡት። የዘላለም አገዛዝ፣ ጌትነት፣ መንግሥት፣ የዘላለም ሥልጣን ተሰጠው ሕዝቡና አሕዛቡ ሁሉ መንደር መንድረው የሚኖሩትና ነገዱም ነገሥታቱም ሁሉ ይገዙለታል አገዛዙም የዘላለም አገዛዝ ነው መንግሥቱም የሚያልፍ የማይጠፋ ነዋሪ ነው"። ለእርሱም ምስጋና ይሁን ከቸር አባቱ ሕይወት ከሆነ መንፈስ ቅዱስም ጋር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ዐርገ እግዚአብሔር በይባቤ። ወእግዚእነ በቃለ ቀርን። ዘምሩ ለአምላክ ዘምሩ"። መዝ 46፥5-6። የሚነበበው ወንጌል ዮሐ 21፥12-15።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "ደለወኒ ዘአሕመምከኒ። ከመ አእምር ኵነኔከ። ይኄይሰኒ ሕገ አፉከ እምአእላፍ ወርቅ ወብሩር"። መዝ 118፥71-72። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ጢሞ 6፥7-ፍ.ም፣ ያዕ 1፥7-17 እና የሐዋ ሥራ 13፥1-13። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 6፥19-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የቅዱስ ባስልዮስ ቅዳሴ ነው። መልካም የጥንት የዕርገት በዓል፣ የአባ ዳንኤል የዕረፍት በዐልና የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፯ (7) ቀን።
❤ እንኳን #ለአገራች_ኢትዮጵያ_የመጀመርያውን ሊቀ ጳጳስ #አባ_ፍሬምናጦስ (አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃንን) ቀብቶ ለሾመው ለእስክንድርያ ሃያኛው ሊቀ ጳጳስ ለታላቁ አባት #ለሐዋርያዊ_ለቅዱስ_አባ_አትናቴዎስ ለዕረፍት መታሰቢያ በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ሐዋርያዊ_አባት_ቅዱስ_አትናቴዎስ፦ ይህም ቅዱስ ሐናፊ ከሚባል የእስላም ነገድና ከአረማውያን ተወላጅ ነው ይባላል። የተወለደው በ298ዓ.ም በእስክድርያ ነው። እርሱም ከመምህር ከሚማሩ ሕፃናት ጋራ እያለ እርስ በእርሳቸው በመጫወት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እየሠሩ ከእነርሱ ውስጥ ዲያቆናትን ኤጲስቆጶሳትንም ሲያደርጉ እሊያን የክርስቲያንን ልጆች አይቶ ጨዋታቸው አንድ ይሆን ዘንድ የክርስቲያንን ልጆች ለመናቸው። እርሱም "አንተ አረማዊ ነህና ከእኛ ጋራ አትደመርም" ብለው ከለከሉት እርሱም "ክርስቲያን እሆናለሁ" አላቸው እነርሱም ደስ ተሰኙበት። ያን ጊዜ ወስደው በሊቀ ጳጳሳት አምሳል አደረጉት ከበታቹም ወንበር አድረሰገው ይሰግዱለት ጀመር። በዚያ ጊዜም ሊቀ ጳጳሳት አባ እለእስክንድሮስ በዚያ አለፈ የክርስቲያን ልጆች ሲጫወቱ በአያቸው ጊዜ አብረውት ላሉ "ይህ ሕፃን ከፍ ከፍ ያለችና የከበረች ሹመትን ይሾም ዘንድ አለው" አላቸው።
❤ አባቱም በሞተ ጊዜ ወደ አባ እለእስክንድሮስ መጣ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቀው። ከዚህም በኋላ የአባቱን ገንዘብ ሁሉ ወስዶ ለድኆችና ለጦም አዳሪዎች ሰጥቶ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሕግ ሥርዓትንም ከአባ እለእስክንድሮስ ዘንድ እየተማረ ኖረ እርሱም ተወዳጅ ልጅ አደረገው። ከዚህም በኋላ ዲቁና ሾመው የመንፈስ ቅዱስንም ጸጋ የተመላ ሆነ።
❤ ስለ ቅዱስ አትናቴዎስ ወደ ቤተ ክርስቲያን አጠራር በተመለከተ ሩፊኖስ የተባለው የዚያ ክፍለ ዘመን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊ የሚከተለውን ጽፏል የእስክንድርያ ክርስቲያኖች የእስክንድርያ 17ኛ ፖትርያርክ የነበረውንና በዲዮቅልጥያኖስ ዘመን በሰማዕትነት ያረፈውን የተፍጻሜ ሰማዕት የቅዱስ ጴጥሮስን በዓል በየዓመቱ በታላቅ ሁኔታ ያከብሩ ነበር። በዚያን ጊዜ ፖትርያርክ የነበረው አባት እለእስክንድሮስ ከበዓሉ ፍጻሜ በኋላ በድንገት ወደ ባሕሩ ሲመለከት በዚያ የነበሩ ልጆች ጳጳስ፣ አጥማቂና ተጠማቂ እየሆኑ በባሕሩ ዳርቻ ሲጫወቱ ተመለከተ። መጀመሪያ የሕፃናት ጨዋታ ነው ብሎ አሰበ። ሁኔታቸውን እየቆየ ሲያየው ግን በቤተ ክርስቲያን የሚፈጸመውን መንገድ የተከተለና ከልጆች ጨዋታነት ያለፈ ነገር ሆኖ ታየው። በዚህ ጊዜ በመደነቅ አብረውት የነበሩት ካህናት ጋር በመካከር ልጆቹን ሁሉንም አስጠርቶ ምን እያደረጉ እንደሆነ ጠየቃቸው እርሱም ቅዱስ አትናቴዎስ ጳጳሳቸው ሆኖ ሌሎች ልጆች ደግሞ ተጠማቂዎች ሆነው ወደ እርሱ ሲቀርቡና እርሱ እያጠመቃቸው እንደነበረ ነገሩት።
❤ አባ እለእስክንድሮስ በጨዋታ መልክ ሲያጠምቅ የነበረው "የጨዋታው ካህን" ምን እያለና እንዴት እንዳጠመቃቸው ሲጠይቃቸው የምሥጢራቱ አፈጻጸም መንገድ በትክክል እንደተፈጸመ በመገንዘቡ አብረውት የነበሩትን ካህናት ስለ ጉዳዩ ካማከራቸው በኋላ "እነዚህን ንጹሕ ልባቸው በመለኰታዊ ጸጋ የተጠሩትንና የተጠመቁትን ልጆች እንደገና ማጥመቅ አስፈላጊ አይደለም" ብለው በመወሰን ጥምቀታቸውን በማጽደቅ አስፈላጊ የሆኑ ቀጣይ ምሥጢራትን ፈጸመላቸው።ከዚያም ሌሎችን ሕፃናት ባርኮ አሰናበታቸው። አጥማቂውን ሕፃን አትናቴዎስን ግን ከእርሱ ጋር ይሆን ዘንድ ወደ መንበረ ፖትርያርኩ ወሰደው።
❤ አባ እለእስክንድሮስም አትናቴዎስን በመንበረ ፖትርያርኩ የቤተ ክርሰቲያንን ትምህርትና ሥርዓት እያስተማረ አሳደገው፤ እርሱም ተወዳጅ ልጅ ሆነው። ከዚህም ጋር ሰዋስው፣ ፍልስፍና፣ ክሂሎተ ነቢብና ሌሎች በዘመኑ የነበሩ ትምህርቶችንም በሚገባ ተማረ። ቆይቶም ለመዓርገ ምንኵስና በቃ። በቅድስናው፣ በሞያውና በግብረ ገብነቱ እንከን የሌለው ወጣት አትናቴዎስ በ23 ዓመቱ ሊቀ ዲያቆን ሆነ። በዚያ ዘመኑ መዓርግ "ሊቀ ዲያቆን" ማለት የሊቀ ጳጳሱ አፈ ጉባኤ፣ እንደራሴ እንደ ማለት ነበር። ብዙውን ጊዜ የሊቀ ጳጳሳት ሲያርፉ በመንበራቸው የሚተካው ሊቀ ዲያቆናቸው ነበር።
❤ የከበረ አባት እለእስክንድሮስ በዐረፈ ጊዜ ይህን አባት አትናቴዎስ በእስክንድርያ አገር ላይ ሊቀ ጳጳሳት አድርገው ሾሙት። ከዚህ አስቀድሞ ግን ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ኤጲስቆጶሳት ስብሰባ በተደረገ ጊዜ አባ እለእስክንድሮስ ከዚህ ዓለም ሳይለይ ይህም አትናቴዎስ ከእርሳቸው ጋራ ተሰብስቧል። የጉባኤውም ጸሐፊ አድርገውት በኒቅያ ከተማ ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን ከእርሳቸው ጋራ ሠራ።
❤ ጻድቁ ቈስጠንጢኖስ በሞተ ጊዜ አርዮሳዊ ልጁ ሁለተኛው ቈስጠንጢኖስ ነገሠ አርዮሳውያንም በዙ ይህንንም አባት አርዮሳዊው ንጉሥ ከመንበረ ሢመቱ አሳደደውና በእርሱም ፈንታ ጊዮርጊስ የተባለ ከሀዲ ሰው ሾመ። ከዚህም በኋላ ብዙ ጊዜ ሲያሳድዱትና ሲመልሱት ኖረ። በስደትም በአንዲት ምዕራባዊት አገር በአለ ጊዜ በዚያ የጣዖት ቤት አለች። በዚያቺም የጣዖት ቤት ብዙ ሕዝቦች በውስጧ የሚሠሩ ብዙ የሰይጣን ሥራዎች አሏት። እርሱም የክብር ባለቤት የሆነ ጌታችን ኢየሱስ ክርሰቶስን ለመነው ያቺም የጣዖት ቤት አፍርሶ የአገር ሰዎች ሁሉ እግዚአብሔር ወደማወቅ መለሳቸው።
❤ ይህንንም አባት አምስት ጊዜ አሳደዱት የሹመቱም ዘመን አርባ ሰባት ሲሆን ዐሥራ አምስቱን ዓመት በስደትና በእሥራት ነው ያሳለፈው። ይህም አባት ብዙ መከራና ድካም መሰደደም ስደረሰበት ሐዋርያዊ ተብሎ ተጠራ።
❤ በሚሞትበትም ጊዜ እግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን ባገኘ ይህን ጣዖት ቤት ያፈርስ ዘንድ በፊቱ እኔ እየሰገድኩ እለምነዋለሁ። ይህም አባት ከአረፈ በኋላ ንጉሥ ልኮ ያንን የጣዖት ቤት አስፈረሰው። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በቅዱስ አትናቴዎስ ጸሎትና ምልጃ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት7 ስንክሳርና ቅዱስ አትናቴዎስ ሐዋርያዊ ሕይወቱና ትምህርቱ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኃይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ጢሞ 3፥1-11፣ 1ኛ ጴጥ 2፥4-11 እና የሐዋ ሥራ 20፥28-31። የሚነበበው ወንጌል ማቴ18፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ አትናቴዎስ ቅዳሴ ነው። መልካም ሐዋርያውዊ አባት የቅዱስ አባ አትናቴዎስ የዕረፍት በዐልና የእመቤታችን የልደቷ በዐለ ሰሞን። ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ #አባ_ይስሐቅ፦ ይኽም ቅዱስ ከደቡባዊ ግብጽ ዳፍራ ከምትባል አገር የተገኘ ታላቅ ሰማዕት ነው፡፡ የታዘዘ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጠለትና "ጣዋ ወደምትባል አገር ሄዶ በዚያም የጌታችን አምላክነት መስክሮ ሰማዕት ይሆን ዘንድ" አዘዘው፡፡ አባ ይስሐቅም እናትና አባቱን ተሰናብቶ ወጥቶ መሄድ መልአኩ እየመራው ሀገረ ጣዋ ደረሰ፡፡ በዚያም በደረሰ ጊዜ ከሃዲውን መኰንን በውሽባ ቤት አገኘው፡፡ ከዚያም ሲወጣ ጠብቆ ቅዱሱ "በጌታዬ በኢየሱስ ክርስቶስ የማምን ክርስቲያን ነኝ" ብሎ በመኰንኑ ፊት መሰሰከረ፡፡ መኰንኑም ከኒቅዮስ አገር እስኪመለስ ድረስ እንዲጠብቀው ለአንዱ ጭፍራ ሰጥቶት አሠረው፡፡ ወታደሩም አባ ይስሐቅን ይዞት ሲሄድ በመንገድ ላይ ሳሉ አንድ ዐይነ ሥውር ሰው "የእግዚአብሔር ቅዱስ ሆይ! አድነኝ" ብሎ ጮኸ፡፡ አባ ይስሐቅም የክብር ባለቤት ጌታችንን ስለዚያ ዐይነ ሥውር ሰው ለመነው፡፡ ወዲያውም የዐይነ ሥውሩ ሰው ዐይኑ በራለትና ማየት ቻለ፡፡ ወታደሩም ይኽንን ድንቅ ተአምር ባየ ጊዜ "በቅዱስ አባ ይስሐቅ አምላክ አምኛለሁ" ብሎ ጮኸ፡፡ ከክርስቲያን ወገኖችም ሆነ፡፡
❤ መኰንኑም ከሄደበት በተመለሰ ጊዜ አባ ይስሐቅን ጠባቂ አድርጎት በአደራ የሰጠው ያ ወታደር በጌታችን ያመነ ክርስቲያን መሆኑን በመኰንኑ ፊት መሰከረ፡፡ እርሱም ምስክርነቱን ከፈጸመ በኋላ ሰማዕት ሆኖ ዐረፈ፡፡ መኰንኑም አባ ይስሐቅን ይዞ ብዙ ካሠቃየው በኋላ ወደ ብህንሳ አገር ላከው፡፡ በዚያም ብዙ አሠቃዩት፡፡ በመርከብም ሲወስዱት ውኃ ያጠጡት ዘንድ ወታደሮቹን ለመናቸው፡፡ ከእነርሱም አንድ ዐይኑ የታወረችበት አንዱ ወታደር ውኃ በጽዋ አምጥቶ ለቅዱስ ይስሐቅ ሰጠው፡፡ አባ ይስሐቅም በውኃው የወታደሩን ፊቱን ቢረጨው የታወረች ዐይኑ በራችለት፡፡ ጽኑ ሥቃይን ያሠቃዩት የነበሩት የብህንሳ አገር ሰዎችም ይኽንን ተአምር ባዩ ጊዜ ተገርመው በጌታችን አመኑ፡፡ ክፉዎች ግን ወደ መኰንኑ ዘንድ ወስደው "ያሻህን አድርግበት" ብለው አሳልፈው ሰጡት፡፡ መኰንኑም ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ ወዲያውኑ አዘዘ፡፡ የከበረች ራሱንም ግንቦት 6 ቀን ቆረጡትና የሰማዕትነት አክሊልን ተቀበለ፡፡ ምእመናንም ሥጋውን ወስደው ያማረች ቤተ ክርስቲያን ሠርተው በውስጧ አኖሩ፡፡ ከእርሱም የሚያስደንቁ ብዙዎች ተአምራት ተገለጡ፡፡ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ እውነተኛ ምስክር በአባ ይስሐቅ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅድስት_ዳላጊ_አራቱ_ልጆቿ፦ እርሱም ሱርስ፣ ኅርማን፣ ያአፋ ናቸው። መኰንኑ አርያኖስም አገረ እስና በደረሰ ጊዜ ልጆቿን እየነዳች ተቀበለችው በፊቱም ቁማ "አርያኖስ ሆይ ሰማይና ምድርን በውስጣቸው ያለውን በፈጠረ በክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ የማምን ክርስቲያን ነኝ" አለችው። ልጆቿም እደርሷ "እኛ ክርስቲያን ነን" እያሉ በግልጽ ጮኹ። መኰንኑም ሰምቶ ቁጣን ተመላ ራሳቸውንም በሰይፍ ቆረጡ ምስክርነታቸውንም ግንቦት 6 ቀን ፈጸመው ነፍሶቻቸውን ወደ ክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ መላእክት ወሰዱ። የቅድስት ዳላጊ አራቱ ልጆቿ በረከታቸውም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት6 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ፍኖተከ እግዚኦ አምረኒ። ወአሠረ ዚአከ ምህረኒ። ወምርሐኒ በጽድቅከ"። መዝ 24፥4። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 6፥15-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 3፥10-15 እና የሐዋ ሥራ 16፥35-ፍ.ም የሚነበበው ወንጌልን ሉቃ 12፥32-41። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፮ (6) ቀን።
❤ እንኳን #ለታላቁ_አባት_ቅዱስ_ሥጋና_ክቡር_ደም ከተቀበሉ በኋላ ስለ ሥጋ ወደሙ ክብር ሲሉ ስልሳ ዓመት ምራቃቸውን ሳይተፉ ለኖሩት፤ የአንዲት ጅብ ሦስት ልጆች ዐይናቸውን ላበሩ፤ አንዲት ጉንዳል በመግደላቸው ለተጸጸቱ እጅግ ሩኅሩኅ ለሆኑት #ለአባ_መቃርስ ለዕረፍት በዓል፣ ንጽሕናን ቅድስናን ድንግልናን ገንዘብ ላደረገች #ለተሐራሚት_ቅድስት_ሰሎሜ_ለዕረፍቷ በዓልና ከግብጽ ደቡብ ዳፍራ ከሚባል አገር ለሆነ ለከበረ #አባ_ይስሐቅ ምስክር ለፈጸበት ለዕረፍቱ በዓልና #ቅድስት_ዳላጊ_ለአራቱ_ሴት_ልጆቿ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍታቸው በዓል መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #ከቅዱስ_ኤስድሮስ አባት ከበንደላዖስ በምስክርነት ከዐረፉ፣ ደግሞ የምንኵስናን ሥራ ገንዘብ ካደረግሁ ይበቃኛል ብሎ ጵጵስና አልሾምም ካለ ከጻድቁ #አባ_አሞን ከዕረፍት መታሰቢያና በሰይፍ ከፈጸመ ከከበረ አባት #ከአባ_ደናስዮስ ዕረፍት ረድኤትንና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_መቃርስ፦ ይህም ቅዱስ በአባቱ በሚቀድመው በታላቁ በክቡር አባ መቃርስ ዘመን ለአስቄጥስ ገዳም አባት ሁኖ ብዙ ትሩፋትን ሠራ። ስለእርሱም እንዲህ ተባለ አንዲት ዘመሚት ነክሳው ገደላት ከዚህም በኋላ ተጸጽቶ ነፍሱን ገሠጻት ስለ ዘመሚቷም ሞት በበረሀ ወደአለ ወንዝ ወርዶ ሥጋውንም ለዘመሚት ገልጦ እንደዝልጉስ እስኪሆን በዚያ ስድስት ወር ኖረ። ከዚህ በኋላ ወደበዓቱ ተመለሰ መቃርስ እንደሆነም ማንም አላወቀም። አንድ ጊዜም እየጸለየ አምስት ቀን አምት ሌሊት ቆመ ልቡም ወደ ሰማይ ተመስጦአል ሰይጣናትም እስከ ተቃጠሉ ድረስ ይቺ ትጋትና ተጋድሎ ከሠራው ትሩፋት ሁሉ ትልቃለች።
❤ አንድ ጊዜም የረዓይትን ቦታዎች ሊያይ ወዶ ወደ በረሀ ውስጥ ገባ ዐሥር ቀኖችም እየተጓዘ ኖረ። በሚመለስም ጊዜ ምልክት ሊሆኑት መንገዱን እንዳይስት ለምልክት የሚኖራቸው ሸንበቆዎች ከእርሱ ጋራ ነበሩና በየመንገዱ ተከላቸው። በደከመውም ጊዜ ጥቂት ሊያርፍ በምድር ላይ ተኛ። ተኝቶም ሳለም እነዚያን ሸንበቆዎች ሰይጣን ነቀላቸው አሥሮም በቅዱስ መቃርስ ራስጌ አኖራቸው። በነቃም ጊዜ አያቸውና ወዲያውኑ አጣቸው አደነቀ እንዲህ የሚልም ቃል ሰማ "መቃርስ ሆይ ሃይማኖት ካለህ አታወላውል በሸንበቆዎችም አትታመን የእስራኤል ልጆች በበረሀ ሲመራቸው የነበረ የብርሃን ምሰሶ እርሱ እንደሚመራህ እመን እንጂ አትጠራጠር" ወዲያውኑ የብርሃን ምሰሶ አይቶ ተመለሰ። ከዚህም በኋላ በጎዳና ሳለ ተጠማ እግዚአብሔርም ከበረሀ ላሞች አንዲቷን ልኮለት ወተቷን ጠጥቶ ረካ ወደ በዓቱም ተመለሰ።
❤ በአንዲት ቀንም ጅብ ወደርሱ መጥታ ልብሱን ይዛ ትስብ ጀመር እርሱም እስከ ዋሸዋ ተከተላት። ሦስት ልጆቿን አወጣችለት በአያቸውም ጊዜ ዕውሮች ሁነው አገኛቸው ከልቡናዋም አሳብ የተነሣ ያቺን ጅብ አደነቃት። ግልገሎቿንም ይዞ በዐይኖቻቸው ውስጥ ምራቁን ተፋ። አዳኝ በሆነ በመስቀል ምልክትም አማተበባቸው ያን ጊዜ ድነው ከእናታቸው ኋላ ሮጡ ጡቷንም ጠቡ ከዚህ በኋላም ወደ በዓቱ ተመለሰ እርሷም የበግ አጐዛ አመጣችለት እርሱም ተቀብሎ በላዩ እየተኛ እስከሚያርፍበት ጊዜ በእርሱ ዘንድ አኖረው።
❤ በአንዲት ጊዜም ደግሞ ልብሱን ለውጦ በሕዝባዊ አምሳል ሆኖ ወደ አባ ጳኵሚስ ገዳም ሔደ በታላቁም ጾም ሳይበላ ሳይጠጣ አርባ መዓልት አርባ ሌሊት ቆመ። የሚሠራውንም እንደቆመ ይታታ ነበር እንጂ አይቀመጥም። መነኰሳቱም አባ ጳኵሚስም "ይህን ሰው ከእኛ ዘንድ አውጣው ሥጋ የለውምና" አሉት አባ ጳኵሚስም "ሥራውን ይገልጥልኝ ዘንድ እግዚአብሔርን እስከምለምነው ታገሡኝ" አላቸው። በለመነውም ጊዜ እግዚአብሔር አስረዳው። በዚያን ጊዜም አባ ጳኵሚስና መነኰሳቱ ሁሉ ወደርሱ ሒደው እጅ ነሱት ከእርሱም ቡራኬ ተቀብለው ደስ ተሰኙበት ወደቤተ መቅደስ ከእርሳቸው ጋራ አስገቡት። በገዳሙ ውስጥም በሥራቸው በመመካት በባልንጀሮቻቸው ላይ የሚታበዩ የዚህን ቅዱስ አባት አባ መቃርስን ጸጋውን አይተው ትሑታኖች ሆኑ።
❤ ከዚህ በኋላም ወደ በዓቱ ወደ አስቄጥስ ገዳም ተመለሰ። በእስክድርያ አገርም ዝናብ በተከለከለ ጊዜ ዝናብን እንዲያወርድ አንበጣንም እንዲያጠፋ ወደ እግዚአብሔር አብሮት ለመጸለይ ወደርሱ ይመጣ ዘንድ ሊቀ ጳጳሳት አባ ጢሞቴዎስ እየማለደ ላከበት። ያንጊዜም ተነሥቶ ወደ እስክንድርያ አገር ሔደ ሕዝቡም በታላቅ ደስታ ተቀበሉት በልቡም ጸለየ ብዙ ዝናብም ዘነበ ከዝናብ ብዛት የተነሣ ምድሪቱ ትጠፋለች ብለው እስቲአስቡ ድረስ ሁለት መዓልት ሁለት ሌሊት እየዘነበ ኖረ። እጅግም ፈርተው "አባታችን ሆይ ዝናቡን አስወግዶ በልክ ይሆን ዘንድ እንዳንጠፋ ወደ እግዚአብሔር ጸልይ" ብለው ለመኑት ያንጊዜም ጸለየ ዝናቡም አባርቶ በእግዚአብሔር ቸርነት ፀሐይ ወጣላቸው።
❤ ይህም አባት ብዙ ታላላቅ ትሩፋቶችን ሠርቷል እግዚአብሔርም በእጆቹ ድንቆች ተአምራትን ገለጠ ርኵሳን አጋንንት ያደሩባቸውንና ብዙዎች በሽተኞችን አዳናቸው። ይህም አባትም የሠራቸው በጎ ሥራዎች ሊቆጥራቸው የሚችል የለም አንድ ሰው በጎ ሥራ እንደሠራ የሰማ እንደሆነ ሰውዬው እንደሠራው እስከሚሠራ አይተኛም።
❤ የክብር ባለቤት ስለሆነ ስለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም ክብር አንዴ ከቆረበ በኋላ ምራቁን ሳይተፋ ስልሳ ዓመት ኖረ። መቶ ዓመት ከሆነውና ተጋድሎውን ከፈጸመ በኋላ በበጎ ሽምግልና ግንቦት 6 ቀን ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ጻድቅ በአባ መቃርስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለሙ ትኑር አሜን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #ቅድስት_ሰሎሜ (ዘወረብ)፦ ይችም ቅድስት ወረብ ከሚባል አገር ናት ወላጆቿም እግዚአብሔርን የሚፈሩ ናቸው በበጎ አስተዳደግም አሳደጉዋት። መኰንን አጭቶ በሰርግ አገባት። ያን ጊዜም አምላካዊ ኃይል ከልክሎት ወደርሷ መቅረብ አልቻለም አባለ ዘሩ ተቀሥፎልና። በእንደዚህም እያለች ራሷን ሠውራ በሌሊት ሔደች በእግዚአብሔርም ኃይል አመለጠች። ቅዱሳን በአሉበት ሁሉ በመዞር በጾም በጸሎት ተወስና ዕውነተኛ መንገድን ጌታ ይመራት ዘንድ በቀንና በሌሊት ስትማልድ ኖረች።
❤ ጌታችንም ልመናዋን ሰምቶ ወደ ደብረ ሊባኖስ ገዳም አደረሳት የመላእክት የሆነ አልባስ ምንኵስናን በአባ ዮሐንስ ከማ እጅ ለብሳ የሰውን ልብ የሚያስደነግጥ ጽኑ ገድልን ተጋደለች። በጾም፣ በጸሎት በተመሰገነ ገድል ሁሉ የፍጹማን አባቶችን ጐዳና ተጓዘች። በመጽሐፈ ገድሏ እንደ ተጻፈ ብዙዎች ድንቆች ተአምራትንም እስከ ማድረግ ደርሳ ከዚህ በኋላ ግንቦት 6 ቀን በሰላም ዐረፈች። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም ቅድስት ሰሎሜ (ዘወረብ) በጸሎቷ ይማረን በረከቷም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፭ (5) ቀን።
❤ እንኳን #ከአራቱ_ዐበይት_ነቢያት አንዱ ለሆነው ለካህኑ ኬልቅዩስ ልጅ ለታላቁ ነቢይ #ለቅዱስ_ኤርምያስ በአይሁድ እጅ በደንጊያዎች ተወግሮ ሰማዕትነት ለተቀበለበት ለዕረፍት በዓል በሰላም አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #ነቢዩ_ቅዱስ_ኤርምያስ፦ ኤርምያስ የስሙ ትርጉም ከእግዚአብሔር የተላከ ብርሃን ማለት ሲኾን፤ ትውልዱ ከነገደ ሌዊ በመኾኑ ክህነትን ከነቢይነት አስተባብሮ የተገኘ ነው። ይህም እውነተኛ ነቢይ የአሞጽ ልጅ የይሁዳ ንጉሥ ኢዮስያስ በነገሠ በዐሥራ ሦስት ዓመቱ ማስተማር ጀመረ። ከዚያም በይሁዳ ንጉሥ በኢዮስያስ ልጅ በኢዮአቄም ዘመን ዐሥራ አንዱ የሴዴቅያስ ዘመን መንግሥቱ እስከሚፈጸም በአምስተኛው ወር ኢየሩሳሌም እስከ ተማረከችበት ጊዜ ያስተምር ነበር።
❤ ነቢዩ ቅዱስ ኤርምያስ እንደ ቅዱስ ኢሳይያስ በበትር የምትመሰል የቅድስት ድንግል ማርያምን ምሳሌ በለውዝ በትር አምሳል ተመልክቷታል (ኤር1፥11)። ይኽ ብቻ ሳይኾን ከኹለት (ሁለት) ደመ መዛሙርቱ ከባሮክና ከአቤሜሌክ የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ የኾነች ዐጽቀ በለስ በንስር አንገት የተላከለት ታላቅ ነቢይ ነው።
❤ ስለ ራሱ እንዲህ ሲል ራሱ ተናገረ "የእግዚአብሔር ቃል ወደኔ መጣ እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ በእናትህ ማሕፀን ሳልፈጥርህ ወደድኩህ ከእናትህም ማሕፀን ሳትወጣ መረጥኩህ ለአሕዛብም መምህር አደረግሁህ" አለኝ። ሁለተኛም እንዲህ ብሎ አስረዳቸው "ወደ ፈጣሪያችሁ እግዚአብሔር ካልተመለሳችሁ ያለዚያ የከላውዴዎንን ንጉሥ ናቡከደነጾርን በላያችሁ እርሱ ያሥነሣዋል ይማርካችኋልም" እንደቃሉም ሆነ። ሁለተኛም ሕዝቡ ተማርከው ሰባ ዘመን እንደሚኖሩ ትንቢት ተናገረ። ደግሞ የክብር ባለቤት ኢየሱስ ክርስቶስ ለኩነተ ሥጋ እንደሚመጣና መከራ እንደሚቀበል የአስቆሮቱ ይሁዳ እንደሚሸጠውና ሠላሳ ብር እንደሚወስድ ተናገረ። ስለ ብዙ ሥራዎችም ተናገረ አይሁድ ግን ሊገድሉት ወደው ገርፈው አሥረው በጒድጓድ ውስጥ ጣሉት እግዚአብሔርም አዳነው። እርሱ ግን ስለእነርሱ ይለምንና ይማልድ ነበር እግዚአብሔርም "ስለ እርሳቸው ወደእኔ አትማልድ እነርሱ ከክፋታቸው አይመለሱምና" አለው።
❤ ናቡከደነጾርም ኢየሩሳሌምን ሕዝብ በማረከ ጊዜ ከእርሳቸው ጋራ አልማረከውም። ነገር ግን ከምርኮ የቀሩት ወደ ግብጽ አገር ወሰዱት የግብጽን ሰዎች ሲያጠፋቸው የነበሩ በግብጽ ወንዞች የሚኖሩ አራዊትን በእርሱ ጸሎት እግዚአብሔር አጠፋቸው።
❤ ከዚያም ወደ ባቢሎን አገር ወሰዱት በዚያም የእስራኤል ልጆች ከምርኮ እስኪመለሱ ትንቢት እየተናገረ ሕዝቡን ሲአስተምር ኖረ። የትንቢት ወራትም በተፈጸመ ጊዜ አይሁድ በደንጊያዎች ወገሩት ነፍሱንም በእግዚአብሔር እጅ ግንቦት 5 ቀን ሰጠ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በነቢዩ ቅዱስ ኤርምያስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት5 ስንክሳር እና መጽሐፈ ተአምኆ ቅዱሳን (የቅዱሳን ሰላምታ) ንባቡና ትርጓሜው መጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ ከሚለው መጽሐፍ።
✝ ✝ ✝
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "ላዕሌከ ተገደፍኩ እማኅፀን። እምከርሠ እምየ አንተ አምላኪየ። ኢትርኀቅ እምኔየ እስመ አልጸቁ እትመንደብ"። መዝ 21፥10-11። የሚነበቡት መልዕክታት ዕብ 11፥32-ፍ.ም፣ 1ኛ ጴጥ 2፥19-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 7፥51-55። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 21፥33-ፍ.ም። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የበዓለ ሃምሳ ጊዜ ለሁላችንም ይሁንልን።
❤ "በስመ አብ ወወልደ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፬ (4) ቀን።
❤ እንኳን ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ሃያ ዘጠነኛ ለሆነ #ለእስክድርያ_ሊቀ_ጳጳሳት_ለአባ_ዮሐንስ ለዕረፍት በዓል ሰላም አደረሰን። በተጨማሪ ከሚታሰቡት፦ #ከቡሩክ_ቅዱስ_ፊቅጦር አገልጋዮች ከሆኑ #ሶሲማና_ኖዳ ከዕረፍታቸ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #አባ_ዮሐንስ፦ ይህ አባት ለአባቶች ሊቃነ ጳጳሳት ለእስክድርያ ሃያ ዘጠነኛ ነው። እርሱም ከእስክንድርያ አገር ነው ከታናሽነቱም በአስቄጥስ በአባ መቃርስ ገዳም መንኵሶ በተጋድሎ ኖረ። ከእርሱ አስቀድሞ የነበረ አባ አትናቴዎስ በዐረፈ ጊዜ አዋቂዎች ኤጲስቆጶሳት ሕዝቡም ሁሉ መረጡት። ወስደውም በግድ ተሾመ አሉት እርሱ ግን አልፈለገም የክርስቶስን መንጋ እንዳይተው ሌላ ጥፋት እንዳያመጣ ብዙ ልመናዎችን ለመኑት አዋቂዎች ኤጲስቆጶሳትና መምህራን ሁሉ አጽንተው ሲለምኑት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፈቃድ ይሆን ብሎ አሰበ።
❤ ከዚህም በኋላ ሊቀ ጵጵስና ሾሙትና በወንጌላዊ ቅዱስ ማርቆስ ወንበር ላይ ተቀመጠ። ስለ መንጋዎቹም ጥበቃ አሰበ ደግሞ ስለ ትምህርት መጻሕፍትንም ስለ ማንበብ በቀናች ሃይማኖትም የሚያጸናቸው ሆነ ምሁራን ካህናትንም ኤጲስቆጶሳትን አድርጎ ሾማቸው። በዚያ ወራት ስሙ ዘይኑን የሚባል እግዚአብሔር የሚፈራ ደግ ንጉሥ ነበረ። ይህንንም ቅዱስ ስለረዳው ሥልጣኑ በአገሮች ላይ ተዳረሰ የቀናች ሃይማኖትም በግብጽ አገሮች ሁሉ ላይ ተዘረጋች። በዚያም ወራት ስንዴና ወይን ዘይትም የተመሉ ብዙ እንቅቦችን ለአብያተ ክርስቲያናትና ለገዳማት ለፍላጎታቸው ንጉሥ ዘይኑን ለከ።
❤ ለዚህም አባት ዘመኑ ሁሉ ጸጥታና ሰላም ሆነ። ጌታችንም በሥራው ሁሉ ተደሰተለት ከዚያም በኋላ በቸርነቱ ጐበኘውና ጥቂት ታመመ በሹመቱም ስምንት ዓመት ከኖረ በኋላ በሰላም ግንቦት4 ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በአባ ዮሐንስ ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ትኑር ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት 4 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የማኅሌት_ምስባክ፦ "ክቡር ሞቱ ለጻድቅ በቅድመ እግዚአብሔር። እግዚኦ አነ ገብርከ። ገብርከ ወልደ አመትከ"። መዝ 115፥15-16 ወይም መዝ 28፥9-10። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 26፥36-47 ወይም ማቴ 5፥1-14።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_የቅዳሴ_ምስባክ፦ "እስመ መምህረ ሕግ ይሁብ በረከተ። ወየሐውር እምኃይል ውስተ ኃይል። ወያስተርኢ አምላከ አማልክት በጽዮን"። መዝ 83፥6-7። የሚነበቡት መልዕክታት 1ኛ ጢሞ 3፥1-11፣ 1ኛ ጴጥ 5፥1-8 እና የሐዋ ሥራ 14፥23-ፍ.ም። የሚነበበው ወንጌል ማቴ 25፥14-31። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱስ ዲዮስቆሮስ ወይም የሠለስቱ ምዕት ቅዳሴ ነው። መልካም የአባታችን የአቡነ መልከ ጼጼቅ የዕረፍት በዓልና የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የልደት በዐል ሰሞን ለሁላችንም ይሁንልን።
የሚያገለግል ፍጹም ንጹሕና ጻድቅ ሰው ነው፡፡
❤ ከዚህ በኋላም አባታችን ተክለ ሃይማኖት ሦስት የብርሃን አክሊሎችና የወርቅ ዘውድ ተቀዳጅቶ ተገለጠለት፡፡ የብርሃን ልብሶችን ለብሶ የመስቀል ምልክት ያለው በትርም ተመርኩዞ ፊቱም እንደ እግዚአብሔር መልአክ እያበራ መጣና ወደ አባታችን መልከ ጼዴቅ ቀርቦም "ልጄ ሆይ ሰላም ለአንተ ይሁን" አለው፡፡ አባታችን መልከ ጼዴቅም መልሶ "የእግዚአብሔር ሰላም ከአንተ ጋር ይሁን አንተ ማነህ አለው፡፡ "እኔ ከእናቴ ማኀፀን ጀምሮ መድኃኔዓለም የመረጠኝ ተክለሃይማኖት ብሎም የሰየመኝ ፍሰሐ ጽዮን ነኝ" አለው፡፡ ያንጊዜም ከእግሩ በታች ወደቅሁ ከኔ ጋር የነበረው የእግዚአብሔር መልአክ አነሣኝ አቡነ ተክለ ሃይማኖት "የዳሞት ንጉሥ ሞተለሚ እንዴት እንዳደረገው የጣዖት ማምለኪያዎችን እንዴት እንዳጠፋ ብዙ ሰዎችን በክርስቶስ እንዴት እንደአሳመነ ያን ጊዜ ነገረኝ፡"፡
❤ ስለዚህም "እግዚአብሔር አከበረኝ ከፍ ከፍ አደረገኝ፤ የብዙዎችም አባት አደረገኝ፤ ልጄ ሆይ አንተም ጸንተህ ተጋደል የብዙዎች አባት ትሆናለህ፤ እግዚአብሔር ለመጋደል ያበርታህ ሰላምንም ይስጥህ"፡፡ ይህንም ብሎ ከእርሱ ተሠወረ፡፡ ከርሱ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ አባታችን መልከ ጼዴቅ መጣና ወዳጄ ሆይ ሰላም ለአንተ ይሁን" አለው፡፡ መልከ ጼዴቅም "አንተ ማነህ" አለው፡፡ "እኔ የድንግል ማርያም ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስ ነኝ" አለው፡፡ ያን ጊዜም ከእግሩ በታች ወደቀ፡፡ ጌታችንም እጁን ይዞ፡፡ አነሣውና "ጽና አትፍራ" አለው፡፡ ያን ጊዜም እናቱ ድንግል ማርያም፣ ከቅዱስ ሚካኤልና ከቅዱስ ገብርኤል፣ ከሱራፌልና ከኪሩቤል ጋር ከነቢያት፣ ከሐዋርያት ጋር፣ ከጻድቃንና ከሰማዕታት ጋር መጣች መድኃኔዓለምም አባታችን መልከ ጼዴቅን "ከእናትህ ማኀፀን ጀምሮ በምስክር ሁሉ ፊት መረጥሁህ ካህንም አደረግሁህ ዛሬም የብዙዎቹ አባት አደርግሃለሁ፡፡ ኃጢአተኞችንም የምትመልስ ትሆናለህ፡፡ ያልጠቆረ ብሩህ አክሊልና በሰው እጅ ያልተሠሩ የብርሃን ልብሶችን እሰጥሃለሁ፡፡ ርስትህ ከአጥማቂዬ ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር ይሁን፤ ሹመትህም ከሃያ አራቱ ካህናተ ሰማይና ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ጋር ይሁን፣ ስምህም የኔ ምሳሌ በሆነው መልከ ጼዴቅ ይሁን" አለው፡፡
❤ የመጀመሪያው በጥምቀት የተሰጠው ስሙ ኀሩየ ወልድ (በወልድ የተመረ) የሚል ነበርና ያን ጊዜም ቁመታቸው እስከ ሰማይ የሚደርስ ብርሃናቸው እንደ ፀሐይ የሚያበራ፤ ሦስት የወርቅ መስቀሎችን ሰጠው" በላያቸው ላይ ውጣ" አለኝ፤ እኔም በእያንዳንዳቸው ላይ ሦስት ጊዜ ወጣሁ እስከ አርያምም አገቡኝ፡፡ በዚያም የእግዚአብሔርን መንበር አየሁ፡፡ በአንድነት በሦስትነት የሚኖር የዘመናት ጌታም በላይ ተቀምጧል፡፡ ይህም ነገር እጅግ ድንቅ ነው ወልድ በምድር ላይ ከእርሱ ጋራ እየተነጋገረ ሳለ በአርያም ደግሞ በሦስትነቱ ተቀምጦ አየሁ፡፡ ጌታም ሥርዓትህ እንዲሁ እንዳየኸው ይሁን፤ እስከ ዕለት ዕረፍትህም ድረስ ስለ ገድልህ ጽናት የሚሆን ሰጥቼሃለሁ" አለው፡፡ በጸሎቱ የተማጸነውን እንደሚምርለትና ሌላም ብዙ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ "እኔም ከአንተ አልለይም፣ መላአክቶቼም ይጠብቁሃል" አለው፡፡ መልከ ጼዴቅም ይህንን በሰማ ጊዜ በፊቱ ሰገደ፡፡ "አቤቱ ለእኔ ለኃጢአተኛው አገልጋይህ ይህን ሁሉ ክብር የሰጠኸኝ ጌታ ሆይ መንግሥትህ ይባረክ" አለው፡፡ ጌታችንም ባርኮት በታላቅ ክብር ወደ ሰማያት ዐረገ፡፡
❤ አባታች መልከ ጼዴቅ እንደዝህ በብዙ ተጋድሎ ሲኖሩ ዕረፍታቸው ሲደርስ ትንሽ በተቅማጥ በሽታ ታመሙ ያንጊዜም ጌታችን እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ከቅዱሳን መላእክቶች ጋር መጣች፡፡ መላእክትንና ቀደምት አባቶችን፣ ነቢያትንና ሐዋርያትን፣ ጻደቃን ሰማዕታትን፣ ቀሳውስትና ዲያቆናትን፣ ደናግልና መነኮሳትን፣ ወንዶችንና ሴቶችን ሕፃናትንም ምስክሮች አድርጎ አቆመ፡፡ ሄሮድስ ያስገደላቸው 144,000 ሕፃናት ከአለቃቸው ከቅዱስ ቂርቆስ ጋር መጡ፡፡ "በእኔና በአንተ መካከል እነዚህ ሁሉ ምስክሮች ይሁኑ፤ ስምህን የጠራ፣ መታሰቢያህን ያደረገ፣ በእጅህ የተጠመቀ፣ በቃልህ የተናዘዘና በእጅህ የተሳለመ ምሬልሃለሁ፤ የገድልህን መጽሐፍ የጻፈውና ያጻፈውን ምሬልሃለሁ ከአንተም ጋር ርስት እሰጠዋለሁ፤ የቤትህ ልጆች መንግሥተ ሰማያትን ከአንተ ጋር ይውረሱ" አለው፡፡ ዳግመኛም "ለምህረት ያልጠራኋትን ነፍስ ለመሳለምም ሆነ ለመባረክ ወይም ለመናዘዝ ወደ አንተ አላቀርብም፤ ከኃጥአንም ወገን አንተ ስለ እነርሱ ከለመንኸኝ እምርልሃለሁ" ብሎ ቃል ኪዳን ገባላቸው። አባታችንም ግንቦት 4 ቀን ነፍሳቸው ከስጋቸው ተለየች። ከጻድቁ አባታችን ከአቡነ መልከጼዴቅ እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን በጸሎታቸው ይማረን! አሜን። ምንጭ፦ ገድለ መልከ ጼጼቅና መዝገበ ቅዱሳን።
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፬ (4) ቀን።
❤ እንኳን #ለኢትዮጵያዊው_ጻድቅ ገዳማቸው ላይ የተቀበረ ሰው እሬሳው ለማይበሰብስ ለታላቁ አባት #ለአቡነ_መልከ_ጼዴቅ_ዘሚዳ ለዕረፍት በዓል እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን።
✝ ✝ ✝
❤ #አቡነ_መልከ_ጼድቅ_ዘሚዳ፦ እኚህ ጻድቅ ከከበሩና ነገሥታት ከሆኑት ወገን በአገረ ጐጃም ኢናይ በምትባል ቦታ የካቲት አሥራ ስድስት ቀን ተወለዱ፡፡ ልደታቸውም እንዲህ ነበር፡፡ ንጉሥ አምደ ጽዮን ምስረነዓዳን ወለዱ፣ ምስረነዓዳም በዝራምበሳን ወለደች፣ በዝራምበሳም ፍሬጽዮንን ወለደ፣ ፍሬጽዮንም መልከ ጼዴቅን ወለደ የእናታቸውም ስም ቅድስት ዓመተ ማርያም ነው፡፡ በተወለዱም ጊዜም በአባትና በእናታቸው ቤት ታላቅ ደስታ ሆነ እግዚአብሔር ለብዙዎች አባት አድርጎ መርጦአቸዋልና፡፡
❤ ለትምህርት በደረሱም ጊዜ መዝሙረ ዳዊት ይማሩ ዘንድ አባትና እናታቸው ለመምህር ሰጧቸው ፡፡ እርሳቸውም አምቢ ብለው ወደ አባትና እናታቸው ቤት ተመለሱ ፡፡ ፈረስ ጋላቢም ሆኑ፡፡ ደግሞ እኚህ ጻድቅ በጐለመሱ ጊዜ አባትና እናታቸው መልኳ የምታምር ሚስት አጩላቸው፡፡ የአባታቸውንም ሹመት የንጉሥ ሠራዊት አለቃ ሆነው ተሾሙ፡፡ በልባቸውም ሰሎሞን እንደተናገረው "ከፀሐይ በታች ያለው ሁሉ ከንቱ እንደሆነ አሰቡ" "በምድር ላይ ቋሚ የፀና ሕይወት የለምና" ይህንም ብለው ከአባትና ከእናታቸው ቤት ተሰደዱ፡፡ የእግዚአብሔርም መልአክ እየመራቸው ቅጽሮ ወደሚባል አገር ደረሱ የበሩም ጠባቂዎች አባታችን መልከ ጼዴቅን ከተሸከሟቸው ሁለት የወርቅ ልብሶች ጋር አቆሙአቸው "አትሻገር ተመለስ" አሏቸው፡፡ ያ የበር ጠባቂ የሆነ ሰውም "ለሌላው እስከምመለስ ጠብቀው" አላቸው ይህን ብሎም ይረዷቸው ዘንድ ጓደኞቹን ሊጠራ ሄደ የሚመራው መልአክም መልከ ጼዴቅ "ከወርቅህ ጋር ከዚህ ሂድ" አላቸው ልብሶቻቸውንም ተሸክመው ሄዱ፡፡ ይመራቸው የነበረ የእግዚአብሔር መልአክም እነዚህን የበርሃ ጠባቂዎች እንደ ድንጋይ የፈዘዙ እንደበድን የደነዘዙ አደረጋቸው፡፡ መናገርም ተሳናቸው፡፡
❤ ከዚህ በኋላም የኢዮስያስ ቦታ ወደ ሆነችው ደጋ ዳሞት ደብረ ምዕራፍ ደረሱ፡፡ ከአባታችን ኢዮስያስ ቀጥሎ (በኋላ) በተሾሙት በአባታችን በአቡነ አሮን እጅ በዚያ መነኰሱ እርሳቸው አስቀድመው በስውር መንኵሰው ነበርና፡፡ አባታችን አቡነ አሮን ንዑድ ክቡር ለሚሆን መልከ ጼዴቅ የምንኩስናን ልብስ አለበሳቸው፡፡
❤ ከዚህም በኋላ አባትና ወንድሞቹ ዘመዶቹም ኤናይ ከምትባል አገሩ እየፈለጉ መጡ፡፡ በመንፈስ ቅዱስም ፈቃድ ተሰወራቸው አላገኙትም አባታችን አሮንንም ይዘው "ልጃችን አባት እናቱን እጮኛውንና ሹመቱን ትቶ ወደ አንተ መጥቷልና ስጠን" አሉት፡፡ አባታችን አሮንም ቅዱስ መልከ ጼዴቅ እንደመነኰሰ ነገራቸው፡፡ ያን ጊዜም አባትና እናቱ ወንድሞቹና ዘመዶቹ ታላቅ ለቅሶን አለቀሱ አዘኑ "ወዮልን ወዮልን ክብራችን ፈርሶአልና ኃይላችንም ተሽሮአልና ወልደን እንደ አልወለድንም ሆነናልና" አሉ፡፡ ከአባታችን ከአቡነ አሮን ጋር አስታረቋቸው አባቱም ያን ጊዜ "የእግዚአብሔር ፈቃድ ይሁን" አለ አስቀድሞ ቅዱሳንን ሲጎበኝና ለነዳያን ሲራራላቸው ባየሁ ጊዜ ይህ ልጅ መነኩሴ እንደሚሆን በልቤ አስብ ነበር፡፡ ትተውትም ወደ አገራቸው ሄዱ፡፡ ከዚህ በኋላም የእግዚአብሔር መልአክ ክቡር መልከ ጼድቅን በዚያ ወስዶ ደብረ መድኃኒት አደረሳቸው፡፡ በዚያም ከቀሲስ አስጢፋኖስ የዳዊትን መዝሙርና የመጻሕፍትን ቃል እየተማሩ ተቀመጡ፡፡ ፈጥነውም ጨረሱ መንፈስ ቅዱስ በእርሳቸው ላይ ይናገራልና፡፡
❤ ከዚህ በኋላ ከትንሽ ዋሻ ገቡ የአምላካቸውን የክርስቶስን መከራ በማሰብ በዚያ ገብተው ቀንና ሌሊት ዘግተው በረደኝ ፀሐይ ልሙቅ፣ ጨለመኝ ብርሃን ልይ ሳይሉ በጸሎት ብቻ ዘግተው በመኖር ራሳቸውን በችንካር እያቆሰሉና ጭንቅላታቸውን እያተሉ ትሉን ለሰማይ አእዋፍ ይመግቡ ነበር፡፡ እግዚአብሔር ወልድ የተገረፈውን ግርፋት እያሰቡ በየቀኑ እስከ ሦስት ሺህ ድረስ ይሰግዳሉ፡፡ ሰውነታቸውንም እንዲሁ ይገርፋሉ፡፡ የክርስቶስን መቸንከር እያሰቡ እጅና እግራቸውን፣ ወገብና ደረታቸውን በብረት ቸንክረው መከራውን ያስባሉ፡፡ ጎኑ በጦር መወጋቱን አስበው አጥንታቸው እስኪሰበር ድረስ ጎናቸውን ወጉ፤ ሐሞትና ከርቤ መጠጣቱን አስበው እርሳቸውም መራራ ይጠጡና እንክርዳድን ይመገባሉ፤ ሞቱን አስበው ደም እንባን ያነባሉ፤ ብፁዕ መልከ ጼዴቅ በቀንና በሌሊት በጾምና በጸሎት ይጋደሉ ዘንድ ጀመሩ፡፡ የዳዊትን መዝሙር በየቀኑ ሦስት ጊዜ ይጸልዩ፣ እየተጋደሉም አርባ መዓልትን ቆዩ፤ ሌሊትም ራቁታቸውን ማቅ ብቻ ለብሰው ከባህር ውስጥ ይቆማሉ፡፡ በነጋም ጊዜ ወደ በዓታቸው ይመለሳሉ፡፡ በየዓመቱም አራት ጊዜ እንዲህ ያደርጋሉ፡፡ በየዓመቱም አርባ ቀን እህል ሳይበሉ ወይን ሳይጠጡ፣ ከቅጠልና ከእንጨት ፍሬ ከሣርም ፍሬ የፅዋው ቁመት በትንሽ ጣት ልክ ከተሰፈረ ጥቂት ውኃ በስተቀር እንደዚህ እየተጋደሉ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል በደብረ መድኃኒት ሰባት ዓመት ኖሩ፡፡ የእግዚአብሔርም መልአክ ይጠብቃቸው ነበር፡፡ በእንደዚህ ዓይነቱ ተጋድሎ የክርስቶስን መከራ እያሰቡ ነቢያትን፣ ሐዋርያትን፣ ሰማዕታትን ደናግል መነኰሳትን መስለው ሁሉን እያከናወኑ እያለ የወዳጆቹን መከራ የማይዘነጋ፣ የሰውን የድካሙን ዋጋ ፈጽሞ የማያስቀር አምላክ ሠራዊተ መላእክትን አስከትሎ መጥቶ "መገረፍህ ስለ እኔ መገረፍ ይሁንልህ፤ የደምህ መፍሰስ ስለ እኔ ደም መፍሰስ ይሁንልህ፤ መቸንከርህም ስለ እኔ መቸንከር ይሁንልህ፤ ሞትህም ስለ እኔ ሞት ይሁንልህ" ብሎ ቃል ኪዳን ገባላቸው፡፡ "ከዚህ ቦታ መጥቶ የተሳለመውን እምርልሃለሁ ነፍሱ በአንተ ቃል ኪዳን የማይማር በአንተ ቦታ ለመሳለምም፣ ንሰሐ ለመግባትም ሆነ ለመቀበር አላቀርብብህም፣ መጥቶም የተቀበረውን ሥጋውን አፈር አይበላውም" የሚል እጅግ ድንቅ ቃል ኪዳን መድኃኔዓለም ሰጣቸው እስከ ዕለተ ምጽዓትም ሲታይ ይኖራል፡፡ በደጃቸው የተቀበረ ሰው አይበሰብስም፡፡
❤ የእግዚአብሔር መልአክ አባታችን መልከ ጼጼቅን "በግራሪያ አገር ወደምትገኝ የቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ደብር ወደሆነች ወደ ደብረ ሊባኖስ ሂድ" አለው፡፡ አባታችን መልከ ጼዴቅም በዚህ መልአክ ትዕዛዝ ሄዱ ደብረ ሊባኖስ ደረሱና በዚያ እያሉ ቅዱሳንን እጅ ነሷቸው ከንቡረ ዕድ እንድርያስ ጋርም ተቀመጡ፡፡ ትንሽ ዋሻ በዓትን ሰጡዋቸውና "ትዕዛዛቱን ለመጠበቅ እግዚአብሔር ያጽናህ የገድልህንም ፍጻሜ ይሰጥህ" አላቸው፡፡ አባታችን እንድርያስ በእሱ ላይ በባረከ ጊዜም አባታችን መልከ ጼዴቅ ወደ በዓቱ ገብቶ ምስጋና ጸሎትና ስግደት ተግቶ ያዘ፡፡ እንደ መጀመሪያውም ታስሮ እያለ በየለቱ እስከ ሦስት ሺህ ስግደት ይሰግድ ነበር፡፡ ደሙም በምድር ላይ እስከሚፈስ ድረስ መንታ በሆነ የገመድ ጅራፍ ሰውነቱን ይገርፍ ነበር፡፡ እንባውም እንደክረምት ነጠብጣብ ይፈስ ነበር፤ የዓይኑ ብሌን እስኪገለበጥ ድረስ ያነባ ነበር፡፡ የሥጋውንም ቁስል እንደ መርፌ ሰርስሮ ወደ ውስጥ አካሉ እስኪገባ ድረስ በማቅ ፀጉር ይሰቀስቅና ይደመድም ነበር፡፡ እንዲህ ሆኖ መከራ ሲቀበልም ከእግዚአብሔር ምሥጋና ዝም አይልም ሥራውንም ፈጽሞ ያደንቅ ነበር፡፡ "ጌታ ሆይ የተኛሁትን አንቃኝ የደከምሁትን አበርታኝ የጨለምሁትን እኔን አብራልኝ" ይል ነበር፡፡ ይህንንም የሚለው ለራሱ ብቻ አይደለም ስለዓለም ሁሉ ነበር እንጅ እሱስ በኢየሩሳሌም ከሐዋርያት ጋርና በዓርያም ካሉ ከሱራፌል ጋር በክህነት
❤ "በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን"። ❤
❤ #ግንቦት ፫ (3) ቀን።
❤ እንኳን #ጌታችን_ከመረጣቸው_ወንጌል_ይሰቡኩ ዘንድ ከላካቸው #ከሰባ_ሁለቱ_አርድእት አንዱ ለሆነ #ለሐዋርያው_ቅዱስ_ያሶን ለዕረፍት በዓል፣ ለተባረከች #ለኢትዮጵያዊው_ንጉሥ_ወናግ_ሰገድ_እናት_ለንግሥት_ለቅድስት_ወለተ_ማርያም ለዕረፍቷ በዓልና ከቤልጊት ሰዎች ለሆነ #ለአባ_ብሶይ ሰማዕትነት ለተቀበሉበት ለዕረፍት በዓል መታሰቢያ እግዚአብሔር አምላክ በሰላምና በጤና አደረሰን። በተጨማሪ በዚች ቀን ከሚታሰቡት፦ #ቅዱስ_ያሶንን ሲያሰቃዩ ምንም ጉዳት እንዳልደረሰበት አይታ በጌታችን አምና ሰማዕትነት ከተቀበለች #ከንጉሡ_ልጅ፣ #ከከበረ_ቀሲስ_አውሳብዮስና_ከሰማዕት_ቅዱስ_ሴም ከመታሰቢያቸው እግዚአብሔር አምላክ ረድኤትና በረከትን ያሳትፈን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅዱስ_ያሶን፦ ይህም ቅዱስ ከሐዋርያት ጋራ ወንጌልን በሰበከ ጊዜ ብዙ መከራዎችን በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተቀበለ ድንቆች ተአምራትንም አደረገ በሃምሳኛው ቀን ከሐዋርያት ጋራ አጽናኝ መንፈስ ቅዱስን ተቀብሏልና።
❤ ትውልዱም ከጠርሴስ አገር ነው ከጠርሴስ ሰዎች አስቀድሞ አመነ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም ከተጠራና ከአመነ በኋላ በብዙ አገሮች ተከትሎ በወንጌል ትምህርት አገለገለው በተሰሎንቄ ከተማም ከቅዱስ ጳውሎስ ጋራ ይዘው በመጐተት ከተሰሎንቄ ገዢ ዘንድ አቀረቡአቸው። ከዚህም በኋላ በጠርሴስ አገር ቅዱስ ጳውሎስ ኤጲስቆጶስነት ሾመው ወልደ እግዚአብሔርንም ቤተ ክርስቲያን በመልካም አጠባበቅ በቅንነት ጠበቀ። ምዕመናንን በቀናች ሃይማኖት ከአጸናቸውና በጎ ምግባርን ከአስተማራቸው በኋላ ከዚያ ወደ ምዕራብ አገር ሒዶ በውስጥዋ የከበረ ወንጌልን አስተማረ። ስሟ ኮራኮራስ ወደምትባል ደሴትም ደርሶ በውስጧ ወንጌልን ሰበከ እግዚአብሔርንም ወደማወቅ መለሳቸው በዲያቆናት አለቃ በሰማዕታትም መጀመሪያ በከበረ ሐዋርያ ቅዱስ እስጢፋኖስ ስም በውስጧ ቤተ ክርስቲያን ሠራላቸው። በዚያች አገር ገዥም በአወቀ ጊዜ ይዞ ከእስር ቤት አስገባው በዚያም ሰባት ወንበዴዎችን አግኝቶ ሃይማኖትን አስተማራቸው በክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ አመኑ የክርስትና ጥምቀትንም አጠመቃቸው። ከዚያም በኋላ በመኰንኑ ፊት ቁመው እኛ ክርስቲያን ነን በክብር ባለቤት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስ እናምናለን ብለው ጮኹ። መኰንኑም ዝፍትና ዲን በተመላ ምጣድ ውስጥ አግብቶ አቃጠላቸው የሰማዕትነት አክሊልንም ተቀበሉ።
❤ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሶንን ከእሥር ቤት አውጥቶ ብዙ አሠቃየው ነገር ግን ምንም ምን ጉዳት አልደረሰበትም። የንጉሡም ልጅ ከቤቷ መስኮት ሁና አይታ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አመነች ልብሶቿንና ጌጦቿን አውጥታ ለድኆችና ለምስኪኖች ሰጠችና ከዚያም በሐዋርያው በያሶን አምላክ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነች አባቷም ሰምቶ እንዲአሥሩዋት አዘዘ እንዳዘዛቸውም አደረጉ። በጢስም አፍነው አሠቃዩዋት ደግሞውም አራቈቷተትና አባቷ በፍላፃ ነደፋት ነፍሷንም በእግዚአብሔር እጅ ሰጠች።
❤ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ያሶንን ወደ ደሴት ሰደደው በደሴትም ውስጥ ያሠቃየው ዘንድ መኰንኑ ከሠራዊቱ ጋራ አብሮ በመርከብ ተሳፈረ እግዚአብሔር ከሠራዊቱ ጋራ በባሕር አሠጠመው። ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሶን ወንጌልን እያስተማረ ብዙ ዘመናት ኖረ።
❤ ሁለተኛም ሌላ መኰንን ተሾመ ቅዱስ ያሶንንም ይዞ በምጣድም ውስጥ ድኝና ዝፍት ሰም መልቶ ነበልባሉ ወደ ላይ እስቲወጣ ድረስ ከበታቹ አነደደ ቅዱስ ያሶንንም በውስጡ ጨመረው። የክብር ባለቤት ጌታችንም አዳነው ምንም ምን ጉዳት አልደረሰበትም መኰንኑም ይህን ድንቅ ሥራ አይቶ በክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቤተሰቡ ጋራ አመነ። ሁሉንም አጥምቆ የከበረ የወንጌልን ሕግና ትዕዛዝ አስተማራቸው አብያተ ክርስቲያንም ሠራላቸው በውስጣቸውም ብዙ ድንቆች ተአምራትን አደረገ ብሩህ በሆነ ገድሉ ጌታችንን ደስ ካሰኘውና ካገለገለው በኋላ በበጎ ሽምግልና ግንቦት3 ቀን ዐረፈ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ ሐዋርያ ቅዱስ ያሶን ጸሎት ይማረን በረከትም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #አባ_ብሶይ፦ ይህንንም ቅዱስ በመናቅና በማቃለል ሰውነቱን በማጣመምና በመቈልመም አሠቃዩት እግዚአብሔርም መልአክ በእጁ አክሊል ይዞ "አትፍራ ጽና እነሆ በእጄ ውስጥ አክሊል አለ" አለው። ደግሞም ብዙ አሠቃይተው ወደ እሳት ጨመሩት ተጋድሎውንም በዚህ ግንቦት3 ቀን ፈጸመ። ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን እኛንም በጸሎቱ በአባ ብሶይ ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋራ ለዘላለም ትኑር አሜን።
✝ ✝ ✝
❤ #ቅድስት_ንግሥት_ወለተ_ማርያም፦ እርሷም የንጉሥ ወናግ ሰገድ እናት ናት። በምግባር በትሩፋት የታወቀች ጻድቅ እናት ናት። ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም ከመከራ ሁሉ ያድነን ለዘላለሙ አሜን። ምንጭ፦ የግንቦት 3 ስንክሳር።
✝️ ✝️ ✝️
❤ #የዕለቱ_ምስባክ፦ "አልቦ ነገር ወአልቦ ነቢብ ዘኢተሰምዐ ቃሎሙ። ውስተ ኵሉ ምድር ወፅአ ነገሮሙ። ወእስከ አጽናፈ ዓለም በጽሐ ነቢቦሙ"። መዝ 18፥3-4። የሚነበቡት መልዕክታት ሮሜ 16፥21-ፍ.ም፣ 1ኛ ዮሐ 2፥26-ፍ.ም እና የሐዋ ሥራ 17፥5-13። የሚነበበው ወንጌል ሉቃ 10፥1-12። የሚቀደሰው ቅዳሴ የቅዱሳን ሐዋርያት ወይም የእመቤታችን የማርያም ቅዳሴ ነው። መልካም የሐዋርያው ቅዱስ ያሶን የዕረፍት በዓልና የእመቤታችን የልደታ በዐል ሰሞን ለሁላችንም ይሁንልን።
